ዕቅበተ እምነት በመጽሐፈ ምሥጢር – ሦስተኛ ክፍል

የካቲት ፳፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፪.፬ አርአያውን ወደ መስቀል አወጣ ለሚሉ መናፍቃን

ሥጋው የተቸነከረው በእውነት ካልሆነ ስለምን ከትንሣኤው በኋላ ቶማስንእጅህን አምጣና በመስቀል ችንካሮች የተጨነከሩትን እጆቼን ዳስስ፤ ጣቶችህንም አምጣወደ ጎኔም አስገባአለው በማለት ሊቁ ስንፍናቸውን ይገልጽባቸዋል፡፡ ከዚሁ ጋር አያይዞ አባ ጊዮርጊስ እግዚአብሔር አይወልድም አይወለድም ለሚሉ መናፍቃን እነዚህን በምን እንከራከራቸዋለን፤የኦሪት ሕግ አለንይሉናል፡፡ የኦሪታቸው ቃል ከእኛ ኦሪት ጋር፣ የነቢዮቻቸውም ቃል ከእኛ ነቢያት ጋር አይተባበርምና የአንደበታቸው ቃል ሁሉ ሐሰተኛ ነው፤ መንገዳቸውም ክፉ መንገድ ነው …” በማለት ክሕደታቸውን ይገልጽልናል፡፡

፪.፭ አርሲስ

“አርሲስ” በሃይማኖተ አበው እንደተጠቀሰው ስመ መናፍቃን ነው፡፡ አርሲስ በነፍስና በሥጋ ወደ ሲኦል ወረደ ብለው የሚናገሩ መናፍቃን ናቸው፡፡ ሊቁ እነዚህን መናፍቃን እስኪ እናንተ አስቀድማችሁ ንገሩን? የእግዚአብሔርን ልጅሞተ› ትሉታላችሁ? ወይስአልሞተምትላላችሁ?ብሎ ይጠይቃቸዋል፡፡ ሞተ” ካሉ “የነፍስ ከሥጋ መለየት በቀር ሞት ምንድን ነው?” አልሞተም” ካሉ ደግሞ ሞት ሳይኖር ትንሣኤ እንዴት ነው?” እያለ ይሞግታቸዋል፡፡ በትምህርታቸው ክርስቶስን የሚሞትና የማይሞት ሁለት ሥጋ ያለው እንዳስመሰሉት በመንገር ይነቅፋቸዋል፡፡ እኛ ግንመለኮታዊ ቃል ከብቻዋ ከነፍስ ጋር ወደ ሲኦል ወረደ፤ ሥጋን ግን ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከመስቀል ላይ አውርደዋት በከፈን ጠቅልለው ከመቃብር ውስጥ ጨመሯት፡፡ ሥጋም ያለ ነፍስ እስከ ትንሣኤው ዕለት ለብቻዋ ቆየች፡፡ መለኮት ግን ከነፍሱ እና ከሥጋው አልተለየም› እንላለን” በማለት መልስ ያሰጣቸዋል፡፡

፪.፮ ፎጢኖስ

በሰርቢያ ግዛት ትገኝ በነበረች የሰርሚየም ሊቀ ጳጳስ የነበረው ፎጢኖስ ለፌ እማርያም ክዋኔሁ (ህላዌሁ) ለወልድየወልድ ህልውና ከማርያም ከተወለደ በኋላ ነው የሚል ኑፋቄ ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ ሊቁ አባ ጊዮርጊስም እኛ ግንህልውናው ከዘመናትና ከጊዜ፣ ከዕለታትና ከሰዓት አስቀድሞ ነው፣ በኋለኛው ዘመን ስለ እኛ ድኅነት ያለ ዘርዐ ብእሲ ከቅድስት ድንግል ማርያም ሰው ሆነ (በሥጋ ተገለጠ)› እንላለን በማለት ቅዱሳት መጻሕፍትን እያመሠጠረ መልስ ሰጥቶታል፡፡

፪.፯ የአብ ቃል ሰው ወደመሆን ተለወጠ ለሚሉ መናፍቃን

እነዚህ መናፍቃን አካላዊ ቃል ሥጋና ደም፣ አጥንትና ጠጉር፣ ሥሮችንም ወደ መሆን ተለወጠ፤ መለኮትም ሰውን ወደ መሆን ተለወጠ ብለው ይናገራሉ፡፡ ይህም ማለት ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የሆነው ተለውጦ ነው ወይም ሰው በመሆኑ አምላክነቱ ጠፍቷል” የሚሉ ናቸው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን ሰው ሆነ ሲባል የጨው ሐውልት እንደሆነች እንደ ሎጥ ሚስት፣ የበርሃ አውሬ እንደሆነ እንደ ናቡከደነፆር ተለውጦ አይደለም ይላል፡፡ የመለኮት ኃይል ሰው ወደ መሆን ተለውጦ ቢሆን ኖሮ ሞትን ባልቀመሰ፣ ሞትንም ቢቀምስ ዓለምን የያዘው የመለኮት ኃይል ነውና፣ የሰማይ ጠፈር በፈረሰ፣ የምድርም መሠረታት በተበታተኑ ነበር፤ ሰውነት መለኮትን ወደ መሆን ተለውጦ ቢሆን መለኮት በእጅ አይነካም፣ ለዐይንም አይታይም፣ በሕሊናም አይመረመርምና ለሰቃዮች ባልተያዘ፣ በመስቀል ላይ እፍረትን ባልታገሠ ነበር በማለት ይዘልፋቸዋል፡፡ እኛ ግንያለጭማሪ ተዋሐደ እንጂ መለኮታዊ ቃል ከባሕርዩ አልተለወጠም፤ ያለመለወጥ የተዋሐደ ሆነእንላለን በማለት በተዐቅቦ እንደተገለጠ ይነግረናል፡፡

፪.፰ መንክዮስ

የክርስቶስ ሥጋ ምትሐት ነው፤ የሰው ልጅ ሥጋ አይደለም የሚል ኑፋቄ ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ የክርስቶስ ሥጋ ምትሐት አለመሆኑን፣ ፍጹም የሰው ሥጋ መሆኑን ከድንግል መወለዱን፣ ጡቶቿን እየጠባ ማደጉን፣ በዮርዳኖስ በዮሐንስ እጅ መዳሰሱን፣ በመስቀል ላይ መቸንከሩን በመጥቀስ መንክዮስ ሆይ! ስንፍናህን አደንቃለሁስለ ብዙዎች ቤዛ መገደሉን ካላመንክ አንተም በኢየሱስ ክርስቶስ ሞት አልዳንህም በማለት ይዘልፈዋል፡፡ እኛ ግን የክርስቶስ ሰውነት ፍጹም የሚዳሰስ ሥጋን የሚያጸና አጥንት የሚፈስ ደም ሰውነትንን የሚያስሩ ጅማቶች፣ የራስ ጠጉርና ቅንድብ፣ የማትታይ ነፍስ የምታስተውልና የምትናገር የሕይወት እስትንፋስ፣ የእጆችና የእግሮች ቡቃያ ጥፍሮች አሉት እንላለን ይለናል፡፡

፪.፱ አውጣኪ

አውጣኪ ወይም አፍቲኪስ የክርስቶስ ሥጋ እንደኛ ሥጋ አይደለም፤ መከራንም አልተቀበለም፤ የክርስቶስ ሥጋ ከሰማይ የወረደ ነው በማለት ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አውጣኪ ነገረ ተዋሕዶን ለማብራራት ሲሞክር ኢየሱስ ክርስቶስ በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ ነው” የሚለውን ትምህርት ቢቀበልም፣ በሥጋው ፍጹም ሰው መሆኑን ግን አልተቀበለም፡፡ ስለዚህ ክርስቶስ ተራበ፤ ተጠማ፤ ደከመ፤ መከራ ተቀበለ፤ ሞተ …” የሚሉትን ቃላት ለመጠቀም ይፈራል፡፡ አባ ጊዮርጊስ ወደ ደረቱ ተጠግቶ የተቀመጠ ወዳጁ ዮሐንስ የክርስቶስን ሥጋ መድከም ለመናገር ካላፈረ፣ በፊቱ መስታወትነት ያልታየህ፣ ጣቶቹ ያልዳሰሱህ፣ ጣቶችህም ያልዳሰሱት አንተ እንዴት ታፍርበታልህ? በማለት የሚወቅሰው ስለዚህ ነው፡፡ እኛ ግን ክርስቶስ በሥጋው ደከመ፣ ወዛ፣ ተራበ፣ ተጠማ፣ ታመመ፣ ሞተ፤ ከኃጢአት በቀር የሰውነትን ሥራ ሁሉ ሠራ እንላለን በማለት የቤተ ክርስቲያንን ቀጥተኛ አስተምህሮ በመግለጥ እኛን ስለማዳን ከተያዘበት ጊዜ ጀምሮ ቅድስት ነፍሱ ከቅዱስ ሥጋው እስከተለየችበት ድረስ የተቀበለውን ፀዋትወ መከራ ያብራራል፡፡

በተጨማሪም አፍቲኪስ የክርስቶስ ሥጋ ከሰማይ ወረደ በማለት ለሚናገረው ኑፋቄው ሊቁ ሲመልስ እናንተ ሰነፎችና ልባችሁ ከማመን የዘገየአዳም ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ› ብሎ መናገርን እንዳስቀደመ ከአዳም ዘር ሰው ሆኖ እንደተወለደ ዕወቁ፡፡ መድኃኒታችን ከለበሰው ከአዳም ሥጋ በቀር የአዳም እንደ እግዚአብሔር መሆኑ ምንድን ነው? በዚያችም ሥጋ በምድር ላይ ጉስቁልናን ለበሰ፤ ያችንም ሥጋ በሰማያት ጌትነትን አለበሳት፡፡ በሰማያት ሥጋ ካለ ከእርሷ ሰው ሆኖ ይወለድ ዘንድ ስለምን በድንግል ማኅፀን አደረ፣ ከሥጋው ጋር በድንግል ማኅፀን አደረ ካላችሁ፣ የሥጋ በሥጋ ውስጥ ማደር ጥቅሙ ምንድን ነው? ቀድሞውንም ሥጋ ካለው የቀደመ ሥጋው በበቃው፤ ከድንግል ሥጋ መወለድን ባልፈለገ ነበር ይላል፡፡ እኛ ግንየክርስቶስ ሥጋና ነፍሱ ከአዳም ባሕርይ ብቻዋን ንጽሕት ድንግል (ከሆነች) ማርያም ከተባለች የገሊላ ሴት ያለ ወንድ ዘር የነሣው ነው› እንላለን በማለት ይመልስለታል፡፡

አባ ጊዮርጊስ የክርስቶስን አምላክነት በመሰከረበት በዚህ አንቀጹ የሚከተለውን ትምህርት አስተምሯል፤ ስለ ትሕትና ነገር መናገርን እናስቀድም፤ ኃይል በሴት ማኅፀን አደረ፤ እሳትም በሥጋና በደም መጐናጸፊያ ተጠቀለለ፡፡ ሕፃናትንም የሚሥል በሕፃናት መልክ ተሣለ፤ የሔዋን አባት ከሔዋን ሴት ልጅ ተወለደ፤ በኪሩቤል ላይ የሚቀመጥ በጉልበት ታቀፈ፤ እሳት በተሣለባቸው በአራቱ እንሰሳ ላይ የሚጫን በላምና በአህያ መካከል ተኛ፡፡ ሥጋዊን ሁሉ የሚመግበው የጡት ወተትን ተመገበ፡፡ በጊዜና በዘመናት የሸመገለ በየጥቂቱ አደገ፤ በታናሽነታቸው ጊዜ ሕፃናትን የሚጠብቃቸው በሜዳ ላይ ዳኸ፤ ለዓመታቱ ቁጥር ጥንት የሌለው በሰው መጠን ጐለመሰ፤ ተራሮችን በኃይል የሚያቆማቸው ደከመ፣ ወዛም፡፡ ኪሩቤል ሊነኩት ሱራፌልም ሊዳስሱት የማይቻላቸው እግሮቹ በአመንዝራይቱ ሴት፣ ልብሶቹም ደም በሚፈስሳት ሴት ተዳሰሰ፡፡

፪.፲ የእለእስክንድርያው ታውዶስዮስና የሕንድክያው ሳዊሮስ

እነዚህ የእግዚአብሔር ልጅ በግድ መከራን ተቀበለ፤ ያለፈቃዱ ሞተ ብለው የተናገሩ መናፍቃን ናቸው፡፡ ሊቁ ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት” ማለቱን፣ አትሙትብን” ያለውን ቅዱስ ጴጥሮስን መገሠጹን፣ ነፍሴን ላኖራት ደግሞም ላነሣት ሥልጣን አለኝ” ማለቱን እየጠቀሰ ካሳፈራቸው በኋላ እኛ ግን በፈቃዱ መከራ ተቀብሎ ሞተ፣ በፈቃዱ በመለኮቱ ኃይል ተነሣ እንላለን ይላል፡፡ በፈቃዱ ስለሆነ መከራውና ሞቱም እርሱ ራሱ በፈቀደ አሰቃዩት፤ እርሱም በወደደ ገደሉት፤ እርሱ በፈቀደ በመስቀል ላይ በብረቶች ቸነከሩት፤ እርሱም በወደደ ሞትን በሥጋ ቀመሰ፤ እርሱ በፈቀደ ሆምጣጤ ከሐሞት ጋር ቀላቅለው አጠጡት፤ እርሱም በወደደ ነፍሱን ለአባቱ አደራ ሰጠ በማለት ይገልጽልናል፡፡

፪.፲፩ ፍላቭያኖስ

የቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳስ የነበረና የመለኮትና የሰውነት ገጽ ሁለት ነው በማለት ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስም መለኮትና ትስብእት ካልተዋሐዱ ኢሳይያስ አማኑኤል ያለው ማንን ነው? ‹ሥጋዬን ካልበላችሁ ደሜንም ካልጠጣችሁ የዘለዓለም ሕይወት የላችሁም› ያለን ማን ነው? በጲላጦስ ፊት የቆመው፣ የተቸነከረውና የተሰቀለው፣ ዓለምን ያዳነው ማን ነው? በማለት ጥያቄውን በጥያቄ ይመልስለታል፡፡

፫. ነገረ መንፈስ ቅዱስ

፫.፩ መቅዶንዮስ

መንፈስ ቅዱስሕጹጽ› (ፍጡር) ነው” ያለ መናፍቅ ሲሆን በሁለተኛው ዓለም አቀፍ የቤተ ክርስቲያን ጉባኤ የተወገዘ ነው፡፡ ሊቁ መንፈስ ቅዱስ ከአብና ከወልድ ያነሰ ቢሆን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ሲያዝዛቸውስታጠምቁ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቁአለ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ያነሰ ከሆነ ስለምን በማይስተካከለው መጠመቅን አዘዘ? በማለት በጥያቄ ይመልስለታል፡፡

፫.፪ “የመንፈስ ቅዱስ ህላዌ ከክርስቶስ ጥምቀት ወዲህ ነው” ለሚሉ መናፍቃን

እነዚህ መናፍቃን ጌታችን አምላካችን መድኀኒታች ኢየሱስ ክርስቶስ በተጠመቀበት ጊዜ የመንፈስ ቅዱስን በርግብ አምሳል መገለጥ የህላዌው መጀመሪያ አድርገው መናገራቸው እንዴት ስሕተትና ኑፋቄ እንደሆነ የእግዚአብሔር መንፈስ በውኆች ላይ ሰፍፎ ነበር የሚለውን ቃል በመጥቀስና በማብራራት መልስ ይሰጣቸዋል፡፡ ሊቁ እኛ ግንመንፈስ ቅዱስ ቅድመ ዓለም የነበረ ለዘለዓለም የሚኖር ነው› እንላለን በማለት አማናዊውን የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ይነግራቸዋል፡፡

ይቆየን