asebot

ሰበር ዜና

የካቲት 21/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ

የጥንታዊው አሰቦት ገዳም ደን ዳግም የእሳት አደጋ ቃጠሎ ደረሰበት፡፡

asebot

የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድስት ሥላሴና አባ ሳሙኤል ገዳም ደን ትላንት የካቲት 20 ቀን 2004 ዓ.ም. ባልታወቀ ምክንያት በተነሣ እሳት ቃጠሎ ደረሰበት፡፡

ትላንት ከቀኑ 5፡00 ሰዓት የተነሣው እሳት እስከአሁን ድረስ ያልጠፋ መሆኑንን የገለጹት የገዳሙ አገልጋይ አባ ወልዴ እንዳሉት እሳቱ እየተስፋፋ ከደኑ አልፎ ወደ ቅድስት ሥላሴ የአባቶች ገዳም እየተቃረበ መሆኑንን ገልጸዋል፡፡

እሳቱን ለማጥፋት የአካባቢው ገበሬ ማኅበር ጥረት እያደረገ ቢሆንም ከውኃ እጥረትና ከሰው ኀይል ማነስ የተነሣ ይህ ዜና እስከ ተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ እሳቱ አለመጥፋቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

ዝርዝርሩን እንደደረሰን እናሳውቃለን፡፡

Derej A5

የመባዕ ሳምንት

Derej A5

abune abusade

ብፁዕ አቡነ አብሳዲ አረፉ

የካቲት 13/2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

abune abusadeብፁዕ አቡነ አብሳዲ በተወለዱ በ92 ዓመታቸው ቅዳሜ የካቲት 10/2004 ዓ.ም. ለእሑድ አጥቢያ በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡ ብፁዕነታቸው በትግራይ ክፍለ ሀገር ሽሬ በ1912 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ በ1926 ዓ.ም ከሽሬ ወደ ኤርትራ በመሔድና ደብረ ማርያም ገዳም በመግባት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመከታተል ዲቁናን ከብፁዕ አቡነ ይስሐቅ፣ ቅስናን ደግሞ ከአቡነ ማርቆስ ተቀብለዋል፡፡ በደብረ ማርያም ገዳም ውስጥ በቆዩባቸው ዐሥር ዓመታት ውስጥ ከአንድ መቶ በላይ ዲያቆናትንና ካህናትን በማስተማር አፍርተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ አብሳዲ በ1943 ዓ.ም በሱዳን በኩል ወደ ኢየሩሳሌም በእግራቸው የሔዱ ሲሆን፤ በግብጽ ለሁለት ዓመታት ለመቆየት ችለዋል፡፡ ከ1959 ዓ.ም. ጀምሮ ከ60 ዓመታት በላይ በኢየሩሳሌም የኖሩ ሲሆን ጥር 30 ቀን 1983 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በኤጲስ ቆጶስነት ከተሾሙት ጳጳሳት መካከል አንዱ ናቸው፡፡ በኤጲስ ቆጶስነት እንደተሾሙ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ረዳት ኤጲስ ቆጶስ ሆነው እስከ ዕለተ እረፍታቸው ድረስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ላይ ይገኙ ነበር፡፡

በቆይታቸውም በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ይዞታ የሆኑትን አብያተ ክርስቲያናትና ገዳማትን ለማስከበር ከፍተኛ ጥረት ያደረጉና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሟገት የተጣለባቸውን ሓላፊነት በመወጣት ሰፊ ሥራ ሠርተዋል፡፡ ብፁዕ አቡነ አብሳዲ ዕብራይስጥንና አረብኛ ቋንቋዎችን አቀላጥፈው ይናገሩም ነበር፡፡

ከቡኢ ምድረ ከብድ የሚወስደው መንገድ አገልግሎት መስጠት ጀመረ

የካቲት 13/2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

በጉራጌ ሀገረ ስብከት የሶዶ ወረዳ ዋና ከተማ ከሆነችው ቡኢ ከተማ ጀምሮ ምድረ ከብድ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ ገዳም ድረስ የሚወስደው የ18 ኪ.ሜትር ጥርጊያ መንገድ በፌደራል መንገዶች ባለሥልጣን መሥሪያ ቤት ሙሉ ትብብር ሥራው ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን የገዳሙ አበምኔት አባ አብርሃም ወ/ኢየሱስ ገለጹ፡፡

ከዚህ ቀደም ይኸው መንገድ በአካባቢው ምእመናን አማካይነት በእጅ ቁፋሮ፣ ድንጋይ በመሸከምና ከጉልበት እስከ ገንዘብ አስተዋጽዖ በማድረግ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነበር፡፡ ነገር ግን ከጊዜ ብዛት በመበላሸቱ በመኪናም ሆነ በእግር ወደ ገዳሙ ለመሔድ እጅግ አስቸጋሪ ሆኖ ቆይቋል፡፡ በዚህም ምክንያት ወደ ገዳሙ ለክብረ በዓላትም ሆነ ለጉብኝት የሚመጡ ምእመናን በመቸገራቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ ቁጥራቸው እየቀነሰ መጥቷል፡፡

 

ሙሉ ወጪውን በመሸፈን መንገዱን በጥሩ ሁኔታ ሠርቶ ያስረከበውን የፌዴራል መንገዶች ባልሥልጣንን በእግዚአብሔር ስም ያመሰገኑት አበምኔቱ በመንገዱ መበላሸት ምክንያት ተቋርጦ የነበረውን የምእመናንና የገዳሙን ግንኙነት ለማጠናከር ይረዳል ብለዋል፡፡

 

ቀደም ሲል ገዳሙ ሰፊ የእርሻ መሬት ርስት የነበረው በመሆኑ በገዳሙ ውስጥ የሚገኙ መነኮሳትና መነኮሳይያት እርሻ በማረስና ሰብሎችን በመዝራት የጓሮ አትክልቶችን በማልማት ይተዳደሩ እንደነበር የገዳሙ አበምኔት ተናግረው፤ በአሁኑ ወቅት ግን ገዳሙ በቂ የእርሻ መሬት የሌለው በመሆኑ መተዳደሪያ ያደረገው በዓመት ሁለት ጊዜያት ጥቅምት 5 እና መጋቢት 5 በጻድቁ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ ዓመታዊ ክብረ በዓላት ከሚመጡ ምእመናን ከሚለግሱት የገንዘብና መባ አስተዋጽኦ ብቻ እንደሆነ የገዳሙ አበምኔት ጨምረው ገልጸዋል፡፡ ገዳሙ የልማት ሥራዎችን በመሥራት ለማጠናከርና በውስጡ የሚኖሩት መነኮሳት በችግር ምክንያት እንዳይበተኑ እንዲሁም ጥንታዊነቱንና ታሪካዊነቱን ጠብቆ ለማቆየት ከምእመናን ብዙ እንደሚጠበቅና በክብረ በዓላትም ሆነ በማንኛውም ጊዜ ገዳሙ ያለበትን ሁኔታ መጥተው በማየት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ አሳስበዋል፡፡

 

ገዳሙ በንጉሥ ላሊበላ ዘመነ መንግሥት  በራሳቸው በጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የተመሠረተ ሲሆን በጾምና ጸሎት የተጋደሉበት እንዲሁም ያረፉበት እንደሆነ ይታወቃል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የቅድስት ቤተልሔም የመጻሕፍት ቤትና የጉባኤ ቤት ተመረቀ

የካቲት 12/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ

{gallery count=1 width=275 height=225 counter=1 links=0 alignment=right animation=3000}Beteleheme{/gallery}በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ፕሮጀክት የተገነባው በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት በታች ጋይንት ወረዳ የምትገኘው የድጓ ማስመስከሪያ ቅድስት ቤተልሔም ቤተ ክርስቲያን የመጻሕፍት ቤትና የጉባኤ ቤት ተመረቀ፡፡

የካቲት 4 ቀን 2004 ዓ.ም በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ እንድርያስ የተመረቀው ይኸው መጻሕፍት ቤትና ጉባኤ ቤት ሙሉ ወጪውን የላስ ቬጋስ ምእመናን በዋናነት መሸፈናቸው ታውቋል፡፡

 

ኅዳር 26 ቀን 2003 ዓ.ም. የመሠረት ድንጋይ ተጥሎ በአንድ ዓመት ውስጥ የተጠናቀቀውን ግንባታ አስመልክቶ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ ሲናገሩ የአብነት ትምህርት ቤቶች ለቤተ ክርስቲያናችን ህልውና ከፍተኛ ጠቀሜታ ያላቸው ናቸው፡፡ በመሆኑም ማኅበረ ቅዱሳን በዚህ ረገድ እያደረገ ያለው አስተዋጽዖ ቀላል የሚባል አይደለም” በማለት አመስግነዋል፡፡

 

በዕለቱ አጠቃላይ የሥራ ሒደቱን ዝርዝር ሪፖርት ያቀረቡት የድጓ ምስክር መምህር የሆኑት ሊቀምሁራን ይትባረክ ካሳዬ እንዳሉት “በግንባታው ምክንያት በተፈቀደልን ቦታ ላይ ፕሮጀክት ተቀርጾ የደብሩ ማኅበረ ካህናት፣ የድጓ አድራሾቹ ሁላችን ልማት እያለማን እራሳችንን የምንችልበት መንገድ ይፈልግልን፤ እስከ አሁን ለጉባኤ ቤታችን ለተደረገልን ሁሉ ማኅበረ ቅዱሳንን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም እናመሰግናለን” ብለዋል፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት የቅስቀሳና ገቢ አሰባሳቢ ክፍል ሓላፊ ዲያቆን ደረጀ ግርማ በበኩሉ ማኅበሩ በቀጣይም ከቅድስት ቤተልሔም የድጓ ማስመስከሪያ ጎን በመሆን በጋራ ችግሮቹን በመፍታት እንደሚሠራ ጠቁሞ የገንዘብ ድጋፍ ያደረጉ የላስቬጋስ ምእመናንንና የአካባባውን ማኅበረሰብ ስለቀና ትብብራቸው አመስግኗል፡፡

 

በዕለቱም በድጓ ያስመሰከሩ የተወሰኑ አድራሾችና በግንባታው በጎ እንቅስቃሴ የነበራቸው ምእመናን ከብፁዕ አቡነ እንድርያስ እጅ የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡ በቅድስት ቤተልሔም የድጓ ማስመስከሪያ በሀገራችን ብቸኛው ማስመስከሪያ መሆኑ ይታወሳል፡፡

ኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅት 49ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን አከበረ፡፡

የካቲት 9/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ምእመናን መታሰቢያ ድርጅት ለኢየሩሳሌም የካቲት 4 ቀን 2004ዓ.ም የተመሠረተበት 49ኛ ዓመት በዓል   ለድርጅቱን መሥራች ክብር አቶ መኮንን ዘውዴ  የመታሰቢያ ሐውልት ቦሌ ሩዋንዳ በሚገኘው መሰብሰቢያ አዳራሽ በር ላይ በማቆም ጭምር ተከብሯል፡፡

በ1955 ዓ.ም. ሚያዝያ 3 ቀን ከሠላሳ በማይበልጡ ኢትዮጵያውያን ወገኖች እንደተመሠረተ የሚነገረው መታሰቢያ ድርጅቱ በክብር አቶ መኮንን ዘውዴ ጠንሳሽነትና አሰባሳቢነት እንደሆነ ይነገራል፡፡ በወቅቱ ቅዱሳን መካናትን ለመሳለም ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም የሔደው የምእመናን ቡድን በዚያ ያለውን ችግርና በገዳማቱ የሚኖሩ አባቶችና እናቶችን በደልና ስቃይ ተመልክቶ የነበረ ሲሆን በተለይ የዴር ሱልጣን ገዳማችን ወደ ጥንቱ ይዞታ ለመመለስ ካልተቻለበት ምክንያቶች አንዱ ከኢትዮጵያ ገዳማውያንን ለመጎብኘት የሚመጣ ሰው የለም የሚል ምክንያት እንደሚሰጥ መረዳታቸው ለድርጅቱ መመሥረት ምክንያት እንደሆነ ተገልጿል፡፡

ክብረ በዓሉን በንግግር የከፈቱት የድርጅቱ ምክትል ሊቀመንበር ኮሎኔል ተፈራ ይገዙ “የድርጅታችን የተመሠረተበትን 49ኛ ዓመት በምናከብርበትና በተልይም የታሪኩ ባለቤት ለሆኑት ክቡር አቶ መኮንን ዘውዴ የተሠራውን የመታሰቢያ ሐውልት በሚመረቅበት በዚህ ዕለት የተሰማንን ከፍተኛ መንፈሳዊ ደስታ ስንገልጽ ኩራት ይሰማናል” ብለዋል፡፡ “ሰው ለታሪክ የተፈጠረ እንጂ ታሪክ ለሰው አልተፈጠረም ያሉት ምክትል ሊቀ መንበሩ በ1955 ዓ.ም በኢየሩሳሌም ገዳማት የሚደርሰው በደል አሳዛኝ ታሪክ መነሻነት በብሔራዊና በመንፈሳዊ ስሜት በመቆርቆር ከብዙ ጥረትና ድካም በኋላ በርካታ አባላትን በማሰበሳብና የገዳማችንን ታሪክ በማስረዳት ለዚህ የቀደሰ ዓላማ ድጋፍ ለመስጠት ቃል የገቡትን ሰዎች ይዘው የኢየሩሳሌምን መታሰቢያ ድረጅትን የመሠረት ድንጋይ ሚያዝያ 16 ቀን 1956 ዓ.ም ያስቀመጡ የመጀመሪያው ታላቅ ሰው ከመሆናቸውም በላይ የድርጅቱን ዓላማ በተግባር በማዋል ከምንም አንስተው አሁን ያለበት ደረጃ እንዲደርስና በዓለም አቀፍ ደረጃም እውቅና እንዲያገኝ ያደረጉ ታላቅ አባት ናቸው” ብለዋል፡፡

 

ክቡር አቶ መኮንን ዘውዴ በተለይ የዴርስልጣን ገዳማችንን በተመለከተ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ተቃዋሚ ወገኖች አጋጣሚ እየጠበቁ ሁከትና ውዝግብ በሚፈጥሩበት ወቅት ፈጥኖ በመድረስና በየቀጠሮም ቀን ከገዳም አባቶች ጋር  በእስራኤልአገር ፍርድ ቤት በመገኘትና ከአባቶች ጎን በመቆም ከፍተኛ የሞራልና የገንዘብ እርዳታ በየጊዜው ለገዳሙ እንዲሰጥ በማድረግ የሀገርና የቤተክርስቲያን ባለውለታ መሆናቸው ተወስቷል፡፡

 

 

በመክፈቻው ንግግራቸው ምክትል ሊቀመንበሩ ኮሎኔል ተስፋዬ ድርጅቱ ያከናወናቸውን ዋና ዋና ተግባራት የገለፁ ሲሆን “በጋምቤላ ክልል የሚገኙ ወጣቶችን ለማስተማርና በመንፈሳዊ ሕይወት ለማደራጀት በቤተ ክርስቲያን የተነደፈውን እቅድ በመደገፍ የጎዳና ተዳዳሪዎችን ችግር ለማስወገድ መንግሥት በልማት እንዲሳተፉ ለሚያደርገው እንቅስቃሴ የ700,000 ብር ድጋፍ በመንግሥትና በህዝብ ከፍተኛ ትኩረት የተሰጠውን የሕዳሴ ግድብ ሥራ የግማሽ ሚሊዮን ብር ቦንድ ያለ ወለድ ግዥ በማድረግ  ድርጅቱ  በኢየሩሳሌም ብቻ ሳይወሰን በአገር ውስጥም ለታሪክና መንፈሳዊ ሥራዎች ድጋፍ በመስጠት ላይ ነው” ብለው በተለይ በተፈጥሮ አደጋ ሳቢያ ወላጆቻቸውን ያጡ ሕፃናትን አሰባስቦ በረጲ፣ በአለም ከተማ፣ በደብረ ብርሃን የሕፃናትን በማስተማርና በመንከባከብና በአሁኑ ወቅት ዘላቂነት ያለው ሥራ ለመሥራት የ800,000 ብር ፕሮጀክት በመቅረጽ ውጤታማ ተግባር ለማከናወን በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል” ብለዋል፡፡

በበዓሉ ላይ የተገኙት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ ርዕስ ሊቃነ ጳጳሳት ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ኘሬዝዳንት የዓለም ሃይማኖቶች ለሠላም የክብር ኘሬዝዳንት “ክቡር አቶ መኮንን ዘውዴን የማውቃቸው የትምህርት ሚኒስቴር በነበሩበት ወቅት ነው፤ ያስተማሩኝ፣  በአዳሪ ትምህርት ቤትም እንድንማር ያደረጉኝ ታላቅ ሰው ናቸው” ያሉት ቅዱስነታቸው ለትውልድ ታሪክንና ክብርን ላቆዩ ስሞች ክብር ይገባቸዋል ለእኝህ አባት መታሰቢያ ሐውልት እንዲያቆምላቸው ድርጅቱ መወሰኑና ታሪክን ለትውልድ እንዲቆይ በማድረጉ ሊመሰገን ይገባዋል፡፡ መልካምነታቸውን ለትውልድ ልናስተላልፍ ይገባናል) ድርጅቱም አገልግሎቱን አጠናክሮ በመላው ዓለም ጽ/ቤት ከፍቶ ሊሠራ ይገባል” ብለዋል፡፡

የክቡር አቶ መኮንን ዘውዴ የመታሰቢያ ሐውልት ምረቃ ላይ ቅዱስ ፓትሪያርኩን ጨምሮ ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች፣ የክቡር አቶ መኮንን ባለቤት ከነ ቤተሰቦቻቸው፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና የድርጅቱ አባላት ተገኝተዋል፡፡ በበዓሉ ላይም የቅዱስ ኡራኤል ሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን መዝሙር ያቀረቡ ሲሆን ቅድስት ሀገረ ኢየሩሳሌምን በማስመልከት ትምህርት ተሰጥቷል፡፡

IMG_0715

ጦምን አስመልክቶ የቅዱሳን አባቶች አስተምህሮ

የካቲት 9/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

“በጦም ወቅት አንድ ክርስቲያን  በፈቃደኝነት አንድ በጎ ሥራን  ጎን ለጎን ቢፈጽም መልካም ነው፡፡ ነገር ግን ከሰዎች ምስጋናን ወይም አንዳችን ነገር ሽቶ የሚጦም ከሆነ ግን ጦሙ በእግዚአብሔር ዘንድ የማይወደድ ጦም ይሆንበታል፡፡ ማንኛውም በጎ ሥራ ስንሠራ ለእግዚአብሔር አምላካችን ካለን ፍቅር የመነጨ ይሁን፡፡ እንዲያ ካልሆነ ግን እግዚአብሔርን ደስ ልናሰኝ አይቻለንም፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስን ጌታችን በመንጎቹ ላይ ሲሾመው ለእርሱ ያለውን ፍቅር ተመልከቶ ነበር፡፡ እግዚአብሔን የሚያፈቅር ሰው የሚፈጽማቸው የትኞቹም በጎ ሥራዎች በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደዱለት ይሆኑለታል፡፡ ፍጹማንም ናቸው፡፡ ስለዚህም ማንኛውንም በጎ ሥራዎቻችንን ስነሠራ እርሱን በማፍቀር ላይ የተመሠረቱ ይሁኑ፡፡”

“አንድ ሰው ምንም እንኳ መላ የሕይወት ዘመኑን በትኅርምት ሕይወት መምራት ያለበት ቢሆንም በዚህ በዐቢይ ጦም ግን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ኀጢአቱን  ለካህን ተናዝዞ ለድሆች ምጽዋትን በማድረግ በአግባቡ ሊጦም ይገባዋል፡፡ እነዚህን ዐርባ የጦም ቀናት በአግባቡ በጎ ሥራዎች አክለንባቸው የጦምናቸው እንደሆነ ቸሩ ፈጣሪያችን ዓመት ሙሉ ባለማወቅ የፈጸምናቸውን ኀጢአቶቻችንን ይደመስስልናል፡፡ (ዮሐንስ አፈወርቅ )

IMG_0715ነገር ግን ብዙዎቻችን በጦም ራስን መግዛትን ከምንለማመድ ይልቅ ለሥጋ ምቾቶቻችን መትጋታችን የሚያስገርም ነው፡፡ እኛ ለራሳችን የተጠነቀቅን መስሎን ደስታን ይፈጥሩልናል የምንላቸውን ምግቦችንና መጠጦችን አብዝተን እንበላለን እንጠጣለን፡፡ … ነገር ግን መጨረሻችን ሕማምና ስቃይ ይሆንብናል፡፡ የሥጋን ምቾት የናቁና በጦም በጸሎት እንዲሁም በትኅርምት ሕይወት መንፈሳዊ ሕይወታቸውን የሚመሩ ቅዱሳን ግን ሥጋና ነፍሳቸውን ሕያዋን አድርገው በመልካም ጤንነት ያኖሯቸዋል፡፡ በተድላና በምቾት ይኖር የነበረው ሰውነታችን በሞት ሲያንቀላፋ ከውስጡ ከሚወጣው ክፉ ጠረን የተነሣ ሽቶ በራሱ ላይ እናርከፈክፍበታለን፡፡ ነገር ግን የቅዱሳን ሰውነት በሕይወት ሳሉም ቢሆን በሞት ከሥጋቸው መልካም መዓዛ ይመነጫል፡፡ ይህ እጅግ ድንቅ የሆነ ነገር ነው ፡፡ እኛ ለሥጋችን ምቾት በመጠንቀቅ ራሳችንን ስናጠፋ እነርሱ ግን ሥጋቸውን ለነፍሳቸው በጦምና በጸሎት በማስገዛታቸው ሥጋቸውን ይቀድሷታል፡፡ የነፍሳቸውን በጎ መዓዛ በመጠበቃቸውም ሥጋቸው መልካም መዓዛን እንድታፈልቅ ሆነች፡፡

ነፍሳችን ንጽሕናዋን በጦም ካልጠበቀች በቀር ቅድስናዋን በኀጢአት ምክንያት ማጣቱዋ የማይቀር ነው፡፡ ያለጦም የነፍስን ንጽሕና ጠብቆ መቆየት የማይሞከር ነው፡፡ ሥጋም መንፈስ ለሆነችው ነፍሳችን መገዛትና መታዘዝ አይቻላትም፡፡ አእምሮአችንም በምድራዊ ምቾቶቻችን ስለሚያዝብን ከልብ የሚፈልቅ ጸሎትን ማቅረብ አይቻለንም፡፡ ስለዚህ ሥጋችን ነፍሳችንን በስሜት ስለሚነዳት ነፍስ እውር ድንብሯ በፍርሃት ወደ ማትፈቅደው ትሔዳለች፡፡ በአእምሮአችን ውስጥ ክፉ ዐሳቦች ተቀስቅሰው ኅሊናችንን ያሳድፉታል፡፡ ስለዚህም የእግዚአብሔር ጸጋ ከእኛ ትወሰዳለች፡፡ ስለዚህም በግልጥ አጋንንት እንደ ፈቀዱት ነፍሳችንን ተሳፍረው ወደ ኀጢአት ይመሩዋታል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐርባ ቀንና ዐርባ ሌሊት ከጦመ በኋላ ተራበ፡፡ ሰይጣንም ወደ እርሱ ይቀርብ ዘንድ መራቡን ገለጠለት፡፡ እንዲህ በማድረግም ጠላታችንን እንዴት ድል እንደምንነሳው በእርሱ ጦም አስተማረን፡፡ ይህ አንድ ጦረኛ ላይ የሚታይ የአሰለጣጠን ስልት ነው፡፡ ለተማሪዎቹ ጠላትን እንዴት ድል መንሳት እንደሚቻል ሊያስተምር ሲፈልግ ለጠላቱ ደካማ መስሎ ይታየዋል፡፡ ጠላቱም የተዳከመ መስሎት ሊፋለመው ወደ እርሱ ይቀርባል፡፡ እርሱም በተማሪዎቹ ፊት ከጠላቱ ጋር ውጊያን ይገጥማል፡፡ ጠላትን በምን ድል መንሳት እንደሚችል በእውነተኛ ፍልሚያ ጊዜ በተግባር ያስተምራቸዋል፡፡ በጌታ ጦም የሆነውም ይህ ነው፡፡ ጠላት ሰይጣንን ወደ እርሱ ለማቅረብ መራቡን ገለጠ፡፡ ወደ እርሱም በቀረበ ጊዜ የእርሱ በሆነ ጥበብ በመጀመሪያውም፣ በሁለተኛውም፣ በሦስተኛው፣ ፍልሚያ በመሬት ላይ ጥሎ ድል ነሳው፡፡

እየጦምህ ነውን? ጦምህን በሥራ ተግብረህ አሳየኝ፡፡ ድሀ አይተህ እንደሆነ ራራለት፡፡ ወዳጅህ ከብሮ እንደሆነ ቅናት አይሰማህ፡፡ አፋችን ብቻ አይጡም፤ ዐይናችንም፣ ጆሮአችንም፣ እግራችንም፣ እጃችንም፣ የሰውነት ክፍሎቻችንም ሁሉ ክፉ ከመሥራት ይጡሙ፡፡ እጆቻችን ከስስት ይጡሙ፤ እግሮቻችን ኀጢአትን ለመሥራት ከመፋጠን ይጡሙ፡፡ ዐይናችም የኀጢአት ሥራዎችን ከመመልከት ይጡሙ፡፡  ጆሮዎቻችንም ከንቱ ንግግሮችንና ሐሜት ከመስማት ይከልከሉ፡፡ አንደበቶቻችንም የስንፍና ንግግርንና የማይገቡ ትችቶችን ከመሰንዘር ይቆጠቡ፡፡ ወንድማችንን እያማን ከዓሣና ከእንስሳት ተዋጽኦዎች መከልከላችም ምን ይረባናል? (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)

የማኅበሩን አገልግሎት ለማገዝ የማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት ተመሠረቱ

የካቲት 9/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

በማኅበረ ቅዱሳን ለሀገር ውስጥ ማእከላትና የግቢ ጉባኤያት ማ/ማስተባበሪያ ዋና ክፍል ተጠሪ የሆኑ 6(ስድስት) ማስተባበሪያ ጽ/ቤቶች ተቋቋሙ፡፡

ማኅበሩ አገልግሎቱን ይበልጥ አጠናክሮ ለማገልገል የተሰጠውን መንፈሳዊና ማኅበራዊ ሓላፊነት ለመወጣት የማስተባበሪያ ጽ/ቤቶች ሚናቸው ከፍተኛ መሆኑን ነው የተገለጸው፡፡

መቀመጫቸው የሰሜን ማእከላት ማስተባበሪያ በመቀሌ፣ የሰሜን ምዕራብ ማእከላት ማስተባበሪያ በባሕርዳር፣ የምዕራብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በጅማ፣ የደቡብ ማእከላት ማስባበሪያ ጽ/ቤት በአዋሳ የምሥራቅ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በድሬደዋና የመሀል ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት አዲስ አበባ ላይ መሆኑ ታውቋል፡፡

ጥር ፳6 እና ፳7 ቀን ፳፻4 ዓ.ም ማእከላት የማስተባበሪያ ጽ/ቤት ምስረታ ላይ የማስተባበሪያ ጽ/ቤት የሚያካልላቸው ማእከላት በተገኙበት ተመስርተዋል፡፡ በምስረታ መርሐ ግብሩ ላይ የማስተባበሪያ ማእከላቱ ጽ/ቤት ተግባርና ሓላፊነት እንዲሁም የሕዝብ ግንኙነት አገልግሎት በማኅበረ ቅዱሳን ምን መምሰል አለበት በሚሉ ርዕሰ ጉዳይ የስልጠናና የውይይት መርሐ ግብር ተካሔዷል፡፡

15 አባላት ያሉት የማስተባበሪያ ጽ/ቤት አስፈጻሚ አካላት የሀገር ውስጥ ማእከላትና ግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ክፍል ጨምሮ በዋና ማእከል ከሚገኙ ዋና ክፍሎች ጋር ግንኙነት በማድረግ ለሚከናወኑ ተግባራት ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር እንደሚሠሩ ይጠበቃል፡፡

333 (2)

ስትተባበሩ ሁሉንም ታሸንፋላችሁ /ለሕፃናት/

የካቲት 8/2004 ዓ.ም.

በቴዎድሮስ እሸቱ

ልጆች እንደምን ሰነበታችሁ ከዚህ በታች ያለውን ተረት በደንብ አንብቡ በርካታ ቁም ነገሮችን ታገኙበታላችሁ መልካም ንባብ፡፡
ከእለታት አንድ ቀን በአንድ ሀገር የሚኖር ሰው ነበር ይህ ሰው ዘጠኝ ልጆች ሲኖሩት ሁሉም እርስ በራሳቸው የማይዋደዱ የማይስማሙ ነበሩ333 (2) ሁሉም አባታቸው የሚያወርሳቸውን የራሳቸውን ድርሻ ይዘው ለብቻቸው መኖር ይፈልጉ ነበር፡፡ ከዚያም አንድ ቀን አባታቸው በጠና ታሞ አልጋ ላይ ተኛ ልጆቹንም ጠራቸውና አንድ ትእዛዝ አዘዛቸው ትእዛዙም “ሁላችሁም ሒዱና ለየራሳችሁ አንድ አንድ ጭራሮ ይዛችሁ ኑ” የሚል ነበር፡፡ ከዚያም ልጆቹ ወደውጪ ሔደው ለየራሳቸው አንድ አንድ ጭራሮ ይዘው ተመለሱ፡፡

 

አባታቸውም ታላቁን ልጅ ጠርቶ የያዝከውን ጭራሮ ስበረው አለው ታላቁ ልጅም ጭራሮዋን ቀሽ አድርጎ ሰበራት እንዲህ እንዲህ እያሉ ሁሉም ልጆች የየራሳቸውን ጭራሮዎች ሰበሯቸው፡፡ ከዚያም አባትየው ትልቁን ልጅ ጠራውና የሁሉንም ወንድሞችህን ጭራሮ ሰብስብ አለው፡፡ታላቁ ልጅም የሁሉንም ጭራሮ ተቀብሎ ሰብስቦ ያዘ አባትየውም በል አሁን የያዝካቸውን ጭራሮ አንድ ላይ ስበራቸው አለው፡፡

22ታላቁ ልጅም ቢሞክር ቢሞክር ቢታገል ጭራሮዎቹን ሊሰብራቸው አልቻለም ሁሉም ልጆች ቢሞክሩ አንድ ላይ የተሰበሰቡትን ጭራሮዎች ሊሰብሯቸው አልቻሉም ከዚያም አባትየው ልጆቹ ወደእርሱ እንዲጠጉ በምልክት ጠራቸውና እንዲህ ብሎ ነገራቸው፡፡

ልጆቼ በመጀመሪያ ሁላችሁም የያዛችኋቸውን ጭራሮዎች በቀላል ሰበራችኋቸው በኋላ ግን333 (1) አንድ ላይ ሲሰበሰቡ ከእናንተ ውስጥ ማናችሁም ልትሰብሩ አልቻላችሁም፡፡ እናንተም የምትለያዩ ከሆነ አንድ ላይ የማትሆኑ ከሆነ ጠላት በቀላሉ ያጠፋችኋል ሌባ ይዘርፋችኋል፤ ጠንካራና ጎበዝ ልትሆኑ አትችሉም፡፡ አንድ ላይ ከሆናችሁ ግን ማንም አይደፍራችሁም፡፡ አሁን እኔ ልሞት ነው የማወርሳችሁን ሀብት በጋራ ተጠቀሙበት በመካከላችሁ መለያየት እንዳይኖር አደራ አላቸው፡፡ ከዚያም ትንሽ ቆይቶ ሞተ እነሱም ከዚያች ዕለት በኋላ ሳይጣሉ እርስ በእርስ በመዋደድ በፍቅር አንድ ላይ መኖር ጀመሩ ተባብረው ስለሚሠሩም ሀብታምና ጠንካሮች መሆን ቻሉ፡፡

ልጆቼ እነዚህ ወንድማማቾች ባይተባበሩ ኖሮ ጠንካሮች መሆን አይችሉም ጠላትም በቀላሉ ያጠቃቸዋል፡፡ እናንተም ከጓደኞቻችሁ በመጠየቅ ለጓደኞቻችሁ የምታውቁትን በማስረዳት ልትተባበሩ ይገባል በትብብር ስታጠኑ የሚከብዳችሁ ሁሉ ይቀላችኋል፡፡

IMG_0038

ምክረ አበው በሐዊረ ሕይወት

  • “ሐዊረ ሕይወት ከመንፈሳዊ ጉዞዎች ሊጠበቁ የሚገባቸውን ተግባራት የሚያመለክት ነው”

የካቲት 5/2004 ዓ.ም

በዲ/ን ኅሩይ ባየ

IMG_0038ማኅበረ ቅዱሳንን ከአባላቱ ውጭ ካሉ ምእመናን ጋር የሚያገኘው መድረክ እንደሆነ ይታመናል ሐዊረ ሕይወት መንፈሳዊ ጉዞ፡፡ ከ4 ሺሕ ምእመናን በላይ ይሳተፉበታል ተብሎ ለሚጠበቀው የዘንድሮው ጉዞ ከማንኛውም ጊዜ በላይ በተቀናጀና በተደራጃ መንገድ ዝግጁቱን ለማሳካት ሙሉ ጊዜውን ሰጥቶ የሚያስተባብር አገልጋይም ተመድቧል፡፡ በአገር ቤት ያሉትን ምእመናን ብቻ ሳይሆን ባሕር አቋርጠው ሰማይን ጠቅሰው ለሚመጡ ምእመናን ሁኔታዎች ተደላድለውላቸዋል፡፡ የዘንድሮው ሐዊረ ሕይወት ከወትሮው በምን ይለያል? የሚሉ እና ተያያዥ ጥያቄዎችን እንዲመልሱልን የጉዞውን መርሐ ግብር የሚያስተባብሩትን ዲያቆን ሙሉዓለም ካሳን የመካነ ድራችን እንግዳ አድርገናቸዋል ተከታተሉን፡፡

መካነ ድር፡- እስኪ አጠር አጠር ካሉ ጥያቄዎች ልጀምርና ጉዞው መቼ ይደርጋል? ስንት ቀንስ ይፈጃል?

 

ዲ/ን ሙሉዓለም፡- ጉዞው መጋቢት 2 ቀን 2004 ዓ.ም ይከናወናል፡፡ መርሐ ግብሩም ደርሶ መልስ ነው፡፡

 

መካነ ድር፡- የዘንድሮው ጉዞ ወደየት ነው የሚደረገው?

 

ዲ/ን ሙሉዓለም፡- ጉዞው በደብረ ብርሃን መስመር ወደ በኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ይደረጋል፡፡

 

መካነ ድር፡– በኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም የተመረጠበት ልዩ ምክንያት አለ?

 

ዲ/ን ሙሉ ዓለም፡- ባለፈው ዓመት ከተመለከትነው ልምድ በመነሣት የዚህን ዓመት ጉዞ ምቹና ተስማሚ ለማድረግ ጥረት በማድረግ ላይ እንገኛለን፡፡ በዚህ ዓመት በርካታ ቁጥር ያላቸው ምእመናን ይዘን እንጓዛለን፡፡ በመሆኑም እስከ 4000 ምእመናን እንደሚጓዙ ይጠበቃል፡፡ ስለዚህ ይህን በርካታ ቁጥር ሊያስተናግድ /ሊቀበል/ የሚችል የተመቸ መልክዐ ምድር ያስፈልጋል፡፡ በአንጻሩም አቅመ ደካማ ሰዎች በጉዞው መሳተፍ ቢፈልጉ ደርሰው በጊዜ ወደ ቤታቸው የሚመለሱበትን ሁኔታ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ ሁሉ በተለየ መልኩ ደግሞ በተመረጠው ደብር አካባቢ ካሉት አድባራትና ገዳማት በኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በጥንታዊነቷና በታሪካዊነቷ በውስጧ ከያዘቻቸው የአብነት መምህራንና ደቀመዛሙርት ቀዳሚ በመሆኗ መርጠናታል፡፡

 

መካነ ድር፡- ሐዊረ ሕይወት ማለት ምን ማለት ነው?

 

ዲ/ን ሙሉዓለም፡- ሐዊረ ሕይወት የሚሉ ሁለቱ ቃላት ከግእዝ ቋንቋ የተወሰዱ ናቸው፡፡ ሙሉ ትርጉማቸውም የሕይወት ጉዞ ማለት ነው፡፡ እንደሚታወቀው በዓለማችን የሚከናወኑ የተለያዩ የጉዞ ዓይነቶች አሉ አንድ ሰው ለመዝናናትም ይሁን ዘመድ ለመጠየቅ ወይም ደግሞ አገር ለማየት ይጓዛል፡፡ ያ ጉዞ ሥጋዊና ምድራዊ ጉዞ ነው፡፡ መንፈሳዊ ጉዞ ቀድሞ በብሉያት እንደተፈጸመው በዘመነ ሐዲስም አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የፋሲካን በዓል ለማክበር ከናዝሬት ወደ ኢየሩሳሌም እንደተጓዘው እሱን አብነት አድርገን እንጓዛለን፡፡ በዓላትን ለማክበር ቅዱሳት መካናትን ለመሳለም ከቦታውም በረከት ለማግኘት እንሔዳለን፡፡ ይህ ጉዞ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ የምናገኝበት ጉዞ ስለሆነ ሐዊረ ሕይወት /የሕይወት ጉዞ/ የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡

መካነ ድር፡- የዘንድሮው ጉዞ ዝግጅትና ዓላማስ ምን ይመስላል?

ዲ/ን ሙሉዓለም፡- ስለ ዝግጅቱ ከመናገሬ በፊት ስለጉዞው ዓላማ ከመናገር ብጀምር ይሻላል፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት “ስም ግብርን ይገልጠዋል” ተብሎ እንደተጻፈው ጉዞው ሥጋዊ ሳይሆን መንፈሳዊ ዓላማን ይዞ የተዘጋጀ መርሐ ግብር ነው በመሆኑም በሥራ ቦታ በመኖሪያ አካባቢ ባለው ውጣ ውረድ ሁከተ ኅሊና ያጋጥማል፡፡ በተለያየ ምክንያት የተጨነቀና የዛለ አእምሮ በእንደዚህ ዐይነት ጉዞ ይታደሳል፡፡ ቃለ እግዚአብሔር ሲነገርም በተከተተ ልቡና ማዳመጥ ያመቻል፡፡ በእንደዚህ ዐይነት ቦታና ሁኔታ የሚነገር ቃለ እግዚአብሔር ወደ ውስጥ ዘልቆ ይገባል የንስሐ ፍሬንም ያፈራል፡፡ ከቦታውም በረከት ያስገኛል፡፡ በዚያውም በተለያየ አጋጣሚ የእግዚአብሔር ቃል ይሰበካል፡፡ በተለየ አጋጣሚ  የምእመናን መንፈሳዊ ሕይወት ለማጠንከር ለመንፈሳዊ ዓላማ ታስቦ የተዘጋጀ እንዲሆን ታስቦ የተዘጋጀ መርሐ ግብር ነው፡፡ በተጨማሪም ከመንፈሳዊ ጉዞ ምን ተግባራት እንደሚጠበቁና ጉዞውን ለሚያዘጋጀው ተቋም የሚያስፈልገውን ሥርዐት ለማመልከትም ያግዛል ተጓዦች በአካል በአእምሮ በነፍስ ተዘጋጅተው በቅዱስ ቦታ ማድረግ ያለባቸውን ጥንቃቄ ያስተምራል፡፡ የጉዞው ዓላማ ሥጋዊ ጥቅምና ቁሳዊ ትርፍ ለማግኘት ታስቦ የተዘጋጀ መርሐ ግብር አይደለም ዋናውና ተቀዳሚ ዓላማችን መንፈሳዊ ትርፍ እንጂ ሥጋዊ ትርፍ አይደለም፡፡

 

ዝግጅቱን በተመለከተ ጉዞው የተሳካ እንዲሆን አባቶች በጸሎት እንዲያስቡን አሳስበናል፡፡ የጉዞውን ትኬት በአካል በስልክ በአጭር የስልክ መልእክትና በኢ-ሜል ለማግኘት መረጃ ለሚጠይቁ ምእመናን ተፈላጊውን መረጃ ለመስጠት የሙሉ ጊዜ አገልጋይ ተመድቧል፡፡ በጉዞው የሚሳተፉት አዲስ አበባ የሚገኙ ምእመናን ብቻ አይደሉም ከክፍለ ሀገርና ከውጭ ሀገር የሚመጡ ተጓዦች ስለሚኖሩ በጉዞው መርሐ ግብር እንዴት መሳተፍ እንደሚችሉ ከወዲሁ ግንዛቤ በመስጠት ላይ እንገኛለን፡፡

መካነ ድር፡– የጉዞ ቲኬቶችን የት ማግኘት ይቻላል?

 

ዲ/ን ሙሉ ዓለም፡- በአዲስ አበባ ያሉ ምእመናን 5 ኪሎ ሸዋ ዳቦ ፊትለፊት በማኅበረ ቅዱሳን ሐመርና ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ማከፋፈያ ሱቅ፣ እሳት አደጋ ፊት ለፊት በቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን፣ በቂርቆስ የገበያ አዳራሽ ብሎክ A ቁጥር 230፣ ጎፋ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አካባቢ፣ ኮልፌ አጠና ተራ እፎይታ ገበያ ፊት ለፊት ሳሪስ ማከፋፈያ አዲሱ ሰፈር፣ መርካቶ ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን ሕንፃ ሥር፣ አምስት ኪሎ በማኅበረ ቅዱሳን ሕንፃ ሥር ንዋየ ቅዱሳት መሸጫ፣ ዓለም ፀሐይ ድልድይ ፊት ለፊት፣ ኪዳነ ምሕረት ከፍተኛ ክሊኒክ፣ መርካቶ ኬኔዲ ሕንፃ 1ኛ ፎቅ እቴነሽ የሕንጻ መሣሪያ ቁጥር 107ና ኮስሪሞ ላንድ አውቶብስ ተራ ትልቁ መናኸሪያ ፊት ለፊት ማግኘት ይቻላል፡፡

 

ከክፍለ ሀገር ለሚመጡ ተጓዦች በየርእሰ ከተማቸው ባለው የማኅበረ ቅዱሳን ማእካላት ጽ/ቤት ቲኬቶች ተዘጋጅተዋል፡፡ ከውጭ ሀገር መምጣት ለሚፈልጉ ምእመናንም http://www.hawirehiywet.somee.com መመዝገብ ይችላሉ፡፡ የውጭ ሀገር ተመዝጋቢዎች ስለ ጉዞው ትኬት ክፍያ በተመለከተ በኢ-ሜይል መልእክት መለዋወጥ ይቻላል፡፡

 

መካነ ድር፡- በጉዞው የሚቀርቡ መርሐ ግብሮች ምንድን ናቸው?

 

ዲ/ን ሙሉዓለም፡- በኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም እንደደረሰን ጸሎተ ቅዳሴውን እናደርሳለን፡፡ ከቅዳሴ ውጭ በቤተ ክርስቲያኑ ካህናት ሊቃውንትና ደቀ መዛሙርት ጋር በመሆን የጋራ ጸሎት እናደርሳለን በመቀጠል በማኅበርና በግል የተጋበዙ ዘማርያን ያሬዳዊ መዝሙር ያቀርባሉ፡፡ በገና ደርዳሪዎችም የበገና መዝሙር ያሰማሉ ከዚያም በሊቃውንት አባቶቻችን ትምሕርተ ወንጌል ይሰጣል፡፡ በመጨረሻም ትምህርት ያከናወኑ፣ ምሥጢር ያደላደሉ፣ በእድሜ የበሰሉ በመከራ የተፈተኑ አባቶቻችን የምክር አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ ምክረ አበው በምእመናን በጣም የሚወደድና የሚናፈቅ መርሐ ግብር በመሆኑ ሰፋ ያለ ጊዜ ተሰጥቶታል፡፡ በዚህ መርሐ ግብር የምእመናን ጥያቄ ይመለሳል፡፡ ሕይወታቸውም ይስተካከል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡ በተዘጋጀው የጉዞ ትኬት ላይ እንደተገለጠው ምእመናን ጥያቄያቸውን በስልክ፣ በኢ-ሜይል በአጭር የሞባይል መልእክት በተለይም በአካል በመቅረብ ጥያቄአቸውን ማቅረብ ይችላሉ፡፡

 

መካነ ድር፡- ከተጓዦች የሚጠበቀው ነገር ምንድን ነው?

 

ዲ/ን ሙሉዓለም፡- በጉዞው ሊደረጉ ስለሚገባቸው ዝግጅቶች ከሞላ ጎደል በትኬቶች ላይ ተገልጠዋል፡፡ ሆኖም ለማስታወስና ትኩረት ልንሰጣቸው የሚገቡ ነገሮችን ማስታወስ እንወዳለን፡፡ የመጀመሪያው የጊዜ አጠቃቀማችን ሥርዓታዊ መሆን አለበት፡፡ ከአዲስ አበባ የምንነሣበት ሰዓት ከንጋቱ 12 ሰዓት ከ30 ላይ ነው፡፡ ከዚህ የጊዜ ገደብ ቀድመንም አንነሣም ዘግይተንም አንጓዝም ስለዚህ በተቻለ መጠን ተጓዞች ሰዓት አክብረው እንዲገኙ እናሳስባለን፡፡ ሁለተኛው ማንኛውም ዐይነት ጽሑፍ ያላቸውን ቲሸርቶች ለብሶ መምጣት አይቻልም፡፡ ከዚህ በተረፈ አለባበሳችን ክርስቲያናዊ መሆን አለበት፡፡ በመጨረሻም አስተባባሪዎች የሚነግሩንን እየሰማን ምንም ዐይነት መጠባበቅ ሳይኖር በተመደብንበት መኪና በተሰጠን ሰዓት መገኘት ከተጓዦቻችን ይጠበቃል፡፡

 

መካነ ድር፡- የዘንድሮው ሐዊረ ሕይወት ካለፈው ዓመት ሐዊረ ሕይወት በምን ይለያል?

 

ዲ/ን ሙሉዓለም፡- የዘንድሮው ሐዊረ ሕይወት በርካታ አዲስ ነገሮችን ይዟል በእውነት ለመናገር የአሁኑ ሐዊረ ሕይወት የተደራጃና የተጠናከረ ነው፡፡ በዚህ ዓመት ለመርሐ ግብሩ ስኬት ሲባል ዝግጅቱ ቀደም ተብሎ ተጀምሯል፡፡ ሰፊ የዝግጅት ጊዜ መኖሩ በርካታ ሥራዎችን ለማከናወን ያመቻል ሌላም ባለፈው ዓመት ለመርሐ ግብሩ ሲባል ዝግጅቱ ቀደም ተብሎ ተጀምሯል፡፡  ሌላው ባለፈው ዓመት ባደረግነው ጉዞ የተሰጡን አስተየየቶች ነበሩ፡፡ እነዚያ አስተየየቶች በአሁኑ ጉዞ ተስተካክለውና ታርመው አገልግሎት ላይ ይውላሉ፡፡ ለምክረ አበው የሰጠነው ጊዜ ሰፊ መሆኑም በራሱ አንድ አዲስ ነገር ነው ከሁሉም በላይ የምእመናን ቁጥር በ1ሺሕ ጨምሯል፡፡ ባለፈው ዓመት 3000 የሚሆኑ ተጓዦች ነበሩ አሁን ግን የምእመናን ቁጥር በ1000 ልዩነት 4000 ይሆናል፡፡ የምዝገባው አተገባበርም ቢሆን የተሳለጠና የተመቻቸ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ከጅማ፣ ከመቀሌ ከአፋርና ከናዝሬት የመጡ ተጓዦች ነበሩ፡፡ አሁን ግን ከእሩቅ ሀገር ለሚመጡ ምእመናን የአዳር መርሐ ግብር አዘጋጅተናል በአጠቃላይ ጉዞው እስኪጠናቀቅ ድረስ ራሱን የቻለ ጽ/ቤት፣ መደበኛ አገልጋይ፣ መኖሩ፡፡ ትምህርቶች በብሉቱዝና በሲዲ ወጪውን የሚሸፍንልን ካገኘን ለማሠራጨት መዘጋጀታቸው አዲስ ነገሮች ናቸው፡፡ እነዚህን የመሳሰሉ ጉዳዮች የዚህን ዓመት ሐዊረ ሕይወት ልዩ ያደርጉታል፡፡

 

መካነ ድር፡- የመነሻ ቦታው የት ነው?

 

ዲ/ን ሙሉዓለም፡– ከአዲስ አበባ ለሚነሡ ምእመናን 5ኪሎ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አጠገብ በማኅበረ ቅዱሳን ጽ/ቤት ነው፡፡ ከአዲስ አበባ ውጪ ያሉ ምእመናን ደግሞ ባሉበት ርእሰ ከተማ በማኅበረ ቅዱሳን ማእከላት ጽ/ቤት መነሻቸውን ያደርጋሉ፡፡ በዚሁ አጋጣሚ ማስታወስ የምፈልገው ጉዳይ ከአዲስ አበባ ዙሪያ የሚመጡ ምእመናን በዋዜማው መጥተው ማደር አይጠበቅባቸውም፡፡ ከቦታው ቅርበት የተነሣ በዕለቱ ቀደም ብለው ቢነሡ መጋቢት 2 ቀን 2004 ዓ.ም ጠዋት መድረስ ይችላሉ፡፡ ከጅማ፣ ከመቀሌ፣ ከአፋርና ራቅ ካለ ቦታ የሚመጡ ምእመናን ግን መጋቢት 1 ቀን 2004 ዓ.ም አዲስ አበባ መግባት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ለእነዚህ እንግዶቻችንም በማኅበረ ቅዱሳን ሕንፃ መኝታ ተዘጋጅቶላቸዋል፡፡

 

መካነ ድር፡- በመጨረሻ የሚያስተላልፉት መልእክት ካለ?

 

ዲ/ን ሙሉዓለም፡- እግዚአብሔር አምላክ ሥራችንን እንዲያከናውንልን ምእመናን በጸሎታቸው እንዲያስቡን ቀዳሚው መልእክቴ ነው፡፡ ሌላው መልእክት ይህ ጉዞ ለሥጋዊ ጥቅምና ለትርፍ የተዘጋጀ የጉዞ መርሐ ግብር አይደለም፡፡ 4000 ሰዎችን የሚያስጠልል ድንኳን፣ 4000 ወንበርና 4000 ሳህን ጀኔሬተርና ሞንታርቦ ከአዲስ አበባ ጭነን ነው የምንሔደው የሕክምና ቡድኖች፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ከእኛ ጋር ይጓዛሉ፡፡ ስለዚህ ከትራንስፓርት ውጭ ከ100,000 ብር በላይ ወጭ ይጠይቃል፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ቀኖና እና ዶግማ የጠበቁ ትምህርቶች በሲዲ ለማሠራጨትም አቅደናል እነዚህን ሁሉ ወጭዎች ለመሸፈን ማስታወቂያ በማሠራትም ይሁን በተለያየ ዘዴ ጉዞውን እንድንደግፍ መልእክቴን አስተላልፋለሁ፡፡

 

መካነ ድር፡– ስለነበረን ቆይታ በእግዚአብሔር ስም ምስጋናችን ከፍ ያለ ነው፡፡

 

ዲ/ን ሙሉዓለም፡- እኔም ተገቢውን መረጃ በተገቢው ሰዓት እንዳደርስ እድሉን ስለሰጣችሁን በእግዚአብሔር ስም አመሰግናለሁ፡፡