aba zewengel 01

የጀበራ ቅድስት ማርያም ገዳምን ዳግም በማቅናት ላይ የነበሩት አባ ዘወንጌል ዐረፉ

ጥር 22 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

aba zewengel 01በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በደምቢያ ወረዳ በጣና ሐይቅ ውስጥ በ1335 ዓ.ም. ተገድማ የነበረችው የጀበራ ማርያም አንድነት ገዳም ከፈረሰች ከበርካታ ዘመናት በኋላ ዳግም ለማቅናት ከፍተኛ ጥረት እያደረጉ የነበሩት አባ ገብረ ኢየሱስ ወልደ ኢየሱስ /አባ ዘወንጌል/ ጥር 20 ቀን 2007 ዓ.ም. በደረሰባቸው ድንገተኛ አደጋ ማረፋቸውን ከገዳሙ የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

 

አባ ዘወንጌል በ1974 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የተፈጥሮ ሳይንስ ፋኩልቲ በፊዚክስ ትምህርት ክፍል የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ሲከታተሉ ቆይተው ሊመረቁ ሁለት ወራት ብቻ ሲቀራቸው ይህንን ዓለም ንቀው በምናኔ ለመኖር በመወሰን ወደ ጀበራ ቅድስት ማርያም አንድነት ገዳም በማምራት ለ10 ዓመታት ቆይተዋል፡፡

 

በ1984 ዓ.ም. ከጀበራ ቅድስት ማርያም አንድነት ገዳም ወደ ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንድነት ገዳም በማምራት ለ20 ዓመታት በአገልግሎት ሲተጉ ቆይተዋል፡፡ በ2005 ዓ.ም. “የአባቶቼ ርስት እንዴት ቆይታ ይሆን?” በማለት አባቶችን ለመጎብኘት ወደ ቦታው ሲያቀኑ ቤተ ክርስቲያኗ ፈርሳ፤ ብዙዎቹ መነኮሳት በሞተ ሥጋ ከዚህ ዓለም በመለየታቸውና ከሞት የተረፉት ደግሞ ተሰደው ሁለት አባቶች ብቻ በእርግና ምክንያት የሚጦራቸው አጥተው በችግር ውስጥ እንዳሉ ይደርሳሉ፡፡

 

በሁኔታው የተደናገጡት አባ ዘወንጌል ከጣና ሐይቅ ማዶ ያሉትን ነዋሪዎች በመቀስቀስ፤ በጎ አድራጊ ምእመናንን በማስተባበር ገዳሟን እንደገና ጥንት ወደነበረችበት ክብሯ ለመመለስ ከፍተኛ ጥረት ማድረጋቸውን ቀጠሉ፡፡ ኮሚቴ በማዋቀር ከበጎ አድራጊ ምእመናን በተገኘ ድጋፍ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኗን ለማስገንባት ሲፋጠኑ ድንገት ለግንባታ የተዘጋጀ ድንጋይ ወድቆባቸው ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተዋል፡፡

 

በ2005 ዓ.ም. የማኅበረ ቅዱሳን የጋዜጠኞች ቡድን በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ለዘገባ በተንቀሳቀሰበት ወቅት በገዳሙ ተገኝቶ ነበር፡፡ አባ ዘወንጌልም በወቅቱ ወደ ጀበራ ቅድስት ማርያም ገዳም ከመጡ ገና 15ኛ ቀናቸው ስለነበር በገዳሟ ውስጥ ቤተ ክርስቲያንም ሆነ ምንም ዓይነት ልማት አልነበረም፡፡

 

ejebera gdamበ14ኛ መቶ ክፍለ ዘመን በዐፄ ዓምደ ጽዮን ዘመነ መንግሥት አባ በረከተ አልፋ በተባሉ አባት ተገድማ እንደ ነበረች የታሪክ ድርሳናት እንደሚያስረዱ የገለጹት አባ ዘወንጌል፤ ገዳሟ በርካታ መናንያንን ስታስተናግድ የኖረች በመሆኗ በገዳማዊ ሕይወታቸውና በትሩፋታቸው ከልዑል እግዚአብሔር በረከትን ያገኙ አባቶችና እናቶች የኖሩባትና ጸሎት ሲያደርሱ የእጆቻቸው ጣቶች እንደ ፋና ያበሩ ስለነበር የአካባበቢው ነዋሪዎች “እጀበራዎች” እያሉ ይጠሯቸው ስለነበር ገዳሟ “ጀበራ” የሚለውን ስያሜ ማግኘቷን አባ ዘወንጌል በወቅቱ ገልጸውልን ነበር፡፡

 

ገዳሟ በድርቡሽ ወረራ ከፍተኛ ጉዳት ከደረሰባቸው የጣና ገዳማት መካከል አንዷ ስትሆን ገዳማውያኑም በመሰደዳቸው እስከ 1956 ዓ.ም. ሙሉ ለሙሉ ፈርሳ ቆይታለች፡፡ በ1956 ዓ.ም መምህር ካሳ ፈንታ በተባሉ አባት ዳግም ተመሥርታ ብትቆይም ከተወሰኑ ዓመታት በኋላ በማረፋቸው ገዳሟን የሚንከባከብ በመጥፋቱ ገዳማውያኑም ወደ ተለያዩ ገዳማት ተበተኑ፡፡ ተሠርታ የነበረችው መቃኞም በምስጥ ተበልታ ፈረሰች፡፡

 

ከ2005 ዓ.ም. ጀምሮ ቤተ ክርስቲኗን የመገንባትና የልማት ሥራዎች በአባ ዘወንጌል አስተባባሪነት እየተሠራ የነበረ ሲሆን፤ በተለይም የቤተ ክርስቲያኗ ግንባታ በመጠናቀቅ ላይ ነበር፡፡

 

በአሁኑ ወቅት ከ15 በላይ መናንያን ተሰባስበውባት በጸሎትና በአገልግሎት በመፋጠን ገዳሟን የማስፋፋት ሥራ እየተሠራ ይገኛል፡፡

 

እግዚአብሔር የአባታችንን ነፍስ ከቅዱሳን አበው ነፍስ ጋር ይደምርልን፡፡

 

የማቴዎስ ወንጌል

ምዕራፍ 13

ጥር 14 ቀን 2007 ዓ.ም.

1. ስለ ዘሪው ምሳሌ
2. ስለ ሰናፍጭ ቅንጣት ምሳሌ
3. ስለ እርሾ ምሳሌ
4. ስለ እንክርዳድ ምሳሌ
5. ስለ ተሰወረው መዝገብ ምሳሌ
6. ስለ ዕንቁ ምሳሌ
7. ስለ መረብ ምሳሌ እና
8. ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አደገባት መንደር ወደ ናዝሬት ስለመሄዱ፡፡

1. የዘሪውም ምሳሌ
በዚህ ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባስተማረው በዘሪው ምሳሌ ውስጥ የምንመለከተው፡- በመንገድ ዳር፣ በጭንጫ መሬት ላይ፣ በእሾህ መካከል እና በመልካም መሬት ላይ ስለወደቁት የዘር ዓይነቶች ነው፡ እዚህ ላይ ዘሪ የተባለው እግዚአብሔር ሲሆን ዘሩ ደግሞ ቃለ እግዚአብሔር ነው፡፡

በመንገድ ዳር የወደቀውን ዘር ወፎች መጥተው በልተውታል፡፡ ይህም ቃሉን ሰምተው ለማያስተውሉ የልበ ዝንግጉዓን ሰዎች ምሳሌ ነው፡፡ ወፎች የተባሉትም አጋንንት ናቸው፡፡ “ወፎች መጥተው በሉት፤” ማለትም አጋንንት መጥተው አሳቷቸው ማለት ነው፡፡ የበሉት ደስ እንዲያሰኝ አጋንነትም በማሳታቸው ደስተኞች ናቸው፡፡ ለማሳት ፈጣኖች በመሆናቸውም በወፍ ተመስለዋል፡፡

በጭንጫ /በድንጋያማ/ መሬት ላይ የወደቀው ዘር ለጊዜው በቅሎ ነበር፡፡ ነገር ግን ፀሐይ በወጣ ጊዜ ጠወለገ፡- ሥርም ስላልነበረው ደረቀ፡፡ ይህም ቃሉን ለጊዜው በደስታ ተቀብለው መከራ እና ስደት በሚመጣ ጊዜ ግን የሚሰናከሉ ሰዎች ምሳሌ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ስፋሐ – አእምሮ ማለትም ጥልቅ ዕውቀት ስለሌላቸው ፈጥነው ሃይማኖታቸውን ይክዳሉ፡፡

በእሾህ መካከል የወደቀው ዘር ደግሞ በቅሎ ፍሬ እንዳያፈራ እሾሁ አንቆ ይዞታል፡፡ ይህም እንደ ቃል እንዳይኖሩ በዚህ ዓለም ሃሣብና ባለጸግነት የሚያዙ እና የሚታለሉ ሰዎች ምሳሌ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ቃሉን ተምረውና አውቀው ሥራ እንሠራለን በሚሉበት ጊዜ በአምስት ነገሮች ይያዛሉ፡፡ እነዚህም፡-

1. ብዕል ሰፋጢት /አታላይ ገንዘብ/
2. ሐልዮ መንበርት /ስለ ቦታ ማሰብ/
3. ትካዘ ዓለም /የዚህ ዓለም ሃሣብ/
4. ፍቅረ ብእሲት /የሴት ፍቅር/
5. ፍቅረ ውሉድ /የልጆች ፍቅር/ ናቸው

በመልካም መሬት ላይ የወደቀው ዘር ግን አንዱም ሠላሳ፣ አንዱም ስድሳ፣ አንዱም መቶ ፍሬ አፈራ፡፡ ይህም ቃሉን ሰምተው ለሚያስተውሉ በተግባርም ለሚገልጡት ሰዎች የተሰጠ ምሳሌ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ቃሉን ሰምተው ሥራውን በሦስት ወገን ይሠሩታል፡፡ በሦስት ወገን የተባለው 1ኛ በወጣኒነት፣ 2ኛ. በማዕከላዊነት፣ 3ኛ. በፈጹምነት ነው፡፡ ክብሩንም በዚያው ይወርሱታል፡፡ በዚህም መሠረት በወጣኒነት ሠላሳ፣ በማዕከላዊነት ስድሳ በፍጹምነት ደግሞ መቶ ፍሬ ያፈራሉ፡፡ ፍሬ የተባለው በሃይማኖት የሚፈጸም ምግባር ነው፡፡

ከሰማዕታት እነ ቅዱስ ጊዮርጊስ እነ ቅዲስ ቂርቆስ፣ ከመነኰሳት እነ አባ እንጦንስ መቃርስን፣ እነ አቡነ ተክለሃይማኖት፣ እነ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ ከሰብአ ዓለም እነ ኢዩብ፣ እነ አብርሃም ባለ መቶ ናቸው፡፡

2. የሰናፍጭ ቅንጣት ምሳሌነት
የሰናፍጭ ዘር ስትዘራ መጠኗ ከዘር ሁሉ ያንሳል፤ በአደገች ጊዜ ግን ከአታክልቶች ትበልጣለች፤ የሰማይም ወፎች መጥተው በቅርንጫፎችዋ እስኪሰፍሩ ድረስ ዛፍ ትሆናለች፡፡ ምሳሌነቷም ለመንግሥተ ሰማያት መሆኑ ተገልጧል፡፡ እዚህ ላይ መንግሥተ ሰማያት የተባለች ወንጌል ናት፡፡ ምክንያቱም በሕገ ወንጌል ጸንቶ የኖረ መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳልና፡፡ በዚህም መሠረት ሰናፍጭ ለወንጌል ምሳሌ የሆነችበት ምክንያት ከዚህ እንደሚከተለው ነው፡፡

– ሰናፍጭ ፍጽምት ናት፣ ነቅ የለባትም፤ ወንጌልም ነቅዓ ኑፋቄ የሌለባት ፍጽምት ናት፡፡
– ሰናፍጭ ላይዋ ቀይ ውስጧ ነጭ ነው፤ ወንጌልም በላይ ደማችሁን አፍስሱ ትላለች በውስጥ ግን ሕገ ተስፋ ናት፡፡ ይህም ተስፋ መንግሥተ ሰማያት ነው፡፡
– ሰናፍጭ ጣዕሟ ምሬቷን ያስረሳል፤ ወንጌልም ተስፋዋ መከራን ያስረሳል፡፡
– ሰናፍጭ ቁስለ ሥጋን ታደርጋለች፣ ወንጌልም ቁስለ ነፍስ ታደርቃለች፡፡
– ሰናፍጭ ደም ትበትናለች፤ ወንጌልም አጋንንትን፣ መናፍቃንን ትበትናለች፡፡
– ሰናፍጭ ከምትደቆስበት ተሐዋስያን አይቀርቡም፤ ወንጌልም በእውነት ከምትነገርበት አጋንንት መናፍቃን አይቀርቡም፡፡
– ሰናፍጭ ስትደቆስም ስትበላም ታስለቅሳለች፤ ወንጌልም ሲማሯትም፣ ሲያስትምሯትም ታሳዝናለች፡፡
– ሰናፍጭ ከበታቿ ያሉትን አታክልት ታመነምናለች፤ ወንጌልም የመናፍቃንን ጉባኤ ታጠፋለች፡፡
– ሰናፍጭ አንድ ጊዜ የዘሯት እንደሆነ ባመት ባመት ዝሩኝ አትልም፤ ተያይዞ ስትበቅል ትኖራለች፡፡ ወንጌልም አንድ ጊዜ ተዘርታ ማለትም በመቶ ሃያው ቤተሰብ ተጀምራ እስከ ምጽአት ድረስ ስትነገር ትኖራለች፡፡
– ሰናፍጭ የሰማይ ወፎች መጥተው በቅርንጫፎችዋ እስኪሰፍሩ ድረስ ዛፍ እንድትሆን፣ ወንጌልም ሕዝብም አሕዛብም ተሰብስበው መጥተው እስኪያምኑባት ድረስ ደግ ሕግ ትሆናለች፡፡

3. የእርሾ ምሳሌነት
መንግሥተ ሰማያት ሁሉ እስኪቦካ ድረስ ሴት ወስዳ በሦስት መስፈሪያ ዱቄት በሸሸገችው ዱቄት ተመስላለች፡፡ ይህም እንደሚከተለው ይተረጐማል፡፡

1ኛ. – እርሾ የጌታ ምሳሌ
– ብእሲት የጥበቡ ምሳሌ
– ሦስቱ መስፈሪያ የሥጋ፣ የነፍስ እና የደመ ነፍስ ምሳሌ ናቸው፡፡
– አዋሕዳ ሸሸገችው የሚለው ደግሞ በተዋሕዶ ሥጋን የባሕርይ አምላክ የማድረጉ ምሳሌ ነው፡፡

2ኛ. – እርሾ የወንጌል ምሳሌ
– ብእሲት የመምህራን ምሳሌ
– ሦስቱ መሥፈሪያ- የሦስቱ ስም የአብ የወልድና የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ናቸው፡፡
– አዋሕዳ ሸሸገችው የሚለው ደግሞ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዲስ የተጠመቁ ሁሉ በጥምቀት የመክበራቸው ምሳሌ ነው፡፡

3ኛ. – እርሾ የጸጋ ምሳሌ
– ብእሲት – የቡርክት ነፍስ ምሳሌ
– ሦስቱ መስፈሪያ ጌታ በመቃብር የቆየባቸው የሦስቱ መዓልትና የሦስቱ ሌሊት ምሳሌ ናቸው፡፡
– አዋሕዳ ሸሸገችው የሚለው ደግሞ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ አንድ ወገን ሆኖ ለመነሣቱ ምሳሌ ነው፡፡

4ኛ. – እርሾ የጌታ ምሳሌ
– ብእሲት የዮሴፍ የኒቆዲሞስ
– ሦስቱ መስፈሪያ ጌታ በመቃብር የቆየባቸው የሦስቱ መዓልትና የሦስቱ ሌሊት ምሳሌ ናቸው፡፡
– አዋሕዳ ሸሸገችው የሚለው ደግሞ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ አንድ ወገን ሆኖ ለመነሣቱ ምሳሌ ነው፡፡

ይቆየን

ምንጭ፡-ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 5ኛ ዓመት ቁጥር 2 ኅዳር 1990 ዓ.ም.

 

 

dscn4600

የከተራ በዓል በጃን ሜዳ

ጥር 10 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

dscn4600የ2007 ዓ.ም. የከተራ በዓል ቅዱስ ፓትርያርኩ፤ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ በኢትዮጵያ የግብጽ አምባሳደር፤ የተለያዩ ሀገራት ዲፕሎማቶች፤ የየአድባራትና ገዳማት ሓላፊዎችና አገልጋዮች፤ የማኅበረ ቅዱሳን መዘምራን፤ የሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን፤ ምእመናንና ክብረ በዓሉን ለመከታተል ከውጭ ሀገር የመጡ ጎብኚዎች በተገኙበት በጃን ሜዳ በድምቀት ተከበረ፡፡

dscn4597ከ11 አድባራትና ገዳማት በክብር የወጡት 13 ታቦታት ከየአጥቢያቸው በሊቃውንቱና በሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን ዝማሬ፤ በምእመናን እልልታና ሽብሸባ ታጅበው ከ6 ኪሎ ወደ ጃን ሜዳ በሚወስደው መስቀለኛ መንገድ ላይ ተገናኝተው በሊቃውንቱ ዝማሬ ቆይታ አድርገዋል፡፡

ከፊት የየአጥቢያ ሰንበት ትምህርት ቤቶችና የማኅበረ ቅዱሳን መዘምራንን በማስቀደም ታቦታቱ በቅዱስ ፓትርያርኩ፤ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤ እንዲሁም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ታጅበው ጃን ሜዳ ደርሰዋል፡፡

dscn4619የእለቱ ተረኛ የቀበና መካነ ሕይወት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትና የሰንበት ትምህርት ቤቱ መዘምራን በዓሉን የተመለከተ ያሬዳዊ ወረብ በየተራ በማቅረብ ቀጥሏል፡፡

በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት መልካም ፈቃድ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ “እነሆ በውኃ መጠመቁን ማን ይከለክለኛል?” የሐዋ. 8፤26 በሚል እለቱን በማስመልከት ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ለፊልጶስ የጠየቀውን ጥያቄ መነሻ በማድረግ ትምህርት ወንጌል ሰጥተዋል፡፡

ቅዱስነታቸው በሰጡት ቃለ ምእዳን “አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ ተጠምቆ የበደል እዳችንን ደምስሶልን ወደ ጥንተ ልጅነታችን የተመለስንበት በመሆኑ ታላቅ በዓል ነው፤ በረከትም የምናገኝበት ነው” ብለዋል፡፡dscn4518

 

በመጨረሻም ታቦታቱ ወደተዘጋጀላቸው ድንኳን በማምራት በትምህርተ ወንጌል፤ በሊቃውንቱ እንዲሁም በማኅበረ ቅዱሳንና በሰንበት ትምህርት ቤቶች መዘምራን ያሬዳዊ ዝማሬ እየቀረበ በዓሉ ቀጥሏል፡፡

 

 

 

 

 

 

 

 

 

dscn4490dscn4544dscn4504dscn4535dscn4520dscn4569

timket 2007

የከተራ በዓል ቅድመ ዝግጅት

ጥር 11 ቀን 2007 ዓ.ም. 

 

በእንዳለ ደምስስ

timket 2007የከተራ በዓልን በማስመልከት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ዓውደ ምሕረትና ግቢ፤ ታቦታት በሚያልፉባቸው ጎዳናዎችና አደባባዮች ማኅበራትና ወጣቶች ተሰባስበው የተለያዩ ኅብረ ቀለማትን በመጠቀም በማስዋብ ላይ ይገኛሉ፡፡

በተዘዋወርንባቸው ቦታዎች ሁሉ ወጣቶቹ በጥድፊያ ላይ ናቸው፡፡

 

በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ግቢውን በማስዋብ ላይ ከሚገኙት ወጣቶች አንዱ ስለ አገልግሎታቸው ላቀረብንለት ጥያቄ ሲመልስ “የጥምቀት ክብረ በዓል ለእኛ ለኢትዮጵያውያን የእምነታችን መገለጫ ከሆኑት ዓበይት በዓላት አንዱ ነው፡፡ በረከት እንድናገኝ፤ ታቦታት በሰላም ከመንበራቸው ወጥተው በሰላም እንዲመለሱ ዓውደ ምሕረት፤ ጎዳናዎችና አደባባዮችን ምንጣፍ በማንጠፍ፤ ምእመናንን በማስተናገድ በዓሉን በድምቀት እንድናከብር በየዓመቱ ተሰባስበን እናገለግላለን” ብሏል፡፡

 

በተዘዋወርንባቸው ቦታዎች የያዝናቸውን ፎቶ ግራፎች እነሆ፡-

timket 07 -03timket 07 -06timket 07- 04

timket 07 -02timket 07- 07

 

timket 01-07

ወተጠሚቆ ሶቤሃ ወጽአ እማይ ጌታችን … ከተጠመቀ በኋላ ከውሃው ወጣ

ጥር 10 ቀን 2007 ዓ.ም.

ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ ሐዲስ 
የአራቱ ጉባኤያት መምህርና የጎንደር መ/መ/መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ

timket 01-07በነቢያት የተነገረው ትንቢት በወንጌል የተጻፈው የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት ከተሥአቱ ከዘጠኙ ታላላቅ በዓላት አንዱ ነው፡፡ጥምቀት ተጠምቀ ተጠመቀ ካለው ግሥ የወጣ ሲሆን ጥምቀት ማለት በውሃ መጠመቅና በወራጅ ወንዝ በሐይቅ ውስጥ በምንጭ የሚፈጸም ነው:: በካህናት እጅ የሚፈጸመው ጥምቀት ከሌላው ጥምቀት ልዩ ነው::

በዘመነ ብሉይ ይፈጸም የነበረው ጥምቀት የንስሓ ጥምቀት ሲሆን በዘመነ ሐዲስ የሚፈጸመው ግን የልጅነት ጥምቀት ነው:: የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት ከሁለቱም ልዩ ነው:: እሱ ሰውን ያከብራል እንጅ ከሰው ክብርን የማይፈልግ የባሕርይ አምላክ ነው:: ለኛ አርአያና አብነት ለመሆን በሰላሳ ዓመቱ በእደ ዮሐንስ በዮሐንስ እጅ በማየ ዮርዳኖስ ተጠምቆ የባሕርይ ልጅነቱንና አምላክነቱነን ከአብና ከመንፈሰ ቅዱስ አስመሥክሮ ዕለቱን ገዳመ ቆሮንቶስ ገብቶ ጾምን ጀምሯል፡፡

 

በሠላሳ ዓመቱ የተጠመቀበት ምሥጢር አዳም የሰላሳ ዓመት፤ ሔዋን የአሥራ አምስት ዓመት ሰው ሁነው ተፈጥረው አዳም በአርባ ቀን ሄዋን በሰማንያ ቀን ከሥላሴ የተቀበሉትን ልጅነት በምክረ ከይሲ ዕፀ በለስን በልተው አስወስደው ነበረና በሰላሳ ዓመቱ ተጠምቆ መልሶላቸዋል፡፡

 

ወየአክል ሠላሳ ክረምቱ ለእግዚእ ኢየሱስ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተጠመቀ ጊዜ ሠላሳ ዓመት ሁኖት ነበር፡፡ ሉቃ ፫-፳፫ በሰላሳ ዓመት የመጠመቁ ምስጢር ይህ ሲሆን እኛ ዛሬ ወንዶች በአርባ ቀን ሴቶች በሰማንያ ቀን በዕለተ ዓርብ ከቀኝ ጎኑ በፈሰሰው ማየ ገቦ ተጠምቀን ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ከማሕጸነ ዮርዳኖስ ሁለተኛ የምንወለድበት ምሥጢር ግን አዳም በአርባ ቀኑ ሄዋን በሰማንያ ቀን ከሥላሴ ልጅነትን አግኝተው ሁለተኛ የተወለዱበትን ምሥጢር የያዘና የጠበቀ ምሥጢረጥምቀትና ሥርዓተ ጥምቀት ነው፡፡ ኩፋ ፬-፱

 

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የፈጸመው ሕግና የሠራው ሥርዓት እንደእንግዳ ደራሽ እንደውሃ ፈሳሽ አይደለም ቅድመ ዓለም በልብ የመከረውን ኋላም በነቢያት ያናገረውን ትንቢትና ምሳሌ ያስቆጠረውን የዘመን ሱባዔ ለአዳም የሰጠውን የመዳን ተስፋ ለመፈጸም ነው እንጅ፡፡ የተነገረውን ትንቢት የተመሰለውን ምሳሌ እንደሚከተለው መጻሕፍት ይነግሩናል፡፡

 

ወአሜሃ መጽአ እግዚእ ኢየሱስ እምገሊላ ውስተ ዮርዳኖስ ከመ ይጠመቅ እምኀበ ዮሐንስ ማቴ ፫-፲፫ ማር፩-፱ ሉቃ ፫-፳፩ ዮሐ ፩-፴፪ ለጌታ ሰላሳ ዓመት ሲመላው ለዮሐንስ መንፈቅ ሲተርፈው ያን ጊዜ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ እጅ ይጠመቅ ዘንድ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ አብ በደመና ሁኖ ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ብሎ ሲመሠክር መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ወርዶ በራሱ ላይ ሲቀመጥ አንዱ አካል ወልድ በዮርዳኖስ ሲጠመቅ የሥላሴ አንድነት ሦስትነት ታወቋል፡፡

 

ያን ጊዜ ጌታ ከገሊላ ወደዮርዳኖስ መጣ አለ፡፡ ምነው አገልጋይ ወደጌታው ይሄዳል እንጅ ጌታ ወደአገልጋዩ ይሄዳልን? አገልጋይ በጌታው እጅ ይጠመቃል እንጅ ጌታ በአገልጋዩ እጅ ይጠመቃልን? ቢሉ ጌታ መምጣቱ ለትሕትና ነው እንጅ ለልዕልና አይደለምና ዳግመኛም ለአብነት ነው ጌታ ዮሐንስን መጥተህ አጥምቀኝ ብሎት ቢሆን ዛሬ ነገሥታት መኳንንት ካህናትን ከቤታችን መጥታችሁ አጥምቁን ባሉ ነበርና፡፡ ካህናት ካሉበት ከቤተ ክርስቲያን ሂዳችሁ ተጠመቁ ለማለት አብነት ለመሆን ነው፡፡

 

ያውስ ቢሆን ጥምቀቱን በዮርዳኖስ ያደረገው ስለምን ነው ቢሉ ትንቢቱን ምሳሌውን ለመፈጸም ትንቢት ባሕርኒ ርእየት ወጐየት ወዮርዳኖስኒ ገብአ ድኅሬሁ ባሕር አይታ ሸሸች ዮርዳኖስም ወደኋላው ተመለሰ ርእዩከ ማያት እግዚኦ ርእዩከ ማያት ወፈርሁ አቤቱ ውሃዎች አንተን አይተው ሸሹ ተብሎ ተነግሯል መዝ ፸፮-፲፮፣ ፻፲፫-፫

 

 ዮርዳኖስ ከላይ ነቁ(ምንጩ) አንድ ነው ዝቅ ብሎ በደሴት ይከፈላል ከታች ወርዶ ይገናኛል ዮርዳኖስ ከላይ (ነቁ)ምንጩ አንድ እንደሆነ የሰውም መገኛው (ምንጩ)አንድ አዳም ነውና ዝቅ ብሎ በደሴት እንዲከፈል እስራኤል በግዝረት አሕዛብ በቍልፈት ተለያይተዋል ከታች በወደብ እንዲገናኝ በክርስቶስ ጥምቀት ሕዝብና አሕዛብ አንድ ሁነዋልና ዳግመኛም አብርሃም ለአምስቱ ነገሥተ ሰዶም ረድቶ አራቱን ነገሥተ ኮሎዶጎሞር ድል ነሥቶ በተመለሰ ጊዜ ደስ ቢለው በመዋዕልየኑ ትፌኑ ቃልከ ወሚመርዕየኒሁ ኪያሃ ዕለተ አው አልቦ አለው፡፡ምሳሌውን ታያለህና ሑር ዕድዎ ለዮርዳኖስ፡፡ ዮርዳኖስን ተሻግረህ ሒድአለው፡፡ ዮርዳኖስን ተሻግሮ ቢሔድ መልከ ጼዲቅ ኅብስተ አኮቴት ጽዋዓ በረከት ይዞ ተቀብሎታልና፡፡ አብርሃም የምእመን ዮርዳኖስ የጥምቀት መልከ ጼዴቅ የካህናት፡፡ ኅብስተ አኰቴት ጽዋዓ በረከት የሥጋው የደሙ ምሳሌ ነውና ያን ለመፈጸም ዘፍ ፲፬-፲፫-፳፬፡፡

 

ዳግመኛም ኢዮብና ንዕማን በዮርዳኖስ ተጠምቀው ከደዌያቸው ድነዋል ኢዮብና ንዕማን የአዳምና የልጆቹ ነገ ካልዕ ፭ ፰-፲፱ ደዌ የመርገመ ሥጋ የመርገመ ነፍስ ዮርዳኖስ የጥምቀት ምሳሌ ነውና ያን ለመፈጸም ነው፡፡ ዳግመኛም እስራኤል ከግብጽ ከወጡ በኋላ በኢያሱ ጊዜ ወደምድረ ርስት ሲሄዱ ከዮርዳኖስ ወንዝ ደረሱ ታቦቱን የተሸከሙና ልብሰ ተክህኖ የለበሱት ሌዋውያን ካህናት በፊት በፊት ሲሄዱ ታቦቱን የሚያጅቡ ሕዝበ እስራኤል ከታቦቱና ከሌዋውያን ካህናት ሁለት ሽህ ክንድ ርቀው ዮርዳኖስ ከላይና ከታች ተከፍሎላቸው በየብስ ተሻግረው ኢየሩሳሌም ገብተዋል ምእመናንም በማየ ገቦ ተጠምቀው ገነት መንግሥተ ሰማያት ለመግባታቸው ምሳሌ ነው፡፡

 

ዛሬም ታቦታቱን ወደጥምቀተ ባሕር በማውረድ በዓለ ጥምቀቱን ለሚያከብሩ ክርስቲያኖች በሙሉ ከታቦታቱ ሁለት ሽህ ክንድ ርቀው መከተል እንዲገባቸው በመጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈ አምላካዊ ትዕዛዝ መሆኑ እንዲህ ተብሎ ተገልጿል “ሕዝቡን የአምላካችሁን የእግዚአብሔርን ቃል ኪዳን ታቦት ሌዋውያን ካህናት ተሸክመውት ባያችሁ ጊዜ ከሰፈራችሁ ተነሥታችሁ ተከተሉት በእናንተና በታቦቱ መካከል ያለው ርቀት በስፍር ሁለት ሽህ ክንድ ይሁን በዚህ መንገድ በፊት አልሄዳችሁበትምና የምትሁዱበትን መንገድ እንድታውቁ ወደታቦቱ አትቅረቡ ብለው አዘዙ” ኢያ፫-፩–፲፯፡፡

 

ዛሬ ሌዋውያን ካህናትና ሊቃውንት በዝማሬ ሕዝበ ክርስቲያኑ በዕልልታና ሆታ ታቦታቱን አጅበው ወደጥምቀተ ባሕር ለሚወርዱ ታቦታት በመጽሐፈ ኢያሱ ምዕራፍ ሦስት ቁጥር ሦስት ላይ የተጻፈው የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ዛሬ ታቦታቱ ወደጥምቀተ ባሕር ወርደው ለማደራቸውና ለበዓለ ጥምቀቱ መነሻ አምላካዊ ሕግና ሥርዓት ሲሆን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ ወደዮርዳኖስ መጥቶ በዮሐንስ እጅ መጠመቁም በዘመነ ወንጌል ክርስቶስ ከተጠመቀበት ሠላሳ ዓመተ ምሕረት ጀምሮ በየዓመቱ ጥር አሥራ አንድ ቀን ለሚከበረው በዓለ ጥምቀት አምላካዊ ታሪካዊ ጥንታዊ ሃይማኖታዊ ክርስቲያናዊ ሕግና ሥርዓት ያለው በዓል ስለሆነ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሲከበር የሚኖርታላቅ በዓል መሆኑን ያስረዳል፡፡

 

ኤልያስም ዮርዳኖስን ተሻግሮ ብሔረ ሕያዋን ገብቷል፡፡ የኤልያስ ደቀ መዝሙር ኤልሳዕም ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በዮርዳኖስ ዳር እንጨት ሲቆርጡ መጥረቢያው ከውሃው ውስጥ ወደቀ ኤልሳዕ የእንጨት ቅርፊት በትዕምርተ መስቀል ከወደቀበት ላይ ቢጥልበት የማይዘግጠው ቅርፊት ዘግጦ የዘገጠውን ብረት አንሳፎ አውጥቶታል እንደዚሁም ሁሉ በባሕርዩ ሕማም ሞት የሌለበት አምላክ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከቅድስት ድንግል ማርም ተወልዶ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በዮርዳኖስ ተጠምቆ በቀራንዮ በቅዱስ መስቀል ተሰቀሎ ከጎኑ ጥሩ ውሃና ትኩስ ደም አፍስሶ በሲኦል የወደቀ አዳምን ለማዳኑ ምሳሌ ነው ነገ ካልዕ ፮-፩–፯፡፡

 

መጠመቁም ለሱ ክብር የሚጨመርለት ሁኖ አይደለም ዮርዳኖስን ብርህት ማሕጸን ለማድረግ እኛ ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ከማሕጸነ ዮርዳኖስ ተወልደን መንግሥተ ሰማያት እንድንገባ ሥርዓተ ጥምቀትን ለማስተማርና አብነት ለመሆን ነው እንጅ ዘኢተወልደ ዳግመ እማይ ወእመንፈስ ቅዱስ ኢይሬእያ ለመንግሥተ እግዚአብሔር ዳግመኛ ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ከማሕጸነ ዮርዳኖስ ያልተወለደ ማለትም ያልተጠመቀ ወደእግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም ዘአምነ ወዘተጠምቀ ይድኅን ወዘሰ ኢአምነ ወኢተጠምቀ ይደየን ያመነ የተጠመቀ ይድናል ያላመነ ያልተጠመቀ ግን ይፈረድበታል እንዲል፡፡ ዮሐ ፫-፫ ማር፲፮-፲፮

 

እኛም ስንጠመቅ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ነው ፡፡ወእንዘ ታጠምቅዎሙ በሉ በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ስታጠምቋቸውም በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቋቸው እንዲል ማቴ ፳፰-፲፱ ኢዮብ ንዕማን ጌታ የተጠመቁበት ዮርዳኖስ ወደቡ አንድ ነው፡፡

 

ትንቢቱን አስቀድሞ በነቢያት አናግሯል ምሳለውንም አስመስሏል ሱባዔውንም አስቆጥሯል በዮርዳኖስ የተጠመቀበት ምስጢሩ ምንድን ነው ቢሉ ዲያብሎስ በአዳምና በሔዋን የጨለማ መጋረጃ ጋርዶ አገዛዝ ስቃይ አጸናባቸው ፡፡ሲጨነቁ አይቶ አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ ሔዋን ዓመቱ ለዲያብሎስ ማለትም አዳም የዲያብሎስ ተገዥ ሔዋንም የዲያብሎስ ተገዥ አገልጋዮች ነን ብላችሁ ስመ ግብርናታችሁን የተገዥነታችሁን ስም ጽፋችሁ ብትሰጡኝ መከራውን አቀልላችሁ ነበር አላቸው ፡፡

 

እነሱም የሚቀልላቸው መስሏቸው ፈቀዱለት እነሱም አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ ሔዋን ዓመቱ ለዲያብሎስ ብሎ በወረቀት ብጽፈው ይጠፋብኛል ሲል በማይጠፋ በሁለት ዕብነ(ሩካም)በረድ ጽፎ አንዱን በዮርዳኖስ አንዱን በሲኦል ጥሎት ይኖር ነበር በዮርዳኖስ የጣለውን ሲጠመቅ እንደ አምላክነቱ አቅልጦ እንደሰውነቱ ተረግጦ አጥፍቶልናል በሲኦል የጣለውንም በዕለተ ዓርብ በአካለ ነፍስ ወርዶ ነፍሳትን ሲያወጣ አጥፍቶልናልእና በዮርዳኖስ የተጠመቀበት ምሥጢር ይህ ነው፡፡

 

ወዮሐንስሰ ዐበዮ እንዘ ይብል አንሰ እፈቅድ እምኃቤከ እጠመቅ ዮሐንስ ግን አገልጋይ በጌታው እጅ ይጠመቃል እንጅ ጌታ በአገልጋዩ እጅ ይጠመቃልን ብሎ አይሆንም አለው ወአንተኑ ትመጽእ ኀቤየ አገልጋይ ወደጌታው ይሄዳል እንጅ ጌታ ወደአገልጋዩ ይሄዳልን አለው እናቱ ኤልሳቤጥ ምንትኑ አነ ከመ ትምጽኢ ኀቤየ እሙ ለእግዚእየ እናቱ ቅድስት ኤልሳቤጥ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከናዝሬት ወደዓይነ ከርም ኤልሳቤጥን ለመጠየቅ በመጣች ጊዜ ኤልሳቤጥ የጌታየ እናቱ እኔ ወደአንች እመጣለሁ እንጅ አንቺ ወደኔ ትመጭ ዘንድ ይገባኛልን ብላ ነበርና ከዚያ አያይዞ ተናገረው ወአውሥአ እግዚእ ኢየሱስ ወይቤሎ ኅድግ ምዕረሰ ጌታም መልሶ አንድ ጊዜስ ተው አለው አንድ ጊዜ ቢጠመቅ ሁለተኛ በፈቃድ ቢጠመቅ በግድ በሰውነቱ ቢጠመቅ በአምላክነቱ መጠመቅ አያሻውምና፡፡

 

እስመ ከመዝ ተድላ ውእቱ ለነ ይህ ለኛ ተድላ ደስታችን ነውና አንተ መጥምቀ መለኮት ተብለህ ክብርህ ይነገራልና እኔም በአገልጋዩ እጅ ተጠመቀ ተብየ ትሕትናየ ሲነገር ይኖራልና ወይደልወነ ከመ ንፈጽም ኵሎ ጽድቀ ትንቢተ ነቢያትንም ልንፈጽምይገባናልና፡፡

 

ዮሐንስ እንዲያጠምቅ ጌታ እንዲጠመቅ ትንቢት ተነግሯልና ዳግመኛም ይህ ለምእመናን ተድላ ነውና እናንተም ብትጠመቁ መንፈስ ቅዱስ ይወርድላችኋል ለማለት ዳግመኛም ይህ ለባሕርይ አባቴ ለአብ ለባሕርይ ልጁ ለኔ ለባሕርይ ሕይወቴ ለመንፈስ ቅዱስ ተድላ ለነ ተድላ ደስታችን ነውና አብ በደመና ሁኖ ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ብሎ ሲመሠክር መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ወርዶ በራሱ ላይ ሲቀመጥ የሥላሴ አንድነት ሦስትነት ይገለጣልና የጀመርነውንም የቸርነት ሥራ ልንፈጽም ይገባናልና ወእምዝ ኀደጎ ከዚህ በኋላ ተወው፡፡

 

ስመ አብ ብከ ወስመ ወልድ ለሊከ ወስመ መንፈስ ቅዱስ ህልው ውስቴትከ ባዕደ አጠምቅ በስምከ ወበስመ መኑ አጠምቅ ኪያከ አብ በአንተ በመንፈስ ቅዱስ ህልው ነው፡፡ አንተም በአብ በመንፈስ ቅዱስ ህልው ነህ፡፡ መንፈስ ቅዱስም በአንተና በአብ ህልው ነው፡፡ ሌላውን በአንተ ስም አጠምቃለው አንተን በማን ስም ላጥምቅህ ቢለው ወልዱ ለቡሩክ ከሣቴ ብርሃን ተሣሃለነ አንተ ካህኑ ለዓለም በከመ ሢመቱ ለመልከ ጼዴቅ ብለህ አጥምቀኝ አለው ከዚህ በኋላ ተያይዘው ወደባሕር ወርደዋል፡፡

 

ወተጠሚቆ እግዚእ ኢየሱስ ሶቤሃ ወጽአ እማይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ ከውሃው ወጣ ጥምቀቱን በውሃ ያደረገው በሌላ ያላደረገው ስለምንድን ነው ቢሉ ትንቢቱ ምሳሌው ሊፈጸም ትንቢት ወእነዝሐክሙ በማይ ወትነጽሑ ተብሎ ተነግሯል ምሳሌ ውሃ ለሁሉ አስፈላጊ ነው፡፡ ያለውሃ መኖር የሚችል የለም፡፡ ጥምቀትም ለሁሉ የሚገባ ነው ያለጥምቀት ወደእግዚአብሔር መንግሥት መግባት አይቻልምና ውሃ መልክ ያሳያል መልክ ያለመልማል ጥምቀትም መልክዐ ነፍስ ያሳያል መልክዐ ነፍስ ያለመልማልና፡፡

 

ወናሁ ተርኅወ ሎቱ ሰማይ ሰማይ ተከፈተለት አሁን በሰማይ መከፈት መዘጋት ኑሮበት አይደለም የተዘጋ በር በተከፈተ ጊዜ በውስጡ ያለው እቃ እንዲታይ ከዚህ በፊት ያልተገለጸ ምሥጢር ተገለጸ ሲል ነው ይኸውም የሥላሴ አንድነት ሦስትነት ነው፡፡

 

ወርእየ መንፈሰ እግዚአብሔር እንዘ ይወርድ ከመ ርግብ ወነበረ ላዕሌሁ መንፈስ ቅዱስ በአምሳለ ርግብ ወርዶ በራሱ ላይ ሲቀመጥበት አየ፡፡ መንፈስ ቅዱስን ርግብ አለው፡፡ ርግብ ኃዳጊተ በቀል ናት፡፡ መንፈስ ቅዱስም ኃዳጌ በቀል ነውና፡፡ ርግብ በኖኅ ጊዜ ሐጸማየ አይኅ ነትገ ማየ አይኅ ስትል ቆጽለ ዕፀ ዘይት ይዛ ተገኝታለች፡፡ መንፈስ ቅዱስም ተስፋ መስቀልን ያበሥራልና ፡፡ ጥምቀቱን በቀን ያላደረገው በሌሊት ያደረገው ስለምን ነው ቢሉ በቀን አድርጎት ቢሆን መንፈስ ቅዱስ በቁሙ ርግብ ነው፡፡ በተባለ ነበርና አሁንስ ርግብ አለመሆኑ መንፈስ ቅዱስ መሆኑ በምን ይታወቃል ቢሉ ጌታ የተጠመቀ ከሌሊቱ በአሥረኛው ሰዓት ነው፡፡ በዚያን ጊዜ ተሐዋስያን ወፎች ርግቦች ከየቦታቸው አይወጡምና ርግብ አለመሆኑ መንፈስ ቅዱስ መሆኑ በዚህ ይታወቃል፡፡

 

መንፈስ ቅዱስም መውረዱ ከውሃው ከወጣ ከዮሐንስ ከተለየ በኋላ ነው ከውሃው ሳለ ወርዶ ቢሆን ለቀድሶተ ማያት የወረደ ነው ባሉት ነበርና ከዮሐንስ ጋርም ሳለ ወርዶ ቢሆን ለክብረ ዮሐንስ የወረደ ነው ባሉት ነበርና ረቦ ወርዷል ያሉ እንደሆነ አብ ምሉዕ ነው አንተም ምሉዕ ነህ እኔም ምሉዕ ነኝ ሲል፡፡ አሰይፎ ወርዷል ያሉ እንደሆነ የብሉየ መዋዕል የአብ ሕይወት ነኝ የአንተም ሕይወት ነኝ እኔም ብሉየ መዋዕል ነኝ ሲል ወርዶ ራሱን ቆንጠጥ አድርጎ ይዞታል ቢሉ አብ አኃዜ ዓለም ነው፡፡ አንተም አኃዜ ዓለም ነህ እኔም አኃዜ ዓለም ነኝ ሲል ምሥጢሩ ግን እናንተም ብትጠመቁ መንፈስ ቅዱስ ይወርድላችኋል ለማለት አብነትለመሆን ነው፡፡

 

ወናሁ መጽአ ቃል እምሰማይ ዘይብል ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ዘቦቱ ሠመርኩ ለተዋሕዶ የመረጥኩት በሱ ህልው ሁኜ ልገለጥበት የወደድኩት የባሕርይ ልጄ ይህ ነው የሚል ቃል ከወደሰማይ ተሰማ፡፡ይህም አብ የተናገረበት ቃል ያው የሚጠመቀው አካላዊ ቃል ነው እንጅ ሌላ ቃል አይደለም የሥላሴ ልብ ቃል እስትንፋስ አንድ ነውና አብ ልብ ወልድ ቃል መንፈስ ቅዱስ እስትንፋስ በመሆን አንድ አምላክ ነውና አብኒ ልቡናሆሙ ለወልድ ወለመንፈስ ቅዱስ ወልድኒ ቃሎሙ ለአብ ወለመንፈስ ቅዱስ ወመንፈስ ቅዱስኒ እስትንፋሶሙ ለአብ፡ወለወልድ አብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ልቡናቸው ነው ወልድም ለአብ ለመንፈስ ቅዱስ ቃላቸው ነው መንፈስ ቅዱስም ለአብ ለወልድ ሕይወታቸው ነው ሲል ጎርጎርዮስ ነባቤ መለኮት እንደተናገረው ነው፡፡

ከበዓለ ጥምቀቱ ረድኤት በረከት ይክፈለን

 

የታክሲ ሾፌሮች፤ ረዳቶችና ተራ አስከባሪዎች ጉባኤ 8ኛ ዓመት ተከበረ

ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም.

በደመላሽ ኃይለ ማርያም

የብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ፍሬ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት ለታክሲ ሹፌሮች፣ ተራ አስከባሪዎችና ረዳቶቻቸው አገልግሎት እንዲሰጥ የመሠረተውን ጉባኤ 8ኛ ዓመት አስመልክቶ ታኅሣሥ 25 እና 26 ቀን 2007 ዓ.ም. “ለፍቅርና ለመልካም ሥራ እንድንነቃቃ እርስ በርሳችን እንተያይ” በሚል የመጽሐፍ ቅዱስ መሪ ቃል በቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ግቢ አባላቱና በርካታ ምዕመናን በተገኙበት ተከበረ፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የደብሩ አስተዳዳሪ እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙ ሲሆን፤ የታክሲ አገልግሎት ሥራን በሚመለከት ከቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ጋር አያይዘው “ኖላዊ” በሚል ርዕስ በተጋባዥ መምህራን ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

የታክሲ ሹፌሮች፣ ረዳቶቻቸው እና ተራ አስከባሪዎች ከማኅበረሰቡ ጋር ያላቸውን በጎ ያልሆነ ግንኙነት ለማሻሻል እና በክርስትና ሕይወታቸው ምሳሌ የሚሆኑ ዜጎችን ማፍራት እንዲቻል፤ እንዲሁም በእነሱ ቸልተኝነት እና ጥድፊያ በመኪና አደጋ እየጠፋ ያለውን የሰውን ሕይወት ለመቀነስ ታስቦ ጉባኤው መመስረቱን የሰንበት ትምህርት ቤቱ ሰብሳቢ ዲያቆን ያሬድ ያስረዳል፡፡

ዲያቆን ያሬድ አክሎም “የአባላቱን ቁጥር ከዚህ የበለጠ በማሳደግና በጉባኤው ውስጥ በማካተት ትምህርተ ሃይማኖት እንዲማሩ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱን ዶግማ፤ ቀኖና እና ትውፊት እንዲያውቁ፤ በሥነ ምግባር የታነጹና ሥርዓት አክባሪዎች ሆነው ከማኅበረሰቡ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ጤናማ ለማድረግ ከፈጣሪ ጋር እንጥራለን” ብሏል፡፡

ከተጋባዥ እንግዶች መካከልም የአዲስ አበባ ትራፊክ ፖሊስ ጽ/ቤት የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊ ም/ኢንስፔክተር አሰፋ መዝገቡ ድንገተኛ፤ ለንስሐ እና ለኑዛዜ የማያበቃውን በትራፊክ አደጋ የሚደርሰውን ሞት ለመከላከል ምእመናን እና የታክሲ ሹፌሮች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በመጪው ዓመት ሃምሳኛ ዓመቱን የሚያከብረው ይህ የፍሬ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት እየሠራ ያለው ሥራ እጅግ በጣም ሊበረታታ የሚገባውና በሌሎችም ሰንበት ትምህርት ቤቶች ሊለመድና ሊሰራበት እንደሚገባ ጉባኤውን የተከታተሉ ምእመናን አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

lidet 01

ቅዱስ ፓትርያርኩ የልደት በዓልን አስመልከቶ የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላለፉ

ታኅሣሥ 27 ቀን 2007 ዓ.ም.

lidet 01ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የ2007 ዓ.ም. የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓልን አስመልክቶ ለመላው ሕዝበ ክርስቲያን ታኅሣሥ 27 ቀን 2007 ዓ.ም. የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላለፉ፡፡

ቅዱስነታቸው ያስተላለፉትን መልእክት ሙሉ ቃል ከዚህ በታች አቅርበነዋል፡፡

ቃለ በረከት ዘእምኅበ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዘተናገረ በእንተ በዓለ ልደት ዓቢይ ዘእግዚእነ ወአምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ሎቱ ስብሐት፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!

– በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
– ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤
– የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
– በሕመም ምክንያት በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤
– እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያውያት፤
የዘለዓለም አባት፤ የሰላም አለቃ፤ ስሙም ድንቅ መካርና ኃያል አምላክ የሆነው ጌታችን፤ አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለ2007 ዓ.ም. በዓለ ልደቱ በሰላም አደረሳችሁ!!

“ውውእቱ ቃል ሥጋ ኮነ ወኃደረ ላዕሌነ፤ ያ ቃል ሥጋ ሆነ፤ በእኛ ላይም አደረ” (ዮሐ.1፣14)

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

የጌታችን፤ የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን በዓል ልደት ስናከብር ከሁሉ በፊት የእርሱን ማንነት በማውሳት፤ በመረዳትና የእምነት ግብረ መልስን በመስጠት ልናከብር እንደሚገባ መገንዘቡ ተገቢ ነው፤
ከዚህ አኳያ ለመሆኑ የተወለደው ማን ነው? ለምንስ ተወለደ? በልደቱ ዕለት ለዓለም የተላለፈው አጠቃላይ መልእክትስ ምንድነው? የሚለውን ማየት በእጅጉ አስፈላጊ ነው፣

ቅዱሳት መጻሕፍት በግልጽ እንደሚያስተምሩን ከሦስት አካላተ እግዚአብሔር አንዱ የሆነው እግዚአብሔር ወልድ የአብና የመንፈስ ቅዱስ ቃል ስለሆነ በተለየ ኩነቱ ቃል፣ ቃለ አብ፤ ቃለ እግዚአብሔር፣ አካላዊ ቃል ተብሎ ይጠራል፤(መዝ.32፣6፤ ዮሐ.1፣1-2፤ ራእ.19፣13) ቃል ከልብ እንደሚገኝ አካላዊ ቃልም ከአብ የተገኘ ነው፤ ይሁንና ቃል ከልብ በመገኘቱ ደኃራዊ አይባልም፤ ልብም ቃልን በማስገኘቱ ይቀድማል አይባልም፡፡ በህልውናም በተመሳሳይም አካላዊ ቃል ከአብ በመገኘቱ ደኃራዊ አይባልም፣ የአካላዊ ቃል አስገኝ በመሆኑ ከወልድ ይቀድማል አይባልም፡፡ በህልውናው (በአኗኗር) ከቃል የተለየ ወይም የቀደመ ልብ እንደማይኖር ሁሉ፣ ከአካላዊ ቃል የተለየ ወይም የቀደመ የአብ ህልውና (አኗኗር) የለም፤ ቃል የሚለው ስም እኩል የሆኑ የሦስቱ አካላተ እግዚአብሔር ቅድምና እና ህልውና በምሥጢር ያገናዘበና በትክክል የሚገልጽ በመሆኑ ወንጌላዊው ዮሐንስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በመለኮታዊና በቀዳማዊ ስሙ ቃል ብሎታል፤

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ “በመጀመሪያው ቃል ነበረ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፤ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ፤ ይህ በመጀመሪያው በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፤ ሁሉ በእርሱ ሆነ፣ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም” በማለት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እግዚአብሔርነት በያማሻያማ መልኩ ያረጋግጣል፤ (ዮሐ.1፣1-3)፡፡ እግዚአብሔር አብ አካላዊ በሆነ ቃሉ በእግዚአብሔር ወልድ ፍጥረታትን ሁሉ እንደፈጠረ፣ አካላዊ በሆነ እስትንፋሱ በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስም ለሕያዋን ፍጥረታት ሁሉ ሕይወትን እንደሰጠ በቅዱስ መጽሐፍ በብዙ ቦታ በግልጽ ተቀምጦአል፤ (ዘፍ.1፣1-3፤ መዝ.32፣6፤ዘፍ.2፣7፤ ሮሜ 8፣11)፡፡
በመሆኑም ከጊዜ በኋላ ሥጋችንን በመዋሐድ ሰው ሆኖ ተወለደ እየተባለ ያለው ፍጥረታትን በሙሉ የፈጠረ፣ ከተፈጠረው ፍጥረት አንዳች ስንኳ ያለእርሱ የተፈጠረ ምንም እንደሌለ የተነገረለት አካላዊ ቃል ማለትም ቃለ እግዚአብሔር ወልድ ነው፤

አካላዊ ቃል ከዘመን መቆጠር በፊት በመለኮታዊ ርቀትና ምልአት ከፍጡራን አእምሮ በላይ በሆነ ዕሪና፣ ዋሕድና፣ ቅድምና፣ ኩነትና ህልውና እንደ አብና እንደ መንፈስ ቅዱስ የነበረ ሲሆን፤ በሞቱ የእኛን ዕዳ ኃጢአት ተቀብሎ ከሞተ ኃጢአት ሊያድነን በአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዓመተ ዓለም መጋቢት 29 ቀን መዋች የሆነው ሥጋችንን በማኅፀነ ማርያም ተዋሕዶ ሥጋ ሆነ፤ (ዮሐ.1፣14)፡፡

ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ሲሆነው ታሕሣሥ 29 ቀን እንደ ትንቢቱ ቃል በዳዊት ከተማ በቤተልሔም ተወለደ፤ የምሥራቹም “ዛሬ መድኅን ክርስቶስ ተወልዶላችኋል” ተብሎ በመላእክት አንደበት ተበሠረ፤ (ሉቃ.2፣10-12፤ ማቴ.2፣1-11)፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋን ተዋሕዶ በተወለደ ጊዜ በቃል ርስትነት ሰው እግዚአብሔር ሆነ፤ በሥጋ ርስትነት አካላዊ ቃል ሰው ሆነ፤ ዕፁብ ድንቅ የሆነ ይህንን ተዋሕዶ የተመለከቱ የሰማይ ሠራዊትም አካለ ሰብእን በተዋሕዶተ ቃል ለአምላካዊ ክብር ላበቃ ለእርሱ “ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን፤ ሰላምም በምድር ይሁን፤ በጎ ፈቃዱም ለሰው ይሁን” ብለው በደስታ ዘመሩ (ሉቃ.2፣13-15)

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

እግዚአብሔር አምላክ ለሰው ልጅ ያደረገው በጎ ፈቃድ፣ በሰማይም ሆነ በምድር ላሉ ፍጥረታት ለማንም ያልተደረገ ነው፤ (ዕብ.1፣1-14)፡፡
ምንም እንኳ ፍጥረታትን ሁሉ በቸርነቱ የሚመግብና የሚጠብቅ እርሱ ብቻ መሆኑ ቢታወቅም፣ አካሉን አካል አድርጎ በተዋሕዶ ወደ አምላክነት ደረጃ ከፍ ያደረገው፣ በመንበረ መለኮት ያስቀመጠውና የሰማይና የምድር ገዢ ያደረገው ግን ከሰው በቀር ከፍጡር ወገን ሌላ ማንም የለም፤ (መዝ.8፣4-6፤ዕብ 2፣16፤ ኢሳ.9፣6-7)፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከሌሎች አብያተ ክርስቲያናት በተለየ ሁኔታ በስሟ ላይ “ተዋሕዶ” የሚለውን ቃል መጠቀሟ የድኅነታችን መሠረት፤ የቃልና ሥጋ ተዋሕዶ መሆኑን ለማሳየት ነው፤
ምክንያቱም ቃል ሥጋን ካልተዋሐደ አይሞትምና፤ ቃል በሥጋ ካልሞተ ደግሞ እኛ ከሞትና ከኃጢአት ዕዳ ነጻ መሆን አንችልምና ነው፤

የአምላክ ሰው ሆኖ መወለድ ለሰው ልጅ ያስገኘለት ክብር እስከዚህ ድረስ መሆኑን መገንዘብና ማወቅ ለሰው ልጅ በጣም አስፈላጊ ነው፤
ክርስቶስ የተዋሐደው ሥጋችን ዛሬ በመለኮት ዙፋን ተቀምጦ ዓለምን ማለትም ሰማያውያኑንና ምድራውያኑን በአጠቃላይ እየገዛ ይገኛል፤ (ዕብ. 2፣5-8)፡፡
ይህ ታላቅና ግሩም ምሥጢር የተከናወነው በሰው ብልሃትና ጥበብ ሳይሆን በእግዚአብሔር ፍቅር ብቻ የተፈጸመ አስደናቂ ጸጋ ነው፤
በዚህ ፍጹም የተዋሕዶ ፍቅር ሰማያውያኑና ምድራውያኑ እውነተኛውን ሰላም ማለትም በጌታችን ልደት የአምላክና የሰው ውሕደት እውን ሆኖ ስላዩ “ሰላም በምድር ሆነ” አሉ፡፡ ሰማያውያኑ ፍጡራን ዛሬም ያለ ማቋረጥ ሰው ለሆነ አምላክ ይህንን የሰላም መዝሙር ይዘምራሉ፤ እኛ ምድራውያኑም የዘወትር መዝሙራችን “ሰላም በምድር ይሁን” የሚለው ሊሆን ይገባል፡፡

ምክንያቱም በሰላም ውስጥ ሃይማኖትን መስበክና ማስፋፋት አለ፤ በሰላም ውስጥ ልማት፣ ዕድገትና ብልፅግና አለ፤ በሰላም ውስጥ መቻቻል፣ መከባበርና መተማመን አለ፤ ሰላም ውስጥ መደማመጥና መግባባት አለ፡፡
ስለሆነም በልደተ ክርስቶስ ከተዘመረው መዝሙር የሰማነው ዓቢይ መልእክት “ሰላም በምድር ይሁን” የሚለው ነውና ከሁሉ በላይ ለእርስ በርስ መፋቀርና ለሰላም መጠበቅ ቅድሚያ መስጠት የዘወትር ግዳጃችን ሊሆን ይገባል፤

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልደቱን ያደረገው በትሑታኑ መኖሪያ ማለትም በእንስሳቱ በረትና በእረኞቹ ሠፈር እንደነበር ልናስታውስ ይገባል (ማቴ. 10፣29-31)
ስለሆነም የእርሱ ደቀመ መዛሙርት የሆን እኛም ከልደቱ መልእክት ትምህርትን ወስደን በዚህ ቀን በጤና፣ በዕውቀት፣ በሀብትና በልዩ ልዩ ምክንያት አካላዊ፣ ሥነ ልቡናዊ መንፈሳዊ ድኽነት ከተጫናቸው ወገኖች ጋር አብረን በመዋል፣ አብረን በመመገብና እነርሱን ዘመድ በማድረግ በዓሉን ልናከብር ይገባል፤ (ማቴ.25፣40)፡፡

በመጨረሻም፤

ልደተ ክርስቶስ መለያየትንና ጥላቻን ያስወገደ፤ በምትኩ እግዚአብሔርንና ሰውን በማዋሐድ ለሰው ልጅ አዲስ የድኅነት ምዕራፍን የከፈተ እንደሆነ ሁሉ፣ እኛ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያትም ድህነትን በአጠቃላይ ለመቀነስ የጀመርነው አዲስ የልማትና የዕድገት መርሐ ግብር ከግብ ለማድረስ አሁንም ሌት ተቀን ጠንክረን በመሥራት ሀገራችንን በልማት እንድናሳድግ አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክ፤ይቀድስ፡፡ አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክኩስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ታኅሣሥ 29 ቀን 2007 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

 

 

1ዐ.4 ቦ / አለ/ በመራሕያን ሲረባ/ Verb to have/

ግእዝን ይማሩ 

ታኅሣሥ 24 ቀን 2007 ዓ.

1ዐ.4 ቦ / አለ/ በመራሕያን ሲረባ/ Verb to have/

ብየ= አለኝ  ምሳሌ  ምንት ብየ ምስሌኪ    ካንቺ ጋር ምን አለኝ

ብከ= አለህ         ምንት ብከ ምስሌሃ   ከርሷ ጋር ምን አለህ

ብኪ = አለሽ       ምንት ብኪ ምስሌሃ   ከርሷ ጋር ምን አለሽ

ብነ = አለን        ምንት ብነ ምስሌክሙ  ከእናንተ ጋር ምን አለን

ብክሙ=አላችሁ     ምንት ብክሙ ምስሌሆሙ  ከእነርሱ/ ከወንዶች/

                                         ጋር ምን አላችሁ

ብክን= አላችሁ / ለሴት/  ምንት ብክን ምስሌየ  ከእኔ ጋር ምን አላቸው

ቦሙ= አላቸው         ምንት ቦሙ ምስሌየ   ከእኔ ጋር ምን አላቸው

ቦን = አላቸው / ለሴት/  ምንት ቦን ምስሌኪ  ከአንቺ ጋር ምን አላቸው

ከላይ ለጠቀስናቸው አፍራሻቸው አል ነው፡፡

 

 ለምሳሌ:-

አልብየ   =  የለኝም

አልብከ   =  የለህም

አልብኪ   =  የለሽም

አልብነ    =  የለንም

አልቦ     =  የለንም፣ የሉም፣ የለም

ቦ        =  አለ ፣አለው

ዘቦ       =  ያለው

 

1ዐ.5 ባለቤት ተውላጠ ስም (Subjective Pronoun)

እግዚአብሔር ለሊሁ ፈጠረ ዓለመ / እግዚአብሔር እርሱ ራሱ ዓለምን ፈጠረ/

ለሊሁ የአምር

ለሊከ እግዚኦ ተአምር እበድየ

ለሊከ እግዚኦ ተአምር ጽእለትየ

ለሊከሰ ሕይወተ ታሐዩ

ለሊኪ አውሰብኪ

ለሊሃ ትበልዕ ኩሎ ዘትረክብ

ትአምሩ ለሊክሙ ኩሎ ነገረ ዘኮነ በይሁዳ

ለሊሁሰ እግዚእ ኢየሱስ ኢያጥመቀ ዳእሙ አርዳኢሁ/ ዳእሙ — እንጂ/

 

       ነጠላ                                ብዙ

ለሊሁ   =  እርሱ እራሱ / Himself/  ለሊሆሙ = እነርሱ እራሳቸው

                                                                (Themselves)

ለሊሃ   =  እርሷ እራሷ (Herself)   ለሊሆን  = እነርሱ / ለሴቶች/

                                               (Themselves)

ለሊከ   =  አንተ እራስህ (Yourself)   ለሊክሙ = እናንተ እራሳችሁ 

                                                                 ( Yourselves)

ለሊኪ አንቺ እራስሽ (Yourself)   ለሊክን = እናንተ እራሳችሁ /ለሴቶች/  

                                                                 ( Yourselves)

ለሊየ /ለልየ = እኔ እራሴ/ ( My self)   ለሊነ   = እኛ እራሳችን

                                                               ( 0urselves)

 

1ዐ.6 ተሳቢ ተውላጠ ስሞች ( Objective Pronouns)

ነጠላ                                        ብዙ

ኪያየ = እኔን ( Me)        ኪያነ  =  እኛን (Us)

ኪያከ = አንተን ( You)      ኪያክሙ = እናንተን (You)

ኪያኪ = አንቺን ( You)        ኪያክን  እናንተን ( You) ለሴቶች

ኪያሁ = እሱን ( Him)         ኪያሆሙ = እነርሱን ( Them)

ኪያሃ = እሷን ( Her)         ኪያሆን  =  እነርሱን ( Them  ለሴቶች/

 

ምሳሌ

ዘርእየ ኪያየ ርእየ አቡየ

መኑ ይጼውእ ኪያከ

ኪያኪ ሰናይተ ዘፈጠረ እግዚአብሔር ይትባረክ

ቀድሱ ኪያሁ ወባርኩ ስሞ

አምላክነ አድኀነ ኪያነ እሞት

ዘተወክፈ ኪያክሙ ተወክፈ ኪያየ

ፈኑ ኪያሆሙ ኀበ አሕዛብ

ርእየ ኪያክን ወተፈስሐ ብክን

® ስለዚህ ተሳቢ ማለት “ን” የሚለውን ቃል ወይም ፊደል

የሚያመጣ ማለት ነው፡፡

 

የሚያበዙ ፊደላት    

አ፡-

    ነጠላ              ብዙ              የብዙ ብዙ

    ደብር             አድባር             አድባራት

    ርእስ             አርእስት

ከዚህ ላይ የቃላቱን መጨረሻ ሁለት ፊደላት ማስተዋል ነው፡፡

ብር፣ እስ / ሳድስ ናቸው፡፡/

 

ን፡- ሀ. ደራሲ + ያን = ደራስያን

       ሠዓሊ + ያን = ሠዓልያን

    ለ. ኢትዮጵያዊ +ያን =  ኢትዮጵያውያን

    ሐ. ቅዱስ = ቅዱሳን

        ብፁዕ =  ብፁዓን

        መዘምር = መዘምራን

ከዚህ ላይ የቃላቱ የመጨረሻው ሁለት ፊደላት ራብዕና ሣልስ ናቸው፡፡

ራሲ፣ ዓሊ፣ እንደገና የመጨረሻዎቹ ሁለት ፊደላት ፁዕና ዱስ ይላል፡፡

 

ት፡- ኢትዮጵያዊት+ ያት – ኢትዮጵያውያት

    ሰማይ  = ሰማያት

    ቅድስት = ቅዱሳት

    ሠናይት = ሠናያት

v  አሁንም ቢሆን የቃላቱን ሁኔታ ማስተዋል ነው፡፡

 

መ፡- ኩሉ — ኩሎሙ         ለሊሁ — ለሊሆሙ        

     አንተ —አንትሙ       ለሊከ —ለሊክሙ

 እ፡- ኃጢአት — ኃጣውእ

፡- መርዔት= መራዕይ             ፡- ኪሩብ = ኪሩቤል

     ሌሊት = ለያልይ                 ሱራፊ = ሱራፌል

 

፡- ዕፅ = ዕፀው                                 

    አብ = አበው                                 

    እድ = እደው                                   

 

የጸያፍ አበዛዝ ምሳሌ

መምህራን፡ መምህራኖች
ደራሲያን ፡ ደራስያኖች
ቅዱሳን ፡ ቅዱሳኖች

ማስታወሻ፡- የጸያፍ አበዛዝ ማለት ፈጽሞ
ግእዝም አማርኛም ያልሆነና ከሕግ
ውጭ የሆነ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ
ከላይ የተጠቀሱት ቃላት
አላዋቂነት ካልሆነ በቀር ፈጽሞ
አይባሉም፡፡                                                                                                                                 

የማቴዎስ ወንጌል

ምዕራፍ ዐሥራ ሁለት

ታኅሣሥ 23 ቀን 2007 ዓ.ም.

ጌታችን እና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቀዳሚት ሰንበት በእርሻ መካከል ባለፈ ጊዜ በጣም ተርበው የነበሩ ደቀመዛሙርት እሸቱን ቀጥፈው እያሹ በሉ፡፡ ፈሪሳውያንም “ሰንበትን ስለ ምን ይሽራሉ?” ብለው ደቀ መዛሙርቱን ከሰሷቸው፡፡ ጌታችን ግን ከሚያውቁት ታሪክ የዳዊትንና የተከታዮችን እንዲሁም የቤተ መቅደሱን አገልጋዮች ታሪክ ጠቅሶ ከነገራቸው በኋላ ‹”ከመቅደስ የሚበልጥ ከዚህ አለ፡፡ ምሕረትን እወዳለሁ፤ መሥዋዕትንም አይደለም ያለው ምን እንደሆነ ብታውቁስ ኃጢአት የሌለባቸውን ባልኮነናችሁም ነበር፡፡ የሰው ልጅ የሰንበት ጌታ ነውና፡፡” ሲል መለሰላቸው፡፡

 

ይህም በበትረ ርኃብ ይመቱ፣ በረኃብ እንደ ቅጠል ይገረፉ ብላችሁ ባልፈረዳችሁባቸው ነበር፡፡ የሰንበት ጌታዋ ወልደ ዕጓለ እመሕያው ክርስቶስ ነውና ሲላቸው ነው፡፡

 

ከዚያም አልፎ ወደ ምኩራባቸው ገባ፡፡ እጁ የሰለለችውንም ሰው ፈወሰው፡፡ በሰንበት ለምን እንዲህ ታደርጋለህ? ባሉት ጊዜም በሰንበት መልካም መሥራት ተፈቅዷል አላቸው፡፡ ብዙ በሽተኞችንም ፈወሳቸው፤ ሕዝቡ በሥራው ሲደነቅ ፈሪሳውያን ግን “ይህ በብዔል ዜቡል በአጋንንት አለቃ አጋንንትን ያወጣል” ብለው በሰደቡት ጊዜ “ኃጢአትና ስድብ ሁሉ ለሰዎች ይሰረይላቸዋል፡፡ ነገር ግን መንፈስ ቅዱስን ለሰደበ አይሰረይለትም፡፡ በሰው ልጅ ላይ ቃል የሚናገር ሁሉ ይሰረይለታል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ላይ ግን የሚናገር ሁሉ በዚህ ዓለም ቢሆን ወይም በሚመጣው አይሰረይለትም” ሲል መለሰላቸው፡፡

 

የሰው ልጅ ያለው ራሱን ነው፡፡ ስድብ ያለውም ክህደትን ነው፡፡ ይህም እርሱ ስድብ እንደሚገባው መናገሩ ሳይሆን ለመሰደቡ /ለመካዱ/ ምክንያት ሥጋ መልበሱ መሆኑን ለማጠየቅ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስን የሚክዱ ግን ምክንያት የላቸውም፡፡ እነዚህ ሰዎች መንፈስ ቅዱስን በካዱት ጊዜ ስለሚለያቸው ስለ ኃጢአቱ እንዲጸጸትና ራሱን እንዲወቅስ የሚያደርግ መንፈስ ቅዱስ ነውና፡፡ ዮሐ. 16፤8፡፡ “በዚህ ዓለም ቢሆን” ሲል ስለ ኃጢአቱ ተጸጽቶ ወደ ካህኑ በመቅረብ እግዚአብሔር ይፍታህ” ስለማይባል ነው፡፡ “በሚመጣው ዓለም” ሲል ደግሞ በምድር ያልተፈታ በሰማይም ስለማይፈታ ነው፡፡ ምክንያቱም ጌታችን ደቀመዛሙርቱን በምድርም የምታሥሩት ሁሉ በሰማይ የታሰረ ይሆናል፡፡” ብሎ ሥልጣን ሰጥቷቸዋልና፡፡

 

በዚያን ጊዜ ጻፎችና ፈሪሳውያን “ከአንተ ምልክት እንድናይ እንወዳለን” ባሉት ጊዜም “ክፉና አመንዝራ ትውልድ ምልክትን ይሻል፤ ከነቢዩ ከዮናስ ምልክት በቀር ምልክት አይሰጠውም” ብሏቸዋል፡፡ ቀጥሎም በዮናስ ስብከት ንስሐ የገቡትን የነነዌ ሰዎችን እና በጆሮዋ የሰማችውን የሰሎሞንን ጥበብ በዓይኗ ለማየት በእምነት ወደ ኢየሩሳሌም የገሰገሰችው የኢትዮጵያ ንግሥት /ንግሥት ሳባን/ በዚህ ትውልድ ላይ ይፈርዱበታል ብሏቸዋል፡፡ ምክንያቱም እነዚያ በዮናስ ስብከት እና በሰሎሞን ጥበብ አምነዋል፡፡ እነዚህ ግን የዮናስ እና የሰሎሞን ፈጣሪ ቢያስተምራቸው አላመኑምና ነው፡፡

 

የባሰ ነገር እንደሚያጋጥማቸው ሲናገር መንፈስ ርኩስ ሰይጣን በጠበል በጸሎት ከሰው ከተለየ በኋላ ተመልሶ ይመጣል፣ ጸሎቱን ጠበሉን ትቶ ባገኘውም ሰው ላይ ከእሱ የከፉ ሰባት አጋንንትን ይዞ ያድርባቸዋል፡፡ “ለዚህ ክፉ ትውልድ ደግሞ እንዲሁ ይሆንበታል” ብሏቸዋል፡፡

 

በመጨረሻም ጉባኤ እንዲፈታ የሚወድ ይሁዳ እናትህ እና ወንድሞችህ በውጭ ቆመዋል አለው፡፡ ጌታችንም ለነገረው “እናቴ ማን ናት? ወንድሞቼስ እነማናቸው?” ሲል መለሰለት፡፡ ወንድሞች የተባሉት አብረውት ያደጉት የዮሴፍ ልጆች ናቸው፡፡ እነዚህም የእመቤታችን አገልጋይና ጠባቂ አረጋዊው ዮሴፍ ከሞተችው ሚስቱ የወለዳቸው ናቸው፡፡ ይህም፡-

1ኛ/ ከእናት ከአባት ክብር የእግዚአብሔር ክብር እንደሚበልጥ፣

2ኛ/ ከጉባኤ መካከል ጉባኤ አቋርጦ መነሣት እንደማይገባቸው ሲያስተምራቸው ነው፡፡