01desie

የደሴ ማእከል የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ሊያካሂድ ነው

ግንቦት 19 ቀን 2007 ዓ.ም

ከደሴ ማእከል

01desieበማኅበረ ቅዱሳን ደሴ ማእከል የአካባቢውን ማኅበረ ምእመናን በማሳተፍ ወደ ታሪካዊው ደብር ቦሩ ደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ሰኔ 7 ቀን 2007 ዓ.ም የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ያካሂዳል፡፡

መርሐ ግብሩ የተዘጋጀበት ዓላማ ምእመናን መንፈሳዊና ማኅበራዊ ሕይወታቸውን ለማነጽ፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀ መንፈሳዊ ጉዞ ምን መምሰል እንዳለበት ግንዛቤ ለመፍጠር፤ እንዲሁም ወደ ገዳማትና አድባራት በመሄድ በረከት እንዲያገኙ እንደሆነ የማእከሉ ጸሐፊ ዲ/ን ሰሎሞን ወልዴ ገልጸዋል፡፡

በመርሐ ግብሩም የአባቶች ቡራኬ፣ ትምህርተ ወንጌል፣ ያሬዳዊ መዝሙር፣ ምክረ አበው፣ ቅኔ፣ ጉብኝት፣ የፕሮጀክት ምረቃ እንደሚኖሩ ተገልጿል፡፡

የጉዞው መነሻ ቦታ የደሴ ማእከል ጽ/ቤት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ከጠዋቱ 12፡00 ስዓት ሲሆን፤ የጉዞው ሙሉ ወጪ (ቁርስና ምሳን ጨምሮ) 60 ብር እንደሆነ ዲ/ን ሰሎሞን ገልጸዋል፡፡

ምእመናን የጉዞ ትኬቱን በማእከሉ ጽ/ቤት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ግቢ ውስጥ፣ በማኅበረ ቅዱሳን መዝሙር ቤት፣ በደብረ ቤቴል ቅድስት ሥላሴና ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን መዝሙር ቤት (ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን መግቢያ በር)፣ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን መዝሙር ቤትና ተድባበ መዝሙር ቤት እስከ ግንቦት 30 ቀን 2007 ዓ.ም ድረስ ማግኘት እንደሚችሉ የደሴ ማእከል ጸሐፊ አስታውቀዋል፡፡

እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ ነው፡፡ ዕብ 11:1

ግንቦት 10ቀን 2007 ዓ.ም

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

እምነት የሚለው የግእዝ ቃል ሲሆን ፔስቲስ የሚልውን የግሪክ ቃል የሚተካ ነው፡፡ ትርጉሙም አንድን ነገር መቀበልና ማሳመን ሞራላዊ ማረግጋገጫ መስጠት ማለት ነው፡፡ እምነት ማለት እውነትን መቀበልና ልባችንን ለዚህ እውነት መስጠት ማለት ነው፡፡ ስለዚህ እምነት ተስፋ ስለምናደርገው እውነት የሚያስረግጥ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው። “እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ፥ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው።” (ዕብ 11:1) እንዲል፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስእንዲህ አለ:- “አምናችሁም በጸሎት የምትለምኑትን ሁሉ ትቀበላላችሁ አላቸው።” (ማቴ 21:22) እንደገናም ለደቀ መዛሙርቱ እንዲህ አላቸው:- የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል እምነት ቢኖራችሁ፥ ይህን ተራራ። ከዚህ ወደዚያ እለፍ ብትሉት ያልፋል፤ የሚሳናችሁም ነገር የለም። ” (ማቴ 17:20) “ስለዚህ እላችኋለሁ፥ የጸለያችሁትን የለመናችሁትንም ሁሉ እንዳገኛችሁት እመኑ፥ ይሆንላችሁማል።” (ማር 11:24) በማለትጌታችን በተለያዩ ጊዜና ቦታ አስተምሯል፡፡ ስለዚህ ጸሎታችን በእምነት ሊሆን ይገባል፤ በእምነት ስንጸልይ እግዚአብሔር ጸሎታችንን ይሰማል::

€œእምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ፣ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው። (ዕብ. 11:1ሰው ተስፋ ካለው የማይታየውን እንዳየ ሆኖ ይረዳል፡፡ እምነት ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅር የምንገልጥበት፣ እርሱን ደስ የምናሰኝበት ጥበብ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እምነት እግዚአብሔርን ደስ የምናሰኝበት ጥበብ መሆኑን ሲያስረዳ ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይ ቻልም ብሏል፡፡ ዕብ. 11፣6፡፡

የእምነት ፍሬ በእምነት እንድንኖርና እንድንሄድ ይረዳናል:: “በሁሉም ላይ ጨምራችሁ የሚንበለበሉትን የክፉውን ፍላጻዎች ሁሉ ልታጠፉ የምትችሉበትን የእምነትን ጋሻ አንሡ” (ኤፌ 6:16) እምነት የሚንበለበሉትን የክፉውን ፍላጻዎች ሁሉ ልናጠፉ የምትችልበት ጋሻ ነው::

ከላይ እንዳየነው እምነት ከመንፈስ ቅዱስ የሚመነጭ የመንፈስ ፍሬ ነው:: ይህም ከመንፈስ ቅዱስ የሚገኝሕያው ፍሬ ነው:: እንዲሁም ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም:: ዕብ 11:2 እንዲህ ይላል:- “ለሽማግሌዎች የተመሰከረላቸው በዚህ ነውና።”(ዕብ 11:2) እምነት መልካም ምስክርነትን ያመጣል::

በእምነት ጥንካሬአቸው የተመሰከረላቸው ሰዎች በእግዚአብሔር በመታመናቸው በሚያቃጥል የእሳት ነበልባል ውስጥ በመጣል፣ ወደ አንበሳ ጉድጓድ በመወርወር፣ በሰይፍ በመተርተር እምነታቸውን ገልጠዋል፡፡ እግዚአብሔርም በቅዱሳን የእምነት ጥንካሬ የልበ ደንዳኖችን ልብ ማርኳል፡፡ንጉሡ ናቡከደነጾር ለጣዖት አንሰግድም ብለው እምነታቸውን የገለጡትን ሠለስቱ ደቂቅን ርዝማኔው አስራ ስድስት ክንድ ከሚደርስ የእሳት ነበልባል ውስጥ በሰንሰለት አስሮ ቢወርወራቸውም ከሰውነታቸው አንዳች ሳይቃጠል በመዳናቸው፤በእርሱ የታመኑትን ባሪያዎቹን ያዳነ የሲድራቅ፣ የሚሳቅና የአብደናጎ አምላክ ይባረክ ዳን. 3፣25 ሲል እግዚአበሔርን አክብሯል፡፡

በዘመነ ሐዲስ በሰው ፍቅር ተስቦ ወደዚህ ዓለም የመጣው ቸሩ አምላክ ለአገልግሎት ከመረጣቸው ሰዎች አንዳንዶቹ ምንም ዓይነት መሠረታዊ የሃይማኖት ዕውቀት አልነበራቸውም፡፡ እግዚአብሔር እነዚህን አላዋቂዎችን የመረጠው በዘመኑ በዕውቀታቸው የሚታበዩ ሰዎችን ዕውቀት ከንቱ ለማድረግ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ጌታችን የዓለምን ጥበብ ከንቱ ለማድረግ አላዋቂዎችን እንደመረጠ ሲያስረዳ፤እግዚአብሔር ጥበበኞችን እንዲያሳፍር የዓለምን ሞኝ ነገር መረጠ፤ ብርቱንም ነገር እንዲያሳፍር እግዚአብሔር የዓለምን ደካማ ነገር መረጠ፤ እግዚአብሔር የሆነውን ነገር እንዲያጠፋ የዓለምን ምናምንቴ ነገር የተናቀውንም ነገር ያልሆነውንም መረጠ፡፡ ብሏል፡፡ 1ኛቆሮ.1፣26-29፡፡

እግዚአብሔር ለእምነት አገልግሎት ሰዎችን ሲመርጥ ሞኞች ጠቢባን ይሆናሉ፤ አላዋቂዎች ሀብተ እውቀት ያገኛሉ፤ ደካማዎች ብርቱዎች ይሆናሉ፡፡ አላዋቂ የነበሩት ተከታዮቹ ጠቢባን፤ ደካማ የነበሩት ብርቱዎች እስከሚሆኑ ድረስ ለቀጣይ የእምነት ሕይ ወታቸው ብርታት እንዲሆናቸው የተለያዩ ጥያቄዎችን ለጌታችን ያቀርቡ ነበር፡፡

ጌታችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይከተሉ ከነበሩ ሰዎች ለጌታችን ካቀረቡት ጥያቄ አንዱ አለማመኔን እርዳው የሚል ነው፡፡ ጌታችን የቃሉን ትምህርት ሰምተው የእጁን ተአምራት አይተው የተከተሉትን በሕይወት ሰጪ ትምህርቱ በነፍስ የተመሙትን ተስፋ የቆረጡትን፣ ባዶነት የሚሰማቸውን መንፈሳዊ ዝለት የገጠማቸውን ሲፈውስ፤ በተአምራቱ ደግሞ በሕማመ ሥጋ የታመሙትን ፈውሷል፡፡ የጌታችንን ሕይወት ሰጪ ትምህርት ፈልገው የተከተሉ አብዛኛዎች በተከፈለ ልብ ነበር፡፡ መድኃኒታችን የተከፈለ ልብ ያላቸውን ማረጋጋት፣ ያዘኑትን ማጽናናት ባሕርዩ በመሆኑ ድክመታቸውን ሳይሸሸጉ የሚቀርቡትን ፈጣን ምላሽ ይሰጣል፡፡

የጌታችን ደቀ መዛሙርት ልጁን እንዲፈውሱለት የወሰደው ሰው፤ ከእርሱና ከደቀ መዛሙርቱ የእምነት ማነስ የተነሣ ፍቱን መፍትሔ ቢያጣም ከጌታችን ዘንድ መጥቶ የእምነቱ ጉድለት በጌታችን እንዲስተ ካክልለት የልጁን ሕማም ሁኔታ ከዘረዘረ በኋላ፤ ቢቻልህ ግን እዘንልን እርዳን ማር.9፣22 የሚል ጥያቄ አቅርቧል፡፡ ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ ቢቻልህ የሚለውን የጥርጣሬ ቃል ቢቻልህ ትላለህ፤ ለሚያምን ሰው ሁሉ ይቻላል፡፡ በሚል ቃል ሲያርመው የተቸገረው ሰው አለማመኑ በእርሱ እንዲጠገንለት በታላቅ ድምፅ አምናለሁ፤ አለማመኔን እርዳው ብሎታል፡፡ ይህ ሰው አምናለሁ አለማመኔን እርዳው በማለት በእምነት ሕይወት ውስጥ ያለበትን ችግር ሳይሸሸግ መናገሩን ማስተዋል ያስፈልጋል፡፡

ምክንያቱም እያመን የማናምን፣ ንስሐ እየገባን የማንፀፀት፣ እየቆረብን ለሥጋ ወደሙ ክብር የማንሰጥ፣ እየቀደስን ያልተቀደስን ብዙዎች ነን፡፡ እኛም እናምናለን ነገር ግን እምነታችን በአንተ ይታገዝ እርዳን ብለን መጠየቅ አለብን፡፡ ብዙ ሰዎች ክርስቶስ መወለዱን፣ መጠመቁን፣ ከሙታን መነሣቱን (ትንሣኤውን መግለጡን) ያምናሉ፡፡ በዚህ ሕይወት ውስጥ ያላቸውን ድርሻ እና ተስፋ ግን ይጠራጠራሉ፡፡ በሌላ አነጋገር እያመንን በእምነት ሕይወት ውስጥ አንኖርም ለዚህ ማለዘቢያ ግን እምነታችን፣ አለማወቃችንና ድካማችን በጌታችን እንዲደገፍ መማጸን ነው፡፡

በማቴዎስ ወንጌል ቅዱሳን ሐዋርያት የታመመውን ልጅ ለመፈወስ አቅም ያጡበትን ምክንያት ለመረዳት፤እኛ ልናወጣው ያልቻልን ስለምንድነው? ሲሉ ጌታችንን ጠይቀውታል /ማቴ.17፣19/፡፡ ይህ ጥያቄ የእኛም ጥያቄ ነው፡፡ እኔ የተሰጠኝን ሓላፊነት ያልተወጣሁት ስለምንድነው? ያልቆረብኩት ስለምንድነው? ከልቤ ውስጥ የሚጉላላውን ቂም ያላወጣሁት ስለምንድነው? የበደልኩትን ያልካስኩት ስለምንድነው? የሚፈታተነኝን የሰይጣን ፈተና ማለፍ ያልቻልኩት ስለምንድነው? መንፈሳዊ ሕይወቴ ማደግ ያልቻለው፣ ራሴን ማወቅ መረዳት ያልቻልኩት ስለምንድነው? ብለን እንድንጠይቅ የቅዱሳን ሐዋርያት ጥያቄ ይጋብዘናል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት እግዚአብሔር ከጎናቸው እያለ የእምነት ጉድለት ስለታየባቸው ማድረግ የሚገባቸውን ለመፈጸም አልቻሉም፤ ነገር ግን ልባቸውን የፈነቀለውን አንገብጋቢ ጥያቄ መጠየቃቸው መልካም ነበር፡፡ ምክንያቱም በእምነት ሊያደርጉት የሚቻላቸውን ነገር ማድረግ የተሣናቸው ስለእምነታቸው ጉድለት መሆኑን ጌታችን አስረግጦ እንዲህ በማለት ነግሯቸዋል፡፡ እውነት እላችኋለሁ የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል እምነት ቢኖራችሁ ይህን ሾላ ተነቅለህ በሌላ ቦታ ተተከል ብትሉት ይታዘዝላች ኋል ሉቃ.17፣6 ብሏቸዋል፡፡ ማመን፣ ያመኑትን ማድረግ ከባድ ነገር ነው፡፡

ዛሬ ስለእምነት፣ በእምነት ሕይወት ስለመኖር፣ የእግዚአብሔርን ቃል መሠረት በማድረግ የቅዱሳንን ገድልና ትሩፋት በመግለጥ ብዙ ነገር ተነግሮናል፡፡ ነገር ግን በአብዛኛዎቻችን ቃሉ በጭንጫ ላይ የተዘራ ዘር ሆኖብናል፤ /ማቴ. 13፣20/ ጌታችን በጭንጫ ላይ ዘር ወደቀ፤ ጥልቅ መሬትም ስላልነበረው ወዲያው በቀለ፤ ፀሐይ በወጣ ጊዜ ግን ደረቀ ያለውን ሲፈታ በጭንጫ ላይ የተዘራውም ይህ ቃሉን ሰምቶ ወዲያው በደስታ የሚቀበል ነው፡፡ ነገር ግን ለጊዜው ነው እንጂ በእርሱ ሥር የለውም፤ በቃሉ ምክንያት መከራ ወይም ስደት በሆነ ጊዜ ወዲያው ይሰናከላል፡፡ ብሏል፡፡

በእምነት መንፈሳዊ ሕይወታቸው አልጸና ብሎአቸው ይቸገሩ የነበሩ ቅዱሳን አባቶቻችን ያቀረቡት ጥያቄ መሠረታዊ ምላሽ አግኝቶ፤ የሰውነ ታቸው ለልብሳቸው፤ የልብሳቸው ለጥላቸው አልፎ ሕሙም ከመፈወስ ሙት እስከ ማስነሣት ደርሰዋል፡፡ ይኸውም ጥያቄያቸው ተቀባይነት አግኝቶ በዚህም አገልግሎታቸው እንደ ሠመረላቸው መረዳት ይቻላል፡፡

እኛም በሃይማኖት ስትኖሩ ራሳች ሁን መርምሩ ተብሎ እንደተነገረን፤ በቅድሚያ መንፈሳዊ ሕይወቴ ያላደገው ለምንድ ነው? ብለን ያለንን የእምነት ጥንካሬና ድክመት መመዘን አለብን፡፡ በማስከተል እንደ ታመመው ልጅ አባት አለማመኔን እርዳው የሚል ጥያቄ አቅርበን፤ የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል ፍጹም እምነት ሲኖረን ጌታችን እንዳለው ተራራ የሆነብን ትዕቢት፣ ከፊታችን የተደ ቀነው ክፋት፣ ምቀኝነት ከሕይወ ታችን ይነቀላል፡፡ እየወላወለ የሚያ ስቸግረን ልቡናችን ክት እንዲሆን ወይም እንዲሰበሰብልን አለማመኔን እርዳው ማለት አለብን፡፡ አለማመናችን በእግዚአብሔር ሲረዳ ባሕሩ እንደ የብስ ጸንቶልን እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ በባሕር ላይ እንረማመዳለን፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሔር አለማመናችንን ሲረዳው የሚሣነን ነገር የለም፡፡ በእኔ የሚያምን ከእኔ የበለጠ ያደርጋል ተብሎ ለቅዱሳን የተገባው ቃል የታመነ ነው፡፡

ያ በእምነት ያልጸናው ሰው ለእግዚአብሔር አምላኩ አለማመ ኔን እርዳው ሲል ያቀረበው ጥያቄ የሁላችንንም ሕይወት የሚወክል ነው፡፡ ዛሬ እምነቱ ሥርዓቱ፣ ትውፊቱ እያ ለን በፍጹም ልብ ያለማመን ችግር አለብን፡፡ ልጁ የታመመበት ሰው አለማመኔን እርዳው ሲል በአንተ ታምኜ የምኖርበትን ኃይል ለአንተ የሚገዛ ልብ እና ሕይወት ስጠኝ ማለቱ እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል፡፡

ከአባቶቻችን የተቀበልነው እምነት የፈተና ጎርፍ ሳይሸረሽረው ነፋስ ሳያ ዘመው በዐለት ላይ ተመሥርቶ እንዲጸናልን ዘወትር ጌታ ሆይ አለማ መኔን እርዳው ማለት አለብን፡፡ ያለማመናችን ችግር በእግዚአብሔር ካልተረዳ ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ በማለት ብቻ መንግሥተ ሰማያትን እንደማንወርስ ተነግሮናል፡፡ በመሆ ኑም ልባሞች ከመብራታቸው ጋር ዘይት ይዘው ሙሽራውን እንደጠበቁ፤ ባለማመን የጠወለገውን ሕይወታ ችንን በቃሉ ዝናምነት በማለምለም አለማመናችን በእግዚአብሔር ቃል መረዳት አለበት፡፡

ማንኛውም የሕይወት ውጣ ውረድ ቢያጋጥመን በእምነት ከጸናን የማናልፈው ነገር የለም፡፡ የማንዘለው የችግር እና የመከራ ግንብ፣ የማንሻገረው ባሕር እና መሰናክል የለም፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በእምነት ከእግዚአብሔር ጋር ከኖርን የሚያስፈራን አንዳች ነገር አለመኖሩን ሲያስረዳ በሞት ጥላ መካከል እንኳን ብሔድ፤ አንተ ከእኔ ጋር ነህና ክፉን አልፈራም፤ በትርህና ምርኩዝህ እነርሱ ያጽናኑኛል መዝ. 22፣4 ብሏል፡፡

ነቢዩ እንደ ነገረን አፋችንን ሞልተን በሞት ጥላ መካከል እንኳን ብሔድ ክፉን አልፈራም በማለት በእምነት ማደግ አለብን፡፡ ቅዱስ ዳዊት በሕይወት ዘመኑ መውደቅ መነሣት ያጋጠመው ሰው ቢሆንም በእምነት በመጽናቱ ፍጻሜው ሠምሮ ልበ አምላክ ለመባል በቅቷል፡፡ በመሆኑም ዛሬ በመንፈሳዊ ሕይወታችን የተደቀነብንን ፈተና የምናልፈው በእምነት ነው፡፡ እግዚአብሔርን ደስ የምናሰኘው በእምነት ነው፡፡ የሚመጣውን ነገር በተስፋ የሚያስረዳንም እምነት በመ ሆኑ አለማመናችንን እርዳው እያልን መጮህ ይገባል፡፡

አለማመናችን በእግዚአብሔር ሲረዳ ወይም በእምነት ስንጸና ረድኤተ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ይሆናል፡፡ እግዚአብሔር ኃያላን የሆኑትን አራዊት ሳይቀር ገራም ያደርግልናል፡፡ በዘመነ ብሉይ ነቢዩ ዳንኤል ከአናብስት ጉድጓድ ሲወረወር የተራቡት አንበሶች ለነቢዩ ገራም የሆኑት የእምነት ሰው በመሆኑ ነው፡፡ በቅድስናቸው የተመሰከረላቸው ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አናምርት /ነብሮች/ እና አናብስት /አንበሶች/ የእግራቸውን ትቢያ እየላሱ የታዘዙላቸው በሥጋዊ ጥበብ ሳይሆን በእምነት ነው፡፡ ዛሬ ዲያብሎስ እንደተራበ አንበሳ በፊታችን በሚያደባበት ዘመን የእምነትን ጥሩር መልበስ ያስፈልጋል፡፡ ለቀደሙት አባቶች ሥጋት የነበሩት ነገሮች ቀሊልና ታዛዥ እንደሆኑ ለእኛም ይሆኑልናል፡፡ ብዙ ጊዜ ፈቃደ ሥጋችን ፈቃደ ነፍሳችንን ሲጫነው የምንወደውን ሳይሆን የማንወደውን እናደርጋለን፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የማልወደውን ክፉን ነገር አደርጋለሁና ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውምÃ ሮሜ. 7፣19፡፡ ሲል እንደተናገረው፤ የሥጋችን ፈቃድ ብዙ ጊዜ ነፍሴ ብይ፣ ጠጪ ደስ ይበልሽ ወደ ማለት ቢያዘነብልም ቅሉ ወደ ፈቃደ ነፍስም መለስ ብሎ እኔ ማነኝ? ጉዞዬስ ወዴት ነው? ተስፋዬስ ማን ነው? ብሎ መጠየቅ ብልህነት ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት ፈቃደ ሥጋው እያየለ ሲያስቸግረው፤ በእንባው መኝታውን እያራሰ በእግዚአብሔር ፊት ቢያለቅስ፤ የኃጢአት አሽክላ እየተ ቆረጠለት በእምነቱ የሚደሰት ሰው ሆኗል፡፡

በእምነት ጉድለት በዲያብሎስ ሽንገላ የእምነት አቅም አጥተን ከቤተ ክርስቲያን ከቅድስና ሕይወት የራቅን ወገኖች፤ አለማመናችንን እግዚአብሔር እንዲረዳው ሳንሰለች ጥያቄ ማቅረብ አለብን፡፡ በእምነት ጉድለት ምክንያት ያጣነውን በረከት፣ ያጣነውን ጽናት እናገኛለን፡፡ ልባሞቹ ቅዱሳን ሐዋርያት ይህን ለመፈጸም ለምን እኛን ተሳነን? ብለው እንደጠየቁ፤ እኛም ራሳችንን መጠየቅ አለብን፡፡ በጎ መሥራት ለምን ተሳነን?

የሰው ልጅ ወደ እምነት ፍጹም ነት ውስጥ ሲገባ ሁሉ ነገር በእግዚአብሔር እጅ እንደሆነ ይረዳል፤ ከጭንቀትም ያርፋል፡፡ በአቅማችንና በፈቃዳችን የተቸገረን መርዳት፣ አምላክን ከልብ መውደድ፣ ማመስገን የእምነት ሰው መገለጫ ናቸው፡፡

በእምነት የጸኑ አባቶችን በአንበሳ ጉድጓድ፣ በእሳት ውስጥ፣ በወህኒ ቤት በተጣሉ ጊዜ የተረዳና የእምነታቸውን ዋጋ የከፈለ እግዚአብሔር ዛሬም አለ፡፡ በመሆኑም መንፈሳዊ ሕይወታችንን በእምነት አሳድገን መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ ያብቃን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ለአብነት መምህራንና ተማሪዎች ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት የሚያግዝ ስልጠና ተሰጠ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ከደሴ ማእከል

በማኅበረ ቅዱሳን ደሴ ማእከልና ደሴ ወረዳ ማእከል አስተባባሪነት ከሚያዚያ 18 – 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ከዘጠኝ ወረዳዎች ለተውጣጡ ዐሥራ ስምንት የአብነት መምህራንና ተማሪዎች ለሐዋርያዊ አገልግሎት የሚያበቃ ስልጠና ተሰጠ፡፡

ለተከታታይ ለሰባት ቀናት በተሰጠው ስልጠናም ትምህርተ ሃይማኖት፤ ሐዋርያዊ ተልእኮ፤ ትምህርተ ኖሎት እና የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ስልጠናው ተሰጥቷል፡፡

በስልጠናው ላይ የተሳተፉት መምህራንና ተማሪዎቹ ከፍተኛ ተሳትፎ ያደረጉ ሲሆን፤ የተሰጣቸው ስልጠና ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት በንቃት እንድንሳተፍ ያደርገናል ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

በሥልጠናው ማብቂያ ላይ በማእከሉ የሕክምና ቡድን ለሁሉም ሠልጣኖች የተሟላ የጤና ምርመራ በማድረግ የመድኃኒት ድጋፍ ተደርጎላቸዋል፡፡

ለካህናት የዐቅም ማጎልበቻ ስልጠና ተሰጠ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ከደሴ ማእከል

በደሴ ከተማ ቤተ ክህነት፤ በማኅረ ቅዱሳን ደሴ ማእከልና ደሴ ወረዳ ማእከል አስተባባሪነት ሚያዚያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ደሴ ከተማ ለሚገኙ ከሰባ በላይ ለሚደርሱ የደብር አስተዳዳሪዎች፣ ካህናት በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ የአንድ ቀን ስልጠና ተሰጠ፡፡

ስልጠናው የተዘጋጀበትን ዓላማ የደሴ ከተማ ቤተ ከህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ መምህር ቆሞስ አባ ለይኩን ወንድይፍራው ሲገልጹ በከተማው ከዐሥር በላይ አብያተ ክርስቲያናት እና በርካታ ካህናት ስለሚገኙ በዞን ከተማነቱም ለምዕራብ ወሎ እና ለሌሎችም አጎራባች አካባቢዎች መጋቢ ነው፡፡ በዚህም መሠረት የካህናትን አቅም በሥልጠና ማገዝ እያጋጠሙን ባሉት ችግሮችና መፍትሔዎቻቸው ዙሪያ መወያየት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ መርሐ ግብሩ እንደተዘጋጀ ገልጸዋል፡፡

ለአንድ ቀን በቆየው ሥልጠና ትምህርተ ኖሎት፤ የካህናት ሚና ከቤተ ክርስቲያን ፈተናዎች እና ከዓለም አቀፍ ነባራዊ ሁኔታዎች አንጻር በሚል ርእስ ቤተ ክርስቲያን ከውጭ እና ከውስጥ እያገጠሟት ባሉ ፈተናዎች እና መፍትሔዎቻቸው እንዲሁም የካህናት ድርሻ ምን መሆን አለበት በሚሉት ርእሰ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

በውይይቱ ወቅት በንስሓ ልጆች አያያዝ ዙሪያ እያጋጠሟቸው ስላሉ ችግሮችና መፍትሔዎቻቸው፣ ዐሥራት አለመክፈል በቤተ ክርስቲያን ላይ እያደረሰ ስላለው ጉዳት፣ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ አሁን ያለበት ደረጃ፣ የአብነት መምህራንና ተማሪዎች እያጋጠማቸው ስላሉ ፈተናዎች እና ሌሎችም ቤተ ክርስቲያንን ከውጭና ከውስጥ እያጋጠሟት ስላሉ ፈተናዎች እና መፍትሔዎቻቸው በማንሳት የጉባኤው ተሳታፊዎች ሰፊ ውይይት አድርገዋል፡፡

ለአብነት ተማሪዎች የአልባሳት ድጋፍ ተደረገ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ከደሴ ማእከል

በማኅበረ ቅዱሳን ደሴ ማእከል የቅዱሳት መካናት ማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍል አስተባባሪነት በሰሜን ወሎ ደላንታ እና መሀል ሳይንት ለሚገኙ የአብነት ተማሪዎች የአልባሳት ድጋፍ ተደረገ፡፡

በነዚህ ወረዳዎች ብዛት ያላቸው የአብነት ተማሪዎች የሚገኙ ሲሆን፤ ከሚያጋጥሟቸው ችግሮች አንዱ የሆነውን የአልባሳት ችግር ለመቅረፍ ከማእከሉ አባላት፣ ከግቢ ጉባኤያት እና ከምእመናን አልባሳትን በማሰባሰብ ድጋፍ ማድረጉን ማእከሉ ገልጿል፡፡

ማእከሉ በሀገረ ስብከቱ የሚገኙ የአብነት መምህራንና ተማሪዎች የሚያጋጥሟቸውን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ችግሮች ለመቅረፍ ጊዜያዊ እና ቋሚ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ ተግባራዊ እያደረገ የሚገኝ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት በዘመናዊ ትምህርት፣ በጤና አጠባበቅ እና በአልባሳት ከሚደረጉ ድጋፎች በተጨማሪ ለዘጠኝ (9) የአብነት መምህራን ለእያንዳንዳቸው ብር 200.00 ወርሃዊ ድጎማ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ ለአንድ የአብነት ት/ቤትም ቋሚ የገቢ ማስገኛ ፕሮጀክት ቀርጾ ተግባራዊ በመደረግ ላይ መሆኑን ማእከሉ ገልጿል፡፡

 

በሊቢያ ለተሠዉ 30 ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች የመታሰቢያ ጉባኤ ተካሄደ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ዲ/ን ዘአማኑኤል አንተነህ(ከጎንደር ማእከል)

በሊቢያ ለተሠዉ 30 ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች በጎንደር ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ለ3 ቀናት የቆየ የመታሰቢያ ጉባኤ ተካሄደ፡፡

ጉባኤውን ያዘጋጁት የጎንደር ከተማ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት፣ በማኅበረ ቅዱሳን የጎንደር ማእከል እና የጎንደር ከተማ የጥምር መንፈሳዊ ማኅበራት በጋራ በመተባበር ሲሆን፤ ከሚያዚያ 24 – 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ጉባኤው ተካሂዷል፡፡

ጉባኤው የተጀመረው ቅዳሜ ሚያዝያ 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ከ7፡00 ሰዓት ጀምሮ ሲሆን፤ ለሦሰት ቀናት በቆየው ጉባኤ በሰባኪያነ ወንጌል ትምህርት፤ ሰማዕታቱን የሚዘክሩ መነባንብ፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ቅኔ፤ ከምእመናን ለቀረቡ ጥያቄዎች በሊቃውንተ ቤተ ክረስቲያን መልስ፤ መዝሙር በጎንደር ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት እና በተጋባዥ መዘምራን፤ የጧፍ ማብራት ሥነ ሥርዓት ተከናውኗል፡፡

በተያያዘ ዜና የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በሊቢያ ለተሠዉት 30 ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች የከተማው ምእመናን በተገኙበት ሚያዚያ 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በርዕሰ አድባራት አደባባይ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ጸሎተ ፍትሐት ተደርጎላቸዋል፡፡ በዕለቱም 30 ሻማዎች በርተዋል፡፡

001sinoddd

የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተጠናቀቀ

ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም.

001sinoddd

ሚያዝያ 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ከቀኑ 10፡00 ሰዓት በጸሎት የተጀመረው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ሲካሔድ ቆይቶ ዛሬ ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም. ረፋድ ላይ ተጠናቅቆ የሚከተለውን መግለጫ ሰጥቷል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 ላይ በተደነገገው ቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዓመት ሁለት ጊዜ ይካሄዳል፡፡

ከሁለቱ አንዱ ከጌታችን ከአምላካችንና ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ አምስተኛው ቀን በዕለተ ረቡዕ የሚውለው የርክበ ካህናት ጉባኤ ነው፡፡

በመሆኑም የርክበ ካህናቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ሚያዝያ 27 ቀን ከሰዓት በኋላ በጸሎት ተከፍቶአል፡፡

በመቀጠልም ሚያዝያ 28 ቀን 2007 ዓ.ም መደበኛ ስብሰባን በጸሎትና በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ የመክፈቻ ንግግር ተጀምሮ ለሦስት ቀናት ሲካሄድ ሰንብቶአል፡፡ ልዩ ልዩ ውሳኔዎችንና መመሪያዎችንም አስተላልፎአል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ለዐራት ቀናት ያህል ባካሄደው ቀኖናዊ ጉባኤ፡-

-ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን የሚጠቅሙትን፣

-ለልማትና ለሰላም የሚበጁትን፣

-ከሀገር ውጭ ለሚገኙና በሀገር ውስጥ ላይ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን ሁለንተናዊ ሕይወት መጠበቅ የሚያስችሉትን ርእሰ ጉዳዮች በማንሣት በስፋትና በጥልቀት አይቶ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አሳልፎአል፡፡

1.ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በጉባኤ መክፈቻ ያደረጉት ታሪካዊ ንግግር የቤተ ክርስቲያንን ሁለንተናዊ ሕይወት የቃኘ የሀገራችን ዕድገትንና የሰላም አስፈላጊነት በስፋት የገለጸ በመሆኑ ጉባኤው በሙሉ ድምፅ ተቀብሎታል፡፡

2.ምልአተ ጉባኤው በቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ተዘጋጅቶ የቀረበውን ዓመታዊ የሥራ መግለጫ ሪፖርት አዳምጦ አንዳንድ ማስተካከያዎችን በማድረግ በሙሉ ድምፅ ተቀብሎታል፡፡

3.ምንም ጥፋትና በደል ሳይኖርባቸው ክርስቲያኖች በመሆናቸው ብቻ በሊቢያ ሀገር አይ ኤስ በተባለ የአሽባሪዎች ቡድን በግፍና በሚዘገንን ሁኔታ የተገደሉ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖችንና የግብፅ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖችን በተመለከተ ቋሚ ሲኖዶስ ቀደም ሲል በሟቾቹ መንፈሳዊ ሕይወት ላይ ተወያይቶ ባቀረበው ሐሳብ መሠረት ምልዓተ ጉባኤው ያለውን ሁኔታ በጥልቀት ከተረዳ በኋላ ሟቾቹ የዘመኑ ሰማዕት እንዲባሉ ተስማምቶ ወስኗል፡፡

4.እንዲሁም እንደ ኢትዮጵያውያን አቆጣጠር ሚያዝያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም በሊቢያ የተሠውት 30 የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አማኞች ልጆቻችን እና እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር የካቲት 15 ቀን 2015 ዓ.ም በሊቢያ የተሠውት 21 የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባላት ክርስቲያኖች በሁሉቱም አብያተ ክርስቲያኖች ሲኖዶስ የሰማዕትነት ክብር የተሰጣቸው ስለሆነ፣ የሁለቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት የ21ኛው ክፍለ ዘመን ሰማዕታት ተብለው በአንድነት እንዲታሰቡ ቅዱስ ሲኖዶስ ተስማምቷል፡፡

5.በልዩ ልዩ ምክንያት ከኢትዮጵያ ሀገራቸው ወጥተው በባዕድ ሀገር የሚገኙትንና ወደ ሀገራቸው በመመለስ ላይ ያሉትን ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንን ከማንኛውም ጥቃት ለመከላከልና ለማቋቋም ቤተ ክርስቲያናችን መንግሥት ከሚያደርገው ጥረት በመቀናጀት አስፈላጊውን ሁሉ እንድታደርግ፣ ይህን በተመለከተ ጉዳዩን የሚከታተል ኮሚቴ የቤተ ክርስቲያናችን የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽንም እርዳታ ሰጪዎችን በማስተባበር ኃላፊነቱን ወስዶ በንቃትና በትጋት እንዲሠራ ጉባኤው ወስኖአል፡፡

6.ሀገራችን ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ አምስተኛውን ሀገራዊ ምርጫ ለማከናወን በሂደት ላይ መሆኗን ቅዱስ ሲኖዶስ አውስቶ ምርጫው ሰላማዊና ፍትሐዊ ሆኖ በሰላም ይጠናቀቅ ዘንድ ቤተ ክርስቲያናችን በጸሎት እንድትተጋ ጉባኤው መልእክቱን አስተላልፏል፡፡

7.ኢትዮጵያ ሀገራችን ለብዙ ዘመናት ተጭኖአት ከቆየ የድህነት አረንቋ በተጨማሪ የእርስ በእርስ ግጭት ጥሎባት ባለፈ ጠባሳ ክፉኛ የተጎዳች ብትሆንም በተገኘው ሰላም ምክንያት ባሳለፍናቸው ዓመታት እየታዩ ያሉ የልማትና የዕድገት፣ የእኩልነትና የአንድነት እመርታዎች የሰላምን ጠቃሚነት ከምንም ጊዜ በላይ መገንዘብ የተቻለበት ስለሆነ፤ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከምንም በላይ ሰላሙንና አንድነቱን አጽነቶ በመያዝ ሀገሩን ከአሸባሪዎችና ከጽንፈኞች ጥቃት ነቅቶ እንዲጠበቅ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦት ያሳስባል፤

8.ሀገራችን ኢትዮጵያ የቴክኖሎጂና የካፒታል እጥረት እንደዚሁም በሀገር ውስጥ ሠርቶ የመበልፀግ ግንዛቤ ማነስ ካልሆነ በቀር በተፈጥሮ ሀብትም ሆነ በማናቸውም መመዘኛ ከሌላው የተሻለች እንደሆነች የታወቀ ስለሆነ፤ ወጣቶች ልጆቻችን ወደ ሰው ሀገር እየኮበለሉ ራሳቸውን ለአደጋ ከሚያጋልጡ በሀገራቸው ሠርተው የተሻለ ኑሮ እንዲኖሩ ኅብረተሰቡም ይህንን ከግንዛቤ ውስጥ አስገብቶ በሰፊው እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ መልእክቱን አስተላልፏል፤

9.ለሀገራችንና ለሕዝቦቻችን ችግሮች ቁልፍ መፍትሔ ሊሆን የሚችለው ልማትን በማጠናከርና ዕድገትን በማረጋገጥ ድህነትን ማስወገድ ስለሆነ ሕዝባችን ይህን ከልብ ተቀብሎ በየአቅጣጫው የተጀመሩትን የልማት ሥራዎች በመደገፍ ሀገሪቱን መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገሮች እኩል ለማሰለፍ የሚደረገውን ሀገራዊ ርብርቦሽ ለማሳካት በርትቶ እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፤

10.በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያ ክርስቲያናት በየቤተ ክርስቲያኑ ዙሪያ ሁሉ የአረንጓዴ ልማትና የራስ አገዝ ልማት በማካሄድ ልማትን እንዲያፋጥኑ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥብቅ መመሪያ አስተላልፎአል፡፡

11.በውጭ ሀገር ከሚገኙ አባቶች ጋር ተጀምሮ የነበረው የእርቀ ሰላም ድርድር ለሀገራችን ልማትና ለሕዝባችን አንድነት የሚሰጠው ጥቅም የማይናቅ ስለሆነ የቤተ ክርስቲያናችን በር ለሰላምና ለእርቅ ክፍት መሆኑን ምልዓተ ጉባኤው ገልጿል፡፡

12.ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ በላይ በተገለፁትና በሌሎችም መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ሲወያይ ሰንብቶ ስብሰባውን በዛሬው ዕለት በጸሎት አጠናቆአል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችን ለሕዝባችንና ለዓለሙ ሁሉ ሰላሙን፣ ምሕረቱንና ፍቅር አንድነቱን ይስጥልን፤

እግዚአብሔር ይባርካችሁ ይቀድሳችሁ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም.

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

001jimaa

የጅማ ማእከል የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር እንደሚያካሄድ ገለጸ

ሚያዝ 29 ቀን 2007 ዓ.ም.

በጅማ ማእከል

001jimaaበማኅበረ ቅዱሳን የጅማ ማእከል ሁለተኛውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ግንቦት 2 ቀን 2007 ዓ.ም. በሊሙ ኮሳ ወረዳ ቤተ ክህነት በምትገኘው ጥንታዊና ታሪካዊ በሆነችው ኮሳ ቅደስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እንደሚያካሄድ ገለጸ፡፡

የኮሳ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ከጅማ 50 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኝ ሲሆን፤ የትኬቱ ዋጋ ምሳን ጨምሮ 150፡00 ብር መሆኑን ማእከሉ ገልጿል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ የወንጌል ትምህርት በተጋባዥ መምህራን፤ ያሬዳዊ ወረብ እና ቅኔ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ ምክረ አበው /ከምእመናን ለሚጠየቁ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጥበት/፤ ያሬዳዊ ዝማሬ በማእከሉ መዘምራን፤ በተጋባዥ ዘማርያንና በአጥቢያው ሰንበት ትምህርት ቤቶች መዘምራን ይቀርባል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ተወካዮች፤ የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ስብከተ ወንጌል ሓላፊዎች፤ የሊሙ ሰቃ፤ የሊሙ ኮሳ፤ የአጋሮና ቀርሳ እንዲሁም የጅማ ከተማ ምእመናን በመርሐ ግብሩ ላይ ይሳተፈሉ ሲል ማእከሉ አስታወቋል፡፡

ጥያቄ ለመጠየቅ ለሚፈልጉ ምእመናን በሚከተለው የኢሜል አድራሻ መላክ እንደሚችሉ ማእከሉ አሳስቧል፡፡

jimmamkhh2@gmail.com ወይም aynisha5@gmail.com

001deb

የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ያስገነባው መንበረ ጵጵስና እና ጽ/ቤት ተመረቀ

ሚያዝያ 28 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

001deb002deb

የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በደብረ ብርሃን ከተማ ያስገነባው ለመንበረ ጵጵስና እና ለጽ/ቤት አገልግሎት የሚውል ባለ ሁለት ፎቅ ሕንፃ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ሚያዝያ 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ተመረቀ፡፡

በሀገረ ስብከቱ የተገነባውን ሕንፃ ለመመረቅ ቅዱስ ፓትርያርኩ፤ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና የጠቅላይ ቤተ ክህነት የልዩ ልዩ መምሪያ ሓላፊዎች ከአዲስ አበባ ወደ በደብረ ብርሃን ሲመጡ በደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በሀገረ ስብከቱ የሚገኙ የሃያ ዘጠኝ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቃነ ካህናትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የዞኑ እና የከተማው የመንግሥት ባለሥልጣናት፤ እንዲሁም የደብረ ብርሃን ከተማ ምእመናን አቀባበል አድርገውላቸዋል፡፡

003deb004deb

ቅዱስነታቸው ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመሆን ሕንፃውን ከመረቁ በኋላ አገልግሎት የሚሰጡትን ክፍሎች በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ኤፍሬምና በሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ እየተመሩ ጎብኝተዋል፡፡

በዐፄ ዘርዓያዕቆብ ደባባይ በተከናወነው መርሐ ግብር ቅዱስነታቸው ባስተላለፉት መልእክት በደብረ ብርሃን ከተማ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እየተሠሩ ያሉ የልማት ሥራዎች የሚያስደስቱ ናቸው፡፡ ከመንበረ ጵጰስናው ግንባታ በተጨማሪ በዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ ደባባይ እየተገነባ የሚገኘው ባለ 5 ፎቅ ሕንፃም ሀገረ ስብከቱ ለሚያከናውነው መንፈሳዊ አገልግሎት ጠቀሜታው የጎላ ነው፡፡ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ተጨማሪ ሀብት የሚያስገኝ በመሆኑ ሌሎችም አህጉረ ስብከቶች ከዚህ ልማት ሊማሩ ይገባል ብለዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ አባ ዘውዱ በየነ ባቀረቡት ሪፖርት በሀገረ ስብከቱ 29 ወረዳ ቤተ ክህነት፤ 2000 አብያተ ክርስቲያናት እንዳሉ የገለጹ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ ከ360 በላይ አብያተ ክርስቲያናት ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም ወደ ሀገረ ስብከቱ ከመጡ በኋላ እንደታነጹ አብራርተዋል፡፡

006deb005deb

ለካህናት ሥልጠና በመስጠት፤ የሰበካ ጉባኤ ክፍያን በማሳደግና በማሰባሰብ፤ ስብከተ ወንጌል በማስፋፋት፤ መምህራንን በማፍራትና በመመደብ፤ በአረንጓዴ ልማት፤ በደብረ ብርሃን ሥላሴ ሰባት መምህራንን በመመደብ በአብነት ትምህርት በርካታ ደቀ መዛሙርትን በማፍራት፤ የካህናት ደዝን በማሳደግ ሀገረ ስብከቱ አገልግሎቱን በማፋጠን ላይ እንደሚገኝ ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል፡፡

ቀድሞ የነበረው የሀገረ ስብከቱ መንበረ ጵጵስና በንግድ ማእከላት አካባቢ በመሆኑና ምቹ አገልግሎት ለመስጠት ባለማስቻሉ ሌላ ባለ ሁለት ፎቅ መንበረ ጵጵስና እና ጽ/ቤትን አጠቃሎ የያዘ ሕንፃ በመገንባት ለዛሬው ምረቃ መብቃቱን ያብራሩት ሥራ አስኪያጁ ባለ አምስት ፎቅ ሁለገብ ሕንፃም በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኙ በሪፖርታቸው ከተዳሰሱት ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ተጀምሮ፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያሬዳዊ ወረብ፤ በሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ያሬዳዊ መዝሙር፤ በደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ መምህር ቅኔ ቀርቧል፡፡

010de009deb

100sinodoss

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በጸሎት ተጀመረ

ሚያዝያ 27 ቀን 2007ዓ.ም

100sinodossበዓመት ሁለት ጊዜ የሚደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ዛሬ ሚያዝያ 27 ቀን 2007ዓ.ም. ከቀኑ ዐሥር ሰዓት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም በጸሎት ተጀመረ፡፡