የሆሣዕና ምንባብ5(ሉቃ.19÷1-11)

ጌታችን ኢየስስም ወደ ኢያራኮ ገብቶ በዚያ ያልፍ ነበር፡፡ እነሆ÷ የቀራጮች አለቃ ስሙ ዘኬዎስ የተባለ አንድ ሰው ነበር፤ እርሱም ባለጸጋ ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስንም ያየው ዘንድ÷ ማን እንደ ሆነም ያውቅ ዘንድ ይሻ ነበር፤ የሰው ብዛትም ይከለክለው ነበር፤ ቁመቱ አጭር ነበርና፡፡ ወደ ፊቱም ሮጠ፤ ያየው ዘንድም በሾላ ላይ ወጣ፤ በዚያች መንገድ ያልፍ ዘንድ አለውና፡፡ ጌታችን ኢየሱስም ወደዚያ በደረሰ ጊዜ አሻቅቦ አየውና÷ “ዘኬዎስ ሆይ÷ ፈጥነህ ውረድ፤ ዛሬ በቤትህ እውል ዘንድ አለኝና” አለው፡፡ ፈጥኖም ወረደ፤ ደስ እያለውም ወደ ቤቱ ይዞት ገባ፡፡ ሁሉም አይተው “ወደ ኀጢኣተኛ ሰው ቤት ሊውል ገባ” ብለው አንጐራጐሩ፡፡ ዘኬዎስም ቆመና ጌታችንን እንዲህ አለው÷ “ጌታዬ ሆይ÷ አሁን የገንዘቤን እኩሌታ ለነዳያን እሰጣለሁ፤ የበደልሁትም ቢኖር ስለ አንድ ፋንታ አራት እጥፍ እከፍለዋለሁ፡፡” ጌታችን ኢየሱሱም እንዲህ አለው÷ “ዛሬ ለዚህ ቤት ሕይወት ሆነ፤ እርሱ የአብርሃም ልጅ ነውና፡፡ የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቶአልና፡፡” ይህንም ሲሰሙ፤ ምሳሌ መስሎ ነገራቸው፤ ወደ ኢየሩሳሌም ቀርቦ ነበርና፤ እነርሱም የእግዚአብሔር መንግሥት ወዲያውኑ የምትገለጥ መስሎአቸው ነበርና፡፡