የቅዱስ ጊዮርጊስ ሰማዕትነት በመጽሐፈ ስንክሳር

ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም.

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አምላክ አመ ዕሥራ ወሠሉሱ ለሚያዝያ በዛቲ ዕለተ ኮነ ፍጻሜ ስምዑ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ሰማዕት ዐቢይ ወክቡር ዘተሰምየ ፀሐየ ወኮከበ ጽባሕ፡፡

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ ሦስት በዚች ቀን ፀሐይና የአጥቢያ ኮከብ የተባለ ታላቅና ክቡር የሆነ የሰማዕቱ የቅዱስ ጊዮርጊስ የምስክርነት ፍጻሜ ሆነ፡፡

የዚህም ቅዱስ አባቱ መስፍን ነው፡፡ ስሙም አንስጣስዮስ ይባላል፡፡ ከቀጰዶቅያ አገር ነው፡፡ የእናቱም ስም ቴዎብስታ ይባላል ከፍልስጥዔም አገር ናት ታናሽ ሆኖ ሳለ አባቱ ዐረፈ፡፡

ሃያ ዓመትም በሆነው ጊዜ የአባቱን ሹመት ሊቀበል ወደ ንጉሥ ዱድያኖስ ዘንድ ሔደ፡፡ ንጉሡም ጣዖትን እንዲአመልኩ ሰዎችን ሁሉ ሲያስገድዳቸው አገኘው፡፡

ይህንንም አይቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ እጅግ አዘነ በእርሱ ዘንድ ያለውን ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች፣ ለምስኪኖች ሰጠ ባሮቹንም ነፃ አወጣቸው፡፡

ከዚህ በኋላ በንጉሥ ፊት ቁሞ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ፡፡ ንጉሡም አባበለው ብዙ ቃል ኪዳንም ገባለት እርሱ ግን አልተቀበለውም፡፡

ለመስማት እንኳ የሚያስጨንቅ ሥቃይን አሠቃየው ጌታችን ግን ያጸናዋል ቍስሉንም ያድነዋል ሦስት ጊዜም እንደሚሞት እርሱም እንደሚአስነሣው በአራተኛውም የምስክርን አክሊልን እንደሚቀበል ነገረው፡፡ ቃል ኪዳንም ሰጠው ስሙ በዓለሙ ሁሉ የተገለጠ ይሆን ዘንድ በተጋድሎና መከራ በመቀበልም ጽኑዕ በሆነ ሥቃይም ሰባት ዓመት እንደሚኖር መላእክትም እንደሚአገለግሉት ነገረው፡፡

ንጉሡም ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለመታዘዙና ባለመመለሱ እጅግ አዘነ፡፡ ስለዚህም አትናስዮስ የሚባል ታላቅ ሥራየኛ አመጣ፡፡ እርሱም መርዝን ቀምሞ በጽዋ መልቶ አስማት ደግሞ እንዲጠጣ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ሰጠው፡፡ ወዲያውኑ የሚሞት መስሎት ነበር፡፡ ቅዱሱም ያንን ጽዋ ጠጣው ምንም ጉዳት አልደረሰበትም፡፡

ያ መሠርይም በክብር ባለቤት በጌታ በኢየሱስ አምኖ በሰማዕትነት ሞተ፡፡ ከእርሱም ጋር ሌሎች ብዙዎች ሰዎች በሰማዕትነት ሙተው የሕይወት አክሊል ተቀበሉ ቁጥራቸውም ሠላሳ ሺህ ሰባት መቶ ነፍስ ነው፡፡

ቅዱስ ጊዮርጊስም በዱድያኖስና በሰባ ነገሥታት ፊት በቆመ ጊዜ በዚያም የተቀመጡባቸው የዕንጨት ወንበሮች ነበሩ፡፡ ቅዱሱንም እሊህን የተቀመጥንባቸውን ወንበሮች እንዲበቅሉ እንዲአብቡና እንዲአፈሩ ታደርጋቸው ዘንድ ከአንተ እንሻለን አሉት፡፡ በዚያን ጊዜ ጸለየ እንዳሉትም አደረጋቸው ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው ቍጥር የሌላቸው ብዙ አሕዛብ በጌታችን አመኑ፡፡

ከዚህም በኋላ ቅዱሱን ወስደው በጐድጓዳ ብረት ምጣድ ውስጥ አበሰሉት፡፡ አቃጥለው አሳርረውም ሥጋውንና ዐጥንቱን ፈጭተው አመድ አድርገው ከረጅም ተራራ ላይ በተኑት፡፡ ጌታችንም ነፍሱን ወደ ሥጋው መልሷት ደግሞ አስነሣው፡፡ ወደ ነገሥታቱም ተመልሶ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ስም ሰበከ፡፡ ቍጥር የሌላቸው አሕዛብ አይተው አደነቁ በጌታችንም አምነው በሰማዕትነት ሞቱ፡፡

ነገሥታቱም ደግመው ሙታኖችን ብታሥነሣ አምላክህ ዕውነተኛ አምላክ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ በእርሱም እናምናለን አሉት፡፡ ቅዱሱም ጸለየ ከጒድጓድም ውስጥ ወንዶችና ሴቶችን ጐልማሶችንም አስነሣላቸው እነዚያም በክብር ባለቤት በጌታችን ስም አስተማሩ የገሀነምንም ወሬ ተናገሩ ጥምቀትንም ተቀብለው ተመልሰው ዐረፉ፡፡

ከሀድያን ነገሥታት ግን ሙታንን ያስነሣህ አይደለም የረቀቁ ሰይጣናትን አሳየህ እንጂ ብለው ተከራከሩ፡፡ ከዚያም ከጭንቀታቸው ብዛት የተነሣ ከአንዲት ድኃ ሴት ዘንድ አስጠበቁት እርሷም እንጀራ ልትለምንለት ወጣች የእግዚአብሔርም መልአክ በላዩ ከበጎ ነገር ሁሉ የተመላ ማዕድን አቀረበለት፡፡ የዚያች መበለትም የቤቷ ምሰሶ ቅርንጫፍን አበቀለ ታላቅ ዛፍም ሆነ፡፡

ያቺም መበለት በተመለሰች ጊዜ የቤቷ ምሰሶ ቅርንጫፍ አብቅሎ ታላቅ ዛፍ እንደሆነ ስለ ማዕዱም ይህን ታላቅ ምልክት አይታ የክርስቲያኖች አምላክ ሰው ተመስሎ ወደ እኔ መጣ አለች፡፡ ቅዱስም እኔ አምላክ አይደለሁም፡፡ የአምላክ ባሪያ ነኝ እንጂ አላት፡፡ እርሷም እንዲህ ብላ ለመነችው የአምላክ አገልጋይ ከሆንክ ቸርነትህ እንድትደርሰኝ እለምንሃለሁ፡፡ ዕውር ደንቆሮ ዲዳ ጐባጣ የሆነ ልጅ አለኝና ታድንልኝ ዘንድ እለምንሃለሁ፡፡ ስለ ጌታችን እምነትም አስተማራትና በመስቀል ምልክት አማተበው ያን ጊዜም አየ፡፡ ቅዱሱም በሌላ ጊዜ እንዲሰማ እንዲናገርና እንዲሔድ እንዲአገለግለኝም እኔ እሻለሁ አላት፡፡

በዚያን ጊዜ ንጉሡ በአገሩ ሜዳ ውስጥ ሲዘዋወር ያቺን ዛፍ አይቶ አደነቀ ስለ እርሷም ጠየቀ ቅዱስ ጊዮርጊስ በእርሷ ዘንድ የተቀመጠባት የዚያች መበለት የቤቷ ምሰሶ እንደሆነ ነገሩት፡፡ ንጉሡም ተቆጣ ቅዱሱንም ከዚያ ወስዶ አስገረፈው በመንኰራኵርም አበራዩት ሙቶም ከከተማ ውጭ ጣሉት ጌታም ከሞት አስነሣው ወደ ነገሥታቱም ተመለከተ ንጉሡም አይቶ ደነገጠ ስለ ሕይወቱም አደነቀ፡፡

ከዚህም በኋላ ይሸነግለው ዘንድ ጀመረ በመንግሥቱ ላይም ሁለተኛ ያደርገው ዘንድ ቃል ገባለት ቅዱስ ጊዮርጊስም እየዘበተበት ነገ በጥዋት ለአማልክቶችህ መሥዋዕትን አቀርባለሁ አንተም ሕዝቡ እንዲሰበሰቡ እዘዝ እኔ ስሠዋ እንዲአዩ አለው፡፡ ንጉሡም ዕውነት የሚሠዋ መስሎት ደስ አለው ወደ ቤተ መንግሥቱም እልፍኝ አስገብቶ አሳደረው፡፡

ለጸሎትም ተነሣ የዳዊትንም መዝሙር አነበበ የዱድያኖስ ሚስቱ እለስክንድርያ ንግሥት ሰምታ ቃሉ ደስ አሰኛት የሚያነበውንም ይተረጒምላት ዘንድ ለመናቸው፡፡ እርሱም እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ሰው እስከሆነበት ጊዜ የሆነውን ሁሉ ሊያስረዳትና ሊያስገነዝባት ጀመረ፡፡ ትምህርቱም በልቡዋ ተቀርጾ በክብር ባለቤት በጌታችን አመነች፡፡

በማግሥቱም ቅዱስ ጊዮርጊስ ለአማልክት ሲሠዋ ለማየት ሰው ሁሉ እንዲሰበሰብ ዐዋጅ ነጋሪ ዞረ የቤቷን ምሰሶ ያበቀለላት ያቺ መበለት ሰምታ ዕውነት መስሏት እጅግ እያዘነች ልጅዋን ተሸክማ እያለቀሰችም ወጣች፡፡

ቅዱስ ጊዮርጊስም በአያት ጊዜ ፈገግ አለ ልጅሽን በምድር ላይ አኑሪው አላት፡፡ ከዚያም ልጅዋን ጠርቶ ወደ አጵሎን ሒድ ወደእኔም ይመጣ ዘንድ በክብር ባለቤት በጌታዬ ኢየሱስ ስም እዘዘው አለው፡፡ ያን ጊዜ ያ ልጅ ድኖ ቅዱስ ጊዮርጊስ እንዳዘዘው ወደ ጣዖቱ ቦታ ሒዶ አዘዘው፡፡ በጣዖቱ ያደረ ያ ርኵስ መንፈስም ከማደሪያው ወጥቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አለት መጥቶ እኔ ሰውን ሁሉ የማስት እንጂ አምላክ አይደለሁም ብሎ በሕዝቡ ሁሉ ፊት አመነ፡፡ ቅዱሱም ትውጠው ዘንድ ምድርን አዘዛትና ወዲያውኑ ዋጠችው ጣዖታቱንም ከአገልጋዮቻቸው ጋራ አጠፋቸው ንጉሡም ከወገኖቹ ጋር ዐፈረ፡፡

ብስጭትና ቁጣንም እንደተመላ ወደ ንግሥት ሚስቱ ዘንድ ገባ፡፡ እርሷም አምላካቸው ጽኑዕና ኃያል ነውና ክርስቲያኖችን አትጣላቸው አላልኩህምን አለችው፡፡ ይህንንም ከእርስዋ ሰምቶ በእርሷ ላይ እጅግ ተቆጣ ወደ ክብር ባለቤት ክርስቶስ እምነት የከበረ ጊዮርጊስ እንደአስገባት አወቀ፡፡

ከዚህም በኋላ ከከተማ ውጭ እንዲጐትቷትና በመጋዝም እንዲሰነጥቋት አዘዘ፡፡ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለች፡፡

በዚያም ጊዜ ስለ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሥራ ነገሥታቱ ሁሉም ደነገጡ ኀፍረት ደግሞ እንዳይጨምርባቸው ከእርሱም እንዲአርፍ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ እንዲጽፍ ንጉሥ ዱድያኖስን መከሩት፡፡

ያን ጊዜም የክቡር ጊዮርጊስን ራስ በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ፡፡ ድል አድራጊ ጊዮርጊስም እጅግ ደስ አለው፡፡ እሳት ከሰማይ አውርዶ ሰባውን ነገሥት ያቃጥላቸው ዘንድ መከራውም ከክርስቲያን ወገን ጸጥ ይል ዘንድ ጌታችንን ለመነው፡፡ ወዲያው እሳት ወርዶ ከሠራዊታቸው ጋር ሰባውን ነገሥታት አቃጠላቸው፡፡

ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ተገልጾ ብዙ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡ በምድር መታሰቢያህን ለሚያደርግ ሁሉ እኔ ኃጢአቱን ሁሉ እደመስሳለሁ በመከራም ውስጥ ሁኖ በባሕርም ሆነ በየብስ ወይም በደዌ በስምህ የሚለምነኝን እኔ ፈጥኜ ከመከራው አድነዋለሁ፡፡ ይህንንም ጌታችን ተናግሮ በክብር ወደ ሰማይ ወጣ፡፡

ከዚህ በኋላ ራሱን ዘንበል አድርጎ በሰይፍ ቆረጡት በመንግሥተ ሰማያት አክሊላትን ተቀበለ፡፡ ከአገልጋዮቹም የቀሩት ሥጋውን ወስደው በልብስ ጠቀለሉት ወደሀገሩ ልዳም ወሰዱት፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሠርተው በውስጥዋ አኖሩት ከእርሱም ቍጥር የሌላቸው ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን የቅዱስ ጊዮርጊስም በረከቱ ረድኤቱ ሁላችን የክርስቲያን ወገኖችን ከሥጋና ከነፍስ መከራ ይጠብቀን ለዘላለሙ አሜን፡፡

ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 20

ሚያዝያ 17 ቀን 2007 ዓ.ም.

ስለ ሰማዕታት፤ ስለ አማንያን፤ ስለ ከሃድያን

ቍ.744፡- ብፁዕ ኤጲስ ቆጶስ ያዕቆብና ቅዱስ እስጢፋኖስ በእኛ ዘንድ የከበሩ እንደሆኑ ሰማዕታት በእናንተ ዘንድ የከበሩ ይሁኑ፡፡ እነዚህም በእግዚአብሔር ዘንድ የተመሰገኑ ናቸው፡፡ ትሩፋታቸውም የማይገኝ ነው፡፡

ቍ.747፡- ሰማዕታትም እኔን በሰው ፊት ያመነኝን ሰው ግን እኔም በሰማይ አባቴ ፊት አምነዋለሁ ብሎ ክርስቶስ ስለእነርሱ የተናገረላቸው እነዚህ ናቸው፡፡/ማቴ.10፤32/ በመከራቸው ጊዜ ብትመስሏቸው ስለ ቁርጥ አሳባችሁ ሰማዕትነት ይቆጠርላችኋል፡፡

ቍ.748፡- ሰማዕታትን ከሚረዱዋቸው ወገን አንዱ መከራ ቢያገኘው ብፁዕ ነው፡፡ እርሱ የሰማዕታት ተባባሪያቸው ነውና፡፡ በመከራዎቹም ክርስቶስን መስለው እኛንም ከካህናት ብዙ መከራ አገኘን፡፡ ከእነርሱም ዘንድ ደስ እያለን ወጣን፡፡ ስለመድኃኒታችን ስለ ክርስቶስ መከራን እንቀበል ዘንድ አድሎናልና፡፡ /የሐዋ. 5፤41/ እናንተም እንደዚህ መከራ በተቀበላችሁ ጊዜ ደስ ይበላችሁ፡፡ እናንተ በፍርድ ቀን ትመሰግናላችሁና፡፡

ቍ.749፡- ስለሃይማኖት የሚያሳድዷቸውን ስለጌታችን ትእዛዝ ከአገር ወደ አገር የሚሸሹትን ተቀበሏቸው፤ አሳርፏቸውም፤ ጥቀሟቸውም፤ እንደ ሰማዕታትም አድርጋችሁ አክብሯቸው፡፡ በተቀበላችኋቸውም ጊዜ እናንተ ደስ ይበላችሁ፡፡ ጌታ ክርስቶስ ስለ እኔ ባሳደዷችሁ ጊዜ እናንተ ብፁዓን ናችሁ፤ ፈጽሞ ደስ ይበላችሁ፤ ዋጋችሁ በሰማይ ታላቅ ነውና፡፡ እንደዚሁም ከእናንተ አስቀድመው የነበሩ ነቢያትን አሳደዷቸው፡፡ እኔን ካሳደዱ ግን ዳግመኛ እናንተን ያሳድዷችኋል፡፡ ከዚች አገር ቢያሳድዷችሁ ወደ ሌላይቱ አገር ሂዱ ብሏልና፡፡ /ማቴ. 5፤11-12፣ ማቴ. 10፤23/

ቍ.750፡- ዳግመኛም እንዲህ አለ፤ በዚህ ዓለም መከራና ኀዘን ያገኛችኋል፡፡ ወደ አደባባይ ያገቧችኋል፡፡ ለእናንተ ምስክር ሊሆንላችሁ ስለ እኔ ወደ ነገሥታቱና ወደ መኳንንቱ ያደርሷችኋል፡፡ እስከ መጨረሻው የታገሠ እርሱ ይድናል፡፡ ለክርስቶስ እንዳልሆነ የሚክድ ከእግዚአብሔርም ይልቅ ፈጽሞ ራሱን የወደደ ሰው ግን ይቅርታን አያገኝም፡፡ የእግዚአብሔር ጠላት የሰዎች ወዳጅ ሊሆን ወድዷልና፡፡ ስለተባረከችውም መንግሥት ፈንታ የዘለዓለም እሳትን ወድዷልና፡፡ /ማቴ. 10፤17-23/ ስለእርሱም ጌታችን በሰው ፊት የካደኝን ስሜንም የለወጠውን እኔም በሰማያዊ አባቴ ፊት እክደዋለሁ፡፡ እለውጠዋለሁም አለ፡፡ /ሉቃ. 12፤8-9/

ቍ.751፡- እንደዚህም ለእኛ ለደቀ መዛሙርቱ ከእኔ ይልቅ አባቱንና እናቱን ወይም ወንድ ልጁንና ሴት ልጁን የሚወድ እኔን አይመስለኝም፡፡ የሞቱንም መከራ ተሸክሞ ያልተከተለኝ እኔን አይመስለኝም አለ፡፡ ሰውነቱን የሚወድ ይጣላት፤ ሰውነቱን የጣላ ግን በእኔ ዘንድ ያገኛታል፡፡ ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢገዛ ነፍሱን ካጣ ምን ይጠቅመዋል? ሰው ለነፍሱ ቤዛ ምን በሰጠ ነበር፡፡ /ማቴ. 10፤37-39፣ ማቴ. 16፤22-27/ ዳግመኛም ሥጋችሁን የሚገድሉትን ሰዎች አትፍሯቸው፡፡ ነፍሳችሁን ግን መግደል አይቻላቸውም፡፡ ነፍስና ሥጋን አንድ አድርጎ በገሃነም እሳት መቅጣት የሚቻለውን ፍሩት እንጂ አለ፡፡ /ሉቃ. 12፤4-5፣ ማቴ. 10፤28/

ቍ.754፡- ብንጨነቅም ኃላፊውን ዘመን ስለመፍራት ሃይማኖታችንን አንለውጥ፡፡ አንዱስ እንኳ አለኝታውን ቢክድ ይኸውም የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ለጥቂትም ዘመን ከሚሆነው ሞት የተነሣ ቢፈራ ድኅነት በሌለበት በጸና ደዌ ነገ ቢያዝ ከዚች ሕይወት የተለየ ይሆናል፡፡ የወዲያውንም ዓለም ያጣል፡፡ ልቅሶ፤ ጥርስ ማፋጨት ባለበት በጨለማ ውስጥ ለዘለዓሙ ይኖራል፡፡ /ማቴ. 8፤13/

ቍ.755 እና 756፡- ያልተጠመቀ ሰውም ልቡ አይዘን፡፡ ስለ ክርስቶስ የተቀበለው መከራ የተመረጠ ጥምቀት ይሆንለታልና፡፡ የሞቱን ምሳሌ በተቀበለ ጊዜ በጌታ አምሳል ሞቷልና፡፡ ሁለት ልብ አይሁን፡፡ እነርሱ ቢገድሉት እርሱም ቢገደል ይጸድቃልና፤ በደሙ ብቻ ተጠምቋልና፡፡

ቍ.761፡- በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምነው ደማቸውን ላፈሰሱ ሁሉ ባረፉበት ቀን መታሰቢያቸውን ያድርጉላቸው፡፡

ቍ.765:- በሰማዕታት በዓል የሚሰበሰቡትን ሰዎች የሚንቃቸው ሰው ትዕቢትን የተመላ ነውና የተወገዘ /የተለየ/ ይሁን፡፡

ቍ.766፡- ምእመናን የክርስቶስን ሰማዕታት ትተው ዓላውያን ሰማዕታ ወደሚሏቸው ቦታ መሄድ አይገባቸውም፡፡ ስለ ክርስቶስ ፍቅር መጋደላችን እንዴት መሆን እንደሚገባው እነሆ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ጻፈ፤ ወደ ሮሜ ሰዎች በላከው መልእክቱ እንዲህ አለ፤ የክርስቶስን ፍቅር ማን ያስተወናል? መከራ ነውን፤ እስራት ነውን፤ ስደት ነውን ረሃብ ነውን፤ መራቆት ነውን መጣላት ነውን፤ ሰይፍ ነውን፤ ስለአንተ ዘወትር ይገደላሉና እንደሚታረዱም በጎች ን ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ በዚህ ሁሉ መከራ የወደደን በመውደዳችን እኛ ድል እንነሳለን፤ እኔም ሊለየኝ የሚችል እንደሌለ አምናለሁ፡፡ ሞት ቢሆን፤ ሕይትም ቢሆን፤ መላእክት ቢሆኑ፤ አለቆችም ቢሆኑ፤ አሁን ያለውም ይመጣም ዘንድ ያለው ሥራ ሁሉ ቢሆን ኃይለኞችም ቢሆኑ፤ ላይኛውም ቢሆን፤ ታችኛውም ቢሆን በኢየሱስ ክርስቶስ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየኝ አይችልም፡፡ /ሮሜ. 8፤35-39/

ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? (ሮሜ 8፡35)

ሚያዝያ 17 ቀን 2007 ዓ.ም.

በዲ/ን ያረጋል አበጋዝ

መጽሐፍ ቅዱስ ከጥንት ጀምሮ የሚነግረንን የሰውና የእግዚአብሔር ግንኙነት ስንመለከት ጎልተው የሚወጡ ሁለት መሠረታዊ ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህም በአንድ በኩል እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ያለው ታላቅ በጎ ሃሳብና ልዩ አባታዊ ቸርነት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ የሰው ልጆች ለዚህ አምላካዊ ጥሪና ቸርነት የሚሰጡት የአጸፌታ መልስ ነው፡፡ የሰዎች አጸፌታዊ መልስም ሁለት ዓይነት ነው፡፡ ይህም ጥቂቶቹ ለአምላካቸው በጎ ምላሽ ሲሰጡ ቀሪዎቹ (በታሪክ ሲታይ ብዙዎቹ) ለአምላካቸው መታዘዝን እምቢ ማለታቸውንና ማመጻቸውን ነው፡፡ የሰው ልጅ ታሪክ የሚያሳየን ከመጀመሪያዎቹ የሰው ልጆች ከአዳምና ከሔዋን ጀምሮ የዲያብሎስን የጎዮንሽ ክፉ ምክር ሰምተው በአምላካቸው ላይ ሲያምጹ፣ ከዚያም የተነሣ ከጸጋ ተራቁተው በራሳቸው ላይ ተደራራቢ ዕዳ በደል ማምጣታቸውን ነው፡፡ ከዚያም ዐመጽ የተጀመረው የሰው ሕይወት እየቀጠለ ክፉው ቃየን የራሱን ወንድም አቤልን በግፍ ደሙን ሲያፈስሰውና ሲገድለው እናያለን፡፡

በሰው ልጆች የመጀመሪያ ጥፋትና ዐመጽ የመጣውን ዕዳና በደል፣ አጠቃላይ በሰው ዘር ላይ የወደቀውን ብዙ ጉዳትና ጥፋት ለማስወገድና ሰውን ወደ ሕይወትና ክብር ለመመለስ ራሱ እግዚአብሔር ሰውን ፍለጋ ልዩ በሆነ አመጣጥ አካላዊ ቃል ሰው ሆኖ ወደ ፈጠራቸው የሰው ልጆች ባሕርያችንን ባሕርዩ አድርጎ ሲገለጥ ደግሞ በደስታ እንደ መቀበል ፋንታ አሁንም ብዙዎች ተቃወሙት፡፡ ነገሩ ድንገት የደረሰባቸውና ያልጠበቁት እንዳይሆንባቸው እግዚአብሔር ከገነት ሲባረሩ ጀምሮ በትንቢት፣ በራዕይ፣ በተምሳሌትና በመሳሰለው ሁሉ ሰው ሆኖ ወደዚህ ዓለም እንደሚመጣ ደግሞ ደጋግሞ ሲናገር ነበር፡፡ ሆኖም ግን ያ ሁሉ ትንቢትና ሱባኤ የተነገራቸው አይሁድ ለማመን የመጀመሪያዎቹ ሊሆኑ ሲገባቸው የእግዚአብሔርን እውነትና ልዩ ጸጋ ለመቀበል አልፈለጉም፡፡ ቅዱስ ወንጌል ውስተ እሊአሁ መጽአ ወእሊአሁሰ ኢተወክፍዎ – የእርሱ ወደ ሆነው መጣ፣ የገዛ ወገኖቹ ግን አልተቀበሉትም በማለት ይህን አሳዛኝ እውነታ ይነግረናል፡፡ ዮሐ. 1፡12

እውነትን የሚቃወሙ አይሁድ ተቃውሟቸውና ጥላቻቸው እያደገ ሄዶ ጫፍ ሲደርስም ምንም እንኳ እርሱ በፈቃዱ ወዶ ቢያደርገውም እነርሱ ግን እናጠፋዋለን መስሏቸው በመስቀል ሰቀሉት፡፡ በመቃብር ለማስቀረትና ከዚያ ወዲያ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ምንም ነገር እንዳይነገርና ታሪክ ብቻ ሆኖ እንዲቀር ለማድረግ በማሰብ መቃብሩን ጥቂት ሰዎች ብቻቸውን ሊያንከባልሉት የማይችሉት ታላቅ ደንጊያ ገጥመው ዘጉት፡፡ ይህም አልበቃቸው ብሎ ከሮማውያን ወታደሮች እንዲመደቡ አድርገው ዙሪያውን እንዲጠብቁ አደረጓቸው፡፡ በገዢው ማኅተምም አተሙት፡፡ ሆኖም ግን ያ ሁሉ ጥረትና ጥበቃ ሥግው ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብሩን ክፈቱልኝ ደንጊያውን አንሡልኝ ሳይል መቃብሩ እንደ ታተመ ሞትን ድል አድርጎ ከመነሣት አላገደውም፡፡ ቅዱሳን መላእክት ወደ መቃብሩ የሄዱትን ቅዱሳት አንስት ምንተ ተኃሥሣሁ ለሕያው ምስለ ምውታን ተንሥአ ኢሀሎ ዝየሰ – ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ? ተነሥቷል እንጂ በዚህ የለም? በማለት የሞትንና የመቃብርን ይዞ የማስቀረትና የማፍረስ የማበስበስ ኃይል ድል አድርጐ መነሣቱን የምሥራች አበሠራቸው፡፡ ሉቃ. 24፡5 ሞትንና የክፋ ኃይልን ሁሉ ድል አድርጎ ለተነሣው ለመድኃኒታችንና ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ክብር ምስጋና ለእርሱ ይሁን!

እርሱ ሞትን ድል አድርጎ ከተነሣ በኋላ ለደቀ መዛሙርቱ ያ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ መከራ የተቀበለውና የሞተው፣ ወደ መቃብር የወረደው እርሱ አሁን ሕያው ሆኖ መነሣቱን በመካከላቸው እየተገኘ የተወጋ ጎኑን፣ የተቸነከሩ እጆቹንና እግሮቹን በማሳየት የተነሣው ያው እርሱ መሆኑን ደጋግሞ አረጋገጠላቸው፡፡ ከዚህም በኋላ እነርሱ ወደ ዓለም ሁሉ ሄደው ይህን የሞትን በክርስቶስ ትንሣኤ መወገድና በእርሱ ለሚያምኑ ሁሉ ሕይወት፣ ልጅነት፣ መንግሥተ ሰማያት በእርሱ ዘንድ የተዘጋጀ መሆኑን እንዲመሰክሩ መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በወረደ ጊዜ ኃይልን ትቀበላላችሁ፥ በኢየሩሳሌምም በይሁዳም ሁሉ በሰማርያም እስከ ምድር ዳርም ድረስ ምስክሮቼ ትሆናላችሁብሎ ላካቸው፤ ። የሐዋ. 1፡8

መድኃኔዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን የሕይወትን ቃል እንዲሰብኩ ወደ ዓለም ሲልካቸው ምን እንደሚጠብቃቸው ሥጋንም የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ፤ ይልቅስ ነፍስንም ሥጋንም በገሃነም ሊያጠፋ የሚቻለውን ፍሩ፣ . . . እያለ አስቀድሞ ደግሞ ደጋግሞ እውነታውን ነግሯቸዋል፣ አስጠንቅቋቸዋል፡፡ ማቴ. 10፡28 እንዲሁም እነርሱን የሚያሳድዷቸው እምነት አያስፈልግም ወይም በእግዚአብሔር መኖር አናምንም የሚሉ ብቻ ሳይሆኑ ይልቁንም እግዚአብሔርን ያገለገሉና ለእርሱ የቀኑ የሚመስላቸው ሃይማኖተኞች ነን ባይ የሆኑ ሰዎችም እንደሚሆኑ እንዳትሰናከሉ ይህን ተናግሬያችኋለሁ። ከምኵራባቸው ያወጧችኋል፤ ከዚህ በላይ ደግሞ የሚገድላችሁ ሁሉ እግዚአብሔርን እንደሚያገለግል የሚመስልበት ጊዜ ይመጣል። ይህንም የሚያደርጉባችሁ አብንና እኔን ስላላወቁ ነው በማለት በሚገባ አስቀድሞ አስጠንቅቋቸዋል፣ አስተምሯቸዋል፡፡ ዮሐ. 16፡1-3 እምነት የለኝም ከሚለው ባላነሰ በተሳሳተ እምነት ውስጥ ያሉም እውነተኛ ክርስቲያኖችን በጽኑ ጭካኔ ሲጨፈጭፉ ኖረዋል፡፡ ማንም ሰው የመሰለውን ማመን ይችላል፡፡ ሆኖም ግን ችግር የሚሆነው ሌላውን ሰው ግድ እኔ የማምነውን ካላመንክ በስተቀር በዚህች ምድር ላይ የመኖር መብት የለህም ሲል ነው፡፡ በምድራችን ላይ ብዙ ግፍ ሲፈጸም የኖረውና አሁንም እየተፈጸመ ያለው ከዚህ የተሳሳተ እምነትና አስተሳሰብ የተነሣ ነው፡- እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ ሰው የሰጠውን ነጻነትና መብት በመጋፋት ሰዎችን በማስተማርና በሳመንና ሳይሆን በኃይልና በጉልበት በማስገደድ የራስን እምነት በሌላው ላይ መጫን፡፡ ይህም ዘርፈ ብዙ ነው፡፡ በእግዚአብሔር እናምናለን የሚሉት ብቻ ሳይሆኑ በእግዚአብሔር መኖር አናምንም፣ ሃይማኖት የለንም የሚሉትም (ይህም በራሱ እምነት ስለሆነ) ሌሎችን እንደ እኛ ካልሆናችሁ በማለት ብዙ ግፍ ሲያደርሱ ኖረዋል፣ ዛሬም ያው ሁኔታ መልኩንና ቅርጹን ቢቀይር እንጂ ጨርሶ አልቀረም፡፡

እንግዲህ የክርስቶስ ተከታዮች (ክርስቲያኖች) ከቅዱሳን ሐዋርያት ጀምሮ በየዘመናቱ የየጊዜውን መስቀል ሲሸከሙና ከመስቀሉ በኋላ የሚገኘውን አክሊል ሲቀበሉ ኖረዋል፡፡ በዘመናት የሚኖሩ ክርስቲያኖች የሚሸከሙት መስቀል አንድ ዓይነት አይደለም፤ ለዚህ ነው ጌታችን መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ ያለው፡፡ ማቴ. 16፡24 መስቀሉን ማለቱ ለእርሱ የተዘጋጀለትን መከራ ማለቱ ነው፡፡ በክርስትና የመጀመሪያው ምስክር የሆነው ቅዱስ እስጢፋኖስ ለአይሁድ የኢየሱስ ክርስቶስን እውነተኛ አምላክነትና መድኃኒትነት፣ እነርሱ (አይሁድ) እንቀበላቸዋለን በሚሏቸው የብሉያት መጻሕፍት ሁሉ የተነገረውና በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው መድኃኒት (መሢሕ) መሆኑን፣ እነርሱም ኢየሱስን መስቀላቸው ታላቅ ጥፋት መሆኑን ሲነግራቸው ተከራክረው መርታት ስላልቻሉ በደንጊያ ወግረው ገደሉት፡፡ . . . ከከተማም ወደ ውጭ አውጥተው ወገሩት። ምስክሮችም ልብሳቸውን ሳውል በሚሉት በአንድ ጎበዝ እግር አጠገብ አኖሩ። እስጢፋኖስም፡- ጌታ ኢየሱስ ሆይ፣ ነፍሴን ተቀበል ብሎ ሲጠራ ይወግሩት ነበር። ተንበርክኮም፡- ጌታ ሆይ፣ ይህን ኃጢአት አትቍጠርባቸው ብሎ በታላቅ ድምፅ ጮኸ። ይህንም ብሎ አንቀላፋ። ሳውልም በእርሱ መገደል ተስማምቶ ነበር። የሐዋ. 7፡57-60 ስለ ክርስቶስ እየመሰከሩ ይህን እውነትና ሕይወት በሚቃወሙ በክፉዎች እጅ መገደልና ሰማዕትነትን መቀበል አንድ ተብሎ ተጀመረ፡፡ በክርስቶስ መከራና መስቀል የተጀመረው የክርስትና ጉዞም በሕይወት መዝገብ ላይ በደም ቀለም መጻፍ ጀመረ፡፡

በመቀጠልም ከሐዋርያት መካከል ቅዱስ ያዕቆብ በሄሮድስ እጅ በሠይፍ በመገደል ሰማዕት ሆነ፡፡ በዚያም ዘመን ንጉሡ ሄሮድስ መከራ ያጸናባቸው ዘንድ ከቤተ ክርስቲያኑ በአንዳንዶቹ ላይ እጁን ጫነባቸው። የዮሐንስንም ወንድም ያዕቆብን በሰይፍ ገደለው። የሐዋ. 12፡1-2 ከዚያ በኋላ ክርስቲያኖችን መግደልና ማሰቃየት እየሰፋና ተቋማዊ መልክ እየያዘ ሄዶ በተለይ በሮማ ግዛት ግዛት ክርስትና በዐዋጅ ሕገ ወጥ ሃይማኖት ነው ተባለ፡፡ በፋርስ ግዛትም እንዲሁ ክርስትና በመንግሥት በይፋ የሚሳደድ ሆነ፡፡ ኔሮን ቄሣር የሮም ከተማ ነዋሪ ክርስቲያኖችን በመግደሉ ሂደት እንዲተባበረውና እንዲደግፈው በማሰብ የከተማን የተወሰነ ክፍል ካቃጠለ በኋላ ይህን ያደረጉት ክርስቲያኖች ናቸው አለ፡፡ ከዚያም ክርስቲኖያችን ያገኛቸው ሁሉ እንደ ሀገር ጠላት በመቁጠር ገደላቸው፡፡ በዚህም ቁጥራቸውን እግዚአብሔር ብቻ የሚያውቃቸው የብዙ ብዙ የሆኑ የክርስቲያኖች ደም ፈሰሰ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስም አንዱ በስቅላት ሌላው በምትረተ ሠይፍ ሞቱ፡፡ አንዳንዶቹ የሮም ቄሣሮች ደግሞ ክርስቲያኖችን ማታ ማታ ሰቅለው በእሳት እያነደዱ እንደ ሻማ እንደ መብራት እስኪጠቀሙባቸው ደረሱ፡፡

በዚያን ዘመን ስለ እግዚአብሔር ፍቅር ብለው ሕይወታቸውን ለሰማዕትነት የሰጡትን ቅዱሳን አባቶችና እናቶች እንዲሁም ሕጻናት ቁጥራቸውን ቀርቶ ግምታቸውን እንኳ ማንም ሊያውቀው አይችልም፡፡ ይህን ለመረዳት አንድ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊ ያለውን ብቻ ጠቅሰን እንለፍ፡፡ በዚያን ዘመን ብዙ ሰዎችን በአንድ ጊዜ በቀላሉ ለመግደል የሚያስችሉ ዘመናዊ የጦር መሣሪያዎች ባለመኖራቸው ምክንያት በግብጽ እና በሦርያ የነበሩ ክርስቲያኖች የሚገድሏቸው ወታደሮች እጃቸው ከመግደል እየደከመና ሠይፋቸው በደም እየታለለ እነርሱም እስኪያርፉና መሣሪያቸውን እስኪወለውሉ ድረስ ክርስቲያኖች በሰማዕትነት ለመገደል ለብዙ ቀናት ወረፋዎችን ይጠብቁ ነበር ይሏል፡፡

መንገድ ላይ እንደ ወደቀውና በድንጋይ ላይ እንደ በቀለው ዘር የጊዜውን መከራ ፈርተውና የዚህን ዓለም ሕይወት ወድደው ክርስቶስን የካዱ ቢኖሩም ብዙዎቹ ክርስቲያኖች ግን በየጊዜው የሚሆነውን መከራ በጽናት ተቀብለው ለሃይማኖታቸው ለክርስቶስ መስክረዋል፡፡ ሲኖሩም ኑሯቸው ሁሉ የሰማዕትነት ሞትን በመጠበቅ ነበር፡፡ ክርስቲያኖችን ከማሳደድ የተመለሰውና ታላቅ ሐዋርያ የሆነው ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህ ሲናገር እንዲህ ያለው ለዚህ ነው፡-

ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ፥ ወይስ ጭንቀት፥ ወይስ ስደት፥ ወይስ ራብ፥ ወይስ ራቁትነት፥ ወይስ ፍርሃት፥ ወይስ ሰይፍ ነውን? ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን፥ እንደሚታረዱ በጎች ተቆጠርን ተብሎ እንደ ተጻፈ ነው። በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን። ሞት ቢሆን፥ ሕይወትም ቢሆን፥ መላእክትም ቢሆኑ፥ ግዛትም ቢሆን፥ ያለውም ቢሆን፥ የሚመጣውም ቢሆን፥ ኃይላትም ቢሆኑ፥ ከፍታም ቢሆን፥ ዝቅታም ቢሆን፥ ልዩ ፍጥረትም ቢሆን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼያለሁ። ሮሜ 8፡36-39

እግዚአብሔርም ምእመናን መከራውን በጽናት እንዲቀበሉ በቅዱስ ቃሉ፣ አጽናኝና አበረታች መላእክትን በመላክና በተለያዩ መንገዶች ሥቃዩን ያሥታግሣቸውና ያበረታቸው ነበር፡፡ ለአብነትም በሮማውያን ቄሣሮች በእነ ኔሮንና ድምጥያኖስ ዘመን ይደርስ የነበረውን መከራ በራእየ ዮሐንስ ላይ በታናሽ እስያ የነበሩትን የቤተ ክርስቲያን አባቶች እንዲህ በማለት ያበረታታቸው ነበር፡-

በሰምርኔስም ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ። ሞቶ የነበረው ሕያውም የሆነው ፊተኛውና መጨረሻው እንዲህ ይላል። . . . ልትቀበለው ያለህን መከራ አትፍራ። እነሆ፥ እንድትፈተኑ ዲያብሎስ ከእናንተ አንዳንዶቻችሁን በወኅኒ ሊያገባችሁ አለው፥ አሥር ቀንም መከራን ትቀበላላችሁ። እስከሞት ድረስ የታመንህ ሁን፣ የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ። መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ። ድል የነሣው በሁለተኛው ሞት አይጐዳም። ራ. 2፡8-11

ስለ ክርስቶስ ፍቅር ሲሉ ወንዶች ብቻ ሳይሆኑ ሴቶችም መከራውን በጽናት ይቀበሉ ነበር፡፡ አንዲት ነፍሰ ጡር የነበረች እናት ሃይማኖቷ ክርስቲያን በመሆኑ ምክንያት ብቻ ታስራ ሳለ በሮማውያን ሕግ ነፍሰ ጡሮች አይገደሉ ስለ ነበር ምነው በውስጤ ያለው ጽንስ ቶሎ ተወልዶልኝ ለሃይማኖቴ መስክሬ በሞትኩ ብላ ጸለየች፡፡ ልትወልድ ስትል ምጡ ሲያስጨንቃት ከጠባቂዎቹ ወታደሮች መካከል አንዱ ባያት ጊዜ ምነው ቶሎ ብዬ ለክርስቶስ መስክሬ በሞትኩ ስትይ አልነበር? ተፈጥሯዊ የሆነው ምጥ ይህን ያህል ካስጨነቀሽ ከእኛ እጅ የምትቀበዪውን መከራማ እንዴት አድርገሽ ትችይዋለሽ? አላት፡፡ እርሷም ይህን (ምጡን) የምቀበለው ብቻዬን ነው፤ ስለ ክርስቶስ የምቀበለውን መከራ ግን የምቀበለው ብቻዬን ሳይሆን ከክርስቶስ ጋር ነው፣ እንዲያውም መከራውን የሚቀበለው ራሱ ነው አለችው፡፡ አዎ፣ ስለ ክርስቶስ ያልተከፈለ ዋጋ የለም፤ ለእርሱ የማይከፈል ውድ ዋጋም የለም!

አሁንም ክፉዎች የመዳንን መንገድና እውነትን አንቀበልም ማለታቸው ሳያንስ ሌሎችንም እንደ እኛ ካልሆናችሁ በማለት ለማስገደድና የራሳቸውን አስተሳሰብና እምነት በሌሎች ላይ በኃይል ለመጫን ዘመናዊ የጦር መሣሪያ ታጥቀው ክርስቶስን አንክድም የሚሉ ክርስቲያኖችን አንገታቸውን እንደ ከብት አጋድመው በሠይፍ እያረዱ ይገኛሉ፡፡ ራሱን እስላማዊ መንግሥት – Islamic State (IS) ብሎ የሚጠራው ቡድን ከወር በፊት 21 ግብጻውያን ክርስቲያን ወንድሞቻችንን ክርስቶስን አንክድም በማለታቸው ብቻ አንገታቸውን አርደው ገድለዋቸዋል፡፡ በሶሪያና በኢራቅ በየጊዜው ብዙ ክርስቲያኖች በሃይማኖታቸው ምክንያት ብቻ ይገደላሉ፣ ይሠቃያሉ፤ የቀሩትም ሀገር ለቀው ይሄዳሉ፡፡

ሰሞኑንም ይኸው ራሱን እስላማዊ መንግሥት – Islamic State (IS) ብሎ በሚጠራው ቡድን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ፍቅር ታምነው የክርስትና ሃይማኖታቸውን አንክድም በማለታቸው ምክንያት የተወሰኑት በጥይት ተደብድበው፣ ሌሎቹ ደግሞ በአሰቃቂ ሁኔታ በሠይፍ ታርደው የተገደሉትን ክርስቲያን ኢትዮጵያውያን ወንድሞቻችንን ስናስብ መከራቸውና ስቃያቸው ይሰማናል፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ ለእመ አሐዱ አካል ሐመ የሐምም ምስሌሁ ኩሉ ነፍስትነ – አንድም አካል ቢሣቀይ ብልቶች ሁሉ ከእርሱ ጋር ይሣቀያሉ፤ እናንተም የክርስቶስ አካል ናችሁ እያንዳንዳችሁም ብልቶች ናችሁ እንደሚለው የእነርሱ ጭንቀትና ስቃይ የእኛም ጭንቀትና ስቃይ ነውና። 1 ቆሮ. 12፡26-27 እነርሱስ አንድ ጊዜ ተቀብለውት ሄደዋል፣ ለእኛ ግን በየጊዜው የማይረሳና ባስታወሱት ቁጥር ውስጥን የሚያደማ የማይሽር የሕሊና ቁስል ነው፡፡ እነዚህ የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልጆች የተቀበሉት መከራና ግፍ የሁላችንም መከራና ግፍ ነው፡፡ ክርስቲያኖች ስለ ክርስቶስ የሚቀበሉት መከራና የሚጋደሉት ተጋድሎ የቤተ ክርስቲያን ራስ የሆነው የክርስቶስ የመከራው አካል ነው፡፡ ጌታችን የኋላውን ቅዱስ ጳውሎስ የቀደመውን ሳውል በሚያስደንቅ ሁኔታ ሲጠራው ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ? አለው፡፡ እርሱም ጌታ ሆይ ማን ነህ? ባለው ጊዜ አንተ የምታሳድደኝ እኔ ኢየሱስ ነኝ ያለው ይህን የሚገልጽ ነው፡፡ የሐዋ. 9፡3-5 ጌታችን የክርስቲያኖችን ስደትና መከራ የራሱ አድርጎ ለምን ታሳድደኛለህ? አንተ የምታሳድደኝ እኔ ኢየሱስ ነኝ አለው እንጂ ለምን ታሳድዳቸዋለህ? አላለውም፡፡ ስለሆነም እነዚህ ወንድሞቻችን ስለ ሃይማኖታቸው የተጋደሉት ተጋድሎና የተቀበሉት መከራ የክርስቶስ የመከራው አካል ነው፤ የሰውነት የአካል ክፍሎች የሚሠሩት ሥራ የራስ ሥራ አካል ነውና፡፡

ይህ የወንድሞቻችን መከራና የግፍ ሞት ሁለት ገጽታ ያለው ነው፡፡ በአንድ በኩል የገዳዮቻቸውን ጭካኔና አረመኔነት ስንመለከተውና የወንድሞቻችንን ስቃይ ስናስበው በእጅጉ ይዘገንናል፤ ማንኛውንም ሰው የሆነን ሁሉ ይነካል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የመዳን መንገድ ስለ ሆነችው ስለ ክርስትና እምነታቸው ሲሉ በእግዚአብሔር ኃይል ጨክነው ለክርስቶስ መስክረው መሞታቸውንና እስከ መጨረሻው ድረስ መጽናታቸውን ስናስበው ደግሞ ልዩ የሆነ ደስታ ይፈጥራል፡፡ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከጥቂት ቀናት በፊት በግብጽ 21 ክርስቲያኖች እምነታቸውን እንደ መሰከሩ ሁሉ አሁን ደግሞ ከኢትዮጵያ 30 እውነተኛ መስካሪዎችን አገኘች፡፡ እነዚህ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ፍሬዎች ናቸውና! እንኳን ወላጆቻቸውንና ከዚህ ሞታቸው አስቀድሞ ያውቋቸው የነበሩት ሰዎች ይቅርና አገዳደላቸውን የሚያሳየውንና አይ ኤስ የለቀቀውን ምስል ወድምፅ የተመለከተን ማንኛውንም ሰው በእጅጉ ያሳዝናል፡፡ ሆኖም ግን እነዚህ ወንድሞቻችን በቅድስት ሥላሴ ስላላቸው እምነት፣ ስለ ክርስቶስ አምላክነትና መድኃኒትነት፣ በአጠቃላይ ሐዋርያዊትና ኦርቶዶክሳዊት ስለ ሆነችውና ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ስለ ተሰጠችው አንዲት ሃይማኖት መስክረው መሞታቸው እያሳዘነ የሚያስደስት፣ እያስለቀሰ እልል የሚያሰኝ ነው፡፡ በቀድሞ ዘመን ክርስቲያኖች ለሃይማኖታቸው መስክረው ወደሚገደሉባቸው ቦታዎች ሲወሰዱ እናቶችና አባቶች ልጆቻቸውን፣ ሚስቶች ባሎቻቸውን፣ ወዳጅም ወዳጁን አይዞህ፣ በርታ፣ ጽና፣ ምስክርነትህን ፈጽም፣ የምትሄደው ወደ ክርስቶስ ነው እያሉ አንዱ ሌላውን ያበረታታ ነበር፡፡ ስለዚህ የእነዚህ ወንድሞቻችን ቤተሰቦች ሰው እንደ መሆናቸው ማዘን ባይቀርም የእነዚህ እውነተኛ ክርስቲያን ወላጆች ቤተሰቦች በመሆናቸው ሊደሰቱና እግዚአብሔርን ሊያመሰግኑ ይገባቸዋል፡፡ ይህ ለሁሉ የሚገኝ
ጸጋና ክብር አይደለምና!

መከራው የክርስቶስን ቤተ ክርስቲያን ጎዳት? ወይስ ጠቀማት?

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዘመነ ሰማዕታት በገጠማት በዚያ ሁሉ መከራ እየደከመች ሄደች ወይስ እየጠነከረች? የምእመናን ቁጥርስ እያነሰ ሄደ ወይስ እየበዛ? ታሪክ እንደሚያስረዳን በክርስቶስ በሞቱና በትንሣኤው የተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመከራው እየበዛችና እየጠነከረች ሄደች እንጂ ጠላቶቿ እንዳሰቡት እየደከመችና እየጠፋች አልሄደችም፡፡ ይልቁንም አሳዶጆቿና ገዳዮቿ የነበሩት ቄሣሮች እነ ኔሮን፣ እነ ድምጥያኖስ፣ እነ ትራጃን፣ እነ ዳክዮስ፣ እነ ቫሌንቲኖስ፣ እነ ጋሌሪዮስ፣ እነ መክስምያኖስ፣ እነ ድዮቅልጥያኖስ፣ እነ ሉቅያኖስና መሰሎቻቸው ሞተው የት እንደ ወደቁ መቃብራቸው እንኳ የማይታወቅ ሲሆን እነርሱ የገደሏቸውና ያሰቃዩዋቸው ክርስቲያኖች ግን ስማቸው በዓለም ይታወቃል፣ መቃብራቸውንና ዐጽማቸው ያረፉባቸውን ቤተ ክርስቲያኖች ምእመናን በታላቅ ክብርና ፍቅር ይሰለሟቸዋል፡፡ ከላይ የተጠቀሱትንና ሌሎችንም ያልተጠቀሱትን ገዳዮቻቸውን ግን በመልካም እንኳ የሚያነሳቸው የለም፣ በግፍ የሞቱትን ቅዱሳን ክርስቲያኖች ግን የክርስቲያኑ ዓለም ብቻ ሳይሆን ቅን ሕሊና ያለው ሰው ሁሉ የሚያከብራቸው ናቸው፡፡

ክርስትና በዓለም የተስፋፋው በአፍና በመጽሐፍ በሚደረገው ስብከት ብቻ አልነበረም፤ ክርስቲያኖች ለክርስቶስ ፍቅር ሲሉ ዓይናቸው እያየ ሞትን ሲንቁትና ፊት ለፊት ሲጋፈጡት በማየትም ነበር እንጂ፡፡ እንደ ሌላው ሰው ሁሉ ሰውነታቸው ሕማምና መከራ የሚሰማውና ስቃይን የማይወድ፣ ለአካላቸው መለዋወጫ፣ ለሕይወታቸውም ምትክ የሌላቸው ሲሆን እንዲህ ሞትን የሚንቁትና ደስ እያላቸው የሚሞቱት በትምህርታቸው እንደሚሉት አምላካቸው በእውነት ሞትን በትንሣኤው ድል ያደረገው በመሆኑና ከዚህ ዓለም ሕይወት በኋላ እርግጠኛ የሆነ ሌላ ሕይወት ቢኖር ነው እያሉ አሕዛብ ከክርስቲያኖች የምስክርነት ዐውድ ሕያው ወንጌልን ይማሩ ነበር፡፡ ከዚህ የተነሣ ክርስቲያኖቹን እንዲገድሉ ከተመደቡት ወታደሮች መካከል እንኳ ሳይቀር በክርስቲያኖች ጽናትና በስቃያቸው ጊዜ እግዚአብሔር በእነርሱ ላይ ከሚሠራቸው የተለያዩ ገቢረ ተአምራት የተነሣ እኔም በእነዚህ ሰዎች አምላክ አምኛለሁ እያሉ በደማቸው እየተጠመቁ ሰማዕታት የሆኑ ብዙዎች አሉ፡፡

ለአብነትም በአርብኣ ሐራ ሰማዕታት የተፈጸመውን ብቻ እናስታውስ፡፡ የሮማ የምሥራቁ ክፍለ ግዛት ገዢ በነበረው በሉቅያኖስ ባለ ሥልጣናት ለጣዖታት መሥዋዕት እንዲያቀርቡ ሲታዘዙ እምቢ በማለታቸው በከተማው ውስጥ በነበረ አንድ በረዷማ የውኃ ኩሬ ላይ የጣሏቸው አርባ ክርስቲያን ወታደሮች ነበሩ፡፡ ከዚያ ከተጣሉበት በረዷማ ኩሬ ፊት ለፊት ደግሞ ለመታጠቢያነት ተስማሚና ምቹ የሆነ የፍል ውኃ መታጠቢያ ነበር፡፡ ከአርባው መካከል አንደኛው ከቅዝቃዜው ጽናት የተነሣ አውጡኝ አለና ወዲያውኑ እየሮጠ በሙቅ ውኃው መታጠቢያ ለመታጠብ ሄደ፡፡ ወዲያውኑ እንደ ገባም ሰውነቱ ብስክስክ ብሎ ሞተ፡፡ የእነዚያን ተጋዳይ ወታደሮች ሥቃያቸውን ሲከታተሉ ከነበሩት አስፈጻሚ ወታደሮች መካከል አንደኛው ራሱን በፍል ውኃው እያሞቀ ይህን እንግዳ ነገር እየተመለከተ ነበር፡፡ በዚያን ጊዜም መላእክት ከሰማያት ወርደው ለአርባው ተጋዳዮች አክሊል ሲያቀዳጇቸው የአንደኛው አክሊል ግን ተንጠልጥሎ በአየር ላይ ሲቀር ተመለከተ፡፡ ያን ጊዜ ያ ወታደር በወጣው ሰው ቦታ ገብቶ በክርስቶስ ታምኖ ወዲያውኑ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ፡፡ (ቅዱስ ባስልዮስ፣ ስለ አርብኣ ሐራ ሰማዕታት፣ ትምህርት፣ ትምህርት 19)

በተለይም ደግሞ በጣም ብዙ ክርስቲያኖችን በመግደልና በማሰቃየት ወደር ያልነበረውን አርያኖስ የተባለውን የግብጽ ገዢ ፍጻሜ ማስታወሱ ለዚህ ሕያው ጥሩ ማሳያ ነው፡፡ አርያኖስ በሮማ ግዛት ውስጥ ክርስቲያኖችን በማሰቃየትና በእነርሱ ላይ ይፈጽም በነበረው በጭካኔው ወደር የለሽ ነበር፡፡ አንድ ቀንም የእርሱ አጫዋች (አዝማሪ) የነበረው ፈልሞን በፊቱ ቆሞ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምን ክርስቲያን መሆኑ መሰከረ፡፡ ያን ጊዜ አርያኖስ ፊልሞንን እና አብላዮስ የተባለውን ጓደኛውን በፍላጻ እንዲነድፏቸው አዘዘ፡፡ አንዲት ፍላጻም ወደ አርያኖስ ተመልሳ ዓይኑን አወጣችው፣ የፍላጻው ሕማምም እጅግ አሠቃየው፡፡ በጣም እየተሠቃየ ሳለ ከክርስቲያኖቹ አንዱ ከሰማዕታቱ ደም ወስደህ ብትቀባው ትድን ነበር አለው፡፡ እርሱም ይህን ያህል እየጠላኋቸውና እያሰቃየኋቸው ይምሩኛልን? ቢላቸው አዎ፣ በክርስትና ጠላትን መውደድና ለጠላት መጸለይ እንጂ መበቀል የለም አሉት፡፡ እንደ ነገሩት ከሰማዕታቱ ደም ወስዶ ቁስሉን ሲቀባው ወዲያውኑ ተፈወሰ፡፡ ከዚያ በኋላ እርሱም በክርስቲያኖች አምላክ አምኖ ጣዖታቱን ሰባብሮ ክርስቲያኖችን ምሕረት የሌለው ሥቃይ ስላሠቃያቸው ታላቅ ጸጸት ተጸጸተ፡፡ ከዚያም ስለ ክርስቶስ መስክሮ በሌላ ገዢ ተገድሎ ሰማዕትነትን ተቀበለ፡፡ (ስንክሳር መጋት 7 እና 8)

ኢየሱስ ክርስቶስ ሞቶ ሞትን ድል ማድረጉና የሞትን ኃይልና አስፈሪነት ማጥፋቱ ለሰዎች ከተገለጠበትና ለዓለምም ከሚገለጥበት አንደኛው መንገድ ይህ የክርስቶስ አካላትና ተከታዮች (ክርስቲያኖች) መከራንና ሞትን በጽናት መቀበላቸው፣ ሞትን መናቃቸውና ፊት ለፊት መጋፈጣቸው ነው፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ የማያምኑ ወይም ስለሚመጣው ሕይወት በሃይማኖታቸው ቁርጠኛ ያልሆኑ ሰዎች እንደ ጦር የሚፈሩትን ሞት፣ እንዲሁም ሌት ተቀን የሚጨነቁለትን የዚህን ዓለም ሕይወት በክርስቶስ ትንሣኤ ያመኑ ክርስቲያን ሰማዕታት ሲንቁትና ፊት ለፊት ሳይፈሩ ስለ ክርስቶስ ፍቅር ሲሉ ሲጋፈጡት ሲያዩ ብዙዎች ከሞት በላይና ባሻገር ስላለው ሕይወትና እውነት በሰማዕታት ጽናትና ብርታት አማካይነት ተምረዋል፡፡ ከአሕዛብ ወገን፣ ሰማዕታቱን ይገድሉና ያሠቃዩ ከነበሩት ከወታደሮችም ሳይቀር በዚሁ ተስበው ለሰማዕትነት የበቁት በጣም ብዙዎች ናቸው፡፡

እንደዚሁም ደግሞ ክርስቶስ ሞትን ድል ባያደርገው ኖሮ ሰማዕታትም ሞትን መጋፈጥና መናቅ ባልቻሉ ነበር፡፡ የእነርሱ ተጋድሏቸው፣ መከራቸውና ድል አድራጊነታቸው የመስቀሉ ድል፣ የትንሣኤው ኃይል ቀጣይ አካልና ሕያው ምስክር ነው፡፡ የእነርሱ ጽናትና ተጋድሎ ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል ያደረገው መሆኑን በተግባር የሚመሰክሩ ምስክሮች ናቸው፤ ምስክሮችህ ድንቆች ናቸው፣ ስለዚህም ነፍሴ ፈለገቻቸው እንደ ተባለ፡፡ ቅዱሳን ሰማዕታት ሰማዕታት – ምስክሮች፣ መስካሪዎች የተባሉትም ለዚህ ነው፡፡ መዝ. 118፡129

ስለሆነም መከራ መስቀል ክርስትና የተመሠረተበት፣ ያደገበትና የኖረበት ሕይወት እንጂ አዲስ ነገር አይደለም፡፡ ክርስትናን የሚያዳክመው መከራ ሳይሆን ምንነቱን አለመረዳትና ቁሳውይነት፣ ቅምጥልነትና ሥጋውይነት ናቸው፡፡ ሰማዕትነትማ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሞትን ያህል ከባድ ነገር ስለ ክርስቶስ ፍቅር ሲሉ ሞትን ባሸነፈው በትንሣኤው ኃይል የናቁትንና ለብዙዎች ኢአማንያን በክርስቶስ ማመንና ሰማዕት እስከ መሆን መድረስ ምክንያት የሆኑ ብዙ መንፈሳዊ ጀግኖችን ያፈራችበት ነው፡፡ ለዚህ ነው በሁለተኛው መቶ ዓመት ማብቂያና በሦስተኛው መቶ ዓመት መጀመሪያ ላይ የነበረው የክርስትና መብት ተሟጋቾችና ጠበቆች መካከል አንዱ የሆነው የሰሜን አፍሪካው የቅርጣግናው ሊቅ ጠርጠሉስ ስለ ክርስትና እምነት ንጹሕነትና እውነተኛነት ለአሳዳጆችና ለመከራ ዳራጊዎች በጻፈው የጥብቅና መጽሐፍ ላይ እንዲህ ሲል የገለጸው፡-

“አሠቃዩን፣ ግደሉን፣ ንቀፉን፣ ኰንኑን፣ አቃጥሉን፣፤ የእናንተ ክፋት፣ ግፍና ጭካኔ የእኛ ንጽሕና ማረጋገጫ ነው፡፡ እናንተ በወገራችሁንና በቆረጣችሁን መጠን ቁጥራችን እልፍ እየሆነ ይሄዳል፤ ደመ ሰማዕታት የክርስቲያኖች ዘር ነው፡፡ – Torture us, condemn us, crucify us, destroy us! Your wickedness is the proof of our innocence. . . . The more we are hewn down by you, the more numerous do we become. The blood of the martyrs is the seed of the Church. Apologeticus, Chapter 50)

አዎ፣ ምንም ያልበደሏቸውንና አንዳችም መከላከያ የሌላቸውን ወንድሞቻችንን በክርስትና ሃይማኖታቸው ምክንያት ብቻ በግፍ መግደላቸው ሁለት እውነታዎችን ፍንትው አድርጎ ያሳያል፡፡ ከእነዚህም አንደኛው እውነተኛ ክርስቲያኖች ለክርስቶስ ያላቸውን ፍቅርና ጽናት፣ እንዲሁም እውነተኛነት ነው፡፡ ሌላው ደግሞ የገዳዮቹ እምነታቸው ከመሠረቱ ስህተትና ውሸት መሆኑን ነው፡፡ ምክንያቱም እውነትን የያዘ ሰው ያ አምነዋለሁ የሚለውን እውነት በማስረዳት ማሳመን ይገባዋል እንጂ እውነትን በግድ መጫን አይቻልም፡፡ ስለሆነም ገዳዮቹ እምነታቸውና አስተሳሰባቸው ሌላውን ሰው ሊያሳምን የማይችል ደካማና ሐሰት ስለሆነ በኃይልና በመሣሪያ ኃይል ካልሀነ በስተቀር የሰውን አእምሮ ማሳመን የማይችል መሆኑን ራሳቸው ቀርጸው ያሠራጩት ምስልና ድምፅ ይመሰክርባቸዋል፡፡ በዚህም በአንድ በኩል እግዚአብሔርን አምነውና መስክረው የሞቱትን የወንድሞቻችንን አሟሟትና ማንነት እንድናውቅ ስላደረጉን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የራሳቸውን የገዳዮቹን የእምነት አስተሳሰብ ባዶነትና ሐሰትነቱ ከጥንትም የታወቀ ቢሆንም አሁን ደግሞ ከራሳቸው ንግግርና ድርጊት እንዲጋለጥ ያደረገውን ምስል ወድምፅ በማሠራጨታቸው እናመሰግናቸዋለን፡፡ እንደ ገደሏቸው ሳይነግሩን የሆነ ቦታ ጥለዋቸው ብቻ ቢሆን ኖሮ ዓለም ይህን ሁሉ ትምህርት ከየት ያገኝ ነበር?

በመጀመሪያው መቶ ዓመት ማብቂያ ገደማ በተፈጸመው የክርስቲያኖች ጭፍጨፋ ስለ ክርስቶስ መስክረው የሞቱ ቅዱሳን ሰማዕታት ነፍሳቸው እንዲህ ብላ ወደ እግዚአብሔር ፍትሕን ጠይቃ ነበር፡- “አምስተኛውንም ማኅተም በፈታ ጊዜ፥ ስለ እግዚአብሔር ቃልና ስለ ጠበቁት ምስክር የታረዱትን የሰዎች ነፍሳት ከመሠዊያ በታች አየሁ። በታላቅ ድምፅም እየጮኹ፡- ቅዱስና እውነተኛ ጌታ ሆይ፣ እስከ መቼ ድረስ አትፈርድም? ደማችንንስ በምድር በሚኖሩት ላይ እስከ መቼ አትበቀልም? አሉ።” በዚህ ጊዜ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጣቸው መልስ “እንደ እነርሱም ደግሞ ይገደሉ ዘንድ ያላቸው የባሪያዎች ባልንጀራዎቻቸውና የወንድሞቻቸው ቍጥር እስኪፈጸም ድረስ ገና ጥቂት ዘመን እንዲያርፉ ተባለላቸው” የሚል ነበር። ራእ. 6፡9-11 እስከዚያው ድረስ ግን “ለእያንዳንዳቸውም ነጭ ልብስ ተሰጣቸው፡፡”

እግዚአብሔር ክርስቲያኖችን በግፍ በገደሏቸው ላይ ፍርድን በቶሎ ያልሰጠበት ዋና ምክንያት እንደ እነዚያ ያሉና ስለ ክርስቶስ መስክረው የሚሞቱ በየዘመኑ የሚነሡ ሰማዕታት መኖራቸውን እርሱ በአምላክነቱ ስለሚያውቅ ይህ የሰማዕትነት ዕድል እንዳይቀርባቸው ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን በየጊዜው ለክርስቶስ እየመሠከሩ የሚሞቱ አሉና እርሱ የሚያውቃቸው እነዚያ ሰዎች ለዚህ ክብር ሳይበቁ እንዳይቀሩ የፍርድ ጊዜውን እርሱ ባወቀ አቆይቶታል፡፡ ግፍ ፈጻሚዎችን ቀድሞ በአንደኛው መቶ ዓመት ላይ አጥፍቷቸው ቢሆን ኖሮ ከዚያ በኋላ እስከ ዛሬ ድረስ፣ ወደፊትም እንዲሁ እርሱ የሚያውቃቸው ሰማዕታት ይህን የሰማዕትነት አክሊል አያገኙም ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያንም እነዚህን የመሰሉ ጌጦቿን አታገኝም ነበር፡፡ ሰማዕታት የቤተ ክርስቲያን ጌጦች ናቸውና፤ በከመ ከዋክብት ያሠረግውዎ ለሰማይ በሥኖሙ ከማሁ ሰማዕትኒ ያሠረግውዋ ለቤተ ክርስቲያን በገድሎሙ – ከዋክብት ሰማይን በውበታቸው እንደሚያስውቡት ሰማዕታትም በገድላቸው ቤተ ክርስቲያንን ያስጌጧታል እንዳለ ቅዱስ ያሬድ፡፡ (ጾመ ድጓ ዘቴዎቅሪጦስ)

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰማዕትነትን መቀበል ሕይወቷ ነው፡፡ በዮዲት ጉዲት ዘመን፣ በግራኝ አህመድ ዘመን፣ በሱስንዮስ ዘመን ቁጥራቸውን እግዚአብሔር ብቻ የሚያውቃቸው ብዙ ክርስቲያኖች በሰማዕትነት መስክረው ዐርፈዋል፡፡ በሙሶለኒ ፋሽስት ወረራ ዘመንም እንዲሁ የደብረ ሊባኖስ፣ የዝቋላ፣ የማኅበረ ሥላሴ፣ እንዲሁም የሌሎች የብዙ ገዳማት መነኰሳትና ባሕታውያን ስለ ሃይማኖታቸው በግፍ ተጨፍጨው በሰማዕትነት ሞተዋል፡፡ ገዳማቱ ግን አሁንም አሉ፣ መነኰሳትና ባሕታውያንም፣ ምአመናንም እንዲሁ አሉ፡፡ ክፉ ያደረጉት ተጎዱ እንጂ ክፉው የደረሰባቸውን አልጎዷቸውም፡፡ እውነተኛ ጉዳት ማለት በጊዜው ጊዜ አይቀር የነበረውን የሥጋ ሞት በሰው እጅ መቀበል ሳይሆን መልካም ሊሠሩበት በተሰጣቸው ጊዜና አእምሮ በሰዎች ላይ ግፍና ጭካኔ ፈጽሞ ከእግዚአብሔር መለየትና ሊቀር ይችል የነበረውን ሞተ ነፍስ በፈቃድ በራስ ላይ ማምጣት ነውና፡፡

ስለሆነም እንዲህ ለሚያደርጉ ክፉዎች ሰዎች ልናዝንላቸውና ልንጸልይላቸው ይገባል፡፡ ጌታችን እንዲህ ብሎ አስተምሮናልና፡

ባልንጀራህን ውደድ ጠላትህንም ጥላ እንደ ተባለ ሰምታችኋል። እኔ ግን እላችኋለሁ፣ በሰማያት ላለ አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፣ የሚረግሟችሁንም መርቁ፣ ለሚጠሏችሁም መልካም አድርጉ፣ ስለሚያሳድዷችሁም ጸልዩ፤ እርሱ በክፉዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን ያወጣልና፣ በጻድቃንና በኃጢአተኞችም ላይ ዝናቡን ያዘንባልና። የሚወዷችሁን ብትወዱ ምን ዋጋ አላችሁ? ቀራጮችስ ያንኑ ያደርጉ የለምን? ወንድሞቻችሁንም ብቻ እጅ ብትነሡ ምን ብልጫ ታደርጋላችሁ? አሕዛብስ ያንኑ ያደርጉ የለምን? እንግዲህ የሰማዩ አባታችሁ ፍጹም እንደ ሆነ እናንተ ፍጹማን ሁኑ።ማቴ. 5፡43-48

አዎ፣ ክርስትና የሚጠሉንን የምንጠላበትና ክፉ ያደረጉብንን በዚያው በክፋት መንገድ አጸፋ የምንመልስበት ሳይሆን ስለ ክፉ አድራጊዎቹ ጥፋት ከልብ የምናዝንበትና የጥፋታቸውን ምንነት ተረድተው ወደ አእምሯቸው ይመለሱ ዘንድ እግዚአብሔርን የምንለምንበት ሕይወት ነው፡፡ ክርስትና ድንጋይ ለወረወረብን መልሰን የምንወረውርበት፣ ጉድጓድ በማሰብን ላይ ሌላ ጉድጓድ የምንቆፍርበት አይደለም፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰቀሉትና ያ አልበቃቸው ብሎ ተጠማሁ ባለ ጊዜ እንኳ መራራ ሐሞትን በአፉ ላደረጉለት ለክፉዎች አይሁድ እንኳ አባት ሆይ፣ የሚያደርጉትን አያውቁም ይቅር በላቸው ብሎ እንደ ጸለየላቸው እኛም ለክፉ አድራጊዎችና ለጠላቶቻችን የምንጸልይበት ሕይወት ነው፡፡ አለዘበለዚያ የእርሱ ደቀ መዛሙርት ልንሆን አንችልም፡፡ ክፉዎች ክፉ በመሆናቸው በእነርሱ ክፋት ተገፋፍቶ ወይም እልክ ውስጥ ገብቶ እነርሱ በሄዱበት የክፋት መንገድ መሄድ ገና ከጅምሩ መሸነፍና ድል መነሣት ነውና፡፡ ምክንያቱም የክፉ ሰው ድርጊቱና ዓላማው ሌላውንም እንደ እርሱ ክፉ ማድረግና ወደ እርሱ የክፋት አስተሳሰብና ድርጊት እንዲሳብ ማድረግ ነው፡፡ ስለዚህ የእኛ አስተሳሰብና ድርጊት እንደ ክፉዎቹ ሰዎች አስተሳሰብና ድርጊት ከሆነ ብርሃን ወደ ጨለማ፣ ጨው ወደ አልጫ ተለወጠ ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ገና ሲጀመር መሸነፍ ነው፤ ክፉው መልካሙን አጠፋው ማለት ነውና፡፡ ለዚህ ነው ቅዱስ መጽሐፍ ክፉውን በመልካም አሸንፉ እንጂ በክፉ አትሸነፉሲል በአጽንዖት የሚያስጠነቅቀን፡፡ ሮሜ 12፡21 በክፉ መሸነፍ ማለት ወደ ክፋ መሳብና ክፉዎቹ እንደሚያደርጉት ለማድረግ መነሣት ነው፡፡ ስለዚህም ነው ክፉውን በመልካም አሸንፉ እንጂ ካለ በኋላ ቀጥሎ በክፉ አትሸነፉ አለ እንጂ “በክፉ አታሸንፉ” አላለም፡፡ ምክንያቱም ክፉን በመልካም ብቻ እንጂ በክፉ
ማሸነፍ አይቻልምና፡፡ ክፉ መሆን ከጀመረ ግን በክፉ ተሸንፏል ማለት ነው፡፡ ሰው በክፉዎች ምክንያት እርሱም የሚከፋ ከሆነ ከጅምሩ ተሸንፏል ማለት ነውና፡፡ ፡፡

ሰማዕቱ ቅዱስ እስጢፋኖስ የድንጋይ ናዳ ሲያወርዱበት ለነበሩት አይሁድ ጌታ ሆይ፣ ይህን ኃጢአት አትቍጠርባቸው ብሎ ጸለየላቸው እንጂ አጥፋቸው አላለም፡፡ ይህ የቅዱስ እስጢፋኖስም ጸሎት እንዲሁ በከንቱ አልቀረም፡፡ እርሱን ሲወግሩ የነበሩትን ሰዎች ሲያስተባብርና ልብሳቸውን ሲጠብቅ የነበረው ሳውል የተባለው ኃይለኛ ጸረ ክርስቲያን ወጣት (የኋላው ቅዱስ ጳውሎስ) የእግዚአብሔር ቸርነት ልቡን እንዲነካውና ወደ ክርስትና እንዲመለስ ታላቅ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ ይህንንም አንድ ሊቅ የቅዱስ እስጢፋኖስ ጸሎት ለቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ጳውሎስን አስገኘላት ብሏል፡፡ በየዘመናቱ የነበሩ ክርስቲያኖች ሁሉ መከራ በሚያደርሱባቸው ላይ እንዲሁ ስህተታቸውን የሚገነዘብ ልቡና እንዲሰጣቸውና ወደ እውነት እንዲመለሱ ጸለዩላቸው እንጂ በክፉው መንገድ እንበቀላቸው ብለው አልተነሡም፡፡ በዘመነ ዲዮቅልጥያኖስ ታላላቅ የቤተ መንግሥት ተወላጆችና መኳንንት ከነበሩት ወገን ሰማዕትነትን የተቀበሉት እነ ቅዱስ ቴዎድሮስ፣ ቅዱስ ፋሲለደስ፣ ቅዱስ ዮስጦስ፣ ቅዱስ አቦሊ፣ ቅዱስ ፊቅጦር . . . በጦር ሜዳ ጀግንነታቸውና አርበኝነታቸው የታወቁ ኃያላን ነበሩ፡፡ ዲዮቅልጥያኖስ ክርስቲያኖችን ማሰቃየት ሲጀምር በመጀመሪያ ያደረጉት ነገር ትጥቃቸውን መፍታትና ስለ ክርስቶስ መክራ ለመቀበል በመዘጋጀት ወደ ፊቱ ቀርበው ሃይማኖታቸውን መመስከር ነበር፡፡ የእነርሱ ታማኝ ሠራዊትና ወዳጆች ከነበሩት ብዙዎች ስለ እነርሱ በመቆጨትና በመቆርቆር ዲዮቅልጥያኖስን ወግተን እናጥፋውና እናንተ ግዙን ሲሏቸው አልተቀበሏቸውም፡፡ እነዚህ ሰማዕታት መጀመሪያ ያደረጉት ነገር በዘመኑ የነበራቸውን አርበኝነት፣ ኃያልነት፣ የወገንና የሠራዊት ድጋፍ ሁሉ ትተው ስለ ክርስቶስ መስክሮ ለመሞት ብቻቸውን መቅረብ ነበር፡፡ ክርስትና በሠይፍ የተመሠረተና ለመስፋፋትም ሠይፍ የሚያስፈል
ገው አይደለምና፡፡ ሠይፍን የሚያነሱማ እነርሱው ራሳቸው በሠይፍ እንደሚጠፉ ባለቤቱ አስቀድሞ ነግሮናል፡፡ ማቴ. 26፡52 ታሪክም ይህንኑ እውነታ ያስተምረናል፡፡

ክርስትና በዚህ ዓለም የድሎትና የቅንጦት ኑሮ የሚመኙበትና የሚኖሩበት ሳይሆን ክርስቶስ በዚህ ዓለም የመስቀል ሞት ስለ እኛ በፈቃዱ እንደ ተቀበለና እንደ ተነሣ ክርስቲያኖችም በዚህ ዓለም የሚደርስባቸውን መከራ በትዕግሥት በጥብዐት በመቀበል በትንሣኤው ኃይል ድል የሚያደርጉበት ነው፡፡ ቅምጥሊቱ ግን በሕይወትዋ ሳለች የሞተች ናት ተብሏልና፡፡ 1 ጢሞ. 5፡6

እነዚህን ወንድሞቻችንን ወደ እግዚአብሔር ፈጥነው እንዲሄዱ አደረጓቸው እንጂ አልጎዷቸውም፡፡ ነፍሳቸውን ከሥጋቸው ለዩዋት እንጂ አልገደሏትም፤ ነፍስን ለመግደል ማንም አይችልምና፡፡ ይህ የሥጋና የነፍስ መለያየት (ሞተ ሥጋ) ደግሞ በሕማምም ሆነ በዕድሜ ብዛት መምጣቱ የማይቀር ነው፡፡ ከዚያ ቀድመው ለክርስቶስ መስክረው ወደ አምላካቸውና መድኃኒታቸው እንዲሄዱ አደረጓቸው እንጂ አንዳችም አልጎዷቸውም፡፡ ራሱ ባለቤቱ ኢየሱስ ክርስቶስ በማይታበል ቃሉ እንዲህ ብሏልና፡- ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል፤ ሕያው የሆነም የሚያምንብኝም ሁሉ ለዘላለም አይሞትም። ዮሐ. 11፡25-26 ለክርስቶስ መስክሮ መሞት ደግሞ ለአንድ ክርስቲያን እጅግ ታላቅ ጸጋና መታደል ነው፤ በሰው ፊት ለሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው በአባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ ተብሏልና፡፡ ማቴ. 10፡32

ቅድስናን (ሰማዕትነትን) እውቅና መስጠትን በተመለከተ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳን የሆኑትን ቅዱሳን ናቸው ስትል ቅድስናቸውን እውቅና የመስጠት ጉዳይ እንጂ ቅዱሳን የማድረግ ጉዳይ አይደለም፡፡ ይህም ማለት እነዚያን ሰዎች ቅዱሳን የሚያደርጋቸው እግዚአብሔር ባሳየው የሕይወት መንገድ መጓዛቸውና እርሱን ደስ ያሰኙ መሆናቸው እንጂ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳን ናቸው ብላ በምትሰጠው ውሳኔ አይደለም ማለት ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ቅድስናቸውን የማወቅ ውሳኔ የሚመጣው ከሰዎቹ ቅድስና እንጂ የሰዎቹ ቅድስና ከቤተ ክርስቲያን ውሳኔ የሚመጣ አይደለም ለማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር የሚያውቃቸው የቤተ ክርስቲያን አካላት የሆኑ ቅዱሳን ሁሉ በዚህ ዓለም ያለው የቤተ ክርስቲያን መዋቅር ሁሉንም ሊያውቃቸው መቸም መች አይችልም፡፡ ምክንያቱም በየበረሓው ወድቀው ከእኩያት ፍትወታትና ከክፉ መናፍስት ጋር ተጋድለው እግዚአብሔርን አገልግለው ያለፉና እንኳን ቅድስናቸው መኖራቸው እንኳ ከእግዚአብሔር በቀር በሰዎች ያልታወቀ ብዙ ቅዱሳን ነበሩና፣ ዛሬም ይኖራሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ወበኀቤዬሰ ፈድፋደ ክቡራን አዕርክቲከ እግዚኦ ወፈድፋደ ጸንዑ እምቀደምቶሙ እኄልቆሙ እምኆጻ ይበዝኁ – አቤቱ ወዳጆችህ በእኔ ዘንድ እጅግ ብዙዎች ናቸው፣ ብቆጥራቸውም ከአሸዋ ይልቅ በዙ የሚለው ለዚህ ነው፡፡ መዝ. 138፡17-18

እንደዚሁም በዚህ ዓለም ሲኖሩ ኃጢአተኞች መስለው፣ እብድ መስለው፣ የውሻ አስከሬን እስከ መጎተትና አመንዝራ እስከ መምሰል ደርሰው፣ ሰው እንኳን ቅድስናቸውን ሊያውቀው ይቅርና ጥሩ ሰዎች እንኳ አድርጐ የማይመለከታቸው ብዙ ቅዱሳን እንደ ነበሩ ዜና አበውና መጽሐፈ ገነት፣ እንዲሁም ስንክሳርና የተለያዩ የቤተ ክርስቲያናችን ድርሳናት ይነግሩናል፡፡ ከሰማዕታት መካከልም ታላላቅ ተጋድሎ የተጋደሉና ብዙ ዓይነት ጸዋትወ መከራ የተቀበሉ፣ ብዙ ጊዜ ሞተው የተነሡና እግዚአብሔር ብዙ ተአምራት ያደረገላቸው ብዙ ሰማዕታት አሉ፡፡ ከእነዚህ መካከል የሚታወቁት ግን በጣም ጥቂቶቹ ብቻ ናቸው፡፡ ሆኖም በሰዎች ዘንድ አለመታወቃቸው በእግዚአብሔር ዘንድ የሚያገኙትን ክብራቸውን በእኛ ዘንድ ከታወቁት ሰማዕታት ያነሰ አያደርገውም፤ የክብራቸው መሠረት በእኛ ዘንድ መታወቅ አለመታወቃቸው፣ በዓል ያላቸውና የሚታሰቡ መሆን አለመሆናቸው አይደለምና፡፡ ይህን በተመለከተ አንድ ሊቅ ሲያስረዳ በሰማይ ባሉ ከዋክብት መስሎ አስረድቷል፡፡ በሰማይ እጅግ በጣም ብዙ የሆኑና ቁጥራቸው ይህን ያህል ተብሎ የማይታወቁ ከዋክብት አሉ፡፡ ለእኛ የሚያበሩልንና መኖራቸውን የምናውቃቸው ካሉት ከዋክብት እጅግ በጣም ጥቂቶቹ ብቻ እንደ ሆኑ ከቅዱሳንም እኛ የምናውቃቸው ለአርአያና ለትምህርት ይሆኑን ዘንድ በጣም ጥቂቶቹን ብቻ ነው፡፡ ሆኖም ከመራቃቸው የተነሣ ለእኛ በጣም ጥቃቅን መስለው የሚታዩንና ከነመኖራቸው የማናውቃቸው ትሪሊዮን ጊዜ ትሪሊዮንና ከዚም በላይ በቁጥር ሊገለጽ የማይቻል የሆኑ ከዋክብት እንዳሉ ሁሉ በቅዱሳንም እንዲሁ ነው፡፡ ለእኛ የሚታዩትና የምናውቃቸውም ሆኑ የማይታዩት የማናውቃቸው ከዋክብት የጋራ መገለጫቸው በሰማይ ያሉ ሰማያውያን መሆናቸው እንደ ሆነ ሁሉ የቅዱሳን የጋራ መገለጫቸው ሁሉም ሰማያውያንና በእግዚአብሔር ዘንድ የከበሩ መሆናቸው ነው፡፡

በእግዚአብሔር ቸርነት የሚገኝ ቅድስና ከሚገኝበት መንገድ አንዱ ሰማዕትነት ነው፡፡ ሰማዕታትም የሰማዕትነት አክሊል የሚቀዳጁት ሰማዕታት ናቸው ተብሎ ሲወሰንላቸው ወይም ዐዋጅ ሲታወጅላቸው ሳይሆን ለአምላካቸው ያላቸውን ጽኑ ፍቅርና ታማኝነት መከራውንና ሞቱን ሳይፈሩ ምስክርነታቸውን በሰጡና ከዚያም የሞትን ጽዋ በጽናት በተቀበሉ ጊዜ ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመዋቅሯ ሰማዕት ብላ እውቅና የምትሰጠው ከእነርሱ ከበረከታቸው ለመሳተፍና ለምስክርነታቸው ዕውቅና ለመስጠትና ለማክበር ነው፡፡ ስለሆነም ይህ ለሰማዕትነታቸው ዕውቅና የመስጠት አለመስጠቱ ጉዳይ እነርሱ በሚያገኙት ጸጋና በሚሆኑት ላይ አንዳችም ለውጥ የማያመጣ ስለሆነ ብዙም የሚያጣድፍ ጉዳይ አለመሆኑንና ረጋ ብሎ አስተውሎ ቢደረግ የሚያመልጥ ነገር አለመኖሩን ተገንዝቦ በተረጋጋ መንፈስ ማድረጉ መልካም ይሆናል፡፡

በአጠቃላይ ከእነዚህ ሰማዕታት የሚከተሉት ነገሮች እንማራለን፡-

1.ክርስትና ከቅዱሳን ሐዋርያት ዘመን አንሥቶ በየዘመናቱ ዓይነቱና ስፋቱ ይለያይ እንጂ ጉዞው በመስቀል ላይ ማለትም በመከራ ላይ መሆኑን፣

2.ክርስትናን ከምድረ ገጽ ለማጥፋትና በዓለም ላይ የአረመኔ ሥርዓት ለመመሥረት አይ ኤስ እና መሰሎቹ የተለያዩ ቡድኖች ክርስቲያኖቹን በመግደልና አብያተ ክርስቲያናትንና ገዳማትን በማቃጠልና በማፍረስ ላይ መሆናቸውን፣

3.ይህ በቤተ ክርስቲያን ላይ እየሆነ ያለው አደጋ ችላ ሊባል የሚገባው ሳይሆን እያንዳንዱ ክርስቲያን በንቃት ሊከታተለው የሚገባ መሆኑንና ሕሊናዊና መንፈሳዊ ዝግጅት፣ እንዲሁም ወደ እግዚአብሔር የሚቀርብ የልብ ጸሎት የሚያስፈልግ መሆኑን፣ እና

4.በመጨረሻም እነዚህ ክርስቲያን ወንድሞቻችን ለክርስቶስ ታምነው ሞትን በጽናት መቀበላቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልጆች ሁላችንም ለኢየሱስ ክርስቶስ ያለንን ጽኑ ፍቅር አጽንተን በመከራም እንኳ ቢሆን ጸንተን እንድንቆም የሚያስተምር ሕያው ወንጌል መሆኑን ነው፡፡ እነርሱ በሠይፍ ለመታረድና በጥይት ተደብድበው እስከሚገደሉ ድረስ ለሃይማኖታቸው ከጸኑ እኛ ከዚያ ደረጃ ባልደረሱ ተራና ጥቃቅን ሰበቦችና ምክንያቶች ኢየሱስ ክርስቶስን እንዳንክድና በእርሱ ካለን ሕይወት እንዳንለይ፣ በክርስቶስ ያለንን እውነተኛ ኦርቶዶክሳዊና ሐዋርያዊ እምነት እስ መጨረሻው አጽንተን እንድንጠብቅ የወንድሞቻችን ደም ሕያው ሆኖ ከፊታችን እየጮኸ ያስተምረናል፡፡

እኛም እንደ ወንድሞቻችን መኑ ያኀድገነ ፍቅሮ ለክርስቶስ ሕማምኑ ምንዳቤኑ ተሰዶኑ ረሐብኑ ዕርቃንኑ መጥባሕትኑ ጻዕርኑ -ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ፣ ወይስ ጭንቀት፣ ወይስ ስደት፣ ወይስ ራብ፣ ወይስ ራቁትነት፣ ወይስ ፍርሃት፥ ወይስ ሰይፍ ነውን? ልንልና በዚህ ሕይወት ልንኖር ይገባናል፡፡ ሮሜ 8፡35

እግዚአብሔር አምላክ ከእርሱ አንድነትና የአባትነት ፍቅር ከሚለይ ነገር ሁሉ ይጠብቀን፣

እኛንም ፈቃዱ ቢሆን እንደ ወንድሞቻችን በጽናት እንድንቆምና ለአክሊለ ሰማዕት እንድንበቃ ያድርሰን፣ አሜን፡፡

dscn6308

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሰማዕታቱን ቤተሰቦችንና ምእመናንን አጽናኑ

ሚያዝያ15 ቀን 2007ዓ .ም.

dscn6308ሚያዝያ ፲፫ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. በደብረ ፍሥሓ መካነ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ አካባቢ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሰማዕታቱን ኢያሱ ይኵኖ አምላክና ባልቻ በለጠ ቤተሰቦችንና ምእመናንን ሊያጽናኑ፤ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፣ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ዘካናዳ፣ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፣ ብፁዕ አቡነ ኖክና ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሄደዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ

ልጆቻችን የምንኮራባቸው መጻሕፍቶቻችን ናቸው፡፡ ልጆቻችን ሰማዕታቶቻችን ናቸው፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የውድ ልጆቻችን የሰማዕታቱ፣ የታማኝ ልጆቻችን፣ የጀግኖች ልጆቻችን፣ በኢትዮጵያዊ ባህላቸው፣ በኢትዮጵያዊ ትውፊታቸው፣ በእምነታቸው፣ በሥርዐታቸው፣ በወጋቸው ጸንተው፣ ለማንም ሳይበገሩ እና ለማንም ሳይደለሉ፣ ለሌላ እጃቸውን ሳይሰጡ፣ ሳይቀለበሱ ጀግንነትን ያስተማሩ ልጆቻችን፣ መጻሕፍት የኆኑ ልጆቻችን ወላጆች እና እዚኅየተሰበሰባችሁ ውድ ወገኖቼ፡-

ከክርስቶስ ልደት በፊት ሰባት መቶ ዓመታት ቀድሞ የነበረው ነቢዩ ኤርያስ፣ በዚያን ጊዜዋ ባቢሎን በዛሬዋ ኢራቅ፤ በዚያን ጊዜዋ ፋርስ በዛሬዋ ኢራን እየዘዋወረ ባስተማረበት ዘመን ስለ ኢትዮጵያውን አድናቆት፣ ክብር፣ ጀግንነት፣ አይበገሬነት በትንቢቱ ምዕራፍ 13 ቁጥር 23 ላይ እንዲኽ ብሏል፡-ኢትዮጵያዊ መልኩን ነብር ዝንጉርጉርነቱን ሊለውጥ ይችላልን?

dscn6309ኢትዮጵያዊ ባህሉን፣ ኢትዮጵያዊ እምነቱን፣ ኢትዮጵያዊ አንድነቱን፣ ኢትዮጵያዊ ጀግንነቱን፣ ኢትዮጵያዊ ትውፊቱን በሌላ ሊቀይር ይችላልን? አይቀየርም፡፡ ነቢዩ ቆቃው ኤያስ በተባለ መጽሐፉም ይህን በስፋት እየገለጸ ይናገራል፡፡

ውድ ወገኖቼ፤ ልጆቻችን እኮ ጀግኖች ናቸው፤ ልጆቻችን እኮ እጃቸውን አልሰጡም፤ ልጆቻችን እኮ አልተንበረከኩም፤ ልጆቻችን እኮ መጻሕፍቶቻችን ናቸው፤ ልጆቻችን እኮ አርበኞቻችን ናቸው፤ አልተማረኩም፤ የጀግና እናት አታለቅስም እንደተባለው ሁሉ፣ እናንተም የጀግኖች እናቶች ናችሁ፤ ልትኮሩ ይገባችኋል፤ ስማቸውን ለውጠው፣ ሃይማኖታቸውን ለውጠው፣ ሥርዐታቸውን ለውጠው፣ ተማርከው ቢሆን ኖሮ ነበር ማልቀስ የሚገባን፡፡

ውድ ወገኖቼ፤ የጀግኖች ወላጆች ናችኹና ልትኮሩ፣ ልትጽናኑ ይገባችኋል፡፡ እሰይ ልጄ፤ ተባረክ ልጄ፤ ለመንግሥተ ሰማያት ያብቃኽ ብላችሁ ልትመርቁ፣ ልትጸልዩ፣ ልትጽናኑ ይገባል፡፡ የመጽናኛ ዕለት ነው፤ ልጆቻችን አስተምረውናል፤ ልጆቻችን አኩርተውናል፤ ልጆቻችን አስከብረውናል፤ አስወድደውናል፤ በዓለም ደረጃ አገራችንን አስተዋውቀዋል፡፡

ውድ ወገኖቼ፤ እንዲኽ ላሉት ነው እንዴ የሚለቀሰው? አገር አጥፍቶ ለሔደ፣ በሙስና ተዘፍቆ ለሔደ፣ ሰክሮ ለሔደ፣ አመንዝሮ ለሔደ፣ ቀምቶ ለሔደ በምድር ኑሮው ተበላሽቶ፣ በሰማይ እንዴት ይኾን ከቶ ተብሎ የሚለቀስለት ለዚኽ ነው፡፡ ብዙ ልጆቻችን በየመልኩ ኸሉም አርበኛ ነው፡፡ አካሉን፣ ሕይወቱን፣ ወላጁን፣ ልጁን፣ ዘመኑን፣ ንብረቱን የሰጠ ስንት አለ? ውድ ወገኖቼ፤ እንዴ፣ እነዚኽማ ልጆቻችን የምንኮራባቸው መጻሕፍቶቻችን ናቸው!! የምንማርባቸው ዩኒቨርስቲዎቻችን ናቸው ልጆቻችን!! ብርሃናችን ናቸው ልጆቻችን!! ማዕተቤን አልበጥስም፤ ወደ ሌላ አንለወጥም፤ አንበገርም አሉ፤ ይኼ ነው ወይ የሚያስለቅሰው? የሚለቀስበትን ነገር እንወቅ እንጂ!

ውድ ወገኖቼ፤ ስለዚህ ልጆቻችንን በሰማዕትነታቸው፣ በጀግንነታቸው ልናከብራቸው፣ ልንማርባቸው፣ ምሳሌአቸውን ልንወስድ፣ ልናወድሳቸው ይገባል፡፡ ስለዚኽ ይኼ የመረጋጋት፣ የሰላም የፍቅር ቦታ ነው፡፡ ልጆቻችን የአገር ፍቅር፣ የአገር ሰላም፣ የአገር አንድነት አስተምረውናል፡፡ በልጆቻችን ተምረናል፤ ጠግበናል፤ ረክተናል፤ ኮርተናል፡፡

የልጆቻችንን ነፍስ በገነት በመንግሥተ ሰማያት ያሳርፍልን፤ ይማርልን፤ ወላጆቻቸውን ይጠብቅልን፤ ከክፉ ነገር ይሰውረን፤ መልካሙን ነገር ያምጣልን፤ ልጆቻችንና ወገኖቻችንን በሰላም ወደ ቤታቸው ይመልስልን፡፡ ሁላችንም ተጽናንተን የሚያኮራ ሥራ እንድንሠራ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡ ነፍሰ ገብሩ ኃይለ ኢየሱስ፣ ኃይለ ሚካኤል ሀገረ ሕይወትን መንግሥተ ሰማያትን ያውርስልን፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን የሐዘን ዳርቻ ያድርግልን፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን የቤተሰቡን ሕይወት፣ የቤተሰቡን ሐዘን በመልካም ነገር፣ በፍቅር ነገር ይለውጥልን፡፡ ቤተሰቡን ያለምልምልን፡፡ ቤተሰቡን ያጽናልን፡፡ ደግ ያልኾኑ ሰዎችን ወደ ደግነት፣ ወደ ምሕረት፣ ወደ ቸርነት ይመልስልን፡፡ ለዓለሙ ኹሉ ሰላም መረጋጋትን ያድልልን፡፡ አገራችን ኢትዮጵያን በክብር በረድኤት ይጠብቅልን፡፡

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ

dscn6312ያለንበት አካባቢ ቤተ መቅደሱ ቂርቆስ ነው፡፡ እንደምታውቁት ቂርቆስ ሕፃን ነው፡፡ በምን መልክ እንደ ዐረፈ ታውቃላችሁ፡፡ ሕፃኑ ቂርቆስ፣ ዓላውያን ነገሥታት በእኛ እምነት እመን፤ እኛ የምናዝዝህን ፈጽም ባሉት ሰዓት አልተቀበላቸውም፡፡ እሳት ነደደ፤ በበርሜል ውስጥ ውኃ ፈላ፡፡ በዚህ ሰዓት እናቱ ደንግጣ ወደ ፈላው ውኃ ለመግባት ስትፈራ ሕፃኑ ቂርቆስ፣ እናቴ ጨክኚ፤ ዛሬ መንግሥተ ሰማያት የምንገባበት ቀን ነው፡፡ አባቶቻችን በሰጡን፣ ባወረሱን፣ ባስተማሩን እምነት ጸንተን ወደ መንግሥተ ሰማያት የምንገባበት ነውና ከዓላዊው ንጉሥ አትፍሪ ብሎ እናቱን ወደ እሳት የጋበዘ ነው፡፡ እስከ መጨረሻው እስከ ዘላለሙ ሰማዕቱ ቂርቆስ ሲባል ይኖራል፤ ታሪክ ሲዘክረው ይኖራል፤ ታሪክ አይደመሰስም፡፡

አሁንም እነዚህ ወንድሞቻችን፣ ወገኖቻችን ሰማዕታት የታሪክ ባለቤቶች ስለኾኑ፣ ታሪክ አትርፈው ስለሔዱ ከእነርሱ በፊት እንደነበሩት ኹሉ ለዘላለም ስማቸው፣ ሥራቸው ሲወሳ ይኖራል፡፡ ሐዘን ሁልጊዜ ሲያነሡት ልብ ይሠቀጥጣል፡፡ ይኼን እያነሡ መናገር በጣም ይከብዳል፡፡ ጭንቅላት ሊሸከመው አይችልም፡፡ እናም እዚህ ያሉትን እያጽናናችኹ፣ እዚያ የቀሩት ደግሞ በሰላም እንዲወጡ ምህላ እያደረግን ልንጸልይ ይገባል፡፡ እኛ እዚኽ ፀሐይ እየሞቅን፣ እየተነጋገርን እናዝለን፤ እዚያ እነርሱ ከወጡበት ሰውነታቸው አልቆ ነፍሳቸው የምትጨነቅ አለችና በሰላም እንዲያወጣቸው ላለፉት ብቻ ሳይኾን ለቀሩትም ጸሎት እያደረጋችኹ በዚኽ እንድትጽናኑ ነው አደራ የምንለው፡፡

ወላጆች ወለዱ እንጂ የሁላችን ልጆች ናቸው፤ ሐዘኑ የኢትዮጵያ ነው፤ እግዚአብሔር ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጽናቱን ይስጥልን፡፡ እዚያ የቀሩትንም በሰላም ያውጣልን፡፡

001 papasat 002

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በሐዘንተኞቹ ቤት ተገኝተው በማጽናናት ላይ ይገኛሉ

ሚያዝያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም.

001 papasat 002በዛሬው ዕለት ከቀኑ ዐሥር ሰዓት ጀምሮ ከስድስት በላይ ሊቃነ ጳጳሳት ሰማእቱ ቅዱስ ቂርቆስ ቤተ ክርስቲያን አካባቢ በሚገኘው በሊቢያ በግፍ በአሰቃቂ ሁኔታ የተገደሉትን ወጣቶች ቤተሰቦችን ለማጽናናት በመኖሪያ ቤታቸው ተገኝተዋል፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳቱ በጥልቅ ሐዘን ላይ ለሚገኙት የሰማእታቱ ቤተሰቦችን፤ ዘመድ ወዳጆቻቸውን እንዲሁም ምእመናንን በቃለ እግዚአብሔር በማጽናናት ላይ ይገኛሉ፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፤ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፤ ብፁዕ አቡነ ማትያስ፤ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፤ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ፤ ብፁዕ አቡነ ሔኖክ ተገኝተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ በሰጡት የወንጌል ትምህርት €œልጆቻችን ብርሃን፤ መጻሕፍቶቻችንና ጀግኖቻችን፤ እንዲሁም የሃማኖትም የሀገርም አርበኞች ናቸው፡፡€ ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በበኩላቸው የሰማእቱ ቅዱስ ቂርቆስንና የእናቱን የቅድስት ኢየሉጣን ታሪክ መነሻ በማድረግ ሰፊ የማጽናኛ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ሚዲያ ክፍል አባላትም በቦታው ተገኝተዋል፡፡

005siklet

ሕማማተ እግዚእነ በልሳነ አበው /የጌታችን መከራ በሊቃውንት አንደበት/

ሚያዝያ 1 ቀን 2007 ዓ.ም.

005sikletየእስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ ቄርሎስ እንዲህ አለ

ታመመ፤ ሞትን ከተቀበለበት ከሥጋ ተዋሕዶ በመስቀል ላይ በፈቃዱ ለሥጋውያን ሞተ፣ ባሕርየ መለኮት ሥጋን ተዋሕዶ በማኅፀን ካደረ ጀምሮ ሥጋ ገንዘቡ እንደመሆኑ በሥጋ ይኸንን ሥርዓት ፈጸመ፡፡

ለማይመረመር ለመለኮቱ ባሕርይ እንደሚገባ ደግሞ እርሱ ኅብስት አበርክቶ ሁሉን ያጠግባል፡፡ አይራብም፣ አይጠማም፣ አይደክምም፣ አያንቀላፋም፣ አይታመምም፣ አይሞትም ሕይወትን ለሁሉ ይሰጣል፡፡ ዳግመኛ በዚያ በሲኦል ተገዝተው ያሉ ነፍሳትን ያድን ዘንድ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወረደ በመለኮቱም ሲኦልን በዘበዘ፡፡

ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ጎርጎርዮስ የወልድን ነገር በተናገረበት ድርሳኑ እንዲህ አለ

እጆቹን፤ እግሮቹን በተቸነከረባቸው ችንካሮች መወጋቱንም እናምናለን፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ እርሱ ደዌያችንን ወሰደ ሕማማችንንም ተሸከመ፤ እኛን ለማዳን ኃጢአታችንንም ለማስተስረይ መከራ ተቀበለ እንዳለ፤ በባሕርዩ ሕማም የሌለበት ሲሆን በሥጋ የታመመ ነው፡፡ በእርሱ ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ ድነናል አለ፡፡ በተገረፈና በተቸነከረም ጊዜ በመከራው ሁሉ መለኮትን ሕማም ተሰማው የሚል ሰው ቢኖር የተለየ የተወገዘ ይሁን፡፡

የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ዲዮናስዮስ ከላከው ሲኖዶሳዊ መልእክት የተገኘ

እርሱ መቼም መች ከመለኮቱ ሳይለይ የሰውነትን ሥራ ሁሉ ገንዘቡ አደረገ፡፡ ይኸውም መራብ፣ መጠማት፣ መንገድ በመሔድ መድከም፣ በመስቀል ላይ መሰቀል፣ በብረት ችንካር መቸንከር ነው፡፡ በሰውነቱ መቸም መች ሰው ነው፣ በአምላክነቱም ሰውን የፈጠረ ነው፡፡ ግን ከማይከፈል ተዋሕዶ በኋላ መከፈል የለበትም፡፡ ሰው እንደ መሆኑ ስለ እኛ የታመመው የሞተው እርሱ ነው፡፡ በመለኮቱ ግን መቸም መች አይታመምም አይሞትም፣ ሕማምንና ሞትንም አይቀበልም፡፡ በሞቱ ሞትን ያጠፋው እርሱ ነው፡፡ ሲኦልንም የበዘበዘው እርሱ ነው፡፡

የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ሐዋርያው ቅዱስ አትናቴዎስ እንዲህ አለ

ነፍሱን ከሥጋው በለየ ጊዜ ያን ጊዜ በሲኦል ፈጥኖ ብርሃን ታየ፡፡ ጌታችን በአካለ ሥጋ ያይደለ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ሔደ፡፡

ሲኦል ተነዋወጠች፣ መሠረቶቿም እፈርስ እፈርስ አሉ፣ ምድርን ያለ ጊዜዋ እንዳታልፍ ክብርት ደሙን በምድር ላይ አፈሰሰ፡፡ ከኅልፈት ጠበቃት በርሷ ያለውንም ሁሉ ጠበቀ፡፡

ስለ ፍጥረት ሁሉ ሥጋውን በመስቀል እንደተሰቀለ ተወው፡፡ ነፍሱ ግን ወደ ሲኦል ወረደች ከዚያ ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን አዳነች፤ ሲኦልንም በዘበዘች፤ ፍጥረትንም ሁሉ ገንዘብ አደረገች፡፡ ሥጋውም በመቃብር ያሉ ሙታንን አስነሣ፤ ነፍሱም በሲኦል ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን ፈታች፡፡

ሃይማኖታቸው የቀና ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ሊቃውንት በአንድ ልብ እንዲህ አሉ

ከብርሃን የተገኘ ብርሃን፣ ከባሕርይ አምላክ የተገኘ የባሕርይ አምላክ፣ የተወለደ እንጂ የተፈጠረ ያይደለ፣ በባሕርዩ ከአባቱ ጋር አንድ የሚሆን፡፡ ሁሉ የተፈጠረበት ያለ እርሱ ግን ምንም ምን የተፈጠረ የሌለ፣ በሰማይ በምድር ያለውም ቢሆን፡፡

እኛን ስለማዳን ከሰማየ ሰማያት ወርዶ በግብረ መንፈስ ቅዱስ ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍጹም ሰው ሆነ፡፡

የሠላሳ ዘመን ጎልማሳ ሆኖ በጶንጦስ ሰው በጲላጦስ የሹመት ዘመን ስለ እኛ ተሰቀለ፣ ስለ እኛም ታመመ ሞተ ተቀበረ፡፡

የቂሣርያ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ባስልዮስ እንዲህ አለ

ምትሐት ያይደለ በእውነት ተራበ፣ ተጠማ እንጂ፡፡ ዳግመኛም ከኃጥአን ከመጸብሐን ጋር በላ ጠጣ፣ ያቀረቡለትንም በላ፡፡ ራሱን አሳልፎ ለመስቀል ሰጠ፣ እጁን እግሩን ተቸነከረ፣ ጎኑን በጦር ተወጋ፣ ከእርሱም ቅዱስ ምስጢር የተገለጠበት ደምና ውኃ ፈሰሰ /ወጣ/፡፡

የኑሲስ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ጎርጎርዮስ እንዲህ አለ

የሚሠዋ በግ እርሱ ነው፣ የሚሠዋ ካህን እርሱ ነው፡፡ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም መሥዋዕት የሚቀበል እርሱ ነው፡፡ በፈቃዱ መከራን በሥጋው የተቀበለ መከራንም ሁሉ የታገሠ እርሱ ነው፡፡ እንደ በግ ሊሠዋ መጣ፣ በግ በሚሸልተው ሰው ፊት እንዳይናገር አልተናገረም፣ በአንደበቱ ሐሰት አልተገኘበትም፡፡

ሰማዕት የሆነ ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ፊልክስ እንዲህ አለ

በሥጋ መወለድ፣ በመስቀል መከራ መቀበል፣ መሞት መነሣት፣ ገንዘቡ የሆነ እርሱ እግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ ስለዚህ በመስቀል ላይ ሳለ ከጥንት ጀምሮ በመቃብር ያሉ ሙታንን ሁሉ አስነሣ፡፡

የሮማ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ አቡሊዲስ እንዲህ አለ

ሙሴም ሞትን ያጠፋ ዘንድ አልቻለም፣ እርሱንም ይዞ ገዛው እንጂ፣ ከእርሱም በኋላ የተነሡ ነቢያትንም ሁሉ ሞት ገዛቸው እንጂ፡፡ ክርስቶስ ግን በቸርነቱ ለሁሉ ሕይወትን ሰጠ፡፡

የሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አዮክንድዮስ እንዲህ አለ

በመስቀል በሥጋ ተሰቅሎ ሳለ ለመለኮት ከሥጋ መለየት የለበትም፡፡ አንዲት ሰዓትም ቢሆን የዐይን ጥቅሻ ያህል ስንኳ ቢሆንም መለኮት ከትስብእት አልተለየም፣ በመቃብር ውስጥ በሰላም መለኮት ከትስብእት አልተለየም፡፡

የኪስኪስ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ኤራ ቅሊስ እንዲህ አለ

ከአብ ጋር አንድ እንደ መሆንህ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ ከእኛ ጋር አንድ እንደመሆንህ በፈቃድህ የሞትክ አንተ ነህ፡፡

በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፣ በኪሩቤል ላይ ያለህ አንተ ነህ፡፡ ከሙታን ጋር በመቃብር የነበርክ አንተ ነህ፣ በአንተ ሕማምና ሞትም ድኅነት ተሰጠ፡፡

ከሙታን ጋር የተቆጠርክ አንተ ነህ፣ ለሙታንም ትንሣኤን የምትሰጥ አንተ ነህ፣ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በመቃብር ያደርክ አንተ ነህ፣ በዘመኑ ሁሉ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የምትኖር አንተ ነህ፡፡

በመለኮት ሕማም ሳይኖርብህ በሥጋ የታመምክ አካላዊ የእግዚአብሔር ቃል አንተ ነህ፡፡

የኢየሩሳሌም ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ አለ

ኃጢአታችንን ለማሥተሰረይ በሥጋ እንዲህ ታመመ፣ እንደሞተ ከነፍሱም በተለየ ጊዜ ሥጋውን እንደ ገነዙ እናምናለን፡፡

የቆጵሮስ ደሴት ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ እንዲህ አለ

ነብይ ዳዊትም ነፍሴን በሲኦል አትተዋትም የባሕርይ ልጅህንም ሙስና መቃብርን ያይ ዘንድ አሳልፈህ አትሰጠውም አለ፡፡ ይህም ጌታ በተዋሐደው አካል ያለውን የነፍስና የሥጋ ተዋሕዶ ያስረዳል፣ የቀና ልቡና ዕውቀት በእርሱ ጸንቶ ይኖር ዘንድ፡፡ ዳዊት እንደተናገረው እውነት ሆነ፣ ነፍስ መለኮትን ተዋሕዳ ወደ ሲኦል ወርዳለችና፣ ሥጋም ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በመቃብር ሳለ መለኮት ከሥጋ አልተለየም፡፡ አምላክ ሰው የመሆኑን እውነት ያስረዳ ዘንድ፣ መለኮት ነፍስን ተዋሕዶ በአካለ ነፍስ የሲኦል ምስጢርን ገልጦ ፈጽሟልና በሲኦልም በቁራኝነት አልተያዘምና፡፡

ምንጭ ስምዐ ተዋሕዶ፤ ሚያዝያ 1-5 ቀን 2007 ዓ.ም.

ሆሳዕና በአርያም

መጋቢት 24 ቀን 2007 ዓ.ም.

በዲ/ን ሚኪያስ አስረስ

ሰውን ከወደቀበት የበደል ጉድጓድ ያወጣው ዘንድ እግዚአብሔር ክንዱን ወደ ዓለም ላከ፡፡ ሰው ሆኖ የተገለጠው የእግዚአብሔር ክንድ በጉድጓድ ተጥሎ የነበረን በዚያም በሥጋ በነፍስ፤ በውስጥ በአፍአ ቆስሎ የነበረ አዳምን በትህትና ሁለተኛ አዳም ሆኖ በሥጋ የቆሰለውን በለበሰው ሥጋ ቆስሎ;በነፍስ የታመመውን በትምህርት አዳነ፡፡ ከእርሱ አስቀድሞ ሰውን ከሞት ወደ ሕይወት፤ ከባርነት ወደ ነፃነት የሚያመጣ ባለመኖሩ እርሱ ሁሉን የፈጠረ ሁሉን የሚያኖር እግዚአብሔር ሰው ሆኖ ለሰው መድኃኒት ሆነ፡፡ በሞቱም መድኃኒትነትን አሣየ፡፡ በነቢይ መድኃኒተ ፈነወ እግዚአብሔር ለሕዝቡ፤ እግዚአብሔር ለሕዝቡ መድኃኒትን ሰደደ፡፡ (መዝ.110፡9) ተብሎ የተነገረው ተፈጸመ፡፡

ክርስቶስ ባለ መድኃኒት ሆኖ በኃጢአት ለታመሙ ደቂቀ አዳም ሁሉ ሕይወትን ይሰጥ ዘንድ ወደዚህኛው ዓለም መጣ፡፡ በምድራዊ ሥርዓት እንደምናየው መድኃኒትና ባለ መድኃኒት እንደሚለያዩ አይደለም፡፡ ሁለቱም እርሱ በመምጣቱ (ሰው በመሆኑ) ፈጸ እንጂ፡፡ መድኃኒት አድርጎ ሥጋውን ደሙን የሰጠ እርሱ ነው፡፡ በካህናት አድሮ ሰው በንስሐ ሲመለስ መድኃኒት ወደሆነው ወደ ራሱ የሚመራ እርሱ ነው፡፡

ክርስቶስ መድኃኒት መሆኑ በሕማሙ እና በሞቱ ነው፡፡ በእመቤታችን ማኅፀን የተጀመረው የእርሱ መድኃኒትነት እና ፍቅሩ ፍፃሜውን ያገኘው በሕማሙ እና በሞቱ ነው፡፡ መሐሪ ንጉሥ እርሱ መሆኑን ይገልጥ ዘንድ በፈቃዱ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ፡፡ ጌታ ወደ ኢየሩሳሌም ከመግባቱ አስቀድሞ ከኢየሩሳሌም 16 ያህል ምዕራፍ በምትርቀው በቤተፋጌ ከደቀመዛሙርቱ ጋር ነበር፡፡

ከደቀ መዛሙርቱም ሁለቱን (ማለትም ጴጥሮስን እና ዮሐንስን) በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሂዱ ወዲያውም ወደ እርሷ ገብታችሁ ከሰው ማንም ገና ያልተቀመጠበትን ውርንጫ ታስሮ ታገኛላችሁ ፈትታችሁ አምጡልኝ፡፡ (ማር 11፡2) በማለት አዘዛቸው፡፡ ዳግመኛም ሰው ወዳልገባባት የተዘጋች የምሥራቅ ደጅ ወደ ምትባል ወደ ድንግል መጥቶ ዘጠኝ ወር ማኅፀኗን ከተማ አድርጎ እንደኖረ፤ ማኅየዊት ከምትሆን ሕማሙ በኋላም ሰው ባልተቀበረበት መቃብር እንደተቀበረ፤ አሁንም ጌታ ወደ ኢየሩሳሌም ለመግባት ማንም ሰው ያልተቀመጠባቸውን በሌላ መንደር የሚገኙ አህያንና ውርንጫን እንዲያመጡ ደቀመዛሙርቱን አዘዘ፡፡

የፍጥረት ሁሉ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በልደቱ እስትንፋሷን የገበረችለትን አህያ አሁን ደግሞ በፈቃዱ ስለ ሰው ሁሉ ሊሞት ሲል ንጉሥነቱን ሊያስመሰክርባት ወደደ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ ካለው 16 ምዕራፍ አሥራ አራቱን በአህያ ላይ ሳይቀመጥ በእግሩ ሄደ፡፡ ከዚያም ሁለቱን ምዕራፍ በአህያ ላይ በመቀመጥ ከተጓዘ በኋላ የኢየሩሳሌምን መቅደስ ሦስት ጊዜ በውርጫዋ ላይ በመሆን ዞረ፡፡ በዚህም ለሰው ሁሉ ያለው ቸርነቱ፣ ሕግ የተሰጣቸው አይሁድ እና ሕግ ያልተሰጣቸው አሕዛብ ላይ እኩል ቀንበርን መጫን እንዳይገባ አጠየቀ፡፡

ወደ ኢየሩሳሌምም ሲሄድ ብዙ ሰዎች ልብሳቸውን በመንገድ ላይ አነጠፉ፣ ሌሎችም ከዛፍ ቅጠሎችን እየቆረጡ ያነጥፉ ነበር፡፡ (ማር. 11፡8)፡፡ ከዚያም ሰዎች ሆሣዕና በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው (ማር. 11፡9) በማለት አመሰገኑ፡፡ ይህም ዛሬ ለቤተ ክርስቲያን እኛ ክርስቲያኖች ቡሩክ ስሙ ለእግዚብሔር ወቡሩክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ስሙ ምስጉን ነው፡፡ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ እርሱ ክርስቶስም ምስጉን ነው በማለት የአብ እና የወልድን መስተካከልን ገልጸን ጌታን እናመሰግናለን፡፡ ጌታን የሚከተሉት ሰዎች ሆሣዕና በአርያም እያሉ ይጮኹ ነበር (ማር.11፡10) ይኸውም በልዕልና፣ በሰማይ ያለ መድኃኒት፣ ከሰማይ የመጣ መድኃኒት ማለት ነው፡፡

የእግዚአብሔር ፍቅር እና መሓሪ መሆን በክርስቶስ ሕማም እና ሞት ከመቼውም ጊዜ በላይ ተገልጧል፡፡ ክርስቶስ የተቀበለው ሕማም እና ሞት የእርሱን አምላክነት እና ንጉሥነት አልሸሸገውም፡፡ እንደውም ዙፋኑን መስቀል በማድረግ ንጉሥነቱን በመድኃኒትነቱ ገልጿል እንጂ፡፡ በነቢይ እግዚአብሔርሰ ንጉሥ ውእቱ እምቅድመ ዓለም ወገብረ መድኃኒተ በማዕከለ ምድር፣ እግዚአብሔር ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፤ በምድር መካከልም መድኃኒትን አደረገ መዝ. 73፤12 ተብሎ የተነገረው እግዚአብር ድኅነትን በፈጸመበት ማዕከለ ምድር ሲሰቀል በመድኀኒትነቱ ንጉሥነቱን መግለጡን ያመለክታል፡፡ ዳግመኛም አንሰ ተሰየምኩ ንጉሠ በላዕሌሆሙ በጽዮን በደብረ መቅደሱ፤ እኔ ንጉሥ ሆኜ ተሸምኩ በተቀደሰው ተራራ ላይ(መዝ.2፡6) ተብሎ የተነገረው ኦርቶዶክሳውያን አበው እነርሱ (አይሁድ) ሰቅለነው ገድለነው ኋላ ፈርሶ በስብሶ ይቀራል ይሉኛል እንጂ እኔ ደብረ መቅደስ በምትባል በመስቀል ላይ ነግሻለሁ በማለት ይተረጉሙታል፡፡

ጌታ ንግሥናው ክብሩ የተገለጠበት ሆነ እንጂ መታመሙ እና መሞቱ ውርደት ክብሩንም የሚሸሽግ አይደለም፡፡ ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ ይትባረክ እግዚአብሔር ዘሰመየ ሕማማት ወልዱ ክብረ ወስብሐት፣ የልጁን ሕማማት ክብርና ምስጋና አድርጎ የሰየመ እግዚአብሔር ይመስገን አለ፡፡ እኛን ያከበረበት በመሆኑ ሕማሙ ክብር እንደተባለ እናስተውል፡፡ በመስቀል ላይ ሆኖም በቀኝ የተሠቀለው ወንበዴ አቤቱ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ (ሉቃ 24 ) በማለት ንጉሥነቱ መስክሮለታል፡፡ ለዚህ ነው ጌታ ወደ ኢየሩሳሌም በምስጋና መግባቱ መድኃኒትነቱን እና ንጉሥነቱን ያሳያል ያልነው፡፡ ዳግመኛም ሁሉን የያዘ ጌታ በአህያ ላይ መቀመጡ ትህትናው ያስረዳል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ዘይነብር ዲበ ኪሩቤል ዲባ ዕዋለ አድግ ነበረ፡፡ በማለት ሰማያዊ ልዑል አምላክ ትሑት ሆኖ እንደተገለጠ ተናገረ፡፡

ጌታ ከመድኃኒትነቱ የተነሣ ድንቅ የሆኑ እና ተአምራትን ለሰዎች አሳየ (ገለጠ)፡፡ እም ሆሳዕናሁ አርአያ ተአምረ ወመንክረ (ቅዳ. ጎርጎ.ዘኑሲስ) እንዲል፡፡ ይኸውም በአህያ ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ አእምሮ ጠባይዕ ያልቀናላቸው ሕፃናት ዕውቀት ተገልጾላቸው ሆሳዕና በአርያም እያሉ ጌታ በማመስገናቸው ነው፡፡ ዳግመኛም በከሃሊነቱ መናገር ለማይችሉ ዕውቀት ለሌላቸው ድንጋዮች ዕውቀት ተሰጥቷቸው መናገር ችለው ጌታን አመስግነዋል፡፡ እርሱ የባሕርይ አምላክ መሆኑ በሰውነቱም ቀድሞ በበደል ምክንያት ለሰው ከመገዛት ውጪ የሆኑ ፍጥረታት ዳግመኛ ሥጋዌ ለሰው እንደተገዙ ከዚህ ሁሉ ማስተዋል ይገባል፡፡

ጌታ ከመድኃኒትነቱ የተነሣ ልጅነት እና ተአምራት ማድረግን ገለጸ፡፡ እም ሆሳዕናሁ አርአያ ጸጋ ወኅይለ እንዲል (ቅዳሴ ጎርጎ. ዘኑሲስ)፡፡ የእርሱ ማዳን ከሰው ተወስዶበት የነበረ የጸጋ ልጅነት እንዲመለስለት አድርጋ በልጅነት ላይ ገቢረ ተአምራት (ተአምራትን ማድረግ) ገልጿል፡፡ ይኸውም እርሱ በረድኤት አድሮባቸው ድንቅ ተአምራትን ሚያደርጉ ቅዱሳን መሠረት ነው፡፡ በተጨማሪም ልጅነትን ካገኙ በኋላ በበደል ሲገኙ ለንስሓ የሚሆን እንባን ሠጠ፡፡ እምሆሳዕናሁ ወሀበ ፈልፈለ አንብዕ ለኅጥአን እንዲል (ቅዳሴ ጎርጎ. ዘኑሲስ) ይኸውም የበደሉትን ያከብራቸው ዘንድ፣ ኀጥአንን ከኃጢአታቸው ያነጻቸው ዘንድ እንዲሁም የሳቱትን በንስሐ ይመልሳቸው ዘንድ ነው፡፡

ዳግመኛም ጌታ መድኀኒት ከመሆኑ የተነሣ ለዕውራን ዳግመኛ ብርሃንን ሰጠ፡፡ ይኸውም ለጊዜው በተፈጥሮ ዐይን ተሰጥቷቸው የታወሩትን ፈውሶ በሥጋ ብርሃን መስጠቱ ሲሆን፤ ፍጻሜው ግን በነፍስ ዕውቀትን ከማጣት የተነሣ ዕውራን የነበሩትን ትምህርትን; ዕውቀትን ገለጸላቸው፡፡ ይኸውም የእርሱ ገንዘቡ ስለሚሆን አንድነት ሦስትነት፣ አምላክነቱን መድኃኒት መሆኑን ገለጠላቸው ማለት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር