የአባ ሙሴ ጸሊም ዕረፍት

አባ ሙሴ ጸሊም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሰኔ ፳፫ ቀን ፳፻፱ .

ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይድረሰውና ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከልዩ ልዩ ዓለማዊ ሥራ ጠርቶ ቃሉን ለመስበክ፣ ስሙን ለመቀደስ እና ክብሩን ለመውረስ ያበቃቸው ቅዱሳን ብዙዎች ናቸው፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን በኃጢአት ሕይወት ከኖሩ በኋላ በንስሓ ተመልሰው ለመንግሥተ ሰማያት ከተጠሩ ጻድቃን መካከል አንዱ የኾኑትን የአባ ሙሴ ጸሊምን የዕረፍት ታሪክ በአጭሩ እንደሚከተለው አዘጋጅተነዋል፤

የአባ ሙሴ ጸሊም (ጥቁሩ ሙሴ) በዓለ ዕረፍት በየዓመቱ ሰኔ ፳፬ ቀን በቤተ ክርስቲያናችን ይከበራል፡፡ አባ ሙሴ ቆዳቸው ጥቁር በመኾኑ ‹ጸሊም› (ጥቁር) በሚል ቅጽል ስም ይጠራሉ፡፡ እኒህ ቅዱስ ለሰማዕትነት ክብር ከመብቃታቸው በፊት በቆዳቸው ብቻ ሳይኾን በግብራቸውም የጠቆሩ ማለትም ኀጢአትን የሚሠሩ ነበሩ፡፡ ያለ መጠን ይበሉ፣ ይጠጡ፣ ይቀሙ፣ ያመነዝሩ እንደዚሁም ሰው ይገድሉ ነበር፡፡ በሥጋቸው ጠንካራ፣ በጕልበታቸውም ኃይለኛ ከመኾናቸው የተነሣም ሊቋቋማቸው የሚችል ማንም እንዳልነበረ መጽሐፈ ስንክሳር ይናገራል፡፡ እግዚአብሔርን ካለማወቃቸው የተነሣ በባዕድ አምልኮ ተይዘው የኖሩት አባ ሙሴ ጸሊም ፀሐይን ለሚያመልኩ ሰዎች አገልጋይም ነበሩ፡፡

በዚህ ዓይነት ሰይጣናዊ ሥራ ከኖሩ ከዓመታት በኋላ የሰውን ልጅ ጠፍቶ መቅረት የማይወደው አምላከ ቅዱሳን እግዚአብሔር ወደ ቤቱ መልሶ አምላክነቱን ለመመስከር፣ ስሙን ለመቀደስ፣ መንግሥቱንም ለመውረስ መርጧቸዋልና የፀሐይን ፍጡርነት፣ ግዑዝነት ገለጸላቸው፡፡ ስለዚህም ብዙ ጊዜ ወደ ፀሐይ በማንጋጠጥ ‹‹ፀሐይ ሆይ አንተ አምላክ ከሆንኽ አነጋግረኝ … የማላውቅህ ሆይ ራስህን አሳውቀኝ›› እያሉ ይመራመሩ ጀመር፡፡ አባ ሙሴ ጸሊም፣ የገዳመ አስቄጥስ መነኮሳት እግዚአብሔርን ያውቁታል፤ ያዩታል፤ እንደዚሁም ያነጋግሩታል እየተባለ ሲነገር ይሰሙ ነበር፡፡ እግዚአብሔርም ወደ ገዳሙ ይሔዱ ዘንድ አነሣሣቸው፡፡ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደዉም ከካህናቱ አንዱ የኾኑትን አባ ኤስድሮስን ‹‹እውነተኛውን አምላክ ታሳውቁኝና ታስረዱኝ ዘንድ ወደ እናንተ መጥቻለሁ›› አሏቸው፡፡ እርሳቸውም እግዚአብሔርን ፍለጋ ወደ ገዳሙ መምጣታቸውን አድንቀው ከአባ መቃርስ ጋር አገናኟቸው፡፡ አባ መቃርስም የክርስትና ሃይማኖትን አስተምረው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቀው ‹‹ታግሠህ የማስተምርህን ትምህርተ ወንጌል ከጠበክ እግዚአብሔርን ታየዋለህ›› እያሉ በተስፋ ቃል እያጽናኗቸው ቆዩ፡፡ ከዓመታት በኋላም በልዩ ልዩ ዓይነት ፈተና ፈትነው አመነኮሷቸው፡፡

አባ ሙሴ ጸሊም ብዙ ገድልን ከሚጋደሉ ቅዱሳን አብልጠው መጋደል በጀመሩ ጊዜም ሰይጣን ለማሰናከልና ከገዳሙ ለማስወጣት በማሰብ ቀድሞ ያሠራቸው በነበረው ግብረ ኃጢአት ሊዋጋቸው ጀመረ፡፡ አባ ኤስድሮስም እያጽናኑ፣ እየመከሩ በተጋድሏቸው ይበልጥ እንዲጸኑ ያተጓቸው ነበር፡፡ የመነኮሳቱ የውኃ መቅጃ ሥፍራ ሩቅ ነበርና አረጋውያን መነኮሳት በመንገድ ብዛት እንዳይደክሙ አባ ሙሴ ዘወትር ውኃ እየቀዱ በየበዓታቸው ደጃፍ ያስቀምጡላቸው ነበር፡፡ እንዲህ እያደረጉ በመጋደልና በማገልገል ላይ ሳሉ ጸላዔ ሠናያት ሰይጣን እግራቸውን በከባድ ደዌ መታቸውና ለብዙ ቀናት የአልጋ ቁራኛ ኾነው ኖሩ፡፡ እርሳቸውም በደዌ የሚፈታተናቸው ጥንተ ጠላት ሰይጣን መኾኑን ተረድተው ሰውነታቸው ደርቆ በእሳት የተቃጠለ እንጨት እስኪመስል ድረስ ተጋድሏቸውን እጅግ አበዙ፡፡ እግዚአብሔርም ትዕግሥታቸውን ዓይቶ ከደዌያቸው ፈወሳቸው፤ የሰይጣንን ውጊያ አርቆ ጸጋውን አሳደረባቸው፡፡

አባ ሙሴ፣ እርሳቸው ወደሚኖሩበት ገዳም የተሰበሰቡ ፭፻ የሚኾኑ ወንድሞች መነኮሳትን በአበ ምኔትነት እያስተዳደሩ ሳሉ ‹‹በመልካም ለሚያገለግሉት ከፍተኛውን ሹመት ይስጧቸው፤ ኢየሱስ ክርስቶስን በማመን ብዙ ባለሟልነት አለና›› (፩ኛጢሞ.፫፥፲፫) በማለት ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረው፣ ከተጋድሏቸውና ከትሕትናቸው አኳያ ማኅበረ መነኮሳቱ ለቅስና መዓርግ መረጧቸው፡፡ ሥርዓተ ክህነት ሊፈጽሙላቸው ወደ ቤተ መቅደስ በአቀረቧቸው ጊዜም ሊቀ ጳጳሳቱ ‹‹ይህን ጠቋራ ለምን አመጣችሁት? ከዚህ አውጡት›› ብለው አረጋውያኑን ተቆጧቸው፡፡ አባ ሙሴ ይህን ቃል ከሊቀ ጳጳሳቱ በሰሙ ጊዜም ‹‹መልክህ የከፋ ጠቋራ ሆይ! መልካም አደረጉብህ›› እያሉ ራሳቸውን በመገሠፅ ከቤተ መቅደስ ወጡ፡፡ ጽናታቸውንና ትዕግሥታቸውን የተመለከቱት ሊቀ ጳጳሳቱም በሌላ ቀን አባ ሙሴን አስጠርተው በአንብሮተ እድ በቅስና መዓርግ ሾሟቸው፡፡ ከዚያም ‹‹ሙሴ ሆይ! እነሆ በውስጥም በውጪም ዅለመናህ ነጭ ኾነ›› ብለው በደስታ ቃል አናገሯቸው፡፡ ሙሴም በተቀበሉት መዓርግ እግዚአብሔርን፣ መነኮሳቱንና ገዳሙን በትጋት ሲያገለግሉ ኖሩ፡፡

እግዚአብሔር በአባ ሙሴ ላይ አድሮ ከአደረጋቸው ተአምራት መካከል ያለ ወቅቱ ዝናብ እንዲዘንብ ማድረጋቸው አንደኛው ነው፤ ከዕለታት አንድ ቀን በበዓታቸው ምንም ውኃ በሌለበት ቀን አረጋውያን በእንግድነት መጡባቸው፡፡ ውኃ የሚቀዳበት ቦታ በጣም ሩቅ ነበርና አባ ሙሴ የሚያደርጉትን አጡ፡፡ እንግዶቹን ወደ በዓታቸው ካስገቡ በኋላም ከመነኮሳቱ ተለይተው ‹‹ውኃ ካልሰጠኸኝ ቅዱሳን አገልጋዮችህን ምን አጠጣቸዋለሁ?›› እያሉ እግዚአብሔርን በጸሎት ይጠይቁት ጀመሩ፡፡ እርሱም በስሙ ለሚታመኑ ድንቅ ሥራውን መግለጥ ልማዱ ነውና ጸሎታቸውን ሰምቶ ዝናብ አዝንቦ የውኃ ጉድጓዶችን ሞላላቸው፡፡ እንግዶቹንም እንደ ሥርዓቱ እግራቸውን አጥበው፣ ምግብና ውኃ ሰጥተው አስተናገዷቸው፡፡ አረጋውያኑ በዝናቡ መጣል እየተገረሙ አባ ሙሴን ‹‹ብዙ ጊዜ ትወጣ፣ ትገባ የነበረው ለምንድን ነው?›› ብለው ጠየቋቸው፡፡ እርሳቸውም ‹‹እግዚአብሔርን ውኃ እንዲሰጠኝ እየተማጸንኹት ነበር፡፡ በቸርነቱም ዝናምን ልኮልን ውኃን አገኘን›› አሏቸው፡፡ በዚህ ጊዜ በቅዱሳኑ ላይ አድሮ ድንቅ ድንቅ ተአምራቱን የሚገልጠውን እግዚአብሔርን አመሰገኑት፤ በአባ ሙሴ ቅድስናም ተደነቁ፡፡

በአንዲት ዕለት አባ ሙሴ ከአረጋውያን ጋር ወደ አባ መቃርስ ገዳም በሔዱ ጊዜ አባ መቃርስ በመንፈስ ቅዱስ ተገልጾላቸው ‹‹ከእናንተ ውስጥ የሰማዕትነት ክብር ያለው አንድ ሰው አያለሁ›› በማለት ለአባ ሙሴ ጸሊም ስለ ተዘገጀው የሰማዕትነት ክብር አስቀድመው ትንቢት ተናገሩ፡፡ አባ ሙሴም ይህን ቃል ሲሰሙ ‹‹አባቴ ሆይ እኔ እኾናለሁ፡፡በሰይፍ የገደለ በሰይፍ ይገደል ዘንድ አለው› የሚል ጽሑፍ አለና›› ብለው መለሱ፡፡ በብሉይ ኪዳን ‹‹በሰይፍ የገደለ በሰይፍ ይሙት፤ ዓይን ያጠፋ ዓይኑ ይጥፋ›› የሚል አንድ ሰው በሠራው ወንጀል መጠን እንዲቀጣ የሚያስገድድ ሕግ ነበር (ዘፀ. ፳፩፥፳፬-፳፭፤ ማቴ. ፭፥፴፰)፡፡ አባ ሙሴ ጸሊም ለገዳማዊ ሕይወት ከመብቃታቸው በፊት ሰዎችን በሰይፍ ሲያጠፉ እንደ ነበሩት ዅሉ እርሳቸውም በሰይፍ ለመሞት መዘጋጀታቸውን ሲገልጹ ‹‹አባቴ ሆይ እኔ እኾናለሁ፡፡በሰይፍ የገደለ በሰይፍ ይገደል ዘንድ አለው› የሚል ጽሑፍ አለና›› ብለዋል፡፡ ይህም በንጹሕ ልቡናቸው ወደ እግዚአብሔር መመለሳቸውን የሚያመለክት ንግግር ነው፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን ያገኙትን ዅሉ በሰይፍ የሚገድሉ የበርበር ሰዎች ወደ በዓታቸው መጡ፡፡ አባ ሙሴም አብረዋቸው የነበሩትን መነኮሳት ‹‹መሸሽ የሚፈልግ ይሽሽ›› አሏቸው፡፡ እነርሱም ‹‹አባታችን አንተስ አትሸሽምን?›› ብለው ጠየቋቸው፡፡ እርሳቸውም እኔ ‹‹‹በሰይፍ የገደለ በሰይፍ ይገደላልስለሚለው የእግዚአብሔር ቃል እነሆ ይቺን ቀን ለብዙ ዘመናት ስጠባበቃት ኖሬአለሁ›› በማለት ለሰማዕትነት መዘጋጀታቸውን ነገሯቸው፡፡ ይህን ቃል እየተነጋገሩ ሳሉም የበርበር ሰዎች ከበዓታቸው ገብተው በሰይፍ ቈርጠው ገደሏቸው፡፡ ከእርሳቸው ጋርም ሰባት መነኮሳት በሰማዕትነት ሞቱ፡፡ አንደኛውም ከምንጣፍ ውስጥ ተሠውረው ከቆዩ በኋላ በእጁ አክሊል የያዘ የእግዚአብሔር መልአክ ቆሞ ሲጠባበቅ በተመለከቱ ጊዜ ከተሠወሩበት በመውጣት የሰማዕትነትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡ በዚህ ጊዜ አባ መቃርስ ‹‹ከእናንተ ውስጥ የሰማዕትነት ክብር ያለው አንድ ሰው አያለሁ›› በማለት የተናገሩት ትንቢት ደረሰ፡፡ ‹‹አስቀድሞም የወሰናቸውን እነዚህን ደግሞ ጠራቸው፤ የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፤ ያጸደቃቸውንም እነዚህን ደግሞ አከበራቸው›› ሲል ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረው ኃይለ ቃልም በአባ ሙሴ ተጋድሎ ተፈጸመ  (ሮሜ. ፰፥፴)፡፡ የአባ ሙሴ ጸሊም ሥጋም በአስቄጥስ ገዳም ደርምስ በተባለ ቦታ እንደሚገኝ፤ ከእርሱም ብዙ ድንቆችና ተአምራት እንደሚታዩ በመጽሐፈ ስንክሳር ተገልጿል፡፡

‹‹እስከ ዛሬ ድረስ መንግሥተ ሰማያት ትገፋለች፤ ግፈኞችም ይናጠቋታል›› ተብሎ እንደ ተጻፈው /ማቴ.፲፩፥፲፪/፣ አባ ሙሴ ጸሊም አስቀድሞ መንግሥተ ሰማያትን ገፍተዋታል፤ ማለትም የእግዚአብሔርን መንግሥት የሚያወርሰውን የጽድቅ ሥራ ትተው ወደ ገሃነም በሚያስጥል ኃጢአት ኖረዋል፡፡ በኋላ ግን እግዚአብሔርን ፈልገው ከማግኘታቸው ባሻገር በመንፈሳዊ ተጋድሎ በመበርታት ለክህነት እና ለቅድስና በቅተው ምድራዊ ሕይወታቸውን በሰማዕትነት አጠናቀዋል፡፡ በክህደት፣ በኑፋቄ እንደዚሁም በኀጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር እቅፍ ርቀን የምንኖር ክርስቲያኖችም ከሃዲ፣ ሰውን ገዳይ፣ ቀማኛ፣ ዘማዊ የነበረውን ሰው ወደ አሚነ እግዚአብሔር እና ወደ ገቢረ ጽድቅ በመለወጥ ደግ አባት፣ መምህር፣ የሚያጽና እና ሥርዓትን የሚሠራ ካህን፣ እንደዚሁም ሰማዕት ለመኾን ያበቃችውን፤ በተጨማሪም በዅሉም አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ስሙ ለዘለዓለሙ እንዲጠራ ያደረገችውን የንስሓን ኃይል በማስተዋል ዛሬዉኑ ወደ እግዚአብሔር እንመለስ፡፡ ኀጢአታችንን ይቅር ይለን ዘንድም ዘወትር እንማጸነው፡፡ እግዚአብሔር እስከ ሺሕ ትውልድ ድረስ ቸርነትን የሚጠብቅ፣ አበሳንና መተላለፍን፣ ኀጢአትንም ይቅር የሚል አምላክ ነውና (ዘፀ. ፴፬፥፯፤ ማቴ. ፮፥፲፪)፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን! እኛንም በአባ ሙሴ ጸሊምና በሰማዕታት ዅሉ ጸሎት ይማረን፡፡ በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፳፬ ቀን፡፡

የንጉሥ ሰሎሞን ዕረፍት

በዝግጅት ክፍሉ

ሰኔ ፳፫ ቀን ፳፻፱ .

በየዓመቱ ሰኔ ፳፫ ቀን ንጉሥ ሰሎሞን፣ አባ ኖብ፣ ቅዱስ መርቆሬዎስ፣ ቅዱስ ቶማስ፣ ቅዱስ ፊልጶስና ሌሎችም ቅዱሳን ይታወሳሉ፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን በመጽሐፈ ስንክሳር የተመዘገበዉን የንጉሥ ሰሎሞንን የዕረፍት ታሪክ በአጭሩ ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

ንጉሥ ዳዊት ሕግ ተላልፎ ከኦርዮ ሚስት ከቤርሳቤህ ጋር በዝሙት በመውደቅ እና ባሏን በማስገደል ኀጢአት በመፈጸሙ እግዚአብሔር አምላክ ነቢዩ ናታንን ልኮ ስለ በደሉ ገሠፀው፡፡ በዚህ ጊዜ ንስሐ ገብቶ መሪር ልቅሶን አለቀሰ፡፡ እግዚአብሔርም ንስሐዉን ተቀብሎ ኀጢአቱን ይቅር አለው፡፡ በኋላም በእግዚአብሔር ፈቃድ ቤርሳቤህን ሚስቱ አደረጋትና ሰሎሞንን ወለዱ፡፡ ሰሎሞን ሲያድግም በዙፋኑ እንደሚተካው ንጉሥ ዳዊት ለቤርሳቤህ ቃል ገባላት፡፡ ብላቴናው ሰሎሞን ፲፪ ዓመት በሞላው ጊዜም አዶንያስ በዳዊት ምትክ ለመንገሥ ዐስቦ በሮጌል ምድር ምንጭ አጠገብ ኤልቲ ዘዘኤልቲ በሚባል ቦታ ላሞችን፣ በጎችንና ፍየሎችን አርዶ የሠራዊት አለቆችን፤ የንጉሥ አሽከሮችንና ካህኑ አብያታርንም ጠርቶ ግብዣ አደረገ፡፡ እነርሱም ‹‹አዶንያስ ሺሕ ዓመት ያንግሥህ!›› እያሉ አወደሱት፡፡

ዳዊትም የአዶንያስን ሥራ ከቤርሳቤህና ከነቢዩ ከናታን በሰማ ጊዜ የዮዳሄን ልጅ ብንያስንና ካህኑ ሳዶቅን፣ ነቢዩ ናታንንም፣ ግራዝማችና ቀኛዝማቹን ዅሉ አስጠርቶ ሰሎሞንን በራሱ በቅሎ ላይ አስቀምጠው፡፡ ሠራዊቱም ወደ ግዮን እንዲያወርዱትና በዚያም ነቢዩ ናታንና ካህኑ ሳዶቅ ቀብተው እንዲያነግሡት፤ ሰሎሞንም በአባቱ ፈንታ በእስራኤል ላይ እንዲነግሥ ንጉሥ ዳዊት አዘዘ፡፡ ካህኑ ሳዶቅም እንደታዘዘው ሰሎሞንን የንግሥና ቅባትን ቀባው፡፡ ቀርነ መለከቱንም ነፉ፤ ሕዝቡም ዅሉ ሰሎሞንን ‹‹ሺሕ ዓመት ያንግሥህ!›› እያሉ ተከትለዉት ወጡ፡፡ ከበሮም መቱ፤ ታላቅ ደስታም አደረጉ፡፡ ከድምፃቸው ኃይል የተነሣ ምድሪቱ ተናወጠች፡፡ ሰሎሞንም በመንግሥት ዙፋን ተቀመጠ፡፡ የንጉሡ አሽከሮችም ‹‹እግዚአብሔር የሰሎሞንን ስም ከስምህ ይልቅ መልካም ያድርገው፤ ዙፋኑንም ከዙፋንህ ይልቅ ከፍ ከፍ ያድርገው›› እያሉ ዳዊትን አመሰገኑት፡፡ ዳዊትም ‹‹ዐይኖቼ እያዩ በዙፋኔ ላይ የሚቀመጥ ልጅ ለእኔ ለባሪያው ዛሬ የሰጠ የእስራኤል ፈጣሪ እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን›› አለ፡፡

ንጉስ ዳዊት የሚሞትበት ጊዜ በደረሰ ጊዜም ‹‹እኔ ሰው በሚሔድበት በሞት ጐዳና እሔዳለሁ፡፡ አንተ ግን ጽና፤ ብልህ ሰውም ኹን፡፡ በሕጉ ጸንተህ ትኖር ዘንድ በሙሴ ሕግ የተጻፈዉን የፈጣሪህ የእግዚአብሔርን ሕግና ትእዛዝ ጠብቅ›› ብሎ ልጁ ሰሎሞንን አዘዘው፡፡ ከዳዊት ዕረፍትም በኋላ ንጉሥ ሰሎሞን በገባዖን ምድር መሥዋዕትን በሠዋ ጊዜ እግዚአብሔር በሕልም ተገልጾ ‹‹እሰጥህ ዘንድ ልብህ ያሰበዉን ለምነኝ›› አለው፡፡ ሰሎሞንም ‹‹እኔ ባሪያህ መግቢያዬንና መውጫዬን የማላውቅ ታናሽ ብላቴና ነኝና ለዚህ ለብዙ ወገንህ በእውነት እፈርድ፤ ክፉዉን ከበጎው ለይቼ ዐውቅ ዘንድ ዕውቀትን ስጠኝ?›› ብሎ ለመነው፡፡ እግዚአብሔርም ‹‹ብዙ ዘመንንና ባለጠግነትን፤ የጠላቶችህንም ጥፋት አለመንኸኝምና፡፡ ነገር ግን ፍርድ መስማትን ታውቅ ዘንድ ለምነሃልና እነሆ እንዳልህ አደረግሁልህ፡፡ እነሆ ከአንተ አስቀድሞ እንዳልነበረ፤ ከአንተም በኋላ እንደ አንተ ያለ እንዳይነሣ አድርጌ ብልህና አስተዋይ ልቡናን፤ ያለመንኸኝን ባለጠግነትንና ክብርንም በዘመንህ ዅሉ ሰጠሁህ›› አለው፡፡

ሰሎሞንም ከእንቅልፉ በነቃ ጊዜ እውነተኛ ሕልም እንዳለመ ዐወቀ፡፡ ወደ ኢየሩሳሌም ሔዶም በጽዮን በእግዚአብሔር ታቦተ ሕግ አንጻር ባለው መሠዊያ ፊት ቆሞ የሰላም መሥዋዕትን አቀረበ፡፡ ለሰዎቹና ለእሱም ታላቅ ግብዣ አደረገ፡፡ በዚያን ጊዜም ሁለት አመንዝራ ሴቶች ወደ እርሱ መጥተው በአንድ ቤት እንደሚኖሩና በሦስት ቀን ልዩነት ልጆችን እንደ ወለዱ፤ አንደኛዋ ሴትም ልጇን በሌሊት ተጭናው በሞተባት ጊዜ ያልመተዉን የሌላኛዋን ልጅ ወስዳ የሞተዉን ልጅ እንዳስታቀፈቻት በማብራራት ‹‹የሞተው ልጅ ያንቺ ነው፤ ደኅናው ልጅ የኔ ነው›› የሚል አቤቱታ ለንጉሥ ሰሎሞን አቀረቡ፡፡ ንጉሡም የሁለቱንም ንግግር ካደመጠ በኋላ ‹‹ደኅነኛዉን ልጅ በሰይፍ ቈርጣችሁ እኩል አካፍሏቸው›› ብሎ ትእዛዝ ሰጠ፡፡ በዚህ ጊዜ ያልሞተው ልጅ እናት ‹‹ልጁን አትግደሉት፡፡ ደኅናዉን ለእርሷ ስጧት›› ስትል፤ ሁለተኛዋ ሴት ግን ‹‹ቈርጣችሁ አካፍሉን እንጂ ለእኔም ለእርሷም አይኹን›› አለች፡፡ ንጉሡም እውነቱን ከሴቶቹ አኳኋን ተረድቶ ‹‹‹ልጁን አትግደሉት› ላለችው ሴት ደኅነኛዉን ሕፃን ስጧት፤ እርሷ እናቱ ናትና›› ብሎ ፈረደ፡፡ በዚህ ፍርዱ ምክንያትም እስራኤል ዅሉ ቅን ፍርድ ይፈርድ ዘንድ የእግዚአብሔር ጥበቡ በእርሱ ላይ እንዳለ አይተዋልና ንጉሡን ፈሩት፡፡

ከዚህ በኋላ ንጉሥ ሰሎሞን የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ማነጽ ጀመረ፡፡ ቤተ መቅደሱንም እስራኤል ከግብጽ ከወጡ በ፬፻፹ኛው፤ ሰሎሞን በነገሠ በ፬ኛው ዓመት፣ በ፪ኛው ወር ጀምሮ በ፲፩ኛው ዘመነ መንግሥቱ፣ በ፰ኛው ወር ሠርቶ በ፯ ዓመታት ውስጥ ፈጸመው፡፡ የራሱን ቤትም በ፲፫ ዓመት ሠርቶ ጨረሰ፡፡ ሰሎሞን ቤተ መቅደሱንና የራሱን ቤት ከፈጸመ በኋላ የእግዚአብሔርን ታቦት ያመጣ ዘንድ የእስራኤልን ሽማግሎች፣ የነገድና የአባቶቻቸዉን ቤት አለቆች ዅሉ በ፯ኛው ወር (በጥቅምት) በኢየሩሳሌም ሰበሰባቸው፡፡ ካህናቱም ታቦቷን፣ የምስክሩን ድንኳንና ንዋያተ ቅድሳቱን ዅሉ ተሸክመው ንጉሡና ሕዝቡም በታቦቷ ፊት ሥፍር ቍጥር የሌላቸዉን በጎችንና ላሞችን እየሠዉ ታቦቷን ከኪሩቤል ክንፎች በታች በቤቱ ውስጥ ወዳለው ወደ ቅድስተ ቅዱሳን አገቧት፡፡

ካህናቱ ከቤተ መቅደስ በወጡ ጊዜ የእግዚአብሔር ብርሃን ቤተ መቅደሱን ሞላው፡፡ ካህናቱም ሥራቸዉን መሥራትና ከብርሃኑ ፊቱ መቆም ተሳናቸው፡፡ ያንጊዜም ሰሎሞን ‹‹‹እግዚአብሔር በደመና ውስጥ እኖራለሁብሏል፤ እኔም ለዘለዓለም የምትኖርበት ማደሪያህ ቤተ መቅደሱን በእውነት ሠራሁልህ›› አለ፡፡ ከዚያም ፊቱን ወደ መሠዊያው መልሶ፣ እጆቹን ዘርግቶ፣ በጕልበቱ ተንበርክኮ ሰገደና ወደ እግዚአብሔር ጸሎት አደረሰ፤ ሕዝቡንም ዅሉ መረቃቸው፡፡ ጸሎቱን ከፈጸመ በኋላም ከመሠዊያው ፊት ተነሥቶ ቆመና ‹‹ለወገኖቹ ለእስራኤል ዕረፍትን የሰጠ እግዚአብሔር ይመስገን›› እያለ በታላቅ ቃል የእስራኤልን ማኅበር መረቃቸው፡፡ ከዚያም ንጉሡና ሕዝቡ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አቅርበው ቅዳሴ ቤቱን አከበሩ፡፡ ሰሎሞን ስለ ሰላም ለእግዚአብሔር የሠዋቸው በጎች በቍጥር ፳፪ ሺሕ ነበሩ፡፡

ዳግመኛም እግዚአብሔር ለሰሎሞን ተገልጾ ‹‹የለመንኸኝን ልመናህንና ጸሎትህን ሰማሁ፤ እንደ ልመናህም ዅሉ አደረግሁልህ፡፡ ስሜ በዚያ ለዘለዓለም ጸንቶ ይኖር ዘንድ የሠራኸዉን ቤተ መቅደስ አከበርሁት፡፡ ልቡናዬም፣ ዐይኖቼም በዘመኑ በዚያ ጸንተው ይኖራሉ›› ብሎ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡ እግዚአብሔር ብዙ ጥበብና ጸጋን የሰጠው ይህ ታላቅ ንጉሥ ለዐርባ ዓመት እስራኤልን በቅንነት አስተዳድሯል፡፡ ከንግሥናው በተጨማሪም ለነፍስም ለሥጋም የሚጠቅሙ፣ ትንቢትንና ትምህርትን የያዙ የጥበብና የመዝሙር መጻሕፍትንም ጽፏል፤ እነዚህም፡- መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን፣ መጽሐፈ መክብብ፣ መጽሐፈ ምሳሌ፣ መጽሐፈ ተግሣፅና መጽሐፈ ጥበብ ናቸው፡፡ ንጉሥ ሰሎሞን ከመንገሡ በፊት ፲፪፤ ከንግሥናው በኋላ ፵፤ በድምሩ ፶፪ ዓመታት በሕይወተ ሥጋ ከኖረ በኋላ በዛሬው ዕለት ሰኔ ፳፫ ቀን ከዚህ ዓለም ድካም ዐርፏል፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን፡፡ እኛንም በቅዱሳን ጸሎት ይማረን፡፡ የአባቶቻችን በረከት ይደርብን፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፳፫ ቀን፡፡

ሕንጸተ ቤተ ክርስቲያን

በዝግጅት ክፍሉ

ሰኔ ቀን ፳፻፱ .

በመጽሐፈ ስንክሳር እንደ ተመዘገበልን ሰኔ ፳ ቀን በኬልቄዶን አውራጃ በቂሣርያ አገር የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ያለ እንጨት፣ ያለ ጭቃና ያለ ውኀ በሦስት ድንጋዮች በተወደደ ልጇ በጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የታነጸበት ዕለት ነው፡፡ ይህ ዕለት በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ ከሚከብሩ ከእመቤታችን በዓላት አንደኛው ሲኾን ታሪኩንም በአጭሩ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

ጌታችን በዐረገ በስምንተኛው ዓመት ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ በርናባስ ወደ ፊልጵስዩስ ገብተው በክርስቶስ ስም አሳምነው ብዙ አሕዛብን ካጠመቁ በኋላ ቤተ ክርስቲያን ሊሠሩላቸው ወደዱ፡፡ በዚህ ጊዜ ርእሰ ሐዋርያት እያለ እኛ መሥራት አይገባንም ብለው በሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ መልእክት ላኩበት፡፡ እርሱም ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር መጥቶ ከቅዱስ ጳውሎስ እና ቅዱስ በርናባስ ጋር በኢየሩሳሌም ተገናኙ፡፡

በዚያም በአንድነት ሱባዔ ይዘው ከቆዩ በኋላ ጌታችን የሞቱትን አስነሥቶ፣ ያሉትንም ጠርቶ ቅዱሳን ሐዋርያትን በፊልጵስዩስ አገር ሰብስቦ ‹‹በእናቴ በድንግል ማርያም ስም ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የሚሠራዉን የአብያተ ክርስቲያናት ሥራ ላሳያችሁ፤ ሥርዓቱንም ላስተምራችሁ ሰብስቤአችኋለሁ›› ብሎ ወደ ምሥራቅ ይዟቸው ወጣ፡፡ በዚያ ሥፍራ የነበሩትን ሦስት ድንጋዮችንም የተራራቁትን አቀራርቦ፣ ጥቃቅኑን ታላላቅ አድርጎ ቁመቱን በ፳፬፤ ወርዱን በ፲፪ ክንድ ለክቶ ለቅዱሳን ሐዋርያት ሰጣቸው፡፡

ከዚህ በኋላ ቅዱሳን ሐዋርያት ሰም እሳት ሲያገኘው እንዲለመልም፣ ድንጋዩ በእጃቸው ላይ እየተሳበላቸው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን ሠርተው ፈጽመዉታል፡፡ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ የተሠራዉም ጌታችን በዐረገ በ፲፱ኛው፤ እመቤታችን በዐረገች በ፬ኛው ዓመት ሰኔ ፳ ቀን ሲኾን፣ በ፳፩ኛው ቀን (በማግሥቱ) ኅብስት ሰማያዊ፣ ጽዋዕ ሰማያዊ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወረደ፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችን ጋር ከሰማየ ሰማያት መጥቶ እመቤታችንን ታቦት፤ ሐዋርያትን ልዑካን አድርጎ፣ እርሱ ሠራዒ ካህን ኾኖ ቀድሶ ካቈረባቸው በኋላ ‹‹እምይእዜሰ አንትሙኒ ከመዝ ግበሩ፤ ከዛሬ ጀምሮ እናንተም እንደዚህ አድርጉ›› ብሎ አዝዟቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡

ይህ ታሪክ ብዙ ምሳሌዎች አሉት፡፡ ይኸውም፡- የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ቁመት በነገሥታት ዘመን የነበሩ የ፳፬ቱ ነቢያት፤ አንድም የ፳፬ቱ ካህናተ ሰማይ አምሳል ሲኾን፣ ወርዱ ደግሞ የ፲፪ቱ ሐዋርያት ምሳሌ ነው፡፡ ሦስቱ ድንጋዮች የሥላሴ አምሳል ሲኾኑ፣ ከታች አቀማመጣቸው ሦስት፤ ከላይ ሕንጻቸው አንድ መኾኑ የሥላሴን ሦስትነትና አንድነት ያመለክታል፡፡ የሠሩትም ሦስት ክፍል አድርገው ሲኾን፣ ይህም የመጀመሪያው የታቦተ አዳም፤ ሁለተኛው የታቦተ ሙሴ፤ ሦስተኛው የታቦተ ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ዳግመኛም የሦስቱ ዓለማት ማለትም የመጀመሪያው የጽርሐ አርያም፣ ሁለተኛው የኢዮር፣ ሦስተኛው የጠፈር ምሳሌ ነው፡፡

አንድም መጀመሪያው የኤረር፣ ሁለተኛው የራማ፣ ሦስተኛው የኢዮር አምሳል ነው፡፡ በኤረር፡- መላእክት፣ መኳንንት፣ ሊቃናት፤ በራማ፡- ሥልጣናት፣ መናብርት፣ አርባብ፤ በኢዮር፡- ኃይላት፣ ኪሩቤል፣ ሱራፌል ይኖራሉ፡፡ እነዚህ ዘጠኙ ነገደ መላእክት የዘጠኙ መዓርጋተ ቤተ ክርስቲያን (መዓርጋተ ክህነት) አምሳል ሲኾኑ፣ ይኸውም መላእክት – የመዘምራን፤ መኳንንት – የአናጕንስጢሳውያን፤ ሊቃናት – የንፍቀ ዲያቆናት፤ ሥልጣናት – የዲያቆናት፤ መናብርት – የቀሳውስት፤ አርባብ – የቆሞሳት፤ ኃይላት – የኤጲስ ቆጶሳት፤ ሱራፌል – የጳጳሳት፤ ኪሩቤል – የሊቃነ ጳጳሳት አምሳሎች ናቸው፡፡

ይህም በታች (በምድር) የሚኖሩ ደቂቀ አዳም ከቅዱሳን በቀር ወደ ላይ (ወደ ሰማይ) መውጣት እንደማይቻላቸው፣ ከመዘምራን እስከ ጳጳሳት ድረስ ያሉ ካህናትም ከእነርሱ በላይ ያሉትን መዓርግ መሥራት (መፈጸም) እንደማይቻላቸው ያጠይቃል፡፡ እንደዚሁም በላይ የሚኖሩ መላእክት ወደ ታች መውረድ እንደሚቻላቸው ሊቃነ ጳጳሳትም ከእነርሱ በታች ያሉ ካህናትን ተልእኮ መፈጸም (መሥራት) እንደሚቻላቸው ያስረዳል፡፡

በጽርሐ አርያም መንበረ ብርሃን (የብርሃን መንበር)፤ ታቦተ ብርሃን (የብርሃን ታቦት)፤ መንጦላዕተ ብርሃን (የብርሃን መጋረጃ)፤ እንደዚሁም ፬ ፀወርተ መንበር (መንበሩን የሚሸከሙ)፤ ፳፬ አጠንተ መንበር (መንበሩን የሚያጥኑ) መላእክት አሉ፡፡ ጽርሐ አርያም – የመቅደስ፤ መንበረ ብርሃን – የመንበር፤ መንጦላዕተ ብርሃን – የቤተ መቅደሱ መጋረጃ፤ ፬ቱ ፀወርተ መንበር – የ፬ቱ ሊቃነ ጳጳሳት ወይም የመንበሩ እግሮች፤ ፳፬ቱ አጠንተ መንበር – የጳጳሳት (የኤጲስ ቆጶሳት) አምሳሎች ናቸው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡

  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ቀን፡፡
  • መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መ/ር አፈወርቅ ተክሌ፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻፭ ዓ.ም፤ ገጽ ፫፻፵፱ – ፫፻፶፩፡፡

‹‹ከእናንተ ብዙ ይጠበቃል›› ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሰኔ ፲፱ ቀን ፳፻፱ .

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ የዕለቱን ወንጌል ሲያነቡ (ሉቃ. ፲፥፩-፲፮)

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በልዩ ልዩ ትምህርት ክፍል ያስተማራቸውን ደቀ መዛሙርት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ የኮሌጁ መምህራንና ሠራተኞች በተገኙበት ሰኔ ፲፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ በቅዱስ ፓትርያርኩ ቡራኬ አስመርቋል፡፡ ተመራቂዎቹም የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱን በሚመለከት ያዘጋጁትን የአቋም መግለጫ በተወካያቸው አማካይነት አቅርበዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በሰጡት ቃለ ምዕዳን ‹‹ታሪካዊቷ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከዘመነ ሐዋርያት ጀምሮ ጠብቃ ያቆየችው ትክክለኛ የኾነ አስተምህሮዋ፣ ባህል እና ትውፊቷ ሳይበረዝና ሳይፋለስ ለትውልደ ትውልድ መሸጋገር ይችል ዘንድ ከእናንተ ብዙ ይጠበቃል›› ሲሉ ተመራቂዎቹን አሳስበዋል፡፡

ዕለቱ፣ ተመራቂዎቹ የቤተ ክርስቲያንን አደራ ተቀብለው በየተሠማሩበት የሥራ መስክ ዅሉ እስከ መጨረሻው በታማኝነት ቃል የሚገቡበት ቀን መኾኑን ያስገነዘቡት ቅዱስነታቸው ‹‹የመንግሥተ እግዚአብሔር መልእክተኛ የኾነ ዅሉ መስቀሉን ተሸክሞ ለማገልገል የተመረጠ ስለ ኾነ በሚያጋጥመው የጕዞ ዐቀበት እና ቍልቍለት ሊቸገር አይገባውም፤ በማን እንደ ተመረጠ ያውቃልና ነው›› በማለት ተመራቂዎቹ ብዙ ፈተና እንደሚጠብቃቸው አውቀው ዅሉንም በትዕግሥት በማሸነፍ የሕይወት አክሊል ባለቤቶች ለመኾን ከወዲሁ እንዲዘጋጁ መክረዋል፡፡

ተመራቂዎቹ በሚላኩበት ቦታ ዅሉ ለቤተ ክርስቲያንና ለትውልድ የሚጠቅም አርአያነት ያለው ሥራ ለመሥራት እንዲችሉ ቤተ ክርስቲያን ስለ እነርሱ ዘወትር እንደምትጸልይም ተናግረዋል፡፡ በቃለ ምዕዳናቸው ማጠቃለያም መንፈሳዊ ኮሌጁ በየጊዜው ተተኪ መምህራንን ለማፍራት እያደረገ ያለውን ጥረት አድንቀው ‹‹ዘመኑ የዕውቀት ነውና የመማር ማስተማር ዘዴው ዘመኑን የዋጀ እንዲኾን ከበፊቱ በበለጠ ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ በቤተ ክርስቲያናችን ስም አደራ እንላለን›› በማለት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የከፋ ሸካ ቤንጂ ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ በበኩላቸው ‹‹በቆያችሁበት የትምህርት ዘመን ከመምህሮቻችሁ ያገኛችሁትን መንፈሳዊ ዕውቀት እግዚአብሔር ሒዱ ብሎ ወደሚልካችሁ ዓለም በመሔድ ሕዝባችሁንና ሃይማኖታችሁን ጠብቃችሁ ሳትታክቱ እንድታገለግሉ ስትል ቤተ ክርስቲያን ሰማያዊ መልእክቷን ታስተላልፋለች›› የሚል ቃለ በረከት ለተመራቂዎቹ ሰጥተዋል፡፡

ሊቀ ኅሩያን መሐሪ አስረስ

መምህር ማሞ ከበደ

በኮሌጁ ተምረው የሚመረቁ መምህራን በልዩ ልዩ የዕውቀት ዓይነት የበለጸጉ ሊቃውንት መኾናቸውን በማውሳት ‹‹ከአሁን በኋላ ዝናብ ዘንቦ መሬትን እንደሚያርሰው ዅሉ ከሞላው የዕውቀት ባሕራችሁ እየቀዳችሁ የምእመናንን አእምሮ እንደምታረሰርሱት ትጠበቃላችሁ›› ያሉት ደግሞ የኮሌጁ ዋና ዲን ሊቀ ኅሩያን መሐሪ አስረስ ናቸው፡፡

‹‹በኮሌጃችን ተምረው የሚመረቁ መምህራን የአብነቱን ትምህርት ከዘመናዊው ጋር አጣጥመው በዕውቀት ላይ ዕውቀት ጨምረው የሚወጡ መንፈሳውያን ሐኪሞች ናቸው፡፡ ትምህርታቸውም ደዌ ሥጋን ብቻ ሳይኾን ደዌ ነፍስንም ይፈውሳል›› ያሉት መምህር ማሞ ከበደ የመንፈሳዊ ኮሌጁ አስተዳደር ምክትል ዲን እና የኮሌጁ መምህርም ኮሌጁ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን ጨምሮ በርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያፈራ እንደ ቆየ አሁንም በማፍራት ላይ እንደሚገኝ አስታውሰዋል፡፡

የኮሌጁ ተመራቂዎች በከፊል

በዚህ ዓመትም በብሉይ ኪዳን አንድ፤ በሐዲስ ኪዳን አንድ፤ በቀን አዳሪ ሲሚናር ዐሥራ አንድ፤ በቀን ተመላላሽ ሃያ ሦስት፤ በማታው መርሐ ግብር ሁለት መቶ ዐርባ አምስት በድምሩ ሁለት መቶ ሰማንያ አንድ ደቀ መዛሙርትን ማስመረቁን፤ ከተመራቂዎች መካከልም አካል ጉዳተኞች እና ሴቶች እንደሚገኙ መምህር ማሞ ከበደ አስታውቀዋል፡፡ አራቱን ጉባኤያት ማስተማር፤ በዲግሪ መርሐ ግብር ማስመረቅ እና የርቀት ትምህርት መጀመር ከኮሌጁ የወደፊት ዕቅዶች መካከል የሚጠቀሱ ተግባራት መኾናቸውንም አስረድተዋል፡፡

የኮሌጁ ተመራቂዎች በከፊል

አጠቃላይ የኮሌጁን የማስተማር ተልእኮ በሚመለከት ከዝግጅት ክፍላችን ጋር ባደረጉት ቆይታ ምክትል ዲኑ እንዳብራሩት ኮሌጁ ከኅዳር ወር ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ ሰርጎ ገብ መናፍቃንን የሚከታተል ኰሚቴ አቋቁሞ ከኦርቶዶክሳዊው የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ያፈነገጠ ባዕድ ትምህርት የሚያስተምሩ ደቀ መዛሙርትን በማጣራት በየጊዜው እንዲወገዙና ከትምህርት እንዲታገዱ ሲያደርግ የቆየ ሲኾን፣ በዘንድሮው ዓመትም እምነቱ ተጣርቶ ውሳኔ እስኪያገኝ ድረስ የሃይማኖት ሕጸጽ የተገኘበት አንድ ደቀ መዝሙር እንዳይመረቅ እገዳ ተጥሎበታል፡፡

ከግራ ወደ ቀኝ፡- ዲያቆን ዳንኤል ታደሰ እና ቀሲስ አድማሱ ሰንበታ

ከዚሁ ዅሉ ጋርም የካህናትና ሰባክያነ ወንጌል እጥረት ካሉባቸው አህጉረ ስብከት መሥፈርቱን የሚያሟሉ ሰባት ደቀ መዛሙርትን በመምረጥ ማኅበረ ቅዱሳን ሙሉ ወጫቸውን ሸፍኖ በመንፈሳዊ ኮሌጁ እያስተማረ መኾኑን፤ ከእነዚህ መካከልም ከምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት የመጡት ሁለቱ ሰባክያነ ወንጌል ቀሲስ አድማሱ ሰንበታ እና ዲያቆን ዳንኤል ታደሰ ለሦስት ዓመታት ተምረው በዘንድሮው ዓመት መመረቃቸውን ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የደረሰን መረጃ ያመላክታል፡፡

ዝግጅት ክፍላችን ያነጋገራቸው ሁለቱ ተመራቂዎችም ማኅበሩ ላደረገላቸው ድጋፍ ምስጋናቸውን በእግዚአብሔር ስም አቅርበዋል፡፡ ለወደፊቱም በየቦታው እየተዘዋወሩ ልዩ ልዩ ፈተናዎችን ተቋቁመው በክህነት እና በስብከተ ወንጌል ሰፊ አገልግሎት በመስጠት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሰጣቻቸውን መንፈሳዊ ሓላፊነት ለመወጣት ዝግጁ መኾናቸውን ገልጸዋል፡፡

ዐውደ ርእዩ በአሜሪካ ቀረበ

በዝግጅት ክፍሉ

ሰኔ ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ›› በሚል ርእስ የተዘጋጀው ፭ኛው ዙር የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ ከሰኔ ፲ – ፲፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በአሜሪካ አገር መቅረቡን የአሜሪካ ማእከል አስታወቀ፡፡

ዐውደ ርእዩ በጸሎተ ወንጌል ሲከፈት

በአትላንታ ንዑስ ማእከል አዘጋጅነት በአትላንታ ከተማ በደብል ትሪ ሆቴል በቀረበው በዚህ ልዩ ዐውደ ርእይ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ የየአጥቢያ ሰንበት ት/ቤቶች እና የመንፈሳውያን ማኅበራት አባላት፣ ታዳጊ ሕፃናትን ጨምሮ በርካታ የአሜሪካ ምእመናን መታደማቸውን የንዑስ ማእከሉንና የዝግጅት ኰሚቴውን ሪፖርት ጠቅሶ ማእከሉ ዘግቧል፡፡

ዐውደ ርእዩ በአባቶች ቡራኬ ሲጀመር

በመኪና ከአራት እስከ ዐሥር ሰዓታት ከሚወስዱ ክፍለ ግዛቶች (ስቴቶች) ጭምር ዐውደ ርእዩን ለመመልከት በአትላንታ ከተማ የተገኙ ምእመናን እንደ ነበሩም ከዝግጅት ኰሚቴው ሪፖርት ለመረዳት ተችሏል፡፡ የተመልካቾች ቍጥር ከመብዛቱ የተነሣ ዐውደ ርእዩ በሁለት ክፍሎች የቀረበ ሲኾን፣ ትዕይንቶቹም በእንግሊዝኛ ቋንቋ እየተተረጐሙ ተመልካቾች በሚረዱት መልኩ ተብራርተዋል፡፡

የብፁዕ አቡነ ፋኑኤል መልእክትና ቃለ ምዕዳን በመጋቤ ሐዲስ ይልማ ቸርነት ሲቀርብ

ዐውደ ርእዩ በጸሎተ ወንጌል በተከፈተበት ዕለት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል መልእክትና ቃለ ምዕዳን በመጋቤ ሐዲስ ይልማ ቸርነት የአትላንታ ዳግማዊ ቁልቢ ደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ወአቡነ ተክለ ሃይማኖት አብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪ ቀርቧል፡፡

በመልእክታቸው እንደ ተጠቀሰው የዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች በእንግሊዝኛ ቋንቋ ተተርጕመው እንዲቀርቡ መደረጋቸው ይበል የሚያሰኝ ተግባር መኾኑን ብፁዕነታቸው አድንቀዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለሕዝበ ክርስቲያኑ በስፋት ለማዳረስ ይቻል ዘንድ ይህ መንፈሳዊ አገልግሎት ተጠናክሮ እንዲቀጥልና በሌሎች ከተሞችም እንዲከናወን ያሳሰቡት ብፁዕነታቸው አገልግሎቱን ሀገረ ስብከታቸው እንደሚደግፍም ቃል ገብተዋል፡፡

የዐውደ ርእዩ ታዳሚ አባቶች እና ምእመናን በከፊል

በዐውደ ርእዩ ከተሰሙ መልካም ዜናዎች አንዱ አንድ መቶ ሦስት የአብነት ተማሪዎችን በአንድ ለአንድ የድጋፍ ዘዴ ለመርዳትና ለማስተማር የሚያስችል ቃል መገባቱ ሲኾን፣ በቍጥር ከአራት እስከ ዐሥር የሚደርሱ የአብነት ተማሪዎችን በግል ወጫቸው ለማስተማር አንዳንድ ምእመናን ቃል ገብተዋል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ለጎንደር በአታ የቅኔ ጉባኤ ቤት ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የሚውል $2,628 (ሁለት ሺሕ ስድስት መቶ ሃያ ስምንት ዶላር) ምእመናን ለግሰዋል፡፡

የዐውደ ርእዩ ተሳታፊ ምእመናን በከፊል

በመርሐ ግብሩ ማጠቃለያ ዕለት መልእክት ያስተላለፉ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ዐውደ ርእዩ አስተማሪ እንደ ነበር አስታውሰው በዚህም ይህን ሠራን ብሎ መታበይ እንደማያስፈልግ እና ስለ ሥራው ዅሉ እግዚአብሔርን ማመስገን ተገቢ እንደ ኾነ አስተምረዋል፡፡

የአትላንታ መካነ ሕይወት አቡነ ገብረ ማንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ሕይወት ቀሲስ ዕርገተ ቃል ‹‹አሁን ታሪክ ተቀይሯል፡፡ የአገልግሎቱ በር ተከፍቷል፡፡ ስለኾነም ማኅበሩ በአትላንታ ሰፋፊ ራዎችን መሥራት ይጠበቅበታል፡፡ ከሕዝቡ ጥያቄና አስተያየት የተረዳነውም ይህንኑ ነው፡፡ ስለዚህ በርቱ›› በማለት አባታዊ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡

‹‹ለዚህ ዅሉ ሥራ መሳካት ምክንያቱ እግዚአብሔር ከኛ ጋር ስለ ኾነ ነው›› ያሉት የአትላንታ መካነ ሕይወት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ቀሲስ ያዕቆብ በበኩላቸው፣ ንዑስ ማእከሉ በዚህ ሥራ ብቻ ሳይወሰን ሌሎች መንፈሳውያን ተግባራትንም አጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል፡፡

ምእመናን የዐውደ ርእዩን ትዕይንቶች ሲከታተሉ (በከፊል)

በዝግጅቱ የቤተ ክርስቲያንን አስተዋጽዖ፣ ፈተናዎችንና የምእመናንን ድርሻ በስፋት እንደ ተረዱበት እና የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ የዅሉም ምእመናን ጉዳይ መኾኑን እንደ ተገነዘቡበት የዐውደ ርእዩ ጐብኝዎች በሰጡት አስተያየት ተናግረዋል፡፡

ምእመናን የዐውደ ርእዩን ትዕይንቶች ሲከታተሉ (በከፊል)

በመጨረሻም ለዚህ መርሐ ግብር መሳካት ትብብርና እገዛ ላደረጉ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎች፣ ለሰበካ ጉባኤ አባላትና ማኅበረ ካህናት፤ ለየሰንበት ት/ቤቶች አባላት፤ ድጋፍ በመስጠት (ስፖንሰር በማድረግ) ለተባበሩ የግል ድርጅቶች እና ለልዩ ልዩ መገናኛ ብዙኃን (ሚዲያ) አካላት የዐውደ ርእዩ አዘጋጅ ኰሚቴ ላቅ ያለ ምስጋናውን በማኅበረ ቅዱሳን ስም አቅርቧል፡፡

ከዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ከፊሉ

ዐውደ ርእዩ በሚቀጥለው ቅዳሜና እሑድ (ሰኔ ፲፯ እና ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም) በዋሽንግተን ስቴት ሲያትል ከተማ እንደሚቀርብ የአሜሪካ ማእከል አስታውቋል፡፡

ከዐውደ ርእዩ ክውን ትዕይንቶች አንዱ (የአብነት ተማሪዎች በትምህርት ላይ)

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ‹‹የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ›› በሚል ርእስ ያዘጋጀው ፭ኛ ዙር ዐውደ ርእይ ከግንቦት ፲፯ – ፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በአዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማእከል ቀርቦ በብዙ ሺሕ ሕዝብ እንደ ተጐበኘ የሚታወስ ነው፡፡

ይህን ዐውደ ርእይ በርካታ የአገር ውስጥ እና የውጭ አገር ማእከላት በየጊዜው እያዘጋጁ ትምህርቱ ለምእመናን እንዲዳረስ በማድረግ ላይ ናቸው፡፡

በቅርቡም ከአገር ውስጥ ማእከላት መካከል ባሕር ዳር ማእከል ከግንቦት ፬ – ፲፫፤ ፍኖተ ሰላም ማእከል ከሰኔ ፰ – ፲፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በቅደም ተከተል ዐውደ ርእዩን አዘጋጅተው ለብዙ ሺሕ ሕዝብ እንዳስጐበኙ ከማእከላቱ የደረሰን መረጃ ያመላክታል፡፡

አባ ገሪማ ዘመደራ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው 

ሰኔ ፲፮ ቀን ፳፻፱ .

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደሚነግረን በጉባኤ ኤፌሶን የተወገዘውን፣ በኋላም በጉባኤ ኬልቄዶን ጊዜ በመለካውያን አማካኝነት የመጣውን የሁለት አካል፣ ሁለት ባሕርይ የኑፋቄ እምነት አንቀበልም በማለታቸው በባዛንታይን ነገሥታት ስቃይ የጸናባቸው ተስዓቱ (ዘጠኙ) ቅዱሳን መነኮሳት ከሶርያና ከታናሽ እስያ ተሰደው በአልአሜዳ ዘመነ መንግሥት በ፬፻፹ ዓ.ም ወደ አገራችን ወደ ኢትዮጵያ መጥተዋል፡፡ በዘመኑ የነበረው የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥትም ከአባቶቹ በወረሰው የደግነትና እንግዳ ተቀባይነት ባህሉ በፍቅር ተቀብሏቸዋል፡፡

እነዚህ ዘጠኙ ቅዱሳን በመላው ኢትዮጵያ ተዘዋውረው ወንጌልን ሰብከዋል፤ በወቅቱ ብሔራዊ ቋንቋ የነበረዉን ግእዝን በሚገባ አጥንተው ቅዱሳት መጻሕፍትን ከሱርስትና ከጽርዕ ቋንቋዎች ወደ ግእዝ ተርጕመዋል፡፡ እንደዚሁም ገዳማትንና አብያተ ክርስቲያናት አሳንጸዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችንም ከፈጸሟቸው መንፈሳውያን ተልእኮዎች፣ ካደረጓቸው ተአምራትና መልካም ሥራዎች አኳያ ቅዱሳን በሚል መዓርግ ትጠራቸዋለች፤ በስማቸውም ጽላት ቀርፃ በዓላቸውን ታከብርላቸዋለች፡፡ ዘጠኙ ቅዱሳን የሚባሉት አባቶች፡- አባ አሌፍ፣ አባ አረጋዊ፣ አባ አፍጼ፣ አባ ሊቃኖስ፣ አባ ገሪማ፣ አባ ጉባ፣ አባ ይምአታ፣ አባ ጰንጠሌዎን እና አባ ጽሕማ ናቸው (የኢ.ኦ.ተ.ቤ.ክ.ታ፣ አባ ጎርጎርዮስ ዘሸዋ፣ ፲፱፻፺፩ ዓ.ም፤ ገጽ ፳፫-፳፬)፡፡ በዛሬው ዝግጅታችንም ከዘጠኙ ቅዱሳን አንዱ የኾኑትን የአባ ገሪማን ታሪክ በአጭሩ እናስታውሳችኋለን፤

በሮም አገር መስፍንያኖስ የሚባል ንጉሥ ነበረ፤ ሚስቱም ሰፍንግያ ትባላለች፡፡ መካን ስለነበረች በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በመማጸን ልጅ እንዲሰጣት እግዚአብሔርን ስትለምን ከኖረች በኋላ ወንድ ልጅ ወለደች፤ ስሙንም ይስሐቅ አለችው፡፡ የያን ጊዜው ይስሐቅ የኋላው አባ ገሪማ በመንፈሳዊ ሥርዓት ካደገ በኋላም የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ተምሮ በዲቁና ማገልገል ጀመረ፡፡ ይስሐቅ ወላጅ አባቱ ሲሞትም በአባቱ ዙፋን ተተክቶ ለሰባት ዓመታት ሮምን በንጉሥነት ሲያስተዳድር ከቆየ በኋላ በዋሻ ይኖሩ የነበሩት አባ ጰንጠሌዎን ዘጾማዕት ‹‹ይስሐቅ ሆይ፣ ሙታኖቻቸውን ይቀብሩ ዘንድ ሙታንን ተዋቸውና የማያልፈዉን የክርስቶስን መንግሥት ትሻ ዘንድ ወደ እኔ ና›› ብለው መልእክት ላኩበት፡፡ መልእክቱ እንደ ደረሰውም መንግሥቱን ትቶ በሌሊት ወደ አባ ጰንጠሌዎን ሲሔድ ቅዱስ ገብርኤል ተገልጾ በብርሃናውያን ክንፎቹ ተሸክሞ ዐሥር ወር የሚወስደዉን መንገድ በሦስት ሰዓታት አስጉዞ ከአባ ጰንጠሌዎን በዓት አደረሰው፡፡

አባ ይስሐቅ (አባ ገሪማ) በአባ ጰንጠሌዎን እጅ ከመነኰሱ በኋላ በጾም፣ በጸሎትና በስግደት ተጠምደው ቆዳቸው ከዐፅማቸው እስኪጣበቅ ድረስ ተጋድሎ ሲፈጸሙ ቆዩ፡፡ ከዚያ በኋላ ወደ መደራ ሔደው በእግዚአብሔር ኃይል ድንቆችንና ተአምራትን እየያደረጉ፣ በሽተኞችን እየፈወሱ፣ አጋንንትን እያስወጡ ብዙ ዓመታት ኖሩ፡፡ ካደረጓቸው ተአምራት መካከልም በጠዋት ሥንዴ ዘርተው፣ በሠርክ ሰብስበው መሥዋዕት ካሳረጉ በኋላ በማግሥቱ ከግራር ዛፍ ላይ በሬዎችን አውጥተው ሥንዴዉን አበራይተው ሰባ ሰባት የእንቅብ መሥፈሪያ መሰብሰባቸው አንደኛው ሲኾን፤ በዓለት ላይ የተከሏት ወይን ወዲያው በቅላ፣ አብባ ፍሬ እንድታፈራ ማድረጋቸውና በወይኑም መሥዋዕት ማሳረጋቸው ደግሞ ሌላኛው ተአምር ነው፡፡ አባ ገሪማ መጽሐፍ እየጻፉ ሳሉ ፀሐይ ሊጠልቅ በተቃረበ ጊዜ ጸሎት አድርሰው ጽሕፈታቸዉን እስኪፈጽሙ ድረስ እንደ ኢያሱ ፀሐይን በቦታው እንዲቆም ማድረጋቸውም በመጽሐፈ ስንክሳር ተመዝግቧል፡፡ ከእጃቸው የወደቀው ብርዕ ወዲያው በቅሎ፣ አቈጥቍጦ እንደ አደገ፤ ምራቃቸዉን ትፍ ያሉበት ሥፍራም እስከ ዛሬ ድረስ ሕሙማንን እንደሚፈውስ መጸሐፈ ስንክሳር ይናገራል፡፡

በአንዲት ዕለትም መቅኑናቸውን ተቀብለው ከመነኮሳት ጋር ሲሔዱ መንገድ ላይ ቤተ ክርስቲያን አግኝተው ሲጸልዩ ካህናቱ ቅዳሴ እንዲያሟሉላቸው ጠየቋቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ሌሎቹ ምግብ በልተው ነበርና ‹‹አንችልም›› ሲሉ አባ ይስሐቅ ምግብ አልተመገቡም ነበርና መቅኑናቸዉን አስቀምጠው ቅዳሴውን አሟሉ፡፡ ባልንጀሮቻቸው ግን በልተው የቀደሱ መስሏቸው ወደ አባ ጰንጠሌዎን መጥተው ‹‹ቀሲስ ይስሐቅ ከበላ በኋላ ቀደሰ›› ብለው ከሰሷቸው፡፡ አባ ጰንጠሌዎንም አባ ይስሐቅ ሲመለሱ ‹‹የምጠይቅህ ምሥጢር ስላለኝ ሰዎችን ከአጠገብህ ገለል አድርጋቸው›› ሲሏቸው አባ ይስሐቅም ‹‹ሰዎች ብቻ ሳይኾኑ ዕንጨቶችና ድንጋዮችም ገለል ይበሉ›› ብለው መለሱላቸው፡፡ ወዲያዉኑም ዕንጨቶችና ድንጋዮች አንድ ምዕራፍ ያህል ከቦታቸው ሸሹ፡፡ በዚህ ጊዜ አባ ጰንጠሌዎን ‹‹ ወልድየ ይስሐቅ ገረምከኒ፤ ልጄ ይስሐቅ ሆይ! ገረምኸኝ›› እያሉ አደነቋቸው፡፡ አባ ገሪማን ሳያዉቁ የከሰሷቸው መነኮሳትም ይቅርታ ጠይቀዋቸዋል፡፡ አባ ገሪማ ተብለው መጠራት የጀመሩትም ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡ ይህንን መሠረት በማድረግ ‹‹ገሪማ ገረምከኒ አስኬማከኒ አልባቲ ሙስና፤ አባ ገሪማ አስገረምኸኝ፡፡ ለምንኵስናህም እንከን የለባትም›› በማለት ቅዱስ ያሬድ በመዝሙሩ አመስግኗቸዋል፡፡

ከዚያም በትግራይ ክፍለ ሀገር ልዩ ስሙ መደራ ከሚባል ቦታ ገብተው በዓት ሠርተው ለ፳፫ ዓመታት በትኅርምት ኖረው መልካም ተጋድሏቸውንና የቀና አካሔዳቸዉን በፈጸሙ ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰኔ ፲፯ ቀን ተገልጦ ስማቸውን የሚጠሩትን፣ መታሰቢያቸዉን የሚያደርጉትን፣ ገድላቸዉን የሚጽፉ፣ የሚያነቡና የሚተረጕሙትን፣ ቤተ ክርስቲያን የሚያንጹትንና የሚያገለግሉትን ስማቸውን በሕይወት መጽሐፍ እንደሚጽፍላቸው ቃል ኪዳን ሰጥቷቸዋል፡፡ አባ ገሪማም ይህንን ታላቅ ሀብት የሰጣቸዉን እግዚአብሔርን አመስግነው ከተደሰቱ በኋላ በብርሃን ሠረገላ ተነጥቀው ብሔረ ሕያዋን ገብተዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን በተለይ በገዳማቸው በመደራ አባ ገሪማ የተሠወሩበት ሰኔ ፲፯ ቀን በየዓመቱ በድምቀት ይከበራል፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን፡፡ እኛንም በጻድቁ ጸሎት ይማረን፤ በረከታቸዉም ከእኛ ጋር ትኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡-

  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፲፯ ቀን፡፡
  • መዝገበ ታሪክ ክፍል ፪፣ መ/ር ኅሩይ ኤርምያስ፣ ገጽ ፺፱-፻፡፡

ሰኔ ሚካኤል – ካለፈው የቀጠለ

ከመጽሐፈ ስንክሳር

ሰኔ ፲፪ ቀን ፳፻፱ .

በዚያን ጊዜም የከበረው መልአክ ሚካኤል ያቺን የሞት መልእክት ደመሰሳት፡፡ በእርሷ ፈንታም በንፍሐት ለውጦ እንደህ ብሎ ጻፈ፤ ‹‹ይቺን ደብዳቤ ይዞ ለመጣ ባሕራን ለሚባል ሰው ይቺ ደብዳቤ ደርሳ በምትነበብበት ጊዜ ልጄ ዕገሊትን አጋቡት፡፡ በውስጥና በውጭ ያለ ንብረቴንና ጥሪቴን፣ ወንዶችና ሴቶች ባሮቼን፣ ጠቅላላ ንብረቴንም አውርሼዋለሁና የፈለገውንም ሊያደርግ ሥልጣን ሰጥቼዋለሁና እኔን አትጠብቁኝ፡፡ እኔ ብዙ እዘገያለሁ የኔ ሹም እገሌ ሆይ! በእኔና በአንተ መካከል ይቺ ምልክት እነኋት፡፡›› ከዚህ በኋላ አሽጐ ለባሕራን ሰጠውና ‹‹ወደ ባለ ጠጋው ቤት ሒደህ ይቺን ደብዳቤ ለሹሙ ስጠው፡፡ በጎዳናም እኔ እንደ ተገናኘሁህ አትንገረው፡፡ እንዳይገድልህም ይህን የሞት ደብዳቤ ለውጬልሃለሁ›› አለው፡፡ ባሕራንም ‹‹እሺ ጌታዬ ያዘዝኸኝን ዅሉ አደርጋለሁ›› አለ፡፡

ባሕራንም ወደ ባለ ጠጋው ቤት በደረሰ ጊዜ ያቺን ደብዳቤ ለሹሙ ሰጠው፡፡ በአነበባት ጊዜ በመካከላቸው ያለውን ምልክት አገኘ፡፡ አስተውሎም እርግጠኛ እንደ ኾነ ዐወቀ፡፡ ከዚህም በኋላ ለባሕራን ሠርግ አዘጋጅቶ እንደሚገባ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በተክሊል የባለ ጠጋውን ልጅ አጋቡት፡፡ ዐርባ ቀን ያህልም ደስታና ሐሴት እያደረጉ ኖሩ፡፡ ከዚህ በኋላ ባለ ጠጋው ከሔደበት መመለሻው ጊዜ ኾኖ በደስታ የኾነውን የመሰንቆና የእንዚራ ድምፅ ሰምቶ ‹‹ይህ የምሰማው ምንድነው›› ብሎ ጠየቀ፡፡ እነርሱም ‹‹ስሙ ባሕራን ለተባለ የአንተን ደብዳቤ ላመጣ ጐልማሳ ሰው ልጅህ ዕገሊትን አጋቡት፡፡ እነሆ ለዐርባ ቀናት በሠርግ ላይ ነው፡፡ ገንዘብህንና ጥሪትህን ዅሉ ወንዶችና ሴቶች ባሮችህን አንተ እንዳዘዝኽ ሰጥተውታል›› አሉት፡፡ ይህንም በሰማ ጊዜ ደንግጦ ከፈረሱ ላይ ወደቀ በድንገትም ሞተ፡፡

ባሕራንም በጎ ሥራዎችን የሚሠራ ኾነ፡፡ የተገለጠለትና ከመገደል ያዳነው የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሚካኤል እንደ ኾነ፤ ሊገድለው የሚሻውን የባለ ጠጋውን ጥሪቱን ዅሉ ያወረሰውም እርሱ እንደ ኾነ ተረዳ፡፡ የዚህንም የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ ሚካኤልን መታሰቢያ በየወሩ ያደርግ ጀመረ፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሠራለት፡፡ የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕሉን አሥሎ በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ አደረገው፡፡ ከእርሱም ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፡፡ ባሕራንም ቅስና ተሹሞ እስከ ዕለተ ሞቱ በዚያች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚያገለግል ኾኖ ኖረ፡፡ በዚህ በከበረ የመልአክት አለቃ ሚካኤል አማላጅነት ከእናቱና ከአባቱ፣ ከልጆቹም ጋራ የዘለዓለም ሕይወትን ወረሰ፡፡

መድኃኒታችን በተነሣባትም ቀን ይህ ክቡር መልአክ ሚካኤል ከውስጠኛው መጋረጃ ውስጥ ገብቶ በክብር ባለቤት ፊት እንዲህ እያለ ይለምናል፤ ‹‹እውነት ስለ ኾነ ቃል ኪዳንህ በምድር መታሰቢያዬን የሚያደርጉትን ትምርልኝ ዘንድ፤ ፈጣሪዬ ሆይ! እኔ አገልጋይህና መልእክተኛህ ከቸርነትህ እለምናለሁ፡፡ አንተ መሐሪና ይቅር ባይ ነህና፡፡›› የክብር ባለቤት ጌታችንም እንዲህ ብሎ ይመልስለታል፤ ‹‹የመንፈሳውያን ሰማያውያን መላእክት አለቃቸው ሚካኤል ሆይ! መታሰቢያህን የሚያደርገውን መሸከም እንደምትችል ከሲኦል ሦስት ጊዜ በክንፎችህ ተሸክመህ እንድታወጣ እነሆ እኔ አዝዤሃለሁ፡፡›› ይህንንም ቃል በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ ብሎት የበዓሉን መታሰቢያ ከሚያደርጉት በክንፎቹ ተሸክሞ የእሳቱን ባሕር አሳለፋቸው፡፡ እነርሱንም ከብቻው ጌታ በቀር የሚቈጥራቸው የለም፡፡

ስለዚህም የዚህን ታላቅ የከበረ የመላእክት አለቃ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ለማድረግ መታገል ይገባናል፡፡ እርሱ ከሰይጣን ወጥመድ ያድነን ዘንድ በዘመናችን ዅሉም ይጠብቀን ዘንድ፤ ኀጢአታችንንም ያስተሰርይ ዘንድ፤ መከራችንንም ያርቅ ዘንድ፤ የምድራችንንም ፍሬ ይባርክ ዘንድ፤ ፈቃዱንም ለመሥራት ይረዳን ዘንድ፤ ከእኛ ወገን የሞቱትን ዕረፍተ ነፍስ ይሰጥ ዘንድ፤ ወደ መንገድ የሔዱ አባቶቻችንና ወንድሞቻተንን ወደ ቤቶቻቸው በሰላም፣ በጤና ይመልሳቸው ዘንድ፤ በመካከላችንም ፍቅር ያደርግልን ዘንድ፤ እስከ መጨረሻዪቱም ሕቅታ ድረስ በቀናች ሃይማኖት ያጸናን ዘንድ፤ የክርስቶስ ወገኖች የኾኑ መኳንንቶቻችንንም ጠብቆ በወንበሮቻቸው ላይ ያጸናቸው ዘንድ፤ የሳቱትንም ወደ ቀናች ሃይማኖቱ ይመልሳቸው ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ ይለምናልና፡፡

ዳግመኛም በዚህች ቀን እግዚአብሔርን የሚፈራ አስተራኒቆስ የሚስቱ የቅድስት አፎምያ የዕረፍቷ መታሰቢያ ኾነ፡፡ ይህም ሰው በየወሩ ሦስት በዓላቶችን እያከበረ ኖረ፡፡ እሊህም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደቱ መታሰቢያ በየወሩ በሃያ ዘጠኝ፤ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም በዓል መታሰቢያ በየወሩ በሃያ አንድ፤ የከበረ የመላእክት አለቃ የኾነ የቅዱስ ሚካኤል በዓል መታሰቢያም በየወሩ በዐሥራ ሁለት ቀን ናቸው፡፡ የሚሞትበትም ጊዜው ሲቀርብ እርሱ ሲሠራው የነበረውን ምጽዋት ይልቁንም እሊህን ሦስቱን በዓላት እንዳታስታጉል ሚስቱን ቅድስት አፎምያን አዘዛት፡፡

እርሷም የከበረ የመልአኩ የሚካኤልን ሥዕል ያሥልላት ዘንድ ባሏን ለመነችው፡፡ እርሱም አሠርቶ ሰጣትና በቤቷ ውስጥ በክብር አኖረችው፡፡ ባሏም ከዐረፈ በኋላ ባሏ ያዘዛትን መሥራት ጀመረ፡፡ ሰይጣን ግን ቀናባት፡፡ በመበለት ሴት መነኵሲት ተመስሎ ከእርሷ ጋር ተነጋገረ፡፡ እንዲህም አላት፤ ‹‹እኔ አዝንልሻለሁ፤ እራራልሻለሁም፡፡ ገንዘብሽ ሳያልቅ፣ የልጅነትሽም ወራት ሳያልፍ አግብተሽ ልጅ ትወልጂ ዘንድ እመክርሻለሁ፡፡ ባልሽም መንግሥተ ሰማያትን ወርሷል፡፡ ምጽዋትም አይሻም፡፡›› አፎምያም እንዲህ ብላ መለሰችለት፤ ‹‹እኔ ከሌላ ሰው ጋራ ላልገናኝ በእግዚአብሔር ፊት ቃል ኪዳን አድርጌያለሁ፡፡ ርግቦችና መንጢጦች እንኳ ሌላ ባል አያውቁም፡፡ በእግዚአብሔር አርአያ ከተፈጠሩ ሰዎች ይህ ሊኾን እንዴት ይገባል?››

ምክሩንም ባልሰማች ጊዜ አርአያውን ለውጦ በላይዋ ጮኸባት፡፡ እንዲህም አላት፤ ‹‹እኔ በሌላ ጊዜ እመጣለሁ፡፡›› እርሷም የከበረ የመልአኩ የሚካኤልን ሥዕል ይዛ አሳደደችው፡፡ ከዚህም በኋላ ሰኔ ዐሥራ ሁለት ቀን የከበረ የመልአኩ የሚካኤል በዓል በሚከብርበት ዕለት እርሷም የበዓሉን ዝግጅት ስታዘጋጅ ሳለች ብርሃናዊ መልአክ መስሎ መጣ፡፡ ‹‹አፎምያ ሆይ! ሰላም ላንቺ ይኹን! እኔ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ነኝ፡፡ ጌታ ወደ አንቺ ልኮኛልና እርሱም ይህን መመጽወትሽን ትተሽ ለአንድ ምእመን ሚስት ትኾኚ ዘንድ አዞሻል፡፡›› ባል የሌላት ሴት መልሕቅ የሌለውን መርከብ እንደምትመስል ዕወቂ፤ እንደ አብርሃምና ያዕቆብ እንደ ዳዊትም እንደነርሱ ያሉ ብዙ ሴቶችን እንዳገባ፤ እግዚአብሔርንም ደስ እንዳሰኙት ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ጥቅሶችን ያመጣላት ጀመረ፡፡

ቅድስት አፎምያም መልሳ ‹‹አንተ የእግዚአብሔር መልአክ ከኾንኽ የመስቀል ምልክት ከአንተ ጋር ወዴት አለ? የንጉሥ ጭፍራ የኾነ ዅሉ የንጉሡን ማኅተም ሳይዝ ወደ ሌላ ቦታ አይሔድምና›› አለችው፡፡ ሰይጣኑም ይህንን በሰማ ጊዜ መልኩ ተለወጠና አነቃት፡፡ እርሷም ወደ ከበረው መልአክ ወደ ሚካኤል ጮኸች፡፡ ወዲያውኑም ደርሶ አዳናት፡፡ ያንም ሰይጣን ይዞ ይቀጣው ጀመረ፡፡ ሰይጣኑም ጮኸ፡፡ ‹‹ማረኝያለ ጊዜዬ አታጥፋኝ፤ እግዚአብሔር እስከ ዓለም ፍጻሜ ታግሦናልና›› እያለ ለመነው፡፡ ከዚያም ተወውና አባረረው፡፡

የከበረ መልአክ ሚካኤልም እንዲህ አላት፤ ‹‹ብፅዕት አፎምያ ሆይ! ሒደሽ የቤትሽን ሥራ አዘጋጂ፡፡ አንቺ ዛሬ ከዚህ ዓለም በሞት ትለዪአለሸና፡፡ እነሆ እግዚአብሔርም ዐይን ያላየውን፣ ጆሮም ያልሰማውን፣ በሰው ልብም ያልታሰበውን አዘጋጅቶልሻል፡፡›› ይህንንም ብሎ ሰላምታ ሰጣት፡፡ ወደ ሰማያትም ዐረገ፡፡ የበዓሉንም ዝግጅት እንደሚገባ ከፈጸመች በኋለ ወደ ኤጲስቆጶሱና ወደ ካህናቱ ዅሉ ላከች፡፡ ወደ እርሷም በመጡ ጊዜ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ይሰጧቸው ዘንድ ገንዘቧን ዅሉ አስረከበቻቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ተነሥታ ጸለየች፡፡ የከበረ የመልአኩ የቅዱስ ሚካኤልንም ሥዕል አንሥታ ታቅፋ ሳመችው፡፡ ያን ጊዜም በሰላም ዐረፈች፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን፡፡ እኛንም በጸሎቷ ይማረን፡፡ የዚህም የከበረ መልአክ ሚካኤል የረድኤቱ ኃይል ዅላችን የክርስቲያን ወገኖችን ይጠብቀን፡፡ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡– መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፲፪ ቀን፡፡

ሰኔ ሚካኤል – የመጀመርያ ክፍል  

ከመጽሐፈ ስንክሳር

ሰኔ ፲፪ ቀን ፳፻፱ .

አንድ አምላክ በኾነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሰኔ ዐሥራ ሁለት በዚች ዕለት የከበረ የመላእክት አለቃ የመልአኩ የሚካኤል የመታሰቢያውን በዓል ያከብራሉ፡፡ የሚያከብሩበትም ምክንያት እንዲህ ነው፤

እስክንድርያ በምትባል ከተማ አክላወበጥራ የተባለች ንግሥት የንጉሥ በጥሊሞስ ልጅ ዙሐል በሚባል ኮከብ ስም ያሠራችው ታላቅ ምኵራብ ነበረና በየዓመቱ ሰኔ በባተ በዐሥራ ሁለት ቀን በዚያ ምኵራብ ሕዝቡ ተሰብስቦ ታላቅ በዓል ያደርጉ ነበር፡፡ በዚያም ምኵራብ ውስጥ ዙሐል የሚሉት ታላቅ የነሐስ ጣዖት ነበረና በዓሉ በሚከበርበት ዕለት ብዙ ፍሪዳዎችን ያርዱለት ነበር፡፡

አባ እለእስክንድሮስ እስከተሾመበት ዘመን ድረስ ለዚያ ጣዖት እንዲህ ሲያደርጉ ኖሩ፡፡ ይኸውም ሦስት መቶ ዓመተ ምሕረት ተፈጽሞ በአራተኛው ምዕት ውስጥ ነበር፡፡ አባ እለእስክንድሮስ በእስክንድርያ ከተማ ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ፣ ጻድቅ ቆስጠንጢኖስም በነገሠ ጊዜ የክርስትና ሃይማኖት ስለ ተስፋፋች ያን ጣዖት ሊሠብረው ወድዶ ሳለ ጐስቋሎች ሰዎች ከለከሉት፡፡ እንዲህም አሉት፤ ‹‹እኛ በዚህ ቦታ ይህን በዓል ማክበርን ለምደናል፡፡ እነሆ ከአንተ በፊት ዐሥራ ስምንት ሊቃነ ጳጳሳት አልፈዋል፤ ይህን ልማዳችንንም አልለወጡብንም፡፡››

አባ እለእስክንድሮስ ግን ገሠፃቸው፤ አስተማራቸው፡፡ ስሕተታቸውንም በመግለጥ እንዲህ አላቸው፤ ‹‹ይህ የማይጎዳና የማይጠቅም ነው፡፡ እርሱንም የሚያመልክ ሰይጣናትን ያመልካቸዋል፡፡ ምክሬንስ ብትሰሙ ቀድሞ እንደ ነበረ አድርጌ ይህን በዓል እሠራላችኋለሁ፤ ይኸውም ቱን እንድንሰብረው፣ ምኵራቡንም እንድንባርከውና በከበረ መልአክ በመላእክት አለቃ በሚካኤል ስም ቤተ ክርስቲያን አድርገን እንድንሰይመው ነው፡፡ እኛም ይህን ታላቅ በዓል እንሠራለን፡፡ የሚታረዱትም ላሞችና በጎች ለድኆችና ለጦም አዳራዎች፣ ለችግረኞችም በከበረው መልአክ ስም ምግብ ይኹኑ፡፡ እርሱ በእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነት ያለው ስለ ኾነ ስለ እኛ ይማልዳልና፡፡›› ይህንንም ብሎ በዚህ በጎ ምክር አስወደዳቸው፤ እነርሱም ታዘዙለት፡፡

ከዚህም በኋላ ያንን ምኵራብ አድሰው በዚህ የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ስም ቤተ ክርስቲያን አደረጉት፡፡ በዚችም ዕለት አከበሩዋት፡፡ እርሷም የታወቀች ናት፡፡ እስላሞችም እስከ ነጉሡበት ዘመን ኑራ ከዚያ በኋላ አፈረሱዋት፡፡ ይህም በዓል ተሠራ፤ እስከ ዛሬም ጸንቶ ይኖራል፡፡

ዳግመኛም በዚች ዕለት እግዚአብሔር የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን በነገዱ ውስጥ በመላእክት ዅሉ ላይ በብዙ ክብር ሾመው፡፡ ይህም የከበረ መልአክ ክብር ይግባውና በጌታችን ፊት ስለ ሰው ልጆችና ስለ ፍጥረትም ዅሉ ይለምናል፤ ይማልዳልም፡፡ የዚህ የከበረ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ተአምራቱ ብዙዎች ናቸው፡፡ ከእነርሱም አንዱ ይህ ነው፤

እግዚአብሔርን የሚፈራ አንድ ሰው ነበረ፡፡ እርሱም የከበረ የሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ በየወሩ በዐሥራ ሁለተኛው ቀን ይልቁንም በሰኔ እና በኅዳር ወር አብልጦ ያከብር ነበር፡፡ በጐረቤቱም ርኅራኄ የሌለው አንድ ባለ ጠጋ ሰው ነበረ፡፡ ይህን እግዚአብሔርን የሚፈራውን ሰው የከበረ መልአክ የሚካኤልን በዓል በሚያደርግበት ጊዜ ይጠላውና ያቃልለው ነበር፡፡ ለድኆች ስለ መራራቱም ይዘባበትበት ነበረ፡፡ የሕይወቱ ዘመንም ተፈጽሞ የሚሞትበትና ከዚህ ከኃላፊው ዓለም ድካምም የሚያርፍበት ጊዜ ሲቀርብ የክቡር መልአክ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ታደርግ ዘንድ፣ ምጽዋት ሰጭም ትኾን ዘንድ ሚስቱን አዘዛት፡፡ ከዚህም በኋላ ዐረፈና ገንዘው ቀበሩት፡፡

ሚስቱም ፀንሳ ነበረች፡፡ የመውለጃዋ ጊዜም ደርሶ ምጥ ያዛት፡፡ በታላቅ ጭንቀት ውስጥ ሳለችም እንዲህ ብላ ጸለየች፤ ‹‹የእግዚአብሔር መልአኩ ሆይ ራራልኝ፡፡ በእርሱ ዘንድ ባለሟልነት አለህና፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ ስለ እኔ ለምንልኝ፡፡›› ይህንንም በአለች ጊዜ በቤቷ ውስጥ ብርሃን በራ፡፡ ከችግርም ዳነች፤ መልአኩ ውብ የኾነ ወንድ ልጅንም ወለደች፡፡ የእግዚአብሔርም መልእክተኛ ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ ሕፃኑን እንዲህ ብሎ ባረከው፤ ‹‹ርኅራኄ የሌለውን የዚህን ባለ ጠጋ ገንዘብና ሀብት፣ ጥሪቱንም ይህ ሕፃን እንዲወርስ እግዚአብሔር አዝዟል፡፡››

ባለ ጠጋውም በቤቱ፣ በዐልጋው ላይ ሳለ ጌታ ጆሮውን ከፍቶለት ይህን ነገር ከመልአኩ ሰማ፡፡ ይህንን በሰማ ጊዜ ታላቅ ኀዘን ደረሰበት፡፡ ሕፃኑንም የሚገድልበትን ምክንያት ይፈልግ ጀመረ፡፡ ነገር ግን ክብር ይግባውና ጌታ ይጠብቀው ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ያ ባለጠጋ ምክንያት አዘጋጅቶ ‹‹የሚያገለግለኝ ልጅ ይኾነኝ ዘንድ ልጅሽን ስጪኝ፡፡ እኔም እየመገብኹና እያለበስኹ አሳድገዋለሁ፡፡ ለአንቺም ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሻለሁ፤›› አላት፡፡ ይህንንም ነገር ከባለጠጋው በሰማች ጊዜ ስለ ችግሯ እጅግ ደስ አላት፡፡ ልጅዋንም ሰጠችው፡፡ እርሱም ሃያውን ወቄት ወርቅ ሰጣት፡፡ ልጅዋንም ወሰደው፡፡ የምሻው ተፈጸመልኝ ብሎ ደስ አለው፡፡

ከዚህም በኋላ በልጁ ቁመት ልክ ሣጥን አሠርቶ ሕፃኑን በሣጥኑ ውስጥ አስገብቶ ዘጋበት፡፡ እስከ ባሕርም ተሸክመው ወስደው በባሕር ጣሉት፡፡ ክብር ይግባውና በጌታችን ፈቃድ ያ ሣጥን ሳይሠጥም ከዚያች አገር የሃያ ቀን መንገድ ያህል ርቃ ወደምትገኝ ወደ አንዲት አገር ወደብ እስከሚደርስ በባሕሩ ላይ ተንሳፈፈ፡፡ በባሕሩም አካባቢ በጎቹን አሰማርቶ የሚጠብቅ አንድ ሰው ነበርና ሣጥኑን በውኃ ላይ ተንሳፎ አየው፡፡ እርሱም ከባሕሩ አውጥቶ ወደ ቤቱ ወሰደው፡፡ ይህን ሣጥን እንዴት እንደሚከፍተው ያስብ ጀመረ፡፡ ይህንም ሲያስብ ወደ ባሕሩ ይሔድ ዘንድ ጌታችን በልቡናው ሐሳብ አሳደረበት፡፡ ወዲያውኑም ተነሥቶ ወደ ባሕሩ ሔደና አንድ ዓሣ የሚያጠምድ ሰው አገኘ፡፡

ዓሣ አጥማጁንም ‹‹መረብህን በኔ ስም ጣል፡፡ ለሚያዘውም ዓሣ ዋጋውን እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ አጥማጁም እንዳለው አደረገ፡፡ ያን ጊዜም ታላቅ ዓሣ ተያዘ፡፡ ዋጋውንም ይዞ ወደ ቤቱ ሔደ፡፡ ለራትም ይጠብሰው ዘንድ አረደው፡፡ በሆዱም ውስጥ መክፈቻ አገኘ፡፡ በልቡም ‹‹ይህ መክፍቻ ይህን ሣጥን ይከፍተው ይኾን?›› አለ፡፡ በሣጥኑ ቀዳዳም በአስገባው ጊዜ ፈጥኖ ተከፈተ፡፡ በውስጡም ይህን ታናሽ ብላቴና አገኘ፡፡ ልጅ የለውም ነበርና ታላቅ ደስታ ደስ አለው፡፡ ጌታችንንም አመሰገነው፡፡ ሕፃኑንም በመልካም አስተዳደግ አሳደገው፡፡ ሕፃኑም አድጎ ጐልማሳ ኾነ፡፡

ከብዙ ዘመናትም በኋላ ያ ባለ ጠጋ ተነሥቶ ወደዚያ አገር ሔደ፡፡ በመሸም ጊዜ ወደ በግ ጠባቂው ደጅ ደረሰ፡፡ በግ ጠባቂውን ‹‹እስከ ነገ የምናድርበት ማደሪያ በአንተ ዘንድ እናገኛለን? ኪራዩንም እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ በግ አርቢውም ‹‹እንዳልኽ ይኹንና እደር›› አለው፡፡ ባለ ጠጋውም በዚያ አደረ፡፡ ራት በሚቀርብም ጊዜ ሕፃኑን ባሕራን› ብሎ ጠራው፡፡ ባለ ጠጋውም ሰምቶ ‹‹ልጅህ ነውን?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ በግ ጠባቂውም ‹‹አዎን፤ ታናሽ ሕፃን ኾኖ ሳለ ከባሕር አግኝቼዋለሁና እግዚአብሔር የሰጠኝ ልጄ ነው›› አለው፡፡ ባለ ጠጋውም ‹‹በምን ዘመን አገኘኸው?›› አለው፡፡ እርሱም ‹‹ከሃያ ዓመት በፊት›› ብሎ መለሰለት፡፡ ያን ጊዜም እርሱ ወደ ባሕር የጣለው መኾኑን ዐውቆ እጅግ አዘነ፡፡

በማግሥቱም ጎዳናውን ሊጓዝ በተነሣ ጊዜ ሰይጣናዊ ምክንያት አመካኝቶ በግ ጠባቂውን እንዲህ አለው፤ ‹‹ዕገሊት ወደምትባል አገር በቤቴ የረሳሁት ጉዳይ ስላለ እንድልከው ልጅህን ትሰጠኝ ዘንድ እሻለሁ፡፡ እኔም የድካም ዋጋውን ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ የብላቴናውም አባት ስለ ገንዘቡ ደስ ብሎት ልጁ ባሕራንን ሰጠው፡፡ እንዲህም ብሎ አዘዘው፤ ‹‹ልጄ ባሕራን፣ ይህ የከበረ ሰው ስለ ጉዳዩ ወደ ቤቱ ይልክህ ዘንድ ና፤ ወደ ቤትህም በሰላም ትመለሳለህ፡፡››

ያን ጊዜም ባለ ጠጋው ወደ መጋቢው እንዲህ ብሎ ደብዳቤ ጻፈ፤ ‹‹ይቺን ደብዳቤ በምታነባት ጊዜ ደብዳቤዋን ይዞ የመጣውን ገድለህ በጉድጓድ ውስጥ ጣለው፡፡ ማንም ዐይወቅ፡፡›› በመካከላቸውም የሚተዋወቁበትን ምልክት ጽፎ አሸጋት፤ ለባሕራንም ሰጠው፡፡ ለመንገዱም የሚኾነውን ስንቅ ሰጠው፡፡ ባሕራንም ተነሥቶ ጉዞውን ጀመረ፡፡ ሲጓዝም ሰንብቶ የአንዲት ቀን ጉዞ ሲቀረው እነሆ የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሚካኤል በንጉሥ ጭፍራ አምሳል በነጭ ፈረስ ላይ ተቀምጦ ‹‹አንተ ጐልማሳ የያዝኸው ምንድነው›› አለው፡፡ ‹‹ወደ ዕገሌ አገር ወደ ቤቱ ለማድረስ ከአንድ ባለ ጠጋ የተጻፈች መልእክት ናት›› አለው፡፡ ‹‹ያቺን ደብዳቤ አሳየኝ›› አለው፡፡ እርሱም ስለ ፈራ ሰጠው፡፡

ይቆየን

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የኖላዊነት ተልእኮው ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳሰቡ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሰኔ ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

የኢትዮጵያ ኦርቶደክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰባክያነ ወንጌል፤ በተለይ ምእመናንን በቅርበት የመከታተል ሓላፊነት ያለባቸው የእግዚአብሔር እንደራሴዎች፣ የቤተ ክርስቲያን ጠበቃዎች የኾኑ ካህናት የነፍስ ልጆቻቸውን ተግተው በማስተማር የኖላዊነት ተልእኮአቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አሳሰቡ፡፡

ብፁዕነታቸው ሰኔ ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከማኅበረ ቅዱሳን ጋዜጠኞች ጋር ባደረጉት ቆይታ በ፳፻፱ ዓ.ም ርክበ ካህናት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተላለፉ ውሳኔዎችን መሠረት በማድረግ በተለይ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴዎችን፣ ዐቂበ ምእመናንን፣ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎትና የልማት ሥራዎችን በሚመለከት ሰፋ ያለ ማብራርያ ሰጥተዋል፡፡

‹‹ቅዱስ ሲኖዶስን የሚመራውና ሥራውን የሚሠራው መንፈስ ቅዱስ ነው፤ ሰው ምክንያት ነው›› ያሉት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በቤተ ክርስቲያን ጉዳይ የመጨረሻው ወሳኝ አካል የኾነው ቅዱስ ሲኖዶስ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት፣ ለምእመናን ሕይወት የሚጠቅሙ መመርያዎችን በየጊዜው ሲያወጣ እና ውሳኔዎችን ሲያሳልፍ አክብሮ መቀበል ክርስቲያናዊ ግዴታ መኾኑን አስረድተዋል፡፡ መመርያዎቹና ውሳኔዎቹ በተግባር ላይ እንዲውሉም የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች እና ሕዝበ ክርስቲያኑ የሚጠበቅባቸውን ድርሻ ሊወጡ እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡

በቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው ተወግዘው ከተለዩ መናፍቃን በተጨማሪ በብፁዕነታቸው ሀገረ ስብከት ደቡብ ምዕራብ ሸዋም ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ውጪ የኾኑ ትምህርቶችንና መዝሙሮችንም በስውር ሲያስተምሩ፤ ሲዘምሩ የነበሩ ዘጠኝ የተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆችን አውግዘው መለየታቸውን ብፁዕነታቸው አውስተው፣ በሦስት መንገዶች ማለትም አውግዞ በመለየት፤ ከቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በማገድ እና ማስጠንቀቂያ በመስጠት ሀገረ ስብከታቸው በመናፍቃኑ ላይ ርምጃ መውሰዱን አስታውቀዋል፡፡

የኑፋቄ ትምህርት እንደሚሰጡ ሕጋዊ ማስረጃ ቀርቦባቸው ከአሁን በፊትም ኾነ በዘንድሮው የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተወግዘው ከቤተ ክርስቲያን አንድነት የተለዩ መናፍቃን ጥፋታቸውን አምነው፣ ስሕተታቸውን አርመው በንስሐ ለመመለስ ዝግጁ ከኾኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በይቅርታ እንደምትቀበላቸው፤ የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ በመተላለፍ ምእመናንን ማሰናከላቸውን ከቀጠሉ ግን በሕግ እንደምትጠይቃቸው አስረድተዋል፡፡

ሐዋርያዊ ተልእኮን በሚመለከትም ማኅበረ ቅዱሳን በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በማዘጋጀት በአማርኛ ቋንቋ እና አፋን ኦሮሞ ትምህርተ ወንጌል ከመስጠቱ ባሻገር ምእመናንን በማስተባበር ለተቸገሩ አብያተ ክርስቲያናት የገንዘብ ድጋፍ በማድረጉ የአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን መደሰታቸውን ብፁዕነታቸው ገልጸዋል፡፡

አያይዘውም የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ ይበልጥ ለማፋጠን ይቻል ዘንድ ማኅበሩ ቅዱሳት መጻሕፍትንና መንፈሳውያን መዝሙራትን በልዩ ልዩ ቋንቋዎች በማሠራጨት አገልግሎቱን ይበልጥ አጠናክሮ መቀጠል እንደሚኖርበት ጠቁመዋል፡፡

የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱን በስፋት ማዳረስ፣ የአብነት ት/ቤቶችን ማስፋፋት፣ የተዘጉ አብያተ ክርስቲያናት አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ እና ገቢ የሚያስገኙ ፕሮጀክቶችን መተግበር ወደፊት ሊከናወኑ የታቃዱ ተግባራት መኾናቸውን ያስታወቁት ብፁዕነታቸው፣ በሀገረ ስብከቱ ሥር የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትን በዘላቂነት ለመደገፍ ሲባል በወሊሶ ከተማ ለሚገነባው ባለ አራት ፎቅ ዅለገብ ሕንጻ ግንባታም መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፍ እንዲያደርግ መንፈሳዊ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

በመጨረሻም ‹‹ዘመኑ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ ፈተና የበዛበት፤ ከውስጥም ከውጪም ጠላቶች የበረከቱበት ወቅት ነው፡፡ በተለይ ትክክለኛ ሰባኪ እና የቤተ ክርስቲያን ልጅ መስለው በቅዱሳን ስም የሚሰበሰበውን ገንዘቧን እየበሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እየጎዱ ያሉ አፅራረ ቤተ ክርስቲያንም እየበዙ ነው፡፡ ስለኾነም ሰባክያነ ወንጌል፣ ቀሳውስት እና ዲያቆናት፣ እንደዚሁም የሰንበት /ቤት ወጣቶች ምእመናኑን በሥርዓት ሊያስተምሩ፤ ሕዝበ ክርስቲያኑም ከኑፋቄ ትምህርት አራማጆች ሊጠነቀቅ፤ በቃለ እግዚአብሔር በመጎልበትም ራሱን ከስሕተት ሊጠብቅ ይገባል›› በማለት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

አርአያነት ያለው ተግባር በአዳማ ማእከል

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሰኔ ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምርያ ማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል በየጊዜው መልካም ተግባራትን ያከናውናል፡፡ ማእከሉ በዚህ ዓመት ከፈጸማቸው አርአያነት ያላቸው ተግባራት መካከል ሦስቱን በዚህ ዝግጅት እናስታውሳችኋለን፤

ከወራት በፊት ማለት በመጋቢት ወር ፳፻፱ ዓ.ም ማእከሉ ከሞጆ ወረዳ ማእከል ጋር በመተባበር ኮምፒውተር ከነፕሪንተሩ ለሉሜ ወረዳ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በስጦታ መልክ አበርክቷል፡፡ የንብረት ርክክቡ በተፈጸመበት መጋቢት ፳፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም የማእከሉ ሰብሳቢ መ/ር ጌትነት ዐሥራት ‹‹ማእከሉ ይህንን ድጋፍ ያደረገው የቤተ ክህነቱን አሠራር ወቅቱ በሚፈልገው መልኩ ማዘመን አስፈላጊ ስለኾነ፤ ማኅበረ ቅዱሳንም የቤተ ክርስቲያናችንን መዋቅር በሚቻለው አቅም ዅሉ የመደገፍና የማገዝ ሓላፊነት ስላለበት ነው›› በማለት ማእከሉ የኮምፒውተር ድጋፍ ያደረገበትን ምክንያት አስረድተዋል፡፡

ማእከሉ ኮምፒውተሩን ለወረዳ ቤተ ክህነቱ ሲያስረክብ

ቤተ ክርስቲያንን በዅለንተናዊ መልኩ ለመደገፍ እና የቤተ ክህነቱ አሠራር ወቅቱን በሚዋጅ መልኩ እንዲቀላጠፍ ለማድረግ ማኅበረ ቅዱሳን እየሰጠ ያለው አገልግሎት የሚያስመሰግነው ትልቅ ተግባር መኾኑን በዕለቱ የተገኙት የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ትፍሥሕት ቀሲስ ሙሉጌታ ቸርነት ተናግረዋል፡፡ ድጋፍ የተደረገለት ወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ሥዩማን ቀሲስ ዋስይኹን ገብረ ኢየሱስም ማእከሉ ይህን ድጋፍ ማድረጉ ማኅበረ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያንን ለመደገፍ ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ተግባር እንደኾነ ገልጸዋል፡፡ ‹‹የተበረከተልን ኮምፒውተር የጽ/ቤታችንን አሠራር ዘመናዊ ከማድረጉ ባሻገር የተቀላጠፈ አገልግሎት ለመስጠትም ያስችለናል›› ያሉት ሥራ አስኪያጁ ስለ ተደረገላቸው ድጋፍም ማኅበረ ቅዱሳንን አመስግነዋል፡፡

ገዳማውያኑ የሕክምና መድኀኒት እና ሳሙና ሲቀበሉ

በሌላ የአገልግሎት ዘርፍ ደግሞ በማእከሉ አስተባባሪነት የአዳማ ከተማ ሆስፒታል ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች በደብረ ከዋክብት ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ለሚገኙ ገዳማውያንና የአብነት ተማሪዎች ግንቦት ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም የሕክምና አገልግሎት ሰጥተዋል፡፡ በዚህ መንፈሳዊ ተግባር ለሰባ ተማሪዎች የእከክ በሽታ፤ ለዐሥራ አራት ተማሪዎች ቀላል የመተንፈሻ አካል ሕመም፤ ለዐርባ ስምንት ተማሪዎች የሆድ ትላትል፤ ለአራት አባቶች የቀላል ሕክምና ርዳታ ተደርጎላቸዋል፡፡

ገዳማውያኑ የአካባቢ ጤና አጠባበቅን የሚመለከት ትምህርት ሲማሩ

በተጨማሪም አንድ መቶ የንጽሕና መጠበቂያ ሳሙና ለገዳማውያኑ ተበርክቷል፡፡ እንደዚሁም ለአንድ መቶ አምሳ የአብነት ተማሪዎች የአካባቢ ጤና አጠባበቅን የሚመለከት ትምህርት ተሰጥቷል፡፡ ይህን አገልግሎት ለመፈጸም መድኃኒት እና ሌሎች ቁሳቁሶች የተገዙበት ወጪ የተሸፈነው በግቢ ጉባኤውና በበጎ አድራጊ ምእመናን እንደ ኾነ ማእከሉ ለዝግጅት ክፍላችን የላከው ዘገባ ያመላክታል፡፡

በቅርቡ ደግሞ ‹‹መልካም ሥራን አብረን እንሥራ›› በሚል መሪ ቃል ልዩ መርሐ ግብር በማዘጋጀት ማእከሉ ግንቦት ፳፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በአዳማ ከተማ የበጎ አድራጎት አገልግሎት ሰጥቷል፡፡ ምእመናንን በማስተባበር የደም እጥረት ላለባቸው ሕሙማን እና ወላድ እናቶች ደም መለገስ፣ የአካባቢን ንጽሕና መጠበቅ የመርሐ ግብሩ ክፍሎች ነበሩ፡፡ በርካታ ምእመናን ከፍተኛ የደም መጠን እንዲለግሱ በማድረጉ የአዳማ ከተማ የደም ባንክ ጽ/ቤት ማእከሉን አመስግኗል፡፡

በመርሐ ግብሩ በቍጥር ከአምስት መቶ በላይ የሚኾኑ በጎዳና የሚኖሩ ወጣቶችን እና ሕፃናትን ንጽሕና የመጠበቅ፤ ልብስ አሰባስቦ የማልበስና ምግብ የመመገብ ተግባር ተከናውኗል፡፡ ወደ ሥራ መሠማራት የሚፈልጉ ወጣቶች ሥራ እንዲጀምሩ ለማገዝም የሊስትሮ ዕቃ ከነቁሳቁሱ ማእከሉ አስረክቧቸዋል፡፡ በዕለቱ የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ የሚያስችል የግንዛቤ ማዳበርያ ትምህርትም በከተማው ትራፊክ ፖሊስ ባለሙዎች ቀርቧል፡፡

ምእመናን ደማቸውን ሲለግሱ

ማእከሉ ከላከልን መረጃ እንደ ተረዳነው የማእከሉ አባላት፣ በአዳማ ከተማ የሚገኙ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች፤ የአቡነ ጎርጎርዮስ ት/ቤት መምህራን፣ ተማሪዎችና ወላጆች፤ እንደዚሁም የአዳማ ከተማ ምእመናን በበጎ አድራጎት መርሐ ግብሩ ተሳትፈዋል፡፡ የአዳማ ከተማ ከንቲባ፣ የከተማው ባህልና ቱሪዝም፣ የማኅበራዊ ጉዳዮች እና የደም ባንክ ጽ/ቤቶች ሓላፊዎች፤ የአዳማ ከተማ ኮሚኒኬሽን ጽ/ቤት ባለሙያዎች እና የኦሮምያ ቴሌቪዥን ድርጅት ጋዜጠኞች በሥፍራው ተገኝተዋል፡፡

የበጎ አድራጎት ተግባሩ በተከናወነበት ዕለት ከሰባት መቶ በላይ ተሳታፊዎች የታደሙበት መርሐ ግብር በአዳማ ከተማ ምክር ቤት አዳራሽ ተዘጋጅቶ ነበር፡፡ በዕለቱ የአዳማ ከተማ ከንቲባ ጽ/ቤት ሓላፊ አቶ ለማ ኃይሌ የመክፈቻ ንግግር ሲያደርጉ ‹‹በርቱልን! እግዚአብሔር ይስጣችሁ! ባደረጋችሁት በጎ ተግባር በከተማው ከንቲባ ጽ/ቤት ስም የተሰማን ደስታ ከፍ ያለ ነው፤›› በማለት የማኅበሩን አገልግሎት አድንቀዋል፡፡ አቶ ለማ አያይዘውም አዳማ ከተማ ለነዋሪዎቿ ምቹ እንድትኾን እና የተቸገሩ ሰዎች ራሳቸውን እንዲችሉ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ‹‹ማኅበሩ ከጽ/ቤታችን ጋር በጋራ እንደሚሠራ ተስፋ እናደርጋለን›› ብለዋል፡፡

በጎዳና ለሚኖሩ ወገኖች የተዘጋጁ አልባሳት

የአዳማ ከተማ የባህልና ቱሪዝም ጽ/ቤት ሓላፊ ወ/ሮ ዘይነባ አማን በበኩላቸው ‹‹ማኅበሩ ያደረገው አስተዋጽዖ ለሌሎች ቤተ እምነት ተከታዮችና የኅብረተሰብ ክፍሎች ትልቅ አርአያነት ያለውና ፈር ቀዳጅ ተግባር በመኾኑ በጽ/ቤቴ ስም ምስጋናዬን እያቀረብሁ፣ ወደ ፊትም ከማኅበሩ ጋር በጋራ ለመሥራት ዝግጁ ነን›› በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በጎ አድራጎት የቤተ ክርስቲያን አንዱ ተልእኮዋ እንደ ኾነ፤ ማኅበረ ቅዱሳንም የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ የሚደግፍ ማኅበር በመኾኑ ይህን የበጎ አድራጎት አገልግሎት ለመስጠት እንደ ተነሣሣ የማእከሉ ሰብሳቢ መ/ር ጌትነት ዐሥራት አስገንዝበዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያንም ኾነ ለአገር እያበረከተ ያለውን ዘርፈ ብዙ አገልግሎትም ሰብሳቢው በሰፊው አስረድተዋል፡፡

ወጣቶቹ አካባቢን በማጽዳት ሥራ ላይ

በመጨረሻም አገልግሎቱን በአግባቡ ለመስጠት እንዲቻል ልዩ ልዩ ድጋፍ ላደረጉ የመንግሥት ተቋማትና የሥራ ሓላፊዎች፤ ለበጎ አድራጊ ምእመናንና በአገልግሎቱ ለተሳተፉ ወገኖች ዅሉ ሰብሳቢው በማኅበሩ ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

እኛም እንደ ዝግጅት ክፍል የቤተ ክርስቲያናችንን መንፈሳዊ ተልእኮ ይበልጥ ለማጉላት፤ የአገራችንን ስም በመልካም ጎን ለማስጠራት ይቻል ዘንድ አዳማ ማእከል ከላይ የተጠቀሱትንና እነዚህን የመሰሉ አርአያነት ያላቸው ተግባራቱን አጠናክሮ ቢቀጥል፤ የሌሎች ማእከላት፣ የሰንበት ት/ቤቶች እና የማኅበራት አባላትም ይህን የማእከሉን ፈለግ ቢከተሉ መልካም ነው እንላለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡