‹‹ያለ ደግ ልጆች ያላስቀረን እግዚአብሔር ይመስገን!›› ብፁዕ አቡነ ሉቃስ

ሐምሌ ፳ ቀን፣ ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

abunu 1209

ይህ ‹‹ያለ ደግ ልጆች ያላስቀረን እግዚአብሔር ይመስገን!›› የሚለው ኃይለ ቃል ከብፁዕ አቡነ ሉቃስ ቃለ ምዕዳን የተወሰደ ሲኾን፣ ይኸውም ማኅበረ ቅዱሳን በጀት በመመደብና ምእመናንን በማስተባበር ለገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ያደረገውን ድጋፍና ያመጣውን ውጤት ለቤተ ክርስቲያን አባቶችና ለበጎ አድራጊ ምእመናን ለማሳወቅ ሐምሌ ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በግዮን ሆቴል በንግሥት ሳባ አዳራሽ ባዘጋጀው ልዩ መርሐ ግብር የተናገሩት ነው፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ፣ የሰሜን ሱዳንና የግብጽ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የትንሣኤ ዘጉባኤ ማሳተሚያ ድርጅት የበላይ ሓላፊ፤ የዐሥር ገዳማት አበ ምኔቶችና እመ ምኔቶች፤ የአብነት መምህራንና ደቀ መዛሙርት፤ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚዎችና የልዩ ልዩ ክፍሎች አገልጋዮች፤ በጎ አድራጊ ምእመናንና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡

2S0A7158 - Copy

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ በዕለቱ ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ “ጸግወኒ እግዚኦ ውሉደ ቡሩካነ ወኄራነ እለ ይትኤዘዙ ለከ፤ አቤቱ ለአንተ የሚታዘዙ፣ የተባረኩ፣ ቸር የኾኑ ልጆችን ስጠኝ፤” የሚል ኃይለ ቃል ጠቅሰው “ያለ ልጆች ያላስቀረን፤ ታዛዥና ቤተ ክርስቲያንን የሚያገለግሉ ልጆችን የሰጠን እግዚአብሔር አምላክ የተመሰገነ ይኹን!” በማለት በየገዳማቱ በጾም በጸሎት ተወስነው፣ በሥራ ተጠምደው የሚኖሩ አባቶች መነኮሳትንና መነኮሳይያትን፤ ለገዳማትና ለአብነት ት/ቤቶች መስፋፋት ልዩ ልዩ ድጋፍ በማድረግ ላይ የሚገኙ ምእመናንንና ይህንን አገልግሎት የሚያስተባብረውን ማኅበረ ቅዱሳንን አመስግነዋል፡፡

 

መርሐ ግብሩ በብፁዕነታቸው ጸሎት ከተከፈተ በኋላ በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል መዘምራንና በመምህር ወልደ ገብርኤል ይታይ ወቅታዊ ይዘት ያላቸው ያሬዳውያን ዝማሬያት ቀርበዋል፡፡

 

ዲያቆን ብርሃኑ አድማስም “ንገሩ” በሚል ኃይለ ቃል የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮና ታሪክ፤ የቅዱሳት መካናትን ጠቀሜታና አስተዋጽኦ፤ እንደዚሁም ያሉባቸውን ችግሮች ለሌሎች በማስረዳት ቤተ ክርስቲያናችንን ከልዩ ልዩ ችግር ነጻ ማድረግና የገዳማትንና የአብነት ትምህርት ቤቶችን ህልውና ማስጠበቅ እንደሚገባ የሚያስገነዝብ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ‹ምርጥ ተሞክሮ› በሚል ርእስ ያሳተመው፤ ልዩ ልዩ ጉዳዮችን የሚዳስሰው የኤሌክትሮኒክስ ጋዜጣም በብፁዕ አቡነ ሉቃስ ቡራኬ ተመርቋል፡፡

Abun 229

ከዐሥሩ ገዳማት ከመጡ አበ ምኔቶችና እመ ምኔቶች መካከልም ከፊሎቹ ስለየገዳሞቻቸው ኹኔታና አገልግሎት እንደዚሁም ስለሚያከናውኗቸው ልማታዊ ሥራዎች የልምድ ተሞክሯቸውን አካፍለዋል፡፡

 

ማኅበሩ ምእመናንን በማስተባበር ካሠራቸው ተግባራት መካከልም በደብረ ሐይዳ አቡነ ቶማስ ገዳም የተገነባው የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት በውሃ እጥረት ምክንያት የተበተኑ መነኮሳትና የአብነት ተማሪዎች  ወደ ገዳሙ እንዲመለሱና ቍጥራቸውም እንዲጨምር ማድረጉን  የገዳሙ አባቶች መስክረዋል፡፡

 

ለደብረ ገሪዛን ካስዋ ጕንዳጕንዶ ማርያም ገዳም ገቢ ማስገኛ ይኾን ዘንድ በአዲግራት ከተማ የተገነባው ሕንፃም ሌላው የማኅበረ ቅዱሳንና የበጎ አድራጊ ምእመናን ተሳትፎ ውጤት ሲኾን፣ ይህም በመቅኑን እጥረትና በልዩ ልዩ ችግር የቀዘቀዘው ገዳም ተመልሶ እንዲሰፋ ማስቻሉንና የአብነት ትምህርት ለመስጠት መልካም አጋጣሚ ማስገኘቱን የገዳሙ አበ ምኔት ተናግረዋል፡፡

 

የሚዛን ደብረ ከዋክብት አቡነ ተክለ ሃይማኖት የሴቶች ገዳም እመ ምኔትም ገዳሙ ከባንክ ፩.፰ (1.8) ሚሊዮን ብር ተበድሮ ባስገነባው ሕንፃ ከ፩ኛ – ፱ኛ (ከ1ኛ – 9ኛ) ክፍል ድረስ ዘመናዊ ትምህርት እያስተማረ እንደኾነና ሌሎችንም የልማት ሥራዎችን በማከናወን ላይ እንደሚገኝ፤ ማኅበረ ቅዱሳንም የሕንፃውን ዲዛይን ከመሥራት ጀምሮ ድጋፍ እንዳደረገላቸው ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም በገንዘብ እጥረት ምክንያት ያልተጠናቀቁ ሕንፃዎች መኖራቸውንና ከተበደሩት ገንዘብም አብዛኛው አለመመለሱን አስታውሰው ለዚህም የምእመናን ድጋፍ እንዳይለያቸው ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

የአቃቂ ደብረ ገነት አቡነ ሳሙኤል ገዳምም በማኅበሩ ድጋፍ የልብስ ስፌት መኪናና ጣቃ ጨርቅ፤ አንድ ተሽከርካሪ፣ እንደዚሁም ላሞችና የቤት ክዳን ቆርቆሮ ርዳታ ማግኘቱን፤ የገዳሙ መነኮሳይያትም በዘማናዊ ልብስ ስፌትና በእንስሳት ርባታ በሚያገኙት ገቢ ወላጅ የሌላቸውንና ረዳት ያጡ ልጆችን በመከባከብና በማስተማር ላይ እንደሚገኙ እመ ምኔቷ አስረድተዋል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ በጎንደር አቡን ቤት ቅዱስ ገብርኤል የቅኔ ጉባኤ ቤት የቅኔ ደቀ መዝሙር የኾነው፤ ከዩኒቨርሲቲ በዲግሪ መርሐ ግብር ከተመረቀ በኋላ ማኅበሩ ባዘጋጀው የአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ነጻ የትምህርት ዕድል በማግኘቱ ሥራውን ትቶ ወደ አብነት ትምህርት ቤት የገባው ዲያቆን እንዳልካቸው ንዋይና ከኢትዮጵያ የሁለት ዓመት ሕፃን እያለ ከወላጆቹ ጋር ወደ ካናዳ አገር የሔደው፤ የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ያዘጋጀውን የአብነት ትምህርት ቤት ሥርዓተ ትምህርት የሚያሳይ ዘጋቢ ፊልም በፌስ ቡክ ተመልክቶ በትምህርቱ በመማረኩ ወደ ዩኒቨርሲቲ መግባቱን ትቶ ወደ ኢትዮጵያ በመመለስ የአብነት ትምህርት መከታተል የጀመረው የቀድሞው ሔርሞን ተስፋዬ የአሁኑ ዘድንግል በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ቅኔ አበርክተዋል፡፡

 

ባለዲግሪው የቅኔ ተማሪ ዲያቆን እንዳልካቸው ስሜቱን ሲገልጽም “ከአሁን በፊት አነጋጋሪ የነበረው የእኔ ወደ አብነት ትምህርት ቤት መግባት ዜና በወንድሜ በሔርሞን ታሪክ ተሸፍኗል፤ ለወደፊትም ወደ አብነት ትምህርት ቤት የሚገቡና የሁለታችንንም ታሪክ የሚያስረሱ ሌሎች ወንድሞቻችንም እንደሚበዙ ተስፋ አደርጋለሁ” ሲል አስተያየት ሰጥቷል፡፡

 

የአፍ መፍቻ ቋንቋው እንግሊዝኛ የኾነውና በጥረቱ የአማርኛም የግእዝም ቋንቋዎች ተናጋሪ መኾን የቻለው የቀድሞው ዘመናዊ ተማሪ የአሁኑ የቅኔ ደቀ መዝሙር ኢትዮ ካናዳዊው ዘድንግል ደግሞ ለአማርኛ አዲስ መኾኑን በሚመሰክሩ ቃላቱ “እግዚአብሔር ቢፈቅድልኝና ቢሳካልኝ ቅኔ ካስመሰከርሁ በኋላ አቋቋም ተምሬ በውጭው ዓለም በማኅሌት ለማገልገልና በካናዳና በአካባቢው የሚኖሩ ወጣቶችን የአብነት ትምህርት ለማስተማር ዐሳብ አለኝ” በማለት የወደፊት ርእዩን አስገንዝቧል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ማጠቃለያም የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ ወይዘሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት ማኅበረ ቅዱሳን ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ካለባቸው ችግር አኳያ ከፍተኛ ትኵረት ሰጥቶ ምእመናንን በማስተባበር በሚገኘው ድጋፍና በተፈጥሮ ሀብቶች በመታገዝ ቅዱሳት መካናቱ ራሳቸውን እንዲችሉ ለማድረግ ልዩ ልዩ አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደሚገኝ ጠቅሰው “በቤተ ክርስቲያናችን ከሚገኙ ብዙ ሺሕ ገዳማትና የአብነት ትምህርት ቤቶች ቍጥር አንጻር ኹሉንም ተደራሽ ለማድረግ አልተቻለም፤ በአሁኑ ሰዓትም የዕለት ጕርስ እንኳን የማያገኙ አባቶችና እናቶች ያሉባቸው ገዳማትና የአብነት ትምህርት ቤቶች ይገኛሉ፡፡ ስለዚህም ለወደፊቱ ከማኅበሩና ከምእመናን ከዚህ የበለጠ አገልግሎት ይጠበቃል” ብለዋል፡፡

 

በመጨረሻም በአባታዊ ምክራቸውና በጸሎታቸው ከማኅበሩ ጎን የማይለዩትን ብፁዕ አቡነ ሉቃስንና ሌሎችንም የቤተ ክህነትና የየገዳማት አባቶችን፤ በጎ አድራጊ ምእመናንን፤ በየጊዜው ርዳታ የሚያደርገውን የአሜሪካ ማእከልን፤ እንደዚሁም ለመርሐ ግብሩ መሳካት ልዩ ልዩ አስተዋጽኦ ያበረከቱ የማኅበረ ቅዱሳን ልዩ ልዩ ማእከል አባላትን፤ በዕለቱ የተገኙ የዐሥሩን ገዳማት አበ ምኔቶችንና እመ ምኔቶችችን ወ/ሮ ዓለምፀሐይ መሠረት ማኅበሩን ወክለው ምስጋና ካቀረቡ በኋላ በብፁዕ አቡነ ሉቃስ ጸሎተ ቡራኬ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ኾኗል፡፡

2S0A7234.MOV02

 

በተያያዘ ዜና ዋና ክፍሉ በደቡብ ምሥራቅ ትግራይ ሀገረ ስብከት ለሚገኙት ለደብረ ገነት ቀቀማ ቅድስት ማርያም እና ደብረ ዓሣ አባ ዮሐኒ ገዳማት የምግብ ድጋፍ ማድረጉን የመቀሌ ማእከል ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቋል፡፡

 

በድጋፍ መርሐ ግብሩም የገዳማቱ መነኮሳት፣ የዋናው ማእከልና የመቀሌ ማእከል አባላት ተገኝተዋል፡፡

 

የመቀሌ ማእከል ዋና ጸሐፊ አቶ ሐጋዚ አብርሃ እንደ ገለጹት ሁለቱ ጥንታውያን ገዳማት ካለባቸው የምግብ ችግር አኳያ ቅድሚያ የተሰጣቸው ሲኾን፣ ለሁለቱ ገዳማትም በአጠቃላይ የሃያ ኩንታል ጤፍ እና ሥንዴ ድጋፍ ተደርጎላቸዋል፡፡

ገዳማት

ከዚህ በፊትም በዚሁ ሀገረ ስብከት በሕንጣሎ ውጅራት ወረዳ ለምትገኘው ቅድስት አርሴማ ገዳም ተመሳሳይ ድጋፍ መደረጉን አቶ ሐጋዚ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

 

በአካባቢው በተከሠተው ድርቅ ምክንያት የገዳማቱ መነኮሳት በደረሰባቸው ረኃብ በዓለ ትንሣኤን ሳይቀር ጥሬ ቆርጥመው ማሳለፋቸውንና የዕለት ጕርስ ለማግኘት በመቸገራቸውም በዓታቸውን ለቀው ለመውጣት መገደዳቸውን የቀቀማ ቅድስት ማርያም ገዳም አበምኔት መምህር አባ ሠርፀ ድንግል እና የደብረ ዓሣ አባ ዮሐኒ ገዳም አበ ምኔት መምህር አባ ተክለ አብ አብርሀ ይናገራሉ፡፡

 

በዚህ ዓመት የተከበረውን የትንሣኤ በዓልን አስመልክቶ በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን በተዘጋጀው መርሐ ግብርም ይህ የገዳሙ ኹኔታ መዘገቡን የመቀሌ ማእከል አስታውሷል፡፡

 

ለወደፊቱም “ገዳማት ለቤተ ክርስቲያን ህልውና መሠረት ናቸው፤ ጳጳሳቱ፣ መነኮሳቱ፣ ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ምንጫቸው ገዳማት ናቸው፡፡ ከኹሉም በላይ ገዳማት ከእግዚአብሔር ምሕረትን የሚለምኑ፣ ዘወትር በጾም በጸሎት የሚተጉ አባቶች መኖሪያዎች ናቸውና ኹሉም ሕዝበ ክርስቲያን ገዳማትን ቢደግፍ መልካም ነው” ሲሉ የገዳሙ አባቶችና እናቶች ጥሪያቸውን ያስተላልፋሉ፡፡

እናቴ ሆይ እሳቱን አትፍሪ፤ እግዚአብሔር ያድነናል፡፡

ሐምሌ ፲፰ ቀን፣ ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

007

በመጽሐፈ ስንክሳር እንደ ተመዘገበው ሐምሌ ፲፱ ቀን ቅዱስ ቂርቆስና ቅድስት ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራ የተቀበሉበትና ስማቸውን የሚጠራ፣ ዝክራቸውንም የሚዘክሩ ምእመናን ይቅርታን፣ ምሕረትን እንደሚያገኙ ከጌታችን ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ቃል ኪዳን የተቀበሉበት ዕለት ነው፡፡ እንደዚሁም እግዚአብሔር አምላካችን ቅዱስ ገብርኤልን ልኮ እነዚህን ቅዱሳን መርዳቱ የሚነገረው በዚሁ ዕለት ነው፡፡ የሰማዕታቱ ቅዱስ ቂርቆስና የኢየሉጣ ታሪክም በአጭሩ የሚከተለው ነው፤

 

አንጌቤን በሚባል አገር በክርስትና ሃይማኖት ጸንታ የምትኖርና እግዚአብሔርን የምትፈራ ቅድስት ኢየሉጣ የምትባል ደግ ሴት ነበረች፡፡ ልጇን ቅዱስ ቂርቆስንም በሃይማኖትና በምግባር አሳድጋዋለች፡፡ የዘመኑን አረማዊ መኰንን እለእስክንድሮስን በመፍራት ከሮም ወደ ጠርሴስ ከልጇ ጋር በተሰደደች ጊዜ መኰንኑ እነርሱ ከሚገኙበት አገር ገብቶ ክርስቲያኖችን እያሳደደ መግደል ጀመረ፡፡

 

የንጉሡ ወታደሮችም ቅድስት ኢየሉጣንና ቅዱስ ቂርቆስን እግዚአብሔርን እንዲክዱ፤ ለጣዖት እንዲሰግዱ ቢያፈስራሯቸውም ቅዱሳኑ ግን ሃይማኖታቸውን ለመለወጥ ፈቃደኛ አልኾኑም፡፡ በዚህም መኰንኑ ተቈጥቶ ጨውና ሰናፍጭ በዓይንና በአፍንጫቸው ውስጥ በመጨመር፤ በጋሉ የብረት ችንካሮች በመቸንከርና መላ ሰውነታቸውን በመብሳት በብዙ ዓይነት መሣሪያ አሠቃያቸው፡፡ እግዚአብሔርም የጋሉ ብረቶችን እንደ ውኀ ያቀዘቅዝላቸው፤ ሥቃያቸውንም ያቀልላቸው ነበር፡፡

 

በሌላ ጊዜም በገመድ አሳሥሮ ሲያስጨንቃቸው ከቆየ በኋላ ራሳቸውን ከቆዳቸው ጋር አስላጭቶ እሳት አነደደባቸው፡፡ ዳግመኛም ከትከሻቸው እስከ እግራቸው ድረስ በሚደርሱ ችንካሮች በቸነከራቸው ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ተልኮ ከሥቃያቸው አድኗቸዋል፡፡ አሁንም ቀኑን ሙሉ በልዩ ልዩ የሥቃይ መሣሪያዎች ቢያስጨንቃቸውም የእግዚአብሔር ኃይልና የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አልተለያቸውም ነበርና ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰባቸውም፡፡

 

እንደገናም በመጋዝ ሰንጥቀው በብረት ምጣድ በቆሏቸው ጊዜ ጌታችን ከሞት አነሣቸውና በመኰንኑ ፊት ድንቅ ተአምራትን አደረጉ፡፡ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ የመኰንኑን ጫማ በጸሎት ወደ በሬነት እንዲቀየር ባደረገ ጊዜም መኰንኑ በተአምራቱ በመቈጣቱ ምላሱን ቢያስቈርጠውም ጌታችን ምላሱን አድኖለታል፡፡

 

ዳግመኛም በፈላ የጋን ውሃ ውስጥ ቅዱሳን ቂርቆስና ኢየሉጣን ሊጨምሯቸው ሲሉ ቅድስት ኢየሉጣ በፈራች ጊዜ ቅዱስ ቂርቆስ “እናቴ ሆይ አትፍሪ፤ አናንያ፣ ዓዛርያና ሚሳኤልን ከእሳት ነበልባል ያዳናቸው እግዚአብሔር እኛንም ከዚህ የፈላ ውሃ ያድነናል” እያለ ያረጋጋትና በተጋድሎዋ እንድትጸና ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላት ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ተያይዘው ወደ ጋኑ ውስጥ ገቡ፡፡ ያ ውሃም እንደ ውርጭ ቀዘቀዘ፡፡ ደግሞም ወታደሮቹ መንኰራኵር ባለበት የብረት ምጣድ ውስጥ ከተው ሥጋቸው እስኪቈራረጥ ድረስ በጎተቷቸው ጊዜም ቅዱስ ገብርኤል በሕይወት አድኗቸዋል፡፡

 

በአጠቃላይ ቅዱስ ቂርቆስና ቅድስት ኢየሉጣ የዚህን ዓለም ጣዕም በመናቅ “ሞት ቢኾን፣ ሕይወትም ቢኾን፣ መላእክትም ቢኾኑ፣ ግዛትም ቢኾን፣ ያለውም ቢኾን፣ የሚመጣውም ቢኾን፣ ኃይላትም ቢኾኑ፣ ከፍታም ቢኾን፣ ዝቅታም ቢኾን፣ ልዩ ፍጥረትም ቢኾን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼአለሁ፤” /ሮሜ.፰፥፴፰-፴፱/ ሲል ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረውን ቃል በተግባር በማሳየት ለክርስቶስ ፍቅር ሲሉ ራሳቸውን ለመከራና ለሞት አሳልፈው ሰጥተዋል፡፡

 

በመጨረሻም ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ተቀብለው በመንፈቀ ሌሊት አንገታቸውን ተቈርጠው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ እስከ ሞት ድረስ በታመኑበት ተጋድሏቸውም ከእግዚአብሔር ዘንድ የሕይወትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡ ተጋድሏቸውን እስኪፈጽሙ ድረስም ቅዱስ ገብርኤል አልተለያቸውም፡፡

 

በቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት ቅድስት ኢየሉጣና ቅዱስ ቂርቆስ ብቻ ሳይኾኑ ብዙ ምእመናንም ተጠቅመዋል፡፡ ለዚህም ስሙ በሚጠራባቸው ገዳማትና አድባራት የሚያደርጋቸው ድንቅ ድንቅ ተአምራት ምስክሮች ናቸው፡፡ ይህም ቅዱሳን መላእክት በእግዚአብሔር ስም መከራ የሚቀበሉ ምእመናንን እንደሚጠብቁና ከልዩ ልዩ ደዌ እንደሚፈውሱ የሚያስረዳ ታሪክ ነው፡፡

 

እኛም በሃይማኖታችን ምክንያት መከራ ባጋጠመን ጊዜ ቈራጥ ልብ ያለው ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ “እናቴ ሆይ አትፍሪ” እያለ እናቱን በመከራ እንድትጸና እንዳረጋጋትና ለሰማዕትነት እንድትበቃ እንዳደረጋት ኹሉ፣ ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔርን መንግሥት በአንድነት ለመውረስ እንድንችል “አይዞህ! አይዞሽ! አትፍራ! አትፍሪ” በመባባል እስከ ሞት ድረስ በመታመን በዚህ ዓለም የሚገጥመንን መከራ በትዕግሥት ለማሳለፍ ቈርጠን መነሣት ይኖርብናል፡፡ ክርስትና ለብቻ የሚጸደቅበት መንገድ ሳይኾን ለኹላችንም የተሰጠ የጋራ የድኅነት በር ነውና፡፡

 

ከዚሁ ኹሉ ጋርም ቅዱስ ቂርቆስንና ቅድስት ኢየሉጣን የተራዳው የእዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል በአማላጅነቱ እንዲጠብቀን “በእግዚአብሔር ታምነን በቀንም በሌሊትም የአንተን ልመና ተስፋ እናደርጋለን” እያልን ዘወትር ልንማጸነው ያስፈልጋል፡፡ እርሱ ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር በተሰጠው ቃል ኪዳን መሠረት ከሚደርስብን ልዩ ልዩ መከራና ሥቃይ ያድነናልና፡፡ “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሠፍራል፤ ያድናቸውማል፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ /መዝ.፴፬፥፯/፡፡

 

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፡፡ እኛንም በቅዱስ ገብርኤል፣ በቅድስት ኢየሉጣና በቅዱስ ቂርቆስ ጸሎትና ምልጃ ይጠብቀን፡፡ የቅዱሳን ተራዳኢነት አይለየን፡፡

የአውሮፓ ማእከል ፲፮ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ተካሔደ

 

ሐምሌ ፲፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአውሮፓ ማእከል

ገገገገገ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል ፲፮ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ከሐምሌ ፩-፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በስዊድን አገር ስቶክሆልም ከተማ ተካሔደ።

 

በጠቅላላ ጉባኤው በተለያዩ የአውሮፓ አገሮች የሚኖሩ ከሰባ በላይ የማእከሉ አባላት፤ የዋናው ማእከልና የሰሜን አሜሪካ ማእከል ተወካዮች፤ እንደዚሁም ጥሪ የተደረገላቸው ካህናትና ምእመናን ተሳትፈዋል።

 

በስቶክሆልም መንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ በመልአከ ብርሃን አባ ገብረ ጊዮርጊስ ካሣዬና በአውሮፓ ማእከል ሰብሳቢ በቀሲስ ዶ/ር ያብባል ሙሉዓለም የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት ተላልፏል።

 

“እስክመጣ ድረስ ያላችሁን ጠብቁ” /ራእ.፪፥፳፭/ በሚል ኃይለ ቃል በመምህር ፍቃዱ ሣህሌ ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል።

 

የዋናው ማእከል መልእክትም በተወካዩ በአቶ ታምሩ ለጋ አማካይነት ለጉባኤው ቀርቧል።

 

በጉባኤው የመገናኛ ብዙኃን አጠቃቀምንና መንፈሳዊ ሕይወትን የሚዳስሱ ጥናቶች የቀረቡ ሲኾን፣ እንደዚህ ዓይነት ጥናቶች ለመንፈሳዊ ሕይወት መጠንከር ጠቃሚ በመኾናቸው ለወደፊቱም በተሻለና በተጠናከረ መልኩ እንዲቀርቡ የሚል አስተያየት በጉባኤው ተሳታፊዎች ተሰጥቷል፡፡

 

በተመሳሳይ መልኩ “ልጆችን በቤተ ክርስቲያን በተቀናጀ መልኩ ለማስተማር የእኛ ድርሻ” በሚል ርእስ አጭር የግንዛቤ ማስጨበጫ ጽሑፍ በተተኪ ትውልድ ሥልጠና አገልግሎት ክፍል ቀርቧል።

 

በተጨማሪም የሰሜን አሜሪካ ማእከል ተወካይ አቶ ትእዛዙ ካሣ “የውጭ አገር የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ተግዳሮቶችና ዕድሎች” በሚል ርእስ በውጭ አገር ያለውን የአገልግሎት ኹኔታና የማእከሉን ተሞክሮ የሚያስገነዝብ ጽሑፍ አቅርበዋል፡፡

 

የማእከሉ የ፳፻፰ ዓ.ም የሥራ አፈጻጸም ዘገባ ቀርቦ በጉባኤው ተሳታፊዎች ሰፊ ውይይት ተደርጎበታል፡፡

 

የቀጣይ ስድስት ዓመት ስልታዊ ዕቅድ አቅጣጫዎችም በዋናው ማእከል ተወካይ በአቶ ታምሩ ለጋና በአውሮፓ ማእከል ምክትል ሰብሳቢ በዶ/ር ታጠቅ ፈቃዱ አማካይነት ለጉባኤው ቀርበዋል፡፡

 

ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት ማእከሉን በሥራ አስፈጻሚነት የሚመሩ አባላትም በአባቶች ጸሎት በዕጣ ተመርጠዋል፡፡ የኦዲት እና ኢንስፔክሽን ክፍል ሓላፊም በጉባኤው ተሰይሟል።

 

የ፳፻፱ ዓ.ም የማእከሉ እና ኦዲትና ኢንስፔክሽን ክፍል የአገልግሎት ዕቅድም ለጉባኤው ቀርቦ ውይይት ከተደረገበት በኋላ በምልዓተ ጉባኤው ጸድቋል፡፡

 

በመጨረሻም ለጉባኤው መሳካት አስተዋጽኦ ላደረጉ ለመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ካህናት፣ ለስዊድን ንዑስ ማእከል አባላት፣ ለሰንበት ት/ቤት ወጣቶችና ለአካባቢው ምእመናን የማእከሉ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ያብባል ሙሉዓለምና የጉባኤው አዘጋጅ ኰሚቴ ሰብሳቢ አቶ ሳምሶን መለሰ ምስጋና ካቀረቡ በኋላ ጠቅላላ ጉባኤው በአባቶች ጸሎት ተጠናቋል።

ዘመነ ክረምት ክፍል አንድ

ሐምሌ ፲፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በበአተ ክረምት ጽሑፋችን እንደ ጠቀስነው በኢትዮጵያ የወቅቶች ሥርዓተ ዑደት አኳያ አሁን የምንገኘው ዘመነ ክረምት ላይ ነው፡፡ በቅዱስ ያሬድ አስተምህሮ ይህ ዘመነ ክረምት በሰባት ንዑሳን ክፍሎች ይመደባል፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን የመጀመሪያውን ክፍለ ክረምት የተመለከተ ጽሑፍ ይዘን ቀርበናል፤

ከሰባቱ የዘመነ ክረምት ክፍሎች መካከል የመጀመሪያው ክፍል (ከሰኔ ፳፭ እስከ ሐምሌ ፲፰ ቀን ድረስ ያለው ጊዜ) ዘርዕ፣ ደመና ይባላል፡፡ በዚህ ወቅት ስለ ዘርዕ፣ ስለ ደመናና ስለ ዝናም የሚያዘክሩ መዝሙራትና ምንባባት ይዘመራሉ፤ ይነበባሉ፡፡ ይህ ወቅት ደመና ሰማዩን የሚሸፍንበት፤ የዝናም መጠን የሚያይልበትና መሬት በዝናም ረክታ ዘር የምታበቅልበት ጊዜ ነው፡፡

ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ <<በልቅሶ የሚዘሩ በደስታ ይሰበስባሉ፡፡ በሔዱ ጊዜ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዶአቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው መጡ፤>> በማለት እንደ ተናገረው /መዝ.፻፳፭፥፭-፮/፣ ይህ ወቅት አርሶ አደሩ በእርሻና ዘር በመዝራት የሚደክምበትና የምርት ጊዜውን በተስፋ የሚጠባበቅበት ጊዜ ነው፤ ይህም የሰውን ልጅ የሕይወት ጉዞና ውጣ ውረድ እንደዚሁም በክርስቲያናዊ ምግባር ስለሚያገኘው ሰማያዊ መንግሥት የሚያስረዳ ምሥጢር አለው፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን የውቅያኖስና የሐኖስ ድንበር ይኾን ዘንድ በውሃ መካከል ጠፈርን ፈጥሮ ከጠፈር በታች (በዚህ ዓለም) ያለው ውሃ በአንድ ቦታ እንዲወሰን ካደረገ በኋላ ከምድር እስከ ብሩህ ሰማይ ድረስ የነበረውን ውሃ ከሦስት ከፍሎ ሢሶውን አርግቶ ጠፈር አድርጎታል፡፡ ሢሶውም ከጠፈር በላይ ያለው ውሃ ሲኾን፣ ስሙም ሐኖስ ይባላል፡፡

ሢሶውንም ይህንን ዓለም ከሰባት ከፍሎ ሰባተኛውን ዕጣ አጐድጕዶ በዚያ ወስኖ ስሙን ውቅያኖስ ብሎታል፡፡ የብሱን ክፍል ደግሞ ምድር ብሎ ሰይሞታል፡፡ ምድርም እንደ ጉበት ለምልማ በታየች ጊዜ እግዚአብሔር በነፋስ ኃይል ጸጥ ካደረጋት በኋላ ከደረቅ ምድር ደረቅ ጢስ፤ ከርጥብ ባሕር ርጥብ ጢስ አስወጥቶ ደመናን አስገኝቷል /ትርጓሜ መዝሙረ ዳዊት ፻፴፬፥፯/፡፡

ደመና ዝናምን የሚሸከመው የማይጨበጠው ጢስ መሰል ፍጥረት ሲኾን፣ በደመና ተሸካሚነት ከውቅያኖስና ከወንዞች በትነት አማካይነት ወደ ሰማይ ተወስዶ እንደ ገና ተመልሶ ወደ ምድር የሚጥለው ውሃ ደግሞ ዝናም ይባላል፡፡ ይኸውም በእግዚአብሔር ጥበብ በደመና ወንፊትነት ተጣርቶ ለፍጡራን በሚመችና በሚጠቅም መጠን በሥርዓት ይወርዳል፡፡ <<ያጸንዖ በፍኖተ በድው ከመ ይዝንም ብሔረ ኀበ አልቦ ሰብእ ወኢይነብሮ ዕጓለ እመሕያው፤ ዝናሙን ሰው በሌለበት በምድረ በዳ ያዘንመዋል፤>> እንዳለ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ፡፡

ይህም በረዶውን በምድረ በዳ አፍሶ የጠራውን ውሃ ሰው ወዳለበት እንዲዘንም ማድረጉን የሚያስረዳ መልእክት የያዘ ሲኾን፣ ምሥጢሩም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንበለ ዘርዕ በልዩ ጥበቡ መፀነሱንና የሰውን ሥጋ ለብሶ ማስተማሩን፤ እንደዚሁም ቅዱሳን ሐዋርያትን <<ሑሩ ወመሐሩ>> ብሎ በመላው ዓለም ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት ማሰማራቱን ያመለክታል /ትርጓሜ ቅዳሴ ኤጲፋንዮስ ፪፥፭-፮/፡፡

እግዚአብሔር አምላክ በረቂቅ ጥበቡ ውሃን ከውቅያኖሶች በደመና እየጫነ ወደ ሰማይ ካወጣ በኋላ እንደ ገና መልሶ ወደ ምድር እያዘነመ ይህንን ዓለም ሲመግብ ይኖራል፡፡ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም ይህንን ጥበብ በማድነቅ <<ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር ጸባዖት አምላክነ በተነ ጊሜ ረቂቅ ዘያአቍሮ ለማይ ያዐርጎ እምቀላይ ወያወርዶ እምኑኀ ሰማይ፤ ረቂቅ በኾነ የጉም ተን ውሃውን የሚቋጥረው፤ ከወንዝ ወደ ላይ የሚያወጣው፤ ከሩቅ ሰማይም የሚያወርደው እግዚአብሔር ቅዱስ፣ ልዩ፣ ምስጉን አሸናፊ አምላክ ነው፤>> በማለት እግዚአብሔርን ያመሰግናል /መጽሐፈ ሰዓታት/፡፡

ዝናም በአንድ በኩል የቃለ እግዚአብሔር ምሳሌ ነው፤ ይኸውም ለዘር መብቀል፣ ማበብና ማፍራት ምክንያት እንደ ኾነ ኹሉ በቃለ እግዚአብሔርም በድንቁርና በረኃ የደረቀ ሰውነት ይለመልማል፤ መንፈሳዊ ሕይወትን የተራበችና የተጠማች ነፍስም ትጠግባለች፤ ትረካለችና፡፡ <<ሲሲታ ለነፍስ ቃለ እግዚአብሔር፤ የነፍስ ምግቧ የእግዚአብሔር ቃል ነው፤>> እንዲል፡፡

በሌላ በኩል በዚህ ዓለም የሚያጋጥም ልዩ ልዩ ፈተናም በዝናም ይመሰላል፤ ጌታችን በወንጌል እንደ ነገረን ቃሉን ሰምቶ በሥራ ላይ የሚያውል ክርስቲያን ቤቱን በዓለት ላይ የመሠረተ ልባም ሰውን ይመስላል፡፡ ጐርፍ ቤቱን በገፋው ጊዜ አይናወጥምና፡፡

ቃሉን የማይተገብር ክርስቲያን ግን ያለ መሠረት በአሸዋ ላይ ቤቱን የሠራ ሰነፍ ሰውን ይመስላል፡፡ ቤቱ በዝናብ፣ በጎርፍና በነፋስ ተገፍቶ የከፋ አወዳደቅ ይወድቃልና፡፡ ይህም ሃይማኖቱን በበጎ ልቡና የያዘ ክርስቲያን ከልዩ ልዩ አቅጣጫ በሚደርስበት መከራ ሳይፈራና በሰዎች ምክር ሳይታለል፤ እንደ ኢዮብ ዓይነት ፈተና ቢደርስበት ሳያማርር፤ እንደዚሁም በምክረ ካህን በፈቃደ ካህን እየታገዘ አጋንንትን ድል እያደረገ ሃይማኖቱን ጠብቆ እንደሚኖር፤ በአንጻሩ ሃይማኖቱን በበጎ ሕሊና ያልያዘ ክርስቲያን ግን ፈተና ባጋጠመው ጊዜ በቀላሉ እንደሚክድና ለአጋንንትም እጁን እንደሚሰጥ የሚያስረዳ ምሥጢር አለው /ትርጓሜ ወንጌል፣ ማቴ.፯፥፳፬-፳፯/፡፡

ዝናም ሲጥል የወንዞች ሙላትና ማዕበላት ቤት እንዲያፈርሱ፤ ንብረት እንዲያወድሙ በክርስቲያናዊ ሕይወት በሚያጋጥም ፈተናም በእምነት መዛል፣ መከራ፣ ችግር፣ ውጣ ውረድ ያጋጥማል፡፡ ዝናም ለጊዜው እንዲያስበርድና ልብስን እንዲያበሰበስ ፈተናም እስኪያልፍ ድረስ ያሰንፋል፤ ያስጨንቃል፤ ያዝላል፡፡ ነገር ግን ዝናም፣ ጎርፍና ማዕበል ጊዜያዊ እንደ ኾነ ኹሉ ፈተናም ከታገሡት ያልፋል፡፡

ዝናም ሲመጣ የውሆችን ሙላትና ጎርፉን ሳንፈራ ወደ ፊት የምናገኘውን ምርት ተስፋ እንደምናደርግ ፈተና ሲያጋጥመንም የምናገኘውን ሰማያዊ ዋጋ በማሰብ በትዕግሥት ማሳለፍ ይኖርብናል፡፡ ስለዚህ ኹላችንም እምነታችንን በጠንካራ መሠረት ላይ በመገንባት በውሃ ሙላትና በማዕበል ከሚመሰል ውድቀት ማምለጥ ይጠበቅብናል ማለት ነው፡፡

የደመና አገልግሎቱ ዝናምን ከውቅያኖስ በመሸከም ወደ ምድር እያጣራ ማውረድ ቢኾንም ነገር ግን በሰማይ የሚዘዋወርና በነፋስ የሚበታተን ዝናም አልባ ደመናም አለ፡፡ በመልካም ግብር፣ በትሩፋት ጸንተው የሚኖሩ ምእመናን ዝናም ባለው ደመና ሲመሰሉ፣ ያለ ክርስቲያናዊ ምግባር በስመ ክርስትና ብቻ የምንኖር ምእመናን ደግሞ ዝናም በሌለው ደመና እንመሰላለን፡፡ ሐዋርያው ይሁዳ <<… በነፋስ የተወሰዱ ውኃ የሌለባቸው ደመናዎች፤ …>> በማለት የተናገረውም የእንደነዚህ ዓይነት ሰዎችን ሕይወት ይመለከታል /ይሁዳ ፩፥፲፪/፡፡

ስለዚህም ውሃ ሳይይዝ በባዶው በነፋስ እንደሚበታተን ዝናም አልባ ደመና ሳይኾን፣ ዝናም እንደሚሸከም ደመና በምግባረ ሠናይ ጸንተን ልንኖር ይገባል፡፡ አንድም ዝናም ያለው ደመና የእመቤታችን የቅድስት ደንግል ማርያም ምሳሌ ነው፡፡ እርሷ ንጹሑን የሕይወት ውሃ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አስገኝታልናለችና፡፡ <<አንቲ ዘበአማን ደመና እንተ አስተርአይኪ ለነ ማየ ዝናም፤>> እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም /ውዳሴ ዘረቡዕ/፡፡ እኛም እንደ እመቤታችን የእግዚአብሔርን ቃል ሕይወታችን በማድረግ ራሳችንን ከማዳን ባሻገር ለሌሎችም አርአያና ምሳሌ ልንኾን ያስፈልጋል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ምድርን ከፈጠረ በኋላ በጥፍር የሚላጡትን (ሎሚ፣ ሙዝ፣ ትርንጎ፣ ወዘተ)፤ በማጭድ የሚታጨዱትን (ስንዴ፣ ጤፍ፣ ገብስ፣ ወዘተ)፤ በምሳር የሚቈረጡትን (ወይራ፣ ዋርካ፣ ዋንዛ፣ ዝግባ፣ ወዘተ)፤ የገነት ዕፀዋትን ፈጥሯል፡፡ ተፈጥሯቸውም እንደ ሰው ከአራቱ ባሕርያት ነው፡፡

ከነፋስ በመፈጠራቸው በነፋስ ያብባሉ፤ ያፈራሉ፡፡ ከእሳት በመፈጠራቸው እርስበርሳቸው ሲፋተጉ እሳት ያስገኛሉ (አንዳንዶቹ)፡፡ ከውሃ በመፈጠራቸው ፈሳሽ ይወጣቸዋል፡፡ ከአፈር በመፈጠራቸው ሲቈረጡ በስብሰው ወደ አፈርነት ይቀየራሉ፡፡ እነዚህም በራሳቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ስንዴ፣ገብስ፣ ጤፍ፣ ወዘተ)፤ በጎድናቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ማሽላ፣ በቆሎ፣ ባቄላ፣ ወዘተ)፤ በውስጣቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ዱባ፣ ቅል፣ ወዘተ)፤ በሥራቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ሽንኩርት፣ ቀይ ሥር፣ ካሮት፣ ድንች፣ ወዘተ) ተብለው በአራት ይመደባሉ /ምንጭ፡- ትርጓሜ ኦሪት ዘፍጥረት ፩፥፮-፲፫/፡፡

እኛ የሰው ልጆችም በተፈጥሯችን (በባሕርያችን) ከዕፀዋት ጋር እንመሳሰላለን፤ በነፋስ ባሕርያችን ፍጥነት፤ በእሳት ባሕርያችን ቍጣ፤ በውሃ ባሕርያችን መረጋጋት፤ በመሬት ባሕርያችን ትዕግሥት ወይም ሞት ይስማማናልና፡፡ በሌላ በኩል የአዘርዕት ከበሰበሱ በኋላ መብቀልና ማፍራት የትንሣኤ ሙታን ምሳሌ ነው፡፡ አዝርዕት ከበሰበሱ በኋላ ፍሬ እንደሚያስገኙ ኹሉ ሰውም ከሞተ በኋላ ተነሥቶ እንደ ሥራው መጠን ዋጋውን ይቀበላልና፡፡ ይህንን ቅዱስ ጳውሎስ በምሳሌ አስተምሮናል፡፡ እንዲህ ሲል፤ <<… የሙታን ትንሣኤ ደግሞ እንዲሁ ነው፡፡ በመበስበስ ይዘራል፤ ባለመበስበስ ይነሣል፡፡ በውርደት ይዘራል፤ በክብር ይነሣል፡፡ በድካም ይዘራል፤ በኃይል ይነሣል፡፡ ፍጥረታዊ አካል ይዘራል፤ መንፈሳዊ አካል ይነሣል። …>> /፩ኛቆሮ.፲፭፥፵፪-፵፬/፡፡

አዝርዕት ተዘርተው ከበሰበሱ በኋላ በቅለው፣ አብበው በራሳቸው፣ በጎድናቸው፣ በውስጣቸውና በሥራቸው እንደሚያፈሩ ኹሉ እኛም በራስ እንደ ማፍራት ፈሪሃ እግዚአብሔርን፤ በጎድን እንደ ማፍራት እርስበርስ መደጋገፍንና መተሳሰብን፤ በውስጥ እንደ ማፍራት ንጽሕናን፤ በሥር እንደ ማፍራት ትሕትናን ገንዘብ ማድረግን ከዕፀዋትና ከአዝርዕት መማር ይገባናል፡፡

እንደዚሁም ዕፀዋት ሠላሳ፣ ስድሳ፣ መቶና ከዚያ በላይ መልካም ፍሬ እንደሚያፈሩ እኛም በመልካሟ መሬት በክርስትና የተዘራን ምእመናን ዘር የተባለውን የእግዚአብሔርን ቃል በሚገባ ተምረን ከወጣኒነት ወደ ማእከላዊነት፤ ከማእከላዊነት ወደ ፍጹምነት በሚያደርስ የጽድቅ ሥራ በመትጋት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መፋጠን ይኖርብናል /ማቴ.፲፫፥፳፫/፡፡

በአጠቃላይ “… ምሳር በዛፎች ሥር ተቀምጧል፤ እንግዲህ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ኹሉ ይቈረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል፤”  የሚለውን ኃይለ ቃል በማሰብ /ማቴ.፫፥፲/፣ ፍሬ የማያፈሩ ዕፀዋት በምሳር ተቈርጠው እንዲጣሉ እኛም ያለ መልካም ሥራ ከኖርን በእግዚአብሔር ዘለዓለማዊ ፍርድ ከገነት፣ ከመንግሥተ ሰማያት የመባረር ዕጣ እንዳይደርስብን ከሃይማኖታችን ሥርዓት፤ ከቤተ ክርስቲያናችን ትምህርት ሳንወጣ የቅዱሳንን ሕይወት አብነት አድርገን ለጽድቅ ሥራ እንሽቀዳደም፡፡ <<እንግዲህ እነዚህን የሚያህሉ ምስክሮች እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን እኛ ደግሞ ሸክምን ሁሉ ቶሎም የሚከበንን ኃጢአት አስወግደን የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤>> ተብሎ ተጽፏልና /ዕብ.፲፪፥፩-፪/፡፡

ይቆየን፡፡

ስብከተ ወንጌል የልማት መሠረት

ሐምሌ ፲፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ሒዱና አሕዛብን ኹሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው ያዘዝኋችሁንም ኹሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” ሲል በአምላካዊ ቃሉ ያዘዘውን መሠረት በማድረግና የቅዱሳን ሐዋርያትን ፈለግ በመከተል ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በርካታ ሰባክያንን እያስተማረች በየቦታው ስታሰማራ ኖራለች፤ ወደፊትም ይህንን ተልእኮዋን ትቀጥላለች፡፡

ምክንያቱም ስብከተ ወንጌል ቃለ እግዚአብሔርን ለማስተማር ብቻ ሳይኾን የሰውን አእምሮ ለማልማት (መልካም አስተሳሰብን ለመገንባት) የሚያስችል ዋነኛው የቤተ ክርስቲያን መሣሪያ ነውና፡፡ ስለዚህም ነው ቤተ ክርስቲያናችን ከየመጻሕፍት ቤቱና ከመንፈሳውያን ኮሌጆች በየጊዜው መምህራንን እያስመረቀች ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት የምታሰልፋቸው፡፡

የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ ለማስፈጸም የተቋቋመው ማኅበረ ቅዱሳንም በየግቢ ጉባኤያቱ ትምህርተ ሃይማኖትን ከሚያስተምራቸው ወንድሞችና እኅቶች በተጨማሪ ከአባቶችና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመመካከር በልዩ ልዩ የአገራችን ክፍሎች የሚገኙ በርካታ ሰባክያንን በየቋንቋው እያሠለጠነና በአባቶች ቡራኬ እያስመረቀ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት እንዲሠማሩ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡

ማኅበሩ በዚህ ዓመትም ይህንን ተልእኮውን በመቀጠል አሠልጥኖ ያስመረቃቸው ሰባክያነ ወንጌል ከመኖራቸውም ባሻገር በአሁኑ ሰዓት እየሠለጠኑ የሚገኙ ወንድሞችም በርካታ ናቸው፡፡

ለዚህም በአዳማ ከተማ በአፋን ኦሮሞ ሠልጥነው የተመረቁ ሰባክያን፤ እንደዚሁም በአዲስ አበባና በሐሮ እየሠለጠኑ የሚገኙ ወንድሞች ማስረጃዎች ናቸው፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል ከበጎ አድራዎች በተገኘ ድጋፍ ከልዩ ልዩ ገጠራማ ሥፍራዎች የተውጣጡ ፳፰ ሰባክያንን በአፋን ኦሮሞ አሠልጥኖ ሐምሌ ፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም አስመርቋል፡፡

Publication1

በምረቃ ሥርዓቱም የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት፣ የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞችና የየአድባራቱ አገልጋይ ካህናት፣ የአገር ሽማግሎች፣ በጎ አድራጊ ምእመናንና የማእከሉ ሥራ አስፈጻሚ አባላት ተገኝተዋል፡፡

በምረቃ መርሐ ግብሩ ትምህርተ ወንጌልና ዝማሬ የቀረበ ሲኾን፣ ምሩቃኑ በማእከሉ የተዘጋጀላቸውን የምስክር ወረቀት፣ የመጽሐፍ ቅዱስና የነጠላ ስጦታ ከአባቶች እጅ ተቀብለዋል፡፡ እንደዚሁም ምሩቃኑ ሥልጠናውን እንዲያገኙ ላደረጓቸው የማእከሉ ሥራ አስፈጻሚ አባላት ልዩ ልዩ ስጦታ አበርክተዋል፡፡

ለሠልጣኞቹ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚዎችና የዝግጅት ክፍላችን አባላት በተገኙበት ሰኔ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለሠልጣኞቹ የእንኳን ደኅና መጣችሁ አቀባበል የተደረገ ሲኾን፣ በዕለቱ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ፡- “ይህንን ሥልጠና ካጠናቀቃችሁ በኋላ ስብከተ ወንጌል መስጠት ብቻ ሳይኾን የአብነት ትምህርት በመማር ሥልጣነ ክህነት ተቀብላችሁ የሚያጠምቃቸውና ቀድሶ የሚያቈርባቸው ካህን ላላገኙ ወገኖቻችን ልትደርሱላቸው ይገባል በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የማኅበሩ ምክትል ዋና ጸሐፊ አቶ ሰይፈ ዓለማየሁ በበኩላቸው፡- “የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በቃል ብቻ ሳይኾን በሕይወትም የሚሰበክ ተልእኮ መኾኑን ሳትዘነጉ በምትሔዱበት ስፍራ ኹሉ ለምታስተምሯቸው ምእመናንም ኾነ ለሌሎች ወጣቶች መልካም ምሳሌ ልትኾኑ ይገባል” ሲሉ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡

የአዳማ ማእከል ሰብሳቢ መ/ር ጌትነት ዐሥራት ደግሞ ሥልጠናው ሌሊትና ቀን ሲሰጥ መቆየቱን ጠቅሰው፣ ከትምህርተ ሃይማኖት በተጨማሪ የሥራ አመራር፣ የጊዜ አጠቃቀም፣ የስብከት ዘዴ፣ ወቅታዊ ኹኔታ፣ አገልግሎት፣ የሕይወት ተሞክሮና ተዛማጅ መርሐ ግብራት በሥልጠናው መካተታቸውን ገልጸዋል፡፡

ሰብሳቢው በመጨረሻም ለሥልጠናው መሳካት አስተዋጽኦ ላበረከቱ አባቶችና በጎ አድራጊ ምእመናን በማእከሉ ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

በተያያዘ ዜና በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር ከ፳፫ ጠረፋማ አህጉረ ስብከት የተውጣጡ ሰባክያንን በማሠልጠን ላይ ይገኛል፡፡

የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብሩ አስተባባሪ አቶ ጌትነት ወርቁ ለዝግጅት ክፍላችን እንደ ገለጹት ከሰኔ ፳፮ ቀን እስከ ሐምሌ ፳፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለአንድ ወር በሚቆየው በዚህ ሥልጠና የሚሳተፉ ሠልጣኞች ብዛት ፻፴ ሲኾን፣ ከእነዚህ መካከል ፵ዎቹ የዓቅም ማጎልበቻ፤ ፺ዎቹ ደግሞ የስብከተ ወንጌል ሥልጠና የሚወስዱ ወንድሞች ናቸው፡፡

ሥልጠናው የዓቅም ማጎልበቻ እና የስብከተ ወንጌል ሥልጠና በሚሉ አርእስት ለሁለት ተከፍሎ የሚሰጥ ሲኾን፣ የዓቅም ማጎልበቻው በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በለቡ አቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርት ቤት፤ የስብከተ ወንጌል ሥልጠናው ደግሞ በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት በሶዶ ዳጪ ወረዳ ቤተ ክህነት በሐሮ ደብረ ጽጌ ቅዱስ በዓለ ወልድ ወቅዱስ ዑራኤል ገዳም የስብከተ ወንጌል አዳራሽ በመሰጠት ላይ ነው፡፡

የዓቅም ማጎልበቻ ሥልጠናው ከዚህ በፊት የስብከተ ወንጌል ሥልጠና ወስደው በየቋንቋቸው ሲሰብኩ ለነበሩ ወንድሞች እንደተዘጋጀና ዓላማውም ሠልጣኞቹ እንደ እነርሱ ያሉ ብዙ ሰባክያነ ወንጌልን እንዲያፈሩ፤ እንደዚሁም የተጠመቁ ወገኖችን በማጽናት በየቦታው የጽዋ ማኅበራትንና ሰንበት ት/ቤቶችን እንዲመሠርቱ፤ የተመሠረቱትንም እንዲያጠናክሩ ለማድረግ ለመጀመሪያ ጊዜ እንደ ተዘጋጀ፤ የስብከተ ወንጌል ሥልጠናው ደግሞ በልዩ ልዩ ቋንቋ የሚያስተምሩ ሰባክያነ ወንጌልን ለማፍራት የሚሠጥ ሥልጠና እንደ ኾነ አቶ ጌትነት አስታውቀዋል፡፡

ለሠልጣኞቹም የሶዶ ዳጪ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቀ ካህንና ሠራተኞች፣ የገዳሙ አበ ምኔትና ካህናት፣ የወረዳው አስተዳዳሪና ሠራተኞች፣ የማኅበረ ቅዱሳን ልዩ ልዩ ክፍሎች አገልጋዮችና በጎ አድራጊ ምእመናን በተገኙበት ሐምሌ ፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በሐሮ ደብረ ጽጌ ቅዱስ በዓለ ወልድ ወቅዱስ ዑራኤል ገዳም የእንኳን ደኅና መጣችሁ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡

በዕለቱ በቦታው ተገኝተን ቃለ መጠይቅ ያደርግንላቸው የወረዳው ቤተ ክህነት ሊቀ ካህን መልአከ ኃይል ቀሲስ ጀምበር ደበላ “ሥልጠናው በሐሮ ገዳም መሰጠቱ የአካባቢውን ምእመናን ከእኛስ ምን ይጠበቃል? እንዲሉና ወረዳ ቤተ ክህነቱም ለተሻለ አገልግሎት እንዲተጋ ያደርገዋል” ካሉ በኋላ ሥልጠናው እስኪጠናቀቅ ድረስ ዓቅማቸው በሚፈቅደው ኹሉ ለሠልጣኞቹ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ቃል ገብተዋል፡፡

የገዳሙ አስተዳዳሪ ሊቀ ጉባኤ አባ ኤልያስ ወልደ ሥላሴ ደግሞ “ሠልጣኞቹ ከ፳፫ አህጉረ ስብከት የተውጣጡ የልዩ ልዩ ብሔረሰብ አባላት ናቸው፡፡ ስለዚህም ኢትዮጵያ ሐሮ ላይ ተሰብስባለች ማለት ይቻላል፡፡ እኛም በሠልጣኞቹ ፊት ስንገኝ በአበባ መካከል ላይ የቆምን ያህል ይሰማናል” ብለዋል፡፡ አያይዘውም “እግዚአብሔር ማኅበሩን ይጠብቅልን” ሲሉ ማኅበረ ቅዱሳንን መርቀዋል፡፡

የሶዶ ዳጪ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ባጫ ኮምቦሌ በበኩላቸው “እንደዚህ ዓይነት ሥልጠና በእኛ ቀበሌ መሰጠቱ ለወረዳው ብቻ ሳይኾን ለአገር ሰላምና ልማትም የጎላ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡ ምክንያቱም ሃይማኖት ሰላም ነው፤ ሃይማኖት ልማት ነው፡፡ ዛሬ የተካሔደው የችግኝ ተከላ መርሐ ግብርም አንዱ የልማት ማሳያ ነው” ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

ከአቀባበሉ ሥርዓት ቀጥሎም በቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም አስተባባሪነት ጥሪ በተደረገላቸው እንግዶችና በሠልጣኞቹ የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር ተከናውኗል፡፡ የችግኝ ተከላው ዓላማም ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን ብቻ ሳይኾን ልማትንም እንደምታስተምር ለማመልከት መኾኑን ቢትወደድ ባሕሩ ተናግረዋል፡፡

በመጨረሻም ለዚህ ሥልጠና ልዩ ልዩ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አባቶች፤ ከአራት መቶ ሺሕ ብር በላይ በማውጣት የሥልጠናውን ሙሉ ወጪ ለሸፈኑት አንድ በጎ አድራጊ ወንድም፤ እንደዚሁም በአዳራሽ፣ በቁሳቁስ አቅርቦትና በመስተንግዶ በማገዝ ላይ ለሚገኙ ምእመናን የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያው አስተባባሪ ማኅበሩን በመወከል ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

ሥላሴ በአብርሃም ቤት

ሐምሌ ቀን ፳፻፰ .

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፯ ቀን እግዚአብሔር አምላክ በአብርሃም ቤት የገባበትና ሣራ ይስሐቅን እንደምትወልድ የተናገረበት ዕለት በመኾኑ በቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ በደማቅ ሥርዓት ይከበራል፡፡ ታሪኩም በአጭሩ እንዲህ ነው፤

 

አባታችን አብርሃም ከተመሳቀለ ጐዳና ድንኳን ሠርቶ መንገደኞችን ኹሉ በእንግድነት እየተቀበለ ሲያስተናግድ ይኖር ነበር፡፡ ጥንተ ጠላታችን ሰይጣን ለተንኮል አያርፍምና ይህንን መልካም ግብሩን ለማሰናክል አስቦ የተጐዳ ሰው መስሎ ከጐዳና ቆሞ ወደ አብርሃም ቤት የሚሔዱ እንግዶችን አብርሃም እንግዳ መቀበል እንደ ተወ፤ እርሱም ሊበላ ሊጠጣ ከቤቱ ቢሔድ ራሱን ፈንክቶ፣ ደሙን አፍሶ፣ አጥንቱን ከስክሶ፣ ልብሱን ገፎ እንደ መለሰው አድርጎ እየተናገረ እንግዳ ወደ ቤቱ እንዳይመጣ አደረገ፡፡ አብርሃምም ማዕደ እግዚአብሔርን ያለ ምስክር (ያለ እንግዳ) አልመገብም ብሎ ሦስት ቀን ሳይመገብ ጾሙን አደረ /ቅዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጓሜ/፡፡

 

በሦስተኛው ቀን እግዚአብሔር በሦስት ሰዎች ተመስሎ ከአብርሃም ቤት ገብቷል፡፡ በኦሪት ዘፍጥረት ተጽፎ እንደምናገኘው በቀትር ጊዜ አብርሃም በድንኳኑ ደጃፍ ተቀምጦ ሳለ እግዚአብሔር በመምሬ አድባር ዛፍ ለአብርሃም ተገልጦለታል፡፡

 

አብርሃምም ሦስት ሰዎች ቆመው ባየ ጊዜ ሊቀበላቸው ከድንኳኑ ደጃፍ ተነሥቶ ወደ እነርሱ ሮጠ፡፡ ወደ ምድርም ሰገደና አቤቱ በፊትህስ ሞገስ አግኝቼ እንደ ኾነ ባሪያህን አትለፈኝ? ብሎ ተማጸነ፡፡ እዚህ ላይ ሦስት ሰዎች፣ሊቀበላቸው፣ወደ እነርሱ፣…” የሚሉት ሐረጋት ሦስትነቱን፤ በፊትህስ ሞገስ አግኝቼ እንደ ኾነ ባሪያህን አትለፈኝ? የሚለው ዐረፍተ ነገር ደግሞ አንድነቱን ያመለክታል፡፡

 

በመቀጠልም አብርሃም ጥቂት ውኃ ይምጣላችሁ፤ እግራችሁን ታጠቡ፤ ከዚህችም ዛፍ በታች ዕረፉ፡፡ ቍራሽ እንጀራም ላምጣላችሁ፤ ልባችሁንም ደግፋ ከዚያም በኋላ ትሔዳላችሁ ስለዚህ ወደ ባሪያችሁ መጥታችኋልና ሲላቸው እነርሱም እንዳልህ አድርግ ብለውታል፡፡

 

በዚህ ኃይለ ቃልም የእግዚአብሔርን ሦስትነት እንረዳለን፡፡ የዘፍጥረት አንድምታ ትርጓሜ እንደሚያስረዳው አብርሃም ሥላሴን ጌቶቼ ከቤት ገብታችሁ ዕረፉ ሲላቸው ደክሞናልና አዝለህ አስገባን ብለውታል፡፡ እርሱም እሺ ብሎ አንዱን አዝሎ ቢገባ ሁለቱ በግብር አምላካዊ ከቤቱ ገብተዋል፡፡

 

አብርሃምም ወደ ሣራ ዘንድ ፈጥኖ ገባና ሦስት መሥፈሪያ ዱቄት ፈጥነሽ አዘጋጂ፤ ለውሺውም፤ እንጎቻም አድርጊ አላት፡፡ እርሷም እንዳዘዛት አደረገች፡፡ ሦስት መሥፈሪያ የሦስትነት፤ ዳቦው አንድ መኾኑ የአንድነት ምሳሌ ነው፡፡ አብርሃምም ወደ ላሞቹ ሔዶ ወይፈን አምጥቶ አርዶ አወራርዶ አዘገጅቶላቸው ተመግበዋል፡፡

 

ወይፈኑም ተነሥቶ ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ብሎ እግዚአብሔርን አመስገኗል፡፡ ነገር ግን ሥላሴ በሰው አምሳል ስለ ተገለጡና ለአብርሃም የበሉ መስለው ስለ ታዩት ተመግበዋል ተባለ እንጂ ለሥላሴ መብል መጠጥ የሚስማማቸው ኾኖ አይደለም፡፡ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን እንዳስተማሩን ሥላሴ ምግብ በሉ ማለት ቅቤ ከእሳት ገብቶ አልቀለጠም እንደ ማለት ነው፡፡

 

ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር አብርሃምን ጠርቶ ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?” አለው፡፡ አብርሃምም ከድንኳኑ ውስጥ እንዳለች ነገረው፡፡ እዚህ ላይ እግዚአብሔር ሣራ ወዴት ናት?” ሲል መጠየቁ ያለችበት ጠፍቶበት ሳይኾን የሚነግራት ታላቅ የምሥራች እንዳለ ለማጠየቅ ነው፡፡ ይኸውም አዳም ወዴት ነህ?” ከሚለው ጥያቄ ጋር ተመሳሳይነት አለው /ዘፍ.፫፥፱/፡፡

 

እግዚአብሔር አምላክ አባታችን አዳምን ወዴት ነህ?” ሲል የጠየቀው ያለበትን ዐላውቅ ብሎ ሳይኾን ቃል በቃል ሊያነጋግረውና ከልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ የሚለውን ቃል ኪዳን ሊገባለት ነበር፡፡ እንደ አዳም ኹሉ ለሣራም ለጊዜው ይስሐቅን እንደምትወልድ፤ ለፍጻሜው ግን እግዚአብሔር ከአብርሃም ወገን ከምትኾን ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋ ለብሶ እንደሚገለጥና ዓለምን እንደሚያድን ለመንገር አብርሃምን ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት? ሲል ጠይቆታል፡፡

 

እግዚአብሔርም የዛሬ ዓመት እንደ ዛሬው ጊዜ ወደ አንተ በእውነት እመለሳለሁ፤ ሚስትህ ሣራም ልጅን ታገኛለችብሎ ለአብርሃም ነገረው፡፡ ሣራ ይህንን ቃል በሰማች ጊዜ ባለቤቷም አርጅቶ፤ እርሷም የሴቶች ግዳጅ ትቷት ነበርና ሲያረጁ አምባር ይዋጁ እንዲሉ እስከ ዛሬ ድረስ ቆንጆ ነኝን? ጌታዬ አብርሃምስ ገና ጐረምሳ ነውን?” ብላ በመጠራጠሯ ሳቀች፡፡

 

እግዚአብሔርም አብርሃምን ሣራ ለምን ትስቃለች? በውኑ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር አለን?” አለው፡፡ ይህንን ኃይለ ቃልም እመቤታችንን በድንግልና ፀንሳ በድንግልና እንደምትወልድ ሲያበሥራት ወንድ ሳላውቅ ይህ እንዴት ሊኾን ይችላል?” ብላ በጠየቀችው ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ተናግሮታል /ሉቃ.፩፥፴፯/፡፡

 

ሣራም ስለፈራች አልሳቅሁም” አለች፡፡ እግዚአብሔርም መሳቋን እንዳወቀባት ከነገራት በኋላ በድጋሜ በዓመቱ ወደ አብርሃም ቤት እንደሚመጣና ሣራ ወንድ ልጅ እንደምትወልድ (ይስሐቅን) አብሥሯቸዋል፡፡ ይህም አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዓመት ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ ሥጋ ለብሼ በመጣሁ ጊዜ ሣራ ወንጌል ምእመናንን ታስገኛለች ማለትም ሐዲስ ኪዳን ተመሥርታ ክርስቲያኖችን ታፈራለች ሲለው ነው፡፡

 

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት እንደ ተረጐሙልን የአብርሃም ድንኳን የእመቤታችን ምሳሌ ነው፤ ቀትር በኾነ ጊዜ ማለትም በስድስት ሰዓት አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ወደ አብርሃም ድንኳን እንደ ገቡ ኹሉ፣ አምስት ሺሕ አምስት መቶው ዓመት ተፈጽሞ በስድስተኛው ሺሕ ዓመት እግዚአብሔር አብ ለአጽንዖ፤ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለአንጽሖ፤ እግዚአብሔር ወልድ በተለየ አካሉ ሥጋን ለመልበስ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አድረዋል፡፡ “በስድስተኛው ወር ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ወደ እመቤታችን ተላከ፤” እንዳለ ቅዱስ ወንጌል /ሉቃ.፩፥፳፮/፡፡

 

ስድስተኛው ወር የሚለው ሐረግ በአንድ በኩል ጌታችን የተፀነሰበት ወርኃ መጋቢት ስድስተኛው ወር መኾኑንና (ከጥቅምት ጀምሮ በመቍጠር)፤ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት በተፀነሰ በስድስተኛው ወር ጌታችን መፀነሱን፤ በሌላ በኩል ደግሞ አምስት ሺሕ አምስት መቶው ዘመን ተፈጽሞ በስድስተኛው ሺሕ ዘመን ቅዱስ ገብርኤል ወደ እመቤታችን መላኩን ያመለክታል /ትርጓሜ ወንጌል/፡፡

 

በአብርሃም ቤት (በድንኳኑ) ውስጥ ወይፈኑ ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ብሎ እንዳመሰገነ ኹሉ እግዚአብሔር አምላክ ከእመቤታችን በተወለደ ጊዜም ቅዱሳን መላእክትና የሰው ልጅ በአንድነት ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ፤ ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይኹን፤ ሰላምም በምድር፤ ለሰውም በጎ ፈቃድ እያሉ እግዚአብሔርን አመስግነዋል /ሉቃ.፪፥፲፬/፡፡

 

እግዚአብሔር አምላክ ለአብርሃም የይስሐቅን መወለድና በሥጋ ማርያም መገለጡን ከነገረው በኋላ ተመልሶ ሔዷል፡፡ ሔዷል ስንልም ሥላሴ ከአብርሃም ቤት ሲወጡ መታየታቸውን ለማመልከት እንጂ እግዚአብሔር መሔድ መምጣት የሚነገርለት ኾኖ አይደለም፡፡ እርሱ በዓለሙ ኹሉ ሰፍኖ የሚኖር አምላክ ነውና፡፡ ነገር ግን በልዩ ልዩ ምሳሌ እየተገለጠ ጸጋውን፣ በረከቱን ማሳደሩን ለመግለጽ መጣ፤ ሔደ፤ ወረደ፤ ዐረገ እየተባለ ይነገርለታል፡፡

/ምንጭ፡- የኦሪት ዘፍጥረት አንድምታ ትርጓሜ፣ ምዕ. ፲፰፥፩-፲፱/፡፡

 

ሐምሌ ፯ ቀን እግዚአብሔር በአብርሃም ቤት ተገኝቶ የይስሐቅን መወለድና የእግዚአብሔርን ሰው መኾን ከመናገሩ በተጨማሪ የአብርሃምን ዘሩን እንደሚያበዛለትና አሕዛብ ኹሉ በእርሱ እንደሚከብሩ ማለትም ከአብርሃም ዘር በተገኘው በኢየሱስ ክርስቶስ አሕዛብ እንደሚቀደሱና ይህንን ምሥጢርም እግዚአብሔር ከወዳጁ ከአብርሃም እንደማይሠውር ቃል የገባለት ቀን ነው፡፡ በተጨማሪም እግዚአብሔር በኀጢአታቸው የተነሣ ሰዶምንና ገሞራን ያጠፋው፤ አብርሃምም በአማላጅነት በፊቱ የቆመው በዛሬው ዕለት ነው፡፡

 

ከዚህ ታሪክ እግዚአብሔር እንደ አብርሃም ልቡናቸው ቅን በኾነና በለጋሾች ማለትም ምጽዋትንና እንግዳ መቀበልን የዘወትር ልማዳቸው አድርገው በሚኖሩ ሰዎች ቤት እንደሚገኝ፤ እግዚአብሔር በረድኤቱ ወደ ሰው ቤት ሲገባም የተዘጋ ማሕፀን እንደሚከፍትና ቤቱን በበረከት እንደሚሞላ፤ እንደዚሁም የተሠወረ ምሥጢር እንደሚገልጽ እንረዳለን፡፡ ለዚህም እግዚአብሔር በአብርሃም ቤት ገብቶ ያደረገው ኹሉ ትልቅ ማስረጃ ነው፡፡ ከዚሁ ኹሉ ጋርም እግዚአብሔር አምላክ በአንድነቱም በሦስትነቱም እየታየ አምላክነቱን ለዘመናት እንደሚገልጥና የቸርነቱን ሥራ እንደሚሠራም ከታሪኩ እንማራለን፡፡

 

ይህ የእግዚአብሔር በአብርሃም ቤት መገለጥም በአንድ ወቅት ብቻ የተፈጸመና ነበር እየተባለ የሚነገር ታሪክ ሳይኾን፣ ለዘለዓለሙ ሲነገርና ሲፈጸም የሚኖር ሕያው ትምህርት ነው፡፡ ይህንንም እግዚአብሔር ለቅዱሳኑ በልዩ ልዩ መንገድ እየተገለጠ ለዘመናት በሚያደርገው ድንቅ ሥራና ተአምር መገንዘብ እንችላለን፡፡

 

ዛሬም ሀብት ንብረት ያለን ምእመናን በትሩፋት ሥራ በመሠማራት ማለትም እንግዶችን በመቀበል፣ ለተራቡ በማብላት፣ በመመጽወት ተግባር ከኖርን፤ በቂ ንብረት የሌለን ደግሞ ልቡናችንን ንጹሕ ከማድረግና ከኀጢአት ከመራቅ በተጨማሪ ቤት ላጡና ለተቸገሩ መራራትን፣ ደግነትን፣ ቀና አስተሳሰብን ገንዘብ ካደረግን እግዚአብሔር በሕይወታችን ውስጥ ያድራል፡፡ አድሮም ይባርከናል፤ ይቀድሰናል፡፡ በአጠቃላይ የምንሻውን መልካም ነገር ኹሉ ይፈጽምልናል፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

 

የብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስና ጳውሎስ ዕረፍት

ሐምሌ ፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፭ ቀን በአንድ በኩል የብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ በዓለ ዕረፍት የሚዘከርበት ዕለት ሲኾን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የጾመ ሐዋርያት ፋሲካ የሚከበረውም በዚሁ ዕለት ነው፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን የእነዚህን ቅዱሳን ታሪክ በአጭሩ ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

ቅዱስ ጴጥሮስ

ጴጥሮስ ማለት በግሪክ ቋንቋ ዓለት (መሠረት) ማለት ነው፡፡ ወላጆቹ ስምዖን ይሉት ነበር፡፡ በአባቱ የሮቤል፣ በእናቱ የስምዖን ነገድ ሲኾን፣ የተወለደውም በገሊላ አውራጃ በቤተ ሳይዳ ነው፡፡ ሰዎችን በወንጌል መረብ እያጠመደ ወደ ክርስትና ሕይወት ይመልስ ዘንድ ጌታችን ከዓሣ አጥማጅነት ለሐዋርያነት ጠርቶታል /ሉቃ.፭፥፲፤ ማር.፩፥፲፮/፡፡ በመንፈሳዊ ቅንዓቱና ለጌታችን በነበረው ፍቅር የሐዋርያት አለቃ ኾኖ ተሹሟል፡፡ ለአገልግሎት ከተጠራበት ጊዜ ጀምሮም በእስያ፣ በሮም፣ በሰማርያ፣ በልዳ፣ በኢዮጴ፣ በአንጾኪያ፣ በገላትያና በሌሎችም አገሮች እየተዘዋወረ ወንጌልን ሰብኳል፡፡ በስብከቱ ምክንያትም ልዩ ልዩ መከራን ተቀብሏል፡፡ በቃል ካስተማረው ትምህርት በተጨማሪ በመጽሐፍ ቅዱስ በስሙ የተመዘገቡ ሁለት መልእክታትን ጽፏል፡፡

በመጨረሻም የክርስቲያኖች ጠላት የነበረው የሮም ንጉሥ ወደ አካይያ ዘምቶ ድል አድርጎ በደስታ ወደ ሮሜ ሲመለስ መኳንንቱን ለማስደሰት፤ ጣዖታቱንም ለማክበር ሲል በቅዱስ ጴጥሮስና በሌሎችም ክርስቲያኖች ላይ የሞት ፍርድ ዐወጀ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ በሮም ሲያስተምር ቆይቶ የሮም መኳንንት እንዳይገድሉት ትጥቁን ለውጦ ከሮም ሲወጣ ጌታችን መስቀል ተሸክሞ ተገለጸለት፤ በዚህ ጊዜ *አቤቱ ጌታ ሆይ ወዴት ትሔዳለህ? ሲል ቢጠይቀው ጌታችንም *ልሰቀል ወደ ሮም እሔዳለሁ* አለው፡፡ *ዳግመኛ ትሰቀላለህን?* ባለው ጊዜም *አንተ ሰትፈራ ጊዜ ነው እንጂ* አለው፡፡ ያን ጊዜም *ጐልማሳ ሳለህ ወገብህን ታጥቀህ ወደ ወደድኸው ትሔድ ነበር፡፡ ስትሸመግል ግን እጅህን ታነሣና ሌላ ሰው ያስታጥቅሃል፤ ወደማትወደውም ይወስድሃል፤* /ዮሐ.፳፩፥፲፰/ በማለት ጌታችን የነገረው ቃል ትዝ አለውና አሟሟቱን የሚያመለክት መኾኑን አስታውሶ ወደ ሮም ተመልሶ ወንጌልን መስበኩን ቀጠለ፡፡

በሮማውያን ሕግ ቅጣት የተፈረደበት ወንጀለኛ የሮም አገር ተወላጅ ከኾነ የወንጀሉ ክብደትና ቅለት እየታየ ግርፋት ወይም ሞት ይፈረድበት ነበር እንጂ በአንድ ወንጀል ሁለት ቅጣት አይቀጣም ነበር፡፡ ወንጀለኛው የውጪ አገር ዜጋ (ከሮም ውጪ) ከኾነ ግን ለምሳሌ ቅጣቱ ግርፋት ከኾነ ከተገረፈ በኋላ እስራት ይጨመርበታል፤ ቅጣቱ ሞት ከኾነም ከገረፉት በኋላ በመስቀል ወይም በሌላ መሣሪያ ይገድሉት ነበር፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ዜግነቱ ሮማዊ አልነበረምና በግርፋትም፣ በእስራትም በሞትም እንዲቀጣ ተፈረደበት፡፡

እንደ ሥርዓታቸውም አስቀድመው ከገረፉት በኋላ ሊሰቅሉት ሲሉ ወታደሮቹን *እንደ ክብር ንጉሥ እንደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ አቁማችሁ ሳይኾን፣ ዘቅዝቃችሁ ስቀሉኝ* አላቸው፡፡ እነርሱም እንዳላቸው አድርገው ሐምሌ ፭ ቀን ዘቅዝቀው ሰቅለውታል፡፡ በመስቀል ላይ ሳለም ተከታዮቹን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ካዘዛቸው በኋላ ነፍሱን ለእግዚአብሔር ሰጠ፡፡ ሥጋውንም ደቀ መዝሙሩ መርቄሎስ ሽቱ ቀብቶ፣ በነጭ ሐር ገንዞ ዛሬ ቫቲካን በምትባለዋ ስፍራ በክብር ቀብሮታል፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ

ቅዱስ ጳውሎስ ለአገልግሎት ከመጠራቱ በፊት ሳውል ይባል ነበር፡፡ ከኦሪቱ ምሁር ከገማልያል ሕገ ኦሪትንና መጻሕፍተ ነቢያትን ተምሯል፡፡ ለሕገ ኦሪት ቀናኢ ከመኾኑ የተነሣም የክርስቶስ ተከታዮችን ኹሉ ያሳድድ ነበር፡፡ ቅዱስ እስጢፋኖስ በድንጋይ ተደብድቦ ሲገደልም የገዳዮቹ ልብስ ጠባቂ ነበር /ሐዋ.፯፥፶፰፤ ፳፪፥፳/፡፡ ክርስቲያኖችን ለማሳደድ ወደ ደማስቆ ሲሔድ ለሐዋርያነት ተጠርቷል /ሐዋ.፱፥፩-፴፩፤ ፳፪፥፩-፳፩/፡፡ ለሐዋርያነት ከተጠራበት ጊዜ ጀምሮ በመላው ዓለም እየተዘዋወረ ወንጌልን በመስበክ ብዙዎችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አሳምኗል፡፡

ሲሰብክም ጣዖት አምላኪ፣ ሕመምተኛ፣ ችግረኛ፣ አረማዊና አይሁዳዊ እየመሰለ ብዙዎችን አስተምሮ ለእግዚአብሔር መንግሥት አቅርቧል /፩ኛቆሮ.፱፥፲፱-፳፫/፡፡ ወንጌልን በመስበኩ ምክንያትም ከአይሁድና ከአረማውያን ዘንድ ብዙ መከራና ስቃይ ደርሶበታል፡፡ ዐረብ፣ አንጾኪያ፣ እልዋሪቆን፣ ሊቃኦንያ፣ ሦርያ፣ ግሪክና ልስጥራን ካስተማረባቸው አገሮች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ በቃል ካስተማረው ሌላ በመጽሐፍ ቅዱስ በስሙ የተመዘገቡ ፲፬ መልእክታት አሉት፡፡

አገልግሎቱን ሊፈጽም ሲልም የሮም ንጉሥ ኔሮን ቄሣር የክርስቲያኖች ቍጥር እየጨመረ የመጣው በቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት በመማረካቸው ምክንያት መኾኑን ተረድቶ፤ ይልቁንም የቤተ መንግሥቱ ሰዎች ሳይቀር በቅዱስ ጳውሎስ በመማረካቸው ተቈጥቶ ቅዱስ ጳውሎስን ወደ ፍርድ ሸንጎው አስቀረበው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በቀኝ እጁ ከሰንሰለቱ ጋር መስቀሉን ይዞ ንጉሡንና ወታሮቹን ሳይፋራ የኢየሱስ ክርስቶስን የእግዚአብሔር ልጅነትና አምላካዊ ሥልጣኑን ይመሰክር ነበር፡፡ ንጉሡም በቍጣ ይሙት በቃ ፈረደበት፡፡

ከላይ እንደ ተገለጸው ሮማውያን የሞት ፍርድ ሲፈርዱ የሚቀጣው ሰው የሌላ አገር ዜጋ ከኾነ ከፍርዱ ውጪ ተጨማሪ ቅጣት ይቀጡትና ይገድሉት ነበር፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ ግን የሮም ዜግነት ስለ ነበረው ሳይገርፉ በአንድ ቅጣት ብቻ በሰይፍ እንዲገደል ወስነውበታል፡፡ ወደሚገደልበት ስፍራ ሲወስዱትም በንግግሩና በአስተያየቱ ኹሉ ምንም ፍርኀት አይታይበትም ነበር፡፡ እንዲያውም በጦርነት ድል አድርጎና ማርኮ እንደ ተመለሰ ወታደር ይደሰት ነበር እንጂ፡፡ ለሚገድሉትም ይቅርታን ይለምን ነበር፡፡ በገዳዮቹና በተከታዮቹ ፊትም የክርስትና ሽልማቱ የእግዚአብሔር መንግሥት መኾኑን የሚያስገነዝብ ቃል እያስተማረ እግዚአብሔር የሚሰጠውን የጽድቅ አክሊል ለመቀበል ይቻኮል ነበር /፪ኛቆሮ.፬፥፮-፲፰/፡፡

ሊገድሉት ሲወስዱትም ከንጉሥ ኔሮን ወገን የኾነችውን የአንዲት ብላቴና መጐናጸፊያ *ዛሬ እመልስልሻለሁ* ብሎ ከተቀበላት በኋላ *መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፤ ሩጫዬን ጨርሻለሁ፡፡ ሃይማኖቴን ጠብቄአለሁ፤ ወደፊትም የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል፤* በማለት በመልእክቱ እንደ ተናገረው /፪ኞጢሞ.፬፥፯-፰/፣ ፊቱን በንጉሡ ልጅ መጐናጸፊያ ተሸፍኖ አንገቱን በሰይፍ ተቀልቶ አገልግሎቱን በሰማዕትነት ፈጽሟል፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ራሱን ከአንገቱ ጋር ቢያደርጉት እንደ ቀድሞው ደኅና ኾኖላቸው በክብር ገንዘው ቀብረውታል፡፡

ሰያፊው ቅዱስ ጳውሎስን እንደ ገደለው ለመናገር ወደ ንጉሡ ሲመለስም ያቺ መጐናጸፊያዋን የሰጠችው ብላቴና *ጳውሎስ ወዴት አለ?* አለችው፡፡ እርሱም *ራሱን ተቈርጦ በመጐናጸፊያሽ ተሸፍኖ ወድቋል* ሲላት *ዋሽተሃል፤ እነሆ ጴጥሮስና ጳውሎስ በእኔ በኩል አልፈው ሔዱ፡፡ እነርሱም የመንግሥት ልብስ ለብሰዋል፡፡ በራሳቸውም በዕንቍ ያጌጡ አክሊላትን አድርገዋል፡፡ መጐናጸፊያዬንም ሰጡኝ፡፡ ይህችውም እነኋት፤ ተመልከታት* ብላ ሰጠቸው፡፡ ከእርሱ ጋራ ለነበሩትም አሳየቻቸው፡፡ አይተውም አደነቁ፤ ስለዚህም በጌታቻን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡

እኛም ቅዱሳን ሐዋርያት ያቆዩልንን የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ጠብቀን፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን እንድንኖርና በመጨረሻም የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንድንበቃ የቅዱሳኑ ጸሎት ይርዳን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሐምሌ ፭ ቀን፤

ዜና ሐዋርያት፡፡

የአሜሪካ ማእከል ልዩ ዐውደ ጥናት ሊያካሒድ ነው

ሐምሌ ፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአሜሪካ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል *የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተዋጽኦ* በሚል ርእስ በፕሪንስተን ከሚገኘው /The Institute for Advanced Semitic Studies and Afroasiatic Studies/ በመባል ከሚታወቀው የሴሜቲክና የአፍሮ እስያ ከፍተኛ ምርምርና ጥናት ተቋም ጋር በመተባበር ሐምሌ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ልዩ ዐውደ ጥናት ያካሒዳል።

ዐውደ ጥናቱ በዋናነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በተለያየ ዘርፍ ለኢትዮጵያና ለዓለም ያበረከተችውን አስተዋጽኦ በጥልቀት እንደሚዳስስና ቤተ ክርስቲያኗ ይህንን አስተዋጽኦና ሚናዋን በዘመናችን እንዴት ማስቀጠል እንዳለባት እንደሚመክር አዘጋጆቹ አስታውቀዋል።

ይህ ዐውደ ጥናት በታዋቂው የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ መደረጉ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን አስተዋጽኦ ለዓለም ለማስተዋወቅ መልካም አጋጣሚ እንደሚፈጥርም ተጠቁሟል፡፡

በዐውደ ጥናቱ የፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር የኾኑት ኤፍሬም ይስሐቅ *የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን* በሚል ርእስ ያሳተሙት መጽሐፍ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ስለሚኖረው ፋይዳና በመጽሐፉ ጠቅላላ ይዘት ላይ ሰፊ ውይይት ይደረጋል፡፡

በአሜሪካ አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት መልካም ፈቃድ በሚዘጋጀው በዚህ ልዩ ዐውደ ጥናት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ካህናት፣ ምሁራን፣ የአሜሪካ ግዛቶችና የአካባቢው ምእመናን፣ እንደዚሁም የውጪ ሀገር ዜጎችና ተጋባዥ እንግዶች እንደሚሳተፉበት ከጥናቱ አዘጋጆች ለመረዳት ተችሏል።

ቅዱስ ታዴዎስ ሐዋርያ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

ሐምሌ ፪ ቀን ከ፲፪ቱ ሐዋርያት አንዱ የኾው የቅዱስ ታዴዎስ የዕረፍቱ መታሰቢያ በዓል ነው፡፡ ከመጽሐፈ ስንክሳርና ከገድለ ሐዋርያት ያገኘነውን የሐዋርያው ታዴዎስን ታሪክ በአጭሩ እነሆ፤

ቅዱስ ታዴዎስ አባቱ እልፍዮስ ይባላል /ማቴ.፲፥፫/፡፡ ሐዋርያው *ታዴዎስ ልብድዮስ*፣ *የያዕቆብ ልጅ ይሁዳ* እየተባለም ይጠራል /ሉቃ.፮፥፲፮፤ ዮሐ.፲፵፥፳፪፤ ሐዋ.፩፥፲፫፤ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት/፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሐዋርያት አስቀድሞ ቅዱስ ታዴዎስን እንደ መረጠው መጽሐፈ ስንክሳር ይናገራል፡፡

ቅዱስ ታዴዎስ በየአገሩ እየተዘዋወረ ወንጌልን በመስበክ ከአይሁድና ከአረማውያን ወገን ብዙዎችን በክርስትና ሃይማኖት አሳምኖ አስጠምቋል፡፡ አንድ ቀን ወደ ሀገረ ስብከቱ ወደ ሦርያ ለስብከተ ወንጌል ሲሔድ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጐልማሳ አምሳል ተገልጦ *ወዳጄ ታዴዎስ ሆይ፣ እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ* ብሎ ሰላምታ ሰጥቶት ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም የሐዋርያት አለቃ ነውና እንደ አባትነቱ ወደ ሦርያ ለማድረስ አብሮት ሔዶ ነበረ፡፡ ከከተማዋ አጠገብ ሲደርሱም አንድ ሽማግሌ በሮችን ጠምደው ሲያርሱ አገኙ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ሽማግሌውን ምግብ በለመናቸው ጊዜ *በሮቼን ጠብቁ* ብላዋቸው ምግብ ሊያመጡላቸው ወደ ቤታቸው ሔዱ፡፡

ሽማግሌው እስኪመለሱ ድረስም ቅዱስ ጴጥሮስ በሮችን ጠምዶ ሠላሳ ትልም ካረሰ በኋላ ቅዱስ ታዴዎስም በዚያ የነበረውን የሥንዴ ዘር መዝራት ጀመረ፡፡ የተዘራው ዘርም ወዲያዉኑ በቅሎ፣ አድጎ፣ እሸት ኾነ፡፡

ሽማግሌው ምግብ ይዘው ከቤታቸው ሲመለሱም ሐዋርያት ያደረጉትን ተአምር አይተው ደነገጡ፡፡ ከእግራቸው ሥር ወድቀው ለሐዋርያት ከሰገዱላቸው በኋላም *እናንተ ከሰማይ የወረዳችሁ አማልክት ናችሁን?* አሏቸው፡፡ እነርሱም *እኛ የእግዚአብሔር ባሮች እንጂ አማልክት አይደለንም* አሉ፡፡

ሽማግሌውም *ስላደረጋችሁልኝ በጎ ሥራ በምትሔዱበት ቦታ ኹሉ ልከተላችሁን?* ባላቸው ጊዜ *ይህንን ልታደርግ አይገባም፤ ነገር ግን በሮችን ለጌታቸው መልስና በቤትህ የምንበላውን ታዘጋጅልን ዘንድ ለባለቤትህ ንገራት፡፡ እኛ ወደዚህች ከተማ ገብተን እግዚአብሔር እስከሚጠራን ጊዜ ድረስ እንቆያለንና* አሏቸው፡፡

ሽማግሌውም ከሥንዴው እሸት ይዘው፣ በሮችን እየነዱ ወደ ከተማ ሲሔዱ የከተማው ሰዎች ወቅቱ የእርሻ እንጂ የእሸት ጊዜ አልነበረምና እየተገረሙ *ይህንን እሸት ከወዴት አገኘኸው?* አሏቸው፡፡ ሽማግሌው ግን ምላሽ አልሰጧቸውም ነበር፡፡

ሽማግሌው ሐዋርያት እንደዘዟቸው በሮችን ለጌታቸው መልሰው ቤታቸውን አዘጋጅተው ራት እንድታዘጋጅላቸው ለሚስታቸው ነገሩ፡፡

ወሬውን የከተማው መኳንንት በሰሙ ጊዜም ሽማግሌውን *በክፉ አሟሟት እንዳትሞት እሸቱን ከወዴት እንዳገኘኸው ንገረን* ብለው መልእክተኞችን ላኩባቸው፡፡ ሽማግሌውም *ሕይወት ከእኔ ጋራ ሳለ ሞትን አልፈራም* ካሉ በኋላ ሐዋርያት ያደረጉትን ኹሉ ነገሯቸው፡፡

መኳንንቱ *ሐዋርያቱን አምጣቸው* ሲሏቸውም ሽማግሌው ወደ እርሳቸው ቤት ሲመጡ ማግኘት እንደሚችሉ ነገሯቸው፡፡

መኳንንቱም ሰይጣን ልቡናቸዉን ስለ ለወጠው ሐዋርያቱን ለመግደል ተነሳሡ፡፡ እኩሌቶቹ ግን *አምላካቸው ኢየሱስ የሚሹትን ኹሉ እንደሚያደርግላቸው ሰምተናልና ልንገድላቸው አንችልም፡፡ ነገር ግን አመንዝራ ሴት ወስደን በከተማው በር ርቃኗን እናስቀምጣት፡፡ እርሷን ሲያዩ ወደ ከተማችን አይገቡም፤* አሉ፡፡

እንደተባባሉትም ሴትዮዋን በከተማው በር ርቃኗን አስቀመጧት፡፡ ሐዋርያው ታዴዎስ ባያት ጊዜም *ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ወደ ከተማው ገብተን በከበረ ስምህ እስክንሰብክ ድረስ ይህቺን ሴት በአየር ላይ ይሰቅላት ዘንድ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን ላክልን* ብሎ ጸለየ፡፡

ጌታችን ጸሎቱን ተቀብሎት ሴትዮዋ በተሰቀለች ጊዜም የከተማው ሰዎችና መኳኳንንቱ ኹሉ እያዩአት *አቤቱ ፍረድልኝ* እያለች ትጮኽ ጀመር፡: መኳንንቱ ግን ሰይጣን ልቡናቸውን አጽንቶታልና የሐዋርያትን ትምህርት አልተቀበሉም፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ታዴዎስ ወደ እግዚአብሔር በጸለዩ ጊዜም ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤልን ልኮ የሰዎቹን ልቡና የማረኩ መናፍስትን ርኩሳንን አባረረላቸው፡፡ ሰዎቹም የሐዋርያትን ትምህርት ተቀብለው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡

ሐዋርያው ታዴዎስም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ካጠመቃቸው በኋላ ኤጰስ ቆጶሳትን፣ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው፡፡ በአየር ላይ የተሰቀለችውን ሴትም አውርዶ ዲያቆናዪት አደርጎ ሾማት፡፡

በሐዋርያት እጅም ብዙ ድንቆችና ተአምራት ተደረጉ፡፡ ዕውሮች አዩ፤ ሐንካሶች ቆመው ሔዱ፤ ዲዳዎች ተናገሩ፤ ደንቆሮዎች ሰሙ፤ ለምጻሞች ነጹ፤ አጋንንትም ካደሩባቸው ሰዎች እየወጡ ተሰደዱ፤ ሙታንም ተነሡ፡፡ የከተማው ሰዎችም ይህንን ተአምር አይተው በቅዱሳን ሐዋርያት አምላክ በእግዚአብሔር አመኑ፡፡

አንድ ሰይጣን ያደረበትና ገንዘብ የሚወድ ጐልማሳ ባለጸጋም ወደ ሐዋርያው ታዴዎስ መጥቶ ሰገደለትና *የእግዚአብሔር አገልጋይ ሆይ እድን ዘንድ ምን ላድርግ?* ሲል ጠየቀው፡፡

ሐዋርያው ታዴዎስም *እግዚአብሔርን በፍጹም ልብህ፣ በፍጹም ኀይልህ ውደደው፡፡ አትግደል፤ አትስረቅ፤ አታመንዝር፡፡ በአንተ ሊደረግብህ የማትሻውን በሌላው ላይ አታድርግ፡፡ ደግሞም ገንዘብህን ሸጠህ ለድኆችና ለምስኪኖች ብትሰጥ በሰማያት ለዘለዓለም የሚኖር ድልብ ታገኛለህ* አለው፡፡

ጐልማሳውም ይህንን በሰማ ጊዜ ተቈጥቶ ሐዋርያውን አነቀው፡፡ የእግዚአብሔር ኀይል በይረዳው ኖሮ ሐዋርያው ከመታነቁ ጽናት የተነሣ ዓይኖቹ ሊወጡ ነበር፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም *የክርስቶስን አገልጋይ እንዴት ደፍረህ ታንቃለህ?* ባለው ጊዜ ጐልማሳው ቅዱስ ታዴዎስን ለቀቀው፡፡

ያን ጊዜም ቅዱስ ታዴዎስ *ጌታችን ሀብታም መንግሥተ ሰማያት ከሚገባ ይልቅ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፍ ይቀላል ሲል በእውነት የተናገረው እንዳንተ ላለው ሀብታም ነው* አለው፡፡

ጐልማሳውም *ይህ ሊኾን አይችልም* ባለ ጊዜ ሐዋርያው ታዴዎስ በመንገድ ሲያልፍ ያገኘውን ባለ ግመል አስቁሞ መርፌ ገዝቶ ሊያሳየው ወደደ፡፡ መርፌ ሻጩም ሐዋርያውን ለመርዳት ፈልጎ ቀዳዳው ሰፊ የኾነ መርፌ አመጣለት፡፡

ቅዱስ ታዴዎስም *እግዚአብሔር ዋጋህን ይክፈልህ፤ ነገር ግን በዚህች አገር የእግዚአብሔር ክብር ይገለጥ ዘንድ ቀዳዳው ጠባብ የኾነ መርፌ አምጣልን* አለው፡፡

ሐዋርያው ቀዳዳው ጠባብ የኾነውን መርፌ ተቀብሎም *ኀይልህን ግለጥ* ብሎ ወደ ጌታችን ጸለየ፡፡ እጁንም ዘርግቶ ባለ ግመሉን *በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ከግመልህ ጋር በመርፌ ቀዳዳው ውስጥ እለፍ* አለው፡፡ ሰውየውም እስከ ግመሉ ድረስ በመርፌ ቀዳዳው አለፈ፡፡

ዳግመኛም *ሕዝቡ የፈጣሪያችንን የክርስቶስን ኀይል ይረዱ ዘንድ ዳግመኛ ገብተህ እለፍ* አለውና ሦስት ጊዜ በመርፌ ቀዳዳው አለፈ፡፡

ሕዝቡም ይህንን ተአምር አይተው *ከቅዱሳን ሐዋርያት አምላክ ከሕያው እግዚአብሔር ልጅ ከኢየሱስ በቀር ሌላ አምላክ የለም* እያሉ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ተናገሩ፡፡

ያ ጐልማሳ ባለጸጋም ከሐዋርያው ታዴዎስ እግር በታች ወድቆ ሰገደና *ኀጢአቴን ኹሉ ይቅር በለኝ፡፡ ገንዘቤንም ኹሉ ወስደህ ለድኆችና ለምስኪኖች አከፋፍልኝ* አለው፡፡ ሐዋርያውም እንደ ለመነው አደረገለት፡፡

የክርስትናን ሃይማኖትን ሕግ አስተምሮም አጠመቀውና ሥጋውንና ደሙን አቀበለው፡፡ ኹሉንም በቀናች የክርስትና ሃይማኖት አጸናቸው፡፡ ከዚያ በኋላም ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ታዴዎስ ከዚያች ከተማ ወጡ፤ ሕዝቡም በሰላም ሸኟቸው፡፡

ቅዱስ ታዴዎስ በየአገሩ እየተዘዋወረ ወንጌልን ሲሰብክ ቆይቶ ከአይሁድና ከአረማውያን ዘንድ ብዙ መከራ ከደረሰበት በኋላ አገልግሎቱን ፈጽሞ ሐምሌ ፪ ቀን በሰላም ዐርፏል፡፡

በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ዘመንም ሐምሌ ፳፱ ቀን የከበረ ዐፅሙ ከሦርያ ወደ ቍስጥንጥንያ ከተማ ፈልሷል፡፡ በዚያች ዕለትም ቤተ ክርስቲያን ሠርተው የቅዱሱን ዐፅም በውስጧ አስቀምጠውታል፡፡ ከዐፅሙም ብዙ ድንቆችና ተአምራት ተገልጠዋል፡፡

ኹላችንንም የሐዋርያው ጸሎት ይጠብቀን፤ በረከቱም ይደርብን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሐምሌ ፪ እና ፳፱ ቀን፤

ገድለ ሐዋርያት፣ ፲፱፻፺፬ ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፣ ገጽ ፻፷፭-፻፸፩፡፡

ሊቀ ማእምራን ወመጋቤ ሐዲስ ወልደ ሰንበት ባይነሳኝ ዐረፉ

ሐምሌ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ቴዎድሮስ ኃይሉ

በሕይወት ዘመናቸው ኹሉ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በቅንነትና በታማኝነት ሲያገለግሉ የነበሩት ታላቁ የቤተ ክርስቲያን ሊቅ፣ የትሕትናና የጸሎት አባት ሊቀ ማእምራን ወመጋቤ ሐዲስ ወልደ ሰንበት ባይነሳኝ ዐረፉ፡፡

0001

ከአቶ ባይነሳኝ ላቀውና ከወ/ሮ በፍታ ተሾመ ሐምሌ ፲፩ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም በላስታ ደብረ ዘመዶ አካባቢ የተወለዱት፤ የአቋቋም፣ የቅኔ፣ የፍትሐ ነገሥትና የሐዲስ ኪዳን ትርጓሜ መምህሩ መጋቤ ሐዲስ ወልደ ሰንበት፣ ልዩ የትርጓሜ ጸጋ የተሰጣቸው፤ ፍቅረ ነዋይ የራቀላቸውና የሚያስተምሩትን ቃለ እግዚአብሔር በሕይወት የኖሩ አባት ነበሩ፡፡

መጋቤ ሐዲስ ወልደ ሰንበት ከ፲፱፻፷፭ ዓ.ም ጀምሮ በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በመካነ ነገሥት ግምጃ ቤት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ለአምስት ዓመታት ያህል በምክትል መምህርነት ያገለገሉ ሲኾን፣ የጉባኤው መምህር የኔታ ክፍሌ ካረፉበት ከ፲፱፻፸ ዓ.ም ጀምሮ እስከ ዕለተ ዕረፍታቸው ድረስም ጉባኤ ተክለው፣ ወንበር ዘርግተው በማስተማር በርካታ ሊቃውንትን አፍርተዋል፡፡

ከመካነ ነገሥት ግምጃ ቤተ ማርያም ቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ቤት ደቀ መዛሙርት ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ መጋቤ ሐዲስ ወልደ ሰንበት ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በሕክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ፹ ዓመታቸው ሐምሌ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተዋል፡፡

ሥርዓተ ቀብራቸውም ሐምሌ ፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በመካነ ነገሥት ግምጃ ቤት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ይፈጸማል፡፡

የሊቁን የመጋቤ ሐዲስ ወልደ ሰንበትን አጠቃላይ አገልግሎትና ሙሉ የሕይወት ታሪክ ወደ ፊት በስፋት ይዘን እንቀርባለን፡፡