ብዙኃን ማርያም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፳ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

dscn9134

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከተወደደ ልጇ ጋር (በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ውስጥ የሚገኝ ሥዕል)

በቤተ ክርስቲያናችን ከሚዘከሩ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ክብረ በዓላት መካከል መስከረም ፳፩ ቀን የሚውለው በዓል ‹‹ብዙኃን ማርያም›› በመባል ይታወቃል፡፡ በዓሉ በሁለት ዐበይት ምክንያቶች ይከበራል፤ የመጀመሪያው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሃይማኖታዊ ውሳኔ ለማዘጋጀት ከሩቅም ከቅርብም የተሰባበሰቡት ቀን፤ ሁለተኛው ደግሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ዕፀ መስቀል በግሸን ደብረ ከርቤ የተቀመጠበት ዕለት መኾኑ ነው፡፡ ሁለቱንም ታሪኮች ከዚህ ቀጥለን እንመለከታቸዋለን፤

በ፫፻፳፭ ዓ.ም አርዮስ የሚባል መናፍቅ የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት አልቀበልም በሚል ክህደት እርሱ ተሰናክሎ ለሌሎችም መሰናክል ኾነ፡፡ ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት አርዮስ ክህደቱን እንዲተው ቢመክሩትም ሊመለስ አልቻለም፡፡ ይህ የአርዮስ ክህደትም በሊቃውንቱ መካከል መለያየትን ፈጥሯል፡፡ ጊዜው ታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ‹‹አብያተ ጣዖታት ይትአጸዋ አብያተ ክርስቲያናት ይትረኀዋ፤ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ! አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ!›› የሚል ዐዋጅ የነገረበት ወቅት ነበርና ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ በአርዮስ ክህደት ምክንያት በኒቅያ የሃይማኖት ጉባኤ እንዲካሔድ በየአገሩ ላሉ ሊቃውንት መልእክት አስተላለፈ፡፡

በዚህም መሠረት ከሚያዝያ ፳፩ ቀን ጀምሮ እስከ መስከረም ፳፩ ቀን ድረስ ፳፫፻፵፰ (ሁለት ሺሕ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንት) ሊቃውንት በኒቅያ ተሰበሰቡ፡፡ ኒቅያ ለዚህ ጉባኤ የተመረጠችበት ምክንያትም ጳጳሱን ከማኅበረ ካህናቱ፤ ንጉሡን ከሠራዊቱ ጋር አጠቃላ ለመያዝ የምትችል ሰፊና ምቹ ቦታ ከመኾኗ ባሻገር ለኹሉም አማካይ ሥፍራ ስለ ነበረች ነው፡፡ በጉባኤው ከተሰበሰቡ ሊቃውንት መካከልም እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ሙታንን ያስነሡ፣ ለምጽ ያነጹ፣ አንካሳ ያረቱ፣ የዕውራንን ዓይን ያበሩ ድውያንን የፈወሱ፣ ሌላም ልዩ ልዩ ተአምር ያደረጉ፤ እንደዚሁም ስለ ርትዕት ሃይማኖታቸው በመጋደል ዓይናቸው የፈረጠ፣ እጃቸው የተቈረጠ ይገኙበታል፡፡

ሊቃውንቱ ሱባዔ ይዘው በጸሎት ከቆዩ በኋላ ኅዳር ፱ ቀን በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሊቀ መንበርነት፣ በእለእስክንድሮስ አፈ ጉባኤነት ጉባኤው ተጀመረ፡፡ ንጉሡ ሊቃውንቱን ‹‹ስማችሁን፣ አገራችሁንና ሃይማኖታችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ›› ባላቸው ጊዜም ከ፳፫፻፵፰ቱ መካከል ፫፻፲፰ (ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ) ሊቃውንት ሃይማኖታቸውን ሲገልጹ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ፤ ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በመለኮት፣ በሥልጣን፣ በፈቃድ፣ በህልውና አንድ ነው›› ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ንጉሡም ‹‹ሃይማኖት እንደ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት ይኹን›› ብሎ ዐዋጅ አስነግሯል፡፡ እነዚህ ሊቃውንት በኦሪት ዘፍጥረት የተጠቀሱት ፫፻፲፰ቱ የአብርሃም ብላቴኖች ምሳሌዎች ናቸው /ዘፍ.፲፬፥፲፬/፡፡

፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በጉባኤው አርዮስን አውግዘው በመለየት ‹‹ነአምን በአሐዱ አምላክ፤ በአንድ አምላክ እናምናለን›› የሚለውን የሃይማኖት ጸሎት (የሃይማኖት መሠረት) እና ሌሎችንም የሃይማኖት ውሳኔዎችን ደንግገዋል፡፡ ሊቃውንቱ ጉባኤውን ያካሔዱት ኅዳር ፱ ቀን ይኹን እንጂ በአንድነት የተሰባሰቡት መስከረም ፳፩ ቀን ስለ ነበረ ይህ ዕለት ‹‹ብዙኃን ማርያም›› እየተባለ ይጠራል፡፡ ብዙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ለሃይማኖታዊ ጉባኤ የተሳባሰቡበት ዕለት ነውና፡፡

በሌላ በኩል መስከረም ፳፩ ቀን የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በአምባሰል ተራራ በግሸን ደብረ ከርቤ የገባበትና በዓሉ የከበረበት ዕለት ነው፡፡ ታሪኩም በአጭሩ የሚከተለው ነው፤

ዐፄ ዳዊት መንፈሳዊና ደግ ንጉሥ ነበሩ፡፡ በዘመናቸው በኢትዮጵያ ቸነፈር ተከሥቶ ሕዝቡ ስለ ተሰቃየባቸው እጅግ አዘኑ፤ በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ቢያመለክቱም ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላኩ ባሕታዊ መጥተው ‹‹የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል አስመጥተህ በአገርህ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አሠርተህ ብታስቀምጥ ረሃቡ፣ ቸነፈሩ ኹሉ ይታገሥልሃል›› አሏቸው፡፡ ዐፄ ዳዊትም ከብዙ ገጸ በረከት (ስጦታ) ጋር ‹‹የጌታችንን መስቀል ላኩልኝ›› የሚል መልእክት አስይዘው መልእክተኞችን ወደ ኢየሩሳሌም ሰደዱ፡፡ መልእክተኞቹም በታዘዙት መሠረት መስቀሉን ይዘው መምጣታቸውን ዐፄ ዳዊት ሲሰሙ ‹‹ክተት ሠራዊት ምታ ነጋሪት›› ብለው መስቀሉን ለመቀበል ጉዞ ጀመሩ፡፡

ዐፄ ዳዊት ስናር (ሱዳን) ደርሰው ከመልእክተኞቹ ጋር ተገናኝተው መስቀሉን በክብር አጅበው ወደ መካከል ኢትዮጵያ ለማስገባት ሲነሡም ከበቅሏቸው ወድቀው ጥቅምት ፱ ቀን ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፤ በዚህም ሠራዊታቸው ተደናግጠው የጌታችንን መስቀል እዚያው ትተው የዐፄ ዳዊትን አስከሬን ይዘው ተመለሱ፡፡ መስቀሉ በስናር ከቆየ በኋላ የዐፄ ዳዊት ልጅ ዘርዐ ያዕቆብ ሲነግሡ ወደ መሃል ኢትዮጵያ አምጥተው ቤተ ክርስቲያን አሠርተው ለማስቀመጥ ቢያስቡም ምቹ ቦታ ግን ሊያገኙ አልቻሉም ነበር፡፡ ንጉሡና ሠራዊታቸው ምቹ ቦታ ሲፈልጉ መስቀሉን በኤረር ተራራ፣ በደብረ ብርሃን፣ በመናገሻ ማርያም ዓምባ፣ በእንጦጦ ጋራ ብዙ ጊዜ አስቀምጠውት ቆይተዋል፡፡

መስቀሉ በእንጦጦ ጋራ ሳለ እግዚአብሔር አምላክ ‹‹አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል፤ መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አስቀምጥ›› የሚል ቃል ለንጉሡ በራእይ ነገራቸው፡፡ መስቀሉን ወደ ወሎ ሀገረ ስብከት እንዲወስዱትም አዘዛቸው፡፡ ንጉሡና ሠራዊታቸው በእግዚአብሔር መሪነት መስቀሉን ይዘው ወሎ ሲደርሱም ጌታችን ወደ አምባሰል እያመለከተ ‹‹አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል፤ መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አስቀምጥ›› ይላቸው ነበር፤ ንጉሡ መስቀሉን ይዘው ወደ ቦታው ሲያመሩ መስቀለኛው የግሸን ተራራን አገኙ፤ በዚያም ቤተ ክርስቲያን አሠርተው በ፲፬፻፵፮ (1446) ዓ.ም የጌታችንን መስቀል በክብር አስቀምጠውታል፡፡

ከዚህ በኋላ ንጉሡ ‹‹መካከሏ ገነት፤ ዳሯ እሳት ይኹን! የበረረ ወፍ፣ የሠገረ ቆቅ አይታደንባት! በድንገት ሰው የገደለ፣ ቋንጃ የቈረጠ ወንጀለኛ አይያዝባት!›› ብለው ዐዋጅ ነግረዋል፡፡ የእመቤታችን ጽላትም አብሮ በግሸን ደብረ ከርቤ እንዲቀመጥ አድርገዋል፡፡ ስለዚህም መስከረም ፳፩ ቀን በየዓመቱ በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡ ኀጢአታቸውን ለካህን ተናዘው፣ ንስሐ ገብተው በዚህ ዕለት ወደ ግሸን ደብረ ከርቤ በመሔድ የሚጸልዩና የሚማጸኑ ምእመናን ኹሉ እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደሚያገኙም ጤፉት በተባለችው መጽሐፍ ተጠቅሷል፡፡

ምንጭ፡- መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መ/ር አፈወርቅ ተክሌ፤ ፳፻፭ ዓ.ም፣ አዲስ አበባ፤ ገጽ ፫፶፬-፫፶፮፡፡

የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ፣ የእመቤታችን አማላጅነት፣ የክርስቶስ የመስቀሉ ኃይል፣ የአባቶቻችን ሊቃውንትና ነገሥታት በረከት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የደመራው ምሥጢር

መስከረም ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በሊቀ ሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ

demera-3

እግዚአብሔር አምላካችን የሠራቸው ታላላቅ ሥራዎች በምልክት የተገለጡ ናቸው፤ ለምሳሌ የሙሴ መስፍንነት፣ የአሮን ሊቀ ካህንነት የተረጋገጠው በአሮን በትር ምልክትነት ነው፡፡ አብርሃም ልጁ ይስሐቅን ሊሠዋ በታዘዘ ጊዜ የሞርያን ተራራ የመረጠው እግዚአብሔር በተራራው ላይ ካሳየው ብርሃን የተነሣ ነው፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያምና ቅዱስ መስቀልም የድኅነታችን ምልክቶች ናቸው፡፡ የአሮንና የሙሴ በትሮች፣ የይስሐቅ ቤዛ የሚኾን በግ የተገኘባት ዕፀ ሳቤቅ ደግሞ የእመቤታችንና የመስቀል ምልክቶች ነበሩ፡፡ ወደ ፊት የምንወርሰው መንግሥተ ሰማያት ክርስቶስ ነው፤ እርሱን ደግሞ ያገኘነው ከመስቀል ላይ ነው፡፡

ጥንተ ጠላት ሰይጣን ይህንን ስለሚያውቅ ቅዱስ መስቀሉን አጥብቆ ይቃወመዋል፤ ስለዚህም አይሁድን አነሳሥቶ ከ፫፻ ዓመታት በላይ ተቀብሮ እንዲቆይ አድርጓል፡፡ በመሠረቱ ለሰይጣን ምሥጢሩ ስለማይገባው ነው እንጂ የመስቀሉ ትክክለኛ መቀበሪያ ሥፍራ የምእመናን ልቡና ነው፡፡ ቀራንዮ ለመስቀሉ መትከያነት የተመረጠችውም ቀዳሜ ፍጥረት አዳም የተቀበረው በዚያ ስለ ነበረ ነው፡፡ ቦታው ‹‹የራስ ቅል ሥፍራ›› /ማቴ.፳፯፥፴፪/ መባሉም የኹላችን ራስ አዳም ዓፅሙ በዚያ ስላረፈ ነው፡፡ መስቀሉ በአዳማውያን ፍጥረታት አእምሮ ውስጥ እንጂ ከዚያ ውጪ የሚኖር ባለመኾኑ ተቀብሮ በቆየባቸው ዓመታት ውስጥም ፍቅሩ ከሰው ልጆች ልቡና አልወጣም፡፡

ጠላት በሠራው ተንኮል ተቀብሮ እንዳይቀር መስቀሉን እንድታወጣ መንፈስ ቅዱስ ንግሥት ዕሌኒን አስነሣት፡፡ ይህች ሴት ቤቷ በሀብት፣ በንብረት ሞልቶ በነበረበት ጊዜና በገረድ፣ በደንገጡር በምትንቀሳቀስበት ወቅት ምን እንደ ሠራች አልተመዘገበላትም ነበር፤ ከክብሯ ወርዳ በተጣለችበት ጊዜ ግን እግዚአብሔር ለሚፈልገው ሥራ ምቹ ኾና ተገኘች፡፡ እርሷ በተጣለችበት ባዕድ አገር ውስጥ ኾና የመስቀሉን ነገር ታስብ፤ ብርሃነ መስቀሉም ዘወትር በልቧ ያንጸባርቅ ነበር፡፡ ሐሳቧን እንዲያሳካላት የለመነችው አምላክም ኪራኮስ የተባለውን አይሁዳዊ ሽማግሌ ልኮ አቅጣጫውን አመላከታት፤ ኪራኮስ የጀመረውን ምሥጢርም መልአኩ ‹‹ደመራ ደምረሽ፣ ሰንድሮስ የሚባል ነጭ ዕጣን ጨምረሽ አቃጥዪው›› ብሎ ተረጐመላት፡፡ እርሷም መልአኩ እንደ ነገራት ብታደርግ ጢሱ ሰማይ ደርሶ ወደ ምድር ተመልሶ መስቀሉ ወደሚገኝበት ተራራ ሰገደ፡፡ በጢሱ ምልክትነት መስከረም ፲፯ ቀን የተጀመረው ቍፋሮ መጋቢት ፲ ቀን አልቆ ዕሌኒ መስቀሉን ከልበ ምድር ለማውጣት ችላለች፡፡

መስቀልና ደመራ እንዲህ ነበር የተገናኙት፡፡ ደመራው ለመስቀሉ መገኘት፣ መስቀሉም ለደመራው መሠራት ምክንያት ናቸው፡፡ በዚህ አንጻር መለኮትና ትስብእት በአንድነት መደመራቸው መስቀሉ እንዲሠራ ምክንያት ኾነዋል፡፡ አምላካችን ሥጋ ለብሶ ‹ክርስቶስ› በሚል የተዋሕዶ ስም ሲጠራ ለመከራ መዘጋጀቱን እንረዳለን፡፡ መስቀሉ የሥጋ ብቻ ነበረ፤ አሁን ግን መለኮትም በሥጋ ባሕርይ የመስቀሉ ተካፋይ ኾነ፡፡ ይህም የደመራው ውጤት ነው፡፡ መለኮት አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዘመን መስቀል የተሸከመ ሥጋን ሲዋሐድ መስቀሉን አስወግዶ አልነበረም፡፡ ይኸው በዕፀ በለስ ምክንያት የተሸከምነው መስቀል ነው፡፡ ሥጋ ዓቅም አጥቶ መስቀሉን ከትከሻው ላይ ሳያወርድ ለዘመናት የተጓዘውን ጕዞ መለኮት ኀይል ኾኖት ድካሙን ሳይለቅ ኀያል፤ ኀይሉን ሳይለቅ ደካማ ኾነ፡፡ መስቀል ትርጕሙ መከራ ቢኾነም ነገር ግን እግዚአብሔር ሲያመጣውና ሰው ሲያመጣው ግን ትርጕሙ ይለያያል፤ ሰው ያመጣው መስቀል ኹላችንን ለመከራ፣ ለሞት አሳልፎ ሰጥቶናል፡፡ የእግዚአብሔር መስቀል ግን መከራነቱ ለሰይጣን እንጂ ለእኛ ሕይወታችን ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድም ‹‹መስቀል ብሂል ዕፀ ሕይወት ብሂል፤ መስቀል ማለት የሕይወት ዛፍ ማለት ነው›› በማለት የመስቀልን ትርጕም ነግሮናል፡፡

አዳም ከገነት ሲወጣ በመላእክት እንዲጠበቅ የተደረገው የሕይወት ዛፍ የክርስቶስ መስቀል ነው፡፡ በዕፀ በለስ ምክንያት ኹላችንም እንደ ተጎዳን በዕፀ ሕይወቱም ተጠቃሚዎች ኾነናል፤ አስቀድመን በአዳም መከራ እንደ ተባበርን አሁን ደግሞ በደስታው እንተባበራለን፡፡ ሞትም ሕይወትም አንድ አድርጎናል፡፡ የክርስቶስ መስቀል ኹሉንም በሕይወት አስተባብሯልና፡፡ በአንጻሩ ሰውና ዲያብሎስን ለያይቷል፡፡ የኀጢአት ቁራኝነትን አጥፍቷል፡፡ ጌታችን በማኅፀን ሲፀነስ ጀምሮ የእኛን መስቀል መሸከም ሲጀምር የእርሱ የኾነውን ለእኛ ስለ ሰጠን ከሰይጣን ጋር መለያየታችን በመስቀሉ ተረጋግጧል፡፡ የአምላካችን መስቀል ምልክቱ ደመራ መኾኑ የእኛን ወደ እርሱ መሰብሰብና የጠላታችንን መበተን የሚያረግጥልን ነው፡፡ ጌታችንም ‹‹ወብየ ካልዓትኒ አባግዕ እለ ኢኮና እምዝንቱ ዐፀድ ወኪያሆንሂ ሀለወኒ አምጽኦን ዝየ፤ ከዚህ በረት ያልኾኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱንም ላመጣቸው ይገባኛል›› በማለት ሊሰበስበን እንደ መጣ ነግሮናል /ዮሐ.፲፥፲፮/፡፡ መስቀሉ ፍጥረት አንድ ደመራ ኾኖ የተሠራበት ስለ ኾነ በደመራ እንዲገለጥ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ኾነ፡፡

መስቀሉ አንድ ደመራ ያደረጋቸው ፍጥረታት

፩. ነቢያትና ሐዋርያት

ነቢያት የሚባሉት ከአዳም እስከ ዮሐንስ መጥምቅ ያሉ አባቶች ሲኾኑ፣ ከክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ጀምሮ ለቤተ ክርስቲያን የወንጌልን የምሥራች እንዲነግሩ የተላኩ አባቶች ደግሞ ሐዋርያት ይባላሉ፡፡ በእርግጥ ሐዋርያ የኾነ ነቢይ የለም እንጂ ነቢይ የኾነ ሐዋርያ አለ፡፡ ነቢያትና ሐዋርያት በዘመን፣ በክብር እና በግብር የማይገናኙ ፍጥረታት ናቸው፡፡ መንፈሰ ረድኤት የተሰጣቸው ነቢያት ለሐዋርያት የተሰጠውን መንፈሰ ልደት ለማግኘት አልተቻላቸውም፡፡ ሐዋርያት ግን ኹሉንም አንድ አድርገው ይዘዋል፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያው ስለዚህ ሲመሰክር ‹‹በጸጋ ላይ ጸጋ ተሰጠን›› በማለት አጕልቶ የተናገረው /ዮሐ.፲፥፲፰/፡፡ ነቢያት በዚህ ምድር የእግዚአብሔርን መንግሥት በመፈለግ ብዙ ደክመዋል፡፡

ሊቃውንቱ ነቢያትን በክረምት፣ ሐዋርያትን በበጋ ገበሬ ይመስሏቸዋል፡፡ የክረምት ገበሬ ላዩ ውሃ፣ ታቹ ውሃ ኾኖበት በጭቃ ወጥቶ በጭቃ ይመለሳል፡፡ ወደ ቤቱ ሲገባም ሚስቱ ጨምቃ ያቆየችለትን ጐመን በልቶ ደስ ሳይለው ይተኛል፡፡ ነቢያትም በዚህ ዓለም በጣዖት አምላኪ ነገሥታት፣ በነቢያተ ሐሰት ስብከት ሲንገላቱ ኖረው ሲሞቱም ሲዖል ይገባሉ እንጂ ገነትን አይወርሱም ነበር፡፡ የበጋ ገበሬ በደረቅ ወጥቶ፣ እሸት በልቶ፣ ተደስቶ ወደ ቤቱ ይመለሳል፤ ከቤቱ ሲገባም እንጀራው በሌማት፣ ጠላው በማቶት፣ ሲቀርብለት ደስ ብሎት ይበላል፤ ይጠጣል፡፡ ሐዋርያትም ልጅነትን አግኝተው ለማስተማር ተልከዋል፤ በሔዱበት ኹሉ ተአምራትን እንዲያደርጉ፣ ልጅነትንም እንዲሰጡ ሥልጣን ተሰጥቷቸዋል፡፡ ሞታቸው ሲደርስም መንግሥተ ሰማያት ተከፍቶ ይጠብቃቸዋል፡፡

ቅዱስ ያሬድም ‹‹ኖትያት ነቢያት ራግናት ሐዋርያት›› በማለት ነቢያትን በዋናተኛ፣ ሐዋርያትን በጀልባ ቀዛፊ መስሎ ይናገራል፡፡ ከቀዛፊዎች ይልቅ ዋናተኞች ይደክማሉ፡፡ ዋናተኞች ውሃው አጥልቋቸው፣ መተንፈስ ተስኗቸው አንዳንዶቹ ከዳር ይደርሳሉ፤ አንዳንዶቹም በድካም በውሃ ውስጥ ሰጥመው ይቀራሉ፡፡ ቀዛፊዎች ግን ምናልባት ሞገድና ማዕበል ካላሰጋቸው በስተቀር ይህ ኹሉ ውጣ ውረድ የለባቸውም፤ በጀልባዋ የተመሰለችው ቤተ ክርስቲያን ለነቢያት በተስፋ እንጂ በአካላ አልተሰጠችም፡፡ ነቢያት ከእርሷ ሳይደርሱ ሞት ቀድሟቸዋል፡፡ ሐዋርያትም በነቢያት ድካም ገብተው ነቢያት የዘሩትን የትንቢት ዘር አጭደዋል፡፡ ወንጌል የነቢያት ዘር ናት፤ ዳሩ ግን ፍሬውን ለመብላት የታደሉት ሐዋርያት ናቸው፡፡ እሸቱ ሲደርስ የገበሬዎቹ የነቢያት ጌታ ክርስቶስ ዘሩን እንዲሰበስቡና እንዲያከማቹ ሐዋርያቱን በእርሻ መካከል ይዟቸው ገብቷል /ማቴ.፲፪፥፩/፡፡ በአበው ፋንታ ውሉድን ለመተካት የመጣው መምህራችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነቢያትንና ሐዋርያትን በመስቀሉ አንድ ማኅበር አደረጋቸው፡፡ ሐዋርያው መስቀሉን ‹‹ገባሬ ሰላም›› በማለት ይጠራዋል /ኤፌ.፪፥፲፫/፡፡ ነቢያትንና ሐዋርያትን አንድ አድርጎ የእግዚአብሔርን መንግሥት ያወረሰ የክርስቶስ መስቀል ነውና፡፡

፪. ሙታንና ሕያዋን

አዳም በዕፀ በለስ ምክንያት የተሸከመው መስቀል ሞትን አምጥቶብናል፤ ክርስቶስ ስለ ሰው ልጆች ድኅነት ሲል የተሸከመው መስቀል ግን ሞትን ገድሎ ሕይወትን ሰጥቶናል፡፡ በዚህ ምክንያት የሞት መውጊያ ሲሰበር፣ የመቃብር ስቃይ ሲቋረጥ፣ የጨለማ ኀይል ሲሻር ከመስቀሉ ሥር ብዙ ሙታን እንደ አሸን ብቅ ብቅ አሉ፡፡ ምድር እስከዚያች ቀን ድረስ ሙታንን ትቀበል ነበር እንጂ ሕያዋንን ማስገኘት አትችልም ነበር፡፡ ሙታንና ሕያዋን የተፈላለጉበት መስቀል የመጀመሪያው ቀን ነው፡፡ በመስቀል ሙታን ሕያዋንን ፍለጋ ከመቃብር ወጥተው ወደ ከተማ ገቡ፡፡ ከታደለው የሕይወት ስጦታ የተነሣ ሞት አካባቢውን ለቆ ስለጠፋ በሩ እንደ ተከፈተለት እሥረኛ ሙታን ከመቃብር እየወጡ ከተማውን ሞልተውታል፡፡ ይህ ዕለት ሙታንን ከሕያዋን ጋር አፍ ለአፍ ያነጋገረ ዕለት ነው፡፡ ደመራው ሙታንን ከሕያዋን የሚለይ አይደለም፤ ታላቅነቱም እስከ ሲዖል ድረስ የሚታይ ነው፡፡

፫. ጻድቃንና ኀጥአን

የአዳም በደል በሕይወት የሚኖሩ ወንድማማቾችን በሁለት ሐሳብ ከፋፍሏቸው ነበር፡፡ የክርስቶስ የጽድቅ መስቀል ግን አንድ ሐሳብ ፈጠረላቸው፡፡ ጻድቁ አቤል ሳይበድል በደል የደረሰበት፣ ሳይገድል የተገደለ መኾኑ ከክርስቶስ ጋር ቢያመሳስለውም ሞቱ ግን ለሰው ልጆች ድኅነት አልጠቀመም፤ የፍጡር ደም ከእግዚአብሔር ጋር ሊያስታርቀን አይችልምና ኹላችንም በመከራ ውስጥ ለመቆየት ተገደናል፡፡ የክርስቶስ ሞት ግን የድኅነታችን መሠረት ኾነልን፡፡ በቤት ውስጥ የሚዘጋጅ መብራት ከፍ ብሎ ሲቀመጥ ኹሉን እንዲያሳይ ከምድር ከፍ ብሎ የተሰቀለው ክርስቶስም ጻድቃነ ብሊትንና ጻድቃነ ሐዲስን በዓይን እንዲተያዩ አድርጓቸዋል፡፡ በመስቀል ላይ የተፈጸመው ዕርቅ የኀጥአንን በደል ደምስሶላቸዋል፤ የጻድቃንን ጽድቅ አረጋግጦላቸዋል፡፡ ጻድቃንም ኀጥአንም አንድ ኾነው መንግሥቱን በጸጋው ወረሱ፡፡ ኢያሱ በኢያሪኮ እንዳደረገው አሞራውያን ወጥተው እስራኤል ብቻ ምድሪቱን የወረሷት አይደሉም፡፡ መስቀሉ ለኹሉም አንድ መንግሥትን አውርሷቸዋል፤ ጊዜው የደመራ ነውና፡፡ በምድር ደምቆ የታየው ይህ ደመራ እስከ መንግሥተ ሰማያት ድረስም ይቀጥላል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

‹‹… መስቀል የገደለውን ጥል እንደ ገና እንዳናመጣው በእጅጉ መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡›› ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

መስከረም ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

abun
የመስቀል ደመራ በዓል ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የየመምሪያ ሓላፊዎች፣ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ ካህናትና ሰባክያነ ወንጌል፣ የሰንበት ት/ቤትና የማኅበራት አባላት፣ በብዙ ሺሕ የሚቈጠሩ ምእመናን፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለ ሥልጣናትና ከልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች የመጡ ጐብኝዎች በተገኙበት መስከረም ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በመስቀል ዐደባባይ ተከብሯል፡፡

img_5471-2

mezmur

በሥርዓቱ ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ‹‹ወለጽልዕ ቀተሎ በመስቀሉ፤ ጥልንም በመስቀሉ ገደለው›› /ኤፌ.፪፥፲፮/ በሚል ኃይለ ቃል መነሻነት ቃለ ምዕዳን ሲያስተላልፉ ‹‹መስቀልን ማሰብና ማክበር ሁለት ነገሮችን እንድናስታውስ ያስገድደናል፤ ይኸውም አንደኛ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ያዳነንን ክርስቶስንና ፍቅሩን፤ ሁለተኛ በመስቀል ላይ የተፈጸመው የድኅነታችን መሥዋዕትነትን እንድናስብ ያደርገናል›› ካሉ በኋላ አያይዘውም መስቀል ሰላምን፣ አንድነትን፣ ነጻነትን፣ ዕርቅን የሚሰብክና የሚያስተምር፤ ስለ ድኅነተ ሰብእ የሚመሰክር፤ የእግዚአብሔር የማዳን ዓርማ፣ የድልና የአሸናፊነት ምልክት መኾኑን አስታውሰዋል፡፡

mk-2

 

‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመስቀል በዓልን በከፍተኛ ድምቀት የምታከብርበት ዋና ምክንያት የመስቀሉ አስተምህሮ የጥል ግድግዳን የሚያፈርስና መለያየትን የሚንድ፤ በምትኩ ሰላምን፣ አንድነትን፣ ወንድማማችነትን፣ መተሳሰብን፣ መከባበርን፣ መተማመንን፣ መቻቻልን፣ መተጋገዝንና ፍጹም ዘላቂ ፍቅርን በዋናነት የሚያስገኝ በመኾኑ ነው›› ያሉት ቅዱስነታቸው መስቀለ ክርስቶስ ዓለምን በአጠቃላይ ለመስበክ የሚያስችል ምቹ መድረክ ማግኘቱንና በዓለ መስቀል በኢትዮጵያ ስም በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መመዝገቡን አድንቀው ‹‹ለዚህ ዕድል ያበቃንን እግዚአብሔርን እጅግ አድርገን እናመሰግነዋለን›› ብለዋል፡፡

 

ቅዱስነታቸው በመቀጠልም ‹‹መስቀል ‹የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው› ብሎ ለገዳዮቹ ምሕረትንና ይቅርታን እየለመነ ፍጹም ፍቅርን ይሰብካል፤ መስቀል በንስሐ ለቀረበ በደለኛ ‹ዛሬዉኑ ከእኔ ጋር በገነት ትኖራለህ› እያለ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ እንዲኖር ይፈቅዳል፤ መስቀል ለሰው ድኅነት ሲባል ራስን አሳልፎ በመስጠት ፍጹም ድኅነትን ይሰብካል፡፡ ሌሎችንም ለሰው ልጅ ጠቃሚ የኾኑ ነገሮችን ያስተምራል፤ ትምህርቱም በነፍስና በሥጋ ያድናል›› በማለት አስተምረዋል፡፡

tirit

ቅዱስ ፓትርያርኩ በመተጨማሪም ‹‹ዛሬ በአገራችን አልፎ አልፎ የሚከሠተው የጥል መንፈስ ያለበት የሚመስል ክሥተት የመስቀሉን ስብከትና ትምህርት በቅጡ
ካለማዳመጥና ካለማስተዋል የተነሣ እንደ ኾነ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ የመስቀልን ምልክት በአካሉ፣ በአንገቱ፣ በግንባሩና በልብሱ የተሸከመ ሰው ወንድሙን አይጠላም፤ መናናቅን አያስተናግድም፡፡ መከፋፈልን፣ መለያየትን፣ መነታረክን፣ መጨቃጨቅንና ራስ ወዳድነትን የመሳሰሉ የዲያብሎስ የጥፋት ሠራዊት መስቀልን ባነገበ ክርስቲያን ዘንድ ቦታ የላቸውም›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በመጨረሻም ‹‹የመስቀሉን ትምህርት ከእኛ አልፎ በዓለሙ ኹሉ ለማዳረስ በምንሮጥበት በአሁኑ ጊዜ የአገራችን ሕዝቦች የመስቀል ትርጕም ሰላምና ፍቅር መኾኑን መረዳት አቅቷቸው በጥላቻ ዓይን የሚተያዩ ከኾነ የማስተማሩን ብቃት ጥያቄ ውስጥ ይከተዋል፤ መስቀል የገደለውንም ጥል እንደ ገና ስበንና ጎትተን እንዳናመጣው በእጅጉ መጠንቀቅ ያስፈልጋል›› በማለት አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡demera-3

ክብረ መስቀል በኢትዮጵያ

መስከረም ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም 

በዝግጅት ክፍሉ

cross

‹መስቀል› ስንል ሦስት መሠረታዊ ቁም ነገሮችን መጥቀስ ይቻላል፤ የመጀመሪያው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ ከሞተ ነፍስ ለማዳን ሲል የተቀበለው መከራና የከፈለው መሥዋዕትነት መስቀል ይባላል፡፡ ሁለተኛው በክርስትና ውስጥ የሚያጋጥም ልዩ ልዩ ዓይነት መከራም መስቀል ነው፡፡ ጌታችን ‹‹እኔን መከተል የሚወድ ቢኖር ራሱን ይካድ፤ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ›› /ማቴ.፲፮፥፳፬/ በማለት መናገሩም በክርስትና ሕይወት ውስጥ የሚደርሰውን ይህንኑ መከራ መታገሥ ተገቢ መኾኑን ሲያመለክተን ነው፡፡ ሦስተኛው ደግሞ ጌታችን የተሰቀለበት ዕፀ መስቀል ሲኾን በሦስቱም ቁም ነገሮች ነገረ መስቀል (የመስቀሉ ነገር) ከክርስትና ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት አለው፡፡ ስለ ክርስትና ሕይወት ሲነሣ ነገረ መስቀልም አብሮ ይታወሳል፡፡ ስለ ክርስትና ሲነገር ክርስቶስ የተቀበለው መከራ፣ የተሰቃየበትና ነፍሱን በፈቃዱ አሳልፎ የሰጠበት ዕፀ መስቀል፣ በክርስትና ሕይወት ውስጥ የሚከሠት ፈተና አብረው የሚነሡ ጉዳዮች ናቸው፡፡

ስለ መስቀል ሲነገር ክርስቶስ ሰውን ለማዳን ሲል በሥጋው የተቀበለው ስቃይ፤ ሰማዕታት በሃይማኖታቸው ምክንያት የሚደርስባቸው ስደት፣ መከራና ሞት፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በየዘመኑ በአረማውያንም በውስጥ ጠላቶችም የሚያጋጥማት የዘረፋና የቃጠሎ፣ እንደዚሁም የሰላም እጦትና የመልካም አስተዳደር እጥረት፤ በተጨማሪም በክርስትና ሕይወት ውስጥ የሚከሠቱ የኑሮ ውጣ ውረዶች መስቀልና ክርስትና የማይነጣጠሉ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ለመኾናቸው ማስረጃዎች ናቸው፡፡ ከዚሁ ኹሉ ጋርም መስቀል ሲባል ክርስቶስ መከራ የተቀበለበት፣ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው የለየበት፣ ድንቅ ተአምራትን ያደረገበት፣ ከኹሉም በላይ ለአዳምና ለልጆቹ ነጻነትን ያወጀበት ዕፀ መስቀልም አንዱ የክርስትናችን አካል ነው፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በጉልላቷና በሌሎችም ንዋያተ ቅድሳቷ መስቀልን እንደ ምልክት ትጠቀመዋለች፡፡ መሠረቷ፣ የልጆቿ መድኀኒት ክርስቶስ በመስቀል ላይ የከፈለው ዋጋ ነውና ሰንደቅ ዓላማዋ መስቀል ነው፡፡ አባቶች ካህናት ጸሎት ሲያደርጉ ‹‹ከመስቀሉ ዓላማ፣ ከወንጌሉ ከተማ አያውጣን›› እያሉ የሚመርቁትም ስለዚህ ነው፡፡ በእጃቸው ይዘውት የሚንቀሳቀሱት፣ እኛንም የሚባርኩትም በመስቀል ነው፡፡

መስቀል የጠላት ሰይጣን ተንኮል የከሸፈበት፣ የክርስቶስ ቤዛነት የተረጋገጠበት የድኅነት ኃይል ነውና፡፡ በየገዳማቱና በየአብነት ት/ቤቱ፤ እንደዚሁም በክርስቲያኖች መኖሪያ ቤቶች ውስጥ በሚከናወኑ ተግባራት መስቀል ሰፊ ድርሻ አለው፡፡ በቅዳሴ ጊዜ፣ በጠበል ቦታ፣ በጸሎት ጊዜያት፣ ወዘተ ቡራኬ የሚፈጸመው በመስቀል በማማተብ ነው፡፡ የመስቀሉን ምልክት ባዩ ጊዜ አጋንንት ይንቀጠቀጣሉ፤ ካደሩበት ሰው ላይም በፍጥነት ይወጣሉ፡፡ ምእመናን በመስቀሉ ስንዳሰስ ከልዩ ልዩ ደዌ እንፈወሳለን፡፡

ወደ አገራችን ክርስቲያናዊ ባህል ስንመለስ በኢትዮጵያ የመድኀኒታችን የክርስቶስ መስቀል በብዙ ተግባራት ላይ በምልክትነት ጥቅም ላይ ሲውል ይታያል፡፡ ለምሳሌ በቡልኮ፣ ጋቢ፣ ነጠላ፣ ቀሚስ ወዘተ የመሳሰሉ የሸማ ልብሶች፤ እንደዚሁም በጆሮ፣ በአንገት፣ በእጅና ሌሎችም ጌጣጌጦች ላይ የመስቀል ምልክት አለ፡፡ ክርስቲያን ልጃገረዶች (በተለይ በሰሜኑ የአገራችን ክፍል) በግንባራቸው፣ በጉንጫቸው፣ በአንገታቸው፣ በደረታቸውና በእጃቸው ላይ በመስቀል ቅርፅ እየተነቀሱ ያጌጡበታል፡፡

ክርስቲያኖች ከዚህ ዓለም በሞት ስንለይም በመቃብር ሣጥናችን ወይም በሐውልቶቻችን ላይ የመስቀል ምልክት ይቀመጣል፡፡ በቤት ውስጥም ስንተኛና ከእንቅልፋችን ስንነቃ ፊታችንንና መላ ሰውነታችንን በትእምርተ መስቀል እናማትባለን፤ አባቶችና እናቶችም ውሃ ሲቀዱ፣ ሊጥ ሲያቦኩ፣ እንጀራ ሲጋግሩ፣ ምግብ ሲቈርሱ፣ ወዘተ በመስቀል አማትበው ነው፡፡ በአጠቃላይ መስቀል ብዙ ነገር ነው፤ መስቀል በክርስትና ሕይወት ውስጥ በሚደረጉ ተግባራት ኹሉ ያለው ድርሻ ጕልህ ነው፡፡ /ለተጨማሪ መረጃ ግሸን ደብረ ከርቤ የቃል ኪዳን አምባ፣ መስከረም ፲፱፻፺፮ ዓ.ም፤ ገጽ ፺፮-፻፪ ይመልከቱ/፡፡

ከዓለም ክርስቲያኖች በበለጠ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ለጌታችን ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል የተለየ እምነትና አክብሮት አላቸው፡፡ ኢትዮጵያውያን ምእመናን ጌታችን ሰውን ለማዳን ሲል ብዙ ጸዋትወ መከራ የተቀበለበትንና ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስ ያገኘንበት መስቀልን ለአፍታም ያህል የማያስታዉሱበት ቅፅበት ባይኖራቸውም በዓመት ለአምስት ጊዜያት ያህል በቤተ ክርስቲያንና በዐደባባይ ያከብሩታል፡፡

በዚህም መሠረት በዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ግማደ መስቀሉ ከእስክንድርያ ወደ ኢትዮጵያ የመጣበትን የመታሰቢያ በዓል በየዓመቱ መስከረም ፲ ቀን ቀደም ባለው ወቅት በነገሥታቱ፣ በመሳፍንቱና በመኳንንቱ ፊት በቤተ መንግሥት ያከብሩት ነበር፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ደግሞ ከካህናትና ከምእመናን ጋር በቤተ ክርስቲያን ዐውደ ምሕረት ያከብሩታል፡፡

እንደዚሁም በ፫ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ንግሥት ዕሌኒ በዕጣን ጢስ አመልካችነት መስቀሉን ከተቀበረበት ቦታ ለማውጣት ቍፋሮ ያስጀመረችበትን የመታሰቢያ በዓል በየዓመቱ መስከረም ፲፮ ቀን ደመራ ደምረው በመለኮስ በታላቅ መንፈሳዊ ሥርዓት በዐደባባይ ያከብሩታል፡፡ በማግሥቱ መስከረም ፲፯ ቀንም ንግሥት ዕሌኒ ቅዳሴ ቤቱን ያከበረችበትን የመታሰቢያ በዓል ታቦት አውጥተው ዑደት በማድረግ በቤተ ክርስቲያን ያከብሩታል፡፡

በማያያዝም መስከረም ፳፩ ቀን ግማደ መስቀሉ በሚገኝበት በግሸን ደብረ ከርቤ ማርያም በታላቅ በዓለ ንግሥ ያከብሩታል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ መስቀሉ ከተቀበረበት ተራራ ተቈፍሮ የወጣበት መጋቢት ፲ ቀንም በቤተ ክርስቲያን በደማቅ ሥርዓት ይከበራል፡፡ /ምንጭ፡- የ፳፻፱ ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓልን በማስመልከት በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የተዘጋጀ ልዩ ዕትም መጽሔት፣ ገጽ ፪/፡፡

በክርስቶስ ደም የተቀደሰው ይህ ክቡር መስቀል ለበርካታ ዓመታት በአይሁድ ምቀኝነት በጎልጎታ ተቀብሮ ከኖረ በኋላ በንግሥት ዕሌኒና በልጇ ቈስጠንጢኖስ ጥረት ከተቀበረበት ወጥቶ ከፀሐይ ብርሃን በላይ አብርቷል፤ ሙት በማስነሣት፣ ሕሙማንን በመፈወስ ብዙ ተአምራትን አሳይቷል፡፡ በመላው ዓለም በሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ደመራ ተደምሮ በዓሉ የሚከበረውም ንግሥት ዕሌኒ መስቀሉ የተቀበረበትን ቦታ ለማግኘት ከእግዚአብሔር መልአክ በተሰጣት አቅጣጫ መሠረት ያነደደችውን ዕጣንና የመስቀሉን መገኛ የጠቆማትን ጢስ ለማስታዎስ ነው፡፡

እግዚአብሔር የተመሰገነ ይኹን! በንጉሥ ዳዊትና በልጃቸው በዘርዐ ያዕቆብ አማካይነት ወደ አገራችን የመጣው የጌታችን መስቀል ቀኝ ክፍል በአገራችን ኢትዮጵያ በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት በግሸን ደብረ ከርቤ ይገኛል፡፡ ከቅዱስ መስቀሉና ከገዳሙ በረከት ለመሳተፍ ብዙ ምእመናን በየዓመቱ ቦታው ድረስ በመሔድ በዓለ መስቀልን ያከብራሉ፡፡

በዓለ መስቀል በቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይኾን በየመንደሩና በየቤቱም ምእመናን ደመራ በመደመር፣ ጸበል ጸሪቅ በማዘጋጀት በድምቀት ያከብሩታል፡፡ በተለይ በደቡቡ የአገራችን ክፍል በዓለ መስቀል በደማቅ ሥርዓት ይከበራል፡፡ ይህም የቀደሙ አባቶቻችን ስለ በዓለ መስቀል ይሰጡት የነበረው ትምህርት ቁም ነገር ላይ መዋሉን የሚያስረዳ መንፈሳዊ ትውፊት ነው፡፡ የአከባበሩ ባህል ከቦታ ቦታ ይለያይ እንጂ በዓለ መስቀል በየዓመቱ በመስከረም አጋማሽ በመላው ኢትዮጵያ በልዩ ድምቀትና በመንፈሳዊ ሥርዓት ይከበራል፡፡

በአጠቃላይ በአገራችን ኢትዮጵያ መስቀልና ክርስትና እንዲህ ሳይነጣጠሉ ተሳስረው ይኖራሉ፡፡ እኛም አባቶቻችን እንዳስተማሩን ይህንን በክርስቶስ ደም የተቀደሰውን መስቀል በዘወትር ጸሎታችን ‹‹… መስቀል ኃይልነ መስቀል ጽንዕነ መስቀል ቤዛነ መስቀል መድኃኒተ ነፍስነ አይሁድ ክህዱ ንሕነሰ አመነ ወእለ አመነ በኃይለ መስቀሉ ድኅነ፤ … መስቀል ኀይላችን፣ ጽንዓችን፣ ቤዛችን፣ የነፍሳችን መዳኛ ነው፡፡ አይሁድ ይክዱታል፤ እኛ ግን እናምንበታለን፡፡ ያመነውም እኛ በመስቀሉ ኀይል እንድናለን፤ ድነናልም›› እያልን ለመስቀሉ ያለንን ክብር እንገልጻለን፤ በክርስቶስ መስቀል ኀይል መዳናችንንም ስንመሰክር እንኖራለን፡፡ ልዑል እግዚአብሔር በመስቀሉ ኃይል ኹላችንንም ከልዩ ልዩ ዓይነት መከራ ይጠብቀን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዘመነ ፍሬ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፲፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ ምእመናን! ከአሁን በፊት ‹ዘመነ ክረምት ክፍል አራት› በሚል ርእስ ባቀረብነው ዝግጅት የሰው ልጅ ዓቅሙ በሚችለው ኹሉ ጠንክሮ እየሠራ የመኖር ተፈጥሯዊና ክርስቲያናዊ ግዴታ እንዳለበት፤ እየሠራም የድካሙን ዋጋ እንዲያገኝ መጸለይ፣ እየጸለየ ደግሞ የጸሎቱን ውጤት ለመቀበል ተግቶ መሥራት እንደሚገባው የሚያስገነዝብ ትምህርትና እንደዚሁም ከነሐሴ ፳፰ እስከ መስከረም ፩ ቀን ድረስ ያለው ክፍለ ክረምት ‹‹ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን መዓልት›› እንደሚባል፣ በዚህ ክፍለ ክረምት ውስጥ ባሉት ቀናትም እነዚህን ፍጥረታት የሚመለከቱ ትምህርታት እንደሚቀርቡ በማስታዎስ ወቅቱን ከክርስቲያናዊ ሕይወት ጋር የሚያስቃኝ ዝግጅት አቅርበን ነበር፡፡ በተጨማሪም ከመስከረም ፩-፰ ቀን ድረስ ያለው ፭ኛው የክረምት ክፍለ ጊዜ ‹‹ዮሐንስ›› እንደሚባልና ይህ ወቅት የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ሕይወት ከአዲሱ ዓመት ጋር እየተጣጣመ በስፋት የሚዳሰስበት ጊዜ እንደ ኾነ መጥቀሳችን የሚታወስ ነው፡፡ በዛሬው ዝግጅታችንም ስድስተኛውን የክረምት ክፍለ ጊዜ የሚመለከት አጭር ትምህርት ይዘን ቀርበናል፤ እንድትከታተሉልን በአክብሮት እንጋብዛለን!

በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ከመስከረም ፱ – ፲፭ ቀን ያለው ክፍለ ክረምት ‹ፍሬ› ይባላል፡፡ ‹ዘመነ ፍሬ› ደግሞ ‹የፍሬ ወቅት፣ የፍሬ ዘመን፣ የፍሬ ጊዜ› ማለት ሲኾን ይኸውም ልዩ ልዩ አዝርዕት በቅለው፣ አድገው፣ አብበው ለፍሬ የሚደርሱበት፤ የሰው ልጅ፣ እንስሳትና አራዊትም ጭምር የዕፀዋቱን ፍሬ (እሸት) የሚመገቡበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚቀርቡ ምንባባትና ትምህርቶችም ይህንኑ ምሥጢር የሚዳስሱ ናቸው፡፡ በክፍል አንድ ዝግጅታችን እንደ ተመለከትነው ዕፀዋት በጥፍር የሚላጡ (ሎሚ፣ ሙዝ፣ ትርንጎ፣ ወዘተ)፤ በማጭድ የሚታጨዱ (ስንዴ፣ ጤፍ፣ ገብስ፣ ወዘተ)፤ በምሳር የሚቈረጡ (ወይራ፣ ዋርካ፣ ዋንዛ፣ ዝግባ፣ ወዘተ) በመባል በሦስት ይከፈላሉ፡፡

ተፈጥሯቸውም እንደ ሰው ልጅ ከአራቱ ባሕርያት ከነፋስ፣ እሳት፣ ውሃና አፈር (መሬት) ሲኾን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚያስተምሩት አራቱ ባሕርያት በዕፀዋት ሕይወት ላይ ለውጥ ሲያመጡ ይስተዋላል፤ ማለት ከነፋስ በመፈጠራቸው በነፋስ ያብባሉ፤ ያፈራሉ፡፡ ከእሳት በመፈጠራቸው አንዳንዶቹ እርስበርሳቸው ሲፋተጉ እሳት ያስገኛሉ፡፡ ከውሃ በመፈጠራቸውም ፈሳሽ ያወጣሉ፡፡ ከአፈር በመፈጠራቸው ደግሞ ሲቈረጡ በስብሰው ወደ አፈርነት ይቀየራሉ፡፡ ከፍሬ አያያዛቸው አኳያም በራሳቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ስንዴ፣ገብስ፣ ጤፍ፣ ወዘተ)፤ በጎድናቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ማሽላ፣ በቆሎ፣ ባቄላ፣ ወዘተ)፤ በውስጣቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ዱባ፣ ቅል፣ ወዘተ)፤ በሥራቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ሽንኩርት፣ ቀይ ሥር፣ ካሮት፣ ድንች፣ ወዘተ) ተብለው በአራት ይመደባሉ /ትርጓሜ ኦሪት ዘፍጥረት ፩፥፮-፲፫/፡፡

ቅዱሳት መጻሕፍት የሰው ልጆችን ሕይወት ከዕፀዋት ጋር በማነጻጸር ይገልጹታል፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ  በነፋስ ባሕርዩ ፍጥነት፤ በእሳት ባሕርዩ ቍጣ፤ በውሃ ባሕርዩ መረጋጋት፤ በመሬት ባሕርዩ ደግሞ ትዕግሥት ወይም ሞት እንደሚስማማው የሚያስተምር ንጽጽር ነው፡፡ በሌላ በኩል አዝርዕት ከበሰበሱ በኋላ ፍሬ እንደሚያስገኙ ኹሉ ሰውም ከሞተ በኋላ ተነሥቶ እንደ ሥራው መጠን ዋጋውን ይቀበላል፡፡ ይህንን ቅዱስ ጳውሎስ በሚከተለው መንገድ ገልጾታል፤ ‹‹… የሙታን ትንሣኤ ደግሞ እንዲሁ ነው፡፡ በመበስበስ ይዘራል፤ ባለመበስበስ ይነሣል፡፡ በውርደት ይዘራል፤ በክብር ይነሣል፡፡ በድካም ይዘራል፤ በኃይል ይነሣል፡፡ ፍጥረታዊ አካል ይዘራል፤ መንፈሳዊ አካል ይነሣል …›› /፩ቆሮ.፲፭፥፵፪-፵፬/፡፡

ዕፀዋት የሚሰጡት ፍሬ እንደየማፍራት ዓቅማቸው ይለያያል፤ ፍሬ የማያፈሩ፣ ጥቂት ፍሬ የሚያፈሩ፣ ብዙ ፍሬ የሚያፈሩ ዕፀዋት ይገኛሉ፡፡ እንደዚሁ ኹሉ ምእመናንም በክርስትና ሕይወታችን የሚኖረን በጎ ምግባር የአንዳችን ከአንዳችን ይለያል፡፡ ፍሬ የክርስቲያናዊ ምግባር እንደዚሁም የሰማያዊው ዋጋ ምሳሌ ነውና፡፡ በክርስትና ሕይወት ያለምንም በጎ ምግባር የምንኖር ኀጥአን ብዙዎች የመኾናችንን፤ እንደዚሁም ጥቂት በጎ ምግባር ያላቸው ምእመናን የመኖራቸውን ያህል በአንጻሩ ደግሞ በጽድቅ ላይ ጽድቅ፣ በመልካም ሥራ ላይ መልካም ሥራን የሚፈጽሙ፤ ከጽድቅ ሥራ ባሻገር በትሩፋት ተግባር ዘወትር ጸንተው የሚኖሩ አባቶችና እናቶችም ጥቂቶች አይደሉም፡፡

ይህንን ዓይነት የክርስቲያናዊ ሕይወት ልዩነት ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹በጥቂት የሚዘራ በጥቂት ደግሞ ያጭዳል፤ በበረከትም የሚዘራ በበረከት ደግሞ ያጭዳል … ለዘሪ ዘርን ለመብላትም እንጀራን በብዙ የሚሰጥ እርሱም የምትዘሩትን ዘር ይሰጣችኋል ያበረክትላችሁማል፤ የጽድቃችሁንም ፍሬ ያሳድጋል›› በማለት ይገልጸዋል /፪ቆሮ.፱፥፮-፲/፡፡ ገበሬ በዘራው መጠን ሰብሉን እንዲሰበስብ ‹‹ለኹሉም እንደየሥራው ዋጋውን ትከፍለዋለህ›› ተብሎ እንደ ተጻፈው ክርስቲያንም በሠራው መጠን ዋጋውን ያገኛልና በጸጋ ላይ ጸጋን፣ በበረከት ላይ በረከትን ከእግዚአብሔር ዘንድ ይጨመርልን ዘንድ ኹላችንም መልካም ሥራን በብዛት ልንፈጽም ይገባናል፡፡ ‹‹… እንግዲህ ወንድሞች ሆይ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ታገሡ። እነሆ ገበሬው የፊተኛውንና የኋለኛውን ዝናብ እስኪቀበል ድረስ እርሱን እየታገሠ የከበረውን የመሬት ፍሬ ይጠብቃል፡፡ እናንተ ደግሞ ታገሡ፤ ልባችሁንም አጽኑ፡፡ የጌታ መምጣት ቀርቦአልና›› እንዳለን ሐዋርያው /ያዕ.፭፥፯-፰/፡፡

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ‹‹ምድርኒ ወሀበት ፍሬሃ፤ ምድርም ፍሬዋን ሰጠች›› /መዝ.፷፮፥፮፤ ፹፬፥፲፪/ የሚለውን የዳዊት መዝሙርና ሌሎችንም ተመሳሳይ ኃይለ ቃላት ሲተረጕሙ ምድር በኢየሩሳሌም፣ በቤተ ክርስቲያን፣ በምእመናን፣ በእመቤታችን፤ ፍሬ ደግሞ በቃለ እግዚአብሔር (ሕግ)፣ በአምልኮተ እግዚአብሔር፣ እንደዚሁም በጌታችን በመድኂታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚመሰል ያስተምራሉ፡፡ በዚህ መሠረት ‹‹ምድርም ፍሬዋን ሰጠች (ትሰጣለች)›› በሚለው ኃይለ ቃል ምድር የተባለች ኢየሩሳሌም የዘሩባትን እንደምታበቅል፤ የተከሉባትን እንደምታጸድቅ፤ አንድም ይህቺ ዓለም ፍሬን፣ አምልኮተ እግዚአብሔርን እንደምታቀርብ፤ አንድም ቤተ ክርስቲያን ወይም ምእመናን እግዚአብሔርን ሲያመልኩ እንደሚኖሩ፤ ከዚሁ ኹሉ ጋርም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መወለዱን ያስረዳል፡፡ ለዚህም ነው በዘወትር ጸሎታችን ‹‹ቡርክት አንቲ እምአንስት ወቡሩክ ፍሬ ከርሥኪ፤ አንቺ ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ፤ የማኅፀንሽ ፍሬም የተባረከ ነው›› /ሉቃ.፩፥፳፰/ እያልን እመቤታችንንና ልጇን ኢየሱስ ክርስቶስን የምናመሰግነው፡፡

በቅዱስ ወንጌል ተጽፎ እንደምናገኘው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የክርስትና ሕይወትን ከዘርና ፍሬ ጋር በማመሳሰል አስተምሯል፡፡ ይኸውም አንድ ገበሬ ዘር ሲዘራ በመንገድ ዳር የወደቀው ዘር ከመብቀሉ በፊት በወፎች እንደ ተበላ፤ በጭንጫ ላይ የተጣለውም ወዲያውኑ ቢበቅልም ነገር ግን ጠንካራ ሥር ስለማይኖረው በፀሐይ ብርሃን እንደ ጠወለገ፤ በእሾኽ መካከል የወደቀው ደግሞ ሲበቅል በእሾኽ እንደ ታነቀ፤ ከኹሉም በተለየ መልኩ በመልካም መሬት ላይ የተጣለው ዘር ግን አድጎ መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ ፍሬ እንደ ሰጠ ያስረዳል፡፡ ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ እንደ ተረጐመላቸው በመንገድ ዳር የተዘራው ዘር የእግዚአብሔርን ቃል ሰምቶ የማያስተውል ክርስቲያን ምሳሌ ነው፤ ሙሉ እምነት ስለማይኖረው በመከራው ጊዜ አጋንንት ይነጥቁታልና፡፡ በጭንጫ ላይ የተዘራው ደግሞ ቃሉን ሰምቶ ወዲያው በደስታ የሚቀበል፣ ነገር ግን ተግባራዊ የማያደርግ ክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡ ይህ ምእመን በጠንካራ እምነት ላይ የጸና አይደለምና በሃይማኖቱ ምክንያት መከራ ወይም ስደት በደረሰበት ጊዜ ፈጥኖ ይሰናከላል፡፡ በእሾህ መካከል የተዘራውም ቃሉን የሚሰማ ነገር ግን በዚህ ዓለም ዐሳብና ባለጠግነት ተታሎ ቃሉን የማይተገብር ክርስቲያን  ምሳሌ ነው፡፡ በመልካም መሬት የተዘራው ደግሞ ቃሉን ሰምቶ የሚተገብር ክርስቲያን ምሳሌ፡፡

እንደዚህ ዓይነት ምእመን በተማረው ትምህርት ጸንቶ ይኖራል፤ መልካም ሥራም ይሠራል፡፡ በመልካም መሬት የተዘራው ዘር ስለ አንዱ ፋንታ መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ እንደሚያፈራ ኹሉ በክርስቲያናዊ ግብር ጸንቶ የሚኖር ምእመንም ሥራውን በሦስት መንገድ ማለትም በወጣኒነት፣ በማእከላዊነትና በፍጹምነት ደረጃ እንደሚወጣ፤ ዋጋውንም በሥራው መጠን እንደሚያገኝ ያስረዳል፡፡ አንድም ባለ መቶ ፍሬ የሰማዕታት፤ ባለ ስድሳ የመነኰሳት፤ ባለ ሠላሳ በሕግ ተወስነው በዓለም የሚኖሩ ምእመናን ምሳሌ ነው፡፡ በተመሳሳይ ምሥጢር ኹሉም የፍሬ መጠን በኹሉም ምእመናን ሕይወት ውስጥ እንደሚስተዋል ሊቃውንት ይተረጕማሉ፡፡ ስለዚህም በሰማዕትነትም፣ በምንኵስናም፣ በዓለማዊ ሕይወትም ውስጥ የሚኖሩ ምእመናን መልካም ግብራቸው እጅግ የበዛ ከኾነ በባለ መቶ ፍሬ፤ መካከለኛ ከኾነ በባለ ስድሳ፤ ከዚህ ዝቅ ያለ ከኾነ ደግሞ በባለ ሠላሳ ፍሬ ይመሰላል  /ትርጓሜ ወንጌለ ማቴዎስ፣ ማቴ.፲፫፥፩-፳፫/፡፡

ዕፀዋት ለመጠለያነት የማይጠቅሙ እንደዚሁም ለምግብነት ወይም ደግሞ ለመድኀኒትነትና ለሌላም ልዩ ልዩ አገልግሎት የሚጠቅም ፍሬ የማያስገኙ ከኾነ ተቈርጠው እንደሚጣሉ ኹሉ ምእመናንም ‹ክርስቲያን› ተብለን እየተጠራን ብቻ ያለምንም በጎ ምግባርና መንፈሳዊ ሕይወት የምንኖር ከኾነ በምድር መቅሠፍት፤ በሰማይም ገሃነመ እሳት እንደሚጠብቀንና ከእግዚአብሔር መንግሥት ውጪ እንደምንኾን ከወዲሁ በመረዳት በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን ልንኖር ያስፈልጋል፡፡ ‹‹… ምሳር በዛፎች ሥር ተቀምጧል፤ እንግዲህ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ኹሉ ይቈረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል›› ተብሎ ተጽፏልና /ማቴ.፫፥፲/፡፡

ከዚሁ ኹሉ ጋርም አዝርዕት ከበሰበሱ በኋላ በቅለው፣ አብበው በራሳቸው፣ በጎድናቸው፣ በውስጣቸውና በሥራቸው እንደሚያፈሩ ኹሉ ምእመናንም በራስ እንደ ማፍራት ፈሪሃ እግዚአብሔርን፤ በጎድን እንደ ማፍራት እርስበርስ መደጋገፍንና መተሳሰብን፤ በውስጥ እንደ ማፍራት ንጽሕናን፤ በሥር እንደ ማፍራት ትሕትናን ገንዘብ ማድረግን ከዕፀዋትና ከአዝርዕት መማር ይገባናል፡፡ እንደዚሁም ዕፀዋት ሠላሳ፣ ስድሳ፣ መቶና ከዚያ በላይ መልካም ፍሬ እንደሚያፈሩ ምእመናንም በመልካሟ መሬት በክርስትና የተዘራን የክርስቶስ ዘሮች መኾናችንን አስተውለን፣ ደግሞም ዘር የተባለውን የእግዚአብሔርን ቃል ተምረን መተግበር እንደሚገባን ተረድተን ከወጣኒነት ወደ ማእከላዊነት፤ ከማእከላዊነት ወደ ፍጹምነት በሚያደርስ የጽድቅ ሥራ በመኖር የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መፋጠን ይኖርብናል፡፡ ከሦስቱ በአንደኛው መደብ ውስጥ ወይም በኹሉም ደረጃዎች አልፈን ዘለዓለማዊ መንግሥቱን እንድንወርስ እግዚአብሔር አምላካችን ይርዳን፡፡

ይቆየን

ጼዴንያ

መስከረም ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዝግጅት ክፍሉ

maryam

በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ መስከረም ፲ ቀን ከሚዘከሩ በዓላት መካከል የእመቤታችን በዓል አንደኛው ሲኾን ይኸውም ጼዴንያ በምትባል አገር ከሥዕሏ ተአምር የተደረገበት ዕለት ነው፡፡ በተአምረ ማርያምና በመጽሐፈ ስንክሳር እንደ ተመዘገበው ቅዱስ ሉቃስ ከሣላት ሥጋ የለበሰች ከምትመስል የእመቤታችን የሥዕል ሠሌዳ ቅባት ይንጠፈጠፍ ነበር፡፡

እመቤታችን ድንግል ማርያምን የምትወድና በሚቻላትም ኹሉ የምታገለግላት፣ ቤቷንም ለእንግዳ ማደሪያ ያደረገች አንዲት ማርታ የምትባል ሴት ነበረች፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አባ ቴዎድሮስ የሚባሉ መነኵሴ ከእርሷ ዘንድ በእንግድነት አድረው በማግሥቱ ከቤቷ ሲወጡ ማርታ የሚሔዱበትን አገር በጠየቀቻቸው ጊዜ  እርሳቸውም ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው ቅዱሳት መካናትን እንደሚሳለሙ ነገሯት፡፡

ማርታም ከእርሷ ገንዘብ ወስደው የእመቤታችንን ሥዕል ገዝተው ይዘውላት እንዲመጡ ለመነቻቸው፡፡ መነኵሴውም በራሳቸው ገንዘብ ሥዕሉን ገዝተው እንደሚያመጡላት ቃል ገቡላት፡፡ አባ ቴዎድሮስ ኢየሩሳሌም ደርሰው ቅዱሳት መካናትን ከተሳለሙ በኋላ ሥዕሏን ሳይገዙ ወደ አገራቸው ተመለሱ፡፡ ያን ጊዜም ‹‹ሥዕል መግዛትን ለምን ረሳህ?›› የሚል የሚያስደነግጥ ቃልን ሰምተው ወደ ገበያ ተመልሰው መልኳ ያማረና የተወደደ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል ገዝተው በሐርና በንጹሕ ልብስ ጠቅልለው ይዘው እየተጓዙ ሳሉ ከሚያስፈራ ዱር ውስጥ ሲደርሱ ወንበዴዎች ተነሡባቸው፡፡ ሊሸሹ ሲሉም ‹‹መንገድህን ሒድ›› የሚል ቃል ከሥዕሏ ወጣ፤ መነኵሴውም መንገዳቸውን በሰላም ተጓዙ፡፡ ሁለተኛም አንበሳ ሊበላቸው በተነሣባቸው ጊዜ ከዚያች ሥዕል የሚያሥፈራ ድምፅ ወጥቶ አንበሳውን አባረረላቸው፡፡

አባ ቴዎድሮስ ይህን ኹሉ ድንቅ ተአምር ባዩ ጊዜም ያቺን ሥዕል ለማርታ ከመስጠት ይልቅ ወደ አገራቸው ሊወስዷት ወደዱ፡፡ በመርከብ ተሳፍረው በሌላ አቅጣጫ ሲሔዱም ታላቅ ነፋስ ተነሥቶ ወደ ማርታ አገር ወደ ጼዴንያ ወሰዳቸው፡፡ ከመርከብም ወርደው ከብዙ እንግዶች ጋር ወደዚያች መበለት ቤት ደረሱ፡፡ ነገር ግን ማንነታቸውን ለማርታ አልገለጡላትም፤ እርሷም አላወቀቻቸውም ነበር፡፡

በማግሥቱም ተሠውረው ወደ አገራቸው ሊሔዱ ሲሉ የቅፅሩ ደጃፍ ጠፍቶባቸው ሲፈልጉ ዋሉ፤ በመሸባቸው ጊዜም ወደ ማደሪያቸው ተመለሱ፡፡ ማታ ማታ በሩን ያዩታል፤ ነግቶ መሔድን ሲሹ ግን የበሩ መንገድ ይሠወርባቸዋል፡፡ እንዲህም ኾነው እስከ ሦስት ቀን ድረስ ቆዩ፡፡ ማርታም ‹‹አባቴ ሆይ አእምሮህ ተነክቷልን? ስትቅበዘበዝ አይሃለሁና ምን ኾነህ ነው?›› ሰትል ጠየቀቻችው፡፡ እርሳቸውም ከእመቤታችን ሥዕል የተደረገውን ተአምር ኹሉ ነገሯት፤ ራሳቸውንም ገለጡላትና ሥዕሏን ሰጧት፡፡ እርሷም የእመቤታችንን ሥዕል ተቀብላ የተጠቀለለችበትን ልብስ በፈታችው ጊዜ ወዝ ከሥዕሊቱ ሲንጠፈጠፍ አገኘች፡፡ ከደስታዋ ብዛት የተነሣም የአባ ቴዎድሮስን እጃቸውንና እግራቸውን ሳመች፡፡

ከዚህም በኋላ ያቺን ሥዕል ወደ ጸሎት ቤቷ ወስዳ በታላቅ ክብር አኖረቻት፡፡ ማንም እንዳይዳስሳትም የነሐስ መስኮትን ሠራችላት፡፡ በቀንና በሌሊትም የሚያበሩ መቅረዞችን በፊቷ ሰቀለች፤ ከመቅረዞች ውጭም የሐር መጋረጃን ጋረደች፡፡ ከሥዕሊቱ በታችም እየተንጠፈጠፈ የሚወርደው የወዝ ቅባት የሚጠራቀምበት ከዕብነ በረድ የተሠራ ወጭት አኖረች፡፡ እኒያ መነኰስም እስከሚሞቱበት ቀን ድረስ የእመቤታችን ድንግል ማርያምን ሥዕል እያገለገሉ ኖሩ፡፡

የአገሩ ሊቀ ጳጳስም የእመቤታችን ሥዕል ሥጋ የለበሰች ኹና ባገኙና ተአምሯንም በተመለከቱ ጊዜ ከዚህ አምላካዊ ግብር የተነሣ አደነቁ፡፡ ከሥዕሏ ከሚንጠባጠበው ቅባት ቀድተው ለበረከት ሲካፈሉም ወዲያውኑ በወጭቱ ውስጥ መላ፡፡ ሥዕሊቱን ወደ ሌላ ቦታም ሊወስዷት በፈለጉ ጊዜም ንውጽውጽታ ኾኖ ብዙዎች በድንጋጤ ወደቁ፡፡ ሥዕሊቱም እስከ ዛሬ ድረስ በዚያች አገር (በጼዴንያ) ትገኛለች፡፡

‹‹እግዚአብሔር በቅዱሳኑ ላይ ድንቅ ነው›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /መዝ.፷፯፥፴፭/ እግዚአብሔር አምላካችን በልዩ ልዩ መንገድ ለሰው ልጅ ተአምራቱን ይገልጣል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ተመዝግቦ እንደምናገኘው እግዚአብሔር ከዓለት ላይ ውኃ እያፈለቀ ሕዝቡን ያጠጣል፡፡ ከግዑዝ ዓለት ውስጥ ውኃ የሚያፈልቅ አምላክ ከሥጋዋ ሥጋ፤ ከነፍሷ ነፍስ ተዋሕዶ ካከበራት ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ወዝ እንዲፈስ ቢያደርግ ምን ይሳነዋል? እንደዚሁም ቅዱሳን ሐዋርያት በቃላቸውም፣ በልብሳቸውም፣ በጥላቸውም ሙታንን በማስነሣት፤ ሕሙማንን በመፈወስ ተአምራትን ያደርጉ ነበር፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ጴጥሮስ በጥላው፤ ቅዱስ ጳውሎስም በልብሱ ቅዳጅ ያደርጓቸው የነበሩ ተአምራትን መጥቀስ ይቻላል፡፡

ሐዋርያት ከእግዚአብሔር ዘንድ በተሰጣቸው ጸጋ በልብሳቸውና በሰውነታቸው ጥላ ተአምራትን ማድረግ እንደ ተቻላቸው ኹሉ አምላክን በማኅፀኗ የተሸከመችው ወላዲተ አምላክ ቅድስት ድንግል ማርያምም በሥዕሏ ወዝ ብዙ ሕሙማንን መፈወስ ይቻላታል፡፡ ከቅዱሳን ልብስና ጥላ የእርሷ ሥዕል ይከብራልና፡፡ ስለዚህም ነው በየዓመቱ መስከረም ፲ ቀን በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት የሚከበረው፡፡ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፤ የልጇ፣ የወዳጇ የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቸርነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በአዲስ ዓመት አዲስ ሕይወት

መስከረም ፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

እግዚአብሔር አምላካችን በዕድሜ ላይ ዕድሜን እየጨመረ፣ በየጊዜያቱ ዘመናትን እያፈራረቀ አዲስ ዓመትን ያመጣልናል፡፡ አሁንም በእርሱ ቸርነት ለ፳፻፱ ዓመተ ምሕረት ደርሰናል፡፡ ወንጌላዊው ዮሐንስ በራእዩ ‹‹እነሆ ኹሉን አዲስ አደርጋለሁ … አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፤ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፡፡ ባሕርም ወደ ፊት የለም›› በማለት እንደ ተናገረው /ራእ.፳፩፥፩-፭/ በየጊዜው ዘመን እያለፈ አዲስ ዘመን ይተካል፡፡ እኛም ዘመን በመጣ ቊጥር ‹‹እንኳን አደረሳችሁ!›› እንባባላለን፡፡ ስለ ትናንትና እንጂ ስለ ነገ ባናውቅም እስከ ዛሬ ድረስ በመቆየታችን እንደሰታለን፡፡

ነገን በጉጉት ለሚናፍቅ ሰው በእውነትም ዓመት አልፎ ዓመት ሲተካ በጣም ያስደስታል፡፡ ነገር ግን ያለፈውን ዓመት ስንዋሽ፣ ስንሰርቅ፣ ስንዘሙት፣ ስንጣላ፣ ስንተማማ፣ ስንደባደብ፣ ስንሰክር አሳልፈን ከኾነ ‹‹እንኳን አደረሳችሁ!›› የሚለው ቃል ርግማን ይኾንብናል፡፡ በመኾኑም ስለ ተለወጠው ዘመን ሳይኾን ስላልተቀየረው ሰብእናችን፤ ስላልተለወጠው ማንነታችን፤ ስላልታደሰው ሥጋችን ማሰብ ይኖርብናል፡፡ በኀጢአት እየኖሩ ዐውደ ዓመትን ማክበር ራስን ያለ ለውጥ እንዲቀጥል ማበረታት ነውና ከምንቀበለው ዘመን ይልቅ መጪውን ዘመን ለንስሐ ለማድረግ መዘጋጀት ይጠበቅብናል፡፡ ያሳለፍነውን የኀጢአት ጊዜ እያሰብን እስከ ዛሬ ድረስ የጠበቀንን እግዚአብሔርን እያመሰገንን ሕይወታችንን በጽድቅ ልናድስ ይገባናል፡፡ በንስሐ ባልታደሰ ሕይወታችን በዕድሜ ላይ ዕድሜ ቢጨመርልን ለእኛም ለዘመኑም አይበጅምና፡፡ ‹‹ባረጀ ልብስ አዲስ እራፊ የሚያኖር የለም፤ መጣፊያው ልብሱን ይቦጭቀዋልና፡፡ መቀደዱም የባሰ ይኾናል›› እንዳለ ጌታችን በወንጌል /ማቴ.፱፥፲፯/፡፡

ስለዚህም ያለፈውን ዓመት በምን ኹኔታ አሳለፍሁት? በመጭው ዓመትስ ምን ማድረግ ይጠበቅብኛል? ልንል ይገባል፡፡ ያለ ክርስቲያናዊ ምግባር እየኖርን ዘመንን ብቻ የምንቈጥር ከኾነ ሕይወታችንን ከሰብኣዊነት ክብር ብሎም ከክርስቲያናዊ ሕይወት በታች እናደርገዋለን፡፡ ራስን ከጊዜ ጋር ማወዳደር መቻል ክርስቲያናዊ ሓላፊነት ነው፡፡ ይኸውም ጊዜ ሳይቀድመኝ ልቅደመው ብሎ ማሰብ መቻል ነው፡፡ በአሮጌ ሕይወት ውስጥ ኾነን ዓመቱን አዲስ ከማለት ይልቅ ከኀጢአት ወደ ጽድቅ በመሸጋገር ራሳችንን በጽድቅ ሥራ ማደስ ይበልጣል፡፡

በመሠረቱ ዘመን ራሱን እየደገመ ይሔዳል እንጂ አዲስ ዓመት የለም፡፡ ሰዓታትም ዕለታትም እየተመላለሱ በድግግሞሽ ይመጣሉ እንጂ ከዚህ በፊት ያልነበረ ሰዓት ወይም ቀን ወይም ደግሞ ወር አለዚያም ዓመት የለም፡፡ ወርኀ መስከረምም ለብዙ ሺሕ ዓመታት ራሱን እየደገመ በየዓመቱ አዲስ ሲባል ይኖራል እንጂ ሌላ መስከረም የለም፡፡ ‹‹የኾነው ነገር እርሱ የሚኾን ነው፤ የተደረገውም ነገር እርሱ የሚደረግ ነው፡፡ ከፀሐይም በታች አዲስ ነገር የለም፡፡ ማንም ‹እነሆ ይህ ነገር አዲስ ነው› ይል ዘንድ ይችላልን? እርሱ ከእኛ በፊት በነበሩት ዘመናት ተደርጎአል›› እንዳለ ጠቢቡ ሰሎሞን /መክ.፩፥፱-፲/፡፡

ስለ ኾነም ምንም እንኳን ሕይወታቸውን በሙሉ በጽድቅ የሚያሳልፉ ወይም በንስሐ የሚኖሩ ብዙ ጻድቃን ቢገኙም ሰውነታችንን ጥለን የምንኖር ኀጥኣን ግን በኀጢአት ያሳለፍነውን ዘመን በማሰብ መጭውን ዘመን ለመልካም ሥነ ምግባር ልናውለው፤ አንድም ለንስሐ መግቢያ ልናደርገው ያስፈልጋል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት፤ በመዳራትና በሥጋ ምኞትም፣ በስካርም፣ በዘፈንም፣ ያለ ልክም በመጠጣት፣ ነውርም ባለበት፣ በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃል›› በማለት አስተምሮናልና /፩ኛጴጥ.፬፥፫/፡፡

ስለዚህም በዚህ አዲስ ዓመት ከክፉ ምግባር ኹሉ ተለይተን፣ ከዚህ በፊት በሠራነው ኀጢአታችን ንስሐ ገብተን ለወደፊቱ በጽድቅ ሥራ ኖረን እግዚአብሔርን ልናስደስት ይገባናል፡፡ ‹‹ይደልወነ ከመ ንግበር በዓለ ዐቢየ በኵሉ ንጽሕና እስመ ይእቲ ዕለት ቅድስት ወቡርክት፡፡ ወንርኀቅ እምኵሉ ምግባራት እኩያት፡፡ ወንወጥን ምግባራተ ሠናያተ ወሐዲሳተ በዘቦቶን ይሠምር እግዚአብሔር፤ አሁንም በፍጹም ንጽሕና ታላቅ በዓልን አድርገን ልናከብር ይገባናል፡፡ ይህቺ ዕለት ከሌሎች ዕለታት ተለይታ የተባረከች ናትና፡፡ ከክፉ ሥራዎችም ኹሉ ተለይተን እግዚአብሔር ደስ የሚሰኝባቸውን አዳዲስ የኾኑ በጎ ሥራዎችን እንሥራ›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /መጽሐፈ ስንክሳር፣ መስከረም ፩ ቀን/፡፡

ዘመን አዲስ የሚባለው እኛ ሰዎች (ክርስቲያኖች) ሕይወታችንን በጽድቅ ስናድስ ነው፡፡ ያለ መልካም ሥራ የሚመጣ ዓመት፤ ከክፉ ግብር ጋር የምንቀበለው ዘመን አዲስ ሊባልም፣ ሊኾንም አይችልም፡፡ የሰው ልጅ መንፈሳዊ ሕይወት በመልካም ሥራ ሲዳብር ግን መጭው ዘመን ብቻ ሳይኾን ያለፈውም አዲስ ነው፡፡ ለአዲስ ዓመት አዲስ ሕይወት እንደሚያስፈልግ በመረዳት ራሳችንን በንስሐ ሳሙና አሳጥበን በንጽሕና ልንኖር ያስፈልጋል፡፡ ‹‹ታጠቡ፤ ሰውነታችሁንም አንጹ፡፡ የሥራችሁን ክፋት ከዓይኔ ፊት አስወግዱ፡፡ ክፉ ማድረግን ተዉ፡፡ አንጽሑ ነፍሰክሙ ወነጽሩ ነፍስተክሙ፤ ልባችሁን አንጹ፤ ሰውነታችሁንም ንጹሕ አድርጉ›› ተብለን ታዝዘናልና /ኢሳ.፩፥፲፮፤ መጽሐፈ ኪዳን/፡፡

የተወደዳችሁ ምእመናን ‹‹ዐዘቅቱ ኹሉ ይሙላ፤ ተራራውና ኮረብታውም ኹሉ ዝቅ ይበል፡፡ ጠማማውም የቀና መንገድ ይኹን፡፡ ሸካራውም መንገድ ትክክል ይኹን፡፡ ሥጋም የለበሰ ኹሉ የእግዚአብሔርን ማዳን ይይ›› ተብሎ እንደ ተነገረው /ሉቃ.፫፥፫-፮/ በኑፋቄ የጎደጎደው ሰውነታችንን በቃለ እግዚአብሔር በመሙላት፤ በትዕቢት የደነደነውን ተራራውን ልቡናችንን በትሕትና በማስገዛት፤ በክፋት የተጣመመው አእምሯችንን በቅንነት በማስጓዝ፤ በኀጢአት የሻከረውን ልቡናችንን በንስሐ በማስተካከል አዲሱን ዓመት የመልካም ምግባር ዘመን እናድርገው፡፡ በተጨማሪም ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹እንግዲህ ያለ እርሾ እንዳላችሁ አዲሱን ሊጥ ትኾኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ አስወግዱ›› በማለት እንዳዘዘን /፩ኛቆሮ.፭፥፯/፣ በኀጢአት እርሾ የተበከለውን ሰውነታችንን በጽድቅ ሕይወት እናድሰው፡፡ በአዲሱ ዓመት በክርስቲያናዊ ምግባር መኖር ከቻልን ከጊዜ ጋር የሚጣጣም አዲስ ሕይወት ይኖረናል ማለት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

አዲሱን ዓመት አስመልክቶ ከቅዱስ ፓትርያርኩ የተሰጠ መግለጫ

ጳጕሜን ፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

005

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

ቃለ በረከት ዘእምኀበ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዘተናገረ በበዓለ ርእሰ ዐውደ ዓመት ዘዕሥራ ምእት ወተስዓቱ ዓመተ ምሕረት፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን ፡፡

  • በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣
  • ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤
  • የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
  • በሕመም ምክንያት በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤
  • እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

ዘመናትና ዓመታት የማይቆጠሩለት እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ከ2008 ዓ.ም ዘመነ ዮሐንስ ወደ 2009 ዓ.ም ዘመነ ማቴዎስ በሰላምና በጤና አደረሳችሁ ፡፡

‹‹ወእስምያ ለዓመተ እግዚአብሔር ኅሪተ፤ የተመረጠችውንና የተወደደችውን የእግዚአብሔር ዓመት እሰብክ ዘንድ ልኮኛል›› (ኢሳ.61፡2፤ ሉቃ.4፡19)፡፡

ሁላችንም እንደምናውቀው እንደ ሌላው ሁሉ ዓመትም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው፤ዓመት የጊዜ መለኪያ ነው፤ ጊዜም የሥራ መሣሪያ ነው፡፡

እግዚአብሔር ዓመታትን ለፍጡራኑ ሲሰጥ ለሥራ፣ ለኑሮ፣ ለምግብና ለጤና ወዘተ በሚመች አኳኋን በተለያዩ ሐውዘ አየራት ከፋፍሎና አመቻችቶ መስጠቱ ዓለም በእርሱ መግቦት የሚመራ መሆኑን ይበልጥ ያጎላዋል ፡፡

ከዚህም ጋር ጊዜያትን ለመለካት የሚያስችሉ መገብተ ብርሃን በጠፈረ ሰማይ ፈጥሮ ሰው በእነርሱ እየታገዘ ጊዜን በመለካት ለሥራውና ለኑሮው እንዲጠቀምባቸው አድርጎአል፡፡

ይህንንም በቅዱስ መጽሐፍ ‹‹እግዚአብሔርም ቀንና ሌሊትን ይለዩ ዘንድ ለምልክቶች፣ ለዘመናት፣ ለዕለታትና ለዓመታት መለያ ይሆኑ ዘንድ ብርሃናት በሰማይ ጠፈር ይሁኑ አለ›› በማለት በግልጽ አስቀምጦታል፤ /ዘፍ.1፡14/፡፡

ስለሆነም ሰው ቀንን በብርሃነ ፀሐይ፣ ወርን በብርሃነ ወርኅ፣ ወቅትን በብርሃነ ከዋክብት፣ ወዘተ. እየለካ ወቅቱን በመዋጀት ለእርሻ ተግባሩ ማለትም ለአዝርእቱ ለአትክልቱ፣ ለፍራፍሬው ምቹ ወቅት የትኛው እንደሆነ በመለየትና በማወቅ በግብርና ተግባር በሚገባ እንዲጠቀምባቸው አስችሎታል፡፡

በሌላም በኩል እግዚአብሔር ለአበው የሰጠው ተስፋ – ድኅነት ማለትም ዘመነ ሥጋዌ ወይም ዘመነ ክርስቶስ በዘመነ ቀመር ስሌት አሠራር መቼ እንደሚሆን ቅዱሳን ነቢያት በኁልቄ ዓመታት ሲቆጥሩ፣ ሲከታተሉና ሲጠብቁ እንደነበሩ በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ በብዙ ቦታ ተጽፎአል፤

በተለይም ነቢዩ ዳንኤል በደልና ኃጢአት የሚደመሰስበት ዘመነ ክርስቶስ ሊደርስ እርሱ ከነበረበት ዘመን አንሥቶ ሰባ ሱባዔ እንደቀረው በግልጽ ጽፎአል፤ በትንቢቱ መሠረትም ተፈጽሞአል፤ (ዳን.9፡24-27)፡፡

ቅዱስ ጳውሎስም ይህ ሱባዔ ሲፈጸም የሆነውን ነገር ሲገልጽ ‹‹የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ልጁን ላከ፤ ከሴትም ተወለደ ብሎአል፤›› /ገላ.4፡4/፡፡

ከዚያም አኳያ እግዚአብሔር ለማዳን ሥራ የመረጠው ወይም ለይቶ ያስቀመጠው ዓመት እንዳለ ከዚህ መገንዘብ ይቻላል፡፡ ይህም ዓመት ምርጥ የሆነ የእግዚአብሔር ዓመት ተብሎ ተገልጾአል፡፡

ቅዱሳን ነቢያት እግዚአብሔር በገለፀላቸው ምሥጢር መሠረት የተወደደው፣ የተመረጠውና ምሕረት እንደዝናም የሚዘንብበት የእግዚአብሔር ዓመት እርሱም ዘመነ ክርስቶስ እንደሚመጣ ብቻ ሳይሆን መቼ እንደሚመጣ ጭምር ዓመታቱን በትክክል እየቀመሩና እየቆጠሩ ሲናገሩና ሲያስተምሩ መኖራቸው የዘመናት ቁጥር በሃይማኖት ዘንድም የላቀ ተፈላጊነት እንዳለው ያመለክታል፡፡

እግዚአብሔር የተናገረውን የማያስቀር ታማኝ አምላክ ነውና የተቆጠሩት ዓመታት በደረሱ ጊዜ፣ የዛሬ ሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመት ልጁን ወደዚህ ዓለም በመላክ ዓለሙን ከፍዳ ኃጢአት ታደገው፡፡

በመሆኑም በተጠቀሰው ዘመን ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ መሥዋዕት ሆኖ የዓለምን ዕዳ – ኃጢአት በመሸከም የሰው ልጅን በምሕረቱ ስለተቀበለው ከልደተ ክርስቶስ ወዲህ ያለው ዘመን ምሕረት እግዚአብሔርን ለማሰብና ለማወጅ ሲባል ‹‹ዓመት ምሕረት›› ወይም እንደ ነቢዩ እንደ ኢሳይያስ አገላለጽ ‹‹የተመረጠ የእግዚአብሔር ዓመት›› ይባላል፡፡

እኛም ኢትዮጵያውያን በክርስቶስ አምላክነትና አዳኝነት ከመጀመሪያው ምእተ – ዓመት መጀመሪያ አንሥቶ ምሕረተ እግዚአብሔርን ገንዘብ ካደረጉ ሀገራት መካከል የመጀመሪያዎቹ ነንና ምሕረቱን ተቀብለን በዘመን አቆጣጠራችን ላይ ‹‹ዓመተ ምሕረት›› እያልን ምሕረተ እግዚአብሔርን ስናስታውስና ስናውጅ እንኖራለን፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናን ወምእመናት!

ዘመን የእግዚአብሔር ጸጋ እንደሆነ ቀደም ብሎ ከላይ ተገልጾአል፤ የእግዚአብሔር ጸጋ እንደመሆኑም መጠን በጥንቃቄና በአግባቡ ልንጠቀምበት ይገባል፤

እግዚአብሔር ዘመናትን፣ ዓመታትንና ወራትን የሚሰጠን ለሃይማኖት ማጽኛ፣ ለሥነ ምግባር ማበልፀጊያ፣ ለንሥሐ ማጎልብቻ ለዕድገት፣ ለብልፅግና፣ ለልማት፣ ለሰላም፣ ለፍቅር፣ ለአንድነትና ለስምምነት በአጠቃላይ የጎደለንን ለመሙላት ያጣነውን ለመተካት፤ የተስተካከለ መንፈሳዊና ሥጋዊ ሕይወት እንዲኖረን ለማስቻል እንደሆነ መገንዘብ አለብን፡፡

በመሁኑም ጊዜ ባለፈው አሮጌ ዘመን የጎደለብንን ሁሉ በአዲሱ ዘመን ለመሙላት እንድንችል በእግዚአብሔር የተሰጠን ልዩ ጸጋ ነውና በሥራ ልንጠቀምበት ይገባል፡፡

ሀገራችን ኢትዮጵያ ባለፉት ክፍለ ዘመናት ያመለጧት ብዙ ነገሮች እንዳሉ የሚታወቅ ነው፤ ይሁን እንጂ ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ቀድሞ ያመለጧትን ነገሮች ለመሙላት ከፍተኛ እንቅስቃሴ ላይ መገኘቷና በዚህም ያመጣችው ለውጥ በቀላሉ የሚታይ አይደለም፤

ይህም የእግዚአብሔር ጸጋ ነውና ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ኢታስትት ጸጋሁ ዘላዕሌከ፤ ከአንተ ያለውን የጸጋ ስጦታ ቸል አትበል›› እንዳለው የተሰጠንን ጸጋ – ልማት በጥቃቅን ነገሮች ልናደናቅፈው አይገባም፡፡

አሁን ባለንበት ዘመን የተገነዘብነው ዓቢይ ቁም ነገር ቢኖር ሰላም የልማት ቁልፍ መሣሪያ መሆኑን ነው፤ በሀገራችን እየፈነጠቀ ያለው የዕድገት ጮራ የሰላም ውጤት እንጂ የሌላ አይደለም፡፡

ከዓለም ተሞክሮ ልምድ ብንወስድም አሁን በከፍተኛ የዕድገት ጣራ ላይ የሚገኙ ሀገራት የልማታቸው ምሥጢር የሰላምና የአንድነት መረጋገጥ እንደሆነ ማስተዋሉ አይከብድም፡፡

ስለሆነም ያለ ሰላም ልማትና ዕድገት ፈጽሞ የሚታሰብ አይደለምና እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ለራሱ ልማት ሲል ለሰላም ጠበቃ መሆን አለበት፡፡

ባለፈው ዓመት ከዛሬ ሠላሳ አንድ ዓመታት በፊት ካጋጠመን ድርቅ ያልተናነሰ ከባድ ድርቅ ያጋጠመን ቢሆንም የሀገራችን ሕዝቦች ሰላማቸውንና አንድነታቸውን ጠብቀው ባስመዘገቡት ዕድገት ምክንያት ሀገራችን ችግሩን በራስዋ ዓቅም መቋቋም መቻሏ የሰላምና የአንድነት ጥቅም እንዲሁም እነርሱን ተከትሎ የተገኘው የዕድገት ጣዕም ምን ያህል እንደሆነ የተገነዘብንበት ዓመት ሆኖ አልፎአል፡፡

ስለሆነም አሁንም በተመረጠውና በተወደደው የእግዚአብሔር ዓመት ውስጥ ሆነን ዛሬ በምንጀምረው አዲስ ዓመት እግዚአብሔር ቸርነቱን አብዝቶልን የዝናሙ ስርጭትና የእህሉ ቡቃያ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢ ተስፋ ሰጪ ሆኖ ስለሚታይ፣ ሕዝቡ በዚህ ተነቃቅቶ ሰላሙንና አንድነቱን በመጠበቅ የበለጠ ልማትና ዕድገት ለማስመዝገብ ጠንክሮ እንዲሠራ፣ እንደዚሁም ከድህነተና ከሰላም እጦት የበለጠ ሌላ ጠላት እንደሌለው ሕዝቡ ተገንዝቦ በአዲሱ ዓመት አለመግባባትን በውይይት፣ ድህነትን በልማት ለማሸነፍ በሁሉም አቅጣጫ እንዲረባረብ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡ ዘመኑን የሰላም፣ የአንድነትና የልማት ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ፤

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

መስከረም 1 ቀን 2009

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ወርኀ ጳጕሜን አምስት፣ ስድስት፣ ሰባት

ጳጕሜን ፬ ቀን ፳፻፰ .

የኢትዮጵያን የዘመን አቈጣጠር ለየት ከሚያደርጉት ነገሮች አንዱ ‹ጳጕሜን› የምትባል 13ኛ ወር ስላለችን ነው፡፡ የቤት ኪራይና የወር ደመወዝ የማንከፍልባትና የማንቀበልባት፤ መብራትና ውኃ ግን ከነሐሴ ወር ጋር ጨምረው የሚያስከፍሉባት፤ ሲሻት አምስት፣ ሲያስፈልጋት ስድስት፣ ስትፈልግ ደግሞ ሰባት የምትኾን ወር ናት፡፡ ከዐሥራ ሁለቱ የኢትዮጵያ ወሮች መካከል ወርኀ ጳጕሜን በብዙ መንገድ የተለየች ናት፡፡

በአንድ በኩል በጣም ትንሿ ወር ናት፡፡ ሲቀጥልም ወርኃዊ በዓላት የማይውሉባት ወር ናት፡፡ ደግሞም ከሌሎች ወሮች በተለየ የቀኖቿ መጠን የሚቀያየሩ ብቸኛ ወር ናት፡፡ ከሌሎች የኢትዮጵያ ወሮች በተለየም ስሟ ኢትዮጵያዊ ያልኾነ ወር ናት፡፡ በሁለት ዘመናት መካከል እንደ መሸጋገሪያ የምትታይ ወርም ናት፡፡

‹ጳጕሜ› ማለት በግሪክ ቋንቋ ‹ጭማሪ› ማለት ሲኾን ዓመቱ በሠላሳ ቀናት ሲከፈል የሚተርፉት ዕለታት ተሰባስበው የሚያስገኟት ተጨማሪ ወር ናት፡፡ ወይም በየዕለቱ በፀሐይና በጨረቃ አቈጣጠር መካከል የሚፈጠሩት ልዩነቶች ተሰባስበው የተከማቹባት ወር ትባላለች፡፡

ዓመቱ በዐውደ ፀሐይ ሲለካ 365 ቀናት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ሲኾን፣ በጨረቃ ሲለካ ደግሞ 354 ቀናት ከ22 ኬክሮስ፣ ከ1 ካልዒት፣ ከ36 ሣልሲት፣ ከ52 ራብዒት፣ ከ48 ኀምሲት ነው፡፡ በሁለቱ አቈጣጠር መካከል (በፀሐይና በጨረቃ) በዓመት ውስጥ ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ7 ኬክሮስ ይኾናል፡፡

በዘመን አቈጣጠራችን ውስጥ ከዕለት በታች የምንቈጥርባቸው ስድስት መለኪያዎች አሉ፡፡ እነዚህም ኬክሮስ፣ ካልዒት፣ ሣልሲት፣ ራብዒት፣ ኀምሲትና ሳድሲት ናቸው፡፡ 60 ሳድሲት 1 ኀምሲት፣ 60 ኀምሲት 1 ራብዒት፣ 60 ራብዒት 1 ሣልሲት፣ 60 ሣልሲት 1 ካልዒት፣ 60 ካልዒት ደግሞ 1 ኬክሮስ ይኾናል፡፡ 60 ኬክሮስ ደግሞ 1 ዕለት፤ 1 ኬክሮስ 24 ደቂቃ ነው፡፡ ወርኀ ጳጕሜንን ለማግኘት የሚረዳንም የየዕለቱን ልዩነታቸውን መመልከቱ ነው፡፡

በየዕለቱ በጨረቃና በፀሐይ መካከል 1 ኬክሮስ ከ52 ካልዒት ከ31 ሣልሲት ይኾናል፡፡ ይህም ማለት 5 ሰዓት ከ48 ደቂቃ ከ46 ካልዒት (ሴኮንድ?) ነው፤ ይህ ልዩነት በአንድ ወር ምን ያህል እንደሚደርስ ለማወቅ በ30 ብናበዛው 30 ኬክሮስ ከ1560 ካልዒት፣ ከ930 ሣልሲት ይኾናል፡፡ የዓመቱን ለማግኘት ደግሞ በ12 ብናበዛው 360 ኬክሮስ ከ18720 ካልዒት፣ ከ11160 ሣልሲት ይመጣል፡፡

ቀደም ብለን 60 ኬክሮስ አንድ ዕለት ይኾናል ባልነው መሠረት 360 ኬክሮስ ለ60 ሲካፈል 6 ዕለታትን ይሰጠናል፡፡ 18720 ካልዒትን በስድሳ በማካፈል 312 ኬክሮስን እናገኛለን፡፡ ያም ማለት ትርፉን 12 ኬክሮስ ትተን 300ውን ኬክሮስ ለ60 በማካፈል 5 ዕለት እናገኛለን ማለት  ነው፡፡ ይኼም 5 ዕለት ከ12 ኬክሮስ ይኾናል፡፡ 11160 ሣልሲትን ለ60 ብናካፍለው 186 ካልዒት ወይም ደግሞ 3 ኬክሮስና 6 ካልዒት ይኾናል ማለት ነው፡፡

ከላይ ኬክሮስን በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነው 6 ዕለት ሕጸጽ ይባላል፡፡ ፀሐይና ጨረቃን እኩል መስከረም አንድ ላይ ዓመቱን ብናስጀምራቸው ፀሐይ የወሯ መጠን ምንጊዜም 30 ሲሆን ጨረቃ ግን በአንደኛው ወር 29 በሌላኛው ወር ደግሞ 30 ስለምትኾን ዓመቱ እኩል አያልቅም፤ የጨረቃ ዓመት የሚያልቀው ነሐሴ 24 ቀን ነው፡፡ ይህም ማለት ጨረቃ በሁለት ወር አንድ ጕድለት ታመጣለች ማለት ነው፡፡

ይህንን ነው ሊቃውንቱ ሕጸጽ (ጕድለት) ያሉት፡፡ በዚህም መሠረት ከላይ ኬክሮሱን በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነውን 6 ዕለት ለጨረቃ ሕጸጽ ስንሰጠው የመስከረም /ጥቅምት 1፣ የጥቅምት /ኅዳር 2፣ የጥር /የካቲት 3፣ የመጋቢት /ሚያዝያ 4፣ የግንቦት /ሰኔ 5፣ የሐምሌ /ነሐሴ 6 ኾነው ተካፍለው ያልቃሉ፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ በጨረቃና በፀሐይ ዑደት መካከል በዓመት ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ይኾናል፡፡ ስድስቱን ዕለታት ጨረቃ ለምታጋድልበት ሕጸጽ ብንሰጠው ቀሪ 5 ዕለት ይኖረናል፡፡ ወርኀ ጳጕሜን ማለት እነዚህ 5 ቀናት ናቸው፡፡

አሁን የዐሥራ አንዱን ዕለታት ከፈጸምን ሽርፍራፊዎቹን (15 ኬክሮስና 6 ካልዒት) እንመልከት፤
ከላይ እንደ ተመለከትነው በፀሐይና ጨረቃ ዓመታት መካከል የተፈጠሩትን 11 ቀናት ስድስቱ ለሕጸጽ ማሟያ ሲገቡ የቀሩት 5 ዕለታት ናቸው ጳጕሜን የምትባለውን ወር ያስገኟት፡፡

በጎርጎርዮሳውያኑ አቈጣጠር እነዚህ 5ቱ ዕለታት በጃንዋሪ፣ ማርች፣ ሜይ፣ ጁላይና ኦገስት ላይ ስለ ተጨመሩ ወሮቹ 31 ሊኾኑ ችለዋል፡፡ ይህንን የከፈለው በ46 ቅልክ የነበረው ዩልየስ ቄሣር ነው፡፡ ለአራቱ ወሮች 30 ቀን፣ ለአንዱ 28/29 (በየአራት ዓመቱ)፣ ለቀሩት ሰባት ወሮች ደግሞ 31 ቀን ሰጥቷቸዋል፤ ለአምስቱ ወሮች 31 ያደረጋቸው ከጳጕሜን ወስዶ ሲኾን ለሁለቱ ወሮች አንዳንድ ቀን የጨመረላቸው ደግሞ ከፌቡርዋሪ 2 ቀናት ወስዶ ወሩን 28 በማድረግ ነው፡፡

ከእንግዲህ የሚተርፉት ከላይ የየዕለቱን ልዩነት በዓመት ስናባዛ የቀሩት 15 ኬክሮስና 6 ካልዒት ናቸው፡፡ ሁለቱን ከላይ ያየናቸውን ስንደምራቸው (12 ኬክሮስ + 3 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት) 15 ኬክሮስ ከ 6 ካልዒት ይመጣሉ፡፡ 1 ዕለት 60 ኬክሮስ በመኾኑ 1 ዕለትን (60 ኬክሮስን) ለማግኘት ከላይ ያገኘነውን 15 ኬክሮስ በ4 ማባዛት ይኖርብናል፡፡

በአራት ዓመት አንድ ጊዜ ጳጕሜን 6 ቀን የምትኾነውም እነዚህ በየዓመቱ የተሰባሰቡ 15 ኬክሮሶች አንድ ላይ መጥተው በአራት ዓመት አንድ ጊዜ አንድ ዕለት ስለሚኾኑ ነው፡፡ እርሷም ሠግር (leap year) ትባላለች፡፡ ጎርጎርዮሳውያኑ ይህቺን ሠግር በፌቡርዋሪ ወር ላይ ጨምረው ወሩን በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ 29 ቀን ያደርጉታል፡፡

15ቱ ኬክሮስ በአራት ዓመት ተደምረው አንድ ዕለት መጡና በአራት ዓመት አንድ ጳጕሜን ስድስት ቀን እንድትኾን አድርገዋታል፡፡ የቀረችው 6 ካልዒትስ የት ትግባ? ከተባለ ካልዒት አንዲት ዕለት ትኾን ዘንድ 3600 ካልዒት ያስፈልጋሉ፡፡ ይህንን ያህል ካልዒት ለማግኘት 600 ዓመታት ያስፈልጉናል፡፡ ለዚህ ነው ጳጕሜን በየስድስት መቶ ዓመታት ሰባት የምትኾነው፡፡

ጳጕሜን 5 ቀን በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ዘንድ ‹ዕለተ ምርያ› ወይም ‹የተመረጠች ቀን› ትባላለች፡፡ ሊቃውንቱ የጌታችንን ልደት ሲያሰሉባት የቆየችው ዕለት በመኾኗ ነው ይህንን ስያሜ ያገኘችው፡፡ የጌታችንን ልደት ቀን የምትወስነው የጳጕሜን 5ኛዋ ቀን ናት፡፡ በዓለ ልደት የሚውለውም ጳጕሜን 5 በዋለበት ቀን ነው፡፡

ለምሳሌ ዘንድሮ (በ2008 ዓ.ም) ጳጕሜን 5 ቀን ቅዳሜ ነው የምትውለው፤ ስለዚህም በ2009 ዓ.ም በዓለ ልደት የሚውለው ቅዳሜ ነው ማለት ነው፡፡ በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ ጳጕሜን 6 ቀን ስትኾን ልደት በ28 የሚከበረው በዓለ ልደት ጳጕሜን 5 ቀንን (ዕለተ ምርያን) ስለማይለቅ ነው፡፡

በዘመነ ዮሐንስ ግን ስድስተኛዋ የጳጕሜን ቀን በዓለ ልደትን በአንድ ቀን ዝቅ ብሎ እንዲከበር ስለምታደርገው ልደትን ታኅሣሥ 28 ቀን እናከብራለን፡፡ ታድያ ምነው ጥምቀት፣ ግዝረትና ሌሎችም በዓላት አይለወጡም? ቢሉ ሊቃውንቱ የሚሰጡት ምላሽ ‹‹ትውልድ ሱባዔ እየቈጠረ በተስፋ የጠበቃት ዕለተ ልደትን ስለ ኾነ ነው፤ ሌሎቹ በዓላትም የመጡት በልደቱ ምክንያት ነው›› የሚል ነው፡፡

በጎርጎርዮሳውያንም ቢኾን በአራት ዓመት አንድ ጊዜ በዓለ ልደት ዝቅ ብሎ ይከበራል፡፡ የእነርሱ የማይታወቀው ጭማሪዋ ፌብርዋሪ ላይ ስለ ኾነች ነው፡፡ ያ ደግሞ አዲሱን ዓመት ካከበሩ በኋላ ስለሚመጣ ነው፡፡ የእኛ ግን የምትወድቀው ጳጕሜን መጨረሻ ላይ በመኾኗና ከአዲስ ዓመት በፊት ስለምትጨመር ቍጥሯ ጐልቶ ይታወቃል፡፡

እንግዲህ ጳጕሜን የምትባለው አስገራሚዋና ትንሿ ወራችን እንዲህ በስሌት የተሞላች፣ በሦስት ዓመታት አምስት ቀን ኾና ቆይታ በአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ ስድስት፣ በየስድስት መቶ ዓመት ደግሞ ሰባት ቀን የምትኾን ወር ናት፡፡ እንደዚሁም ታላላቆቹ ወሮች ምንም ሳይፈጥሩ የልደትን ቀን የምትወስን፣ የዓመቱን ሠግር የምታመጣ፣ ታሪከኛ ወር ናት፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡- የዲያቆን ዳንኤል ክብረት ገጽ፣ ፳፻፮ ዓ.ም (ከመጠነኛ ማስተካከያ ጋር)፡፡

 

ዘመነ ክረምት ክፍል አራት

ጳጕሜን ፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በክፍል ሦስት ዝግጅታችን ከነሐሴ ፲ እስከ ፳፰ ቀን (ከማኅበር እስከ አብርሃም) ድረስ ያለው የዘመነ ክረምት ክፍለ ጊዜ ‹‹ዕጕለ ቋዓት፣ ደሰያት፣ ዓይነ ኲሉ›› እንደሚባል፤ ይኸውም የሰውን ልጅ ጨምሮ የሰማይ አዕዋፍ፣ የምድር አራዊትና እንስሳት ሳይቀሩ እግዚአብሔርን ተስፋ አድርገው በደስታ መኖራቸው፤ በተጨማሪም በዝናም አማካይነት በዙሪያቸው ያለው የውሃ መጠን ከፍ ሲልላቸው ደሴቶች ኹሉ በልምላሜ ማሸብረቃቸው የሚነገርበት ክፍለ ክረምት እንደ ኾነ በማስታዎስ ከሕይወታችን ጋር የሚጣጣም ትምህርት አቅርበን ነበር፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ቀጣዩን ክፍል ይዘን ቀርበናል፡፡

ከዚያ በፊት ግን ባለፈው ከጠቀስናቸው ትምህርቶች መካከል ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ …›› /ሉቃ.፲፪፥፳፪-፴፩/ የሚለው ኃይለ ቃል እንደ እንስሳት ሳትሠሩ እግዚአብሔር ምግብ እንዲሰጣችሁ ለምኑት ማለት ነውን? የሚል ጥያቄ ሊያስነሣ ስለሚችል በመጠኑ ክለሳ አድርገንበት እንለፍ፤ ኃይለ ቃሉን ለማብራራት ያህል የሰው ልጆች ከእንስሳት ከምንለይባቸው ባሕርያት አንደኛው ሠርተን መብላት መቻላችን ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም የታታሪነትንና የሠርቶ ማደርን ጥቅም እንጂ ሳይሠሩ ተቀምጦ መብላትን አላስተማሩንም፡፡ በብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች የሰው ልጅ እጁ ከሥራ መለየት እንደማይገባው ተጠቅሷል፡፡ ለምሳሌም ጥቂቶቹን እንመልከት፤

በኦሪት ዘፍጥረት እንደ ተጻፈው አባታችን አዳም ከሳተ በኋላ በምድር ጥሮ፣ ግሮ እንዲኖር ተፈርዶበታል፡፡ ይህንንም ‹‹… የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ፡፡ ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ›› ከሚለው ኃይለ ቃል ለመረዳት እንችላለን /ዘፍ.፫፥፲፰-፲፱/፡፡ በተመሳሳይ መልኩ እግዚአብሔር አማላክ አዳምን ከዔደን ገነት ያስወጣው የተገኘባትን መሬት ያርስ ዘንድ ነው /ዘፍ.፫፥፳፫/፡፡ ይህም የሰው ልጅ ሠራቶ አዳሪ ፍጥረት መኾኑን የሚያመላክት ነው፡፡

ጠቢቡ ሰሎሞንም ‹‹አንተ ታካች! እስከ መቼ ትተኛለህ? ከእንቅልፍህስ መቼ ትነሣለህ? ጥቂት ትተኛለህ፤ ጥቂት ታንቀላፋለህ፡፡ ትተኛም ዘንድ ጥቂት እጅህን ታጥፋለህ፡፡ እንግዲህ ድህነትህ እንደ ወንበዴ፣ ችጋርህም ሰይፍ እንደ ታጠቀ ሰው ይመጣብሃል›› በማለት ሰው ሰነፍ ከኾነ (ካልሠራ) ክፉ ድህነት እንደሚመጣበት ተናግሯል /ምሳ.፮፥፱-፲/፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ ‹‹ከእናንተ ሊሠራ የማይወድ አይብላ›› በማለት ሥራ የማይወድ ሰው ምግብ መሻት እንደሌለበት አስረድቷል /፪ኛተሰ.፫፥፲/፡፡

ታዲያ መጽሐፍ ቅዱስ ስንፍናን የሚያወግዝ፣ ሥራን የሚያበረታታ ኾኖ ሳለ ለምንድን ነው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፡፡ …›› ሲል ያስተማረው ለሚለው የሰው ልጅ ሠራተኛ ፍጥረት ቢኾንም ዝናም አልጥልለት ሲል፤ የዘራበት መሬት ሳያበቅል ሲቀር፤ የወር ደመወዙ ሲዘገይ፤ እኽል የሚሸምትበት ገንዘብ ሲያጣ፤ ወዘተ. በመሳሰሉት ፈተናዎች ውስጥ በኾነ ጊዜ ምን ልበላ፣ ልጠጣ ነው? ልጆቼ እንዴት ሊኾኑብኝ ነው? ዛሬን እንዴት ላልፍ ነው? በሚሉትና በመሳሰሉት የጭንቀትና የተስፋ መቍረጥ ስሜቶች ሳይያዝ የዕለት ጕርሱን፣ የዓመት ልብሱን ይሰጠው ዘንድ የጠፋውን ዝናም ማምጣት፤ የደረቀውን ዘር ማለምለም፤ ባዶ የኾነውን ቤት መሙላት የሚቻለውን እግዚአብሔርን በእምነት ኾኖ በጸሎት ይጠይቀው ለማለት ነው፡፡

ሲጠቃለል የሰው ልጅ ይርበኛል፣ ይጠማኛል ማለቱን ትቶ በእግዚአብሔር አምሳል መፈጠሩን በማሰብ ዓቅሙ በሚችለው ኹሉ እንዲሠራ፤ የጐደለውን እንዲሞላለት ደግሞ ጸሎቱን ወደ ፈጣሪው እንዲያቀርብ ሲያስረዳ ጌታችን ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት፣ ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፡፡ …›› ብሏል፡፡ ስላለፈው ትምህርት ይህንን ያህል ከገለጽን ወደ ዛሬው ዝግጅታችን እናልፋለን፤

በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ከነሐሴ ፳፰ እስከ መስከረም ፩ ቀን (ከአብርሃም እስከ ዮሐንስ) ድረስ ያለው ክፍለ ክረምት ‹‹ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን መዓልት›› ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ክረምት ውስጥ ባሉት ቀናት በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እነዚህን ፍጥረታት የሚመለከቱ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎች ይነገራሉ፤ ይተረጐማሉ፤ ይመሠጠራሉ፡፡

‹‹ጎሕ፣ ነግሕና ጽባሕ›› ንጋት፣ ማለዳ፣ ሌሊቱ ወደ ቀን፤ ጨለማው ወደ ብርሃን የሚሸጋገርበት ክፍለ ጊዜ የሚል ትርጕም አላቸው፡፡ ብርሃን ደግሞ የጨለማ ተቃራኒ፣ የፀሐይ ብርሃን የማይታይበት ክፍለ ዕለት ሲኾን ‹‹ዕለት›› ማለትም በአንድ በኩል የፀሐይ ብርሃን የሚታይበት ጊዜን፣ በሌላ በኩል ደግሞ ከእሑድ እስከ ሰኞ ያሉትን፣ እንደዚሁም ከ፩-፴ የሚገኙ ዕለታትንም ያመላክታል /ዘፍ.፩፥፭-፴፩/፡፡ በአጠቃላይ ‹‹ጎሕ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን፣ መዓልት›› ኹሉም የግእዝ ቃላት ሲኾኑ ተመሳሳይ ትርጕምና ጠባይዕ ያላቸው ፍጥረታት ናቸው፡፡

ስለ ንጋትና ብርሃን ለመናገር በመጀመሪያ ስለ ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት አፈጣጠር ማስታዎስ ያስፈልጋል፡፡ ይኸውም እግዚአብሔር አምላክ በዕለተ ረቡዕ በመጀመሪያው ሰዓተ ሌሊት ‹‹ለይኩን ብርሃን፤ ብርሃን ይኹን›› ባለ ጊዜ ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት ተፈጥረዋል፡፡ የፀሐይ ተፈጥሮዋ ከእሳትና ከነፋስ ሲኾን ጨረቃንና ከዋክብትን ደግሞ ከነፋስና ከውኀ አርግቶ ፈጥሯቸዋል፡፡ ሲፈጥራቸውም ከኹሉም ፀሐይን፤ ከከዋክብት ደግሞ ጨረቃን አስበልጦ ፈጥሯቸዋል፡፡ የፈጠራቸውም እጠቀምባቸዋለሁ ብሎ ሳይኾን ለሰው ልጅና በዚህ ዓለም ለሚገኙ ፍጥረታት እንዲያበሩ ነው፡፡

እነዚህ የብርሃን ምንጮች ልዩ ልዩ ምሳሌያት አሏቸው፤ ጻድቃን ኹልጊዜ በምግባር በሃይማኖት ምሉዓን በመኾናቸው በፀሐይ፤ ኀጥኣን ደግሞ አንድ ጊዜ ሙሉ፣ ሌላ ጊዜ ጐደሎ እየኾኑ ይኖራሉና በጨረቃ ይመሰላሉ፡፡ አካሔዳው በሰማይና በምድር መካከል መኾኑ ምእመናን ጻድቃን በተፈጥሯቸው ምድራውያን ኾነው ሳሉ ሰማያዊውን መንግሥት የመውረሳቸው ምሳሌ ነው፡፡ ሰሌዳቸው ከነፋስ፣ ከእሳትና ከውኀ መኾኑ የመመህራን መንፈሳዊ ቍጣ ምሳሌ ነው፡፡ አንድም እሳት የመለኮት፤ ውኀ የትስብእት፤ ነፋስ የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ነው /ሥነ ፍጥረት አንድምታ ትርጓሜ/፡፡

በሌላ ምሥጢር ስንመለከታቸው ‹‹ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን መዓልት›› ወይም ኹሉንም በአጠቃላይ በብርሃን ምንጭነት ወይም በብርሃን ብንሰይማቸው ብርሃን እግዚአብሔር ነው፡፡ እርሱ በጨለማው ዓለም፤ በጨለማው ሕይወታችን፤ በጨለማው ኑሯችን የሕይወትን ወጋገን፣ ንጋት፣ ቀን የሚያወጣ አምላክ ነውና /ዮሐ.፩፥፭-፲/፡፡ ስለዚህ ‹‹እግዚአብሔር ብርሃኔና መድኀኒቴ ነው፤ የሚያስፈራኝ ማነው?›› በማለት በብርሃን በተባለ በእግዚአብሔር መታመን ያስፈልገናል /መዝ.፳፮፥፩/፡፡ ዳግመኛም የእግዚአብሔር ሕግ ብርሃን ይባላል፡፡ ብርሃን ጨለማን እንደሚያስወግድ ኹሉ የእግዚአብሔር ሕግም ከኀጢአት ባርነት፣ ከሲኦል እሳት ያድናልና፡፡ ‹‹ሕግህ ለእግሬ መብራት፤ ለመንገዴም ብርሃን ነው›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት /መዝ.፻፲፰፥፻፭/፡፡

እንደዚሁም ብርሃን ክርስቲያናዊ ምግባርን ያመለክታል፡፡ ብርሃን ለራሱ በርቶ ለሌሎችም እንዲያበራ ክርስቲያናዊ ምግባርም ከራስ ተርፎ ለሰዎች ኹሉ ደምቆ ይታያልና /ዮሐ.፲፪፥፴፮፤ ፩ኛ ዮሐ.፩፥፯/፡፡ እኛም ‹‹ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ›› ተብሎ እንደ ተጻፈ የጽድቅ ሥራ የማይገኝበት ጊዜ የጨለማ ዘመን ከመምጣቱ በፊት የጽድቅ ሥራ መሥራት በምንችልበት ጊዜ ኹሉ በመልካም ምግባር ጸንተን እንኑር፡፡

ደግሞም መልካም ግብር ያላቸው ምእመናን ብርሃን ተብለው ይጠራሉ፤ ብርሃን በግልጽ ለሰዉ ኹሉ እንደሚታይና እንደሚያበራ መልካም ምግባር ያላቸው ምእመናንም በጽድቅ ሥራቸው ለብዙዎች አርአያ፣ ምሳሌ ይኾናሉና፡፡ ‹‹እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፡፡ በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሠወር አይቻላትም›› እንዳለ ጌታችን በወንጌል /ማቴ.፭፥፲፬/፡፡ እንግዲህ ኹላችንም በጨለማ ከሚመሰለው ኀጢአት ወጥተን ወደ ጽድቅ ሕይወት እንመለስና እኛም በርተን ለሌችም ብርሃን እንኹን፡፡ አምላካችን ከኀጢአት ተለይተን፣ ንስሐ ገብተን እንደ ጻድቃኑ ‹‹የዓለም ብርሃን›› ለመባል የበቃን ያድርገን፡፡

በአጠቃላይ ይህ ወቅት ‹‹ቡሄ ካለፈ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት›› እንደሚባለው ክረምቱ እየቀለለ፤ ዝናሙ እያባራ፤ ማዕበሉ እየቀነሰ፤ ሰማዩ እየጠራ የሚሔድበት የንጋት፣ የወጋገን፣ የብርሃን ጊዜ ነው፡፡ ልክ እንደ ዘመኑ እኛም በልባችን የቋተርነውን የቂም ደመና፤ በአእምሯችን የሣልነውን የክፋት ጨለማ፤ በወገን ላይ ያደረስነውን የዝናምና ማዕበል አድማ በንስሐ ፀሐይ አስወግደን ወደ ብርሃኑ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ፤ ወደ ብርሃኑ ሕገ እግዚአብሔር፤ ወደ ብርሃኑ ምግባረ ሠናይና ወደ ብርሃኑ ክርስትና እንድንመለስ ልዑል እግዚአብሔር ‹‹በሕይወታችሁ ውስጥ ብርሃን ይኹን›› ይበለን፡፡ እርሱ ‹‹ብርሃን ይኹን›› ካለ የኀጢአት ጨለማ በእኛ ላይ ለመሠልጠን የሚችልበት ዓቅም አያገኝምና፡፡

ከአራተኛው ክፍለ ክረምት (ከጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃንና መዓልት) ቀጥሎ የሚገኘው አምስተኛው ክፍል ደግሞ ከመስከረም ፩-፰ ቀን (ከዮሐንስ እስከ ዘካርያስ) ያለው ጊዜ ሲኾን ይኸውም ‹‹ዮሐንስ›› በመባል ይታወቃል፡፡ ይህ ክፍለ ጊዜ የዓዋጅ ነጋሪው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ትምህርት፣ ጥምቀት፣ ምስክርነት፣ አገልግሎት፣ ዜና ሕይወት፣ ክብር፣ ቅድስና፣ ገድልና ዕረፍት፣ እንደዚሁም ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለማጥመቅ መመረጡ ከአዲሱ ዓመት ጋር እየተጣጣመ በስፋት የሚዳሰስበት የብሥራት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ሳምንት የቅዱስ ዮሐንስን አገልግሎት የሚመለከቱ ትምህርቶች በቤተ ክርስቲያን በስፋት ይቀርባሉ፡፡ የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በረከት በኹላችን ላይ ይደር፡፡

ይቆየን፡፡