ጾመ ሐዋርያት እና ጾመ ድኅነት

ግንቦት ፳፮ ቀን ፳፻፱ .

በዓለ ጰራቅሊጦስን ተከትለው ሁለት ዐበይት አጽዋማት ይጀመራሉ፡፡ እነዚህም ጾመ ሐዋርያት እና ጾመ ድኅነት (ረቡዕና ዓርብ) ሲኾኑ፣ ቍጥራቸውም ከሰባቱ አጽዋማት ነው፡፡

በቅዱሳት መጻሕፍት ተመዝግቦ እንደምናገኘው በብሉይ ኪዳን ነቢዩ ሙሴ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበለውን ሕገ ኦሪት ለሕዝቡ ከማስተማሩ በፊት ጾሟል (ዘፀ.፴፬፥፳፰)፡፡ ቅዱሳን ነቢያትም የተስፋውን ቃል መፈጸም እየተጠባበቁ እግዚአብሔርን ውረድ፤ ተወለድ እያሉ ይጾሙ፣ ይጸልዩ ነበር፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጾም የምግባር መሠረት መኾኑን ሊያስተምረን ወንጌልን ከመስበኩ አስቀድሞ ጾሟል (ማቴ.፬፥፩-፲፩)፤ ሐዋርያትም በበዓለ ኀምሳ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ ሕገ ወንጌልን ለሕዝቡ ከማስተማራቸው አስቀድሞ ጾመዋል፡፡ እኛም እነርሱን ተከትለን፣ በእነርሱ ሥርዓት በመመራት፣ በሐዋርያት ላይ ያደረው የመንፈስ ቅዱስ ጸጋና ሀብት በእኛም ላይ እንዲያድርብን በየዓመቱ ጾመ ሐዋርያትን እና ጾመ ድኅነትን፣ ሌሎችንም አጽዋማት አክብረን መጾም እንደሚገባን በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተወስኗል (ፍት.ነገ. ፲፭፥፭፻፹፮)፡፡

ጾመ ሐዋርያት ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው በመላው ዓለም ተዘዋውረው ወንጌልን ከመስበካቸው በፊት የጾሙት ጾም ነው፡፡ ጾመ ድኅነት ደግሞ ስያሜው እንደሚያመለክተው ‹የመዳን ጾም› ማለት ሲኾን፣ ይህም በብሉይ ኪዳኑ አጽዋማት በጾመ አስቴር እና በጾመ ዮዲት የተተካ የሐዲስ ኪዳን ጾም ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን በሐማ ምክንያት በእስራኤል ላይ ታውጆ የነበረው ሞት በጾመ አስቴር እንደ ተሻረ ዅሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም በዕለተ ረቡዕ በጌታችን ላይ በተፈጸመው ምክር የሰይጣን ሴራ ፈርሷልና በጾመ አስቴር ምትክ ረቡዕን እንጾማለን፡፡

በብሉይ ኪዳን በጾመ ዮዲት ምክንያት ሆሎሆርኒስ ድል እንደ ተደረገበት ዅሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ በከፈለው መሥዋዕትነት ዲያብሎስ ድል ተደርጓልና በጾመ ዮዲት ምትክ ዓርብን እንጾማለን፡፡ ዕለተ ረቡዕ የጌታ ሞት የተመከረበት፤ ዓርብም አምላካችን የተሰቀለበት ዕለት ነውና በመስቀሉ መሥዋዕትነት ያገኘውን ድኅነት ዘወትር ማሰብ ስለሚገባን ዅልጊዜ እንድንጾማቸው በቅዱስ ሲኖዶስ ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡ የእነዚህ የሁለቱ ቀናት (የረቡዕ እና ዓርብ) ጾም ‹ጾመ ድኅነት› ይባላል፡፡

በአጠቃላይ ጾመ ሐዋርያትና ጾመ ድኅነት እንደ ጾመ ነነዌና ዐቢይ ጾም የበዓላትና የአጽዋማት ማውጫ ቀመርን ተከትለው የሚመጡ ከሰባቱ አጽዋማት መካከል የሚመደቡ የጾም ጊዜያት ናቸው፡፡ የጾመ ሐዋርያት ፋሲካ (መፈጸሚያ) የቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ በዓለ ዕረፍት (ሐምሌ ፭ ቀን) ሲኾን፣ ጾመ ድኅነት ግን ከበዓለ ኀምሳ በስተቀር ዓመቱን ሙሉ የሚጾም ጾም በመኾኑ ፋሲካው በዓለ ትንሣኤ ነው፡፡

በዚህ ዓመት ጾመ ሐዋርያት ግንቦት ፳፰፤ ጾመ ድኅነት ደግሞ ግንቦት ፴ ቀን ይጀመራሉ፡፡ በመኾኑም የምንጠቀመው በራሳችን መልካም ተግባር፤ የምንወቀሰውም በራሳችን መጥፎ ድርጊት መኾኑን ተረድተን ይኼ የቄሶች፤ ይኼ የመነኰሳት ነው የሚል ሰበብ ሳንፈጥር ዅላችንም በአንድነት ብንጾማቸው ከእግዚአብሔር ዘንድ የምናገኘው ጸጋና ሀብት ይበዛልናልና ራሳችንን ለጾም እናዘጋጅ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የዘመነ ጰራቅሊጦስ ምንባባት

ግንቦት ፳፮ ቀን ፳፻፱ .

በዓለ ጰራቅሊጦስ ሀብተ መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት የተሰጠበት፤ ብዙ ሺሕ ምእመናን የሥላሴን ልጅነት ያኙበት ዕለት በመኾኑ ‹የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን› ተብሎ ይጠራል፡፡ በዓሉ ከዘጠኙ የጌታችን ዐበይት በዓላት አንዱ ሲኾን፣ በያዝነው ዓመትም ግንቦት ፳፯ ቀን ይዘከራል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከወረደበት ሰንበት (ከኀምሳኛው ቀን) ጀምሮ እስከሚቀጥለው ሰንበት ያለው ጊዜም (ስምንቱ ቀናት) ‹ዘመነ ጰራቅሊጦስ› ወይም ‹ሰሙነ ጰራቅሊጦስ› ይባላል፡፡ ይህም መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ ስለ መውረዱና በምእመናን ላይ ስለ ማደሩ የሚነገርበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ሰሙን በቤተ ክርስቲያን የሚነገረው ቃለ እግዚአብሔር፣ የሚሰጠውም ትምህርት የመንፈስ ቅዱስን በሐዋርያት ላይ መውረድ የሚመለከት ነው፡፡

በበዓለ ጰራቅሊስ ዕለት ‹ይትፌሣሕ› የሚለው የትንሣኤ መዝሙር በቤተ ክርስቲያን ይዘመራል፡፡ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎችም በትንሣኤ ዕለት የተነበቡት ናቸው፡፡ ምንባባቱ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ፣ በማረጉና መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት በመላኩ፤ እንደዚሁም ሥጋውን ቈርሶ፣ ደሙን አፍስሶ የሰውን ልጅ ከዘለዓለም ሞት በማዳኑ የሰው ዘር ብቻ ሳይኾን የሰማይ መላእክት፣ የምድር ፍጥረታት ሳይቀሩ ሐሤት እንደሚያደርጉ፤ ምድርም በክርስቶስ ደም በመንጻቷ የጌታችንን ትንሣኤ በደስታ እንደምታከብር የሚያስረዳ መልእክት አላቸው፡፡

ከበዓለ ጰራቅሊጦስ በኋላ ባሉት ሰንበታት (እሑዶች) የሚዘመሩ መዝሙራትም ትንሣኤን፣ ዕርገትን፣ የመንፈስ ቅዱስን መውረድ የሚያስረዱ ሲኾኑ፣ ምሥጢራቸውም ከሙታን ተለይቶ ለተነሣው፣ አዳምና ልጆቹን ከዲያብሎስ ተገዢነት እና ከሲኦል ባርነት ላወጣቸው ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ እንደሚገባ ያስተምራል፡፡ ከኀምሳኛው ቀን (ከበዓለ ጰራቅሊጦስ) ቀጥሎ በሚመጣው እሑድ (በስምንተኛው ቀን) የሚዘመረው መዝሙር፡- ‹‹ወረደ መንፈስ ቅዱስ ላዕለ ሐዋርያት ከመ ዘእሳት ወተናገሩ በነገረ ኵሉ በሐውርት …›› የሚል ሲኾን፣ ትርጕሙም መንፈስ ቅዱስ በእሳት አምሳል በሐዋርያት ላይ መውረዱንና በእርሱ ኃይል በዓለሙ ዅሉ ቋንቋዎች መናገራቸዉን የሚያስረዳ ነው፡፡

በዚህ ዕለት በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች፡- ኤፌ.፬፥፩-፲፯፤ ፩ኛዮሐ.፪፥፩-፲፰፤ ሐዋ.፪፥፩-፲፰፤ መዝ.፷፯፥፲፰ (ምስባክ)፤ ዮሐ.፲፬፥፩-፳፪ ሲኾኑ፣ የምንባባቱ ፍሬ ሐሳብም የሚከተለው ነው፤

የጳውሎስ መልእክት፡- እያንዳንዳችን መንፈስ ቅዱስ በገለጸልን መጠን የየራሳችን ልዩ ልዩ ጸጋ እንዳለን፤ የዮሐንስ መልእክት፡- የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚፈጽም ለዘለዓለም ሕያው እንደ ኾነ፤ የሐዋርያት ሥራ፡- መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ እንደ ወረደና በዓለሙ ዅሉ ቋንቋዎች መናገር እንደቻሉ፤ መዝሙረ ዳዊት (ምስባኩ)፡- እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ልዩ ልዩ ጸጋን እንደሚሰጥ፤ የዮሐንስ ወንጌል፡- እግዚአብሔር እኛን ልጆቹን እንደ ወላጅ አልባ እንደማይተወን ያስረዳሉ፡፡ ቅዳሴው ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ ሲኾን፣ ይህም ምሥጢረ ሥላሴን፣ የጌታችንን ሰው መኾን፣ ሕማሙን፣ ሞቱን፣ ትንሣኤዉን፣ ዕርገቱንና መንፈስ ቅዱስን መላኩን ይናገራል፡፡

ቅድስት በኾነች በጽርሐ ጽዮን በሐዋርያት ላይ የወረደው የእግዚአብሔር አብ ጸጋ፣ የእግዚአብሔር ወልድ ፍቅር፣ የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አንድነት በዅላችን ላይ ይደር፤ እጽፍ ድርብም ይኹን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በዓለ ጰራቅሊጦስ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ግንቦት ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹ጰራቅሊጦስ› የሚለው ቃል ከሦስቱ አካላት አንዱ የኾነው የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ መጠሪያ ስም ሲኾን፣ ትርጕሙም በጽርዕ (ግሪክ) ቋንቋ ናዛዚ (የሚናዝዝ)፣ መጽንዒ (የሚያጸና)፣ መስተፍሥሒ (የሚያስደስት) ማለት ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት በወረደበት ዕለት በቤተ ክርስቲያን የሚከበረው ይህ በዓል ‹በዓለ ጰራቅሊጦስ› ወይም ‹በዓለ ጰንጠቆስጤ› በመባል ይታወቃል፡፡ ‹ጰንጠቆስጤ› በግሪክ ቋንቋ በዓለ ኀምሳ፣ የፋሲካ ኀምሳኛ ዕለት፣ በዓለ ሠዊት (የእሸት፣ የመከር በዓል) ማለት ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፱፻፮-፱፻፯)፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ካረገ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ዐሥራ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት፣ ሰባ ሁለቱ አርድእት፣ አምስት መቶው ባልንጀሮች እና ሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት በኢሩሳሌም ከተማ በአንድነት ኾነው በጸሎት ይተጉ ነበር፡፡ ጌታችን በሚያርግበት ጊዜ ‹‹እነሆ አባቴ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ፤ እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ፤›› ሲል ለሐዋርያቱ በሰጣቸው የተስፋ ቃል መሠረት በዐረገ በዐሥረኛው ቀን መንፈስ ቅዱስን ልኮላቸዋል (ሉቃ. ፳፬፥፵፱)፡፡ ዅሉም በአንድ ቦታ ተሰባስበው ሳሉ በበዓለ ጰራቅሊጦስ ማለዳ እንደ ዐውሎ ነፋስ ያለ ድምፅ ድንገት ከሰማይ ወርዶ የነበሩበትን ቤት ሞላው፡፡ ከዚያም የተከፋፈሉ የእሳት ላንቃዎች በዅሉም ላይ አረፉባቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ዅላቸውም መንፈስ ቅዱስ ባደላቸው መጠን በየአገሩ ቋንቋዎች ዅሉ ተናገሩ (ሐዋ.፪፥፩-፬)፡፡

ጌታችን መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት የላከበት ይህ ዐቢይ በዓል ዐሥራቱን፣ በኵራቱን፣ ቀዳምያቱን ካህናተ ኦሪት ስለሚቀበሉበት በብሉይ ኪዳን በዓለ ሠዊት ተብሎ ይከበር ነበር፡፡ በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ስለ ተቀበሉበት በበዓለ ሠዊት ምትክ በዓለ ጰራቅሊጦስ ገብቶበታል፡፡ የበዓለ ትንሣኤ መነሻው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ማለትም በግብጽ፣ እስራኤል ከሞት የዳኑበት የመታሰቢያ በዓል እንደ ኾነው ዅሉ፣ ለበዓለ ጰራቅሊጦስም መነሻው ይኸው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ነው፡፡ የአይሁድ ፋሲካ ከተከበረ ከሰባት ሳምንታት በኋላ በኀምሳኛው ቀን የሩቆቹ ከከተሙበት ወጥተው፣ የቅርቦቹ ከተሰባሰቡበት ተገናኝተው ለበዓሉ ፍጻሜ የሚኾነውን በዓለ ሠዊት (የእሸት በዓል) ያከብሩ ነበር፡፡

ከግብጽ እስከ ከነዓን ምድር የደረሰው የእንስሳት መሥዋዕት ሲጠናቀቅ በኀምሳኛው ቀን ይሰባሰብ የነበረው የአይሁድ ጉባኤም መንፈስ ቅዱስ ከወረደበት ዕለት ጀምሮ ተበትኗል፡፡ መሥዋዕተ ኦሪቱ በአማናዊው መሥዋዕት በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም እንደ ተለወጠ ዅሉ ጉባኤ አይሁድም በኢየሩሳሌም ከተማ በተሰበሰቡ በቅዱሳን ሐዋርያት ጉባኤ ተለውጧል (ተቀይሯል)፡፡ ይህችውም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ከጉባኤያት ዅሉ ከፍ ከፍ ያለች የመንፈስ ቅዱስ ቤት ናትና፡፡ ‹‹ከዅሉ በላይ በምትኾን፣ ሐዋርያት በሰበሰቧት፣ በአንዲት፣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን፤›› እንዳሉ ሠለስቱ ምእት በጸሎተ ሃይማኖት፡፡

ሐዋርያት በጽርሐ ጽዮን ተሰባስበው ሳሉ መንፈስ ቅዱስ በእሳት አምሳል ወርዶ ሰማያዊ ሀብትን፣ ዕውቀትና ጸጋን አድሏቸዋል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላም በአእምሮ ጐልምሰዋል፤ ጥቡዓን (ቈራጦች)፣ ጽኑዓን ኾነዋል፤ ለስብከተ ወንጌል የሚፋጠኑበትንና ለሰማዕትነት የሚዘጋጁበትን ልቡና ታድለዋል፡፡ ቀድሞ ይናገሩት ከነበሩት ቋንቋ በተጨማሪ ፸፩ ቋንቋዎች ተገልጠውላቸው ምሥጢራትን በልዩ ልዩ ቋንቋ መተርጐም ጀምረዋል፡፡ ሐዋርያት በየገአሩ ቋንቋ ሲናገሩ የሰሙ በዚያ የነበሩ ሰዎችም በሐዋርያት ተገረሙ፡፡ አንዳንድ የአይሁድ ወገኖች ግን በሐዋርያት ላይ ያዩት ክሥተት አዲስ ነገር ስለኾነባቸው ‹‹ጉሽ ጠጅ ጠጥተው ሰክረው የኾነ ያልኾነውን ይቀባጥራሉ›› እያሉ ሐዋርያትን ያሟቸው ነበር፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ይህንን ዐሳባቸውን በመንፈስ ቅዱስ አውቆ ‹‹ሰክረዋል የምትሉ እናንተ እንደምትጠራጠሩት አይደለም፡፡ ጊዜው ማለዳ፣ ሰዓቱም ገና ሦስት ሰዓት ነውና፡፡ ዳሩ ግን በነቢዩ ኢዩኤልከዚህም በኋላ እንዲህ ይኾናል፤ መንፈሴን በሥጋ ለባሽ ዅሉ ላይ አፈሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ› (ኢዩ.፪፥፳፰) ተብሎ የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ፣ ይህንን ድንቅ ተአምር ያደረገው እናንተ የሰቀላችሁት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤›› በማለት ሰፊ ትምህርተ ወንጌል ሰጥቷቸዋል፡፡

በትምህርቱም ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት፣ ምሳሌ የመሰሉለት አምላክ ወልደ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ መነሣቱን፣ ማረጉንና ዳግም በክብር በምስጋና መጥቶ በሕያዋንና በሙታን ላይ የሚፈረድ መኾኑን ሐዋርያት እንደሚመሰክሩ በአይሁድ ፊት አሰምቶ ተናገረ፡፡ በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት የተማረኩ አሕዛብም ‹‹ምን እናድርግ?›› ብለው በጠየቁት ጊዜ ከክፋታቸው ተመልሰው፣ ንስሐ ገብተው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንዲጠመቁ ነገሯቸዋል፡፡ በዚያችም ሰዓት ሦስት ሺህ ሕዝብ በኢየሱስ ክርስቶስ አምኖ ተጠምቋል (ሐዋ.፪፥፩-፵፩)፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት፡- ‹‹በዚህች ቀን በሦስት ሰዓት ኢየሱስ ክርስቶስ ጰራቅሊጦስን ልኮልናልና በላያችን ኃይልን ሞላ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ሥልጣን እንዳለው በአዲስ ቋንቋ ተናገርን፤›› በማለት በዕለቱ ያዩትንና የተደረገላቸውን፣ እንደዚሁም የበዓሉን ታላቅነት ከመሰከሩ በኋላ ይህንን በዓል ማክበር እንደሚገባ አዝዘዋል፤ በዚህ ወቅት መጾምና ማዘን ተገቢ አለመኾኑንም ተናግረዋል (ዲድስቅልያ ፴፥፴፰-፴፱፤ ፴፩፥፷፱-፸)፡፡

ከዚህ ላይ ማስተዋል የሚገባን ቁም ነገር ‹መንፈስ ቅዱስ ወረደ› ሲባል፣ በሰዉኛ ቋንቋ መንፈስ ቅዱስ ከከፍታ ወደ ዝቅታ፣ ከሩቅ ወደ ቅርብ መምጣቱን ወይም መምጣቱን ለመናገር አይደለም፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ በሐዋርያት ላይ አድሮ ሰማያዊ ሀብትን፣ ዕውቀትን፣ ጥበብንና ልዩ ልዩ ጸጋን ማደሉን ለማስረዳት ነው እንጂ፡፡ ይኸውም ሥራዉን በሰው ላይ መግለጡን፣ ጸጋዉንም ማብዛቱን ለማመልከት የሚያገለግል ቋንቋ ነው፡፡ ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ ወረደ የሚለው ትምህርት መንፈስ ቅዱስን በቦታ፣ በጊዜና በወሰን መገደቡን አያመለክትም፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ በዓለሙ ዅሉ የሞላ ነውና፡፡ በሰው ላይ አድሮ ጥበብን ሲገልጥ ግን ‹ሞላ፤ አደረ፤ ወረደ› ተብሎ ይነገራል፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ለጊዜው ለሐዋርያት ቢሰጥም፣ በእነርሱ ላይ ብቻ ሳይገደብ እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ በምእመናን ላይም አድሮ ይኖራልና፡፡

በዓለ ትንሣኤውን በደስታ እንድናሳልፍ ፈቅዶ እስከ ዛሬ ድረስ ስለ ጠበቀን፣ አሁን ደግሞ በጾም፣ በጸሎት ኾነን እርሱን የምናመሰግንበትን ወቅት ስላመጣልን አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ስሙ ለዘለዓለሙ የተመሰገነ ይኹን፡፡

ምንጮች፡

  • መዝገበ ታሪክ፣ ክፍል ፪፤ መ/ር ኅሩይ ኤርምያስ፤ ፲፱፻፺፭ ዓ.ም፤ ገጽ ፹፬-፹፭፡፡
  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፰ ቀን፡፡
  • መጽሐፈ ግጻዌ፡፡
  • ማኅቶተ ዘመን፣ መ/ር በሙሉ አስፋው፤ ፳፻፩ ዓ.ም፤ ገጽ ፻፺፭-፪፻፬፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡