ጾመ ፍልሰታ/ጾመ ማርያም/

መጋቤ ሐዲስ ብርሃን አንለይ

ፍልሰታ ማለት ፈለሰ፤ተሰደደ፤ተጓዘ፤ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ሄደ ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ቃል ሲሆን ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ «ፈለሰት ማርያም እምዘይበሊ ኀበኢይበሊ፤ ድንግል ማርያም ከሚያልፈው ዓለም ወደማያልፈው ዓለም፣ ከምድር ሕይወት ወደ ሰማያዊ ሕይወት፣ ተሻገረች» በማለት ፍልሰታ የሚለውን ቃል ትርጓሜ አመሥጥሮ ገልጾታል፡፡

ጾመ ፍልሰታ ከእመቤታችን ድንግል ማርያም የዕረፍት ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ እመቤታችን በዚህ ዓለም ፷፬ ዓመታትን በሕይወተ ሥጋ ከቆየች በኋላ ጌታችን የእናቱን ተድላ ነፍሷን እንጂ ተድላ ሥጋዋን አይወድምና ጥር ፳፩ ቀን ፵፱ ዓመተ ምሕርት አረፈች፡፡ ዕረፍቷም እንደሌላው ሰው በሕማምና በድካም አይደለም፡፡ በገነት ዕፀዋት መዓዛ ተመስጣ ቅድስት ነፍሷ ከሥጋዋ ተለይታለች፡፡ ታሪኩ በነገረ ማርያም እንደተጻፈው ሐዋርያት እመቤታችንን በአጎበር አድርገው አክብረው ወደጌቴሴማኒ መካነ መቃብር ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ ለምቀኝነት አያርፉም ነበርና ቀድሞ ልጇን ተነሣ ዐረገ እያሉ ሲያውኩ ኖረዋል፤  እርሷን ደግሞ ተነሣች ዐረገች እያሉ ሊያውኩን ነውና «ኑ የማርያምን ሥጋ በእሳት እናቃጥለው» ብለው በምቀኝነት ተነሱ፡፡ ከመካከላቸው አንድ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ከሐዋርያት እጅ ለመንጠቅ ዘሎ ሄዶ የአልጋውን ሸንኮር ሲይዝ የታዘዘ መልአክ በረቂቅ ሰይፉ እጆቹን ቆረጠው፡፡ እጆቹም በአልጋው ሸንኮር ላይ ተንጠልጥለው ቀሩ፡፡ የምሕረት እናት የሆነችው ድንግል ማርያም ቅዱስ ጴጥሮስ ጸልዮ እጆቹን እንዲመልስለት ነግራው እንደነበረ አድርጎለታል፡፡

የእመቤታችን ሥጋዋን መላእክት ከዮሐንስ ወንጌላዊ ጋር በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር ወስደው አስቀምጠውታል፡፡ ሥጋዋ ያለበትን ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ አይቶ እነርሱ ባለማየታቸው እመቤታችን ባረፈች በ፮ኛው ወር ከነሐሴ ፩ ቀን እስከ ፲፬ ቀን ድረስ ከጾሙ በኋላ በ፲፬ኛው ቀን ሥጋዋን እንደገና ከጌታ ተቀብለው በጌቴሴማኒ ባለው መቃብር ቀብረውታል፡፡ ከዚህ በኋላ እንደ ልጇ በ፫ኛው ቀን ተነሥታ መላእክት እየዘመሩላት ወደሰማያት ስታርግ፤ ሐዋርያው ቶማስ ከሀገረ ስብከቱ በደመና ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመለሰ ዕርገቷን በማየቱ መላእክት «እመቤትህ እርሷ ናት፤ስገድላት» አሉት፤ እርሱም «ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ ይላል፤ከደመናው ሊወድቅ ወደደ» ምክንያቱም ቀድሞ የልጇን ትንሣኤ፤ዛሬ ደግሞ የእርሷን ትንሣኤ ለማየት ብሎ ነው፡፡ እመቤታችንም «ትንሣኤየን ያየህ አንተ ነህ ሌሎቹ አላዩም» ብላ ሐዋርያት ገንዘው የቀበሩበትን የሐር ግምጃ ሰጥታ አጽናንታ ሰደደችው፡፡

ቅዱስ ቶማስ ኢየሩሳሌም ሲደርስ የእመቤታችን ነገር እንዴት ሆነ ብሎ ጠየቃቸው፤እነርሱም አግኝተው እንደቀበሯት ነገሩት፤ እርሱም ያየውን ምሥጢር በልቡ ይዞ «ሞት በጥር፤ በነሐሴ መቃብር፤ ለሰሚውም አያምር፤ይህ እንዴት ይሆናል?»፤ ቢላቸው ቅዱስ ጴጥሮስ «ድሮም አንተ ተጠራጣሪ ነህ፤ማን ያርዳ የቀበረ፤ ማን ይናገር የነበረ እንዲሉ፤ ገንዘን የቀበረን እኛ እያለን እንዴት ትጠራጠራለህ» ብለው ወደ መቃብሯ ሄደው መቃብሯን ቢከፍቱት ባዶ ሆኖ አገኙት፡፡ በዚህ ተደናግጠው ተያዩ፤ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ቶማስ «አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችን ተነሣች፤ዐረገች፤ ይኸው ምልክቱ» ብሎ ገንዘው የቀበሩበትን ሰበን አሳያቸው፤እነርሱም አምነው ሰበኗን ለበረከት ተካፈሉት፡፡

በዓመቱ ነሐሴ ፩ ቀን ሐዋርያት በመንፈሰዊ ቅናት ተነሳስተው «ቶማስ ትንሣኤዋን አይቶ እኛ ሳናይ እንዴት ይቀርብናል» በማለት ነሐሴ ፩ ቀን ሱባኤ ጀምረው በ፲፮ኛው ቀን የሐዋርያትን ሱባኤ ተቀብሎ እመቤታችንን መንበር ጴጥሮስን ተራዳኢ፣ ካህን እስጢፋኖስን ሠራዔ ዲያቆን አድርጉ ቀድሶ አቅርቧቸዋል፡፡ ከዚያ ጊዜ በኋላም ከነሐሴ ፩ እስከ ፲፭ ቀን  ጾመ ፍልሰታ ተብሎ ሁሉም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታይ ይጾመዋል፡፡ የጾሙና የትንሣኤዋ በረከት ተካፋይ ያድረገን፤አሜን

አብያተ ክርስቲያናት መቃጠላቸውና መዘረፋቸው ተገለጸ

 

                                                                                                                                                                                                                                                                       በሕይወት ሳልለው     

በሲዳማ ጌዴኦ አማሮና ቡርጂ አህጉረ ስብከት በሁላ ወረዳ ቤተክህነት ሥር ወይም በሁላና ቦና ዙሪያ ወረዳ ፫ አብያተ ክርስቲያናት በጥፋት ኃይሎች መቃጠላቸውና ፪ ደግሞ መዘረፋቸው  ተገለጸ፡፡ከሐምሌ ፲፩ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ጀምሮ ለሦስት ተከታታይ ቀናት በቆየው የሲዳማ ዞን ክልል ይሁንልን ጥያቄ ረብሻ ለአብያተ ቤተ ክርስቲያናት መቃጠልና መዘረፍ መንስኤ መሆኑም ተገልጿል፡፡

መጋቤ ጥበባት ቀሲስ ሞላልኝ መርጊያ፤ የሲዳማ፤ጌዴኦ፤አማሮና ቡርጂ አህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ «ሀገረ ስብከቱ ከወረዳ ቤተክህነት ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ጥበቃቸውን እንዲያጠናክሩና ምእመናንም ተደራጅተው ራሳቸውንና አብያተ ክርስቲያናትን እየጠበቁና እንዲከላከሉ መልእክት የተላለፈ ቢሆንም የጥፋት ኃይሎቹ ከአካባቢው የፀጥታ ኃይልና ከምእመናን አቅም በላይ በመሆናቸው የከፋ ጉዳት ሊያደርሱ ችለዋል» በማለት አስረድተዋል፡፡የደረሰው ቃጠሎ በመጀመሪያ በዶያ ቅዱስ ሚካኤል የ፲፰ አባወራዎችን ንብረት በማጥፋት፤ ፸፪ ንዋያተ ቅዱሳትን ሙሉ በሙሉ በእሳት አውድሟል፡፡ ቤተክርስቲያኗን ለማትረፍ ሲረባረቡ የነበሩትን ፲ ሰዎችም አደጋ እንደደረሰባቸው ታውቋል፡፡

ዶያ ቅዱስ ሚካኤል

በሌላ በኩል በ፳፻፰ ዓ.ም. ተመሥርቶ ከኅዳር ፲ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም. ጀምሮ አገልግሎት መስጠት የጀመረው የጋታማ ገብረ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን በአካባቢው ጥፋት ኃይሎች በእሳት ሙሉ ለሙሉ ተቃጥሏል፡፡ ፵፫ አባወራዎች ንብረታቸው ሲዘረፍና ሲቃጠል፤  በአይነት ፵፯ የሚሆኑ ንዋያተ ቅድሳት ሙሉ በሙሉ በእሳት ተቃጥለዋል፡፡

፵፫ የሚሆኑ አባወራዎች ደግሞ ከቤተሰቦቻቸው ጋር በየሰው ቤት ተጠልለው እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የገታማ ገብረ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን

የሉዳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን የውስጥ ንዋያተ ቅድሳት በእሳት ተቃጥለዋል፡፡ የቤተ  ክርስቲያኑ በር፤መስኮት እና መንበር ሲሰባበር፤ደጀ ሰላሙ ሙሉ በሙሉ ወድሟል፡፡ ሥርዓተ አምልኮ ሲፈጽሙ በነበሩ ምእመናን ላይም የሀብት ዝርፊያ በቤታቸው ተካሔዷል፡፡ አቶ ሽፈራው ማሞ በተባሉት አባት ከፍተኛ የአካል ጉዳትም እንደደረሰ ምንጮች አያይዘው ጠቅሰዋል፡፡

ሉዳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን

የጭሮኔ ቅዱስ አማኑኤል ቤተክርስቲያን ታቦተ ሕጉ እስከ አሁን ያለበት ቦታ አልታወቀም፡፡ ቤተ ክርስቲያኑንና ንዋያተ ቅዱሳቱን ያቃጠሉት ግለሰቦች የካህናትን ልብሰ ተክህኖና የሰንበት ተማሪዎች አልባሳትን ለብሰው፤ ቆብ አጥልቀውና መስቀል ይዘው በመዞር ከጨፈሩ በኋላ ተመልሰው ቤተ  ክርስቲያኗን ማቃጠላቸውን የዐይን እማኞች አብራርተዋል፡፡

ንዋያተ ቅዱሳቱን

በተጨማሪም በ፲፱፻፱ የተመሠረተው የቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን ደግሞ በደረሰው ጥቃት ሙሉ ለሙሉ ተዘርፏል፡፡ አገልግሎት እየሰጡ የነበሩ መቃብር ቤቶች በርና መስኮቶች ተሰባብሯል፡፡

የቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ  ክርስቲያን

ሦስት ኦርቶዶክሳውያን በአሰቃቂ ሁኔት ተገድለዋል፡፡ ፪፻፶ ምእመናን ተሰደው ቦሬ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ተጠልለው ይገኛሉ፡፡በተፈጠረው ችግር የ፹፭ ዓመቱ አቶ ግርማ መልካ መንገድ ላይ ተገድለው ሲገኙ፤አቶ የኔነህ ተስፋዬ መገደላቸውን፤ እና ወጣት አድሱ የኔነህ ደግሞ አባቱን እያሳከመ እንዳለ መገደሉን ተገልጿል፡፡

ይህን ችግር ለመቅረፍ ሀገረ ስብከቱ ከመከላከያ ሠራዊት ጋር በመተባበር በአካባቢው ላይ የነበሩትን ምእመናን ለመታደግ ችሏል፡፡ የተጎዱ ምእመናንን ለመደገፍና የተቃጠሉ አብያተ ክርስቲያናትን መልሶ ለማቋቋም ኮሚቴ መቋቋሙን የሐዋሳ ማእከል ገልጿል፡፡

በመሆኑም የኮሚቴው አባላት በጥፋቱ የተቃጠሉ አብያተ ክርስቲያናት መረጃ በመሰብሰብ፣ ምእመናንን በማጽናናትና ከሐዋሳ ከተማ ነዋሪዎች ድጋፍ በማሰባሰብ ተጎጂዎችን እየረዱ እንደሆነ ሀገረ ስብከቱ ገልጿል፤ ይበልጥ ለመደገፍ በባንክ አካውንት ቁጥር 1000290647936፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ውስጥ ከፍቶ ገንዘብ በማሰባሰብ ላይ ይገኛል፡፡

«ዕረፍተ ኅሊና»

                                                                                                                             

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ

እውነተኛ ዕረፍት በጎ ኅሊና ነው፤ ይውም ከእግዚአብሔር ጋር የሚያገናኝ ዘላለማዊ ዕረፍት ነው፤ክርስቲያን ዕረፍትን ለመፈለግ ሲል መከራ ሸሽቶ አይሔድም።ይልቁንም ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ብሎ በሚደክመው ድካም ውስጥ እጅጉን ይደሰታል።በዚህ ወደ አምላኩ በሚወስደው መንገድ በመጓዝ በሚገጥመው ፈታኝ ጉዞ በሚደርስበት ሥጋዊ ድካም ውስጥ መንፈሳዊ ደስታ ያለበትን ምቾትን ያገኛል። ለዚህ ነው (ሲራክ ፮፥፳፫) ላይ «ልጄ ሆይ ስማኝ፤ በምክሬም ጽና፤ ምክሬን አታቃልል፡፡ እግሮችህን ወደ ቀንበርዋ አግባ፤ ዛንጅርዋንም ባንገትህ እሰር፡፡ጫንቃህን ዝቅ አድርገህ ተሸከማት። በእግር ብረትዋ አትበሳጭ፡፡ በፍጹም ነፍስህም ወደ እርሷ ተሰማራ፤ በፍጹም ኃይልህ መንገዷን ጠብቅ፤ ፍለጋዋንም ተከተል፤ ፈልጋት፤ ታገኛታለህም፤ በፍጻሜህም ዕረፍትን ታገኛለህ፤ደስታም ይሆንሃል»

የዳኞችን ፍርድ በገንዘብ ማስለወጥ ይቻላል፤ ኅሊና ግን ከዚህ ልዩ ነው፡፡ ማንንም የማይገባውን ቅጣት ቀጥቶ አያውቅም፤ አስፈጻሚዎቹ እጅና እግር እና ሌሎች አካሎቻችን ፍርዱን ስለሚያበላሹበት ከኅሊና ፈቃድ ውጪ አይንቀሳቀሱም፡፡ ኅሊናው ሁልጊዜ በሰው ላይ እንጅ በራሱ አልፈርድለት ካለ ይህ ሰው እንስሳ ሆኗል ማለት ነው፤ (መዝ. ፵፰÷፳)፡፡  «ሰው ግን ክቡር ሆኖ ሳለ አላወቅም፤ልብ እንደሌላቸው እንስሳትም ሆነ፤መሰላቸውም» ብሎናል፤ ቅዱስ ዳዊት ዕራቁቱን የሚሄደው ሰው መብዛቱ፤ ቅጥ የሌለው ኑሮ በብዙዎቹ ዘንድ እየተለመደ መምጣቱም የዚህ ምልክት ነው፡፡

የኑሮ ውድነት ዘወትር ሲወራ የኅሊና ዋጋ ክርስትና ከሆነ በብር ለምን ይለካል? የምግብ እጥረት ላጋጠማቸው ምግብ የሚያቀርብ ድርጅት ተመሠረተ፤ የኅሊና ዕረፍት ላጡ እና ሕሊናቸውን ሸጠው ሰውነታቸው መቃብር ለሆነባቸው ሰዎችስ ምን ይደረግ ትላላችሁ? እኔ ግን አንድ ነገር እላችኋለሁ፤ የአምላካችን ቅዱስ ቃል መቃብራትን ይከፍታል፡፡ መቃብር የሆነ ልቡናችሁን ይከፍት ዘንድ ቅረቡ፤ (ማቴ ፳፯፥፶፪)«መቃብሮችም ተከፈቱ፤ ተኝተው ከነበሩ ከቅዱሳን በድኖችም ብዙዎች ተነሡ፤ ይለናል” የሰው ልጅ በዓላማው፣ በአመለካከቱ፣ በመረዳት ችሎታው፣ በአኗኗር ዘይቤው፣ እንደሚለያይ ሁሉ በዓለም ሲኖር የሚገጥሙትን ሥጋዊና መንፈሳዊ ችግሮች የመቋቋምና በትክክለኛ መንገድ የመጓዝ ችሎታውም ይለያያል፡፡ ሰዎች ለነገሮች የሚኖራቸው እይታ የተለያየ ነው፡፡ አንዳንዱ የሚገጥሙትን ተግዳሮቶች ቀለል አድርጎ ሲመለከታቸው ሌላው ደግሞ በጣም አክብዶና አጋኖ ሊመለከታቸው ይችላል፡፡ ሁለት ሰዎች አንድን ተመሳሳይ ክስተት የሚመለከቱበት ወይም የሚረዱበት መንገድ እንደሚለያይ ሁሉ የሚፈቱበት መንገድም ይለያያል፡፡ ለምሳሌ ተመሳሳይ የኢኮኖሚ ደረጃ ያላቸው ሁለት ሰዎች ከሥራ ቢሰናበቱ አንደኛው መታገሥን መርጦ የነገን ሲያልም ሌላኛው ግን ጨለማ ውስጥ እንደገባ መሥሎ ሊታየው ይችላል፡፡የአእምሮ ውጥረትን የመቋቋም ችሎታ በአጭር ጊዜ የሚመጣ ክሂሎት ሳይሆን በረጅም ጊዜ ልምምድ የሚመጣ ክሂሎት ነው፡፡

በኤልያስ ዘመን ፫ ዓመት ከመንፈቅ ሰማይ የነጠፈው ምድርም የተራቆተው (፩ ነገ.፲፯፥፩)፤ በሌላም ጊዜ ውሃን በማዝነም ፈንታ እሳትን እና ዲንን ያዘነመው (ዘፍ.፲፱፥፳፬፣፪፣፳፩፥፲፪)፤ በንጉሥ ሕዝቅያስ ዘመን በለኪሶን ሜዳ በአንድ ሌሊት አንድ መቶ ሰማንያ አምስት ሽህ ሬሳ የተገኘው(ኢሳ.፵፯፥፵፮) በሞዓብ ሜዳ ከነበረው ሕዝብ መካከል ፳፫ ሺህ ሬሳ በአንድ ቀን የተገኘው (፩ ቆሮ.፲፥፰) የሰው ልጅ ድንበር በማፍረሱም አይደል?

ዛሬስ ምድር በሰቆቃ የተሞላች መሆን፤ ለዓለማችን ፈውስ በሌለው ቁስል መመታትና በረከት ማጣት ተጠያቂው ማን ይሆን? ምን አልባት በአእምሮአችን ሌላ መልስ አስቀምጠን ይሆናል እንጅ ክፉውም ሆነ ደጉ ነገር የሥራችን ውጤት ነው፡፡ የፈርኦን ባሪያዎች በግብፅ ለተቃጣው መቅሠፍት ሁልጊዜ ተጠያቂ የሚያደርጉት ሙሴን ነበር እንጅ አንድም ቀን ይህ የኃጢአታችን ደምወዝ ነው ብለው አያውቁም(ዘፀ.፲፥፯)

ዛሬም ያለው ትውልድ ለአየር ንብረት መዛባት በኢንዱስትሪ የበለጸጉ ሀገራትን ለታናናሽ ሀገራት የጦርነት ቀጠና መሆን፤ ኃያላን መንግሥታት ለድኃ ሀገራት አለመበልጸግ ቅኝ ገዥዎችን ምክንያት ማድረግ ልማዱ ነው(የእኛ ለእነርሱ የክፋት ድርጊት ራሳችንን አመቻችተን ማቅረባችንን አናስተውልም)፡፡ የሆነብንን ሁሉ እንደ ነቢይ አምነን ለምንቀበል ሰዎች ስለ ኃጢአታችንና ስለ በደላችን ይህ ሁሉ ሆነ ሳለ ያለ ሕግ የሚበድሉ ሁልጊዜም ያለሕግ ይቀጣሉና(ዳን. ፱፥፲፮-፲፯)፤

ይህን ገጽታውን በግልባጩ የተመለከትነው እንደሆነ ደግሞ ምድረ በዳ የሌለው የአጋንንት ማረፊያ ነው፤ (ማቴ. ፲፪፥፵፫) በጾም እና በጸሎት ከሰው ልጆች እንዲወጡ የተገደዱ አጋንንት ወደ ምድረ በዳው ይሰማራሉ፤ ማረፊያ የሌለው በመሆኑ ግን ተመልሰው ወደ መጡበት ቤት ይገባሉ፡፡ በእርግጥ አሁንም የሚሸጋገሩት ከምድረ በዳ ባዶ ወደሆነ ቤት ነው፡፡ ይህ ለእነርሱ ምቹና ባዶም በመሆኑ አጋንንት ያድሩበታል፡፡ የሥጋ ፍሬን ብቻ ስለሚያፈሩ የመንፈስ ፍሬን ረስተውታልና ስለዚህ ያድሩበታል፡፡ ሰው በገዛ ፈቃዱ ሕይወትን ትቶ የኮበለለ ቢሆንም እግዚአብሔር ግን በሞት ወደ ተቀጣው የሰው ልጅ መጣ፡፡ የደከመውን የሰው ልጆች ባሕርይ ሊያበረታ መንገድ ከመሔድ ደክሞ ሊያርፍ ተቀመጠ ፤ ድካም ሳይኖርበት የሚታየውን እና የማይታየውን ዓለም የፈጠረ አምላክ ዛሬ ግን አዳምን ሊያድነው ወዶ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ለባሕርዩ የማይስማሙ ድካምና ሕማም የቃል ገንዘቦች ሆነው ተነገሩ፡፡«ኢየሱስም መንገድ ከመሄድ ደክሞ በጉድጓድ አጠገብ ተቀመጠ» (ዮሐ.፬፥፮) ተብሎ ለኃያሉ አምላክ ሲነገርለት እንደምን ይገርማል፡፡ መላእክትን ያለ ዕረፍት ሌሊት እና ቀን እንዲያገለግሉ ኃይል የሆናቸው ጌታ እኮ ነው (ራዕ.፬፥፰) ዛሬ ግን ደከመ፤ በእርሱ ድካም ፍጥረት እንዲበረታ ይህ ሁሉ ሆነ፡፡ ያውም ጊዜው ቀትር ነበር፤ የሚያቃጥል ፍጥረት ሁሉ ጥግ ፍለጋ እንዲሸጐጥ የሚያደርግ አስቸጋሪ ሰዓት!ማንም ሰው በኃጢአቱ እንዲሞት የእግዚአብሔር ፈቃድ አይደለም። (ሕዝ. ፲፰፥፴፪)

ክርስቲያን በእምነት ሕይወት ውስጥ ዕረፍትን ያገኛል እንዳለን ነቢዩ ኤርምያስ ፮፥፲፮ ላይ «በመንገድ ላይ ቁሙ፤ ተመልከቱ፤ የቀደመችውንም መንገድ ጠይቁ፤ መልካሚቱ መንገድ ወዴት እንደሆነች ዕወቁ፤በእርሷም ላይ ሒዱ፤ ለነፍሳችሁ ዕረፍትን ታገኛላችሁ»። እንዳለ እውነተኛ ዕረፍት የሚገኘው ከእግዚአብሔር ስለሆነ እኛም ወደ እርሱ በመቅረብ የማያቋርጥ ዕረፍትን እናገኛለን፡፡ እንዲሁም ለምናከናውነው ሥራ ሁሉ ስልቹ አንሆንም፤  ምክንያቱም የምናመልከው አምላክ ዘለዓማዊ ዕረፍትን ስለሚሰጠን ሥራን ሙሉ ለሙሉ በማቆም ማረፍ ሳይሆን መሰላቸትን በማቆም መንፈሳዊ ሥራንና ማኅበራዊ በጎ ሥራ በማከናወን ማረፍ ማለት ነው።

ልዑል እግዚአብሔር ሰውን ከፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ በሥርዓትና በሕግ እንዲመራ አድርጎታል። ለአኗኗሩ ሥርዓት አበጅቶለት ፍጥረታትን እንዲገዛ አዞና ሥልጣን ሰጥቶት በገነት እንዳስቀመጠው እውነት ነው። ስለሆነም የእግዚአብሔር ሕግ ስንልም ከእግዚአብሔር ፈቃድ የመነጨ፣ በእግዚአብሔር የተሰጠ፣ አምላካዊ ድንጋጌ ነው። በመጽሐፈ ሔኖክ ፲፱፥፳፪ ላይ የሰው ልጅ እንደ ንጹሐን መላእክት ሃይማኖቱን አውቆና ጠብቆ ፈጣሪውን በመፍራትና በማምለክ እንዲኖር ነው። በመዝሙር ፩፥፪ ላይ፤ «የእግዚአብሔር ሕግ ብቻ ፈቃዱ የሆነ፤ ሕጉንም በቀንና በሌሊት የሚያስብ፤ እርሱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደተተከለች፤ ፍሬዋን በየጊዜው እንደምትሰጥ፤ ቅጠሏ እንደማይረግፍ ዛፍ ይሆናል፣ የሚሠራውም ሁሉ ይከናወንለታል»

አስተውል! ያንተ ሕይወት ማለት እኮ እስከ ሞት የሚፋለም ባለቤት ያላት የናቡቴ ርስት ናት፡፡ ሕይወትህ በተቃራኒው የቆመች ምድረ በዳ ብትሆንብህም እንኳ አትፍራ፤እግዚአብሔር የምድረ በዳውም ፈጣሪ ነውና ለአርባ ዘመናት የመራውን ሕዝብ የውርጭ መና ከደመና አውርዶ የመገባቸው፤ውኃውንም ከዐለት ላይ አፍልቆ ያጠጣቸው፤ በምድረ በዳ መሆኑን አትርሳ፤ (መዝ ፸፯፥፳-፵) አንተም መናና ውኃ የተባለ የእግዚአብሔር ቃል ተመግበህና ጠጥተህ ምድረ በዳ የሆነ ሕይወትህን ልታለመልምበት ይገባል፡፡ ትናንት ከትምህርት ምድረ በዳ የነበረችውን የእነ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫን ሕይወትና የእነ ቅዱስ ያሬድን ሰውነት በልብህ ተመልከታት፤ትውልድ በልቶ የማይጨርሰው የዘለዓለም ስንቅ ተገኝቶባታልና፡፡