abune endrias

አቡነ እንድርያስ ገዳም/አቡነ እንድርያስ ዋሻ

ሰኔ 21 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የማኅበረ ቅዱሳን የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ክፍል አባላት በሰሜንና ደቡብ ጎንደር እንዲሁም በምዕራብ ጎጃም ሀገረ ሰብከቶች በመንቀሳቀስ የአድባራትና ገዳማት እንቅስቃሴዎችን ቃኝተን  ከተመለስን ሰነባበትን፡፡ ክፍል ስድስት ድረስ ጸበል ጸዲቅ በሚል ርዕስ ስናቀርብ መቆየታችን ይታወሳል፡፡ በዚህም መሠረት ቀጣዮቹን ክፍሎች ማቅረባችንን እንቀጥላለን፡፡  

የቴሌቪዥን ክፍል አዘጋጁ ቶማስ በየነ ከቪዲዮ ካሜራ ባለሙያው ሙሉጌታ ቢሆነኝ እኔን ጨምሮ ሊቀ መንኮራኩር ነብያት መንግሥቴ /ማዕረግ የራሳችን/ ሾፌራችን አብራሪነት ከአዲስ ዘመን ከተማ በስተ ሰሜን አቅጣጫ ወደ አቡነ እንድርያስ ዋሻ ገሰገስን፡፡

የአስፋልቱን መንገድ አገባደን ኮሮኮንቹን ጥቂት ወደ ቀኝ ታጥፈን እንደተጓዝን ከፊት ለፊታችን እንደ ጦር የሾሉ ንጣፍ ድንጋዮች አጋጠሙን፡፡ ሊቀ መንኮራኩር ነብያት መኪናውን በንዴት አቁሞ “እንዴት በዚህ መንገድ ላይ ሂድ ትሉኛላችሁ?`ለመኪናው አስቡ እንጂ!” በማለት ከመኪናው ወርዶ በኩርፊያ ከፊት ለፊት ከሚታየው ትልቅ ድንጋይ ላይ ቁጭ አለ፡፡

ያለን አማራጭ በእግር መጓዝ ስለነበር ለቪዲዮ ቀረጻ የሚያገለግሉንን መሣሪያዎች ከመኪናው ላይ አውርደን በመከፋፈል ተሸክመን ጉዟችንን ቀጠልን፡፡ ከአርባ ደቂቃ የእግር ጉዞ በኋላ አቡነ እንድርያስ ዋሻ ደረስን፡፡  የአቡነ እንድርያስ ገዳም ከአዲስ ዘመን ከተማ በስተሰሜን አቅጣጫ ከተራራ ሥር የሚገኝ የዋሻ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ በአካባቢው በተለምዶ አቡነ እንድርያስ ዋሻ በመባል ይታወቃል፡፡

abune endriasገዳሙ አራት በሮች ሲኖሩት እያንዳንዳቸው ከአንድ  ወጥ እንጨት ተጠርበው የተሠሩ ናቸው፡፡ እያንዳንዱ ደረጃና የበሩ መቃን በጣና ደሴት ውስጥ ከሚገኙት ከደብረ ሲና ማርያም፤ ከደብረ ገሊላ ኢየሱስ አቡነ ዘካርያስ ገዳም፤ ማን እንደ አባ ያሳይ መድኀኔዓለም ገዳም፤ . . . ጋር ተመሳሳይነት አላቸው፡፡ ገዳሙ ምንም ዓይነት እድሳት ያልተደረገለት ሲሆን ጥንታዊነቱን ጠብቆ የሚገኝ የዋሻ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡  

ቀሲስ ቢራራ በላቸው ይባላሉ፡፡ የገዳሙ አገልጋይና ቁልፍ ያዥ ናቸው፡፡ ስለ ገዳሙ ካጫወቱንና በገዳሙ ውስጥ ከሚገኘው ከአቡነ እንድርያስ ገድል ካገኘነው በጥቂቱ ላቅርብላችሁ፡፡

ቦታው ከክርስቶስ ልደት በፊት በ899 ዓ.ዓ. በዐፄ ባዚን ዘመነ መንግሥት የተመሠረተና የአካባቢው ሰዎች በእንጨት ምስል ቀርጸው ጣዖት እያመለኩ ቆይተውበታል፡፡ ለ440 ዓመታትም የኦሪት መሥዋዕት ሲሠዋበት የነበረ ሲሆን፤ የአካባቢው ነዋሪዎች ዋሻው ውስጥ የሚኖሩ ሁለት ባልና ሚስት  ዘንዶዎችን እርጎ እየመገቡ ያመልኳቸው እንደነበር በገዳሙ ውስጥ የሚገኘው ገድለ አቡነ እንድርያስ ይገልጻል፡፡

በሩን አልፈው ወደ ውስጥ ሲዘልቁ ሰፊውን ቅኔ ማኅሌት ያገኛሉ፤ ከፊት ለፊት ቅድስትና መቅደሱ፤ እንዲሁም በትልቁ የተሳሉ የአቡነ እንድርያስ ስዕሎች ጎልተው ይታያሉ፡፡ በቤተ መቅደሱ ግራና ቀኝ ሰልፋና ደፈር በተባሉ ሰዎች በጥርብ ድንጋይ የተከለሉ ቦታዎች አሉ፡፡ /ሰልፋና ደፈር የዘንዶዎቹ ቀላቢዎች/ እንደነበሩ ገድለ አቡነ እንድርያስን በመጥቀስ አባቶች ይናገራሉ፡፡

ገዳሙ ከክርስቶስ ልደት በኋላም የአካባቢው ሕዝብ ዘንዶዎቹን በማምለክ የቆየ ሲሆን አቡነ እንድርያስ በ13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በአቡነ ተክለ ሃይማኖት በደቀመዛሙርትነት ተመርጠው ምድረ እንፍራንዝ /የአሁኑ ሊቦ ከምከም ወረዳ አካባቢ/ ሄደው ክርስትና እንዲያስተምሩ፤ ህዝቡንም እንዲያጠምቁ ተልከዋል፡፡

አቡነ እንድርያስ ተልእኳቸውን ለመፈጸም ወደ አካባቢው ሲመጡ ረድአቸውን አቡነ ቶማስን አስከትለው ስለነበር አካባቢውን እንዲቃኙና ለጸሎabune endrias 2ት የሚመች ቦታ እንዲፈልጉ ላኳቸው፡፡ ይህ ዋሻ በአቡነ እንድርያስ ረድእ በነበሩት በአቡነ ቶማስ አማካይነት የተገኘ ሲሆን ዘንዶዎቹን ሲመለከቱ በመፍራታቸው ቦታው እንደማይሆናቸውና የዘንዶዎቹን አስፈሪነት ለአቡነ እንድርያስ ይገልጹላቸዋል፡፡ አቡነ እንድርያስም “በእግዚአብሔር ኃይል እናሸንፋቸዋለን” በማለት መጥተው በመስቀላቸው በማማተብ በእግዚአብሔር ስም ይገስጿቸዋል፡፡ በዚህ ቅጽበት አቡነ እንድርያስ የያዙት መስቀል ከመሬት ወድቆ የቀኝ በኩል ክንፉ በመሰበሩ ወደ እግዚአብሔር ቢጸልዩ የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ እንደነበረ አድርጎ ሰጥቷቸዋል፡፡ ከዘንዶዎቹ አንዱ ከአካባቢው ማዶ ተምዘግዝጎ ግራርጌ ጉበያ ማርያም ከሚባል ቦታ ላይ ወድቋል፡፡ አንደኛው ግን እስከ ዛሬ ድረስ የደረሰበት ባይታወቅም ወደ ዋሻው ውስጠኛ ክፍል ገብቶ እንደቀረ ይነገራል፡፡

አቡነ እንድርያስ ገዳሙን አቅንተው የአካባቢው ምእመናንን ክርስትና በማስተማር ታላቅ ተድጋሎ የፈጸሙበት ቅዱስ ስፍራ ነው፡፡ ወደ ገዳሙ በተአምራት አብረዋቸው የመጡ አራት በግምት አንድ ሜትር ቁመት ያላቸውና ከ20 እስከ አሥራ አምስት ሣንቲ ሜትር ስፋት ያላቸው ድንጋዮች መካከል ሁለቱ በደወልነት አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ ሲደወሉ ወፍራምና ቀጭን ድምጽ ስለሚያወጡ የወንድና የሴት ደወሎች ይባላሉ፡፡ በአገልግሎት ወቅት ዋሻው ድምጽ እያስተጋባ ስለሚያስቸግር አቡነ እንድርያስ ገስጸውት እስከ ዛሬ ድረስ ዋሻው ምንም ዓይነት ድምፅ አያስተጋባም፡፡

በገዳሙ ውስጥ ዜና ማርያም የተባለችው ቅድስት እናት ለ25 ዓመታት በጸሎት ተወስና ቆይታበታለች፡፡ ከእንጨት ተፈልፍሎ በቁመቷ ልክ በተሠራ ገንዳ ውስጥ ገብታ የገንዳውን ግራና ቀኝ በደረቷ አቅጣጫ በመብሳት በጠፍር በማሰር ትጸልይ ነበር፡፡/ ዜና ማርያም ትጸልይበት የነበረው የእንጨት ገንዳ ዛሬም በገዳሙ ውስጥ ይገኛል፡፡/

በገዳሙ ውሰጥ በጥንቃቄ ጉድለት እየተበላሹ የሚገኙት ቅርሶች እንደ አልባሌ እቃዎች ተጥለዋል ማለት ይቻላል፡፡ ዘንዶው እርጎ ይጠጣበት የነበረው ገንዳ፤ የዜና ማርያም መጸለያ ገንዳ፤ በእንጨት የተሠራ የኦሪት መሠዊያ፤ የመሥዋዕተ በግዕ ሥጋ ማስቀመጫ፤ የደሙ ማኖሪያ፡ ዐፄ ዘርዓያዕቆብ ለገዳሙ ከሰጧቸው 6 ነጋሪቶች መካከል ሁለቱ፤  ብዛት ያላቸው የሰው አጽሞች ይገኛሉ፡፡ ከአጽሞቹ መካከል አንዱ ሙሉ ለሙሉ ሳይፈርስ ከራስ ቅሉ እስከ እግር ጥፍሩ በዘመናዊ ሳጥን ተደርጎ ከላይ በመስታወት ታሽጎ ይታያል፡፡ የአጽሞቹን እድሜ መገመት እንደማይቻልና ቀድሞም እንደነበሩ ቀሲስ ቢራራ በላቸው ይገልጻሉ፡፡

የአቡነ እንደርያስ የእጅ መስቀል በገዳሙ ውስጥ በቅርስነት ተጠብቆ ይኖር እንደነበር፤ ብዛት ያላቸው ምእመናን በመስቀሉ ታሽተው ከያዛቸው ደዌ ይድኑ እንደነበር ቀሲስ ቢራራ በላቸው የዐይን ምስክር እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን በቅርቡ በአንድ ግለሰብ የአቡነ እንድርያስ መስቀል መዘረፉንና የግለሰቡ ማንነት ታውቆ ክስ ተመሥርቶበት በቀጠሮ ላይ እንደሚገኝ ገልጸውልናል፡፡ የአቡነ እንድርያስን ዋሻ ቆይታችንን አጠናቀን ስንወጣ የገዳሙ አበምኔት የክሱን ሁኔታ ለመከታተል ከሔዱበት ሲመለሱ አግኝተናቸው ነግረውናል፡፡

abune endrias 1ገዳሙ ለስርቆት የተጋለጠ በመሆኑ የገዳሙ ጥንታዊ መጻሕፍት ተሰብስበው በአንድ ታማኝ በሆነ ግለሰብ ቤት ውስጥ እንዲቀመጥ መደረጉንም ቅርሶቹን ለማየት በጠየቅንበት ወቅት ከተሰጠን ምላሽ ለማወቅ ችለናል፡፡ የብራና መጻሕፍት ገድለ ሠማእታት፤ ስንክሳር የዓመት /2/፤ ጸሎተ እጣን፤ ግንዘትና . . . ሌሎችም ንዋያተ ቅዱሳት በዚሁ ታማኝ ነው በተባለው ሰው እጅ ላይ ይገኛሉ፡፡ በየዓመቱም ቆጠራ እንደሚካሔድ በስፍራው ከነበሩት አባቶች ተገልጾልናል፡፡

ምእመናን ተጠምቀው ከተያዙበት ደዌ የሚፈወሱበት ጸበል ከገዳሙ በስተ ደቡብ ይገኛል፡፡ ጸበሉ በምንጭነት የሚፈልቅ ሲሆን ምንም ዓይነት ከለላ ስላልተደረገለት ለከብቶችና ለአራዊት የተጋለጠ ነው፡፡

የኢየሱስ፤ የቅዱስ ሚካኤልና የአቡነ እንድርያስ ታቦታት፤ እንዱሁም የአቡነ እንድርያስ መቃብር በዚሁ ዋሻ ቤተ መቅደስ ውስጥ ይገኛሉ፡፡ አቡነ እንድርያስ ግንቦት 20 ቀን 1246 ዓ.ም. ወደ ገዳሙ እንደገቡ ገድላቸው የሚገልጽ ሲሆን ዓመተ ምሕረቱን ባይገልጽም ጳጉሜ 3 ቀን እንዳረፉ ይጠቅሳል፡፡ገዳሙ ምንም ዓይነት የገቢ ምንጭ የሌለው ሲሆን አገልጋዮቹ የራሳቸውን የእርሻ መሬት እያረሱ በሚያገኙት ይተዳደራሉ፡፡

ስዱዳን ለስዱዳን

ሰኔ 21 ቀን 2005 ዓ.ም

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ

ባለፈው ጽሑፌ በገባሁት ቃል መሠረት በባዕድ ምድር የሚኖሩ ወገኖች፤ የስደት ሕይወትን ከጀመሩበት አንሥቶ የጠበቁትን በማጣታቸው ችግር ውስጥ የገቡትን ወገኖቻቸውን እንዴት መርዳት እንዳለባቸው ለመጻፍ አሳቦቼን እያብላላሁ ነበር፡፡ ግንቦት ሃያ ቀን ምሽት እኔና ቤተሰቤ አልፎ አልፎ በምናየው የኢ.ቢ.ኤስ ቴሌቪዥን ጣቢያ አንድ ቃለ ምልልስ ተመለከትኩ፡፡ ቃለ ምልልሱን ያደረገችው በጣቢያው «ሄለን ሾው» የተሰኘ ሳምንታዊ ፕሮግራም ያላት ሄለን አሰፋ ነበረች፡፡ የዕለቱን ውይይት ያደረገችው ትእግሥት ከተባለች በመካከለኛው ምሥራቅ ነዋሪ ከሆነች ኢትዮጵያዊት ጋር ነበር፡፡ ትዕግሥት በወጣትነት የዕድሜ ክልል ውስጥ ትገኛለች፡፡

እንደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊት ወጣት ሠርታ ለመለወጥና ቤተሰቦቿን ለመለወጥ ወደ ዐረብ አገር ተሻግራ ለዓመታት የቆየች ናት፡፡ ትዕግሥት ከሄለን ጋር ባደረገችው ውይይት እንደገለጸችው ወደ የመን ከተሻገረች በኋላ እንደ አብዛኛዎቹ እኅቶቻችን በሰው ቤት ተቀጥራ ብዙ ችግሮችን አልፋለች፡፡ በአሠሪዎቿ ምግብ ከመነፈግና ከመራብ ጀምሮ እስከ መደብደብና መታሠር፤ በመጨረሻም እስከ መባረር ደርሶባታል፡፡ ከብዙ ድካም በኋላ በዐረብ አገር የሚሠሩ እኅቶቻችንን ሥቃይ አልፋበት ያየችው ትዕግሥት ላቧን አንጠፍጥፋ ያጠራቀመቻትን ገንዘብ ይዛ በእሷ የደረሰ እንዳይደርስባቸው የኢትዮጵያውያን እኅቶቻችንን ሥቃይ ቢቻል የሚያጠፋ ባይቻል ደግሞ የሚያቃልል ድርጅት ለማቋቋም ትወስናለች፡፡ በዚህ እንቅስቃሴዋ ላይ አንድ መቀመጫውን በኒውዮርክ ያደረገ በስደተኞች ላይ የሚሠራ ድርጅት ጋብዟት ወደ አሜሪካ እንደተሻገረች በቃለ መጠይቁ ገልጻለች፡፡

ትዕግሥት በዐረብ አገር ስለሚገኙ እኅቶቻችንና ሳይፈልጉ ስለሚወልዷቸው ሕጻናት ሥቃይ ስትገልጽ በዕንባም ጭምር ነበር፡፡ በዚያ የሚኖሩ እኅቶች በአጋጣሚ ስሕተት ወይም ተገደው የሚወልዷቸው ሕጻናት የመማርና እንደ ሕፃን የመጫወት መብት ተነፍጓቸው ከወላጆቻቸው ጋር እንደሚመቱ፣ እንደሚራቡና እንደሚታሰሩ ስትገልጽ ሐዘን በሰበረው ድምፅ በዕንባ እየታጠበች ነበር፡፡ ይህች እኅት እነዚህን በከፋ ችግር ላይ ያሉ ሕፃናትና ወላጆቻቸውን ለመርዳት በምታደርገው እንቅስቃሴ በአሜሪካ ያሉ ኢትዮጵያውያን ምን እንዲረዷት እንደምትፈልግ ተጠይቃ አጽንኦትና ትኩረት ሰጥታ የተናገረችው ከወላጆቻቸው ጋር እየተሠቃዩ ያሉ ሕፃናት መጠለያ የሚያገኙበትን፣ ተምረውና እንደ ልባቸው የሚያድጉበትን ዕድል እንፍጠር፤ ወላጆቻቸውንም እንርዳ የሚል ነበር፡፡

ይህ የትዕግሥት መልእክት የዚህ ጽሑፍም የመጀመሪያ መልእክት ነው፡፡ ከብዙ ድካም በኋላ የስደት ሕይወታቸው የሠመረላቸው ኢትዮጵያውያን ወገኖቻቸው በልዩ ልዩ ምክንያት ተሰደው ወደሚኖሩበት አገር ሲመጡ በግልም በማኅበርም ሆነው መርዳት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ለዚህ የተቀደሰ ተግባር ደግሞ በየሚኖሩበት አገር በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር ተሰባስበው የሚገለገሉና የሚያገለግሉ ምእመናን ምቹ ሁኔታ ተፈጥሮላቸዋል ማለት ይቻላል፡፡ የተቸገሩትን ስለመርዳት፣ ሀገርና ወገንን ስለመውደድና ስለ ፍቅር አብዝታ በምታስተምር ቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር ናቸውና፡፡

ባለፈው ጽሑፋችን እንዳየነው በልዩ ልዩ ምክንያት አገር ወገናቸውን ትተው ወደ ባዕድ ምድር የሚሔዱ ወገኖች ስለሚሰደዱበት አገር ነባራዊ ሁኔታ መረጃ አይሰበስቡም፡፡ በብዛት እንደ ሚታየው ከሔዱም በኋላ በቀላሉ የተለያዩ መረጃዎችን የሚያገኙበት ዕድል የላቸውም፡፡ እንዴትና የት ሥራ እንደሚያገኙ፣ ኑሮአቸው እስከሚ ስተካከልና ራሳቸውን እስከሚችሉ አገሩ ያዘጋጃቸው የዕርዳታ ዕድሎች መኖር አለመኖራቸውን፣ ቋንቋ የትና እንዴት በቀላሉ መማር እንደሚችሉ ወዘተ ቀድመው የሔዱ ኢትዮጵያውያን በግልም በማኅበርም ሆነው ለአዳዲስ ስዱዳን ወገኖቻቸው ማካፈል ይገባቸዋል፡፡ የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ በውጭው ዓለም በነበረው ቆይታ ያረጋገጠው ለአዳዲስ ስዱዳንም ሆነ እዛ በቆዩ ኢትዮጵያውያን መካከል ያለው የመረጃ ልውውጥ ከሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በእጅጉ ያነሰ መሆኑን ነው፡፡ ይህ ነገር ወደፊት መሻሻል አለበት፡፡ ወገኗን ብቻ ሳይሆን ባዕዳኑን በየዘመኑ በአክብሮት እየተቀበለች፣ ከገጠማቸው ችግርም እየታደገች ከኖረችና ካለች አገር የሔዱ መሆናቸውን ሊያስታውሱ ይገባል፡፡

የስደት ሕይወት እስከሚለምዱት ድረስ ከባድ ነው፡፡ ተወልደው ካደጉበት ቀዬ፣ ባሕልና ቋንቋ ተለይተው፣ ከቤተሰብ ሙቀትና ክብካቤ ርቀው የሚጀምሩት ሕይወት ነውና፡፡ በብዙ ቦታዎች እንደሚታየው በዚህ ፈታኝ ወቅት ተገቢውን ዕርዳታ ያገኙ ወገኖች በስደት ሕይወታቸው ሁሉ ከወገናቸው ርቀው የሚኖሩ፣ በመንገዳቸው እንኳን ኢትዮጵያዊ ካዩ ወይ መንገድ ቀይረው የሚሔዱ ካልሆነም ሰላምታም ሳይሰጡ የሚያልፉ፣ በጥቅሉ የተገለሉ ናቸው፡፡

በተለያዩ ጊዜያት በልዩ ልዩ መንገዶች እንደ ሰማነው የተሻለ ኑሮ ፍለጋ ረጅሙን በረሐ በሕገ ወጥ መንገድ አቋርጠው፤ ከዚያም አደገኛ በሆነ ሁኔታ ውቅያኖስን አቋርጠው ወደ ጣልያንና ሊባኖስ ይሻገራሉ፡፡ በዚህ ዓይነት ከሚሔዱት ሩብ ያህል የሚሆኑት በመንገዳቸው በሚገጥማቸው አደጋ የበረሃና የውኃ ሲሳይ ሆነው ይቀራሉ፡፡ እግዚአብሔር ጠብቋቸው በረሃውን አልፈው፣ ውቅያኖሱን ዘልቀው ጣልያን የሚደርሱት ወገኖች የተለያዩ ችግሮች ሲያጋጥሟቸው እንደነበር የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ አስተውሏል፡፡ ከሚገጥሟቸው ችግሮች ውስጥ አንዱ በዚያ በሚኖሩ መናፍቃን የሚፈጠርባቸው ችግር ተጠቃሽ ነው፡፡ የጽሑፉ አዘጋጅ በቅርበት እንደተመለከተው በተለይ ጣልያን ያሉ ኢትዮጵያውያን ፕሮቴስታንት አዳዲስ ስዱዳን ወገኖቻችንን በልዩ መንገድ እየተቀበሉ፣ በችግራቸው እየገቡ እምነታቸውን ያስለውጧቸዋል፡፡ ከብዙ ድካምና ሰቀቀን በኋላ ወደማያውቀው አገር የገባ ሰው እንኳን በመልክ የሚመስለው ቋንቋውን እያወራ ልርዳህ ብሎ የቀረበው ሰው አግኝቶ ማንንም ቢሆን መቀበሉ አይቀርም፡፡

በዚህ የተነሣ በጥምቀት ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ከማኅጸነ ዮርዳኖስ ተወልደው የእናት ቤተ ክርስቲያንን ጡት እየጠቡ ያደጉ ወገኖች፤ በደጇ ተመላልሰው ዕንባቸውን እያፈሰሱ ያደጉባትን ቤተ ክርስቲያን ትተው ሔደዋል፡፡ እየሔዱም ነው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ በዚያ ያለችው ቤተ ክርስቲያን ልጆቿን አስተባብራ፣ ስዱዳን ልጆቿን ተቀብላ ማጽናናትና ማስተናገድ አለመቻሏ ነው፡፡

በደሙ የመሠረታት አምላክ የተመሰገነ ይሁንና ዛሬ ቤተ ክርስቲያችን በዓለም ሁሉ የተበተኑ ልጆቿን እየተከተለች ያልደረሰችበት የዓለም ክፍል የለም፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ይህንን ሥርጭት ያደረገችው በምናውቃቸው ውስጣዊና ውጫዊ ችግሮች አልፋና እያለፈች እንደሆነ ቢታወቅም ሐዋርያዊ ጉዞዋ ካለው ችግር አንጻር ሲመዘን የሚያስደስት እንጂ የሚያሳዝን አይደለም፡፡ ይሁን እንጂ ምንም እንኳን ሁሉም ናቸው ባይባልም በአብዛኛው አብያተ ክርስቲያናት አገልግሎታቸው በቤተ መቅደስ ብቻ የተወሰነ ነው፡፡ ነገር ግን ቤተ  ክርስቲያን ሐዋርያዊ እጇ ረጅም መሆን አለበት፡፡ በመሆኑም ወደ አካባቢዋ የመጡ ልጆቿን ወዳሉበት ሔዳም የመሰብሰብ አገልግሎት መፈጸም ይጠበቅባታል፡፡ ይህ ተልእኮዋ በተለይ አዲስ ስዱዳንን በመሰብሰብና ከወገናቸው ጋር እንዲተዋወቁ፣ የሀገሩን ባሕልና ቋንቋ እንዲለምዱ ማድረግ ይጠበቅባታል፡፡ ለዚህ ደግሞ በባዕድ ምድር ያሉት አብያተ ክርስቲያናት ይህንን ደገኛና በእጅጉ አስፈላጊ የሆነ ተግባር እንዲያከናውኑ የሚያደርጋቸውን ዕቅድና አሠራር መዘርጋት አለባቸው፡፡

ማጠቃለያ
በጽሑፉ እንደተመለከትነው ሕይወታቸውን በስደት መሥርተው የቆዩ ወገኖች ወደ አካባቢያቸው የሚመጡ ስዱዳንን በመቀበል ሊኖራቸው የሚገባቸውን ሚና በአጭሩ ተመልክተናል፡፡ ከምእመናኑም በተጨማሪ የእነሱ ኅብረት የሆነች ቤተ ክርስቲያንና አስተዳደሯ ይህንኑ ደገኛ ተግባር በመፈጸም ረገድ ልትከተለው የሚገባትን አቅጣጫ አሳይተናል፡፡ በዚህ አጭር ጽሑፍ ከተሰነዘሩት ጥቂት አሳቦች የበለጠ ኑሮአቸውን በስደት ካደረጉ ወገኖች ሊቀርቡ የሚችሉ አሳቦች እንደሚኖሩ ይታመናል፡፡

በመሆኑም በተደጋጋሚ እንደገለጽነው ይህ ዓምድ የተከፈተው ከዝግጅት ክፍሉ ከሚጻፉ ትምህርቶች በተጨማሪ ኑሮአቸውን በውጭው ዓለም ያደረጉ ምእመናን የሕይወት ልምዳቸውንና ተሞክሯቸውን በመለዋወጥ እንዲማሩ ለማድረግ ነው፡፡ ስለዚህ ወገኖቻችን ይህንን ዕድል በመጠቀም አገልግለው በረከት እንዲያገኙ ዛሬም ግብዣችንን እናስተላልፋለን፡፡
 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት 18 ከሰኔ 1-15 ቀን 2005 ዓ.ም.

ሰዋስወ ግእዝ (ክፍል ሁለት)

ሰኔ 19 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ት ኑኀሚን ዋቅጅራ

 ፩.፪. የግእዝ ፊደላት አካፋፈል

መጀመሪያ ጊዜ ለሄኖስ በጸፍጸፈ ሰማይ (በሰማይ ገበታነት) የተገለጹለት ፊደላት አሁን በፊደል ገበታ ላይ በቅደም ተከተል እንደምናያቸው ሳይሆን ከዚህ በተለየ መልኩ ተዘበራርቀውና የእብራይስጡን የቋንቋ ስልት ይዘው ነው እነሱም አሌፋት በመባል የራሳቸው ስያሜ ነበራቸው

አ – አሌፍ                           ሐ – ሔት                            ሠ – ሣምኬት

በ – ቤት                            ጠ – ጤት                            ጸ – ጻዴ

ገ – ጋሜል                          የ – ዮድ                              ፈ – ፌ

ደ – ዳሌጥ                          ከ – ካፍ                              ዐ – ዔ

ሀ – ሄ                               ለ – ላሜድ                           ቀ – ቆፍ

ወ – ዋው                           መ – ሜም                           ተ – ታው

ዘ – ዛይ                             ነ – ኖን                                ረ – ሬስ

በማለት በእብራይስጡ አጠራር ይጠሯቸው ነበር፤ ነገር ግን እነዚህን የግእዝ ፊደላት በኢትዮጵያ ቀዳማዊ ጳጳስ በአቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን የግእዝ ፊደላትን አሻሽለው አሁን በፊደል ገበታ ላይ የምናያቸውን በቅደም ተከተል ከማስቀመጣቸው በፊት ያሉት ፊደላት፡-

 

ቀዳማዊ የግእዝ ፊደላት በሚል ስያሜ የሚጠሩ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ከሀ – ጀምሮ በዝርዝር በቀደም ተከተል የምናያቸው ፊደላት ደግሞ ደኀራዊ የግእዝ ፊደላት ብለን በሁለት እንመለከታቸዋለን፡፡

 

፩.፫. ቀዳማዊና ደኀራዊ የግእዝ ፊደላት፣-

፩. ቀዳማዊ የግእዝ ፊደላት የምንላቸው በአሁኑ ጊዜ በፊደል ገበታ ላይ አ፣ በ፣ ገ፣ ደ…./አቡጊዳ/ በማለት የምንጠራው የፊደል አቀማመጥ ነው እነዚህ ፊደላት በመነሻ ፊደል ብቻ ነበር የተጻፉት፡፡

 

                                      ቀዳማዊ የግእዝ ፊደላት

                                      

                                     

                                       

                                     

                                      

                                     

                                      

                                     

                   

በዚህ ዓይነት አቀማመጥ በነጠላ በግእዝ ፊደሉ ብቻ ነበር የተቀመጡት ከዚህ በኋላ ግን በእነዚህ ፊደላት ላይ የተወሰኑ ቅጥያዎችን በመጨመር በመጀመሪያ ደረጃ እነዚህን ፊደላት ወደ ሰባት የፊደላት አዘራዘር በመለወጥ ለእያንዳንዱ ፊደል የተለያዩ ቅርጽና ድምጽን በመፍጠር ፊደላቱ ወደ ሰባት ድምጽ /ሥልት/ ተለውጠው እንዲጻፉ በወቅቱ ከነበሩት ሊቃውንት አባቶች ጋር በመነጋገር የፊደላቱን ቅርጽ አዘጋጅተውልናል፡፡


 

 

ግእዝ

ካዕብ

ሣልስ

ራብዕ

ሐምስ

ሳድስ

ሳብዕ

፲፩

፲፪

፲፫

፲፬

፲፭

፲፮

፲፯

፲፰

 

 

ግእዝ

ካዕብ

ሣልስ

ራብዕ

ሐምስ

ሳድስ

ሳብዕ

፲፱

፳፩

፳፪

፳፫

፳፬

፳፭

፳፮

 

ደሐራዊ የግእዝ (የኢትዮጵያ) ፊደላት አጻጻፍ

 

ግእዝ

ካዕብ

ሣልስ

ራብዕ

ሐምስ

ሳድስ

ሳብዕ

፲፩

፲፪

፲፫

፲፬

፲፭

፲፮

፲፯

፲፰

፲፱

፳፩

፳፪

፳፫

፳፬

፳፭

፳፮

 

የግእዝ ቋንቋ እንደ ሌሎች ቋንቋዎች እራሱን የቻለ ሕግና ሥርዓትን ተከትሎ የሚነገር ጥንታዊ ቋንቋ ነው፡፡ አንድን ቋንቋ እንደ ቋንቋ ከሚያስቆጥሩት መሠረታዊ ነገሮች አንዱ እና ዋንኛው የራሱ የሆኑ ፊደላት ሲኖሩት እና የራሱን የአነጋገር ሥርዓት ተከትሎ መሄድ ሲችል ነው፡፡ ይህም በመሆኑ በዛሬ አምዳችን ስለ ግእዝ ቋንቋ ፊደላት ብዛትና የፊደላቱንም ስያሜ ትርጒም እንመለከታለን፡፡

  1. የግእዝ ፊደላት አጠቃላይ ብዛት ፳፮ (26) ነው፡፡
  2. የግእዝ ፊደላት በሰባት የአዘራዘር ስልት ይዘረዘራሉ፡፡
  3. የግእዝ ፊደላት ብዛት ከነ አዘራዘራቸው ፻፹፪ (182) ናቸው፡፡
  4. ይህም ማለት እየአንዳንዱ ፊደል በሰባት ሥልት ስለሚዘረዘር ነው፡፡

ምሳሌ. ሀ. ግእዝ ሁ. ካዕብ ሂ. ሣልስ ሃ. ራብዕ ሄ.ሐምስ ህ.ሣድስ ሆ. ሣብእ ከፊደል ሀ እስከ ፐ ያሉት ፊደላት በዚህ ዓይነት መንገድ ይዘረዘራሉ፡፡

 

በፊደል ገበታ ላይ የምናገኛቸው የፊደላት ብዛት አጠቃላይ ፴፫ (33) ሲሆኑ ቀሪዎቹ ፯ (ሰባት) ፊደላት የአማርኛ ፊደላት በመባል ይጠራሉ፡፡ እነዚህን ፊደላት ከነ አዘራዘራቸው በሌላ ጊዜ እናያቸዋለን፡፡ ለዛሬ ፳፮ (26)ቱን የግእዝ ፊደላት በቅደም ተከተል ከነትርጒማቸው እንመለከታለን፡፡

 ፩.   ሀ- ብሂል ሀልዎቱ ለአብ እም ቅድመ ዓለም፡፡

   ሀ- ማለት የአብ አኗኗሩ ከዓለም በፊት ነው፡፡

  ፪.  ለ- ብሂል- ለብሰ ሥጋ እምድንግል፡፡

   ለ. ማለት- ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ሥጋን ለበሰ፡፡

  ፫. ሐ. ብሂል ሐመ ወሞተ ወተቀብረ፡፡

  ሐ.ማለት ክርስቶስ ታመመ፣ ሞተ፣ ተቀበረ፡፡

  ፬.  መ. ብሂል መንክር ግብሩ ለእግዚአብሔር፡፡

   መ-ማለት የእግዚአብሔር ሥራው ድንቅ ነው

  ፭. ሠ- ብሂል ሠረቀ በሥጋ፡፡

    ሠ- ማለት ጌታ በሥጋ ተወለደ (ተገለጠ)፡፡

  ፮.  ረ- ብሂል ረግዓት ምድር በቃሉ፡፡

   ረ- ማለት ምድር በቃሉ ረጋች (ጸናች)፡፡

  ፯.  ሰ- ብሂል ሰብአ ኮነ እግዚእነ፡፡

    ሰ- ማለት ጌታችን ሰው ሆነ፡፡

    ፰. ቀ- ብሂል ቀዳሚሁ ቃል፡፡

   ቀ- ማለት በመጀመሪያ ቃል ነበር፡፡

   ፱.…….    በ- ብሂል በትኅትናሁ ወረደ እግዚእነ፡፡

   በ- ማለት ጌታችን በትሕትናው ወደኛ ወረደ (ተወለደ)፡፡

        ፲.  ተ- ብሂል ተሰብአ ወተሰገወ፡፡

        ተ- ማለት ጌታችን ሰው ሆነ፡፡

        ፲፩ . ኀ- ብሂል ኀያል እግዚአብሔር፡፡

        ኀ- ማለት እግዚአብሔር ኀያል ነው፡፡

        ፲፪.  ነ- ብሂል ነሥአ ደዌነ ወፆረ ሕማመነ፡፡

 ነ- ማለት ጌታችን ደዌያችንን ያዘልን ሕመማችንን ተሸከመልን

        ፲፫.  አ- ብሂል አአኲቶ ወእሴብሖ ለእግዚአበሔር አቀድም (አእኲቶቶ ለእግዚአብሔር)

                    አ- ማለት እግዚአብሔርን በፍጹም ልቤ አመሰግነዋለሁ (እግዚአብሔርን ማመስገንን አስቀድማለሁ)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

ይቆየን

የስደት ጦስና ተስፋ

ሰኔ 19 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ

ወቅቱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ለወታደራዊ ሥልጠና ወደ ብላቴ የውትድርና ማሠልጠኛ ጣቢያ እንዲሔዱ የተገደዱበት ነበር፡፡ ተማሪዎቹ በወቅቱ የነበረው መንግሥት ባዘዘው መሠረት ወደ ማሠልጠኛ ጣቢያው ሔደው ለወራት የውትድርናውን ትምህርትና ሥልጠና ወሰዱ፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሔር ጥበቃ ሥልጠናው አልቆ ወደ ጦር ግንባር መወሰጃ ጊዜአቸው ሲደርስ ያዘመታቸው መንግሥት በኃይል ሥልጣኑን ለቀቀ፡፡ በየከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ በአውቶቡስ ተጉዘው ብላቴ በረሃ የከተሙት ተማሪዎች መንግሥት ሲፈርስ የእነሱም ካምፕ ፈረሰ፡፡ ግማሹ ወደየመጣበት ሀገሩ፤ ግማሹ ደግሞ ከሚወዳት እናት ሀገሩ ተለይቶ ወደ ኬንያ ተሰደደ፡፡

ወደ ኬንያ ከተሰደዱት ተማሪዎች አንዱ ክብረት /ትክክለኛ ስሙን ቀይሬዋለሁ/ ነበር፡፡ ክብረት ወደ ኬንያ የተሰደደው ጠላ ጠምቀው በቆልት አብቅለው በመሸጥ ያስተማሩትንና የሚወዳቸውን እናቱን ለመለየት እየጨነቀው ነበር፡፡ ምንም እንኳን ምርጫቸው እንደ አብሮ አደግ ጓደኛቸው ክብረት ወደ ኬንያ መሔድ፤ ከዚያም አውሮፓ¬ ወይም ካናዳ ከተቻለም አሜሪካ መግባት የነበረ ቢሆንም፤ በሁኔታዎች አስገዳጅነት ከብዙ ድካምና ረሃብ በኋላ አገራቸው የገቡት የክብረት ሁለት የሠፈር ልጆች፤ እንደደረሱ ለክብረት እናት በማለዳ ሔደው “እትዬ አበባ /ስማቸው አይደለም/ እንኳን ደስ አለዎት እኛ ፈሪዎች ወደ አገራችን ስንመጣ ደፋሩና ነገን ያሰበው ልጅዎ ኬንያ ገባ፡፡ ራሱን ለውጦ ይለውጥዎታል” ይሏቸዋል፡፡ ይህ አባባላቸው የክብረት ጓደኞች እንዳሰቡት ለእትዬ አበባ የምሥራች አልነበረም፡፡ ድንጋጤው ኡኡታውና ደረት ድቂው ዕድሜ የጎሰመውን አካላቸውን አዝለፍልፎ ለጣላቸው እትዬ አበባ መርዶ ነበር፡፡ ምክንያቱም ለእትዬ አበባ ስደት ማለት ሞት ነው፡፡ እንኳን ጠላ ጠምቀው በመሸጥ ላሳደጉት ብቸኛ ልጃቸው ለማንም ኢትዮጵያዊ ተመኝተውትም አያውቁ፡፡

ይህ በቅርቡ ሃያ ዓመት የሞላው እውነተኛ ታሪክ ነው፡፡ ትላንት የእኛ እናቶች ስደትን እንደሞት ያዩ ነበር፡፡ ተሰደደ/ች ሲሏቸው ሞተ/ች ብለው ያለቅሱ፤ ይጮኹ ነበር፡፡ ወዳጅ ዘመድ ተሰብስቦም ያስተዛዝን ነበር፡፡ ዛሬ ግን ተቀይሯል፡፡ የአንድ ቤተሰብ አባል እንኳን ሔደ ተብሎ፤ የደስታ ድግሱ ፌስታው የሚጀመረው ገና የግብዣ ወረቀት ሲላክ ነው፡፡ የስደት ጉዞው እውን ሲሆን ቪዛ ሲመታለትማ /ሲመታላትማ/ ሰርግና ምላሽ ነው፡፡ ትላንት እነ እትዬ አበባ ልጅዎ ውጭ አገር ሔደ ሲባሉ ልባቸው በሐዘን ተወግቶ ቀሪ ዘመናቸውን በለቀሶና በቁዘማ ፈጽመው ወደ መቃብር ይወርዱ ነበር፡፡ ዛሬ እናት ወይም አባት የልጃቸውን መሰደድ በኩራትና በደስታ ሲናገሩ እንሰማለን፡፡ ለዛሬው ወጣት ወንድሜ ወይም የፍቅር ጓደኛዬ ውጭ አገር ነው ማለት በኩራት የሚናገሩት ስኬት ነው፡፡ ይህ ለምን ሆነ) አንባብያን አሳባችሁን ስጡ፡፡

በየትኛውም መንገድ ወይም ምክንያት በርካታ ኢትዮጵያውያን ሀገራቸውን ትተው በስደት ሕይወታቸውን እንደሚገፉ እርግጥ ነው፡፡ ቁጥራቸው ውጭ ካሉት ወገኖቻችን ቢልቅ እንጂ የማያንስ ኢትዮጵያውያንም እነሱም ውጪ እንዳሉት እንዲሰደዱ ሲጸልዩ፣ ሲሳሉ፣ ገንዘባቸውን ሲያባክኑ፣ ሕይወታቸውን አደጋ ላይ ሲጥሉ እንደሚኖሩ ምስክሮች ነን፡፡ “የውጭ ጉዞዬ እንዲሳካ ቤቱ መጥቼ አልቅሼ ነበር፤ ተሳክቶልኝ አሁን እዚህ እገኛለሁና እልል በሉልኝ” የሚሉ ማስታወቂያዎች በየዐውደ ምሕረቱ እንሰማለን፡፡ “ይህ ደላላ ቪዛ ሊያስመታልኝ ይህን ያህል ሺሕ ብር ሰጥቼው ካደኝ” የሚሉ ፕሮግራሞች በኤፍ ኤም ሬድዮዎቻችንም ጭምር እናደምጣለን፡፡ “ሊቢያ ለመግባት በረሃ አቋርጠው ሲጓዙ የበረሃው ዋዕይ ሕይወታቸውን ቀጠፋቸው፤ የመን ለመግባት በጀልባ ተጭነው ሲቀዝፉ የነበሩ ኢትዮጵያውያን ጀልባቸው በሞገድ ተመትታ በመስጠሟ ሁሉም አለቁ” የሚሉ ዜናዎች በየጊዜው እናነባለን፣ እንሰማለን፡፡ “በዚህ ዐረብ አገር ትሠራ የነበረች ኢትዮጵያዊት በአሠሪዋ አሲድ ወይም የፈላ ውኃ ተደፋባት፤ ከፎቅ ተወረወረች፤ አስከሬኗ መጣ” የሚሉ መርዶዎች መስማት ልማዳችን ሆኗል፡፡ ይህ ሁሉ ለምን ሆነብን) አንባብያን አሳባችሁን፤ ገጠመኞቻችሁን የደረሰባችሁን ሁሉ ወደ ዝግጅት ክፍሉ ላኩ፡፡

በልዩ ልዩ ምክንያት ከሀገር ወጥተው ከውቅያኖሱ ባሻገር ከሚኖሩት ወገኖቻችን በዕውቀታቸውና በሙያቸው አገሩ ፈልጎአቸው በስኬት የሚኖሩ ያሉትን ያህል፤ ኑሮ ከሀገሩ እንግዳ ባሕልና የአየር ጠባይ የበለጠ ከብዶአቸው በምሬትና በመሳቀቅ የሚኖሩ፤ አልፎ አልፎም ራሳቸውን የሚያጠፉ እንዳሉ እንሰማለን፤ እናያለንም፡፡ ይህ ችግር በተለይ ገና የስደቱን ኑሮ አሐዱ ብለው በጀመሩት ይበዛል፡፡ ከብዙ ጸሎትና ድካም በኋላ ያሰቡት ተሳክቶ የሔዱ ወገኖች የቅርብና የልብ ወዳጅ ዘመድ ካጠገባቸው ከሌለ ከፍተኛ ችግር ውስጥ ይገባሉ፡፡ ብዙ ጊዜ እንደምንሰማው ገና እንደሔዱ የሚያጋጥማቸው ችግር ሕሊናቸውን ከመጉዳቱ ባሻገር ጠባሳው በስደት ሕይወታቸው ሁሉ ዘልቆ ኑሮአቸውን ከባድ ያደርግባቸዋል፡፡

የሥነ ልቡና ምሁራን አንድ ሰው የጠበቀውን እና የጓጓለትን ነገር ሲያጣ የሚያጋጥመውን ሥነ ልቡናዊ ስብራት ሥነ ልቡናዊ መራቆት /Psychological Crisis/ ይሉታል፡፡ በአገራቸው ምድር ሳሉ ሁሉም ለምለም ሆኖ በምናብ ይታያቸው የነበረ የባዕድ ምድር፤ ምድሩ ላይ ቆመው ሲያዩት ልምላሜው በቀ ላሉ ምግብ የማይሆን ሆኖ ሲያገኙት፤ በአጭሩና ካለ ብዙ ድካም በኪስ እንደሚታጨቅ ያሰቡት ገንዘብ ብዙ ድካምና ራስን ዝቅ ማድረግ እንደሚጠይቅ ሲረዱ ከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ ይገባሉ፡፡ ጭንቀታቸው በርትቶም የጤና እክል ይገጥማቸዋል፡፡ ይህ የጤና ችግር ደግሞ በስደቱ ምድር በጉልበታቸው ሮጠው በዕውቀታቸው ተወዳድረው ሕይወታቸውን እንዳያሻሽሉ ዕንቅፋት ይኾንባቸዋል፡፡ ለመሆኑ በርካታ ኢትዮጵያውያን የስደትን ሕይወት ሲጀምሩ ከፍተኛ መደናገጥ፣ መታመምና አልፎ አልፎም ኅልፈተ ሕይወት የሚያጋጥማቸው ለምንድን ነው) የተወሰኑትን ምክንያቶች ከዚህ በታች እናያለን፡፡

1. የተሳሳተ መረጃ
ሀገር ቤት ያለን ኢትዮጵያውያን ስለውጭው ዓለም የምንረዳው በዋና ነት በዚያ ከሚኖሩ ወገኖቻችን ነው፡፡ ምንም እንኳን የባዕድ ሀገር ሕይወት ምን ዓይነት እንደሆነ ካዩትና ከደረሰባቸው እውነቱን የሚናገሩ ቢኖሩም፤ በአብዛኛው በስደት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ለዕረፍት ወደ ሀገራቸው ሲመጡም ሆነ እዚያው ባሉበት ሆነው ለወዳጅ ለዘመዳቸው የሚያስረዱት፤ በእጅጉ እንደሚመች፣ ሰው ዐቅሙ እስካለው ድረስ ሥራ አማርጦ በመሥራት ገንዘብ እንደሚዛቅበት ነው፡፡ ለዚህ ከእውነት የራቀ ምስክርነታቸው ማስረጃ ለማድረግም ብዙ ደክመው /በግሌ እንዳየሁትም/ ለራሳቸው በአግባቡ ሳይመገቡና ሳይለብሱ ያጠራቀሟትን ገንዘብ ወደዚህ ሲልኩ ጥቂቷና በብዙ ድካም ያገኟት ገንዘብ በሀገራችን ምንዛሬ በርክታ ከወዳጅ ዘመድ እጅ ስትገባ የስደት ሀገሩን ለምለምነት ትሰብካለች፡፡ በፎቶ ግራፍ ተቀርጾ የሚላከው በረጅሙ ወርኃ በረዶ ወቊር የገረጣ ፊት ሀገር ቤት ለሚኖረው ሰው የባዕድ አገር ሕይወትን ምቾት የሚሰብክ ነው የሚመስለው፡፡

በሀገራችን የዲዮስጶራ ሰርግ የሚባል አለ፡፡ የዲዮስጶራ ሰርግ አንድ ወይም ሁለቱ ተጋቢዎች ከውጭ መጥተው ጋብቻቸውን የሚፈጽሙበት ሰርግ ነው፡፡ ይህንን ሰርግ ልዩ የሚያደርገው /ሁሉም ማለት አይደለም/ ወጪው በእጅጉ የበዛ፤ የሰርጉ ታዳሚዎች እስከሚሰለቻቸው ድረስ መብል መጠጡና የመናፈሻው ሥርዓት የበዛ፣ ሙሽሮች የሚሞሸሩበት መኪናም ጭምር ከሰማይ የወረዱ እስከሚመስል ድረስ ለታዳሚ ዓይን ግራ የሚያጋባ፤ በጥቅሉ “የናጠጠ” ሰርግ መሆኑ ነው፡፡ ይህንን ያየ ወጣት ታዳሚ በሀገሩ በድሎት የሚኖርም ቢሆን እንኳ እሱም ባሕር ማዶ ተሻግሮ በመሥራት በልጽጎ በመመለስ በተመሳሳይ ሁኔታ ማግባትን ይመኛል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ የብዙዎች ዲዮስጶራ ተጋቢዎች የውጭ ሕይወት እዚህ መጥተው ሰርጋቸውን ድል ባለ ሁኔታ እንደደገሱለት አይደለም፡፡ ነገር ግን ያላቸውን ካሟጠጡ በኋላ ከሌላውም ተበድረው ድል ያደርጉታል፡፡ ይህ ከእውነታ ውጭ የሆነ የዲዮስጶራ ወገኖቻችንን የውጭ አገር ገለጻና ካላቸው በላይ ገንዘብ መርጨት ሲያዩና ሲሰሙ የቆዩ ወገኖች እነሱም ዕድሉን አግኝተው ሲሔዱ፤ ያ በርቀት የሳሉት የባዕድ ምድርና ሕይወት እንዳልጠበቁት ሆኖ ሲያገኙት ከፍተኛ የመንፈስ ስብራት ያጋጥማቸዋል፡፡

2. የገቡት ቃል
ኢትዮጵያውያን የስደት ሕይወት እንደጀመሩ ለከፍተኛ የመንፈስ ስብራት የሚዳርጋቸው ሌላው ምክንያት ሀገራቸውን ከመልቀቃቸው በፊት ለወዳጅ ዘመዳቸውና ጓደኛቸው ገብተውት የሚሔዱት ቃል ኪዳን ነው፡፡ ከላይ ባየነው መልኩ ወደ ውጭ እንደሔዱ በገንዘብ ባሕር ላይ የሚሰጥሙ ይመስላቸውና ለቪዛው ፕሮሰስና ለትራንስፖርት እንደሁም ለሽኝት ድግስ ብዙ ብር ይበደራሉ፡፡ ወደውጭ ለሚሔድ የሚያበድር አይጠፋምና፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አብረዋቸው ሲቸገሩ ለኖሩት ወላጆቻቸውና ዘመዶቻቸው ከፍተኛ የዕርዳታ ተስፋ ይሰጣሉ፡፡

ይሁን እንጂ ብዙ ጊዜ እንደሚታየው የስደት ሕይወት እንደተጀመረ ከተሻለ ኑሮ ላይ አያፈናጥጥም፡፡ ተሰዳጁ ሥራ ያዘም አልያዘ ከገባበት ቀን ጀምሮ ውጭ ስላለው ሕይወት አስቀድሞ በመረዳት ራስን አሸንፎ መሠረት ለማስያዝ ረጅም ጊዜ ይወስዳል፡፡ በዚህ ስደት ተሰዳጁ ሀገሩ ትቶት የመጣውን ቃልኪዳን እያሰበ፤ አብረውት ሲቸገሩ የነበሩ ቤተሰቦቹን ጉጉትና ጠኔ በሕሊናው እየሳለ ይጎዳል፡፡ ጉዳቱም የመንፈስ ስብራት ይሆንና ሠርቶ ሊያገኝበት ከሀገሩ ይዞት የሔደው ጉልበት እየደከመ በሽታ ላይ ይወድቃል፡፡ ይህ ጉዳት እንዲደርስበት ያልፈለገ ደግሞ ገንዘብን በአቋራጭ ለማግኘት ሲል ኢትዮጵያዊ መልኩና የሀገሩ ሕግ በማይፈቅድለት ተግባር ተሠማርቶ የባሰ ችግር ላይ ይወድቃል፡፡

3. አለመዘጋጀት
እንኳን ለቀዋሚ ኑሮ ይቅርና ለጊዜያዊ ዕረፍት ወይም ሥራ የሚደረግ ጉዞ ከፍተኛ ዝግጅትን ይጠይቃል፡፡ ከዝግጅቶቹ ውስጥ ስለሚሔዱበት ሀገር ባሕል፣ ቋንቋና አሠራር ማወቅ መሠረታዊ ጉዳይ ነው፡፡ ብዙ ጊዜ እንደሚታየው በርካታ ወገኖቻችን ወደ ውጭ የመሔድ ዕድል ሲያጋጥማቸው፤ ለራሳቸውና በዚያ ለሚያገኟቸው ዘመ ዶች የሚያካፍሉት ሽሮና በርበሬ እየሸ ከፉ በአውሮፕላን ገብተው የሚበሩባትን ቀን በጉጉት ከመጠበቅ ባለፈ ሁኔታ ዝግጅት አያደርጉም፡፡ በዚህም የተነሣ እንደሔዱ ከፍተኛ ድንጋጤና ሥነ ልቡናዊ ጫና ውስጥ ይገባሉ፡፡ ሥራ ለመፈለግ የሀገሩን ቋንቋ በሚገባ አላወቁም፣ በነጻነት ለመንቀሳቀስ አስቀ ድመው ስለሀገሩ አነዋወርና ሕግ አላጠኑም፡፡ ይህ ዓይነት ችግር በተለይ ኢትዮጵያውያን በማይበዙባቸው ሀገራት ጎልቶ ይታያል፡፡

ኑሮአቸውን በስደት የሚጀምሩ ወገኖች ለወዲያው ለሚያጋጥማቸው የሕሊና ስብራት ምክንያቶቹ እነዚህ ብቻ አይደሉም፡፡ ለአብነት ያህል ከተጠቁሱት የምንገነዘበው ግን የስደት ሕይወት ሀገር ላይ ተቀምጦ እንደሚያስ ቡት የተመቻቸ /የተደላደለ/ እንዳልሆነና የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶች እንዳሉ በመረዳት ተዘጋጅቶ መሔድ እንደሚገባ ነው፡፡ በሚቀጥለው ዕትም በተለይ የስደት ሕይወትን የሚመሩ ወገኖች ከሚደርስባቸው ሥነ ልቡናዊ ስብራት ለመታደግ በዚያ ካለችው ቤተ ክርስቲያንና ምእመናኗ ምን ይጠበቃል) የሚለውን እንመለከታለን፡፡ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያላችሁ ምእመናን የሕይወት ተሞክሯችሁንና ለሌላው ትምህርት ይሆናል የምትሉትን በዝግጅት ክፍሉ የስልክና የፖስታ ሳጥን ቁጥር፣ በኢሜይል እንዲሁም በአካል እየመጣችሁ እንድታደርሱን በአክብሮት እንጋብዛለን፡፡

መፍትሔዎች፡-

  1. በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ስለሚኖሩበት ምድርና ሕይወት ሳይጨምሩና ሳይቀንሱ እውነቱን በአገር ቤት ለሚኖሩ ወዳጅ ዘመዶቻቸው ይግለጹ፡፡ ሥራ ለማግኘት ምን ያህል ርቀት እንደሚጓዙ፣ ከብዙ ድካም በኋላ ስለሚያገኙት ገንዘብ፣ በወር ስለሚሸፍኑት ቢል ብዛት፤ ስለአየር ጠባዩ፣ ስለ አሠሪና ሥራ ግንኙነት፣ ስለ ቤተሰብ ሕይወት ወዘተ. . . በግልጽ ቢናገሩ ወገኖቻችን በመጓጓትና ትልቅ ነገርን በመጠበቅ ሔደው ከመደንገጥ፣ ከበሽታ ነጻ ይሆናሉ፡፡

  2. በተለያየ ምክንያት ሀገራቸውን ለቀው የሚሔዱ ሰዎች በተቻላቸው መጠን የሚሔዱበትን ሀገር እንደሀገራቸው ሁሉ የራሱ ተግዳሮት የሌሉት፣ ሁሉም ነገር አልጋ በአልጋ እንደሆነ አድርገው መሣል የለባቸውም፡፡ ይህንን ካደረጉ ለቀሪ ዘመዶቻቸው የሚገቡት ቃል አይኖርም፡፡ ቢኖርም ሊያጋጥም የሚችለውን ተግዳሮት ግንዛቤ ውስጥ የከተተ ይሆናል፡፡

  3. ኑሮአቸውን በባዕድ ምድር ለማድረግ ወስነው የሚሔዱ ወገኖች አስቀድሞ ልዩ ልዩ ዝግጅቶችን ማድ ረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ እዚያ ሲሔዱ ከሚበሉትና ከሚጠጡት በተጨማሪ ሀገሩ ምን ዓይነት የአየር ጠባይ አለው) ቋንቋውን በሚገባ አውቀዋለሁን) ሕግጋቱና የአነዋወር ይትበሃሉ ሁሉ ምን ይመስላል) ወዘተ ለሚሉት ጥያቄዎች በቂ ምላሽ መያዝ /ማዘጋጀት/ ይገባቸዋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር  

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት 17 ከግንቦት 16-30 ቀን 2005 ዓ.ም.

ጰራቅሊጦስ (ለሕፃናት)

ሰኔ 14 ቀን 2005 ዓ.ም.

በቤካ ፋንታ

 

  • እግዚአብሔር የሠራት ቀን ይህች ናት/ መዝ 118፥24/

ይህች ታላቅ ዕለት  ከቅድስት ሥላሴ አንዱ አካል የሆነው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለቅዱሳን ሐዋርያት፣ ለቅዱሳን አርድእትና ለቅዱሳት ሴቶች የተገለጠባት ዕለት ናት፡፡    እነዚህ ሁሉ በጸሎት ተግተው በሚጸልዩበት ወራት መንፈስ ቅዱስ  በተከፋፈሉ የእሳት ልሳን አምሳል የወረደበት ቅዱስ ቀን ነው፡፡

አስቀድሞ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያት ደብረ ዘይት በተባለ ታላቅ ተራራ ላይ ሳሉ እንዲህ ብሎ አስተምሯቸው ነበር “ኀይልን ከላይ ከአርያም እስክልክላችሁ ድረስ በኢየሩሳሌም በጸሎት ቆዩ፡፡”/ሉቃ 24፡36/ መቶ ሃያው ቤተሰብም በኢየሩሳሌም ሀገር በምትገኝ በቤተ መቅደስ በአንድነት ሆነው በጸሎት በመትጋት ቆዩ፡፡ ልጆችዬ መቶ ሃያው ቤተሰብ የሚባሉት 12ቱ ሐዋርያት፣ 72ቱ አርድእት/አገልጋዮች/ እና 36ቱ ቅዱሳን አንስት/ሴቶች/ ናቸው፡፡

ከዕርገት በኋላ በአሥረኛው ቀን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሐዋርያት ወዳሉበት፣ በጸሎትና በምሥጋና ወደ ሚተጉበት ሥፍራ በእሳት አምሳል /ምሳሌ/ ወርዶ በእያንዳንዳቸው ላይ ተቀመጠባቸው፡፡ ይሄንንም  ሁኔታ ተከትሎ  ምስጢር ተገለጠላቸው፣ ይፈሩ የነበሩት ሐዋርያትም ወንጌልን ለማስተማር ደፋሮች ሆኑ፣ በተለያየ ቋንቋዎች እንዲናገሩ እውቀት ተሰጣቸው፤ የእግዚአብሔርንም ጸጋ ተቀበሉ፡፡ ይህንን ታላቅ ኀይል እና ሰማያዊ ስጦታን የሰጣቸውን እግዚአብሔርን በታላቅ ዝማሬና እልልታ አመሰገኑት፡፡

በዓለ ሃምሳ የሚባለውን የአይሁድን በዓል ለማክበር ከተለያዩ ሀገራት የመጡ በጊዜው  የነበሩ ቁጥራቸው በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ  ሰዎች የሐዋርያቱን ታላቅ የዝማሬና የእልልታ ድምፅ ሰሙ፡፡ ከመቶ ሃያው ቤተሰብ መካከል አንዱ የሆነው  ቅዱስ ጴጥሮስ የተሰበሰቡት ሁሉም እንዲሰሙት ድምፁን ከፍ አድርጎ ቃለ እግዚአብሔርን እንዲህ ብሎ አስተማራቸው፡፡ “እናንተ የእስራኤል ሰዎች ሆይ እኛን የሰው ልጆችን ለማዳን እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ወደ ምድር መጥቶ ከክፉ ሥራ ተመለሱ፣ ኀጢአትን አታድርጉ፣ በቅድስና ኑሩ፣ ወደ እኔም ተመለሱ ቢላችሁ፤ እናንተ ግን ምንም በደል ሳይኖርበት ገረፋችሁት፣ አንገላታችሁት፣ በመስቀል ላይም ሰቀላችሁት፡፡ እርሱ ግን እግዚአብሔር ነውና ሞትን ድል አድርጎ ተነሣ፡፡ እርሱ ግን አሁንም ይቅር ባይ ነውና ከኀጢአታችሁ ተመለሱ ንስሐም ግቡ ፡፡” በማለት አስተማራቸው፡፡

የተሰበሰቡት ሰዎች ሁሉ ተገረሙ፡፡ ምክንያቱም ሐዋርያት በፊት የሚያውቁት አንድ ቋንቋ ብቻ ነበረ፡፡ በዚህ ሰዓት ግን ሰባ ሁለት ቋንቋን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ገልጦላቸው ለሁሉም በየቋንቋቸው አስተማሯቸው፡፡ ይህንንም ድንቅ ተአምር ከተመለከቱት ብዙዎች እግዚአብሔርን አመሰገኑት፡፡ ወደ ሐዋርያትም ቀርበው “አባቶቻችን እናንተ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ናችሁና ምከሩን፡፡ እንደ እናንተ የእግዚአብሔር ልጆች እንድንሆንና በቅድስና እንድንኖር ምን እናድርግ?”በማለት ጠየቁ፡ በዚያች ቀን ቁጥራቸው  ሦስት ሺ ያህል ሰዎች በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት አምነው  ክርስቲያን ለመሆን ቀረቡ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም እንዲህ አላቸው፡፡ “እነሆ ሁላችሁም ንስሐ ግቡ፡፡ በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምናችሁ ተጠመቁ፡፡” አላቸው በዚያው ዕለትም ሦስት ሺ ሰዎች ወደ ሐዋርያት በመቅረብ ኀጢአታቸውን ተናገሩ፤ ሐዋርያትም እግዚአብሔር ይፍታችሁ እያሉ ልጅነትን የሚያሰጣቸውን ጥምቀት አጠመቁዋቸው፡፡

ከዚያ ቀን ጀምሮም በየዓመቱ ይህችን ታላቅ የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን የምትባለውን በዓለ ጰራቅሊጦስን ክርስቲያኖች በታላቅ ደስታና ምሥጋና እናከብራታለን፡፡ እናንተም ልጆችዬ እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት በቤተ ክርስቲያን ተገኝታችሁ ቅዳሴ በማስቀደስ፣ መዝሙር በመዘመር እና በመጸለይ ይህችን ታላቅ በዓል ልታከብሯት ይገባል፡፡

የእግዚአብሔር አብ ጸጋ የእግዚአብሔር ወልድ ቸርነት የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አንድነት ከሁላችን ጋር ይሁን  አሜን፡፡

በባዕድ ምድር እስከመቼ?

ሰኔ 14 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ

የስምዐ ጽድቅ ዝግጅት ክፍል በዝርወት ለሚኖሩት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች የእናት ቤተ ክርስቲያናቸውን አስተምህሮ፣ ምክርና ተግሳጽ ይሰሙ ዘንድ ዓምድ በከፈተላቸው ጊዜ፤ መጀመሪያ ወዲያውም ዓምዱን ማስተዋወቂያ  ቢሆን ብዬ የጻፍኩት ጽሑፍ ዐራት እትሞች ዘልቆ ተፈጸመ፡፡ ጽሑፉን አስመልክቶ ከተለያዩ ጓደኞቼ ካገኘሁአቸው አስተያየቶች በመነሣት እንደ አብርሃም ሁሉ የያዕቆብን የስደት ሕይወት በመመርመር ለዛሬዎቹ ስዱዳን አርኣያ በሚኾን መልኩ በአጭሩ ለማቅረብ መረጥኩ፡፡ ጽሑፉ ይኸውና፡፡ በዚሁ አጋጣሚ ግን ኑሮአቸውን በስደት ያደረጉ ወንድሞችና እኅቶች ዕለት ከዕለት ከሚያጋጥማቸው ችግር በመነሣት ጽሑፎችን አዘጋጅተው ወደ ዝግጅት ክፍሉ በመላክ ቢማማሩ መልካም ነው፡፡

ሕይወተ ያዕቆብ
ከአያቱ አብርሃምና አባቱ ይስሐቅ ቀጥሎ ሦስተኛው የሕዝበ እስራኤል አባት /3rd Patriarch/ ተብሎ የሚታወቀው ያዕቆብ ወላጆቹ ይስሐቅና ርብቃ በጋብቻ በተጣመሩ ሃያኛው ዓመት ላይ ተወለደ፡፡ እሱ ሲወለድ አባቱ የ60 ዓመት ጎልማሳ ነበር፡፡ /ዘፍ. 25ሚ20፤ 25ሚ26/፡፡ ይስሐቅና ርብቃ በሃያ ዓመት የጋብቻ ሕይወታቸው ወልደው ለመሳም አልታደሉም ነበር፡፡ በዚህ የተነሣም የአብራካቸው ክፋይ የሆነ ፍሬ ይሰጣቸው ዘንድ አምላክን ይማጸኑ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ጩኸታቸውን ሰምቶ በርብቃ ማኅፀን ያዕቆብና መንትያው ኤሳው ተፀነሱ፡፡ ነገር ግን በልመናና በጩኸት የተፀነሱት ያዕቆብና ኤሳው ገና በማኅፀን ውስጥ ሳሉ እየተገፋፉ እናታቸውን ይሠቃዩ ጀመር፡፡ በዚህ የተሠቃየችው ርብቃ እንደ ገና ፅንሱን ወደ ሰጣት አምላክ ምሕረትን በመለመን ጮኸች፡፡ በዚህ ጊዜ በማኅፀኗ የተቀረጹ ልጆቿ እስከሚወለዱና ከተወለዱም በኋላ ዕድሜ ልካቸውን የሚጣሉና አንዱ በሌላው ላይ እየተነሣ እንደሚጥለው በራእይ ተረዳች፡፡ ይህንን ምስጢር በልቡናዋ ያዘችው እንጂ ለባሏ አልነገረችውም ነበር፡፡ ሕፃናቱ ሲወለዱ እንደተነገረው ትንቢት አንዱ ከሌላው የማይመሳሰል ሆነው ተወለዱ፡፡ በኲሩ ዔሳው እንደ ጽጌረዳ አበባ ሰውነቱ ሁሉ ቀይና ጸጉራም ሆኖ፣ በኋላ የተወለደው ያዕቆብም የወንድሙ የዔሳውን እግር ይዞ ወደዚህ ዓለም መጡ፡፡ የኋለኛው በዚህ ግብሩ ያዕቆብ ተብሏል፡፡

 

ያዕቆብ ብሂል አኀዜ ሰኰና አዕቃፄ ሰኰና ማለት ነው፤ ሲያድጉም ዔሳው የበረሃ ሰው አርበኛ አዳኝ ሲሆን ያዕቆብ ግን ጭምት ሰው ነበር፤ በድንኳንም ይቀመጥ ነበር፡፡ ዔሳው አድኖ በሚያመጣለት ምግብ የተነሣ የአባቱን ከፍ ያለ ፍቅር ሲያገኝ ያዕቆብ ደግሞ ከቤት ውሎ እናቱን ስለሚያጫውትና ስለሚታዘዛት የእናቱን ከፍ ያለ ፍቅር አገኘ፡፡ አባታቸው ይስሐቅ በእርጅና ምክንያት ጉልበቱ ደክሞ ዓይኑ ደግድጎ ከቤት በዋለ ጊዜ አንድ ቀን የሚወደውን ልጁን ዔሳውን እኔ እንደ ምወደው አድርገህ የምበላው አዘጋጅተህ እበላ ዘንድ ሳልሞት ሰውነቴ /ነፍሴ/ እንድትመርቅህ /እንድትባርክህ/ ወደ ዱር ሄደህ አድነህ አምጣልኝ አለው፡፡ ይህንን የሰማች ርብቃም የምትወደውን ልጇን ያዕቆብን እንደ ዔሳው አስመስላ አልብሳ አባቱ ይስሐቅ የጠየቀውን ምግብ እንደሚወደው አድርጋ አዘጋጅታለት ይዞ ወደ አባቱ እንዲገባና የአባቱን በረከት እንዲቀበል የምትችለውን ሁሉ በማድረግ አዘጋጀችው ዔሳውን መስሎ ወደ አባቱ በመግባትም የአባቱን በረከት ለመቀበል በቃ፡፡ በረከት በመቀበል እንደቀደመው የተረዳው ወንድሙ ዔሳውም “በጽድቅ ተሰምየ ያዕቆብ እስመ ፪ ጊዜ አዕቀጸኒ  ቀዳሚ ብኲርናየ ነሥዓኒ ወናሁ ዮምኒ ወዳግመ በረከትየ፤ ያዕቆብ በእውነት ስያሜውን አገኘ፡፡ አንደኛ ብኲርናዬን ሁለተኛ በረከቴን ወስዶብኛልና ሁለት ጊዜ አሰነካክሎኛ” በማለት ምሬቱን ገልጿል፡፡ /ዘፍ.27፥6/ ያም ሆነ ይህ ሁሉም በፈቃደ እግዚአብሔር የተከናወነ ሆነ፡፡

ምክንያተ ስደቱ
ለያዕቆብ ስደት ምክንያት ከሆኑት ጉዳዮች አንዱ ትዳር ነው፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ አባቱ ይስሐቅ ያዕቆብን ጠርቶ መርቆ “ከከነዓን ሴቶች ልጆች ሚስት አታግባ፡፡ ተነሥተህ በጤግሮስና በኤፍራጥስ መካከል ወደሚኖር ወደ እናትህ አባት ወደ ባቱኤል ቤት ሒድ፡፡ ከናትህ ወንድም ከላባ ልጆች ሚስት አግባ ብሎ አዘዘው፡፡ ፈጣሪዬ ካንተ ጋራ በረድኤት ይኑር፡፡ ያክብርህ ያግንህ ያብዛህ፡፡ ብዙ የብዙ ወገን ያድርግልህ አለው፡፡ እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠውን ምድር ከነዓንን ትወርሳት ዘንድ የአባቴ የአብርሃምን በረከት ይስጥህ፡፡ ካንተ በኋላ ላሉ ለልጆችህም ይስጣቸው” አለው፡፡ /ዘፍ.28፥1-5/

ከያዕቆብ ሕይወት ምን እንማራለን?
ሀ. የእግዚአብሔርን ውለታ እያሰቡ ፍቅርን በሥራ መግለጽ
ያዕቆብ በስደት ሕይወቱ እግዚአብሔር በተለያዩ ጊዜያት እየተገለ ጠለት መክሮታል፤ አበረታቶታል፤ ሲያጠፋም ገሥጾታል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ያዕቆብ አባቱ ይስሐቅ “ከከነዓናውያን ሴቶች ልጆች ሚስት አታግባ፤ ተነሣና ወደ እናትህ አባት ወደ ባቱኤል ቤት ወደ ሁለቱ ወንዞች መካከል ሒድ፤ ከዚያም ከእናትህ ወንድም ከላባ ሴቶች ልጆች ሚስትን አግባ፡፡ ሁሉን የሚችል አምላክም ለብዙ ሕዝብ ጉባኤ እንድትሆን ይባርክህ ያፍራህ ያብዛህ ስደተኛ ሆነህ የተቀመጥህባትን እግዚአብሔርም ለአብርሃም የሰጣትን ምድር ትወርስ ዘንድ የአብርሃምን በረከት ለአንተ ይስጥህ ለዘርህም እንዲሁ እንደ አን” ብሎ ምክር ያዘለ ትእዛዝ በሰጠው መሠረት ከቤርሳቤህ ተነሥቶ የርብቃ ወንድም ላባ ወደ ሚገኝበት በሁለቱ ወንዞች መካከል ወደምትገኝ ወደ ሶርያ ጉዞ ጀመረ፡፡ ሲጓዝ ውሎ ሎዛ ተብላ ትጠራ ከነበረች ቦታ ሲደርስ መሸበት፤ ደከመውም፡፡

 

በዚያውም ድንጋይ ተንተርሶ ተኛ፡፡ በሕልሙም መሰላል በምድር ላይ ተተክሎ ራሱም ወደ ሰማይ ደርሶ በመሰላሉም የእግዚአብሔር መላእክት ሲወጡበትና ሲወርዱበት ተመለከተ፡፡ በመሰላሉ ላይ የቆመው እግዚአብሔርም “የአባትህ የአብርሃም አምላክ የይስሐቅም አምላክ እኔ እግዚአብሔር ነኝ፤ ይህችን አንተ የተኛህባትን ምድር ለአንተም ለዘርህም እሰጣለሁ፤ ዘርህም እንደ ምድር አሸዋ ይሆናል፤ አሕዛብ ሁሉ በአንተ ይባረካሉ፤ ይከብራሉ፡፡ ያዕቆብን ያከበረ ያክብርህ እየተባባሉም ይመራረቃሉ፡፡ ካንተም በኋላ በልጅህ ይመራረቃሉ፡፡ በምትሔድበት መንገድ ሁሉ በረድኤት ጠብቄ ወደዚህ አገር እመልስሀለ” አለው፡፡ /ዘፍ.28፥13-ፍጻ/ 

ይህ አምላካዊ ቃል ኪዳን ከወላጅ ከዘመድ ተለይቶ የስደት ጉዞ ላይ ለነበረው ያዕቆብ ታላቅ ቃል ኪዳንና የምሥራች ነበር፡፡ በመሆኑም ያዕቆብ ይህንን ቃል ኪዳን ለሰጠው አምላክ ውለታውን እያሰበ ፍቅሩን ለመግለጽ ፈጣን ነበር፡፡ ያ ታላቅ ሕልም ያየበት ሌሊት ሲነጋ ተነሥቶ የእግዚአብሔር ስም ማስጠሪያ ይሆን ዘንድ ተንተርሶት ያደረውን ድንጋይ ወስዶ ሐውልት አድርጎ አቆመው፤ በላዩም ዘይት አፈሰሰበት፡፡ ስሙንም ቤቴል ብሎ ጠራው፤ ቤተ እግዚአብሔር ማለት ነው፡፡ በዚህም ብቻ አላበቃም፡፡ ስእለትም ተሳለ፡፡ “እግዚአብሔር በረድኤት ከኔ ጋራ ካለ በምሔድበትም ሀገር ሁሉ በረድኤት ከጠበቀኝ የዕለት ጉርስ ያመት ልብስ ከሰጠኝ ወደ አባቴም ቤት በደኅና ከመለሰኝ እግዚአብሔር ፈጣሪዬ ይሆንልኛል አለ፡፡ ፈጣሪውስ የግድ ፈጣሪው ነው እወደዋለሁ አመልከዋለሁ ሲል ነው፡፡ አንድም ይህን የሰጠኝ እግዚአብሔር አምላኬ ነው ማለት እሱን ብቻ አመልካለሁ ሌላ አላመልክም ማለት ነው፡፡ ይህችም የተከልኋት ደንጊያ የእግዚአብሔር ማደሪያ ትኾንልኛለች አለ፡፡ የሰጠኸኝን አሥራቱንም ሁሉ ላንተ ካሥር አንድ እሰጣለ“ አለ፡፡/ዘፍ.28፥20-ፍጻ/

በስደት በምንኖርበት ጊዜ እግዚአብሔር በተለያየ መንገድ የቸርነት ሥራውን ይሠራልናል፡፡ በበረከቱ ይጎበኘናል፡፡ በዚህ ጊዜ አባታችን ያዕቆብ እንዳደረገው ያንን ላደረገ እግዚአብሔር ውለታውን መክፈል ባይቻልም ፍቅራችንን በሥራ ለመግለጽ የተጋን መሆን አለብን፡፡ በያለንበት ክፍለ ሀገር ስሙ የሚቀደስበት መንግሥቱ የሚሰበክበት አብያተ ክርስቲያናት እንዲታነጹ ማድረግ፤ በተቋቋመበት ቦታ የምንኖር ከሆነም እንዲጠናከሩ ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡ እግዚአብሔር አብዝቶ ከሚሰጠን በረከትም አሥራት ማውጣት ይኖርብናል፡፡          

ለ. በስደት ሕይወት ትዕግሥት ማድረግ
አባቱ የመከረውን ምክርና የሰጠውን ትእዛዝ በመቀበል ያዕቆብ ወደ ሶርያ ሔዶ የሕይወት ጓደኛውን ራሔልን ቢያገኝም እንዳሰበው አገር አቋርጦ የመጣላትን የትዳር አጋሩን ይዞ ወደ አገሩ በቶሎ መመለስ አልቻለም፡፡ ይልቁንም አባቷ ላባ ባስቀመጠው ቅድመ ሁኔታ መሠረት ለሰባት ዓመታት የበግ ጠባቂው ሆኖ ሲያገለግል ቆይቷል፡፡ ከተሰደደ በኋላ አይቶ የወደዳትን ራሔልን በእጁ ያስገባ ዘንድ ሰባቱን ዓመት አገልጋይ ሆኖ የቆየው ያዕቆብ የተሰጠውን የጊዜ ገደብ ጨርሶ ልሂድ ብሎ ሲነሣ የራሔል አባት አልፈቀደለትም፡፡ ራሔልን ይዞ ለመሔድ ከፈለገ ሌላ ሰባት ዓመታትን እያገለገለ መቆየት እንዳለበት ነገረው፡፡ ያዕቆብ በተገባለት ቃል መሠረት ሰባት ዓመት ሲጠናቀቅ መሔድ ባለመቻሉ ቢያዝንም የመጣበት ዓላማ ግድ ይለዋልና ሌላ ሰባት ዓመታት ጨመረ፡፡ የእናቱ ፍቅር የወንድሙን የዔሳውን ብኲርናና ምርቃት መውሰድ እስኪያስችለው በፍቅርና በክብካቤ ያደገው ያዕቆብ ለ14 ዓመታት በግ ጠባቂ እረኛ ሆኖ በቀን ፀሐይና በሌሊት ቊር ሲሠቃይ ቢቆይም ተስፋ በመቁረጥ ተማሮ ወደ እናቱ አልሔደም፡፡ እርጅና ተጫጭኖት ሞት አፋፍ ላይ ሳለ ትቶት የመጣው አባቱ አሳስቦትና ናፍቆት ልሒድ አላለም ዓላማውን ማሳካት ነበረበትና በትዕግሥት ቆየ፡፡

ዛሬ በልዩ ልዩ ምክንያት በስደት የምንኖር ወገኖች ተወልደን ያደግንበ ትን ሀገርና ባሕል ትተን ስንመጣ ይነስም ይብዛ ይዘነው የመጣነው ዓላማ አለን፡፡ ይሁን እንጂ በስደት ሕይወት በሚያጋጥሙን ችግሮች የተነሣ ከዓላማችን የምናፈነግጥ ቁጥራችን ቀላል አይደለም፡፡ ብዙ ሰዎች እንደዚህ ዓይነት ችግር ውስጥ የሚገቡት በዋናነት በሁለት ምክንያት ነው፡፡ የመጀመሪያው ሲመጡ በአዕምሮአቸው ሥለውት የመጡት ነገርና ሲደርሱ የሚያጋጥማቸው የተለያየ መሆን ነው፡፡ ሲመጡ ውጭ አገር ገንዘብ በቀላሉ የሚታፈስ እንደሆነ አስበው ይመጡና ካሰቡት ቦታ ደርሰው ሲያዩት እንዳሰቡት ሳይሆን ሲቀር ይደናገጡና ከሀገራቸው የወጡበትን ቀን ይረግማሉ፡፡ ተስፋም ቆርጠው ሕይወታቸውን በአግባቡ መምራት ይሳናቸዋል፡፡

ነገር ግን ከአባታችን ከያዕቆብ የስደት ሕይወት የምንማረው ከዚህ የተለየ ነው፡፡ አባቱ ተነሥተህ ወደ ወገኔ ሒድና ሚስት የምትሆንህን ይዘህ ና ሲለው ምናልባት በወጣትነት አእምሮው እንደ ደረሰ በዓይኑ ዐይቶ የፈቀዳትንና የወደዳትን ይዞ እንደሚመለስ አስቦ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ሶርያ ሲደርስ ያጋጠመው ሌላ ነገር ነው፤ የ14 ዓመታት የእረኝነት ሕይወት፡፡ ይሁን እንጂ በዚያ ደንግጦ ወይም ተበሳጭቶ ወደ አገሬ ልመለስ አላለም፡፡ በዚያው ሲቆይም ዕለት ዕለት ሲበሳጭና ተስፋ ሲቆርጥ እንደነበረ መጽሐፍ አያስነብበንም፡፡ ስለዚህ በስደት ሕይወት ስንኖር ባልጠበቅነው ሁኔታ በሚያጋጥመን ችግር የተነሣ ሳንሳቀቅ ከሀገራችን ስንወጣ ይዘነው የወጣነውን ዓላማ አጽንተን ለስኬታማነቱ እየታገልን ልንኖር ያስፈልጋል፡፡ ያንን ያደረግን እንደሆነ ያዕቆብ ራሔልን ከነአገልጋዮቿ ይዞ አገሩ እንደገባ እኛም በዕውቀት በልጥገን በገንዘብ ከብረን አገራችን እንገባለን፡፡

ሌላው ምክንያት የወጡበትን ዓላማ በአግባቡ ለመረዳት አለመቻል ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ሰዎች ወደ ውጭ የሚወጡት በተረዳ ነገር ሰፍረው ቆጥረው በዕቅድ ያወጡትን ዓላማ ሳይዙ ነው፡፡ ያ ባለመሆኑም በስደት ሕይወታ ቸው በሚያጋጥማቸው ችግር በቀላሉ መደናገጥና መማረር ብሎም ተስፋ መቁረጥ ያጋጥማቸዋል፡፡ በስደት ሕይወት ይቅርና በየትኛውም ሕይወቱ ቢሆን ሰው የሚመራበት የሕይወት ዓላማ ያስፈልገዋል፡፡ ዓላማ የሌለውና ዓለማውን በአግባቡ ያለተረዳ ሰው በየመንገዱ በሚፈጠሩ ችግሮች /መሰና ክሎች/ በቀላሉ ለመውደቅ የተመቻቸ ይሆናል፡፡ ዓላማ ያለውና በአግባቡ ዓላማውን የተረዳ ሰው ግን በጥንካሬ የሚጓዝ፣ በቀላሉ የማይወድቅና ቢወድቅም ፈጥኖ የሚነሣ ሰው ነው፡፡ አባታችን ያዕቆብ ከሀገሩ የወጣበትን ዓላማ ያልተረዳ ቢሆን ኖሮ በፍጹም አስቦትና ሆኖት የማያውቀውን ሕይወት ለ14 ዓመታት ይቅርና ለ4 ቀናትም ቢሆን ታግሦ ሊቆይ አይችልም ነበር፡፡  

    
ሐ. ያሰቡትን ካገኙ በኋላ ወደ ተወለዱበት ሀገር መመለስ
ያዕቆብ ከ21 ዓመታት አገልግ ሎት በኋላ ራሔልን ሲያገኝ ራሔልንና በስደት ያጠራቀመውን ሀብት ይዞ ወደ ተወለደበት ሀገር ሊመለስ ወሰነ፡፡ ዓላማውን ካሳካ በኋላ በባዕድ ምድር ተጨማሪ ዓመታትን በባዕድነት መቆ የት አልፈለገም፡፡ ፈጣሪው እግዚአ ብሔርም ተመለስ አለው፡፡ /ዘፍ.31፥3/ እሱም ተመለሰ፡፡

ሰዎች በስደት ሕይወት ሲኖሩ ከሀገር ይዘውት የሚመጡት ግልጽና የጸና ዓላማ ሊኖር እንደሚገባ ሁሉ ዓላማቸውን ከግብ ካደረሱ በኋላ ሊኖር ስለሚገባው ሕይወት ማሰብ አግባብ ነው፡፡ በተለያዩ ቦታዎች ከሀገራቸው ከወጡ በኋላ ረጅም ጊዜ በስደት የኖሩ ሰዎች ዓላማቸውን ካሳኩ በኋላም ወደ ሀገራቸው ለመመለስ የማያስቡ ይኖራሉ፡፡ በእርግጥ ከእነዚህ ውስጥ ወደ ሀገራቸው እንዳይገቡ የሚያደርጓቸው በቂ ምክንያቶች የሚኖሯቸውም አይጠፉም፡፡

ዓላማን ከግብ ካደረሱ በኋላ ወደ ሀገር መመለሱ ለተመላሹ ከሚሰጠው የአእምሮ ዕረፍትና የተረጋጋ ሕይወት ባሻገር ከተመላሹ በሚገኘው ዕውቀት፣ ልምድ፣ ሀብትና ጥረት ወገንና ሀገር እንዲጠቀም ያስችላል፡፡ ያዕቆብ ዓላማውን ካሳካ በኋላ በመመለሱ ሕዝበ /ሀገረ/ እስራኤልን በአዕማድነት የመሠረቱ ልጆች ለማፍራት ችሏል፡፡

በዚህም ዘመን ሰፊ ራእይ ሰንቀን ሩቅ አልመን ወደተለያዩ ሀገሮች የተሰደድን ኢትዮጵያውያን በከፈልነው መሥዋዕትነትና በእግዚአብሔር አጋዥነት ዓላማችን ከተሳካልን በኋላ ወደ ሀገራችን ልንመለስ ያስፈልጋል፡፡ “ሠናይ ለብእሲ ለእመ ይከውን መቅበርቱ ውስተ ርስቱ፤ የሰው ሞቱ፤ መቃብሩም በሀገሩ /ርስቱ/ ቢሆን መልካም ነው“ እንደተባለ መመለስ የማያስችለን መሠረታዊ ችግር ከሌለ በስተቀር የተሰደድንበት ዓላማ ከተሳካ በኋላ በባዕድ ምድር ውሎ ከማደር ይልቅ ባካበትነው ቁሳዊና አእምሮአዊ ሀብት ሀገርንና ወገንን በመጥቀም ለመጠቀም ቤተሰብን ይዞ፤ ሀብትንም ሸክፎ ርስት ሆና ወደ ተሰጠችን ምድረ ኢትዮጵያ ለመግባት ማመንታት የለብንም፡፡ ያዕቆብን ተመለስ ብሎ ያዘዘው እግዚአብሔር ፈጣሪያችን ወደሀገራችን እንድንመለስ ፈቃዱ እንደሆነም እንረዳለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት 16 ከግንቦት 1-15 ቀን 2005 ዓ.ም.

ለማእከላት ጸሐፊዎችና ለማስተባበሪያ ሓላፊዎች ሥልጠና ተሰጠ

ሰኔ 13 ቀን 2005 ዓ.ም.

ታመነ ተ/ዮሐንስ

ሰኔ 1 እና 2 ቀን 2005 ዓ.ም በማኅበሩ ሥራ አመራርና አስፈጻሚ አካላት አወያይነት የማእከላት መደበኛ ጸሐፊዎች፣ መደበኛ መምህራንና የስድስቱ ማእከላት የማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊዎችን ያሳተፈ ሥልጠናና ውይይት ተካሔደ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የሀገር ውስጥ ማእከላትና ግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ሓላፊ የሆኑት ዲ/ን አንዱአምላክ ይበልጣል በስልጠናው መክፈቻ መርሐ ግብር ላይ በሰጡት ማብራሪያ ተሳታፊዎቹ ለማኅበሩ አገልግሎት ከፍተኛ ድርሻ ያላቸው በመሆናቸው በማኅበሩ የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ፕላን ዙሪያ ማወያየት ለአገልግሎቱ መቃናት አጋዥ የሆነ ሥልጠና መስጠት ተገቢ ሆኖ እንደተገኘ ገልጸዋል፡፡

በዚህም መሠረት በሙያው ልምድ ባላቸውና የማኅበሩ የልማት ተቋማት አስተዳደር ቦርድ አባል በሆኑት በአቶ መንክር ግርማ “Communication & team development” በሚል ርዕስ ሥልጠና የተሰጠ ሲሆን አባላቱ በቀጣይ የአገልግሎት ቆይታቸው ችግሮችን በምን ዓይነት ሁኔታ መፍታት እንዳለባቸው ግንዛቤ እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡

በተጨማሪም ማኅበሩ ያለበትን ነባራዊ ሁኔታ ማእከላቱ እንዲረዱ በማድረግ በዋነኝነት ያለባቸው የሥራ ሓላፊነት የስብከተ ወንጌል ማስፋፋትና ማጎልበት ስለሆነ ሰፊውን ጊዜ በስብከተ ወንጌል አገልግሎቱ ላይ ያሉ ችግሮችና መፍትሔዎቻቸው ዙሪያ ውይይትና የልምድ ልውውጥ ተካሒዷል፡፡  

 
በስልጠናው ላይ ከስድስቱ ማስተባበሪያ ማእከላት ሠላሳ አምስት ተሳታፊዎች ተገኝተዋል፡፡

 

ዕርገት(ለሕፃናት)

ሰኔ 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በአብርሃም ቸርነት/ዘገዳመ ኢየሱስ/

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በተነሣ በአርባኛው ቀን ቅዱሳን ሐዋርያት በጸሎት ይተጉ ወደነበረበት ቤት በመሄድ ደቀመዛሙርቱን ይዟቸው ከቤት በመውጣት መንገድ ጀመረ፡፡ እርሱ ከፊት ከፊት እየመራቸው እነርሱ እየተከተሉት ወደ ረጅሙና በረጃጅም ዛፎች ወደ ተሞወው ደብረ ዘይት ተራራ ይዟቸው ወጣ፡፡

በተራራው ጫፍ /አናት/ ላይ ሲደርሱ፤ በመካከላቸው ቆሞ ሐዋርያትን እንዲህ ብሎ መከራቸው “ከእኔ የተማራችሁትን ትምህርት ጠብቁ በቤተ ክርስቲያንም ጸንታችሁ ኀይልን ከሰማይ እስክልክላችሁ ቆዩ” ብሎ አዘዛቸው፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ አሥራ ሁለቱን ሐዋርያት እጁን በላያቸው ጭኖ (በአንብሮተ ዕድ) ሾማቸው፡፡

ይህንንም እየነገራቸው ከምድር ወደ ሰማይ ከፍ፣ ከፍ፣ ከፍ አለ፡፡ ነጭ የሆነችና ለዓይን በጣም የምታምር ብሩህ ደመናም አምላካችንን ተቀበለችው፡፡ ከዓይናቸውም እየራቀ፣ እየራቀ፣ ከእይታቸው ተሰወረባቸው፡፡
ሐዋርያትም ኢየሱስ ክርስቶስን በጣም ይወዱት ስለነበረ ሲለያቸው አዝነው አተኩረው ሰማይ ሰማዩን ለረጅም ሰዓት ተመለከቱ፡፡ ድንገትም ነጫጭ ልብስ የለበሱ ሁለት ቅዱሳን መላእክት በአጠገባቸው ቆመው ታዩአቸው፡፡ መላእክቱም ሐዋርያትን እንዲህ አሏቸው፡፡ “እናንተ የገሊላ ሰዎች ሆይ ወደ ሰማይ እያያችሁ ለምን አዝናችሁ ቆማችሁ፡፡ ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ ያረገው ኢየሱስ ከእናንተ ወደ ሰማይ ሲያርግ እንዳያችሁት እንዲሁ ዳግመኛ ወደ ምድር ይመጣል፡፡” አሏቸው፡፡

ሐዋርያቱም የመላእክቱን ማረጋጊያ ቃል ከሰሙ በኋላ ፈጥነው በኢየሩሳሌም ወደምትገኘው ቤተ መቅደስ በመሄድ እግዚአብሔር ቃል የገባላቸውን ኀይል ከሰማይ እንዲልክላቸው ቀን ከሌሊት በአንድነት ሆነው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምንም ከመካከላቸው አድርገው በጸሎት እየተጉ ቆዩ፡፡
ጥቅስ፡- ሉቃ.24፥50-53፣ ሐዋ.1፥9-14

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚታየውን የአሠራር ብልሹነት ማሰወገድ እንደሚገባ ተገለጸ

ሰኔ 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በትዕግሥት ታፈረ

በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ውስጥ የሚታየውን የአሠራር ብልሹነት ማሰወገድ እንደሚገባ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖትና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ገለጹ፡፡

ቅዱስነታቸው ይህንን የገለጹት በግንቦቱ ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ባስተላለፈው ውሳኔ መሠረት የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤ እንዲሁም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው የተመረጡት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ሓላፊዎችና ሠራተኞች ጋር ሰኔ 4 ቀን 2005 ዓ.ም. የትውውቅ መርሐ ግብር በተካሄደበት ወቅት ነው፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የወላይታና ዳውሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በትውውቅ መርሐ ግብሩ ላይ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል የሁሉም እገዛ እንደሚያስፈልግ የገለጹ ሲሆን “ለቤተ ክርስቲያናችን ተልእኮ ከተመረጥንና እንድናገለግል ከተጠራን አገልግሎታችን የተሻለ መሆን አለበት፡፡ የሚያዘን ሥርዓታችን፤ ፍቅራችንና ሕጋችን እንጂ ሥልጣናችን ሊሆን አይገባም፡፡ ሥልጣናችን የሚያዘን ከሆነ ሥራችን ሙሉ ሊሆን አይችልም፡፡ ትክክለኛ መሪን ማንም አይጠላም፤ መሪዎችን ተመሪዎች የሚጠሏቸው ከቆሙለት ዓላማና ተግባር ውጪ በአምባገነንነት፤ በጉቦኝነት፤ በዘረኝነት፤ በአድሏዊነት ሱስ ሲጠመዱ ተመሪዎች ያኮርፋሉ፤ ይጨነቃሉ፤ ማንንም ስለማያምኑ እንደ ቃየል ጥላቸው ያስደነግጣቸዋል፡፡  ስለዚህ ሀሰትን የምትጠየፉ፤ አሉባልታን የምትንቁ፤ ሥራን የምትወዱ፤ ሰላምን የምትናፍቁ፤ ፍቅር የምትላበሱ መሆን አለባችሁ፡፡ ወደፊት አብረን ስለምንጓዝ  እግዚአብሔር እንዲረዳን ቅድሰት ቤተ ክርስቲያናችንን አሳድገን እኛም ተረድተን ሌሎችን እንድንረዳ ያስፈልጋል” ብለዋል፡፡

በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሓፊ ሆነው የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በበኩላቸው ባደረጉት ንግግር “መሰባሰባችን መልካም ነው፡፡ ሁላችንም ግዴታችንን ከተወጣን ያለው ችግር ይወገዳል፡፡ በእውነተኞች ሰዎች ቸርነትና በጎነት አገር ትቀናለች፡፡ አገር ስትቀና ሰው ሁሉ በሰላም ይኖራል፡፡በኅብረት ሆነን ዘመኑን በመዋጀትና በመገምገም በትክክል ሥራችንን ከሠራን ይቃናልናል፡፡” በማለት ተናግረዋል፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነት አስተዳደርና ሠራተኞች እንዲሁም የተለያዩ የቤተ ክርስቲያኒቱ አካላት ሠራተኞች ችግሮች ናቸው ያሏቸውን አሳቦች ያቀረቡ ሲሆን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ወጥ የሆነ የአሠራር ዘዴ ያለመኖር፤ አለቆች በተለዋወጡ ቁጥር በሚመጣው ሰው ላይ ሠራተኛው ለመንጠልጠል የራሱን ዘዴ መቀየስ፤ በአሠራር ሥርዓቱ ሁሉም ሠራተኛ እኩል መመራት ያለመቻል፤ ሹማምንትን በመፍራት፤ በመስገድና በመሽቆጥቆጥ አማላጅ በመላክ የተሻለ ሥራ ለማግኘት ጥረት ማድረግ፤ ወዘተ. . . የሚሉት በሠራተኞቹ የተጠቀሱ ሲሆን ይህ አካሄድ በአስተዳደርና በስብከተ ወንጌል ተልእኮ ስኬታማ ጉዞ ላይ አሉታዊ ተጽእኖ እንደሚፈጥር በመግለጽ የአሠራር ዘዴ /System/ መዘርጋት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በሰጡት ቃለ ምእዳን “ቤተ ክርስቲያናችን ከጥንታዊያንና ከታሪካዊያን የዓለም አብያተ ክርስቲያናት አንዷና አንጋፋዋ መሆኗ የተረጋገጠላት ናት፡፡ ይህ ሊሆን የቻለው አባቶቻችን ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፤ ከሐዋርያትና  ከሊቃውንቱ ተረክበው ሕልውናዋንና ክብሯን ጠብቀው ስላስተላለፉልን ነው፡፡ እኛም ለሚቀጥለው ትውልድ ለማስተላለፍ ትልቅ ሓላፊነት ይጠብቀናል፡፡ ስለዚህ ጥንተ ቅድስናዋን፤ ንጽሕናዋንና ታሪኳን መመለስ አለብን፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በሃይማኖት እንከን የላትም፡፡ በአሁኑ ወቅት በአስተዳደር ጤነኛ አይደለችም፤ ብዙ ብልሹነት ይታያል፡፡ ለቤተ ክርስቲያናችን የማይስማሙ ነገሮች ወደ ቤተ ክርስቲያናችን ገብተው መንገዳችንን እያበላሹብን ነው፡፡ ሙስና፤ ዘረኝነትና ሌሎችም ክፉ ነገሮች ይታያሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የመልካም ሥራ መሪ እንድትሆን እንፈልጋለን፡፡ አስተማሪ እንጂ ተማሪ መሆን የለባትም፡፡ ሓላፊነት፤ ተጠያቂነት፤ እውነተኛነት፤ ሃቀኝነትና የሕግ የበላይነት የሰፈነባት መሆን ይገባታል፡፡” ብለዋል፡፡

ሰዋስወ ግእዝ

ሰኔ 13 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ት ኑኀሚን ዋቅጅራ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

በቅድሚያ በሕያውና ዘለዓለማዊ በሆነ በእግዚአብሔር ስም የከበረ ሰላምታዬን እያቀረብኩ ስለ ግእዝ ቋንቋ አጠር ባለ መልኩ እገልጻለሁ፡፡

የግእዝ ቋንቋ ቀዳማዊነት

ቋንቋ ማለት መግባቢያ መተዋወቂያ መነጋገሪያ አሳብ ለአሳብ መገላለጫ ወዘተ…… ማለት ነው፡፡ ሕዝብ ባለበት ቦታ ሁሉ ቋንቋ አለ፤ ቋንቋም ባለበት ቦታ ሕዝብ አለ፤ ያለ ሕዝብ ቋንቋ ያለ ቋንቋ ሕዝብ ሊኖር አይችልም፡፡ ይህን መነሻ በማድረግ ስለ ግእዝ ቋንቋ አመጣጥ አጠር ባለ መልኩ ስንነጋገር፡-

ከአንዳንድ ቀደምት የታሪክ ጸሐፊዎችና የግእዝ ቋንቋ መጻሕፍትን ጽፈው ካስረከቡን ቀደምት የቤተ ክርስቲያን አባቶችና የቋንቋው ባለቤቶች እንደምንረዳው፡- የግእዝ ቋንቋ አመጣጥ በኢትዮጵያ መነሻ ሊሆነን የሚችለው ከስምንተኛው ምዕተ ዓመት ቅድመ ልደት ክርስቶስ ጀምሮ ነገደ ሴም /የሴም ዘሮች/ወገኖች/ ቋንቋቸውን ይዘው ወደ ኢትዮጵያ ከመጡበት ጊዜ ጀምሮ ሴማዊ ቋንቋ በኢትዮጵያ ሀገራዊ ቋንቋ ሆነ፡፡ ነገደ ሴም ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣታቸው በፊት ቋንቋቸውን በመግባቢያነት አሳድገው፣ ሥነ ጽሑፋቸውን አስፋፍተው፣ በባቢሎን በአካድና፣ በአሶር ይኖሩ ነበር፡፡ በኋላ ግን ለሁለት ተከፍለው ግማሾቹ ሴማውያን ሰሜንና ምስራቅ እስያን፣ ግማሾቹ ሴማውያን ደግሞ ደቡቡ እስያን ይዘው ይኖሩ ነበር፡፡

የሰሜን እስያ ሴማውያን ቋንቋ /የአካድ ቋንቋ/ አማራይክ፣ ዕብራይስጥንና ፊንቄን ሲያስገኝ የደቡብ እስያ ሴማውያን ቋንቋም /አካድ ቋንቋ/ ሳባን ግእዝንና የተለያዩ በኢትዮጵያ ውስጥ በመግባቢያነት የምንጠቀምባቸውን ሴማውያን ቋንቋዎች አስግኝቷል፡፡ በደቡብ እስያ ይኖሩ የነበሩ ነገደ ሴም በተለያየ ምክንያት እየፈለሱ ወደ ደቡብ ዐረብ፣ ወደ የመንና ወደ አካባቢዋ መጥተዋል ከዝያም ፈልሰው ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት በአክሱምና በአካባቢዋ ሰፍረው ይዘዋቸው ከመጡት ቋንቋዎቻቸው መካከል በታሪክ ጎልተው የሚታወቁና አገልግሎት ሲሰጡ የነበሩትና በአሁኑ ሰዓትም በአገልግሎት ላይ የሚገኙት ቋንቋዎች የሳባ እና የግእዝ ቋንቋዎች ናቸው፡፡

ነገደ ሴም /ሴማውያን/ ቋንቋዎቻቸውን /ሳባና ግእዝን/ ከነገደ ካም ቋንቋ ጋር አስማምተው በመያዝ ሁሉንም ቋንቋዎች ሲናገሩዋቸው ኖረው ነበር፡፡ በኋላ ግን ሳባና ግእዝ እየተለመዱና እየተስፋፉ እየዳበሩም ከመሄዳቸው የተነሣ የነገደ ካምን ቋንቋ እየዋጡት መጥተው ሁለቱ ሳባ እና ግእዝ ቋንቋዎች ብቻ ሀገራዊ ቋንቋዎች ይሆኑ ጀመር እየቆዩ ግን ሁለቱ /ሳባና ግእዝ/ በጣም ተመሳሳይና ተቀራራቢ በመሆናቸው እንደ አንድ ቋንቋ ሆነው ይነገሩ ጀመር፡፡ ይኸም ጽሑፉ /ፊደሉ/ በሳባ እንዲጻፍ እና መነጋገሪያ ቋንቋውን ደግሞ በግእዝ እንዲሆን በመደረጉ ነው፡፡ ነገደ ሴም በሳባ ቋንቋቸው ሳባውያን፣ በግእዝ ቋንቋቸው ደግሞ አግአዝያን ተብለው የሚጠሩት ከዚህ መነሻነት ነበር፡፡

ለዚህም መረጃ የሚሆኑን ሳባና ግእዝ ቋንቋዎች ተጽፈውባቸው የሚገኙት ጥንታውያን የኢትዮጵያ ቅርሶች እንደ የአክሱምና የላሊበላ ሐውልቶች በየሐ እና በአዱልስ ወዘተ….. የተለያዩ በድንጋይ ላይ የተቀረጹ ጽሑፎችና ቅርጻ ቅርጾች እስከ አሁን ቆመው የሚገኙ የዚህ ቋሚና ግልጽ ማስረጃዎች ናቸው፡፡ የሳባና የግእዝ ቋንቋዎች በዚህ ሁኔታ እስከ 324 /፫፻፳ወ፬/ዓ.ም. አካባቢ ድረስ አብረው ሲነገሩ ቆይተዋል በኋላ ግን የሳባ ንቋ እየተዳከመና በግእዝ ቋንቋ እየተዋጠ ይሄድ ጀመር እንደ ምንም እየተንገዳገደ እስከ 350 /፫፻፶/ ዓ.ም. ቆይቶ ከዚህ በኋላ ከሥነ – ጽሑፍ ከመነጋገሪያነትም ፈጽሞ ቀረ የግእዝ ቋንቋ ግን ከ324 /፫፻፳ወ፬/ዓ.ም. ጀምሮ ብቸኛ ሀገራዊ ቋንቋ በመሆን እስከ ፲፪ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ማለትም የአማርኛ ቋንቋ ብሔራዊ ቋንቋ ሆኖ ሲያገለግል እንደ ነበር የታሪክ ጸሐፊዎች በግልጽ አስቀምጠውታል፡፡
፩.፪. የግእዝ ፊደላት አመጣጥ

ስለ ግእዝ ቋንቋ ስንነጋገር በመጀመሪያ ለማንኛውም ቋንቋ መሠረት ስለሚሆነው ስለ ፊደል አመጣጥ ማወቅ ተገቢ ነው፡፡ ስለ ፊደል አመጣጥ ሊቃውንት ብዙ ትንታኔ ይሰጡበታል ይኸውም ፊደል ማለት ጽሑፍ ነው ምክንያቱም “ፈደለ” ጻፈ ከሚለው ከግእዝ ቃል የወጣ ነው ይላሉ፡፡ ይሁን እንጂ “ፈደለ” የሚለውም ቃል የሦስት ፊደላት ጥምረት በመሆኑ እነዚህ ፊደላት ከየት እንደመጡ መነሻቸውን /ምንጫቸውን/ ማወቅ ተገቢ ነው፡፡

እንደ ቤተ ክርስቲያናችን ትምህርት ለዚህ በቂ የሆነ መረጃ እናገኛለን፡፡ የፊደል ስልት አንድም ቅርጽ የተጀመረው የአዳም ሦስተኛ ትውልድ በሆነው በነቢዩ በሄኖስ ዘመን ነው፡፡ ነቢዩ እግዚአብሔርን በማገልገል የታወቀ ደግ ስለ ነበር ለደግነቱ መታወቂያ /መታሰቢያ/ ይሆነው ዘንድ በእግዚአብሔር ፈቃድ የሕግ ማሰሪያ የሚሆነውን ፊደል በጸፍጸፈ ሰማይ /በሰማይ ገበታነት/ ተገልጦ ታይቶታል፡፡

ስለዚህ የፊደል ቅርጽ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ለሥነ-ጽሑፍ በር መክፈቻ በማድረግ ተጠቅመውበታል፡፡ መጠሪያ ስሙንም ጽሑፍ ለማለት ፊደል ብለውታል፡፡ ይኸስ እውነትነቱ ምን ያህል ያገለግላል ቢሉ በዚያን ጊዜም በጸፍጸፍ ሰማይ ታየ የሚባለው ፊደል የእብራይስጥ ፊደል እኛ አሁን አሌፉት እያልን የምንጠራው ነው፡፡

ስለዚህ ይህ ፊደል ከፊደልነት ጥቅሙ ጋር እንደ ኅቡዕ ስም ይገመታል /ይታመናል/ ምክንያቱም የእያንዳንዱ ፊደል ትርጒም ከእግዚአብሔር ህልውና እና እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ካደረጋቸው የቸርነት ሥራዎች ጋር የተዛመደ ትርጒም ስለሚሰጥ (ስለአለው) ነው፡፡ ይህ እውነታ እና የስም አጠራር ትርጒም ግን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት አባቶች የፊደላት ትርጒም አሰጣጥ ላይ በግልጽ ተጽፎ የሚገኝ ነው /ጥንታዊ የኢትዮጵያ ትምህርት በሊቀ ሥልጣናት ሀብተ ማርያም ወርቅነህ/ በተጻፈው መጽሐፍ በግልጽ እንረዳዋለን ይህን መነሻ በማድረግ የሥነ-ጽሑፋችን በር መክፈቻ የአሌፋቶችን ስም ፊደል የሚል ስያሜ በመስጠት እንጠቀምበታለን፡- ስለዚህ ማንኛውንም ነገር ለመጻፍ ለመጪውም ትውልድ ለማስተላለፍ በጽሑፍ መቀረጽ ስላለበትና ራሱ ፊደሉ የሥነ-ጽሑፍ መጀመሪያ ስለሆነ ጽሑፍ ለማለት ፊደል ተብሎ ተጠርቷል፡፡

ለዚህም የቤተ ክርስቲያን  አባቶች ሊቃውንት አጽንዖት ሰጥተው ሲያስቀምጡት “ዘእንበለ ፊደል ኢይትነገር ወንጌል” ይላሉ ይህ ማለት ወንጌል ሳይቀር የሚጻፈው /የሚተረጎመው/ በፊደል አማካኝነት ነው፡፡ ከዚህም ሌላ ስለ ፈደል ጠቃሚነት የሚሰጡትን ሐተታዎች ከብዙ በጥቂቱ እንመልከት፡-

፩. ፊደል- ብሒል ነቅዓ ጥበብ ውእቱ፡፡

ፊደል የአእምሮ መገመቻ የምሥጢር መመልከቻ ነው ምክንያቱም ያለ ፊደል ምንም አይታወቅምና ፡፡

፪. ፊደል – ብሂል ነቅዓ ጥበብ ውእቱ፡፡

ፊደል የጥበብ ሁሉ መገኛ ምንጭ ነው፡፡

፫. ፊደል – ብሂል መራሔ ዕውር ውእቱ፡፡

ፊደል የእውር መሪ ነው፤ ምክንያቱም ሰውን ሁሉ ከድንቂርና አውጥቶ ወደ ብርሃን ይመራልና፡፡

፬. ፊደል – ብሂል ጸያሔ ፍኖት ውእቱ፡፡

ፊደል ማለት መንገድ ጠራጊ ነው፤ ምክንያቱም አላዋቂነትን /ድንቁርናን/ ከሰው ልጅ ጠርጎ /አጽድቶ/ ከፍጹም ዕውቀት ያደርሳልና፡፡

፭. ፊደል ብሂል -ርእሰ መጻሕፍት ውእቱ፡፡

ፊደል ማለት የመጻሕፍት ሁሉ ራስ /አናት/ ነው ምክንያቱም ያለ ፊደል ምንም ነገር መጻፍ አይቻልምና፤ /ኢተወልደ መጽሐፍ ዘእንበሌሁ ለፊደል/ ያለ ፊደል ምንም ነገር ሊጻፍ አይቻልምና

የግእዝ ቋንቋ ከሴማውያን ፊደሎች መካከል አንዱና ዋናው ጥንታዊ ቋንቋ ስለሆነ፣ የራሱ የሆነ ብዙ ቃላትን ከነፍቺዎቻቸው ይዞ ይገኛል፡፡ ከዚህ አንጻር ፊደል የማንኛውም ጽሑፍ መነሻ ስለሆነ፣ ጽሑፍ ብሎ ለመጥራት መጠሪያውን ፊደል ብለውታል፡፡ በአጠቃላይ ቋንቋ እንደ ማንኛውም ቋንቋ የራሱ የሆነ የአጻጻፍን ሥልትና ቅርጽ የተከተለ ጥንታዊና መሠረታዊ ቋንቋ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

ይቆየን