metshafe_bilhat.jpg

የአዳዲስ ፈጠራ ግኝቶች ማበረታቻ የሽልማት ፕሮጀክት ትግበራ ተጀመረ።

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
 
metshafe_bilhat.jpgየሙያ አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል የአዳዲስ ፈጠራ ግኝቶች ማበረታቻ የሽልማት ፕሮጀክት ትግበራ ጀመረ። በፕሮጀክቱ ትውውቅ መርሐ ግብር ላይ ለትግበራ መነሻ ይሆናል የተባለው «መጽሐፈ ብልሃትም» ተገምግሟል።
 
ፕሮጀክቱ ማኅበረ ቅዱሳንና ኢንጅነር ሙሉጌታ ዘርፉ በተፈራረሙት የመግባቢያ ሠነድ መሠረት ፈጠራንና መልካም የሆነውን የቴክኖሎጂ ሽግግር ማበረታት፥ ቤተ ክርስቲያንን፣ ትውልድን ፣ ሀገርን የሚጠቅም አቅም ለማሳደግ አስተዋጽኦ ማድረግ እንደሆነ በመርሐ ግብሩ ትውውቅ ወቅት የተበተነው ወረቀት ያስረዳል፡፡
መርሐ ግብሩን ያዘጋጀው የማኅበረ ቅዱሳን የሙያ አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል ሲሆን በፕሮጀክት ትውውቅ መርሃ ግብር ላይ የክፍሉ ሓላፊ ዶ/ር ሣሙኤል ኃ/ማርያም እንደተናገሩት ከሆነ የፕሮጀክቱ ዋነኛ ዓላማ በሁሉም የዕድሜ ክልል ያሉ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ በየደረጃቸው መስራትና የፈጠራ ባለቤት የሚሆኑበትን መንገድ ማሳየት ነው፡፡ በግኝቱ ውስጥ ለሚያሸንፋ ግለሰቦች ሽልማቶችን በመስጠት ፈጠራን ያበረታታል በተጨማሪም ያለብንን የተለያዩ ችግሮች በሙያ በማገልገል በተሰጠን መክሊት አትርፈንባቸው ገብርሄር ተብለን ሰማያዊ ሽልማት እንድናገኝ ነው፡፡

በትውውቅ መርሐ ግብሩ ላይ የተገኙትም የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም እንደገለጹት ማኅበሩ ይህንን ፕሮጀክት ለተጠቃሚ ለማድረስ ሲወስን ከዘርፉ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ቤተ ክርስቲያንንና ሀገሩን በአካባቢያው ከሚያገኛቸው ቁሳቁሶች በማዘጋጀት እንዲጠቀም ነው፡፡ በዚህ በኩል ሁላችንም የድርሻችንን እና የሚጠበቅብንን ሁሉ ማድረግ ይገባናል ብለዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ለፕሮጀክቱ ትግበራ መነሻ ይሆናል የተባለውና በኢ/ር ሙሉጌታ ዘርፉ የተዘጋጀው መጽሐፈ ብልሃት አንደኛ መጽሐፍም ተገምግሟል፡፡ መጽሐፉ በ24 ክፍሎችና በ92 ገጾች በምርምርና ሥርዐት የተዋቀረ መሆኑን ዶ/ር ኢ/ር ብርሃኑ ይግዛው የግምገማ ግብረ መልስ /Feed back/ ሲያቀርቡ ገልጸዋል፡፡

ገምጋሚው መጽሐፉ የተጻፈበትን ሥርዓትና ስልት ሲገልጹ፥ ሥልጣኔ የሚፈጥሩት እንጂ የሚቀበሉት ነገር ያለመሆኑን ያመሰጠረ መጽሐፍ ነው ብለው፥ በይዞታቸው ጥንታዊ ግኝቶች፣ በአቀራረብ ስልታቸው ግን አዲስ ሊባሉ የሚችሉ እሳቤዎችን፣ ምን አልባትም በቴክኖሎጂ ዘርፍ ገና ያልተፈለሰፉ ግን ሊተገበሩ የሚችሉ ድንቅ ሀሳቦችንም እያዋዛ የሚያቀርብ መጽሐፍ ነው ብለዋል፡፡   

ስለ መጽሐፉ ጠቀሜታ በዘረዘሩበት የግምገማቸው አካል ምርምርና ሥርፀት ምን ሊሆን እንደሚችል የሚያስረዳና፥ እያንዳንዱ ሰው የፈጠራ ችሎታን በተመለከተ እንዲማር የሚያደርግ ነው፡፡ እኒህም የመጠቁ ቤተ ሙከራዎችን በማይጠይቅ ሁኔታ ነው ብለዋል፡፡

ዶ/ር ኢ/ር ብርሃኑ በማጠቃለያ ሀሳባቸው መጽሐፉ ጥቂት ሊያካትታቸው ስለሚገቡ ነገሮች ጠቅሰው፥ ይህ በጎ ጀማሮ በየት/ቤቱ፣ በቤተሙከራዎች እንዲሁም በፋብሪካዎች ተሠራጭቶ በዚህ ረገድ ሁሉም የኢትዮጵያ ክልሎች ይሄው በጎ የቴክኖሎጂ መሠረታዊ ሀሳብ የሚስፋፋበትን መንገድ በመቀየስ የበኩላቸውን ጥረት ማድረግ እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡

የማ/ቅዱሳን ሙያ አገልግሎትና አቅም ማጐልበቻ ዋና ክፍል ማኅበሩ ከተነሣለት ቤ/ክንን በሙያ በእውቀትና በገንዘብና በጉልበት ለማገልገል ካለው ዓላማ አንፃር የቤ/ክንን ልጆች በሙያ አገልግሎት ለማሣተፍ የተቋቋመ ክፍል ነው፡፡