በስልታዊ ዕቅድ ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ተሰጠ

ታኅሣሥ 22 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ


ማኅበረ ቅዱሳን ከ2005 ዓ.ም – 2008 ዓ.ም ድረስ የሚተገበረውን የ4 ዓመት ስልታዊ ዕቅድ ዙሪያ በ6 ማእከላት ማስተባበሪያ አማካኝነት ለሁሉም ማእከላት የግንዛቤ ማስጨበጫ ምክክር መሰጠቱ ተገለጸ፡፡

ዲ/ን አንዱአምላክ ይበልጣል የሀገር ውስጥ ማእከላትና ግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ክፍል ሓላፊና ምክትል ዋና ጸሐፊ እንደተናገሩት መቀመጫቸው ባሕር ዳር፣ መቀሌ፣ ጅማ፣ ሓዋሳ፣ ድሬደዋና አዲስ አበባ ላይ በሆኑ 6 የማእከላት ማስተባበሪያ ቢሮዎች አማካኝነት ለሁለት ቀናት በስልታዊ ዕቅድ ወሳኝ ጉዳዮች፣ ዓላማ፣ ግቦችና ስልቶች ላይ የግንዛቤ ማስጨበጫ የተሰጠ ሲሆን በሀገር ውስጥ ባሉ 44 ማእከላት የማእከላቱ ድርሻ ላይ ምክክር ተደርጓል ብለዋል፡፡

 

የስልታዊ ዕቅድ የግንዛቤ ማስጨበጫውን ተከትሎም የአባላት አሳብ መስጫ፣ ቅሬታ አቀራረብና አፈታት ሥርዓትና የግንዛቤ ምክክርና የግቢ ጉባኤያት የገንዘብና የንብረት አጠቃቀም መመሪያ ላይ ውይይት ተደርጓልም በማለት ተናግረዋል፡፡

 

ለሁለት ቀናት በተደረገው የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብር ላይ 44 ማእከላት የ6ቱ የማእከላት ማስተባበሪያ አማካኝነት ሁለት ተወካዮች የተገኙ ሲሆን ማኅበረ ቅዱሳን ከጥር 1 ቀን 2005 ዓ.ም በአዲሱ ስልታዊ ዕቅድ አገልግሎቱን እንደሚጀምር ዲ/ን አንዱአምላክ አስረድተዋል፡፡

ST. Gebreale

እኛ የምናመልከው አምላክ ኪሚነደው ከእሳቱ እቶን ያድነን ዘንድ ይችላል፡፡ ት.ዳን.3፥17

ታኅሣሥ 18 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ኀይለ ኢየሱስ ቢያ

 

ST. Gebrealeንጉሡ ናቡከደነጾር በዱራ ሜዳ ላቆምኩት የወርቅ ምስል ካልሰገዳችሁ ከእጄ የሚያድናችሁ አምላክ ማን ነው? ብሎ በኀይልና በዛቻ በጠየቃቸው ጊዜ ሠለስቱ ደቂቅ በልበ ሙሉነት፥ በፍጹም እምነት፥ መልስ የሰጡበት ኀይለ ቃል ነው፡፡ ከኀይለ ቃሉ ቅዱስ ዳዊት አመንኩ በዘነበብኩ /በተናገርሁት አመንሁ፤ እንዳለ መዝ.115፥1 ፍጹም እምነታቸውንና ታማኝነታቸውን፣ ጽናታቸውን እንረዳለን፡፡ ዛሬ የምናከብረው የሊቀ መላእክት የቅዱስ ገብርኤል በዓል ሠለስቱ ደቂቅን ከባቢሎን እሳት ያዳነበት ነው፡፡ ታሪኩ የተፈጸመው በብሉይ ኪዳን ዘመን ከ605-562 ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በነገሠው በናቡከደነጾር ዘመን ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን ከጣዖት አምላኪና አስመላኪ ኀያላን ነገሥታት መካከል አንዱ ናቡከደነጾር ነበር፡፡ ምስሉ የቆመው በ587 ቅ/ል/ክ እንደሆነ መተርጎማን ያስረዳሉ፡፡ ዳን.3፥1 ናቡከደነጾር እስራኤላውያንን በማረከበት ዘመን ዳንኤልንና ሦስቱን ሕፃናት በልዩ ሁኔታ አክብሯቸው ነበር፡፡

 
 
            • ዳንኤልን ብርጣሶር አለው አሰበ በል አምኃ ቤል ሲል ነው
            • አናንያንም ሲድራቅ አለው ወልደ ሰቃየ አትክልት /አትክልተኛ/ ማለት ነው
            • ሚሳኤልንም ሚሳቅ አለው ፀሐቂ ተጋሂ ፍንው ለግብር መልእክት  /ትጉህ ፈጣን መልእክተኛ/ ማለት ነው፡፡
            • አዛርያንም አብደናጎም አለው ገብረ ዳጎን /የጣዖት አገልጋይ/ ማለት ነው፡፡ የቀድሞ ስማቸው ትርጉም ግን
            • ዳንኤል ማለት ፍትሕ እግዚአብሔር ዳኛ እግዚአብሔር
            • አናንያ ማለት ደመና
            • ሚሳኤል ማለት ሰምዓኒ እግዚአብሔር /እግዚአብሔር ስማኝ/
            • አዛርያ ማለት ረድኤት ማለት ነበር፡፡ ት.ዳን.1፥7

            ንጉሡ እነዚህን ሕፃናት ለሦስት ዓመት በቤተ መንግሠት ጥሩ ምግብ እየተመገቡ የከለዳውያንን ትምህርትና ቋንቋ ያጠኑ ዘንድ አዝዞ ነበር፡፡ እነርሱ ግን ትምህርቱን እየተማሩ በንጉሡ ቤት የተዘጋጀውን ምግብና መጠጥ ሳይመገቡ ጥራጥሬና ውኃ እየተመገቡ በፈተና ያለፉ ነበሩ፡፡ ዳን.1፥8-21

            ጠቢባንና አስተዋዮች በመሆናቸው በባቢሎን አውራጃዎች ላይ ተሾሙ፡፡ ዳን.2፥46-49 የሠለስቱ ደቂቅ በንጉሡ ዘንድ መወደድና መሾም ያስቀናቸው ባቢሎናውያን ለናቡከደነጾር “በባቢሎን ሀገሮች ለሚሠራ ሥራ የሸምካቸው ከአይሁድ ወገን የሚሆኑ ትእዛዝህን እምቢ ያሉ አምላክህን ያላመለኩ ለሠራኸውም ለወርቁ ምስል ያልሰገዱ ሚሳቅና ሲድራቅ አብደናጎም የሚባሉ ሦስት ሰዎች አሉ” ብለው ከሰሷቸው ያን ጊዜም ንጉሡ ተቆጣና እንዲሰግዱ አዘዘ፡፡ እነርሱም አንሰግድም አሉ፡፡ “ያን ጊዜም …… ዳን.3፥13-19”

            ናቡከደነጾር ሦስት ዓይነት መንገዶችን ተጠቅሞ ለምስሉ ለማሰገድ ጥረት አድርጓል

            1. በመጀመሪያ ዐዋጅ በማወጅ ነው ይህ ዐወጅ ከተራው እስከ ባለሥልጣናቱ ያሉትን የሚመለከት ነበር፡፡ በተለይም ባለሥልጣናቱ ቀድመው በመስገድ አርአያ እንዲሆኑ ተጋብዘዋል፡፡
            2. ሁለተኛው የሕዝቡን ልብ በሙዚቃ እንዲደሰቱ በደስታው ተውጠው ሳያስቡት እንዲሰግዱ ማድረግ
            3. የመጨረሻው በማስፈራራት /ወደ እሳት ትጣላላችሁ እያለ/ እንዲሰግዱ ማድረግ ነው፡፡ ነገር ግን የቱንም ያህል ቢያባብልና ቢጥር ሠለስቱን ደቂቅ ለማሰገድ ያደረገው ሙከራ  አልተሳካለትም፡፡

            ሠለስቱ ደቂቅ ጣዖት አናመልክም ካሉ ለምን ወደ ጣዖቱ መጡ? ቢሉ

            1. ለምስክርነት፡- የአምልኮ ጣዖትን ከንቱነትና የእግዚአብሔርን ክብር ለመመስከር
            2. ለአርአያነት፡- በምርኮ ያሉት እስራኤላውያን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ አርአያ ለመሆን ነው፡፡

            ሠለስቱ ደቂቅ ለንጉሡ የትእዛዝ ለመቀበል ምክንያት አላቸው፡፡ ግን ተቃወሙት

            1. ወጣቶችና ምርኮኞች ናቸው
            2. በንጉሡ ሥልጣን ሥር ናቸው፡፡
            3. አንዴ ብቻ ስገዱ ተባሉ እንጂ እግዚአብሔርን ተው አልተባሉም ስለዚህም፡- “ለዛሬ  ተመሳስለን እንለፍ” ማለት ይችላሉ፡፡
            4. “የንጉሡ ውለታ ይዞን ነው” ማለት ይችላሉ
            5. “በባዕድ ሀገር ስለሆንን ነው፡፡”
            6. እንኳስ እኛ በባዕድ ምድር በሰው እጅ ያለነው ቀደመቶቻችን በራሳቸው ፈቃድ ጣዖት አምልከዋል፡፡
            7. “ከሰው ጋር ሲኖሩ ሞኝ ሆኖ አህያ ሲጭኑ ሦስት ሆኖ ነው” በማለት ምክንያት መፍጠር ይችሉ ነበር፡፡ ነገር ግን ምንም ምክንያት አልሰጡም፡፡

            ከሠለስቱ ደቂቅ ሦስት ነገር እንማራለን

            ማመን፣ መቁረጥ እና ማድረግን፡፡ ሃይማኖት እነዚህን 3 ነገሮች ይፈልጋል፡፡ ሦስቱ ሕፃናት በእግዚአብሔር ፍጹም አመኑ፣ ይህንንም እምነታቸውን ሲገልጡ “የምናመልከው አምላካችን ከሚነደው እቶን ያድነን ዘንድ ይችላል” በማለት ተናግረዋል፡፡ የመጣባቸውን ሁሉ ለመቀበል ወሰኑ ቆረጡ “አምላካችን እኛን ማዳን ይችላል ነገር ግን ፈቃዱ ከዚህ እሳት ገብተን ሠማዕትነትን እንድንቀበል ቢሆን ከእሳት እንገባለን” በማለት አንድ ልብ፣ አንድ ቃል ሆነው አቋማቸውን ገለጡ፡፡ የቆረጡትን ነገር አደረጉት፤ ወደ እሳት ውስጥ ተወረወሩ ሦስቱም ነገሮች ስለተፈጸሙ እግዚአብሔር መልአኩን ልኮ እሳቱን አብርዶ አዳናቸው፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል” በማለት የተናገረው ቃልም ተፈጽሞላቸዋል፡፡ /መዝ.33፥7/ ጠባቂ መልአካቸው ቅዱስ ገብርኤል በእሳት ውስጥ ገብቶ ከመከራ ሥጋ አድኖአቸዋል፡፡ የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራና መልአኩል ልኮ የፈጸመውን ትድግና ያየው ናቡከደነጾር “ናቡከደነፆርም መልሶ፡- መልአኩን የላከ ከአምላካቸውም በቀር ማንም አምላክ እንዳያመልኩ ለእርሱም እንዳይሰግዱ ሰውነታቸውን አሳልፈው የሰጡትን የንጉሡንም ቃል የተላለፉትን በእርሱ የታመኑትን ባሪያዎቹን ያዳነ፥ የሲድራቅና የሚሳቅ የአብድናጎም አምላክ ይባረክ፡፡ እኔም እንደዚህ የሚያድን ሌላ አምላክ የለምና በሲድራቅና በሚሳቅ በአብድናጎም አምላክ ላይ የስድብን ነገር የሚናገር ወገንና ሕዝብ በልዩ ልዩም ቋንቋ የሚናገሩ ይቆረጣሉ ቤቶቻቸውም የጉድፍ መጣያ ያደረጋሉ ብዬ አዝዣለሁ አለ፡፡ የዚያን ጊዜም ንጉሡ ሲድራቅንና ሚሳቅን አብድናጎንም በባቢሎን አውራጃ ውስጥ ከፍ ከፍ አደረጋቸው፡፡” ዳን.3፥28-30

            ናቡከደነጾር ሦስት ነገሮችን አስተውሏል

            1. ሠለስቱ ደቂቅ ፈጣሪያቸውን በመዝሙር ሲያመሰግኑ ሰምቷል፡፡
            2. እሳቱ በወጣቶች ላይ ምንም ጉዳት እንዳላደረሰባቸው አስተውሏል
            3. ሰው ያልሆነ ፍጡር አብሯቸው መኖሩን አውቋል ከዚህ የተነሣ አማኞችንም ፈጣሪያቸውንም አመስግኗል፡፡ “መልአኩን የላከ…. የታመኑትን ባሪያዎቹን ያዳነ የሲድራቅና የሚሳቅ የአብድናጎም አምላክ ይመስገን” ብሏል፡፡ ዳን.3፥28

            የእግዚአብሔርን ጥበቃ ስናነሣ ጥበቃው በብዙ ዓይነት /መንገድ ነው፡፡

            1. የእግዚአብሔር ጥበቃ፡- እግዚአብሔር በመግቦቱ ዓለምን ይጠብቃል ይመራል፡፡ መዝ.22፥1፣ ማቴ.5፥45፣ ማቴ.6፥25፣ 1ኛ ጴጥ.5፥7
            2. የቅዱሳን መላእክት ጥበቃ፡- ቅዱሳን መላእክት በተልእኮ ይጠብቃሉ ይራዳሉ ያማልዳሉ፡፡ መዝ.33፥7 “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል ያድናቸውማል፡፡” ይላል
            3. የካህናት ጥበቃ በማስተማርና በምክር በጸሎት ይጠበቃሉ ዮሐ.21፥15፣ 1ኛ ጴጥ.5፥2፣ ዕብ.13፥17 “ለመምህሮቻችሁ ታዘዙ… ስለ ነፍሳችሁ ይተጋሉና”
            4. የሕግ ጥበቃ ሕግ ሲያከብሩት ሰውን ይጠበቃል ይመራል፡፡ መዝ.118፥105 “ሕግህ ለእግሬ ብሥራት ለመንገዴም ብርሃን ነው”

            ከዚህም ውስጥ የቅዱሳን መላእክትን ጥበቃ ብንመለከት

            ቅዱሳን መላእክት ምንድን ናቸው? አገልግሎታቸው ምንድ ነው ብንል

            • የቅዱሳን መላእክት ተፈጥሮ እግዚአብሔር አምላክ በዕለተ እሑድ እምኀበ አልቦ ኀበ ቦ/ካለመኖር ወደመኖር አምጥቶ የፈጠራቸው ንጹሐን ቅዱሳን ረቂቃን ፍጥረታት ናቸው፡፡ ኩፋ.2፥5-9፣ መዝ.103፥4፣ ቈላ.1፥16-17
            • ቅዱሳን መላእክት በነገድ መቶ ናቸው ማቴ.18፥11-14 ሳጥናኤል በመሳቱ 99 ነገደ መላእክት ሲሆኑ 100ኛ ነገድ አዳም ሆኗል፡፡
            • ቅዱሳን መላአክት ቁጥራቸው አይታወቅም ት.ኤር.33፥22
            • ቅዱሳን መልእክት ሕያዋን ናቸው ሞት የለባቸውም ማቴ.22፥30

            የቅዱሳን መላእክት አገልግሎት በሁለት ይከፈላል

            1ኛ. እግዚአብሔርን ያለ ዕረፍት ማመስገን

            ራዕ.4፥6-11፣ ራዕ. 5፥6-14፣ ኢሳ.6፥1፣ መዝ.102፥20፣ ሄኖክ 11፥16 “ለእነርሱ ዕረፈታቸው ምስጋናቸው ነውና ያመሰግናሉ ያከብራሉም አያርፉም”

            2ኛ. ሰውን ያለ ዕረፍት ማገልገል /መጠበቅ/ ነው ማቴ.18፥10፣ ዕብ.1፥14፣ ዘፀ.13፥21፣ ዳን.6፥22 /”አምላኬ መልአኩን ልኮ የአንበሶችን አፍ ዘጋ”/፣ ዳን.12፥1

            • ቅዱሳን መላእክት የሰው ልጆች የዘላለም ሕይወትን እንዲወርሱ ያግዛሉ ይራዳሉ፡፡ ዕብ.1፥14
            • ቅዱሳን መላእክት ከእግዚአብሔር ወደ ፍጥረታት ለምሕረትም ለመዓትመ ይላካሉ፡፡

            ለምሕረት ሲላኩ

            ት.ዘካ.1፥12 “የእግዚአብሔርም መልአክ መልሶ “አቤቱ ሁሉን የምትችል ሆይ እነዚህን ሰባ ዓመት የተቈጣሃቸውን ኢየሩሳሌምንና ይሁዳን ከተሞች የማትምራቸው እስከ መቼ ነው?” እያሉ እግዚአብሔርን ይለምናሉ፡፡ ሮሜ.9፥23፣ ዘፍ.19፥12-23 “….ራስህን አድን” አሉት

            ለመዓት ሲላኩ

            2ኛ ነገ.19፥35 “በዚያችም ሌሊት የእግዚአብሔር መልአክ መጣ ከአሦራውያንም ሰፈር መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ ገደለ ማለዳም በተነሡ ጊዜ እነሆ ሁሉ በድኖች ነበሩ” 2ኛ ሳሙ.24፥16

            • ቅዱሳን መላእክት ከሰው ወደ እግዚአብሔር ልመናን ምልጃን ያቀርባሉ /የምዕመናንን ጸሎት ያሳርጋሉ/ ራዕ.5፥8፣ ራዕ.8፥2-5፣ ማቴ.18፥10፣ ዮሐ.1፥52
            • ቅዱሳን መላእክት ከክፉ ነገር ሁሉ ይመልሳሉ /ወደ በጎ ይመራሉ/ ዘኁ.22፥32 የእግዚአብሔር መልአክ “መንገድህ በፊቴ ቀና አልነበረምና አቋቁምህ ዘንድ መጥቼአለሁ አለው፤ ለክፋት ተነሥቶ የነበረውን ለበጎ አደረገው፡፡
            • ቅዱሳን መላእክት የሰው ልጆችን ያጽናናሉ ያበረታታሉ፡፡ 1ኛ ነገ.19፥5፣ ዳን.10፥13-21፣ ሉቃ.22፥43 “የሚያበረታታው የእግዚአብሔር መልአክም ከሰማይ ታየው” ማቴ.4፥11 “እነሆም መላእክት ሊያገለግሉት መጡ” እኛንም በችግራችን ጊዜ ሊያገለግሉን ይመጣሉ፡፡
            • ቅዱሳን መላእክት ከሰይጣን ተንኮልና ስሕተት ይጠበቃሉ ይታደጋሉ ዘፀ.23፥20-23፣ መዝ.90/91፥11-12
            • ቅዱሳን መላእክት እግዚአብሔርን ለሚገዳደሩና ለሚጠረጠሩ ይቀስፋሉ  መዝ.34፥5-6

            በአጠቃላይ ስለ ቅዱሳን ምልጃ ስናነሣ 3 ነገሮች መኖራቸውን ማወቅ መረዳት ይገባናል፡፡

            1. የሚለመነው የሚማለደው እግዚአብሔር ይቅር ባይ መኖሩን ዘፀ.32፥11-15
            2. የሚለምን/ የሚማልድ አስታራቂ መልአክ/ጻድቅ መኖሩን ት.ዘካ.1፥12
            3. የሚለመንለት ሰው/ ተነሣሂ ይቅርታ ጠያቂ/ መሆን አለበት ሉቃ.18፥13፣ ዘፍ.20፥7
            • የሚለመንለት ሰው አማኝ ተነሣሂ መሆን አለበት ት.ሕዝ.14፥14፣ መዝ.33፥7
            • ለማስታረቅ በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ፣ ብቃት መመረጥ መወደድ ያስፈልጋል የሐዋ.19፥11-20፣ ዘኁ12፥1
            • ለማስታረቅ በሰው ፊትም ቢሆን መወደድ መከበር ተሰሚነት ያስፈልጋል፡፡
            • በአጠቃላይ ሠለስቱ ደቂቅ በእምነታቸው ጽናት የእግዚአብሔርን ቸርነት የሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤልን ጠባቂነት በግልጽ አሳየተው አስረድተዋል፡፡ ከዚህም የተነሣ ነው ንጉሡ “መልአኩን የላከ.. የታመኑትን ባሪያዎቹን ያዳነ የሲድራቅና የሚሳቅ፣ የአብደናጎም አምላክ ይመስገን” ያለው፡፡
            • እኛም በክርስትናችን ጸንተን በሥነ ምግባራችን ለሌሎች ምሳሌ በመሆን ከዚህ ክፉ ዓለም በእግዚአብሔር ቸርነት በቅዱሳን ጸሎትና ተራዳኢነት በወላዲተ አምላክ አማላጅነት ንስሐ ገብተን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ተቀብለን የስሙ ቀዳሽ የመንግሠቱ ወራሽ ለመሆን ያብቃን፡፡

            የሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አይለየን

            ወስብሐት ለእግዚአብሔር

            አሜን

            ምንጭ፡- ድርሳነ ቅዱስ ገብርኤል

            • ስንክሳር ግንቦት 10 ቀን
            • መዝገበ ታሪክ
            • ትንቢተ ዳንኤል ከዘመነ ባቢሎን እስከ ዓለም ፍጻሜ፡፡

            የጥናትና ምርምር ማእከሉ ያዘጋጀው የጥናት ጉባኤ ተራዘመ

            ታኅሣሥ 17 ቀን 2005 ዓ.ም.

            በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል ታኅሣሥ 20 ቀን 2005 ዓ.ም. “በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የፓትርያርክ ምርጫና የአባቶች እርቀ ሰላም” በሚል መሪ ቃል አዘጋጅቶት የነበረው የጥናት ጉባኤ ላልተወሰነ ጊዜ የተራዘመ ሲሆን የሚካሄድበትን ጊዜ ወደፊት የምናሳውቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

            eg 1

            የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እና የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የልምድ ልውውጥ አደረጉ

            ታኅሣሥ 17 ቀን 2005 ዓ.ም.

            በዲ/ን ኅሩይ ባየ

            eg 1

            ከታኅሣሥ 11-15 ቀን 2005 ዓ.ም. ለአምስት ተከታታይ ቀናት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እና የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የልምድ ልውውጥ አደረጉ፡፡ የልምድ ልውውጡ የተከናወነው በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ሲሆን በአምስቱ ዕለታት በየቀኑ እስከ አንድ ሺሕ ለሚሆኑ የተለያዩ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች መካፈላቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

             

            ታኅሣሥ 11 ቀን 2005 ዓ.ም. በጉባኤው መክፈቻ ዕለት ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ እና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ እና የኢሊባቡርና ጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የቅዱስ ሲኖዶስ ልዩ ጸሐፊና የአዲስ አበባ ምዕራብ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን የበላይ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቢመን የላዕላይ ግብፅ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ቄስ ዳውድ ለሜይ የግብፅ መንበረ ማርቆስ ካቴድራል ካህን፣ የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ዲያቆናትና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የአድባራት የስብከተ ወንጌል ክፍል ሓላፊዎች፣ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅና የቅዱስ ጳውሎስ ሰዋሰወ ብርሃን ከፈተኛ ትምህርት ቤት ደቀ መዛሙርት፣ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ተገኝተዋል፡፡

             

            eg 3 2“ተዘከር ማኅበረከ ዘአቅደምከ ፈጢረ ወአድኀንከ በትረ ርስትከ ደብረ ጽዮን ዘኀደርከ ውስቴታ… አስቀድመህ የፈጠርሃትን ማኅበርህን የተቤዥሃትንም የርስትህን በትር በእርስዋ ያደርህባት የጽዮንን ተራራ አስብ” /መዝ.73፥2/ የሚለው የዳዊት መዝሙር በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅድሳን ገዳም ዲያቆናት ተሰብኮ የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ አምስት በብፁዕ አቡነ ናትናኤል ከተነበበ በኋላ የኪዳን ጸሎት ደርሷል፡፡ በመቀጠልም ዐቃቤ ርእሰ መንበሩ ግብፅና ኢትዮጵያ እኅትማማች ዓብያተ ክርስቲያናት መሆናቸውን አስታውሰው የቆየ ቤተሰባዊ ግንኙነታቸውን አጠናክረው በመቀጠል የልምድ ልውውጥ ለማድረግ የመጡ ግብፃውያንንና የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን አመስግነዋል፡፡

             

            ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ በመሸፈን በአሜሪካና በግብፅ የሚገኙ የበጎ ፈቃደኛ አገልጋዮች ልዑካንን በመመደብ የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ላለፉት አምስት ቀናት የልምድ ልውውጥ እንዲደረግ ላደረገችው አስተዋጽኦ ምሥጋናቸውን የገለጡት የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን የኤች አይቪ መከላከያና መቆጣጠሪያ መምሪያ ሓላፊ ቄስ ሶምሶን በቀለ ልማት ኮሚሽኑ በማስተባበር እና የቋሚ ተሳታፊ ሠልጣኞችን የትራንስፓርት ወጪ መሸፈኑን ገልጠዋል፡፡

             

            በሰባቱ ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያን ላይ ያተኮረው የልምድ ልውውጥ በከፍተኛ መነቃቃትና ፍላጎት ተካሂዷል፡፡ ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት እነዚህን ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያን ለማስተማር ያላቸው ብቃት እንደተጠበቀ መሆኑን የገለጡት ቄስ ዳውድ ለሜይ በሥርዓት አፈጻጸሙ ላይ የልምድ ልውውጥ ማድረግ እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል በተጨማሪም ምእመናን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት፣ የሚታይና የማይታይ ጸጋ ለማግኘት እነዚህ ምሥጢራት ከሕይወታቸው ጋር አስተሳስረው ሁል ጊዜ በማንኛውም ቦታ በየትኛውም ጊዜ የምስጢራት ተካፋይ መሆን እንደሚያስፈልግ ሁለቱም አብያተ ክርስቲያናት ጠንክረው መሥራት እንዳለባቸው ልዑኩ በአጽንኦት ገልጠዋል፡፡

             

            “ሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ለእኛ አዲስ ናቸውን?” የሚሉ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች አሳባቸውን ያቀረቡ ሲሆን ቄስ ዳውድ በምሳሌ እንዳስረዱት በጉባኤ የተገኘ አንድን ሕፃን ልጅ ጠርቼ አባትህ አለ? ብዬ ብጠይቀው ካለ አለ ማለቱ አይቀርም አሁንም ተጨማሪ ጥያቄ እንድጠይቀው ፍቀድልኝ አሉ አባትህ ስንት ብር በኪሱ ይዟል? አላውቅም አለ፡፡ የት ነው የሚሠራው? አላውቅም፡፡ ደመወዙ ስንት ነው? አላውቅም፡፡ የሚገርም ነው ሕፃኑ አባቱን ያውቃል ስለ አባቱ ግን የማያውቀው ብዙ ነገር አለ፡፡ … በማለት ምላሻቸውን በምሳሌ አስቀምጠዋል፡፡ በዚህ መነሻነት ሰባቱ ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያንን በጥልቀትና በዝርዝር ማወቅ የተለያዩ ነገሮች መሆናቸውን በማብራራት ይልቁንስ በመንፈሳዊ ሕይወት ለመጠንከር፣ ከዲያብሎስ ቀስት ለማምለጥ፣ በመንፈስ ቅዱስ ለመቃኘት፣ ምስጢራቱን ማወቅ ሳይሆን መጠቀም እንዲገባ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

             

            በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በኩል የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርት፣ ከአዲስ አበባ ደቡብ ሀገረ ስብከት የተውጣጡ የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ከማኅበረ ቅዱሳን ዘማርያን ያሬዳዊ መዝሙር ያቀረቡ ሲሆን ሦስት ወጣቶችም በገና እየደረደሩ ዝማሬያቸውን አቅርበዋል፡፡

             

            eg 3 1የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዝማሬ ስሰማ ንጉሥ ዳዊት በዓይነ ኅሊናዬ፤ ይመጣል በመጽሐፍ ቅዱስ የተዘረዘሩት የዜማ ዕቃዎች መልካቸቹውን ሳይቀይሩ ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተሸጋገሩ መዝለቃቸውን አድንቀው ለወደፊት ይህ ትውፊት ሳይቋረጥ መቀጠል እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ በእነሱ በኩል ከሁለት የዘለለ የዜማ ዕቃ እንደሌላቸው ያስታወሱት ቄስ ዳውድ የእኛ ዜማ ጣዕም እጅግ የሚመስጥ ደስ የሚል እንደሆነ ሳይሸሽጉ ተናግረዋል፡፡ በዝማሬያችን የተመሰጡት ግብፃውያን የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች በፍጹም ተመስጦ ለመዘመር ሲሞክሩ ታይተዋል፡፡

             

            የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን በመወከል ዲያቆናትና የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ በአረብኛና በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተለያዩ መዝሙራትን በማቅረብ የዝማሬውን መልእክት ቄስ ዳውድ አብራርተዋል፡፡

             

            በአጠቃላይ በጉባኤው የተለያዩ ጥያቄዎች ተነሥተዋል፡፡ ተገቢና ግልጽ ምላሾች ተሰጠተዋል፡፡ ሆኖም በሁለቱ ዓብያተ ክርስቲያናት ያለው መሠረታዊ አንድነት የዶግማ እንጂ የሥርዐት ስላልሆነ በልምድ ልውውጡ የተገለጡ እንግዳ ሥርዓቶች ከኢትዮጵያና ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንፃር መታየት እንዳለባቸው ሊቃውንቱ አሳስበዋል፡፡ ትምህርተ ኖሎት፣ ሐዋርያዊ ተልእኮ፣ በጎ አስተዳደርና የግጭት አፈታትን በሚመለከቱ የጥናት ጽሑፎች በኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ቀርቦ ሰፊ ውይይትና በቂ ግንዛቤ ተገኝቶበታል፡፡

             

            የልምድ ልውውጡ በጎ ገጽታ እንዳለው እና ለወደፊቱ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በዕለቱ ከተሰጡ አስተያየቶች ለመረዳት ተችሏል፡፡

            men 16

            ሥልጠናው የአቋም መግለጫ በማውጣት ተጠናቀቀ

            ታኅሣሥ 17 ቀን 2005 ዓ.ም.

            በእንዳለ ደምስስ

            men 16

            ማኅበረ ቅዱሳን ከታኅሣሥ 6-11 ቀን 2005 ዓ.ም. ከ65 በላይ ለሚሆኑ የገዳማት አበመኔቶች፣ እመምኔቶችና ተወካዮች “የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ ለማሳካት የገዳማት ድርሻ” በሚል መሪ ቃል የግማሽ ቀን ዐውደ ጥናትና በዩኒቨርስቲ ምሁራን፤ በቅርስ ጥበቃ ባለሥልጣን፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የገዳማት መምሪያ እንዲሁም በተጋባዥ ምሁራን ለአምስት ቀናት ሲሰጥ የቆየው ሥልጠና ተጠናቀቀ፡፡

             

            ሥልጠናው ያተኮረው፡-

            • ገዳማት ያላቸውን ልዩ ልዩ ሀብታት ምንድናቸው? እንዴትስ ጥቅም ላይ ይውላሉ?

            • የአካባቢ ጥበቃ /ከብዝሃ ሕይወት ጋር በተያያዘ/

            • የሥራ ፈጠራ ክህሎትና የገቢ ማስገኛ እቅድ ዝግጅት

            • የቅርስ አጠባበቅ፣ ገዳማት ከቅርስ ጉብኝት እንዴት ተጠቃሚ ማድረግ ይችላል?

            • የቤተ ክርስቲያንን ተልዕኮ ለማሳካት የገዳማትና የመነኮሳት ድርሻ

            • የገዳማት አስተዳደር ለማጠናከር የሰው ኀይል አጠቃቀም

            • የመረጃ ልውውጥና የውሳኔ አሰጣጥ

            • የሀብት ቁጥጥርና አስተዳደር ምን መምሰል ይኖርበታል?

            • የፕሮጀክት ጥናትና የፕሮጀክት ትግበራ . . . ወዘተ በሚሉ ዋና ዋና ርዕሰ ጉደዮች ላይ በስፋት ሥልጠናው ተሰጥቷቸዋል፡፡

             

            በሥልጠናው ላይ የቡድን ውይይት በማድረግ፣ ገዳማት ከገዳማት ተሞክሮና ልምድ ልውውጥ፣ እንዲሁም የእርስ በርስ የመተዋወቅ ሥራዎች ለመሥራት ተችሏል፡፡

             

            በሥልጠናው ላይ ያገኙትን ግንዛቤ ለመገምገምም በቅዱሳት መካናት ልማትና ማህበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የተዘጋጀ ፈተና የተሰጣቸው ሲሆን በውጤታቸው መሠረት ብልጫ ላመጡ 3 መነኮሳት የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ገድል ተሸልመዋል፡፡ ሥልጠናውንም ወስደው በማጠናቀቃቸው ሁሉም ሰልጣኞች ከብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት እጅ የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡

             

            በመዝጊያ መርሐ ግብሩ ላይ ሥልጠናውን የወሰዱት የገዳማት አበምኔቶች፤ እመምኔተችና ተወካዮች ሥልጠናው ከፍተኛ ግንዛቤ እንደፈጠረላቸው በመግለጽ የጋራ የአቋም መግለጫ አውጥተዋል፡፡

             

            በአቋም መግለጫቸውም፡-

            1. ገዳማውያንና ገዳማውያት ገዳማት ያላቸውን የተፈጥሮ ሀብት በመጠቀም እራሳቸውን ችለው ሌላውን እንዲረዱ፤

            2. በገዳማት የሚገኙ ቅርሶችን በአግባቡ በመያዝና በመጠበቅ ለትውልድ ማስተላለፍ እንዲችሉ፤

            3. የቁሪት ገዳማት ወደ አንድነት ገዳማዊ ሥርዓት እንዲመጡ /እንዲገቡ/ የሚደረግበት መንገድ እንዲመቻች፤

            4. ገዳማውያን እና መነኮሳት ለተልዕኮ ከገዳማቸው በሚወጡ ጊዜ ተልዕኮአቸውን ፈፅመው እስኪመለሱ ድረስ የሚቆዩበት ማረፊያ ቤት በወረዳ በዞን እና በአዲስ አበባ ላይ እንዲመቻች ቢደረግ፤

            5. በየገዳማቱ የሚገኙ ነገር ግን ያልታተሙ የቅዱሳን አባቶች የገድል መጻሕፍት እንዲታተሙ ቢደረግ

            6. በኢትዮጵያ ያሉ ገዳማት ወጥ በሆነ አንድ ሥርዓተ ገዳም እንዲተዳደሩ ቢሆን፤

            7. ያለ በቂ ሥራ ወይም ምክንያት ከገዳም ወደ ገዳም በመዘዋወር እና ከተማ በመምጣት እና በመቀመጥ ስም የሚያጎድፉ መነኮሳት በሚመለከተው አካል ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድባቸው ቢደረግ፤

            8. ቅድሳት ስዕላትን እና መስቀል ይዘው በየመንገዱ በቤተ ክርስቲያን ስም መለመኑ እንዲቆም እንዲደረግ፤ ያለ አግባብ ለዚሁ ጉዳይ ፈቃድ የሚሰጡ አካላትም እንዲታቀቡ እንዲደረግ፤

            9. በየገዳማቱ ያሉት የአብነት ትምህርት ቤቶች እንዲጠናከሩ እና ባልተቋቋሙባቸው ገዳማት የአብነት ትምህርት ቤቶች እንዲቋቋም ቢደረግ፤

            10. የኢትዮጵያ ገዳማት በገዳማት መምሪያው አማካይነት ቢያንስ በዓመት አንድ ጊዜ እንድንሰበሰብ እና እንድንወያይ ቢደረግ፤

            11. የገዳማውያን ጉዳይ በገዳማውያን አባቶች እንዲታይ ቢደረግ፤

            12. ገዳማት ከሚሠሩት የልማት ሥራ ለመንግሥት ከሚከፍሉት ግብር ነፃ የሚሆኑበት መንገድ ቢመቻች፤

            13. በመጨረሻም ከመመሪያው ሥር ሆኖ ስለገዳማት መጠናከርና ለችግሮቻቸው መፈትሔ የሚሰጥ 12 አባላት ያሉት አንድ ዐቢይ ጉባኤ /ኮሚቴ/ የመረጥን ስለሆነ እንዲፀድቅልን በማለት በአንድ ድምፅ ተስማምተን አቋም ይዘናል፡፡ በማለት የአቋም መግለጫቸውን አሰምተዋል፡፡

             

            በማቅኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር ዲ/ን አእምሮ ይሔይስን የሥልጠናውን ውጤት በማስመልከት ጠይቀናቸው ሲመልሱም  “ሥልጠናው ወደፊት በገዳማት ላይ ለምንሠራቸው ሥራዎች በር የከፈተ ነው፡፡ ከመነኮሳቱ ግብረ መልስ እንደተረዳነው ሥልጠናው ጥሩ ግንዛቤ እንደፈጠረላቸው አመላክቶናል፡፡ በተሻለ ሁኔታና ባቀድነው መሠረት ተከናውኗል፡፡ ወደፊትም አሠልጥነን የምንለቃቸው ሳይሆን ለመነሻ የሚሆን ከየገዳማቱ ምን ሊሠራላቸው እንደሚፈልጉ ከሰጡን መረጃ ተነሥተን ጥናቶችን በማጥናት እገዛ እናደርጋለን፤ ክትትላችንንም እንቀጥላለን፡፡” በማለት ገልጸዋል፡፡

             

            በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

             

            ከመርሐ ግብሩ መጠናቀቅ በኋላ በሥልጠናው ስላገኙት እውቀትና የተሰማቸውን ስሜት እንዲገልጹልን ገዳማውያን አባቶችን የጠየቅናቸው ሲሆን የሚከተለውን ምላሽ ሰጥተውናል፡፡

             

            ስለ ሥልጠናው ከገደማውያን አባቶች አንደበት

            • “ለገዳማት ልማት ትልቅ ለውጥ ነው፡፡ እስከ ዛሬ እንደዚህ ዓይነት ሥልጠና አጋጥሞን አያውቅም፡፡ እስከ ዛሬ እንዴት ናችሁ? ብሎ የሚጠይቀን አልነበረም፡፡ አሁን የሚጎበኘን አካል ያገኘንበት ነው፡፡ ከሥልጠናው ጠቃሚ እውቀት አግኝተናል፡፡”

            አባ ወ/ገብርኤል ንጋቱ ከሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ወገራ የቅድስት ማርያም ወአቡነ ምእመነ ድንግል አንድነት ገዳም አበምኔት

             

            • “በዚህ ሥልጠና ለየት ያለ እውቀት አግኝቻለሁ ፤ ያላወቅሁትን እንዳውቅ የራሴንም ገዳም እንድመለከት አድርጎኛል፡፡ የተማርኩተን ለገዳማውያኑ በማሳወቅ የልማት ሥራዎችን እንዴት መተግበር እንደሚቻልና ገዳማችንን እንዴት መሳደግ እንደምንችል ተገንዝቤያለሁ፡፡”

            አባ ኢሳያስ ወልደ ሰንበት የዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅድስ ገዳም አበምኔት

             

            • “ማኅበረ ቅዱሳን ፋና ወጊ የሆነና ገዳማትን ያሰባሰበ ጉባኤ በማዘጋጀቱ ታላቅ ደስታ ተሰምቶናል፡፡ በገዳማችን እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ሥራዎች አሉ፡፡ በልማት ራሳችንን የቻልንበት ሁኔታ ላይ ነን፡፡ የገዳማት አንድነትና ትስስር የሚያጠናክርና መፃያትን ጊዜያት እንድንመለከት አስችሎናል፡፡”

            አባ ተክለ ሥላሴ ገብረ ሕይወት የምሥራቅ ሸዋ ጮባ በዓታ ለማርያም ገዳም አበመኔት

             

            • “ገዳሙ የአንድነት ገዳም ነው፡፡ ብዙ መጻሕፍትንና ቅርሶችን አጠቃሎ የያዘ ነው፡፡ አምስት ጳጳሳትን የፈራ ገዳም ነው፡፡ በሥልጠናው መካፈሌ ለቅርሶቻችን አያያዝ ጠቃሚ መረጃ አግኝቼበታለሁ፡፡”

            አባ ዘመንፈስ ቅዱስ ረዳ ከትግራይ አክሱም ጭህ ሥላሴ የአንድነት ገዳም አበምኔት

             

            • “በገዳማችን 5 መነኮሳትና 6 ዲያቆናት ብቻ ነን ያለነው፡፡ ገዳሙ ጥንታዊ ነው፡፡ ያገኘነው እውቀት የሚያስደስት ነው፡፡ ውኃ አለን፡፡ በመስኖ ተጠቅመን የልማት ሥራዎችን ለመሥራት ያበረታታናል፡፡ እስካሁን በመስኖ ተጠቅመን ያከናወነው ነገር የለም፡፡”

            መምህር ገብረ ማርያም ግደይ የትግራይ ተንቤን እንዳጨጌ ደብረ ፅጌ ኪዳነ ምሕረት ገዳም አበምኔት

             

            • “ከሥልጠናው በየበኩላችን በየገዳማቱ በልማትም ሆነ በመንፈሳዊ ሕይወት ለውጥ የምናመጣበትና የቤተ ክርስቲያንን ትውፊት በጠበቀ መልኩ እንዴት መለወጥ እንዳለብን አስገንዝቦኛል፡፡ ለገዳሙ መነኮሳት የተማርኩትን አስተምራለሁ፡፡ አደራ ተሸክሜአለሁና፡፡”

            አባ ወልደ ሠማዕት አብርሃም ከዋልድባ አብረንታት ቤተ ሚናስ ማኅበር የገዳሙ አርድዕትና ተወካይ

             

            • “እየወሰድን ያለው ሥልጠና ቤተ ክርስቲያናችን በፍቅርና በሰላም በልማት ላይ ትኩረት አድርጋ እንድትኖር የሚያመላክት ትጥቅ ነው የገበየሁት፡፡ ይህንን ተሞክሮ የቅዱስ ሲኖዶስም ሆነ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የገዳማት መምሪያ የኢትዮጵያ ገዳማትን ሁሉ አሰባስቦ ጠንካራ ሥራ መሥራት ይገባል፡፡”

            አባ አብርሃም ወልደ ኢየሱስ የምድረ ከብድ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንድነት ገዳም አበምኔት


            • “ሥልጠናው ገዳማት እርስ በርሳችን እንድንተዋወቅ አድርጎናል፡፡ እንደ 120 ቤተሰቦች ነው የሆንነው፡፡ ገዳማት ከገዳማት መተዋወቅ የአንዱን ተሞክሮ ሌላው መስማትና መመልከት መቻሉ ለወደፊት የተሻለ ነገር እንድንሠራ ያደርገናል፡፡”

            ቆሞስ ደሴ ዓለም የጎጃም ደጋ ዳሞት ደብረ ፀሐይ ዋልጣ ቅድስት ማርያም ገዳም አበምኔት

             

            ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን መርሐ ግብር በሚያካሒድበት ወቅት ከገዳማውያን አባቶች በረከት ያገኙ ዘንድ በመስተንግዶ እንዲራዱ ለማኅበራትና ለምእመናን ባደረገው ጥሪ መሠረት መንፈሳዊ ማኅበራትና በጎ አድራጊ ምእመናን ምላሻቸውን በመስጠት የመነኮሳቱንና መነኮሳይያትን እግር በማጠብ፤ የምግብና መጠጥ ወጪ በመሸፈንና በማስተናገድ ከፍተኛ ድጋፍ አድርገዋል፡፡ ማኅበራትና ምዕመናን ላበረከቱት ድጋፍ ማኅበሩ ምስጋናውን አቅርቧል፡፡

            liche 10

            ከልቼ ቤተመንግሥት እስከ ታዕካ ነገሥት ኢየሱስ

            ታኅሣሥ 15 ቀን 2005 ዓ.ም.

            በመ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

            liche 10በአብዛኛው ኢትዮጵያውን ዘንድ የሚወደዱትና “እምዬ” በሚል ቅጽል የሚጠሩት ዐፄ ምኒልክ ለሀገሪቱም ሆነ ለቤተ ክርስቲያን ባለውለታ ነበሩ፡፡ “እምዬ” የሚለውን ቅጽል ሕዝቡ የሰጣቸው፤ የተራበውን ሕዝብ ግብር የሚያበሉ፤ ያለ ፍርድ ሰው የማይቀጡና ደግ ስለሆኑ ነው፡፡

            ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ ከአባታችው ከሸዋው ንጉሥ ኃይለ መለኮት ሣህለ ሥላሴና ከእናታቸው ወይዘሮ እጅጋየሁ ለማ አድያም ነሐሴ ፲፪ ቀን ፲፰፻፴፮ ዓ.ም. ደብረ ብርሃን አካባቢ አንጎለላ ከሚባል ሥፍራ ተወልደው፤ በአንጎለላ መቅደላ ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ክርስትና ተነሡ። አያታቸው ንጉሥ ሣህለ ሥላሴ የምኒልክን መወለድ ሲሰሙ “ምን ይልህ ሸዋ” በሉት ብለው ስም አወጡ። እሳቸው “…ምኒልክ በሚል ስም የሚነግሥ ንጉሥ ኢትዮጵያን ታላቅ ያደርጋታል” የሚል ትንቢት ስለነበር ‘ምኒልክ’ የኔ ስም ነው ብለው ነበር። ሆኖም፣ በህልማቸው ከልጁ ጋር አብረው ቆመው ከሳቸው ጥላ የልጁ ጥላ በልጦ፤ በእግር የረገጡትን መሬት ሲያለካኩ እሳቸው ከረገጡት ልጁ የረገጠው ረዝሞ አዩ። ከዚህ በኋላ “ምኒልክ የኔ ስም አይደለም። የሱ ነው። ስሙን ምኒልክ በሉት” ብለው አዘዙ። ጳውሎስ ኞኞ “አጤ ምኒልክ” በተባለው መጽሐፍ ።

            ምኒልክ እስከ ሰባት ዓመታቸው ድረስ መንዝ ውስጥ ጠምቄ በሚባል አምባ ከእናታቸው ዘንድ አደጉ።አያታቸው ንጉሥ ሣህለ ሥላሴ ሲሞቱliche 7 የሸዋውን አልጋ የምኒልክ አባት ንጉስ ኃይለ መለኮት ወረሱ።ዓጼ ቴዎድሮስ በጥቅምት ወር ፲፰፻፵፰ ዓ/ም ትግራይንና ወሎን አስገብረው፣ ምኒልክ ገና የአሥራ ሁለት ዓመት ልጅ ሳሉ፤ የድፍን አማራንና የወሎን ጦር አስከትተው የሸዋውን ንጉሥ ኃይለ መለኮትን ለማስገበር ሸዋ ገቡ። ሁለቱ መሪዎች ጦርነት ለመግጠም ተዘጋጅተው ሲጠባበቁ ንጉሥ ኃይለ መለኮት ባደረባቸው ሕመም ጥቅምት ፴ ቀን ፲፰፵፰ አረፉ። በዚህ ጊዜ የሸዋ መኳንንት ሕፃኑን ምኒልክን ከጠላት እጅ እንዳይወድቅባቸው ይዘው ሸሹ፤ ዳሩ ግን ዐጼ ቴዎድሮስ እንደሚከታተሏቸው ስላወቁ ኅዳር ፴ ቀን ፲፰፵፰ ዓ/ም የልጅ ምኒልክ ሠራዊትና የዐፄ ቴዎድሮስ ሠራዊት በረከት በተባለው ቦታ ላይ ገጥሞ የምኒልክ ሹማምንት አቶ በዛብህ፣ አቶ አንዳርጋቸው ሁሉ ተያዙ። ልጅ ምኒልክም ለቴዎድሮስ ገቡ። ምኒልክ መቅደላ ገብተው በቁም እሥር ይቀመጡ እንጂ ከቴዎድሮስ ልጅ ከመሸሻ ጋር አብረው አደጉ። ወዲያውም የደጃዝማችነት ማዕረግ ተሹመው በጥር ወር ፲፰፻፶፮ ዓ.ም የዓፄቴዎድሮስን ልጅ ወይዘሮ አልጣሽን አገቡ። በዚህ ሁኔታ ፳፪ ዓመታቸው ድረስ ለአሥር ዓመታት ዐፄ ቴዎድሮስ ግቢ ኖሩ።

            ዐፄ ቴዎድሮስ ምኒልክን እንደልጃቸው ያዩዋቸውና በታላቅ ጥንቃቄም ያስተምሯቸው ነበር። ምኒልክም ቴዎድሮስን እንደአባት ይወዷቸው እንደነበር ይገለጻል። ምኒልክ ከመቅደላ ሰኔ ፳፬ ቀን ፲፰፻፶፯ አምልጠው አንኮበር ገቡ።

             

            በአንኮበር ጥቂት ወራት ከተቀመጡ በኋላ ወደ ደብረ ብርሃን ወርደው አዲሱን ከተማቸውን ልቼን እያሠሩ ተቀመጡ። ዐፄ ምኒልክ የመጀመሪያ ቤተመንግሥታቸው ልቼ እንደነበረ የታሪክ ድርሳናትና የልቼ ቤተ መንግሥት ፍርስራሽ ያስረዳል፡፡ በተለይም ዐፄ ምኒልክ ከየካቲት ፲፰፻፷ ዓ.ም እስከ ታኅሣሥ ፲፰፻፸፰ ዓ.ም በልቼ ቤተመንግሥት እንደነበሩ በተጻጻፉት ደብዳቤ አማካኝነት ታውቋል ፡፡

            ምኒልክ ከልቼ ቤተመንግሥት ሳሉ ከሀገር ውጭም ሆነ ከሀገር ውስጥ መልእክቶችን ተለዋውጠዋል። ከየካቲት ፮ ቀን ፲፰፻፸፰ ዓ.ም እስከ የካቲት ፲ ቀን፲፰፻፸፰ ዓ.ም ከዐፄ ዮሐንስ ጋር ልቼ ላይ ውጊያ አደርገዋል፡፡ በኋላም የካቲት ፲፪ ቀን ፲፰፻፸፰ ዓ.ም ውጊያ ለማቆም ፣የልቼ ሥልጣን ማካፈልንና በሌሎች ጉዳዮችም ለመረዳዳት ስምምነት አድርገዋል፡፡ ይህም የልቼ ስምምነት ተብሎ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡

            ኤስ ሩቬንደንና ሪቻርድ ፓንክረሥት እንደዘገቡት ዳግመኛ በመጋቢት ፲፰፻፸፰ ዐፄ ዮሐንስና ዐፄ ሚኒሊክ ልቼ ላይ የማዕረግ አጠቃቀምን በተመለከተ ስምምነት ላይ ደረሱ፡፡ ጸሐፌ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ ታሪከ ነገስት ዘዳግማዊ ምኒልክ በተሰኘው መጽሐፋቸው የዐጼ ምኒልክን ንግሥናና የልቼ ቤተ መንግሥትን ሥነ ሥርዓት እንዲህ ይገልጹታል ፤ “….(ምኒልክ) መስቀልን ውለው ልቼ ከተማቸው ወጡ፡፡ ከዚያም በሥርዓተ መንግሥት ዘውድ የሚደፉበት፣ አዳራሽ የሚገኙበት ጊዜ ነውና ልቼ ከተማ ከዕድሞው ግቢ ሰፊ ዳስ ተሠርቶ ግብር ለማብላት ልክ መጠን የሌለው ሁኖ ተዘጋጅቶ ነበረ፡፡ ደግሞም ከዳሱ አፋፍ ከሰገነቱ ዝቅ ያለ ሥራው ልዩ ልዩ የሆነ መንበር ተሠርቶ ነበር፡፡ በዚህም ጊዜ የዳሱ ጌጥ ሥራው የቆመበትም ሁሉ በልዩ ልዩ ዓይነት ግምጃ የተሸፈነ ነበር፡፡  ከዚህም አስቀድመው ባዋጅ ‘በምገዛው አገር የሚኖር ካህን ከየደብሩ መስቀልና ጥና ከአልባሳቱ ጋር እየያዘ በጥቅምት ሁለት ቀን ይግባ’ ብለው አዘውት ጠቅሎ ገባ፡፡ በዚህም ጊዜ በእስክንድርያ ሃይማኖት ሳይገዘት ሰንብቶ የነበረው ሲገዘት ሰነበተ፡፡

            ከዚህም በኋላ በጥምቅት በ፫ ቀን ቅዳሜ ማታ ንጉሥ ከነሠራዊታቸው ከልቼ ተነሥተው ደብረ ብርሃን ወርደው አደሩ፡፡ ሲነጋ ንጉሡ ከመቅደስ ልብሰ መንግሥት ለብሰው መምህር ገብረ ሥላሴ፣ መምህር ግርማ ሥላሴ ንጉሡን በወርቅ አልጋ አስቀመጧቸው፤ ዘውዱንም ደፉላቸው፡፡ በዚያን ጊዜ የመምህራኑ ጸሎት ይህ ነው፡፡ እግዚኦ በኃይልከ ይትፌሣሕ ንጉሥ ምኒልክ ወብዙኅ ይትሐሠይ በአድኅኖትከ፤ ፍትወተ ነፍሱ ወሀብኮ፤ ወስእለተ ከናፍሪሁ ኢከላእካ፤ እስመ በጻሕካ በበረከት ሠናይ፤ ወአነበርከ አክሊለ ዲበ ርእሱ ዘእምዕንቍ ክቡር፤ ሐይወ ሰአለከ ወሀብኮ፤ ለነዋኅ መዋዕል ለዓለመ ዓለም እያሉ ምስጋና እየጨመሩ በየመሥመሩ ሁሉ ንሴብሕ ወንዜምር ለፅንዕከ ብለው ይህንን መዝሙር እያደረሱ የወርቅ ሰይፍ አስታጠቋቸው፡፡ ቅንት ሰይፈከ ኃያል ውስተ ሐቌከ በሥንከ ወበላሕይከ አርትዕ ተሠራሕ ወንገሥ እያሉ ይህንን መዝሙር በእንተዝ ይገንዩ ለከ አሕዛብ እግዚኦ ለዓለም ወለዓለመ ዓለም እስከሚለው ድረስ ሲጨርሱ ካህናቱም ከቅድስት ቁመው በአንድ ቃል ተቀጸል ጽጌ ምኒልክ ሐፄጌ ተቀጸል ጽጌ አሉ፡፡ ሊቀ መኳስ አጥናፍ ሰገድ ካባ ላንቃ ለብሶ፡፡ ራስ ዳርጌ ራስ በና ራስ ወርቅ አሥረው ወጡ፡፡ ባለወርቅ መጣምር በቅሎዎቻቸው ቀረቡ፡፡ ንጉሡ ከበቅሎ ሲሆኑ ግራ ቀኝ ሰይፍ ተመዞ ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ ለጊዜው ተሸልመው የነበሩ ቁጥር የሌላቸው ሊቃውንት ከቤተ ክርስቲያን በወጡ ጊዜ ዑደት ሲሆን እንደ ፊተኛው ተቀጸል ጽጌ ምኒልክ ሐፄጌ ተቀጸል ጽጌ እያሉ ዞሩ ስፍራው ጠቦ በሩቅ ካህናት ንሴብሖ ይሉ ነበር፡፡

            ከዚህም በኋላ ጕዞ ተጀመረ፡፡ ሲጓዝም መኳንንቱም በየማዕርጋቸው ሠራዊቱም አጊጦ ጭፍራውም በየአለቀው አምሮ ተሰልፎ ይሄድ ነበር፡፡ እንዲህም ባማረ ጕዞ ተጕዘው ልቼ ከተማቸው ገቡ፡፡ ካዳራሽ ገብተው ከዙፋን ሲቀመጡ ከአደባባዩ የነበሩ መድፎች ፳፪ ጊዜ ተተኰሱ፡፡ ከዚህ ቀጥሎ ከቡሎ ወርቄ ጀምሮ እስከ ሣሪያ ተሰልፎ የነበረው ከቅጥሩም ውስጥ የተሰለፈው ነፍጥ በተተኰሰ ጊዜ ከብዛቱ የተነሣ የክረምት ነጐድጓድ መሰለ፡፡ በንጉሡም ዙፋን አጠገብ በተዋረድ በልዩ ልዩ ዓይነት ሥጋጃው ወላንሣው እየተነጠፈ ተዘጋጅቶ ነበር፡፡

            ራሶችም መኳንንቱም በየማዕርጋቸው ተቀምጠው ግርማ መንግሥት ሆኖ አዳራሽ ተገኝተው ዋሉ፡፡ …. ይህም ነገር በተደረገ ጊዜ ያየውም የሰማውም እጅግ አደነቀ፡፡ ይህም የሆነ  ፲፰፻፸፩ ዓመተ ምሕረት በዘመነ ሉቃስ በጥቅምት በአራት ቀን ነው፡፡ በዚህም ጊዜ ዘውዳቸውን በደስታ በፍቅር ለእግዚአብሔርም ለሰውም አስመርቀው ለሠራዊትዎ ብዙ ቀን አዳራሽ (ልቼ) ተገኙ፡፡” ሲል፦ አክታ ኢትዮጲካ የተሰኘው መጽሐፍ እንደገለጸው ደግሞ ፲፰፻፸፪ ዓ.ም ፋዘር ማሲያ የተባለው ጣልያናዊ በዐፄ ሚኒልክ ልቼ ተጠርቶ ነበር፡፡ ይህም የሆነው የጣሊያን ጆኦግራፊ ማኅበር ወደኢትዮጵያ መግባት ስለፈለገ ፋዘር ማሲያ ማብራሪያ እንዲሰጥ ታስቦ ነው፡፡ ካርዲናል ማሲና እንደዘገበውም ፲፰፻፸፪ዓ.ም ልቼ በተደረገው የሶስት ቀን ድግስ ንጉሥ ምኒልክ ተገኝተው ነበር፡፡ ለዚህም ድግስ አዲስ የመመገቢያ አዳራሽ ተሰርቶ ነበር፡፡

            በ፲፰፻፸፮ ዓ.ም የ፷፭ ዓመት አዛውንቱ ማርኬዝ ኦራሊዬ አንቲኖሪ ከጂዮቫኒ፤ ቻሪኒና ሎሬንዝ ላንዳኒ እንዲሁም ከጣሊያን ወታደሮቻቸው ጋር በመሆን በአንኮበር በኩል በጥቅምት ፯ ቀን ልቼ ደርሰው ነበር፡፡ በዚያም ከዐፄ ሚኒልክ ጋር ተገናኝተው ወደ አዳራሽ አስገቧቸው ግብዣም ተደረገላቸው ፡፡ በ፲፰፻፸፯ ዐፄ ሚኒልክ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች በአውሮፓውያን ወታደራዊ ዘዴ እንዲሰለጥኑ በማሰብ አልጀሪያ የነበረ የፈረንሳይ ጦር አባል ሎያዥ ፓይተር የተባለን ሰው ልቼ መጥቶ እንዲያሰለጥን አድርገዋል፡፡ በ፲፰፻፸፯ መጨረሻ አንቲኖሪና ቻሪኒ በሴባስቲያኖ ማርቲና አንቶኒዬ ቺቺ አማካኝነት ቺሪና ቺቺ ኢትዮጵያን ለማሰሰ መጥተው ግንቦት ፲፬ ቀን ፲፰፻፸፯ ከልቼ ተነሡ ፡፡

             

            የልቼ ታዕካ ነገሥት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን

            liche 3የልቼ ታዕካ ነገሥት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ቀድሞ የዐፄ ምኒልክ ልቼ ቤተ መንግሥት ይባል ነበር፡፡ በአሁኑ ዘመን ደግሞ የታዕካ ነገሥት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ተበሎ ተሰይሞ በቤተ ክርስቲያን ስም ነው የሚታወቀው፡፡ ስያሜውን የሰጡት የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም ናቸው፡፡ ቀድሞ በደብረ ብርሃን ከተማ ዙሪያ በእግዚአብሔር ፈቃድ የተመሠረቱ በርካታ አብያተ ክርስቲያናት ነበሩ:: ኋላ በግራኝ አህመድ ከፈረሱት ከአብያተ ክርስቲያናት መካከል የኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ይገኝ ነበር:: ይህንንም ስለሚያውቁ ይሆናል አቡነ ኤፍሬም በደብረ ብርሃን (ልቼ) ቤተ ክርስቲያኑ እንዲሠራ የመሠረት ድንጋይ ያኖሩት::

            በድርሳነ ዑራኤል ዘሐምሌ ሁለተኛ ምእራፍ ላይ ተመዝግቦ የሚገኘው አሳብ እንዲህ ይላል “…ከዚህ በኋላ ሃይማኖቱ የቀና ዘርዐ ያዕቆብ ነገሠ እሱም መጀመሪያ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ደብረ ብርሃን ላይ ታላቅ ቤተ ክርስቲያን ሠራ ሁለተኛም ቅድስት በሆነች በእናቱ በድንግል ማርያም ስምሦስተኛም የመላእክት አለቃ በሆነ በቅዱስ ዑራኤል ስም …” በዚህ አካባቢ የሚኖረው ሕዝብ በአቅራቢያው ቤተ ክርስቲያን ባለመኖሩ ለቀብርም ሆነ፤ ለአገልግሎት ርቆ ለመሄድ ተገዶ ነበር:: በዚህም የተነሣ ይህ ቤተ ክርስቲያን እንዲተከል ግድ ስላስፈለገ ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም መጥተው፤ ቦታውን ባርከው፣ ስሙንም የታዕካ ነገሥት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ብለው መሰየማቸውን መሪጌታ ክፍለ ክርስቶስ ያስረዳሉ::

            እዚህ ቦታ ላይ ዐፄ ምኒልክ ቤተ መንግሥታቸው እንደነበረ ከመጻሕፍትና ከሀገር ሽማግሌዎች እንዲሁም መጽሐፍ በመመልከት ነው ታሪኩንliche 4 ያገኘነው:: እዚህ ቦታ ላይ የምናያቸው ተጨባጭ ነገሮች  በወቅቱ ዐፄ ምኒልክ ለችሎት በሚያስቀርቡ ጊዜ ሕዝቡ ለፍርድ ሲመጣ ድንጋዮችን ይዞ በመምጣት በመከማቸታቸው ኋላም ለአጥር አገልግሎት ውሏል፡፡ ይህም ዙሪያውን በሦስት ረድፍ የድንጋይ ካብ (እንደ አጥር ሆኖ ስፋቱ ሁለት ሜትር ቁመቱ ሶስት ሜትር) የተከበበ ነው:: ይህ የካብ ድንጋይ አረጀ እንጂ ድሮ እንደተሠራ ነው:: ቢፈርስም እንኳን ታሪኩ እንዳይጠፋ እንደዚሁ ነው የተካበው::

             

            ዐፄ ምኒልክ እዚህ ቦታ ላይ በንግሥናቸውና ለኢትዮጵያ ቅን ተጠሪ ሆነው በነበሩበት ሰዓት የማይጠፋ አትክልት፣ የማይጠፋ ሀብት ለኢትዮጵያ ሕዝብ አስቀምጠውለት ከሄዱት አንዱ  ባሕር ዛፍ ነው:: ቦታው ረግረጋማ ስለነበር ከአውስትራሊያ የባሕር ዛፍ አምጥተው ስለነበር ዛሬ ብዙ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነው::

             

            ልጆች በነበርንበት ሰዓት ት/ቤት ስንሄድ ቦታውን እንዲሁ እናየዋለን እንጂ ገባ ብለን በአካባቢው መጥተን የምናየው ነገር አልነበረም:: እግዚአብሔር ፈቃዱ ሲሆን ግን ተሰብስበን ይህንን ለመሥራት ወይም ደግሞ የሚሠሩትን አካል እንደ እናንተ ያሉትን የእግዚአብሔር ቤተሰቦች የሆኑትን ለመጥራት ተነሣሥተናል:: በወቅቱ ግን እሳቸው የሠሩትም ያደረጉትም በችሎት የተቀመጡበትም እኛን ሊያነሳሳ እና የእግዚአብሔር ፈቃድ ሆኖ ቅዱስ ሥጋው እና ክቡር ደሙ እንዲፈተትበት ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንዲውል እግዚአብሔር ፈቃዱ ሆነ፡፡ ይህን ያስቻለው የንጉሡ ቅንነት ነው ብዬ ነው እኔ  የማስበው:: ይህ ታሪክ ደግሞ የዚህ አካባቢ ብቻ ሳይሆን የመላው ኢትዮጵያ ታሪክ ነው፡፡

            licheክምር ድንጋይ የሚመስለው በሙሉ ቤት ነው ፡፡ ሁሉም የድንጋይ ቤት ነው:: ቤተ መንግሥት ሰለሆነ በብዙ ዓይነት ነው ቤቱ፡፡  ቤቶቹ ባሉበት ፈርሰው ክምር ድንጋይ ቢሆኑም አጥሩ እንደ ኢያሪኮ ግንብ ሶስት ዙር ባለበት ቢገኝም ድንጋዩም ሆነ መሬቱ የሀገር ሀብትና ንብረት ስለሆነ ማንም ግለሰብ መውሰድና ማጥፋት ሳይችል ታሪኩ እንዳይረሳ እግዚአብሔር እስከፈቀደ ድረስ መቀመጥ አለበት::

            ቤተመንግሥት ሰለሆነ ብዙ ዓይነት ነው፡፡ ዋናው ቤተ መንግሥታቸውና የችሎት አዳራሽ አለ፡፡ የንጉሣዊያን ቤተሰብ  መኖሪያ ነው ተብሎ የሚገመት አለ፡፡  የግብር አዳራሽ አለ፡፡ የወታደር ሰፈር አለ፡፡ የግብር ቤት አለ፡፡ ሠራተኞች ሰፈር አለ፡፡ የእንግዶች ማረፊያ አለ፡፡liche2 የመኳንንቱ ቤት ወዘተ. ፍራሹና ግንቡ ይታያል፡፡  የችሎት ቦታቸው የነበረው ቦታ ለቤተ ክርስቲያኑ እንደ መቃኞ እያገለገለ ይገኛል፡፡

            በተጨማሪም ፈረስ መፈተኛቸው የነበረው ሜዳ አሁንም ማንም ሳያርሰው ይገኛል፡፡ የውኃ ምንጫቸው ክረምት ከበጋ አትደርቅም አለች፡፡ የገበያ ቦታቸው የተንጣለለው ሜዳ አሁንም አለ፡፡ በማለት መሪጌታ ገልጸውልን፤ ማሳሰቢያቸውን እንዲህ በማለት አስከተሉ “ታሪኩ እንዳይረሳ እግዚአብሔር ፋቃዱ ሆኗል፡፡ ድንጋዩን ማንም ሳይጠብቀው አግኝተነዋል፡፡ አሁን ደግሞ ቤተ ክርስቲያን እየተሠራ ነው፡፡ እንግዲህ ተባብረን ታሪኩን እንጠብቅ ቤተ ክርሰቲያኑን እንሥራ፡፡”

            liche 6ቀድሞ የንጉሥ ምኒሊክ ቤተ መንግሥት የነበረው ቦታ ዛሬ የንጉሥ ክርስቶስ መመስገኛ ሥፍራ ሆኗል፡፡ ታሪካዊነቱ እንዳለ ሆኖ ቤተ ክርስቲያን በመሠራት ላይ ይገኛል፡፡ ወደፊት ተመራማሪዎች፣ ጎብኚዎች፣ የሃይማኖቱ ተከተዮች ልቼ ታዕካ ነገሥት ኢየሱስ ይመጣሉ፡፡ ሁሉንም እንደፍላጎቱ ማስተናገድ እንዲቻል፡፡ የሁላችንም ትኩረት ተሰጥቶት ቦታውን ማቃናት፣መጠበቅ፣ መገንባት ወዘተ. ይኖርብናል፡፡ ለዚህም አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይርዳን፡፡

            ታህሣሥ 6 ቀን 2005 ዓ.ም ምሽት ላይ በአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ የአማርኛ ፕሮግራም ዲ/ን ዓባይነህ ካሴ የተሰጡት ቃለ ምልልስ ማኅበሩን የማይወከል መሆኑን ስለማሳወቅ

            በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ። አሜን።
            በማኅበረ ቅዱሳን ያላቸውን ሓላፊነት በመጥቀስ ዲ/ን ዓባይነህ ካሴ ታህሣሥ 6 ቀን 2005 ዓ.ም ምሽት ላይ በአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ የአማርኛ ፕሮግራም ለቃለ ምልልስ ቀርበው  በወቅታዊው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች ላይ ሓሳብ መስጠታቸው ይታወሳል።  ማኅበረ ቅዱሳንን በመወከል  ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫም ሆነ ቃለ ምልልስ መስጠት የሚችሉት የማኅበሩ ሰብሳቢ ወይም ዋና ጸሐፊ ወይም የማኅበሩ ሕዝብ ግኑኝነት ሓላፊ ናቸው፡፡ ስለዚህ  ዲ/ን ዓባይነህ ካሴ  በቃለ ምልልሳቸው የሰጡት አስተያየት የግል አስተያየታቸው መሆኑን በአክብሮት  እንገልፃለን።

            ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን
            የማኅበረ ቅዱሳን ጽ/ቤት
            ታህሣሥ 12 ቀን 2005 ዓ.ም
            አዲስ አበባ
            dn tewedreose getachew

            ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ ምን ይላሉ?

            ታኅሣሥ 12 ቀን 2005 ዓ.ም.

            • “በቤተ ክርስቲያን ነጻነት ያለበት አመራር ሊኖር ይገባል”

            ዲ/ን ቴዎድሮስ ጌታቸው

            በደብረ ገነት ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል

            ከሐመረ ብርሃን ሰንበት ት/ቤት

            dn tewedreose getachewየቅዱስ አባታችን ዕረፍት ምክንያት በማድረግ ቤተ ክርስቲያን አዲስ ፓትርያርክ ለመምረጥ በዝግጅት ላይ መሆኗ ይታወቃል፡፡ እንደ እኔ አመለካከት የቤተ ክርስቲያናችንን አንድነት ለማስጠበቅ ዕርቁን አስቀድሞ  መካሔድ ያስፈልጋል፡፡  ምርጫውም መፈጸም ያለበት ከዕርቁ በኋላ ቢሆን ተገቢ ይመስለኛል፡፡

             

            ምርጫውን በማስመልከት በተለይ በዚህ ዘመን እርስ በእርስ የሚጣረሱ ወሬዎች እየወጡ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ባለን ሰዎች፣ በካህናቱም ዘንድ እየተወራ፣ እየታየም ያለው “እገሌ ይመረጥልን፤ ምርጫው ከእገሌ አይ ወጣም” በማለት አላስፈላጊ የቲፎዞ ነገር ነው፡፡ ብፁዓን አባቶቻችን የፓትርያርክ ምርጫውን ተረጋግተው ማካሔድ አለባቸው፡፡ አንዳንዶች ምርጫው በጎጥ፣ በጎሣ ላይ የተመሠረተ እንዲሆን፤ በቡድን የሚንቀሳቀሱ አሉ ይባላል፡፡ ይህ ክርስቲያናዊ ነው ብዬ አላምንም፡፡ አባቶቻችን እነዚህን እኩይ ሤራ የሚያራምዱትን ሰዎች በንቃት ሊከታተሏቸውና ሤራቸውንም ከምንጩ ሊያደርቁት ይገባል፡፡ እግዚአብሔር የፈቀደው፣ መንፈስ ቅዱስ ያዘጋጀውን ሰው ለመመረጥ ተረጋግቶ ሁኔታዎችን ማጤን የሚያስፈልግበት ወቅት በመሆኑ፤ አባቶቻችን በዚህ ላይ ጥንቃቄ ሊያ ደርጉ ይገባል እላለሁ፡፡ ከዛ ይልቅ ለቤተ ክርስቲያን የሚበጃት ማነው? የሚለውን ነው መመልከት ያለብን፡፡ የዘር ጉዳይ በካህናቱ ብቻ ሳይሆን ወደ አንዳንድ ምእመናንም ወርዶ ይታያል፡፡ ብፁዓን አባቶች እነዚህ አላስፈላጊ ግፊት ከሚያደርጉ ሰዎች ሊጠነቀቁ፣  ምእመ ናንም ከዚህ ዓይነት ድርጊት ሊቆጠቡ ይገባል፡፡

             

            ምርጫው የተሳካ ይሆን ዘንድም ጳጳሳቱ፣ ሊቃውንቱ፣ ካህናቱና ምእመናኑ በአንድነት ጸሎት ማድረግ ይገባቸዋል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን የሚበጃትን አባት እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ እንዲያዘጋጅልን ቅድሚያ ጸሎት ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችም ከአባቶች እግር ሥር ሆነን የጸሎቱ ተካፋይ በመሆን እግዚአብሔር ጥሩ አባት እንዲሰጠን ተግተን መጸለይ አለብን፡፡

             

            ፓትርያርኩ ከተመረጡ በኋላ በቤተ ክርስቲያን የሚጠብቃቸው ተግዳሮቶች በእኔ ዕይታ የመጀመሪያው የቤተ ክርስቲያኗን አስተዳደር የሚመለከት ነው፡፡ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ አጥቢያ ድረስ ያለው አስተዳደሯን ማስተካከል ያስፈልጋል፡፡ ከቤተ ክርስቲያኗ ውስጥ ከሚታዩት አስተዳደራዊ ችግሮች የተነሣ፤ የተለያዩ በደሎች እየተፈጸሙ ነው፡፡ ምእመናንም ይህን በመመልከት ከቤተ ክርስቲያን እየራቁ ያሉ፣ ጥቂት አይደሉም፡፡ ‹‹ተሐድሶዎች›› በስውር የሚያደርጉትን እንቅስቃሴም ትኩረት ሊሰጡት ይገባል፡፡ ሌላው በቤተ ክርስቲያኗ ሥር ሰዶ የሚታየው የጎጥና የጎሳ ችግር ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን የሚሾመው መስፈርቱ ዕውቀቱ፣ በመንፈሳዊ ሕይወቱ እንጂ ከየትኛው ዘር የመጣ ነው የሚለው መቅደም የለበትም፡፡ ስለዚህ ተመራጩ ፓትርያርክ እነዚህን ሥር የሰደዱ ጉዳዮች የማስተካከል ትልቅ ሓላፊነት ይጠብቃቸዋል፡፡

             

            ሌላው ቃለ ዓዋዲው በሥራ እንዲተረጐም መሥራት ያለባቸው ይመስለኛል፤ በአሁኑ ወቅት በቤተ ክርስቲያን  ከቃለ ዓዋዲው ውጭ የሚሠሩ ሥራዎች እየበዙ መጥተዋል፡፡ ከቤተ ክርስቲያን አምባገነናዊ አሠራር መወገድ አለበት፡፡ አምባገነናዊ አሠራር ጥሩ ሙያ ያላቸውን፣ ለቤተ ክርስቲያን የሚያስቡ ቅን አገልጋዮችን ያርቃል፡፡ ተመራጩ ፓትርያርክም ሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ በላይ ለተዘረዘሩት ጉዳዮች ትኩረት በመስጠት፤ ቤተ ክርስቲያን ነጻነት ያለበት አመራር እንዲኖራት ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

             

            በሰንበት ትምህርት ቤት የተሰባሰብንም ወጣቶች የቤተ ክርስቲያናችንን ወቅታዊ ጉዳይ እየተወያየን ነው፡፡ ዘመኑ የቴክኖሎጂ በመሆኑ አብዛኛዎቹ ወጣቶች ስለ ቤተ ክርስቲያን  የተለያዩ መረጃዎችን ያገኛሉ፡፡ በዚህም  ምንማድረግ አለብን? የሚለው መወያያችን ሆኗል፡፡ የውይይታችን ጭብጥም እግዚአብሔር ጥሩ አባት እንዲሰጠን ከመመኘት አንጻር በመሆኑ በግልም፣ በጉባኤም ጸሎት እያደረግን ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም በሐመር መጽሔት ይህን መድረክ ከፍቶ ወጣቶች፣ ምእመናን፣ ለዚህች ቤተ ክርስቲያን ቅን የሚያስቡ ሁሉ አስተያየት እንድንሰጥ በማድረጉ በጣም እናመሰግናለን፡፡ ወደፊትም በዚሁ ይቀጥል እላለሁ፡፡

             

            • “በተፈጠረው ክፍተት ክፉዎች እየተጠቀሙበት ስለሆነ ዕርቁ ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል ”

            ዘሪሁን መንግሥቱ

            በመንበረ መንግሥት /ግቢ/ ቅዱስ ገብርኤል ገዳም

            ከዓምደ ሃይማኖት ሰንበት ት/ቤት

            ቤተ ክርስቲያናችን ፓትርያርክ እንዴት መመረጥ እንዳለበት ሁሉም ሕዝበ ክርስቲያን የሚያውቀው መመሪያ ሊzerehune mengestueኖራት ይገባል፡፡ ሰዎች በዘር፣ በጐጥ፣ በአካባቢ ፓትርያርክ ለማስመረጥ ጥረት እንደሚያደርጉ  አሁን ያለው ነባራዊ ሁኔታ ያሳያል፡፡ ይህ ደግሞ ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅም አይደለም፡፡ ሐዋርያትን የመረጣቸው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም የሚመሩ አባቶች የሚመርጥ እግዚአብሔር ነው፡፡

             

            ቤተ ክርስቲያን በታሪኳ ገጥሟት የማያውቀው ፈተና በዘመናችን ተከስቷል፡፡ ከምርጫው በፊት ዕርቁ መፈጸም አለበት፡፡  እንዲያውም ዕርቁ ዘግይቷል ነው የምለው፡፡ ቤተ ክርስቲያን አሐቲ ሆና ልጆቿ  በአመለካከት የተነሣ ተከፋፍለው “እኔ እገሌን ነው የምከተለው” የማለት አስተሳሰብ ተፈጥሯል፡፡ አባቶቻችን በአሁኑ ወቅት አንድ መሆን አለባቸው፡፡ ሐዋርያት በይሁዳ ምትክ ማትያስን ሲመርጡት እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው እንጂ ተከፋፍለው አልነበረም፡፡

             

            ቤተ ክርስቲያንን ለመታደግ በሁለቱም በኩል አባቶች  ወደ አንድ መምጣት አለባቸው፡፡  እዚህ ላይ መታየት ያለበት እስከ ዛሬ ዕርቅ ባለመፈጸሙ ምክንያት ጵጵስና የማይገባቸው ሰዎች ጵጵስና እንዲያገኙ ሆነዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ከመመሪያዋ፣ ከቃለ ዓዋዲዋ ከምትመራበት ሕግና ሥርዐት ውጪ እንድትመራ አድርገዋል፡፡ ይህ ክፍተት በመፈጠሩ የእኛን እምነት የማያምኑ ነገር ግን አማኝ መስለው ምእመናንን የሚያሳስቱ የተለያየ አጀንዳ ያላቸው ሰዎች ተጠቅመውበታል፡፡

             

            በምርጫው ላይ ትልቁ ድርሻ የጳጳሳቱ ነው፡፡ አባቶቻችን ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ማድረግ የሚገባቸው ብዬ የማስበው ምርጫው እንደ ሐዋርያት መሆን አለበት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በሚያዘው መሠረት ተተኪው ፓትርያርክ እንዲመረጥ ሁኔታዎችን ማመቻቸት አለባቸው፡፡ ሊቃውንት አባቶችም በፓትርያርክ ምርጫ ላይ የራሳቸው የሆነ አስተዋጽኦ አላቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ፈተና ሲገጥማት በችግሯ ጊዜ ሊሆን የሚገባውን ከመግለጽ ዝም ብለው በኋላ “እንዲህ አደረጉት፣ እኛ እኮ እንዲህ ብለን ነበር” ከማለት ይልቅ በዚህ ጉዳይ ላይ ምን መደረግ እንዳለበት ለምእመናኑ ግልጽ የሆነ ነገር ማስረዳት፣ ውዥንብሮችን ማጽዳት፣ ፓትርያርክ ለመምረጥ ከሕዝቡ ምን ይጠበቃል? የሚለውን ማስተማር አለባቸው፡፡ ይህን መሥራት ከሊቃውንቱ በተጓዳኝ ከሊቃነ ጳጳሳቱም ይጠበቃል፡፡ ካህናቱም “እገሌ ስለሚጠቅመኝ ይሾምልኝ፤ ነገ ዕድገት ይሰጠኛል” ብለው ለመሾም፣ ለመሸለም፤ የተለየ ነገር ለማግኘት ብለው ሳይሆን፤ በትክክለኛው ሥርዐት እንዲመረጥ እገዛ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ለንስሐ ልጆቻቸው በአገልግሎት ለሚያገኟቸው በርካታ ምእመናን  ከአሉባልታ በጸዳ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዐት ለምእመናን የመንገር ሓላፊነት አለባቸው፡፡

             

            ሰንበት ትምህርት ቤት በርካታ ወጣቶችን የያዘ ተቋም በመሆኑ፤ ወጣቱ ከምንም በላይ በፓትርያርክ ምርጫው ሂደት ላይ በንቃት እየተከታተለ ይገኛል፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤት ያሉ ወጣቶች ከሊቃውንቱ እግር ሥር ቁጭ ብሎ በመማር ከአባቶች የወረደውን መመሪያ ብዥታ ባልፈጠረ መልኩ ምእመናን የሚያውቁበትን መንገድ ማመቻቸት፤ ቴክኖሎጂውን በመጠቀም ለምእመናን ትክክለኛውን መረጃ በመስጠት ሂደት ላይ ሙያዊ እገዛ ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡

            ፓትርያርኩ ከተመረጡ በኋላ በመጀመሪያ የሚጠብቃቸው ሥራ ቤተ ክርስቲያኒቱን አንድ ማድረግነው፡፡ ሌላው መረጃን በተመለከተ ዛሬ የተለያዩ ወሬዎች እየተናፈሱ ነው፡፡ “እገሌ እንዲህ ነው፤ እገሌ እንዲህ ስለሆነ ነው…” የሚሉ ወሬዎችን ምእመናኑ ከማይመለከታቸው አካላት መረጃ እየሰሙ ነው፡፡  ለምሳሌ፡- ቤተ ክርስቲያንን የማያውቀው  ስለ ቤተ ክርስቲያን ሲጽፍ ይታያል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ስም ለማጉደፍና አባቶቻችን የሌሉበትን ስም እየሰጡ ለማጥፋት የሚጥሩ አካላት አሉ፡፡ ከዚያ ጐንም የተሰለፉ ምእመናንም አሉ፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን አደረጃጀቷ ምን እንደሚመስል፣ ምእመናኖቿ  ምን ዓይነት አገልግሎት መስጠት እንዳለባቸው፣ ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት ለመስጠት ተቋሞቹ እንዴት መደራጀት አለባቸው፤ ገዳማቶቿ እንዴት ቴክኖሎጂውን በመጠቀም መገናኘት አለባቸው? የሚሉ ጉዳዮች መልስ ከሚመረጡት አባት ይጠበቃል፡፡

             

            ሲኖዶሱም ጠንካራ መሆን አለበት፡፡ ውሳኔዎችን ከሥር ከሥር እየተከታተለ ተግባራዊ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ በእያንዳንዱ ሥራ አባቶች እታች እየወረዱ ማስፈጸም ላይጠበቅባቸው ይችላል፡፡ ከቅዱስ ሲኖዶስ ቀጥሎ አህጉረ ስብከቶች በተዋረድ የሚያስፈጽሙበትና ክትትል የሚደረጉበትን መንገድ ማመቻቸት ይጠበቅባቸዋል፡፡

             

            ተመራጩ ፓትርያርክ ይህን ትልቅ ሓላፊነት ለመወጣት በመጀመሪያ ያልተሠሩ ሥራዎችን መለየት፣ ቤተ ክርስቲያኗን ተጭነው ያሉ በዘልማድ የተቀመጡ አሠራሮችን ነቅሰው ማውጣት አለባቸው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ቢሮክራሲውን ማስወገድ፣ አስተዳደራዊ ቦታዎች በተማሩ እና በመንፈሳዊ ሕይወታቸው አርአያ በሚሆኑ  ሰዎች መተካት አለባቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ባስተማረቻቸው ልጆቿ ነው መተዳደር ያለበት እንጂ፤ እንደ ፓርላማ ኮታ “ከእገሌ ብሔር መቅረት የለበትም” በሚል ስሜት ቤተ ክርስቲያን መመራት የለባትም፡፡ ስለዚህ በአሁኑ ወቅት በየገዳማቱ፣ በየአድባራቱ የሚሾሙ በትክክል ተምረው ነው ወይ? የሚለውም መታየት ያለበት ጉዳይ ነው፡፡

             

            ሰንበት ት/ቤቶች በፓትርያርክ ምርጫው ላይ “የእኛ ሱታፌ ምንድን ነው?” በማለት እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነታችን መወያየት፣ የመፍትሔ ሐሳብ ማቅረብ ከሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ይጠበቃል፡፡

             

            • “ ‘እነ እገሌ ይመረጡልን’   የሚሉ ቡድኖችን ቅዱስ ሲኖዶስ ማዳመጥ የለበትም”

             

            ወጣት አንተነህ ዐወቀ

            በደብረ ገሊላ ቅዱስ አማኑኤል ካቴድራል

            ከእግዚአብሔር ምስሌነ ሰንበት ት/ቤት

            antenehe awekeምርጫው ከመደረጉ በፊት፤ መቅደም ያለበት ዕርቁ ነው፡፡ በተለይ በዚህ ዘመን ቤተ ክርስቲያን ለሦስት ተከፍላለች፡፡ እዚህ ባለው ሲኖዶስ የምትመራ ቤተ ክርስቲያን፣ ውጭ ባለው ሲኖዶስ የሚመራና እንዲሁም ገለልተኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተብሎ የሚታወቅ አለ፡፡ በዚህ ወቅት እነዚህ ሦስት ወገኖች ወደ አንድ መምጣት አለባቸው፡፡

             

            ቤተ ክርስቲያን መለያየት የለባትም፤ የቤተ ክርስቲያን አንድነት ለሀገር አንድነት ትልቅ ጥቅም አለው፡፡ ለምሳሌ፡- የኒቂያ ጉባኤ ስንመለከት፤ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ የአርዮስ ክህደት ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን፤ ለሀገርም ችግር ይፈጥራል ብሎ በማሰቡ አባቶች ተሰባስበው  ችግሩን እንዲፈቱ ያደረገበት ሁኔታ አለ፡፡ ስለዚህ አሁንም በውጭና በሀገር ውስጥ ባሉት አባቶች መካከል የተፈጠረው ችግር ሰላማዊ በሆነ ነገር መፈታት አለበት፡፡ ቤተ ክርስቲያን አንድ ስትሆን ነው በአንድነት መሥራት የሚቻለው፡፡ ስለዚህ ዕርቁ ከሁሉም በፊት ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል፡፡

             

            ለፓትርያርክ ምርጫው የጳጳሳቱ፣ የካህናቱ፣ የሊቃውንቱ፣ የሰንበት ት/ቤት አባላት፣ የምእመናኑ፣ የምሁራኑ ቤተ ክርስቲያኗ ጥሩ መሪ እንዲኖራት፣ ምእመናንን በአግባቡ መምራት እንድትችል የድርሻችንን አስተዋጽኦ ማበርከት እንችላለን ብዬ አስባለሁ፡፡ ወጣቱ ስለ ቤተ ክርስቲያን ዕለት ዕለት መረጃ የሚያገኝበት ቤተ ክርስቲያን ምን መሆን አለባት? የቀድሞ አባቶች ያሳለፉት ነገር ምንድን ነው? አሁንስ ያለው ነባራዊ ሁኔታ ምን ያሳያል? ወደፊትስ ምን መሆን አለበት? የሚለው ነገር በደንብ እየተረዳን ያለንበት ጊዜ ነው፡፡ ስለዚህ ለቤተ ክርስቲያን ይበጃል፣ ይጠቅማል የሚለውን  እንደየ ችሎታችን፣ እንደየ ዕውቀታችን፣ እንደየ አቅማችን ማድረግ የሚጠበቅብንን ነገር ሁሉ ማድረግ አለብን ብዬ አስባለሁ፡፡

             

            በሰንበት ትምህርት ቤት እርስ በእርስም ቢሆን ስለ ፓትርያርክ ምርጫ እንወያያለን፡፡ ዛሬ ወጣቱ በቤተ ክርስቲያን ዙሪያ ላይ በርካታ መረጃዎች በኢንተርኔት፣ በፌስ ቡክ፣ በተለያዩ ብሎጐች ያገኛል፡፡ ትናንት በነበሩ አባቶች ምን ተሠራ? ዛሬስ ያሉት ምን እየሠሩ ነው? የሚለውን እየተመለከትን ነው፡፡ ትናንት በቤተ ክርስቲያን ላይ ተፈጥሮ የነበረው ችግር ነገ እንዳይቀጥል የድርሻችንን አስተዋጽኦ እንዴት ማበርከት እንዳለብን ሁሌም በተገናኘን ቁጥር እናወራለን፡፡ ምናልባትም ይህ ወቅት ቤተ ክርስቲያን ትልቅ ራእይ ይዛ ለአገልግሎት የምትነሣበት ጊዜ ሊሆን ይችላል፡፡ እግዚአብሔር ፈቅዶና ወዶ አሁን የታሰበው ምርጫ ወደ ግቡ ደርሶ በጆሮአችን የምንሰማበት ደረጃ ከደረሰን ትልቅ ለውጥ ይኖራል፤ ከበፊቱም የተሻለ ነገር አለ ብዬ አስባለሁ፡፡ ወጣቱ የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ በአትኩሮት እንዲከታተል ያደረገው የሚሰማቸው፣ የሚያያቸው፣ እየተደረጉ ያሉ ትንሽም ቢሆን ፍንጭ የሚሰጡ ነገሮች ስላሉ ነው፡፡

             

            ፓትርያርኩም ከተመረጡ በኋላ ብዙ ከሚጠብቃቸው ሥራዎች ዋና ዋናዎቹ፡- በመጀመሪያ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ውስጥ ችግር ሆነው ያሉ ነገሮችን ለመቅረፍ መነሣት አለባቸው፡፡ ለቤተ ክርስቲያን ትልቅ ፈተና ሆኖ ያለው የዘረኝነትና የገንዘብ ጉዳይ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ክህነት በዘር ነበር፤ የሌዊ ወገን የሆነ ነበር የሚያገኘው፡፡ በሐዲስ ኪዳን ግን ክርስቶስ ራሱ ሊቅ ካህናት ሆኖ ያለ ዘር ሁሉም ለዚህ አገልግሎት የታጨና ብቁ ሆኖ የቀረበውን ቤተ ክርስቲያን በምትሰጠው መስፈርት የሚያሟላ ከሆነ ይሾማል፡፡ ስለዚህ ተመራጩ ፓትርያርክ ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ የዘረኝነት መንፈስ ማስወገድ ይጠበቅባቸዋል፡፡ በዚህ ዘመን መነኩሴው የመነኮሰው ከየት ነው? የት ነው የተማረው? ምንኩስናውን የሰጠው ማነው? የሚለውን ሊመለከቱ ይገባል፡፡ እነዚህ ነገሮች ዛሬ ካልጠሩ፣ ነገ እነዚህ መነኮሳት ናቸው አድገው የጵጵስናን ማዕረግ የሚያገኙት፡፡ ስለዚህ ምንጩና መነሻው ያልታወቀ መነኩሴ ነገ የጵጵስናውን መዓርግ አግኝቶ ለቤተ ክርስቲያን አደጋ የሚሆንበት ነገር እንዳይፈጠር በመነኮሳት አሿሿምና አገልግሎት ላይ ክትትል ሊያደርጉ ይገባል፡፡

             

            ዛሬ  በቤተ ክርስቲያን  ገንዘብ የዘረፈ፣ የአስተዳደር በደል ያደረሰ፣ መንጋውን ሳይመራ  በቤተ ክርስቲያን ላይ ችግር ሲፈጥር የነበረውን አባት ወደ ሌላ ቦታ ተወስዶ ይሾማል፡፡ ይህ የሚያሳየው በቀድሞው ቦታ ሲያጠፋ የነበረውን ጥፋት ሌላ ቦታ ሔዶ ይደግመዋል፡፡ ስለዚህ እንደዚህ ዓይነት አሠራሮች መቅረት መቻል አለባቸው፡፡ ዛሬ መንግሥት በሥራ ብልሹነት፣ በሙስና፣ በእምነት ማጉደል ከሓላፊነት የሚያነሣቸውን ሰዎች በሌላ ቦታ በሓላፊነት አይመድባቸውም እንዲቀጡ ያደርጋል እንጂ፤ በእኛም ቤተ ክርስቲያን እነዚህ ነገሮች መለመድ አለባቸው፡፡

             

            በአሁኑ ወቅት በቤተ ክርስቲያን ሁሉም አብያተ ክርስቲያናት የአንድ ክርስቶስ አካል እንደሆኑ ታስቦ ለአገልግሎት የሚያስፈልጉ ንዋየ ቅድሳትና በቂ መተዳደሪ ሀብት በእኩል መጠን ማግኘት ባለመቻላቸው ዕጣን፣ ጧፍ…፣ እንዲሁም አገልጋይ ካህናትም በማጣት እስከ መዘጋት የደረሱ አብያተ ክርስቲያናት አሉ፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ጥሩ ገቢ ኖሯቸው፣ ጥሩ ደመወዝ የሚያገኙ ገዳማት አድባራት አሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ የፋይናንስ አሠራሯን ማስተካከል ይጠበቅባታል፡፡ ተመራጩ ቅዱስ ፓትርያርክ ቤተ ክርስቲያን አንድ ወጥ የሆነ የፋይናንስ አያያዝ ሊኖራት እንደ ሚገባና የተቸገሩት እንዲረዱ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

             

            ሌላው ቤተ ክርስቲያን የምታደርጋቸውን ነገሮች ሁሉ የምንሰማው ከቤተ ክርስቲያን ሳይሆን፤ ከውጭ አካላት ነው፡፡ ለምሳሌ፡- በፓርላማ ስብሰባ ጊዜ “በፓርላማው እንዲህ፣ እንዲህ አንኳር ነገሮች ተነግረዋል፤ በእነዚህ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔዎች አሳልፏል፡፡ በማለት መገናኛ ብዙኃኑ ለሕዝቡ መረጃ ያቀብላሉ፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ግን በየጊዜው ምን እየተደረገ?  ምን እየተሠራ? እንዳለ አናውቅም፡፡ እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነታችን ግን ቤተ ክርስቲያኗ የሠራቻቸውን መስማት፣ ማወቅ ያለብን ከቤተ ክርስቲያኗ ነው፡፡ ተመራጩ ፓትርያርኩም ለዚህ ጉዳይ ትኩረት በመስጠት ወቅታዊ መረጃዎች ለምእመናን የሚደርሱበትን መንገድ ሊያመቻቹ ይገባል፡፡

             

            ስለ ነገዋ ቤተ ክርስቲያን ዕድገት ወጣቶችን የሚመለከተን በመሆኑ፤ በምን አቅጣጫ መሔድ፣ አስተዋጽኦአችንንም እንዴት ማበርከት እንዳለብን ከአባቶቻችን ጋር በመመካከር የድርሻችንን እንወጣ፡፡ ለቤተ ክርስቲያን ይበጃል የምንለውን ገንቢ የሆኑ አስተያየቶች አሁን በሐመር መጽሔት በሚሰጥበት አግባብ እንስጥ፡፡

            • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 20ኛ ዓመት ቁጥር 7 ኅዳር 2005 ዓ.ም.

            like kahenate hayle selasa

            ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ ምን ይላሉ?

            ታኅሣሥ  11 ቀን 2005 ዓ.ም.

            • “እግዚአብሔር ከእኛ በላይ የሚመለከታቸው አባቶች አሉ”

            ሊቀ ካህናት ኃይለ ሥላሴ ዓለማየሁ

            ከሰሜን አሜሪካ ከኮሎራዶ ስቴት

            like kahenate hayle selasaቤተ ክርስቲያን የሚጠብቅ የሚመራ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት ቅዱስ አባታችን በማረፋቸው የተነሣ ሀገራችን ትልቅ ሐዘን ላይ ናት፡፡ በዚህ ወቅት ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው  የጸሎቱ ጉዳይ ነው፡፡ እግዚአብሔር በመንበሩ ደግ አባት እንዲያስቀምጥ በጸሎት ሊለመን ይገባል፡፡ አሁን ቤተ ክርስቲያን ጥንቃቄ ልታደርግበት ይገባል ብዬ የማስበው በሰው ሰውኛ መንገድ በመጓዝ ለቤተ ክርስቲያን የሚሆነውን አባት ለመምረጥ ከተሞከረ ነው፡፡ እግዚአብሔር ሙሴን፣ አሮንን እንደጠራቸው ሁሉ የሚመረጡት አባት እግዚአብሔር የጠራቸው አባት እንዲሆኑ መጸለይ ያስፈልጋል፡፡ ሁላችንም ኢትዮጵያውያን ነን፤ ሁላችንም የቤተ ክርስቲያን ልጆች ነን፤ ሁሉም አባቶቻችን የቤተክርስቲያን አባቶች ናቸው፡፡ «እገሌ ከእገሌ» ሳይባል መንፈስ ቅዱስ የጠራው አባት ለዚህች ቤተ ክርስቲያን መሪ እንዲሆን መጸለይ ያስፈልጋል፡፡

             

            በሰው ሰውኛውን ተመልክተን “አቡነ እገሌ” ቢሆኑ ይሻላል የምንለው የሚጠቅም አይሆንም፡፡ እግዚአብሔር ከእኛ በላይ የሚመለከታቸው አባቶች ስለሚኖሩ “እገሌ ከእገሌ” ይሻላል ብሎ መምረጥ ያለበት እግዚአብሔር ነው፡፡ መብቱን ለመንፈስ ቅዱስ ከሰጠነው ትክክለኛ አባት ሊመርጥ ይችላል፡፡ ስለዚህ ሁላችንም በኅብረት ሆነን ሥራው ውጤታማ እንዲሆን መተባበር በምንችለው አቅም ማገልገል፣ መጸለይ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሥራ የሚጠቅም ይመስለኛል፡፡ ነገ ሊጸጽተን የሚችል ሥራ መሥራት የለብንም፡፡ ነገ የሚጸጽተን ሥራ መሥራት ቤተ ክርስቲያናችንን ሊጎዳ ይችላል፡፡ ሰው ይጠቅመኛል ብሎ የሚያስቀምጠው ሰው ሰውኛውን ይሆንና ቤተ ክርስቲያንን ሊጎዳ ይችላል፡፡ ትልቁ ነገር ቤተ ክርስቲያንን የማይጎዳ ሥራ መሥራት ነው፡፡ ይህ ሲሆን ነው እግዚአብሔር የሚያግዘን፣ በረከቱን የሚያበዛልን፡፡

             

            እግዚአብሔር ፈቅዶ በዚህ መንበር የሚያስቀምጣቸው አባት ቀዳሚ ሥራቸው እግዚአብሔር የሰጣቸውን መንጋ መሰብሰብ ነው፡፡ የትናንትናው ዘመን ከዛሬው ዘመን የተለየ ስለሆነ ዘመኑን መዋጀት ያስፈልጋል፡፡ ዘመኑን መዋጀት ሲባል አንድ አባት ብቻቸውን የሚሠሩት ነገር አይደለም፡፡ የመንፈሳዊ አባታችን እጅ፣ እግር፣ ዐይን እኛ ልጆቻቸው ስለሆን ልጆቻቸውን አስተባብረው አንድ አድርገው ሊመሩ ይገባል፡፡ ይህች ቤተ ክርስቲያን የአንድነት፣ የሰላም ምሳሌ ናት፡፡ ለኢትዮጵያ አንድነቷ፣ ሰላሟ፣ መሠረቷ ይህች ቤተ ክርስቲያን ስለሆነች፤ ሰላሙ ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል፡፡ ማንም ቢሆን ከዚህች ቤተ ክርስቲያን እንዲወጣ የሚፈልግ የለም፡፡ ክርስቶስ ደሙን ያፈሰሰው፣ መሥዋዕት የሆነው፣ ቀራንዮ ላይ የዋለው ለዓለሙ ሁሉ እንጂ ለተወሰኑ ሰዎች አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ጠላቶች የሏትም ሁሉም የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ጠላት የሆኑ ካሉ ደግሞ በተቻለ መጠን ማስተማር ቅድሚያ ይሰጠዋል፡፡

             

            ተመራጩ ፓትርያርክ ቅዱስ  ሲኖዶስን አስተባብረው ቤተ ክርስቲያንን የሚጠብቁ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ ዛሬ የምትጠብቃቸው ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ከእነዚህም አንዱ የውጪ መንጋ ነው፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ የአብነት ትምህርት ቤቶች፣ ስብከተ ወንጌል አገልግሎት፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ወዘተ የመጠበቅ ትልቅ ሓላፊነት አለባቸው፡፡ ፓትርያርኩ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጋር ተባብረው ቅዱስ ሲኖዶስ በሚያወጣው ሕገ ደንብ መሠረት በመገዛት የቅዱስ ሲኖዶስ ወሳኔ አስፈጻሚ እየሆኑ ይህን ተግባር ማከናወን ይጠበቅባቸዋል፡፡ ስለዚህ ተመራጩ አባት ያለባቸው ሓላፊነት ቀላል አይደለም፡፡ ይህንንም ከአንድ ሰው ብቻ የምንጠብቀው ነገር አይደለም፡፡ ሁላችንም ተባብረን የድርሻችንን ስንወጣ የሚመረጡት አባት ሓላፊነታቸውን መወጣት ይችላሉ፤ ትልቁ ሓላፊነት የቅዱስ ሲኖዶስ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡

             

            • “በሁለቱም አባቶች ዘንድ እርቁ ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል”

            መላከ ጽዮን በላቸው ወርቁ

            በሰሜን አሜሪካ በኒዮርክና

            አካባቢው ሀገረ ስብከት የራችስተር

            ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም

            ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ

            የቤተ ክርስቲያኒቱ የእርቅና የሰላም ጉዳይ እጅግ በጣም አንገብጋቢና ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አባቶች በአስተዳደራዊmelake tsyone ምክንያት ተለያይተው በተፈጠረው ችግር በአሜሪካን በሚኖሩ ካህናት፣ ወጣቶች ምእመናን ዘንድ እጅግ በጣም ከፍ ያለ የመለያየት መንፈስ ፈጥሯል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መጠናከር በአንድነት መሥራት ሲገባ፤ በአንጻሩ ክፍተት ተፈጥሮ እርስ በርስ ካለመግባባት የተነሣ ለቤተ ክርስቲያን ጠላቶች በር የከፈተ ጉዳይ ሆኗል፡፡ እርቀ ሰላሙን ለመፈጸም የማንም ተፅዕኖ ሳይኖር በአባቶች ተነሣሽነት ቁርጥ ውሳኔ ያስፈልጋል፡፡ ለትውልድ፣ ለታሪክ ሲባል በፍቅር፣ በሰላም፣ በአንድነት ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግሉ ሕዝቡን ለማዋሐድ በአባቶቻችን በኩል የተፈጠረውን ችግር በእነርሱ በኩል መፍትሔ እንዲያመጣ መከናወን አለበት፡፡

             

            በአሜሪካን ሀገር በእርቅ ኮሚቴው የሚሳተፉ ሰዎች በአቀረቡልን ጥያቄ መሠረት የማኅበረ ቅዱሳን አባላት፣ በየቀጠና ማእከላቱ በየአጥቢያው የገንዘብም የዐሳብም አስተዋጽኦ እያደረጉ ነው፡፡  ባለን ሚዲያ፣ በድረ ገጽም ሆነ በሌሎች ለእርቁ ትኩረት በመስጠት ጽሑፎችን በማዘጋጀት፤ በትምህርተ ወንጌሉም በዚሁ ርእሰ ጉዳይ ላይ አተኩረን  እየሠራን ነው፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በማረፋቸው በዐቃቤ መንበር የሚመራ በቅዱስ ሲኖዶስ ተሠይሟል፡፡ በዚህ ሂደትም ውስጥ ተጀምሮ የነበረው እርቅ ትኩረት ተሰጥቶት በሁለቱም አባቶች ዘንድ የመጀመሪያ አጀንዳ ሆኖ እርቁ ቢፈጸም ሁላችንንም የሚያስደስት ነው፡፡

             

            ቤተ ክርስቲያን የራሷ ቀኖና አላት፡፡ መንፈሳዊ አባቷን በቀኖናዋ መሠረት ምርጫዋን ትፈጽማለች፡፡ ከምርጫው በፊት ሊታዩ የሚገባቸው ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህም የቤተ ክርስቲያን ሕግ፣ ደንብና መመሪያው ለምርጫው በግልጽ ተቀምጦ (መስተካከል ካለበት የሚስተካከለው ታይቶ) በአግባቡ ምሉዕ እንዲሆን ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ ኖሮበት ምርጫው እንዲከናወን ቢደረግ፡፡ ሌላው ከምርጫው በፊት ሌሎች ሊከናወኑ የሚገባቸው ሂደቶችም ካለፈው የተማርናቸው ስሕተቶች ምንድን ናቸው) ብሎ ቅዱስ ሲኖዶስ ሊያያቸው የሚገባቸው ነገሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ የቅዱስ ፓትርያርኩ የሥራ ሓላፊነት ዝርዝራቸው በቀኖናው ላይ ተጠቅሷል፡፡ በግልጽ ያልሰፈረ ካለ ከምርጫው በፊት የቤተ ክርስቲያኒቷ ሕግ ከመንበረ ፓትርያርኩ ጀምሮ በአደረጃጀቱ፣ በአወቃቀሩ ታች ድረስ ምሉዕ ሆኖ የሥራ ሓላፊነቱ ጭምር በግልጽ ተዘጋጅቶ ቢጸድቅ፤ የማንም ተፅዕኖ ሳይኖርበት የሚመረጠው አባት እግዚአብሔር ያስቀመጠው ስለሚሆን ሊፈጠሩ ይችላሉ ብለን የምንሰጋቸው ክፍተቶች  ይቀንሳሉ፡፡ በዚህም በኩል የምእመናን ተሳትፎ የጎላ መሆን አለበት፡፡ ቃለ  ዐዋዲው በአጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ ምእመናን ያላቸውን ቦታ ያመለክታል፡፡ ከሁሉም በላይ ምርጫው እስኪከናወን ድረስ ሱባኤ ገብተው ለእግዚአብሔር ጸሎት ማድረስ አለባቸው፡፡ እግዚአብሔር ምርጫውን ሙሉ በሙሉ ገብቶ እንዲያከናውነው፣ እንዲያስፈጽመው መደረግ አለበት፡፡

             

            ቀጣዩ ተሿሚ ፓትርያርክም ቦታ መንፈሳዊ ልጆቹን  በሰላም፣ በፍቅር፣ በአንድነት የሚያስተሳስር፤ የቤተ ክርስቲያኒቱን ዶግማና ቀኖና በትክክል ጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፍ የሚያደርግ፣ ትምህርተ ወንጌልን የሚያስፋፋ፣ ስብከተ ወንጌልን የሚያጠናክር የቀደሙት የቤተ ክርስቲያን አባቶች ጀምረዋቸው የነበሩ ሥራዎች ማጠናከር በተለይም ገዳማትና የአብነት ትምህርት ቤቶች መርዳት ይጠበቅባቸዋል፡፡

             

            በገጠር በካህን እጥረት ምክንያት ብዙ አብያተ ክርስቲ ያናት እየተዘጉ ነው፡፡ በአንጻሩ ደግሞ በከተማ አካባቢ በርካታ ካህናት ተከማችተው ይታያሉ፡፡ የገጠሯ ቤተ ክርስቲያን እንዳትዘጋ ትኩረት መስጠት ካህናቱ ማእከላዊ በሆነ አስተዳደር እንዲተዳደሩ ማድረግ፤ ተተኪው ትውልድ ወጣት ከመሆኑ አንጻር ጊዜውን፣ ጉልበቱን፣ ሕይወቱን ሰጥቶ ቤተ ክርስቲያን ላገልግል የሚለውን በመምራት፣ መንገድ ማሳየት ይጠቅቸዋል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን የውስጥ ጠላት የሆኑ መናፍቃን፣ ተሐድሶዎች  ቀዳዳ፣ ክፍተት ፈልገው የበግ ለምድ ለብሰው ቤተ ክርስቲያን በመግባት ሃይማኖቷን፣ ዶጋማዋን እንዳይቆነጻጽሉ ሥርዐቷን እንዳያፈርሱ መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡

             

            ዘመኑን በተከተለ የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር እንዲኖራት ትኩረት ሰጥቶ የገንዘብና የንብረት አስተዳደሯን በአግባቡ በሕግና በሥርዐት የሚመራ ባለሙያዎችን በየደረጃው ማስቀመጥ ይኖርባቸዋል፡፡ በአጠቃላይ ከላይ የተጠቀሱትንና ቤተ ክርስቲያኒቱንና አሁን የጀመረቻቸውን መልካም እሴቶች የሚያበረታታ፤ ካህናቱ ከምእመናኑ ጋር ያላቸው ውሕደትና ጥምረት አጣጥሞ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ 21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የማሻገር ሓላፊነት ከአዲሱ ቅዱስ ፓትርያርክ የሚጠበቁ ናቸው ብዬ አምናለሁ፡፡

             

            • “ኦርቶዶክስ ተዋሕዶን በገጠር የሚያስፋፋት አባት እንጠብቃለን”

            ቀሲስ ታምራት

            ከጎሬ

            kesis tamerateየፓትርያርክ ምርጫ ቤተ ክርስቲያናችን በመንፈስ ቅዱስ ስለምትመራ ነገሮቹን ሁሉ ለመንፈስ ቅዱስ አሳልፎ መስጠት ያስፈልጋል፡፡ ያ ማለት ደግሞ ከካህናት አባቶች፣ ከእያንዳንዳዱ ክርስቲያን፣ ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ከሰባክያን ብሎም ከሲኖዶስ ምርጫው የተሳካ ይሆን ዘንድ በጸሎት ድጋፍ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

             

            በዚህ ዘመን ለቤተ ክርስቲያን የሚበጃት ዓለሙን ሊዋጅ የሚችል ታሪኳን፣ ትውፊቷን፣ ሃይማኖቷን  ጠብቆ ለሚቀጥለው ትውልድ ማስተላለፍ የሚችል አባት እንዲመረጥ እያንዳንዱ ሰው ገንቢ ያልሆነ አስተያየት ከመስጠትና ከዘረኝነት ነጻ ሆኖ እግዚአብሔርን ብቻ አስቦ ምርጫው በተስፋ ሊጠብቅ ይገባል፡፡

             

            አሁን የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን የሚመሩ አባት ፓትርያርክ እንደሚታወቀው ከፊት ለፊታችንጠ እግዚአብሔር ቢፈቅድ ይመረጣል፡፡ የሚመረጡት አባት ደግሞ ምን ማድረግ አለባቸው) ከሚመረጡት አባት ምን ይጠበቃል) የሚለውን ጉዳይ  እኔ በሁለት መልኩ ነው የማየው፡፡ የመጀመሪያው በሞት ያለፉት ቅዱስነታቸው ጀምረዋቸው ያሉ መልካም እሴቶች አሉ፡፡ ከእነዚህም አንዱ ቤተ ክርስቲያናችንን በዓለም ደረጃ ዕውቅና እንድታገኝ አድርገዋታል፡፡ የሚመረጡት ፓትርያርክ ይህንኑ ተግባር ለዓለም የማሳወቅ፣ የማስቀጠል ሥራ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሁለተኛው ቤተ ክርስቲያኒቱ ባሳለፈችው ሁለት ሺሕ  ዓመታት ውስጥ ሐዋርያዊ ተልእኮዋ ስንመለከት እንደ ዕድ ሜዋ የሚያረካ አገልግሎት ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍል ያደረሰ አይደለም፡፡ ያም ከተለያዩ ምክንያቶች  የተነሣ ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ አሁን ተመራጩ ፓትርያርክ ይህንን ክፍተት ለመሙላት እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የሚችሉትን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

             

            በገጠር አካባቢ የሚገኙ ምእመናን የተጠናከረ አገልግሎት አላገኙም፡፡ የገጠሯ ቤተ ክርስቲያንም ተዘግታ ያለችበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በሰፊው እየተካሔደ ያለው በከተማ አካባቢ በመሆኑ፤ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የከተማ ሃይማኖት እየሆነች አገልግሎቷ በከተማ ብቻ እንዲወስን የሚያደርጋት አጋጣሚ እየመጣ ነው፡፡ እኛ ከተማ ከተማውን  እየሠራን ሌሎች ቤተ እምነቶች ደግሞ ገጠር ገጠሩን እየሠሩ ቤተ ክርስቲያናችን ከተማ ላይ እየቀረች ገጠሩን ለሌሎች አሳልፈን እየሰጠን ነው፡፡

             

            ስለዚህ ቅዱስ ሲኖዶስ አሁን የሚመረጡት አባት የቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ መዋቅር አስተካክለው ቤተ ክርስቲያን ያላትን የገንዘብም ሆነ የሰው ሀብት ልማት በትክክል በሥራ ላይ ማዋል፤ አገልግሎቷም በገጠር እንዲስፋፋ የሚያደርጉ አባት ቢሆኑና ሲኖዶሱም ሕገ ደንቡን አክብሮ የሚመራ መሆን አለበት፡፡ ይህን የሚያደርግ አባት እግዚአብሔር እንደሚሰጠን አምናለሁ፡፡

             

            • “ጥሩ አሠራር የሚዘረጋ አባት ያስፈልገናል”

            ኅብስተ ኪዳነ ማርያም

            ከደሴ

            hebesta kidanemaryameቅዱስ አባታችን በማረፋቸው ምክንያት ቅዱስ ሲኖዶስ ፓትርያርክ ለመምረጥ በዝግጅት ላይ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዚህ ሂደት ምእመናንና ካህናቱን የሚያስተዳድር አባት እግዚአብሔር እንዲሰጠን መጸለይ አለብን፡፡

             

            በፓትርያርክ ምርጫ ላይ ወገንተኛ መሆን ተገቢ አይደለም፡፡ ምእመናን፣ ወጣቶችም አንዱን ወገን መደገፍ ሳይሆን ለቤተ ክርስቲያን የትኛው ይጠቅማል የሚለውን ማሰብ አለብን፡፡ ስለዚህ ችግሮችን የሚፈቱ ጥሩ አሠራር የሚዘረጉ አባት እንዲመረጡ እግዚአብሔርን በጸሎት እንጠይቃለን፡፡

             

            ስለ ግብፅ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የተጻፉ መጻሕፍትን ስናነብ ግብፃውያን  አባቶችና ምእመናኑ ያላቸው ግንኙነት፣ አባቶች ያላቸው ትጋት፣ ምእመናኑ እንዴት እንደሚጠብቁትና እንደሚንከባከቡት  ስናነብ በጣም ያስቀናል፡፡ እኛስ መቼ ነው እንደዚህ የምንሆነው የሚል ቁጭት በውስጤ አለ፡፡ የእኛም አባቶች ለወጣቱ ትውልድ ቤተ ክርስቲያን በደንብ የማሳወቅ፣ አባቶችና የንስሐ ልጆች ግንኙነት እንዲጠናከር፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ያለው አሠራር ግልጽ እንዲሆን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ የሚመረጠው ፓትርያርክ ከላይ እስከታች አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ድረስ ያለው ምእመናን ቤተ ክርስቲያን በቂ አገልግሎት እንዲያገኝ ምእመኑም በመንፈሳዊ ሕይወቱ አዲስ አሠራር መዘርጋት አለባቸው፡፡ ይህን ያህል ፐርሰንት አስገብተዋል፣ ይህን ያህል አማኞች አሉ የሚለው የቁጥር ሪፖርት በቂ አይደለም፡፡ በእውነት የተመዘገቡ ቤተ ክርስቲያን የምታውቃቸው ምእመናን፣ አስተዋጽኦቸው በአግባቡ እያበረከቱ ያሉ ምን ያህል ክርስቲያኖች አሉ? ስንቶችን ካለማመን ወደ ማመን አምጥተናል? የሚሉ ጉዳዮች ትኩረት ሊሰጥባቸው የሚገቡ ናቸው፡፡

             

            ከዚህም በተጨማሪ ቅዱስ ሲኖዶስ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን ማጠናከር፣ ሰበካ ጉባኤ በልማት እንዲሳተፉ፣ ትምህርት ቤቶች፣ አጸደ ሕፃናት እንዲስፋፋ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ በአንዳንድ ቦታዎች አብነት ትምህርት ቤቶች እየተዘጉ፤ መምህራኑ ጉባኤያቱን እያጠፉ ወደ ከተማ እየተሰደዱ ነው፡፡ ይህን በደንብ አጥንቶ ሊሟሉ የሚገባቸውን ነገሮች በማሟላት ጉባኤያቱ እንዳይፈቱ ማድረግ ከተመራጩ ፓትርያርክና ከቅዱስ ሲኖዶስ የሚጠበቅ ተግባር ነው፡፡

            • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 20ኛ ዓመት ቁጥር 5 መሰከረም 2005 ዓ.ም.