የባሕረ ሐሳቡ ደራሲ ቅዱስ ድሜጥሮስ
አካሄዱን ሁሉ ከእግዚአብሔር ጋር ያደረገ፣ እርፍ አርቆ፣ ድኮ ታጥቆ፣ ወይን አጽድቆ የሚኖር፣ የቀለም ትምህርት ብዙም ያልነበረው ሰው ድሜጥሮስ በቅን ልቡናው መንፈስ ቅዱስ ገልጾለት ባሕረ ሐሳብን የደረሰ ቅዱስ ሰው ነው፡፡ ጌታ ባረገ በ፻፹(180) ዓ.ም የእስክንድርያ መንበር ዐሥራ ሁለተኛ ሊቀ ጳጳስ ሆኖ ተሹሟል። በሹመቱም ጊዜ በትህርምት ኗሪ ነውና አሁን አጽዋማትንና በዓላትን የምናወጣበትን ይህን የቁጥር ዘመን ባሕረ ሐሳብ ተገልጾለት ደርሶታል፤ ተናግሮታል፤ ተናግሮት ብቻም አልቀረም፤ ለሦስቱ ሊቃነ ጳጳሳት ለሮሙ በቅዱስ ጴጥሮስ መንበር ሥር ለነበረው ለአባ ፊቅጦር፣ በቅዱስ ዮሐንስ መንበር ሥር ለነበረው ለኤፌሶኑ ሊቀ ጳጳስ በቅዱስ ጴጥሮስ ካልእ ሥር ለነበረው ለአንጾኪያው መንበር ለቅዱስ መክሲሞስ ዐራተኛ፣ ለኢየሩሳሌም ኤጲስ ቆጶስ ለአባ አጋብዮስ ልኮላቸዋል። እነርሱም ሐዋርያት ከአስተማሩት ትምህርት ጋር አንድ ቢሆንላቸው ተቀብለው ኑረውበታል፤ አስተምረውበታል፡፡ (ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፬፥፵፩፣ ስንክሳር ኅዳር ፲)
