ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ

በሕይወት ሳልለው

በሸዋ ቡልጋ ክፍለ ሀገር ጌዬ በተባለ አካባቢ የተወለደችው ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ አባቷ ደረሳኒ እና እናቷ ዕሌኒ በእግዚአብሔር ፊት የታመኑ ሰዎች ነበሩ፡፡ ልጃቸውን የቤተክርስቲያን ሥርዓት፤ የብሉይና የሐዲስ ኪዳንን መጻሕፍት በማስተማር አሳደጓት፡፡ ዕድሜዋ ለአቅመ ሔዋን ሲደርስ ወላጆቿ የኢየሱስ ሞዓ ልጅ የሆነውን ሠምረ ጊዮርጊስን አጋቧት፤ ዐሥር ወንዶችና ሁለት ሴቶች ልጆችን ወለደች፤ እርሷም ልጆቿን በሥርዓትና በሕገ እግዚአብሔር አሳደገቻቸው፡፡

በዚያ ዘመን የነበረው ንጉሥ ዓፄ ገብረ መስቀል ደግ ሰው ነበር፡፡ በአንድ ወቅት ንጉሡ ስለ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ቁንጅናና ደግነት በሰማበት ወቅት በግዛቱ ከተደነቁት ፻፸፬ ሴቶች መካከል አንዷ ስለነበረች ስለእርሷ ዝና አወቀ፡፡ ንጉሡም ያገለግሏት ዘንድ ፪፻፸፪ ያህል ብላቴናዎችን ላከላት፡፡ ነገር ግን ይህ ውዳሴ ከንቱ እንዳይሆን ወደ እግዚአብሔር ባመለከተች ጊዜ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል በራዕይ ተገልጾላት፡፡ «ሰላም ላንቺ ይሁን የተወደድሽ ክርስቶስ ሠምራ ሆይ፤ የእግዚአብሔር ቸርነት የሆነውን የሰማይ ኅብስትም ተመገቢ» ብሎም መገባት፡፡ በውስጧም መንፈስ ቅዱስ መላባት፤ ፈጣሪዋን አመሰገነች፤ ከንጉሡ የተላኩላትንም አገልጋዮች አስተባብራ ቅዱስ ሚካኤል እንዳዘዛት በስሙ ቤተክርስቲያን አሠራች፡፡ የመልአኩን የቃል ኪዳን ታቦት ወደ ቤተ መቅደስ በማስገባት በዚያ ስታገለግልና ስታስገለግል ኖረች፡፡

ከዕለታት በአንዱ ቀን ግን ከአገልጋዮቿ አንዷ ላይ ርኩስ መንፈስ አደረ፤ አልታዘዝም ማለትም ጀመረች፡፡ ይህን ጊዜ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ደጋግማ መከረቻት፤ ያቺ ብላቴና ግን ልትመከር አልቻለችም፤ በዚህም ሳቢያ ክፉኛ ብታዝንባት ብላቴናዋ ሞተች፡፡ እጅጉን ያዘነችው እናታችን «ይህማ የነፍስ ግድያ ይሆንብኛል» ብላ አምርራ አለቀሰች፤ ወደ እግዚአብሔር በጸለየች ጊዜ ፈጣሪ አገልጋይቱን ከሞት አስነሳላት፡፡ ውስጧም በሐሴት ተሞላ፤ እንዲህም አለች «በዓለማዊ ሕይወት ውስጥ ስኖር ይህን ተአምር ካደረገልኝ በምናኔ ሕይወት ብኖር ደግሞ ምን ያህል ድንቅ ሥራ ያደርግልኛል፤» ብላ ባለቤቷንና ልጆቿን እንዲሁም ወላጆቿን ትታ መነኮሰች፡፡ ነገር ግን የመጨረሻው ልጇን ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም በገባች ጊዜ አብራ ይዛው ሔደች፡፡ የአካባቢው ሰዎች ከሩቅ ቦታ እንደመጣች አውቀው አስጠጓት፤ እርሷም ልጇን በዚያው አስቀመጣ በገዳሙ ውስጥ በጸሎት፤ በጾምና በስግደት ስትተጋም ቆየች፡፡ ልጇ ግን እናቱን ባጣ ጊዜ አለቀሰ፤ተራበም፡፡ በደጃፉ ስታለፍ የነበረች አንዲት ሴት ልጁን ተጠግታ ልታነሳው ብትሞክር ቅዱስ ሚካኤል ፈጥኖ ደርሶ ነጥቆ ወሰደው፤ ወደ ገነትም አስገባው፡፡ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራም ወደ ልጇ በተመለሰች ጊዜ ሞቶ አገኘችው፡፡ መሪር ኃዘንም አዘነች፤ ይህን ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተገልጾ ልጇ በገነት እንዳለ ነግሮ አጽናናት፡፡ ወደ ጣና ባሕርም መርቶ ወሰዳት፤ በዚያም ለ፲፪ ዓመት በባሕር ውስጥ ገብታ ሰውነቷ ተበሳስቶ ዓሣዎች በውስጧ እስኪያልፉ ድረስ ቆማ ጸለየች፤ ጌታችን  ኢየሱስ ክርስቶስም ተገልጾ ቃልኪዳን ሰጣት፤ ፲ አክሊላትም ወረዱላት፡፡ በጸሎትና በስግደትም መትጋት በቀጠለችበት ወቅት ቅዱስ ሚካኤልን፣ ቅዱስ ገብርኤልን፣ ቅዱስ ሩፋኤልንና እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያምም ረዳት እንዲሆኗት ጌታችን ፈቀደላት።

እናታችን ክርስቶስ ሠምራ ደግና ርኅሩኅ ነበረችና ጌታን እንዲህ ብላ ለመነችው «አቤቱ ፈጣሪዬ እኔን ባሪያህን ከክፉ ነገር ሁሉ ሠውረኸኛልና ዲያብሎስን ትምረው ዘንድ እለምንሃለሁ፡፡ ይኸውም ስለ አዳምና ስለ ልጆቹ በጠቅላላውም ስለ ሰብአ ዓለም ሥጋቸው ሥጋዬ ስለሆነ እንዳያስታቸው ክፉ ሥራ እንዳያሠራቸው ብዬ ነው ማርልኝ ማለቴ» አለችው፡፡ ጌታችንም «ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ ሆይ ዕፁብ ድንቅ ልመና ለመንሽኝ! ሌሎች በኋላሽም የነበሩ በፊትሽም የሚመጡ ያልለመኑትን ልመና ለመንሽኝ» አላት፡፡ ቅዱስ ሚካኤልንም ወደ ዲያብሎስ እንዲወስዳት አዘዘው፡፡

ሲኦል ሲደርሱ ምሕረትን የሚሻ ከሆነ እንድትጠይቀው ቅዱስ ሚካኤል ባዘዛት ጊዜ፤ «ሳጥናኤል» ብላ ጠራቸው፡፡ ዲያብሎስም መልሶ ሳጥናኤል ብሎ የጠራኝ ማን ነው? አለ፡፡ እርሷም «እኔ ነኝ» አለችው፡፡ ወደ እኔ ለምን መጣሽ ሲላት  «ከፈጣሪህ ጋር አስታርቅህ ብየ» አለችው፡፡ እርሱም አንቺን ከቤትሽ ከንብረትሽ ሳለሽ አስትሻለሁ ብየ ብመጣ ያጣሁሽ ሰው እኔን ልታስታርቂኝ መጣሽ? ግን ይህን ያደረገ ያ የቀድሞው ጠላቴ ሚካኤል ነው፤ ሲጻረረኝ የሚኖር ከክብሬም ያወረደኝ እሱ ነው እንጂ አንቺ ምን ጉልበት አለሽ ብሎ እጇን ይዞ ወደ ሲኦል ወረወራት፡፡

በዚያች ቅጽበት ቅዱስ ሚካኤል ሲኦልን በሰይፉ መታው፤ ተከፈተም፤ በውስጡም ብዙ ነፍሳት እርስ በርስ ሲነባበሩ አየች፤ ነፍሷም ታበራ ስለነበር ፲ ሺህ ያህል ነፍሳት መጥተው በላይዋ ሰፈሩባት፤ ከሲኦልም ይዛቸው ወጣች፤ እነዚያን ነፍሳት የማረላትንም ፈጣሪዋን አመሰገነች፡፡

ጌታችን ኢየሱስም ለእናታችን ክርስቶስ ሠምራ ማረፊያዋ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በስተቀኝ እንደሚሆን እና ስሟም ከእንግዲህ በኋላ በትረ ማርያም ተብሎ እንደሚጠራ ነገራት፡፡ እመቤታችንም ተገልጻ «ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ ሆይ፤ አንቺን የወለደች ማሕፀን የተባረከች ናት፤ አንቺንም አጥብተው ያሳደጉ ጡቶች የተባረኩ ናቸው፡፡ አንቺንም ያዩ ዐይኖች የተባረኩ የተቀደሱ ናቸው፤ አንቺንም የሚያመሰግኑ ንዑዳን ክቡራን ናቸው፤ያንቺን ገድል የሚሰሙ፤ የሚያሰሙ የተባረኩ ናቸው»፤ አለቻት፡፡

ከዚህ በኋላ ሥጋዋ ከነፍሷ ተዋሕዶ ወደ መሬት ተመለሰች፤ በቁመቷ ልክ ጉድጓድ አስቆፍራ፤ በዙሪያዋ ጦሮችን አስተከለች፤ ይህም ወደፊትና ወደኋላ በምትልበት ጊዜ እንዲወጋት ነበር፤ ለ፲፪ ዓመትም እየሰገደች ኖረች፡፡

ጌታችንም እንዲህ አላት፤«አንቺን የሚወዱ፤ ስምሽን የሚጠሩ፤ ዝክርሽን የዘከሩና በዓልሽን ያከበሩ እስከ ፲፪ ትውልድ እምርልሻለሁ»፡፡ በመጨረሻም ነሐሴ ፳፬ ቀን ነፍሷ ከሥጋዋ ተለይታ መላእክት አሳረጓት፤ የቅድስት ክርስቶስ ሠምራ የከበረ ዐፅም ጌዬ የተባለ ገዳም ውስጥ ተቀምጧል፤ ይህም ገዳም እርሷን መዘከርና መማጸን ለሚሹ ምእመናን የተሠራ ነው፡፡

ምንጭ፡- ገድለ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ፤ ነገረ ቅዱሳን ቁጥር ፪ እና ዝክረ ቅዱሳን 

«ክቡር ሞቱ ለጻድቅ በቅድመ እግዚአብሔር፤የጻድቅ ሞት በእግዚአብሔር ፊት የከበረ ነው፤» (መዝ.፻፲፭፥፭)

ዲያቆን ዐቢይ ሙሉቀን

«ክቡር ሞቱ ለጻድቅ በቅድመ እግዚአብሔር፤ የጻድቅ ሞት በእግዚአብሔር ፊት የከበረ ነው»፤ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት ስለሕዝቅያስ በተናገረው በዚህ ኃይለ ቃል ሊያስረዳን የፈለገው የነፍስ ከሥጋ መለየት ከሚያልፈው ዓለም ወደማያልፈው ዓለም፣ ውጣ ውረድ፣ ድካም ካለበት ዓለም ውጣ ውረድ ድካም ወደሌለበት ዓለም መሄድ ነውና። ስለሆነም እንደ ቤተክርስቲያናችን አስተምህሮ በዚህች ዕለት የቅዱሳን ዕረፍት ነው እየተባለ ይነገራል። ድካም ካለበት ድካም ወደሌለበት ስለሆነ ዐረፈ ወይም ዐረፈች እየተባለ ይነገራል። በነሐሴ ፳፬ በዓለ ዕረፍቱን የምናከብረው ጻድቁ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዐረፈ እንጂ ሞተ አይባልም፤ ሞቱ በእግዚአብሔር ዘንድ የከበረ ነውና።

በዚህ ዕለት ቤተክርስቲያን የቅዱሱን በዓለ ዕረፍት ምክንያት በማድረግ እግዚአብሔርን ከምታመሰግንበት ያሬዳዊ ዜማ እንጥቀስ። «ሞቶሙሰ ለጻድቃን ሕይወቶሙ ውእቱ እስመ ለጻድቅ ይትሌዓል ቀርኑ በክብር ጻድቃን እለ አሥመርዎ ለእግዚኦሙ ምድረ ብርህተ ወጽዕዱተ ይወርሱ፤የጻድቃን ሞታቸው ሕይወታቸው ነው። የጻድቅ ክብሩ ከፍ ከፍ ይላልና። ጌታቸውን ደስ ያሰኙት ጻድቃን ብርህትና ጽዕዱት የሆነች ምድርን ይወርሳሉ» (ቅዱስ ያሬድ)።

እንግዲህ ከላይ በተጠቀሰው ቃለ እግዚአብሔር መሠረት ሞታቸው ሕይወታቸው ነው የተባለ በመጀመሪያ ደረጃ ሞተ ሥጋ እንደሆነ ልብ ማለት ያስፈልጋል፤ ምክንያቱም ጻድቃን ሞተ ሥጋን እንጂ ሞተ ነፍስን ሊያዩ አይችሉም። ሞተ ነፍስን የሚያዩ ከሆነ ጥንቱኑ ጻድቃን ሊባሉም አይችሉም። ሞተ ሥጋቸው ግን ወደ ተሻለውና ወደሚበልጠው ዓለም የሚሄዱበት ስለሆነ ሕይወታቸው ነው ተባለ።

ሌላው ደግሞ የጻድቃን ሞት እንጂ የኃጥአን ሞት ሕይወት ሊሆን አይችልም። ምክንያቱም ኃጥእን ምንም እንኳ ወደማያልፈው ዓለም የሚሄዱ ቢሆንም መከራ ወደ አለበት፣ ሥቃይ ወደሚበዛበት እንጂ ዕረፍት ወደአለበት መሄድ አይችሉም። መከራና ሥቃይ የሚበዛበት ዓለም መሄድ ደግሞ ሕይወት ሊባል አይችልም። እንዲያውም ነቢዩ ዳዊት «ሞቱ ለኃጥእ ጸዋግ፤የኃጥእ ሰው ሞት ክፉ ነው» (መዝ.፴፫፥፳፩) በማለት አስረድቷል። ጻድቃን ሞተ ሥጋን እንጂ ሞተ ነፍስን አያዩም። ኃጥኣን ግን ሞተ ሥጋም ሞተ ነፍስም ያገኛቸዋል። ስለዚህ ለኃጥእ ሰው ሞተ ሥጋውም ሆነ ሞተ ነፍሱ ክፉ እንጂ መልካም የሚባል አይደለም።

ሞት የሰው ልጅ የፈጣሪውን ትእዛዝ በመተላለፍ የሰለጠነበት ነው። «በሕይወታችሁ ስሕተት ለሞት አትቅኑ፤በእጃችሁም ሥራ ጥፋትን አታምጡ። እግዚአብሔር ሞትን አልፈጠረምና፤ የሕያዋንም ጥፋት ደስ አያሰኘውምና። ነዋሪ ይሆን ዘንድ ፍጥረቱን ፈጥሮአልና፣ የዓለም መፈጠርም ለድኅነት ነውና፣ በእነርሱም ዘንድ የጥፋት መርዝ አልነበረምና፣ ለሲኦልም በምድር ላይ ግዛት አልነበረውምና። ጽድቅ አትሞትምና። ክፉዎች ግን በእጃቸውና በቃላቸው ጠሩት ባልንጀራም አስመሰሉት። በእርሱም ጠፉ። የእርሱ ወገን መሆን ይገባቸዋልና ከእርሱ ጋር ቃል ኪዳን አደረጉ» (ጥበ.፩፥፲፪-፲፯) በማለት መፍቀሬ ጥበብ ሰለሞን ነግሮናል።

ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ ሃይማኖትና ምግባር የማይነጣጠሉ እንደሆኑ በምሳሌ ሲያስተምር የጠቀሰው የነፍስና የሥጋን ህልውና ነው። «ከመ ሥጋ ዘአልቦ መንፈስ ምውት ውእቱ ከማሁ ሃይማኖትኒ እንተ አልባቲ ምግባረ ሠናይ ምውት ይእቲ ለሊሃ፤ከነፍስ የተለየ ሥጋ የሞተ እንደሆነ እንዲሁ ከሥራ የተለየ እምነት የሞተ ነው» (ያዕ.፪፥፳፮) እንዲል፤ ስለዚህ ነፍስ ያለሥጋ ሥጋም ያለ ነፍስ ህልውና አይኖራቸውም። ይህ ማለት በሰውነት ህልውና እንጂ ነፍስና ሥጋ ተለያይተው ነፍስም በገነት  ወይም በሲኦል ሥጋም በመቃብር አይኖሩም ማለት አይደለም፡፡ በመሆኑም የሥጋ ሞት የሚባለው የነፍስ ከሥጋ መለየት ነው። ይህ የነፍስ ከሥጋ መለየት የጻድቅ ከሆነ በእግዚአብሔር ዘንድ የከበረ ነው።

ነፍስ በባሕርይዋ የምትሞት አይደለችም፤ ሞተ ነፍስ የሚባለው የማትኖርበት ጊዜ ስላለ ሳይሆን ከምትኖርበት ሁኔታ አንጻር ነው። ይህ ማለት ነፍስ በሃይማኖት ጸንታ በምግባር ቀንታ ባለመኖሯ ወደ ሲኦል በኋላም ገሃነመ እሳት ትወርዳለች። የነፍስ ሞት ማለት ገነት በመግባት ፈንታ ሲኦል፣ መንግሥተ ሰማያት በመግባት ፈንታ ገሃነመ እሳት መግባት ነው። «ድል የነሣው ሁለተኛውን ሞት አያይም» (ራእ.፪፥፲፩) ተብሎ የተጻፈው ነፍስ ከሥጋ መለየትን ሳይሆን ገሃነመ እሳት መውረድን አያይም ለማለት ነው።

ሞት ማለት መለየት ነውና ነፍስ ከፈጣሪዋ ከእግዚአብሔር ተለይታ ካልፈጠራት ከዲያብሎስ ጋር መኖር ስትጀምር የነፍስ ሞት ይባላል። ሁለተኛ ሞት የተባለውም ፈጣሪ ያዘጋጀውን መንግሥተ ሰማያት አጥታ በኃጢአቷ ምክንያት ገሃነመ እሳት መውረድ ነውና «ድል የነሣው ሁለተኛውን ሞት አያይም» ማለት ከላይም እንደተገለጸው ገሃነመ እሳት አይገባም ማለት ነው።

በአጠቃላይ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት «የጻድቅ ሰው ሞት ክቡር ነው» ሲል ሞተ ሥጋን አያይም ማለት ሳይሆን ሞተ ነፍስን አያይም ማለት እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል። መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ ደግሞ ሞተ ሥጋን መቅመስ የግድ ነውና ይህ እንደ ጻድቁ ተክለ ሃይማኖት መንግሥተ ሰማያትን የሚወርስበት ሞት ክቡር ነው፤ሕይወት ነው፣ ዕረፍት ነው እያለ ይገልጸዋል፡፡ እኛም ንስሓ ገብተን ሥጋውን ደሙን በልተን እንደዚህ በእግዚአብሔር ዘንድ ክቡር ለተባለው ሞት እንዲያበቃን የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የጻድቁ የተክለ ሃይማኖት ረድኤት በረከት አይለየን፤ አሜን።

በዘመናችን የቤተክርስቲያን ፈተናዎች

የተከበራችሁ አንባብያን ባለፉት ሠላሳ ዓመታት በቤተክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየደረሰ ያለውን መከራ በተለይም ደግሞ ባለፉት ሁለት ዓመታት የተፈጸመውን ግፍ የሚገልጽ ተከታታይ ጹሑፍ በማቅረብ ላይ መሆናችን ይታወቃል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ይዞታ ነጠቃ፤ የአብያተ ክርስቲያናት ቃጠሎና የምእመናን ግድያ  ዋናዎቹ የግፍ ተግባራት ናቸው፤ ከባለፈው የቀጠለውንና የመጨረሻውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡ መልካም ንባብ

በማርክሲዝም ሌሊዝንም አስተምሮ የተበረዘ ሰው ሁል ጊዜ ባላንጣና ጠላት በመፈለግ ጠላቱን ካላጠፋ መኖር እንደማችል ሲሰብክ የሚኖር መሆኑን በሙያው ምርምር ያደረጉ አካላት ይናገራሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደ ሃይማኖትም እየተጋባ መጥቷል፡፡ ከሃይማኖት ሰዎች የሚጠበቀው እናመልከዋለን የሚሉትን አምላክ በቃልም በምግባርም መግለጥ ነው፡፡ ሌላውን እያጠፉና  አማራጭ እያሳጡ እምነትን ማስፋፋት አይቻልም፡፡ ሌላውን አጥፍተው መኖር የሚፈልጉት የሚያደርጉት ምድራውያን ገዥዎች ናቸው፡፡ ስለሃይማኖት የሚያስተምሩ አካላት ከዚህ ዓለም የተለየ ዘለዓለማዊ ርስት እንዳለ የሚያምኑ በመሆናቸው ዘለዓለማዊ ርስት ማውረስ የሚችለውን አምላክ የሚያስደስቱበትን ተግባር ይፈጽማሉ፡፡ ሰው በመግደልና ተቀናቃኝን በማጥፋት ተደስቶ የሚኖር የሚመሰለው ምድራዊ የሥጋ ፍላጎት ያለው ምድራዊ ገዥ እንጂ ዘለዓለማዊ መንግሥትን የሚሻ መንፈሳዊ ሰው አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ወደ አሕዛብ የምትገባው ወንጌልን ይዛ እንጂ እንደ ቀኝ ገዥዎች በአንድ እጅ ወንጌል በሌላ የጦር መሣሪያ ይዛ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ይህን የምታደርገው ባለቤቱ በወንጌል እንዲያምኑ ያደረገው በፍቅር እንጅ በግዳጅ ባለመሆኑ ነው፡፡እንዲህ ያለው እኩይ ተግባር የቤተ ክርስቲያን አለመሆኑን መረዳት የሚገባውም ቤተ ክርስቲያን በሞት እንጂ በመግደል ጸንታ ስለማታውቅ ነው፡፡

ቤተክርስቲያን የገጠማት ፈተና ያላሳሰባቸው አካላት የሰጡት መግለጫ መንግሥትን በሚከተለው መንገድ  አሳስቧል፡፡ ሀገርና ሕዝብን ለመምራት የተቀመጠው መንግሥት  በየአካባቢው  እየደረሰ ባለው  የአብያተ ክርስቲያናት ቃጠሎ፣ የኦርቶዶክሳውያንን መፈናቀል ፣ድብደባ ከዚያም ሲያልፍ አሰቃቂ ግድያ ላይ ያሳየው ቸልተኝነት የበርካታ ሚሊዮን አባሎቻችንን ልብ በእጅጉ የሰበረ ወደፊትም ቢሆን ለደኅንነታችን መጠበቅ ምንም አይነት ዋስትና እንደሌለን እንዲሰማን ያደረገ በመሆኑ የመንግሥትን ለዘብተኝነት በእጅጉ  እንቃወማለን ›› ይላል፡፡ አንድ መንግሥት ለዜጎቹ ዋስትና  ሲሰጥ ዜጎቹን በመንግስት እምነት  ማሳደር ብቻ  ሳይሆን  ለመንግሥትም  ጠበቃ ይሆናሉ፡፡ ምርጫ ቢደረግ ይመርጡታል፤ ቢናገር ይሰሙታል፡፡ ቢያዝዝ ይፈጽሙለታል፤ እንኳንም ተናግሮ ሳይናገርም ማድረግ የሚገባቸውን ይሠራሉ ፡፡ ክርስቲያኖች በዚህ ምድር ላይ ሲኖሩ በጌታ ለገዥዎቻችሁ ታዘዙ ›› የሚለውን  አምላዊ ቃል ሲፈጽሙ ኖረዋል፡፡ ወደ ፊትም ይፈጽሙታል፤ ይህ ማለት ግን በክርስቲያኖች ላይ በደል ሲፈጽም መንግሥትን አያሳስቡም ማለት አይደለም፡፡ ለገዥዎቻችን መታዘዝ እንዳለብን የሐዋርያውን ቃል አምነን እንሠራለን፡፡ አድሎአዊ ተግባር  ሲፈጸም ስናይ ደግሞ እንናገራለን፡፡ ነህምያ የኢየሩሳሌም መፍረስ ሲያሳስበው ስለኖረ ኃዘንና ትከዜው በፊቱ ላይ መነበብ በጀመረ ጊዜ የማረከው ንጉሥ ምን እንዳሳዘነው ጠየቀው ፡፡ ነህምያም ከዚህ በላይ መከራ አለመኖሩን በመረዳት አባቶቼ የሠሯት ኢየሩሳሌም ፈርሳ እንዴት ደስተኛ እሆናለሁ በማለት መለሰለት፡፡ በነህምያ መልስ ቅንነቱን ሲመለከት የኖረው ንጉሥ የሚያመልከው አምላክ የሚመለክበትን ቤተ መቅደስና ሙሉ ከተማዋን እንዲያንዱ ፈቃድ ሰጥቶ ሰደደው፡፡ በእኛ ዘመንም መፈጸም ያለበት እንዲህ ነው፡፡ አንተ ከፈርኦን አታንስ እኛም ከሙሴ አንበልጥ የሚለውን ንግግር ማሰብ ይገባል፡፡

 ሀገራችን ክርስቲያኖችን እያጠፉ የሚደሰቱበት ክርስቲያኖች ደግሞ በኃዘን የሚኖሩባት መሆን የለባትም፡፡ ሁላችንም እኩል ደስታውንም ኃዘኑንም የምንካፍልባት መሆን ይኖርባታል፡፡በሃይማኖት ሰበብ የተቀሰቀሰ ግጭት ቶሎ ስለማይበርድ መፍትሔ መፈለግ ተገቢ ነው እንላለን፡፡

 በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ  ቤተክርስቲያን ሠለስቱ ምእት የመቶ ሃያ ማኅበራት ኅብረት ደግሞ ‹‹ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በጅማ፣ በኢሉባቡር፣በከሚሴ፣በድሬድዋ፣በምሥራቅና በምዕራብ ሐረርጌ፣በፍቼ፣ሶማሌ (ጅጅጋ) ፣በባሌ፣ በአሩሲና በሌሎችም የሀገሪቱ ክፍሎች አብያተ ክርስቲያናት እየተቃጠሉ፤ ክርስቲያኖች እየተገደሉ፤ እየተሰደዱና ተገደው ሃይማኖታቸውን እንዲቀይሩ እየተደረገ፤  ንብረታቸው እየተቀማና እየተቃጠለ የአብያተ ክርስቲያናት ይዞታዎች ጥምቀተ ባሕርን ጨምሮ እየተቀሙ እንደሆነ በተለያዩ ሚድያዎች የሰማነውና በአካልም በቦታው ተገኝተን ያየነው እውነታ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ለሀገር ባለውለታ መሆኗ ተረስቶ ቤተክርስቲያንና አማኞቿን የማይመጥን ስም እየተሰጣት እንዲህ ያሉ ጥቃቶች መንግሥት ባለበት ሀገር እየተፈጸሙ፤ ሰዎች በነፃነት የፈለጉትን የማምለክና በሰላም ወጥቶ የመግባት ሕገ መንግሥታዊ መብታቸውን ተነፍገው በስጋትና በመከራ ውስጥ በመሆናቸው የተሰማንን ጥልቅ ኃዘን እንገልጣለን›› ብለዋል፡፡ ሀገሪቱ የምትታወቅባቸው የመስህብ ቦታዎች የቤተክርስቲያኗ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ቤተክርስቲያንን አጥፍተን ሌላ እንመሥርት ካልተባለ በስተቀር እንዲህ አይነት ተግባር በየትም ተደርጎ አያውቅም፡፡እንዲህ አይነት ዘመኑን የማይመጥን  ጥፋትና አድሎአዊ አሠራር መቆም ይኖርበታል፡፡ሥልጣን ላይ ስንቀመጥ መልካም ብንሠራ እኛ ዘለዓለማዊ አይደለንምና ስንወርድ ደግሞ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም እንኖራለን፡፡ ሰዎች በመውረዳችን ያዝናሉ መልካም ተግባራችንን ሲዘክሩ ይኖራሉ እንጂ እንኳን ወረዱ አይሉንም፡፡ስለዚህ አጥፊዎች ከእኩይ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ ማድረግ አጥፊዎች እንወክለዋለን የሚሉትንም ሆነ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያኖችን፤ አባቶችን አቅርቦ ማወያየትና ችግሩን በመለየት የማያዳግም እርምት መስጠት ይገባል፡፡

      ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፯

 

በዘመናችን የቤተክርስቲያን ፈተናዎች

የተከበራችሁ አንባብያን ባለፉት ሠላሳ ዓመታት በቤተክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየደረሰ ያለውን መከራ በተለይም ደግሞ ባለፉት ሁለት ዓመታት የተፈጸመውን ግፍ የሚገልጽ ተከታታይ ጹሑፍ በማቅረብ ላይ መሆናችን ይታወቃል፡፡ የቤተክርስቲያን ይዞታ ነጠቃ፤ የአብያተ ክርስቲያናት ቃጠሎና የምእመናን ግድያ ዋናዎቹ የግፍ ተግባራት ናቸው፤ ከባለፈው የቀጠለውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡ መልካም ንባብ!

ክርስቲያኖች መከራ ቢገጥማቸውም ፈርተው ከእምነታቸው እንደማያፈገፍጉ፣ ከራሳቸው ሕይወት ይልቅ ለታቦታቱና ለንዋያተ ቅድሳቱ ቅድሚያ እንደሚሰጡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያነበብነው፤ በቅርብም ሲፈጸም ያየነው ተግባር ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ከመከራ እንዲሰውራቸው ብቻ ሳይሆን በሰማዕትነት እንዲያበረታቸውም ይለምኑ ነበር፡፡ ቤተክርስቲያን ለሁለት ሺህ ዘመናት ያልተፈተነችበት የመከራ አይነት፣ያልተፈጸመም ተአምር አለመኖሩን ክርስቲያኖች ብቻ ሳይሆን አሕዛብም የሚመሰክሩት እውነታ ነው፡፡ አሕዛብ ቤተክርስቲያንን ለማጥፋት ሲነሡ ክርስቲያኖች ታቦታትና ንዋያተ ቅድሳትን ይዘው እንዲሸሹ ከማድረግ በተጨማሪ  እግዚአብሔር አምላክ በማይታበል ቃሉ ታቦታቱም ሆኑ አብያተ ክርስቲያናቱ እንዲሰወሩ ሲያደርግ ኖሯል፡፡ በግብጽ የነበረ የቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ታቦት በእስላሞች በፈረሰ ጊዜ እግዚአብሔር አምላክ ጽላቱን ሰውሮት ከብዙ ዘመን በኋላ በኢትዮጵያ ውስጥ ከአባ ተክለ ሃይማኖት የትውልድ አካባቢ ጽላልሽ ቤተክርስቲያን ሲተከል  ታቦቱን ሰጥቷቸው አክብረውታል፡፡ እንዲህ አይነት ተአምራት በየዘመናቱ ተፈጽመዋል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ቤተክርስቲያንን ሊያቃጥሉ፤ ክርስቲያኖችን ሊገድሉ የተሰለፉ ወገኖች ሲጋፉት ለነበሩት ሃይማኖት ጠበቃ እንዲሆኑም አድርጓል፡፡ ከጥፋታቸው አልመለስ ካሉም ተቀስፈው እንዲሞቱ ሲያደርግ ኖሯል፡፡ ይህንን የምንጽፈው በአንድ በኩል በእምነት ያሉትን ለማጽናናት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ታሪክን መጥቀስ እንጂ ከታሪክ መማር የማይፈልጉ ወገኖች አንብበው እንዲጠቀሙበት በማሳብ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን እየተሳደደች ትዕግሥቷን አሕዛብ አይተው እንዲማሩ ለማስተማር ጭምር ነው፡፡

የምዕራባውያን ተልእኮ አስፈፃሚ የሆኑ መናፍቃንና ግብረ አበሮቻቸው ኢትዮጵያውያንን የአስተሳሰብ ድሃ ለማድረግና የነጮችን  የበላይነት አምነው እንዳይቀበሉ እንቅፋት የሆነችባቸውንና የሰውን ልጅ  ለሁሉም እኩልነትን የምታስተምረውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን  ለመበቀል የሚችሉትን ሁሉ ያደርጋሉ ዝናራቸውን ቢያራግፉና ቀስታቸውን ቢጨርሱም ለማሸነፍ እንደማይችሉ እያወቁት ራሳቸውን የሚጎዳ ተግባር ይፈጽማሉ፡፡ በዐድዋ በማይጨውና በሌሎች ከውጭ ወራሪዎች ጋር በተደረጉ ጦርነቶች የተሳተፉት ኦርቶዶክሳውያን ብቻ ባይሆኑም ቤተክርስቲያን ለሀገር መሞት ክብር መሆኑን በማወጅ፤ ምሕላ በመያዝ፤ ለዘማቾች የቁም ፍትሐት በማድረግ ያበረከተችውን አስተዋጽኦ በማሰብ መልካቸው እና ቋንቋቸው የሚመስሉንን አሠልጥነው ይልካሉ፡፡ ገንዘብ ማግኝት የሃይማኖተኝነት መስፈርት አስመስለው የዋሃንን ያሳስታሉና በቻሉት ሁሉ የቤተክርስቲያንን አስተዋጽኦ ከትውልድ አእምእሮ አጥበው ለማውጣት ብቻ ሳይሆን የፈጠራ ታሪክ እየፈበረኩ ጥላቻ ሲነዙ ይሰማሉ፡፡የሚያስፈልግውም ይህን የሐሰት ጽሑፍ እውነተኛ መረጃ ይዞ መንግሥት በፍርድ ቤትም መጠየቅ አስፈላጊ ነው፡፡

ኅዳር ፯ እና ፰ በ፲፱፻፺፰ ዓ.ም ኮፈሌ አንሻ በተባለ ቦታ የእስልምና እምነት ተከታዮች ስድስት ክርስቲያኖችን ማረዳቸው እስልምና ባለበት ሀገር ሁሉ ተገዳዳሪያቸውን የማጥፋት ተግባራቸው ማሳያ ነው፡፡በምእመናን ብዛት ከፍተኛውን ቊጥር ያላትን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ማጥቃት፤ ማዳከምና ምእመናንን አስገድዶ ማስለም የሚፈጸሙ ተግባራት ናቸው፡፡ በእምነት ስም የተደራጁ ቡድኖች እና የእምነቱ ተከታዮች ቤተክርስቲያንን ሲያጠቁ እና በተለያዩ ጊዜያት ጥቃቶችን ሲፈጽሙ ይታያሉ፡፡ ክርስቲያኖችን  አስገድዶ በማስለም፤ ፈቃደኛ ካልሆኑ ደግሞ የመግደል ተልኳቸውን ሲፈጽሙ ለደረሰው ጥፋት ክርስቲያኖች ለሚመለከተው አካል  አቤቱታ ሲያቀርቡ ፍትሕ አለመሰጠቱ ወደፊት መስተካከል ይርበታል፡፡ይህ ድርጊት በወቅቱና በጊዜው ካልታረመ መጨረሻ ለሌለው ብጥብጥ እንደሚዳረግ መታወቅ ይኖርበታል፡፡

በቡርቃ ጉዲና እና በአዲስ ልማት ቀበሌዎች ከ፪፻ በላይ ክርስቲያን አባወራዎች ይኖሩ የነበሩ ሲሆን በ፳፻፲፩ ዓ.ም በተደረገው የክርስቲያኖች ቈጠራ ፻፹፭ ሆነዋል፡፡ ይህም የሆነው የክርስቲያኖች ግድያና ስደት ስለተባባሰና ድርጊቱ ሲፈጸም እየታየ ተው ባይ በመጥፋቱ ነው፡፡ ጥፋቱ ተጠናቅሮ በመቀጠሉም ከሚያዚያ ወር  መጀመሪያ እስካሁን ፲፭ አባወራዎች በጋሌ ሰረጡ ቅድስት ኪዳነምሕረት ቤተክርስቲያን ውስጥ ከቤተክርስቲያኑ አስተዳዳሪ ቄስ ጋር በድንኳን ተጠልለው እየኖሩ ነው፡፡ በክርስቲያኖችና በአብያተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰ ያለው ጥፋት ይቁም የምንለውም እንዲህ አይነት ኢሰብአዊ ተግባራት ሲፈጸሙ ሰለምንመለከት ነው፡፡ ሀገራችን ለውጥ ላይ መሆኗ ይታወቃል፡፡ ለውጡን ያልፈለጉት ወገኖች ኢትዮጵያውያን ከቀያቸው እንዲፈናቀሉ በማድረግ የሀገራችንን ገጽታ እያበላሹ መሆኑን ባንዘነጋውም በአንዳንድ አካባቢዎች ክርስቲያኖች ላይ ብቻ ያነጣጠረ ጥቃት ሥልጣን ላይ በተቀመጡ አካላት ጭምር ሲፈጸም መታየቱ ለሰላም ሳይሆን ለብጥብጥ  እየተሠራ ያስመስላልና መፍትሔ ሊፈለግለት ይገባል፡፡

የመንግሥት አካላት ሕዝብን ለማገልገል ኃላፊነት እንዳለባቸው ከተረዱ ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ዘር፣ቋንቋ፣ቀለም፤ ሃይማኖት፣ሳይለዩ ማገልገል ይኖርባቸዋል፡፡ለሚያልፍ ሥልጣን ታሪክ የማይረሳው ጠባሳ ትቶ ማለፍ ተገቢ አይደለም፡፡ በየቦታው ለሚከሠቱ ግጭቶች መፍትሔ ከመፈለግ ተቆጥበው ተረጋግቶ ለሥራ የተሰማራንና ስለሀገሩ የሚጸልይን ክርስቲያን መነካካት ጥፋት እንጂ ሰላምን አያመጣም፡፡

ሐምሌ ፲፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በባሌጎባ በተፈጠረ የሃይማኖት ግጭት ፭ ምእመናን ተገድለዋል፡፡ እንዲህ አይነት ጥፋቶች አሁንም ቀጥለዋል የሃይማኖት ግጭቶች ሲከሠቱ ግጭቶችን ማን እንዳስነሣቸው ማጣራትና ተገቢ የሆነ እርምጃ መስጠት ይገባል፡፡ እየታየ ያለው ግን እየተሰደዱ፣ እየተገደሉ ታቦታችሁን ይዛችሁ ውጡ የሚባሉትን ክርስቲያኖች መብታቸውን ሲጠይቁ ማሰርና ያለፍርድ ማጉላላት ነው፡፡ ይህን ተግባር ለማስታገስ በየአካባቢው የሚገኙ የመንግሥት አካላት ኃላፊነታቸውን በአግባቡ የማይወጡ ከሆነ የክርስቲያኖችን ችግር የፈጠረው ማን እንደሆነ፤ እነ ማን ያላግባብ እንደታሰሩ፤ ማን የሚባል ፖሊስ እንዳሰራቸው፤ ለምን ፍርድ ቤት እንዳላቀረባቸው፤ ፍርድ ቤት ለማቅረብ ጠበቃ የማግኘት መብታቸውን ማን እንዳስከለከለ መረጃውን አደራጅተው ለመንግሥት አካላትም በየደረጃው ለሚገኙ የቤተ ክህነት አገልጋዮችም ማሳወቅ ይኖርባቸዋል፡፡ መንግሥትንም በሕጋዊ መንገድ ለመጠየቅ ያግዛል፡፡ አጥፊዎች እናምንበታለን ከሚሉት  የእምነት ተቋማት ጋር ለመወያየትና አሳማኝ መረጃ ይዞ በፍርድ ቤት ለመጠየቅ ይጠቅማል፡፡ይህ ሁሉ እየተደረገ ጎን ለጎን መረሳት የሌለበት ጉዳይ እግዚአብሔር አምላክ፤ችግሩን እንዲያስወግደው በጾም በጸሎት መጠየቅ ይገባል፡፡ እግዚአብሔርን በንጹሕ ልቡና ሆነን ከጠየቅነው የተፈጠረው ችግር ይርቃል፡፡ በኃጢአታችን ምክንያት ከመጣም ይቅር ይለናል፡፡ ለክብር ከሆነም ያጸናናል፡፡ በእምነት ጸንተን ብንሞት እንኳ ገዳዮቻችንን ማርኮ ያመጣል፡፡ የሰማዕትነት ደም ደርቆ አያውቅም የተባለው ሞታቸው አሕዛብን ማርኮ የሚያመጣ በመሆኑ ነው፡፡

 በክርስቲያኖችና በቤተ ክርስቲያን ላይ እየተፈጸመ ያለው ጥፋት አለመቆሙ ያሳሰበው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የሰ/ት/ቤት ወጣቶች፤ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርትና ምሩቃን እንዲሁም የመንፈሳዊ ማኅበራት ተወካዮች በወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ጉዳዩች ላይ መግለጫ ሰጥቷል፡፡ መግለጫው በአንድ በኩል አጥፊዎች ሕግና ሥርዓት ባለበት ሀገር ከእኩይ ድርጊታቸው እንዲታገሡ ጥፋታቸውን የደረስንበት መሆኑን እንዲረዱ የሚያሳስብ ሲሆን በሌላ በኩል መንግሥትም አጥፊዎችን ለሕግ ማቅረብ  እንዳለበት ለማሳሰብ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ክርስቲያኖች አንድነትና ትብብር የሚያደርጉበትና ከፊት ይልቅ መትጋት የሚገባቸው መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ያለችበት ሁኔታ ያሳሰበው የቤተክርስቲያን አካል የቅድስት ቤተክርስቲያናችን ውለታና እያደረገችው ያለው አስተዋጽኦ ተረስቶ ለሀገራዊ ጥፋት  ባለቤት ተደርጋ መኮነኗን በጽኑ እንቃወማለን፤ ቤተክርስቲያን ከትላንት እስከ ዛሬ የሰላም መልእክተኛ እንጂ አጥፊዎች የሐሰት ታሪክ ፈጥረው እንደሚያወሩት ሕዝብን ከሚያስጨፈጭፉ አካላት ጋር ተባብራ ያጠፋች አይደለችም፡፡ በእውነት ለመናገር ካስፈለገ  በደቡብ፤ በምሥራቅ፤ በኦሮምያም ጭምር ክርስትና ያበበው በሀገሩ ባህል ላይ መሆኑን  መረዳት አይሳነውም፡፡ በአንጻሩ ሌሎች እምነቶች በገቡበት ቦታ ግን ነባሩ ባሕል ተደምስሶ ሀገራችን እስከማይመስል ደርሷል፡፡ አስተዋይ አእምሮ ላለው ሰው በታሪክ ተወቃሽ የሚሆነው ነባሩን ባህል አስገድዶ ሃይማኖት ያስለወጠ እንጂ ባህላችሁን ጠብቃችሁ ዘላለማዊ ርስትን የምትወርሱበትን ወንጌልን መቀበል ትችላላችሁ  የምትለው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን መሆን አይደለችም፡፡

ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፯

 

በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

የተከበራችሁ አንባብያን እንደምን ሰነበታችሁ? ባለፉት ተከታታይ ጽሕፎች ላይ በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን የገጠማትን ፈተና በተለይ የቤተ ክርስቲያንን ቃጠሎና የይዞታ መነጠቅን በተመለከተ መጠነኛ መረጃ የሚሰጥ ጽሑፍ ማቅረባችን ይታወቃል፡፡ ቀጣዩን ደግሞ እንደማከተለው አቅርበነዋል፡፡

ሀገራችንን የምንወድና ሰላማውያን ከሆንን ቀርበን መወያየት፣ ጥፋተኞችን መገሠጽ፣ አጥፊዎችን ለሕግ ማቅረብና ለተፈጠረው ጥፋት ይቅርታ ጠይቆ ካሳ ካስፈለገ መክፈል ነው፡፡ በሃያ ሰባት ዓመታት በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሰውን እንተውና ለውጥ ከመጣ በኋላ የጥፋት ኃይሎች የፈጸሙትን በመጠኑ ለማቅረብ እንሞክር ቢባል እንኳ ተዘርዝሮ አያልቅም፡፡ ‹‹ሚያዝያ ፳፻፲፩ ዓ.ም ሐረር ሳሮሙጢ በሚኖሩ በአራት ካህናትና በምእመናን ላይ የመግደል ሙከራ ተደርጐ ከባድ ድብደባ ቢፈጸምባቸውም በእግዚአብሔር ቸርነት ተርፈው ሆስፒታል ገብተዋል፡፡›› ይህ የሚያሳየው ጥፋቱ ተጠናክሮ መቀጠሉን ነው፡፡ ይህንን ጥፋት እየፈጸሙ ሰላማውያን ነን ቢሉን ማመን አንችልም፡፡ ሰላም የሚመጣው በተግባር እንጂ በቃል አይደለም፡፡ መንግሥት አጥፊዎችን ለሕግ ያቅርብልን፣ ወደ ፊትም ጉዳት እንዳይደርስብን ጥበቃ ያድርግልን የምንለው ለዚህ ነው፡፡ ጥፋቱ አንድ ጊዘ ተፈጽሞ በመቆሙም አይደለም፡፡ በድሬዳዋ፣ በከሚሴ፣ በኤፍራታና ግድም፣ በሰሜን ሸዋ ሰላሌ፣ በምዕራብ ሸዋ፣ ወሊሶ፡ በጅማ ሊሙኮሳ በተከታታይ የተፈጸመውን በማየት እንጂ፡፡

በድሬዳዋ ሀገረ ስብከት የተፈጸመውም ከዚህ ጋር ተቀራራቢ ነው፡፡ በድሬዳዋ ከተማ ዳር የሚገኘውን ‹‹የመካነ ሕይወት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያንን ይዞታ እንወስዳለን በማለት ከመጋቢት ፳፻፲፩ ዓ.ም ጀምሮ ተደጋጋሚ ጥቃቶች በእስላሞች ተፈጽመዋል፡፡ የፖሊስ አባላቱ ችግር በተፈጠረበት ቦታ በሰዓቱ ቢደርሱም ጥቃት ፈጻሚዎቹን በመያዝና ወደ ሕግ በማቅረብ ፈንታ እንዲሸሹ ማድረጋቸውን ለማወቅ ችለናል፡፡ በአንጻሩ ደግሞ የቤተ ክርስቲያንን ይዞታ አናስነካም፣ ቤተ ክርስቲያን ጉዳት ሲደርስባት ቆመን አናይም ያሉ ወጣት ክርስቲያኖችን አስረው በመግረፍ የጥቃቱ ተባባሪ ሆነዋል፡፡››

ማኅበረ ቅዱሳን ወንጀል የሠሩ አካላት አይጠየቁ አላልንም፡፡ ጥፋተኛ ተለቅቆ፣ ተጎጂው የሚታሰርበትና የሚሰቃይበት አሠራር ይስተካከል በማለት ግን እንጠይቃለን፡፡ የፍትሕ አካላትም ከአንድ ወገን የሰሙትን ብቻ ይዘው ወደ ውሳኔ ከመግባት ይልቅ ከሃይማኖት ነፃ በሆነና የተቀመጡበትን ኃላፊነት ባገናዘበ መልኩ ሁለቱንም ወገን ፊት ለፊት አቅርቦ እውነቱን በማውጣት አጥፊዎችን ለሕግ ማቅረብ ይኖርባቸዋል ለማለት ነው፡፡ በወቅቱ የቤተ ክርስቲያኑን ይዞታ ለመቀራመት አሰፍስፈው የነበሩ ወገኖች የምኒሊክ ሃይማኖት ይውጣልን በማለት ይጮኹ እንደነበር የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ ይህ ድርጊት የሰውን ልጅ የእምነት ነፃነት የሚፃረር ነው፡፡

የቤተ ክርስቲያንን ይዞታ ለመቀራመትና ደኗን ጨፍጭፎ ለማውደም የተሰለፉ ወገኖች ቤተ ክርስቲያኗን ከምኒሊክ ጋር ለማያያዝ ምን ሞራላዊስ ሃይማሃታዊስ ችሎታ ይኖራቸዋል፡፡ ክርስትናም ጌታችን ለሐዋርያት ያስተማረው እንጂ በሰዎች የተፈጠረ ሃይማኖት አይደለም፡፡ ምኒሊክ ከመነሣታቸው ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት ፍጹም አምላክ የሆነው እግዚአብሔር ወልድ ፍጹም ሰው በመሆን የመሠረተው፣ ዓለምን ከጨለማ ወደ ብርሃን ያመጣበት ሃይማኖት ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስን ሊገድሉ በለስ አልቀናቸው ያሉ አይሁድ የሮማውያን ሕግ የሰጣቸውን መብት በትክክል መጠቀም ሲገባቸው ሕጉን ጠምዝዘው ጳውሎስን ካልገደልን እህል አንበላም፣ ውኃም አነጠጣም ብለዋል፡፡ ታሰሮ የነበረውን ቅዱስ ጳውሎስ ወደ አደባባይ እንዲያወጣላቸው ሀገረ ገዥውን ሕጋውያን መስለው ጠይቀው የግል ጥላቻቸውን በሕግ ሽፋን ለመፈጸም ተማምለው እንደነበር ሁሉ ዛሬም እየተፈጸመ ያለው የጥንቱ ተመሳሳይ ክፍት ነው፡፡ ሕግ የሰጠውን መጠቀም መብት ነው፡፡ ሕግን ጠምዝዞ ግላዊ ፍላጐትን ለማሟላትና ሌላውን ለማጥፋት መሞከር ግን ወንጀል ነው፡፡ የማይገለጥ የተከደነ፣ የማይታወቅ የተሰወረ ጉዳይ ባለመኖሩ ተደብቀን ብናጠፋ ሁለት ቀን ሳናድር እውነቱ ይገለጣል፡፡ የአጥፊዎች አሳብ ታሪክ ምንም ይበል እኛ ብቻ ደኅና ካላሉና ሀገር ብትበተን ምን አገባን ካላሉ በስተቀር ያልተረዱት እውነታ ወደ ሌላው የወረወሩት ቀስት እነሱንም እንደሚወጋቸውና ለሌላው ያነደዱት እሳት ራሳቸውንም እንደሚያቃጥላቸው ነው፡፡

በዚሁ በያዝነው ዓመት ባሳለፍነው የሚያዝያ ወር ሌላም ዘግናኝ ድርጊት በእስልምና እምነት ተከታዮች ጅማ ሀገረ ስብከት ሊሙኮሳ በሚባል ቦታ ተፈጽሟል፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው ‹‹ሚያዝያ አምስት ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ለሚዘክረው አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጽዋ ጉዝጓዝ ቄጠማ ሊያጭድ በሔደበት ሚጡ ወንዝ ዳርቻ አቶ ልየው ጌትነት የተባለን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ  ቤተ ክርስቲያን የእምነት ተከታይ አንገቱን ቀልተዉ በመጸዳጃ ቤት ጉድጓድ ውስጥ ከጣሉት በኋላ በላዩ የከብት ፍግ ጨምረውበታል፡፡ የመጸዳጃ ጉድጓዱ ባለቤት አቶ መሐመድ ሃምዛ የተባሉ ግለሰብ ነው፡፡ ወዳጅ ዘመዶቻቸው ቄጤማ ሊያጭድ ወጥቶ የቀረውን አቶ ልየው ፍለጋ ቢወጡ የደም ነጠብጣብ በማግኘታቸው ነጠብጣቡን ተከትለው ሲሔዱ ለማመን በሚከብድ ሁኔታ ገድለው ከአጨደው ቄጠማ ጋር መጸዳጃ ቤት ውስጥ ጥለውት ተገኝቷል፡፡›› ይህን ወንጀል የፈጸመው አካል ተጠርቶ ወደ ሕግ አልቀረበም፡፡ ከሁለት ዓመት ላላነሰ ጊዜ በደረሰባቸው ተደጋጋሚ ግፍ በአካባቢው ይኖሩ የነበሩ ክርስቲያኖች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ድንኳን ተክለው መኖር ጀምረዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ስታስጠልል ዘርና ሃይማኖት እንደማትመርጥ የመካቆሪሾች አባርረዋቸው ለመጡት የመሐመድ ተከታዮች ክርስቲያኑ ንጉሥ አረማህ ተቀብሎ በሰላም እንዲኖሩ የፈቀደላቸው መሆኑን የምንመሰክረው እኛ ብቻ ሳንሆን ምዕራባውያን ጭምር ናቸው፡፡ ይህንንም ጉዳይ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ‹‹የእነሱ መንግሥታት (ምዕራባውያን) በ፳ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እኔን የመሰለ ስደተኛ በሀገሩ መቀበሉን እንደ ትልቅ ሰብአዊ ድርጊት ሲቆጥረው፤ የእኔ ሀገር ንጉሦች የጄኔቫ ኮንቬንሽን (ስምምነት)፣ ሰብአዊ መብትና ዲሞክራሲ የሚባል ነገር በሰው ልጅ አእምሮ ባልታሰበበት ከአንድ ሺህ አምስት መቶ ዓመታት በፊት በእምነታቸው ከዘመኑ የሀገራችን ሰዎች እምነት የተለዩ የነቢዩ መሐመድ ተከታዮች ጥገኝነት መስጠታቸውን፣ እነዚህን ስደተኞች መልሱልን በማለት ዓረቦች ለላኩት መልእክተኛ፣ ንጉሣችን በእያንዳንዱ ስደተኛ ክብደት የሚመዝን ወርቅ ብትሰጡኝ እንኳን አሳልፌ አልሰጣችሁም›› (አንዳርጋቸው፣፳፻፲፩፥፲፱) በማለት መመለሳቸውን ጽፈዋል፡፡

ስለዚህ ጉዳይ በጥልቅ ለማወቅ የፈለገ ሰው የእነ ጆን ሰፔንሰር ትሪሚንግሆምን እስላም ኢን ኢትዮጵያን እና የጎበዜ ጣፈጠን እስልምና በአፍሪካ ማንበብ ይጠቅመዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያንን እንግዳ ተቀባይነት በማቃለል ማጣጣል ተገቢ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ነገሥታት ጠብቀው ባቆዩዋት ሀገር እየኖሩ ነገሥታትን የሚተቹና ቤተ ክርስቲያንን ከነገሥታት ጋር እየደረቡ ለመምታት የሚፈልጉ ወገኖች እንደሚተርኩት ሳትሆን ትክክለኛ በመሆኗ በቅርቡ በለገጣፎም ሆነ በቡራዩ የተፈናቀሉ የእስልምናም የሌላ እምነት ተከታዮች እንጠጋ ብለው ሲመጡባት አታምኑብኝም የምትል ሳትሆን ልጆቼ ኑ ብላ እጇን ዘርግታ የምትቀበል መሆኗን አሳይታለች፡፡ ቤት ፈርሶባቸው ቤተ ክርስቲያን የተጠለሉ ወገኖች በኢሳት የቴሌቭዥን ጣቢያ ሲናገሩ ሰምተናልና፡፡

የሚጠቅመንም ካለፈው መጥፎ ታሪክ እየተጠነቀቅን መልካም ከሆነው ያለፈ ታሪካችን መማር ነው፡፡ ድሮ ተፈጽሟል እያሉ የሐሰት ታሪክ እየደረቱ የጥፋት ነጋሪት መምታት እልቂት እንጂ ሰላም ስለማያማጣ አጥፊዎች ደግመው ደጋግመው ተረጋግተው እንዲያስቡበት ማሳሰብ እንወዳለን፡፡ መንግሥትም አጥፊዎችን እንዲያስታግሥልን ደግመን እንጠይቃለን፡፡ ይህንን ጽሑፍ የምንዘጋው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፣ የመንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርትና ምሩቃን እንዲሁም የመንፈሳዊ ማኅበራት ተወካዮች በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በሰጡት መግለጫ ነው፡፡ እንዲህ ይላል ‹‹እስከ ዛሬ ሲፈጸሙ በኖሩ ጥቃቶች ላይ ከጥንስሱ ጀምሮ እጃቸውን የከተቱ፣ ያለ አንዳች ፍርሃት በአደባባይ ጭምር በክርስቲያኑ ሕዝብ ላይ ሲሳለቁ እና በል ሲላቸውም ዕልቂትን ሲያውጁ በከረሙና እያወጁ ባሉ ከመንግሥት ጭምር የፈረጠምን ነን ባይ ግለሰቦች እና ተቋማት መንግሥት ለፍርድ እንዲያቀርብልን እንጠይቃለን›› ይህ ቃል ሰላም ወዳድ ከሆነ አስተዋይ አካል የሚነገር ነው፡፡ ጥፋትን በጥፋት መመለስ ለሀገር አይጠቅምምና፡፡

 ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፮

 

ስምና የስም ዓይነቶች

ዲያቆን ዐቢይ ሙሉቀን

የተከበራችሁ አንባብያን ባለፈው ትምህርታችን ላይ የቤት ሥራ የሰጠናችሁ መሆኑ ይታወሳል፡፡ በመሆኑም መልሱን እንደሚከተለው እንሥራ፡፡

፩. ምት፡-  ሠናይት ብእሲት ታቀርብ ማየ እግር ለምታ፤ መልካም ሴት ለባሏ የእግር ውኃ ታቀርባለች፡፡

   ፪. ብእሲት፡- ብእሲ ወብእሲት አሐዱ አካል እሙንቱ፤ ባልና ሚስት አንድ አካል ናቸው፡፡

፫. ሥእርት፡- ሥዕርት ይትረከብ እምላዕለ ርእስ፤ ፀጒር ከራስ ላይ ይገኛል፡፡

፬. ምክዳን፡- ለብሓዊት ገብረት ምክዳነ ለጽሕርታ፤ ሸክላ ሠሪ ለማድጋዋ መክደኛን ሠራች፡፡

   ፭. ክድ፡- ጊዮርጊስ ወሀበ ክሣዶ ለሰይፍ፤ ጊዮርጊስ አንገቱን ለሰይፍ ሰጠ፡፡

   ፮. ገቦ ፡- ገቦ ኢየሱስ አውሐዘ ደመ ወማየ ለመድኃኒተ ኵሉ ዓለም፤ የኢየሱስ ክርስቶስ ጎን ለዓለም  ሁሉ መድኃኒት ደምና ውኃን አፈሰሰ፡፡

ማስታወሻ ፡- ከላይ ለተሰጡት ጥያቄዎች መልሱ ይህ ብቻ ነው ማለት አይደለም፡፡ በዚህ አንጻር ሌላም ተስማሚ ዐረፍተ ነገር እንደሠራችሁም ተስፋ እናደርጋለን፡፡

መራሕያን

መራሕያን ማለት፣ መሪዎች ዋናዎች ማለት ነው፡፡ በነጠላው መራሒ የሚለው መራሕያን ብሎ ይበዛል፡፡ መራሕያን በሌላ አገላለጽ ተውላጠ ስሞች ማለት ነው፡፡

አነ           እኔ                    አንትን      እናንተ

ንሕነ          እኛ                   ውእቱ       እርሱ

አንተ          አንተ                 ውእቶሙ     እነሱ

አንትሙ       እናንተ                ይእቲ        እሷ

አንቲ          አንቺ                 ውእቶን       እነሱ

የግእዝ መራሕያን በቊጥር ዐሥር ሲሆኑ ሁሉም በዐረፍተ ነገር እየገቡ የየራሳቸውን አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ መራሕያን (ተውላጠ ስሞች) በስም ቦታ እየገቡ የስምን ተግባር ያከናውናሉ፡፡ በስም ቦታ ብቻ ሳይሆን በግስ ቦታም እየገቡ ማሰሪያ አንቀጽ በመሆን ያገለግላሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ነባር አንቀጽ ይባላሉ፡፡ ማሰሪያ አንቀጽነታቸውን (ነባር አንቀጽነታቸውን) በሌላ ክፍል የምናይ ይሆንና በስም ቦታ እየገቡ የስምን አገልግሎት መያዛቸውን በዚህ እትም እንመለከታለን፡፡

፩. አነ ውእቱ ብርሃኑ ለዓለም፤ ለዓለም ብርሃን እኔ ነኝ፡፡ (ዮሐ.፰፥፲፪)

፪. ንሕነ አባል ወውእቱ ርእስ፤ እኛ ሕዋሳቶች ነን እርሱም ራስ ነው፡፡

፫. አንተሰ አንተ ክመ ወአመቲከኒ ኢየኃልቅ፤ አንተ ግን ያው አንተ ነህ ዓመትህም ከቶ አያልቅም፡፡ (መዝ.፻፩፥፳፯)

፬. አንትሙ ውእቱ ፄዉ ለምድር፤ እናንተ የምድር ጨው ናችሁ፡፡ (ማቴ.፭፥፲፫)

፭. አንቲ ተዐብዪ እምብዙኃት አንስት፤ ከብዙ ሴቶች አንቺ ትበልጫለሽ፡፡ (ውዳሴ ማርያም ዘዐርብ)

፮. አንትን አንስት አሠንያ ማኅደረክን እናንተ ሴቶች ቤታችሁን አሣምሩ፡፡

፯. ውእቱ የአምር ኵሎ፤ እርሱ ሁሉን ያውቃል፡፡

፰. ውእቶሙ ተሰዱ እምሀገሮሙ፤እነርሱ ከሀገራቸው ተሰደዱ፡፡

፱. ይእቲ ተዐቢ እምኪሩቤል፤እርሷ ከኪሩቤል ትበልጣለች፡፡ (ውዳሴ ማርያም ዘረቡዕ)

፲. ውእቶን ደናግል ዐቀባ ማኅፀንቶን እነዚያ ደናግል አደራቸውን ጠበቁ፡፡

መራሕያንን ከዐረፍተ ነገር በዘለለ በአንድ አንቀጽ እንዴት አገልግሎት ላይ እንደሚውሉ እንመልከት፡፡

አነ ሶበ እጼሊ ወትረ አአኵቶ ለእግዚአብሔር እንዘ እብል አምላክ አንተ ለኵሉ ዘሥጋ ወለኵላ ዘነፍስ፤ ወንጼውዐከ በከመ መሐረነ ቅዱስ ወልድከ እንዘ ይብል አንትሙሰ ሶበ ትጼልዩ ከመዝ በሉ፤ ካዕበሂ እኄሊ ከመ አንትሙ ትብሉ ከመ ንሕነኒ ንሕድግ ለዘአበሰ ለነ::

ወኤፍሬምኒ ወደሳ ለድንግል እንዘ ይብል አንቲ ውእቱ ሰዋስው ዘርእየ ያእቆብ፤ እስመ ይእቲ ተነግረት በሕገ ኦሪት፡፡ ነቢያት ወሐዋርያት ሰበኩ ክርስቶስሃ፡፡ እስመ ውእቱ ከሠተ ሎሙ ወውእቶሙ አእመሩ በእንቲአሁ፡፡ ውእቱሂ ከሠተ ምሥጢረ ለአንስት ወይቤሎን አንትን  ሑራ ንግራሆሙ ለአርዳእየ፡፡ ወውእቶን ሰበካ ትንሣኤሁ ለወልድ፡፡

ከላይ በተገለጸው ምንባብ ዐሥሩም መራሕያን አገልግሎት ላይ እንደዋሉ መረዳት ያስፈልጋል፡፡

ይቆየን

 

በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

የተከበራችሁ አንባብያን እንደምን ሰነበታችሁ? ባለፉት ተከታታይ ዕትሞች ላይ በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን የገጠማትን ፈተና በተለይ የቤተ ክርስቲያንን ቃጠሎና የይዞታ መነጠቅን በተመለከተ መጠነኛ መረጃ የሚሰጥ ጽሑፍ ማቅረባችን ይታወቃል፡፡ ቀጣዩን ደግሞ እንደማከተለው አቅርበነዋል፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያለስሟ ስም፣ ያለ ግብሯ ግብር እየተሰጣትና ለማጥፋት ምክንያት እየተፈለገላት መሆኑ እየታየና እየተሰማ ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከቅዱስ ሲኖዶስ እስከ አጥቢያ በተዘረጋው መዋቅር መሥራት የሚገባትን፣ ማኅበራት፣ ዘማርያንና ሰባክያን መፈጸም የሚኖርባቸውን፣ ምእመናንና ምሁራን ማከናወን የሚጠበቅባቸውን ማሳወቅ ዘመኑ የማጠይቀው ተግባር ነው፡፡ በአንድ በኩል ከሌሎች የእምነት ተቋማት ጋር መተባበር እና መረጃ በመለዋወጥ መሥራት የሚገባንን፣ በሌላ በኩል እየተፈጸመ ያለውን ጥፋት ለመንግሥት በማሳወቅ በአጥፊዎች ላይ እርምት እንዲወሰድ ማገዝ ይገባል፡፡ የአጥፊዎችን የተሳሳተ ትርክታቸውንና ለቤተ ክርስቲያን ያላቸውን ጥላቻ እንዲያስወገዱ እንዲያደርግ ማሳሰብ ሲገባ በሌላ በኩል ደግሞ ከዛሬ ነገ ይማራሉ፣ በመረጃ የተደገፈ ትንታኔ በማቅረብ አስተማሪ የሆነ ጽሑፍ ያቀርባሉ ብለን ብንጠብቅም ዝም ማለታችንን እንደ ፍርሃት፣ አለመጻፋችንን እንደ አላዋቂነት ለሚቈጥሩ ወገኖች ሚዛኑን የጠበቀና ትክክለኛ መረጃ መስጠት ይገባል፡፡

ከትላንት እስከ ዛሬ የፈጸሙትን ጥፋት በማሳየት ማን ጥፋተኛ እንደሆነ አንባብያን የራሳቸውን ፍርድ እንዲሰጡ ማንቃትና ለተጨማሪ ንባብ መቀስቀስ ያስፈልጋል፡፡ ‹‹ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል›› አካሔዳቸውን መግለጥ ባልቻልን ምንም እውነትን ብንይዝ ካልተገለጠ ጠቀሜታው ይደበዝዛል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ከአንዳንድ ባለሥልጣናት እየተጠጉ የሚፈጽሙትን ጥፋትም ማጋለጥ ያስፈልጋል፡፡ ሥራ አጥ ወጣቶች ሠርተው የሚበሉበት፣ ምሁራን ተመራምረው ሀገር የሚያበለጽጉበት ተግባር ከመፈጸም ይልቅ ሀገሪቱን ሁሉ ቤተ እምነት ካላደረግን፣ የሚያዩትን ባዶ ቦታ ሁሉ ካልሠራንበት የሚለው አካሔድ እንደ ሀገር አስማምቶ ሊያኖረን እንደማይችል ማስገንዘብ ይገባል፡፡ እውነት እንነጋገር ከተባለ ሰማንያ በመቶ የሚሆነው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ ያለው ቤተ እምነትና ፕሮቴስታንትና እስልምና ቢደመር ሃያ በመቶ ባይሆኑም እያንዳንዳቸው ያላቸው ቤተ እምነት ከኦርቶዶክሱ እጥፍ ሊሆን ምንም አይቀረው፡፡ ይህን እያወቅን እንኳ ያልጠየቅነው ከሁሉ በፊት ለሀገር ማሰብና ለሰላም መስፈን መሥራት ይገባል ብለን ስለምናምን ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያኗ ላይ እየተፈጸመ ያለው ጥፋት ያሳሰበው ዜና ቤተ ክርስቲያን በጥቅምት ኅዳር ፳፻፲፩ ዓ.ም ዕትሙ ‹‹ለሁሉም በተሰጠው ገደብ የለሽ የእምነት ነፃነት መሠረት፣ ሁሉም የራሱን እምነት በሰላም ማራመድ ሲገባው በተቃራኒው ፀረ ኦርቶዶክስ ዘመቻ በሁለት ግንባር በመካሔድ ላይ ይገኛል፡፡ በአንድ በኩል ቀደም ሲል በዝርዝር እንደተገለጠው ፀረ ክርስትና አቋም ያለው ቡድን በአንዳንድ አካበቢዎች የሚገኙትን የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያን እያቃጠለ ነው፡፡ ካህናትንና ምእመናንንም እያረደ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ እነ ፖስተር ኢዩ ጩፋን የመሳሰሉት የእነ ሬንሐርድ ቦነኬ ደቀመዛሙርት በቡድን ተሰማርተው ሕዝቡን በወንጌል ሳይሆን በመናፍስት በማስገደድና በካራቴ በማሳመን የእነርሱ ተከታይ ለማድረግ እየጣሩ ነው›› በማለት በርእሰ አንቀጹ ጽፎ ነበር፡፡

የሚገርመው ይህ ጥፋት በመቀነስ ፈንታ እየጨመረ፣ በመሻሻል ፈንታ እየባሰበት መምጣቱ ነው፡፡ የችግሩ መሞከሪያ፣ የጸጥታው ማስፈጸሚያ ቤተ ክርስቲያንና ክርስቲያኖች እስከሚመስሉ ድረስ በክርስቲያኖች ሞትና መከራ ላይ መከራ እየተደረገ ሀገር ትረጋጋለች ተብሎ ስምምነት ላይ የተደረሰ ያስመስላል፡፡ ይህ ጥፋት ሁል ጊዜ ሰበብ እየተፈለገ እንዲቀጥል አንፈልግም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሲቃጠል በግል የተፈጸመ፣ ክርስቲያኖች ሲገደሉ የግል ጠብ እየመሰለ መነገሩ በጀርባው ሌላ ተንኮል ያለ መሆኑን እየተገለጠልን መምጣቱን መረዳት ይገባል፡፡ ሀገር በጠባጫሪነትና ሁሉ ነገር ለእኔ በሚል መንፈስ መገንባት እንደማትችል የታወቀ ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን መረጃው እያለው እንደ ሌለው፣ ግልጽ አድልዎ እየተፈጸመ መሆኑን እያወቀ ዝም ያለው አጥፊዎችም አደብ ይገዛሉ፣ መንግሥትም እርምት ይወስዳል በማለት ነው፡፡ አሁን ግን የሚፈጸመው ጥፋት እየከፋ መጥቷል፡፡ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስን ማኅበር ለመዘከር የቤት ጉዝጓዝ ሊያጭድ የሔደን ክርስቲያን በገጀራ ከትክቶ ሽንት ቤት መክተት፣ በየቦታው ኦርቶዶክሶች እየተመረጡ አካባቢያቸውን እንዲለቁ መደረጉ የአደባባይ ምሥጢር ነው፡፡ ይህ ሲደረግ መረጃው እንዳይወጣ መደበቁ እንደ ሀገርም እንደ ቤተ ክርስቲያንም መሠራት ያለባቸው ጉዳዮች መኖራቸውን የሚያሳዩ ናቸው፡፡

በቤተ ክርስቲያን እንዳይሠለስ እንዳይቀደስ ከማድረግ በተጨማሪ በደቡብ ክልል ጎፋ ዞን የሚገኘው የመሎላሃ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ጥምቀተ ባሕር ሥልጣን ላይ በተቀመጡ የፕሮቴስታንት ተከታዮች ለአውቶቢስ መናኽሪያ መሰጠቱና ታቦትና ንዋያተ ቅድሳታችሁን ይዛችሁ ውጡ ተብለው በእግራቸው ፻ ኪሎ ሜትር በላይ ታቦትና ንዋያተ ቅድሳት ይዘው መንከራተታቸው በፈጠረው የማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ጫና የተደናገጡ ባለ ሥልጣናት ታቦቱ ወደ መንበሩ እንዲመለሰ ያደረጉበት ታሪክ የሦስት ወር ትዝታ ነው፡፡ እንዲስተካከል የምንፈልገውም እንዲህ አይነቱ መጥፎ ተግባር ነው፡፡ ሕሊናቸው የመራቸውን፣ መንግሥት የሰጣቸውን ኃላፊነት የሚወጡ የሌላ እምነት ተከታይ ወገኖች እንዳሉ ሁሉ የተሰጣቸውን ኃላፊነት ለጥፋት የሚጠቀሙ መኖራቸው፣ በጥፋት ላይ ጥፋት እያስከተለ በመሆኑ በቶሎ መታረም አለበት፡፡

በሶማሌ ክልል አሥር አብያተ ክርስቲያን እንዲቃጠሉና ከሃያ ሰባት በላይ ምእመናን እንዲገደሉ፣ ብዙዎችም እንዲቈስሉ የተደረገው በመንግሥት መዋቅር ነው፡፡ የዚህን ድርጊት ተገቢ አለመሆን የተረዳው አዲሱ የሶማሌ መንግሥት አመራር ቤተ ክርስቲያኗን ይቅርታ መጠየቁን ጠቅላይ ሚኒሰትሩ የደሴ ከተማ ነዋሪዎችን ባወያዩ ጊዜ ሲናገሩ ሰምተናል፡፡ አጥፊዎች ከስሕተታቸው ቢመለሱና አስቀድመው ጥፋት ከመፈጸማቸው በፊት ደጋግመው ቢያስቡ መልካም ነው፡፡ ይህም ባይሆን ከተፈጸመ በኋላም ይቅርታ መጠየቃቸው የሚያሰመሰግን ነው፡፡ ይቅርታ መጠየቁ ብቻውን በቂ ባለመሆኑም ተጨማሪ ተግባራትን መፈጸም ይገባል፡፡ በያዘው ሥልጣን የቤተ ክርስቲያንን ይዞታ እየነቀለ፣ ክርስቲያኖችን የገደለ በቃሉ ብቻ ይቅርታ በማለት እንዳይቀጥል ደንብና ገደብ ቢኖረው መልካም ነው፡፡ ይቅርታው ከስሕተት መታረሚያ፣ ዳግም ስሕተት ላለመፈጸም ቃል መግቢያ እንዲሆን መሥራት ይገባል፡፡ ይህንን ጉዳይ ወደ ፊት ሰፋ አድርገን ስላምናቀርበው በዚሁ እናቁምና በተለያዩ ቦታቸው የተፈጸሙ በምእመናን ላይ የደረሱትን ግድያዎች እናስከትላለን፡፡

ሐ. በምእመናን ላይ የደረሰ ግድያ፡-

ቤተ ክርስትያን ባለችበት ሁሉ ምእመናን አሉ፡፡ ምእመናን ቤተ ክርስቲያናቸው እየተቃጠለች ቆመው ማየት ስለማይችሉ ወይ አብረው ይቃጠላሉ ካልሆነም በአጥፊዎች ይገደላሉ፡፡ ይህም ፍርሃታቸውን ሳይሆን ጥብዓታቸውን፣ በመግደል ሳይሆን በመሞት አሸናፊዎች መሆናቸውን ማረጋገጣቸውን ያሳያል፡፡ በሊቢያ የሚገኘው አሸባሪው አይኤስአይኤስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ክርስቲያኖችን ብቻ መርጦ ለመግደል ሲወስዳቸው በሰማዕታቱ ላይ ይነበብ የነበረው በራስ መተማመን ወደ ሞት ሳይሆን ለንግሥና ታጭተው የሚሔዱ ይመስል ነበር፡፡ ብዙዎች የውጭ ሚዲያ ጋዜጠኞችና የማኅበራዊ ብዙኃን መገናኛ ጸሐፊዎች እንዲህ አይነት ምእመናንን በእምነት አንፃ የምታወጣ ቤተ ክርስቲያን አማኝ መሆን የሚያስገኘውን ክብር ሲገልጡ ነበር፡፡ በአንጻሩ በመግደል እናሸንፋለን ብለው ያሰቡ አሸባሪዎች የሚቀናባቸው ሳይሆን የሚጠቋቆምባቸው ቢያተርፉና የሚተቻቸው ቢያገኙ እንጂ የተስተካከለ አእምሮ ካለው ሰው ምስጋና አያገኙም፡፡ አራት ዓመት ቢያልፍም የክርስቲያኖች ጥብዓታቸው፣ ሞትን ለዘለዓለማዊ ሕይወት መውረሻ መሆኑን ስለአወቁ በደስታ መጓዛቸው ዛሬም ድረስ ይተረካል፡፡ ባለፈው ታኅሣሥ የሊቢያ መንግሥት በጅምላ ተገድለው የተቀበሩበትን ቦታ አግኝቶ ለኢትዮጵያ መንግሥት እንደሚመልስ ሲናገር ክብራቸውን በመግለጥ ጭምር ነው፡፡

የክርስቲያኖች መገደል ተገቢ አለመሆኑን የምንገልጠው በዐዋጅ የሚፈጸም ስለሚመስል እንጂ እንደ ዘመነ ሰማዕታት ክርስቲያኖችን የሚፈጅ መንግሥት ቢሆን ለምን ለማለት አይደለም፡፡ መንግሥት በውጭና በሀገር ውስጥ የነበሩትን አባቶች ማስማማቱ፣ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሀገር መሆኗን መግለጡ፣ በደርግ ተወስደው የነበሩ ቤቶችን መመለሱ መልካም ነው፡፡ ይህ ብቻ ግን በቂ አይደለም መሬታችን ኦርቶዶክስ ሃይማኖትን እየሰበከ ሕዝቡ የሌላ እምነት ተከታይ እንዲሆን የሚሠሩ ስለአሉ ቆመን ማየት የለብንም፡፡ የአጥፊዎችን ድርጊት ይህንንም በገሀድም ሆነ በስውር የሚደግፉ ስለአሉ መንግሥት መፍትሔ እንዲሰጥ ለማሳሰብ ነው፡፡ መንግሥትን ስናሳስብ የሰማዕትነትን ዋጋ ዘነግተን፣ ሰማዕትነትን ፈርተን ሳይሆን ዕለት ዕለት ሰማዕትነት እንደምንቀበል አምነን ዘመኑ የሚጠይቀውን ለመፈጸም የምንችለውን ሁሉ ለማድረግ ነው፡፡ ይህንንም መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹አይሁድ ስለ ጳውሎስ ከፊት ይልቅ አጥብቀህ እንደምትመረምር መስለህ ነገ ወደ ሸንጎ ታወርደው ዘንድ ሊለምኑህ ተስማምተዋል፡፡ እንግዲህ አንተ በጄ አትበላቸው፤ እስኪገድሉት ድረስ እንዳይበሉና እንዳይጠጡ ተማምለው ከእነሱ ከዐርባ የሚበዙት ሰዎች ያደቡበታልና፤ አሁንም የተዘጋጁ ናቸው፣ የአንተንም ምላሽ ይጠብቃሉ አለው፡፡›› (ሐዋ.ሥ ፳፫፥፳‐፳፪) በማለት የተገለጠውን ማስተዋል ይገባል፡፡ ጥፋትን የሚፈጽሙና የግል ጥቅማቸውን የሚያሳድዱ አካላት ፍትሐዊና ቀና የሆነውን አሠራርና ሕግ ለራሳቸው በሚመች መንገድ የሚጠቀሙበት መሆኑን ይህ ቃል ያስረዳል፡፡ ልንነቃ የሚገባው የአካሔዳቸውን መሠሪነት ነው፡፡ እነሱ ሐሰትን ታሪክ አስመስለው ሲጽፉ ሕሊናቸውን አየቆጠቁጠውም እንዲያውም ለአምላካቸው መብዓ ያቀረቡ የሚመስላቸው አካሔዳቸው ተገቢ አለመሆኑን የሚያስገነዝብ መልስ ሲሰጣቸው ደግሞ መረጃ ይዞ ተከራክሮ እውነቱን ከማውጣት ይልቅ ትክክለኛ ጉዳይ የጻፉትን አካላት ስም በማጥፋትና ጉዳዩን ሌላ መልክ በመስጠተ ሌሎች እንዳይጽፉ ለማድረግ ይሞክራሉ፡፡ የተቀመጡበትን ወንበር መከታ አድርገው ሕዝብን በሕዝብ ላይ እንደማነሣሣት፣ ሃይማኖትን ከሃይማኖት እንደማጋጨት ይቈጥሩታል፡፡ መታወቅ የሚኖርበት ኦርቶዶክሳውያን ሲጽፉ ብቻ ጠብ አጫሪ መባል የማይገባቸው መሆኑን ነው፡፡ የሕዝብ ሰላም የሚያሳጣ፣ ከልማት ጥፋትን የሚያመጣ ተግባር ከፈጸሙ ለዚህ የጥፋት ተልእኮአቸው መልስ መስጠታችን፣ ሕዝበ ክርስቲያኑን ማንቃታችን የማይቀር ነው፡፡ እውነተኞች ከሆኑ የምንለያይበትንና የምንጋጭበትን እየፈለፈሉ በማውጣት ተአማኒነት ያለው ጽሑፍ ማቅረብ ነው፡፡ በዚህ ፈንታ የሚመርጡት በለመዱበት መንገድ መንግሥት በተቀየረ ቊጥር እየተጠጉ ኦርቶዶክሳውያንን ማስጠላት ነው፡፡ ይህን የምንለው እየተፈጸመ ያለው ጉዳይ ለሀገር አንድነት የማይጠቅም በመሆኑ በሌላ በኩል እነሱ በሔዱበት መንገድ መሔድ የሚያደርሰውን ጥፋት በመገንዘብ ነው፡፡

ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፮

ማእከለ ክረምት

ዲያቆን ዘክርስቶስ ፀጋዬ

ዘመነ ክረምት የሚጋመስበት ወቅት ማዕከለ ክረምት ይባላል፡፡ በዚህ ክፍል ውስጥ ሁለት  ንኡስ ክፍል ይገኛሉ፤ እነርሱም ዕጒለ ቋዓት እና ደሰያት / ዐይነ ኩሉ/ በመባል ይታወቃሉ፡፡ ይህም ወቅት ከነሐሴ ፲፩ – ፳፯ ቀን ድረስ ያለውን ፲፯ ዕለታት ያካትታል፡፡ ፍጥረታትና በባሕር የተከበቡ ደሴቶች የሚታወሱበት ወቅትም ነው፡፡

ዕጒለ ቋዓት- የሚለው ቃል ቁራን ያመለክታል፤ ቁራ ከእንቁላሉ ተቀፍቅፎ ሲወጣ ያለ ፀጉር በሥጋው ብቻ ይወጣል፡፡ እናትና አባቱም እነርሱን ባለመምሰሉ ደንግጠው ይሸሹታል፤ በዚህ ጊዜ የሚንከባከበው ሲያጣ እግዚአብሔር በረድኤት አፉን ከፍቶ ምግብ ሲሻ ተሐዋስያንን ብር ብር እያደረገ ከአፉ ያስገባለታል፡፡ (ኢዮ. ፴፰፥፵፩) «ለቁራ መብል የሚሰጠው ማን ነው?›› ብሎ እንደገለጸው እግዚአብሔር የሰጠውን እየተመገበ ቆይቶ ሲጠነክር እንደ እናትና አባቱ ያለ ፀጉር ያወጣል፡፡ በዚህ ጊዜ ግን አባቱና እናቱ ቀርበው ይንከባከቡታል፡፡ ቁራ በሥነ ፍጥረት አቆጣጠር በክንፍ ከሚበሩ አዕዋፍ ነው፡፡ ይህም አምላካችን እግዚአብሔር ለፍጥረቱ የሚያስብ በመሆኑ ይህን ዘመን ርኅራኄ ለተመላው ሥራው መታሰቢያ እንዲሆን ቤተክርስቲያን ዕለ ቋዓት በማለት ታስታውሳለች፡፡

ደሰያት – የሚለው ቃል በውኃ የተከበቡ ቦታዎችን ያመለክታል፡፡ እነዚህን ቦታዎች በውኃ እንዲሸፈኑ አድርጎ በውስጣቸው ያሉትን ሰዎች እንስሳት፤ አራዊትና አዕዋፍ ሁሉ የሚጠብቃቸው፣ በተስፋና በእምነት አበርትቶ የሚያኖራቸው እግዚአብሔር ነው፡፡ ስለዚህም ሰዎች እግዚአብሔርን በዚህ ያመሰግኑታል፡፡ ደሴት የቤተክርስቲያን ምሳሌ ናት፤ አንዲት ደሴት በውስጧ ብዙ ፍጥረታትን ትይዛለች፡፡ ከደሴት የተጠጉ ድኅነትን እንደሚያገኙ ሁሉ ወደ ቤተክርስቲያን የተጠጉ ሁሉ ከሞተ ሥጋ ከሞተ ነፍስ ይጠበቃሉ፡፡

በዚህ ዕጒለ ቋዓትና ደሰያት ወቅት ክፍለ ክረምቱ እየተገባደደ፣ ውኃው እየጠራ፣ መሬቱ እየረጋ፣ ደመናውና ጉሙ እየተቃለለ፣ የወንዝ ሙላት እየቀነሰ፣ የክረምት ምግባቸውን ይዘው በየዋሻው የከረሙ ጭልፊቶችና አሞራዎች ድምጻቸውን እየሰሙ ምግብ ፍለጋ ሲወጡ የሚታይበት ወቅት ነው፡፡

‹‹ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት፣ ቡሄ ካለፈ የለም ክረምት›› እንዳለው፤ ዝናብ ይቀንሳል፣ ምድሪቱም መቀዝቀዝና መጠንከር የምትጀምርበት ወቅት ነው፡፡

ቅድስት ቤተክርስቲያን በዚህ ወቅት እግዚአብሔር አምላክ ለሥጋ ሁሉ ምግብን የሚሰጥ ምሕረቱም ለዘላለም የሆነውን የሰማይን አምላክ መሆኑንና ፍጥረታትም ሁሉ እርሱን ተስፋ የሚያደርጉ መሆናቸውን የሚገልጡ መዝሙራት፣ ትምህርት፣ ስብከት ይሰጣል፣ ይነበባል፡፡ (መዝ.፻፵፬፥፲፮-፲፯)

በተጨማሪ በዚህ በማእከለ ክረምት ‹‹ዕረፍተ አበው›› ከነሐሴ ፳፯ እስከ ነሐሴ ፳፱ ድረስ ባለው ጊዜ ይታሰባል፡፡ ከ፳፪ቱ አርዕስተ አበው አብርሃም፣ ይስሐቅና ያዕቆብ የቤተሰቦቻቸው ዕረፍት ይታሰባል፡፡ የአብርሃም ታዛዥነት እና የይስሐቅ ቤዛነት ይታሰባል፡፡ የተቀበሉትም ቃልኪዳን ‹‹ወተዘከረ ሣህሉ ዘለዓለም ዘሠርዓ ለአብርሃም መመሐለ ለይስሐቅ ወዐቀመ ስምዐ ለያዕቆብ ያረኁ ክረምተ ይገብር ምሕረተ እምሰማይ ይሁብ ወእምድር በረከተ ያጸግብ ነፍሰ ርኅብተ›› በማለት ይዘመራል፡፡

ስምና የስም ዓይነቶች

ዲያቆን ዐቢይ ሙሉቀን

ስም “ሰመየ፤ ስም አወጣ፣ ጠራ፣ ለየ” ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም መጠሪያ መለያ፣ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ስም ማለት መጠሪያ፣ መለያ፣ አንድን አካል ከሌላው አካል የምንለይበት ማለት ነው፡፡ “እግዚአብሔር አምላክም የምድር አራዊትንና የሰማይ ወፎችን ሁሉ ደግሞ ከምድር ፈጠረ፤በምን ስም እንደሚጠራቸውም ያይ ዘንድ ወደ አዳም አመጣቸው፤    አዳምም ሕያው ነፍስ ላለው ሁሉ በስሙ እንደጠራው ስሙ ያው ሆነ፡፡ አዳምም ለእንስሳት ሁሉ ለሰማይ ወፎችም ሁሉ ለምድር አራዊትም ሁሉ ስም አወጣለቸው” (ዘፍ፪፥፲፱-፳) እንዲል፡፡ በመጽሀፈ ቀሌምንጦስም “ወሰመዮሙ ለኵሎሙ በበአስማቲሆሙ ወተአዘዙ ሎቱ ኵሉ ፍጥረት ወዓቀቡ ቃሎ፤ አዳም ለሁሉም በየስማቸው ሰየማቸው፣ ስም አወጣላቸው፤ ፍጥረት ሁሉ ለአዳም ይታዘዝና ቃሉንም ይጠብቅ ነበር” (ቀሌ፩፥፵፪) በማለት ተጽፎ እናገኛለን

የስም ዓይነቶች ፡-

ባለፈው እትማችን እንደገለጽነው ስም ከቃል ክፍሎች አንዱ ሲሆን በውስጡ ደግሞ የራሱ የሆኑ ክፍፍሎች አሉት በስም ውስጥ የሚካተቱትን የስም ዓይነቶች ከተለያየ አንጻር የተለያየ አከፋፈል አለ፡፡ ለምሳሌ ከአገልግሎት አንጻር፣ከአመሠራረት አንጻር እና ሌሎችም ሁለቱን በዚህ ርእሰ ጉዳይ እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

 የስም ዓይነቶች ከአመሠራረት አንጻር በሁለት ይከፈላሉ፡፡ እነሱም፡-

፩. ዘር(ምሥርት ስም)፡-

ከግስ የሚመሠረቱት ስሞች ምስርት ስሞች ይባላሉ፡፡ የግስ ዘር ያላቸው ወይም አንቀጽ ያላቸው ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ፡- አምላክ፣ ፈጣሪ፣መልአክ፣ ሐራሲ፣ ሐናጺ፣ ቤት፣ ወዘተ

. ነባር ስም፡-

አንቀጽ የሌለው ሁሉ ነባር ይባላል፡፡ ነባር ማለት እርባታ የሌለው በቁም ቀሪ ማለት ነው፡፡ እቤርት፣ ዕብን፣ ዳዊት፣ ወዘተ

ማስታወሻ፡- ነባር ስም የሚባል እንደሌለ አንዳንድ ሊቃውንት ያስረዳሉ ከእነዚህ መካከል ኪዳነ ወልድ ክፍሌ አንዱ ናቸው፡፡ ምንጩ ማለት ቃሉ የተመሠረተበትን ግስ ስለማይታወቅ፣ ስላልተለመደ እንጂ ነባር የሚባል ስም የለም፡፡ ሁሉም የግሰ አንቀጽ አለው ባይ ናቸው፡፡

. የስም ዓይነቶች ከአገልግሎት አንጻር በአምስት ይከፈላሉ፡፡ እነሱም፡-

፩. ስመ ባሕርይ (የባሕርይ ስም)

፪. ስመ ተቀብዖ (የሹመት ስም)

፫. ስመ ግብር (የግብር ስም)

፬. ስመ ተጸውኦ (የመጠሪያ ስም)

፭.ስመ ተውላጥ (መራሕያን)

የባሕርይ ስም ፡-  አምላክ፣ ፈጣሪ፣ እግዚእ፣ወዘተ

ስመ ተጸውዖ (የመጠሪያ ስም) ፡-

ይህ ስም እያንዳንዱ ሰው፣ እንስሳ፣ አራዊት፣ ዕፅዋት፣ ቦታ፣ ወዘተ ተለይቶ የሚጠራበት ስም ነው፡፡ “ፍጡር የሆነ ሁሉ ለግሉ የሚጠራበት ሰውም እያንዳንዱ ከእናት ከአባቱ ተሰይሞ እገሌ፣ እገሊት ተብሎ የሚጠራበት ይህን የመሰለ ሁሉ ነው” (መጽሐፈ ሰዋስው መጽሔተ አእምሮ፣ ገጽ ፮) እንዲል፡፡ ለምሳሌ ዳዊት፣ ሰሎሞን፣ ኢሳይያስ፣ ይድራስ፣ ሲና፣ ታቦር፣ ዘይት፣ ኢትዮጵያ፣ ኢየሩሳሌም፣ ከነአን

ስመ ተቀብዖ (የሹመት ስም) ፡-

ሰዎች ሲሾሙ የሚያገኙት ወይም የሚሰጣቸው የክብር ስም ነው፡፡ “የተቀብዖ ስም ሹመት ያለው ሁሉ …በመንፈሳዊና በሥጋዊ ነገር የሹመት ስም እርሱን የመሰለ ሁሉ ነው” ((መጽሐፈ ሰዋስው መጽሔተ አእምሮ፣ገጽ ፮) እንዲል፡፡ ለምሳሌ፡- ንጉሥ፣ ጳጳስ፣ ካህን፣ ዲያቆን፣ ሀቤ ምእት፣ መልአከ ሰላም፣ መለአከ ኃይል ወዘተ

ስመ ግብር (የግብር ስም) ፡-

ሥራን የሚገልጽ ስም ነው፡፡ “ፍጥረት ሁሉ በሥራው በግብሩ በአካሄዱ በነገሩ ሁሉ የሚጠራበት ነው ነው” (መጽሐፈ ሰዋስው መጽሔተ አእምሮ፣፮) እንዲል፡፡ ሐራሲ፣ ሐናጺ፣ መምህር፣ ለብሀዊ፣ ነጋዲ፣ ጸራቢ፣ ወዘተ

ስመ ተውላጥ፡- (መራሕያን) በስም ፈንታ የሚገቡ እንደስም የሚያገለግሉ ናቸው፡፡

አነ፣ ንሕነ፣ አንተ፣ አንትሙ፣ አንቲ፣ እንትን፣ ውእቱ፣ ውእቶሙ፣ ይእቲ፣ ውእቶን ናቸው፡፡ መራሕያን

ከላይ የተገለጸውን ጽንሰ ሐሳብ በምሳሌ እንመልከተው፡፡

                        ጉባኤ ቃና

ኢክህለ ሞት ሐራሲ ዐዲወ  ዕርገት ቀላይ፤

እስመ ለቀላይ ዕርገት ይመልኦ ደመና ዘቦ ሰማይ፡፡

ትርጉም

   ሞት ገበሬ   በዕርገት ወንዝ መሻገርን አልቻለም፤

ዕርገት ወንዝን ያለ የሆነ የሰማይ ደመና ይመላዋልና፡፡

ምሥጢሩ

ሰሙ፡- አንዳንድ ወንዝ እርሱ እንኮ ገና በደመና ነው የሚመላ ይባላል፡፡

ወርቁ፡- ጌታችን  በደመና  ማረጉን ለማስረዳት ነው፡፡

በዚህ ጉባኤ ቃና ከላይ በተመለከትነው ማብራሪያ መሠረት ነባርና ዘር(ምሥርት) ብለን በስም ክፍል ብቻ የሚመደቡትን እንጥቀስና የስም ክፍሎቻቸውን እንገልጻለን፡፡

ስም፡- ሞት፣ ሐራሲ፣ ቀላይ፣ ደመና፣ ዕርገት፣ ወልድ፣ አብ፣

ከአመሠራረት አንጻር የስም ዓይነት

ነባር ስም፡- ቀላይ

ምሥርት ስም፡- ሐራሲ፣ ደመና፣ ዕርገት፣ ወልድ፣ አብ፣

ከአገልግሎት አንጻር የስም ዓይነት

ስመ ተጸውዖ ፡- ወልድ፣ አብ፣

የግብር ስም ፡- ሐራሲ

እንዲሁ ሌላም እንጨምር

ሰላም ለኪ ፤እንዘ ንሰግድ ንብለኪ፤ ማርያም እምነ ናስተበቊዐኪ፤ እምአርዌ ነዐዊ ተማኅፀነ ብኪ፤ በእንተ ሐና እምኪ፤ ወኢያቄም አቡኪ፣ ማኅበረነ ዮም ድንግል ባርኪ፡፡

ስም፡- ማርያም፣ እምነ፣ አርዌ፣ ነዐዊ፣ ሐና፣ ኢያቄም፣ አቡኪ፣ ድንግል፣

ከአመሠራረት አንጻር የስም ዓይነት

ነባር ስም፡- ማርያም፣ ሐና፣ ኢያቄም ፣እምነ

ምሥርት ስም፡- አርዌ፣ ነዐዊ፣ አቡኪ፣ ድንግል፣

ከአገልግሎት አንጻር

ስመ ተጸውዖ ፡- ማርያም፣ ሐና፣ ኢያቄም

የግብር ስም ፡- ነዐዊ

የስምን ምንነትና የስም ዓይነቶችን ለአሁኑ እንዲህ ዓይተናል፡፡ በሚቀጥለው ደግሞ በየወገኑ በየወገኑ ከፋልፈልን የስምን ዓይነት ለምሳሌ ተዘምዶን የሚያመለክቱ፣ የአካል ክፍሎችን የሚያመለክቱ፣ የቁሳቁስ ወዘተ በማለት ከምሳሌ ጋር እንመለከታለን፡፡ እስከዚያው ግን ውድ አንባቢ የሚከተለውን መልመጃ ሠርተው እንዲቆዩ እናሳስባለን፡፡

መልመጃ

በሚከተለው ምንባብ ውስጥ ያሉትን ስሞች አውጥተህ/ሽ የስም ክፍላቸውን ዘርዝር/ሪ

ጸሎተ እግዝእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ ታዐብዮ ነፍየ ለእግዚአብሔር ወትትሐሠይ መንፈስየ በአምላኪየ ወመድኃኒየ እስመ ርእየ ሕማማ ለአመቱ ናሁ እምይእዜሰ ያስተበፅዑኒ ኵሉ ትውልድ እስመ ገብረ ሊተ ኃይለ ዐቢያተ ወቅዱስ ስሙ ወሣህሉኒ ለእለ ይፈርህዎ ወገብረ ኃይለ በመዝራዕቱ ወዘረዎሙ ለእለ የዐብዩ ኅሊና ልቦሙ ወነሰቶሙ ለኃያላን እመናብርቲሆሙ አዕበዮሙ ለትሑታን ወአጽገቦሙ እምበረከቱ ለርኁባን ወፈነዎሙ ዕራቆሙ ለብዑላን ወተወክፎ ለእስራኤል ቊልዔሁ ወተዘከረ ሣህሎ ዘይቤሎሙ ለአበዊነ ለአብርሃም ወለዘርዑ እስከ ለዓለም፡፡

ስም………………………….

የስም ዓይነት

ስመ ተጸውዖ ………………..

ስመ ግብር …………………..

ስመ ባሕርይ…………………….

ስመ ተቀብዖ፡………………….