meskel damera

ወሰአረ መርገመ በዲበ ዕፀ መስቀል

መስከረም 16 ቀን 2006 ዓ.ም.

በመ/ር ምስጢረ ሥላሴ ማናየ

 

  • መርገምን በመስቀል ላይ ሻረ” ቅዱስ አትናቴዎስ ሃይማኖተ አበው

በቅmeskel dameraድሚያ ከዘመን ወደ ዘመን ያሸጋገረን ለብርሃነ መስቀሉ ያደረሰን በሀብቱ የሳበን በረድኤቱም ያቀረበን አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን፡፡

ከላይ በርዕሱ ያነሣነው ኃይለ ቃል ቅዱስ አትናቴዎስ የመስቀሉን ነገር በተናገረበት ድርሳኑ የተናገረው ነው፡፡ አስተሀፈረ ኃጢአተ በዲበ ምድር ወሰአረ መርገመ በዲበ ዕፀ መስቀል ወአብጠለ ሞተ በውስተ ሲዖል ወነሰተ ሙስና እምውስተ መቃብር”

“በምድር ላይ ኃጢአትን አሳፈረ መርገምን በመስቀል ላይ ሻረ ሞተ ነፍስን በሲዖል አጠፋ ፈርሶ በስብሶ መቅረትን በመቃብር አፈራረሰ” በማለት ጌታችን ለሰው ልጆች ነጻነት እና ድኅነት የከፈለውን የቤዛነት ሥራ በተናገረበት ክፍል የተናገረው ነው የሰው ልጆች ነጻነታቸው የተዋጀው በመስቀል ተሰቅሎ ቅድስት ነፍሱን ከቅድስት ሥጋው በሥልጣኑ ለይቶ ዲያብሎስን በመስቀሉ ገሎ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍሶ በአካለ ነፍስ ወደ ሲዖል ወርዶ ነፍሳትን ከዲያብሎስ ባርነት ከአጋንንት ቁራኝነት ከሲዖል ግዛት ነጻ አውጥቷቸዋልና፡፡

“ሞተ በሥጋ ወሐይወ በመንፈስ ወወረደ ኀበ እለ ሙቅሕታ ትነብር ነፍሶሙ ወሰበከ ሎሙ ግዕዛነ” በሥጋ ሞተ በመንፈስ /በመለኮት/ ግን ሕያው ነው እርሱም ደግሞ ሄደ በወህኒ /በሲዖል/ ለነበሩ ነፍሳት ነጻነትን ሰበከላቸው” 1ጴጥ.3፡18

መስቀል በዓለመ መላእክት
መስቀል በዓለመ መላእክት በጥንተ ፍጥበረት ሰባቱ ሰማያት በተፈጠሩበት ዕለተ እሑድ ሥላሴ ጽርሐ ዓርያምን ከእሳት ዋዕዩን ትቶ ብርሃኑን ነሥቶ በፈጠረበት ጊዜ በውስጧ ታቦት ዘዶርንና የብርሃን መስቀልን ቀረፀባት ይላል ሊቁ ኤጲፋንዮስ ሥነ ፍጥረትን አምልቶ አጉልቶ በጻፈበት አክሲማሮስ በተባለ መጽሐፉ ይህ በእንዲህ እንዳለ እግዚአብሔር መላእክትን ፈጥሮ በተሰወራቸው ጊዜ ዲያብሎስ እኔ ፈጠርኳቸው ባለበት ሰዓት በአለመ መላእክት በመላእክትና በዲያብሎስ በተደረገው ጦርነት መላእክት ዲያብሎስን ድል ያደረጉት በመስቀል መሣሪያነት ነው፡፡

“በሰማይ ሰልፍ ሆነ ሚካኤልና መላእክቱ ዘንዶውን /ዲያብሎስን/ ተዋጉት ዘንዶውም ከመላእክቱ ጋር ተዋጋ አልቻላቸውም ከዚያም ወዲያ በሰማይ ቦታ አልተገኘለትም ዓለሙን የሚያስተው ሁሉ ምድር ተጣለ መላእክቱም /ሠራዊተ ዲያብሎስ/ ከእርሱ ጋር ተጣሉ” ራዕ.12፡7፡፡

በዚህ ውጊያ መካከል የነበረውን ሁኔታ ሲገልፅ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ዲያብሎስ ሁለት ጊዜ ዲያብሎስ ድል ነሳቸው በሦስተኛው ፈጣሪያቸውን ጠየቁ ፈቃድህ አይደለምን ዲያብሎስን እንድንዋጋው አሉት፤ መላእክት ፈቃዴስ ነው ግን ድል የምታደርጉበትን ኃይል እንድታውቁ ብዬ ነው ብሎ በክንፋቸው ላይ የብርሃን መስቀል ቀረጸላቸው በእጃቸው የብርሃን መስቀል አስያዛቸው ሄደው ገጠሙት “ጐየ እግዚእ ምስለ ዓርያሙ” ጌታ ሰማይን ጠቅልሎ ሸሸ ብሎ እየደነፋ ወደ ምድር ወረደ ይላል፡፡ ስለዚህ መስቀል ፀረ ዲያብሎስነቱ የታወቀው ጌታችን ከመሰቀሉ በፊት ነው፡፡ ኃይሉም የተገለጠው ያን ጊዜ ነው፡፡

በሌላ መልኩ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ የመላእክትን ምስጋና በገለጠበት እንዲህ ሲል ጽፏል “ንጉሡ ዖዝያን በሞተበት ዓመት እግዚአብሔርን ከፍ ባለ ዙፋኑ ላይ ተቀምጦ አየሁት ኪሩቤልና ሱራፌል ዙሪያውን ነበሩ ለእያንዳንዱም ስድስት ስድስት ክንፍ ነበራቸው በሁለት ክንፋቸው ፊታቸውን ይጋርዳሉ በሁለት ክንፋቸው እግራቸውን ይጋርዳሉ በሁለት ክንፋቸው ጽንፍ እስከ ጽንፍ ይበራሉ፡፡ ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ እያሉ ያመሰግናሉ” ኢሳ.6፡1-6፡፡

ሲበሩ ክንፋቸውን መዘርጋታቸው የመስቀል ምልክት ከመሆኑም በተጨማሪ አምላክ ሰው ሆኖ በመስቀል ተሰቅሎ ዓለምን እንደሚያድነው ምልክት ነበር፡፡
ይህን ሊቁ ቅዱስ ያሬድ “በአርአያ ትዕምርተ መስቀል” በመስቀል ተሰቅለህ ዓለምን ታድናለህ ሲሉ ነው ብሎ ተርጉሞታል፡፡

መስቀል በዘመነ አበው
በዘመነ አበው መስቀል የመባረኪያ ምልክት እንደነበረ የሚያሳዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች አሉ ለምሳሌ፡-
“በተአምኖ አመይመውት ያዕቆብ ባረኮሙ ለደቂቀ ዮሴፍ ለእለ አሐዱ” ያዕቆብ በሚሞትበት ጊዜ የዮሴፍን ልጆች በእምነት ባረካቸው” ዘፍ.47፡31፣ ዕብ.11፡22 “ወአስተሐለፈ እዴሁ ላዕለ ርዕሰ ኤፍሬም ወምናሴ” እጆቹን በኤፍሬምና በምሴ ላይ በመስቀል አምሳል አመሳቀለ እጆቹንም በራሳቸው ላይ ጭኖ ባረካቸው ይላል፡፡ 

ዛሬም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህኑ ቀድሶ በሚወጣበት ጊዜ በእጆቹ ይባርካል ይህም የሚያሳየው ቤተ ክርስቲያኗ መሠረቷ ከላይ በዓለመ መላእክት ከታች በዘመነ አበው ያየነው መስቀል መሆኑን ነው፡፡ “በአምስት ቀን ተኩል ከልጅ ልጅህ ተወልጄ በመስቀል ተሰቅዬ ሞቼ አድንሃለሁ” የሚል የተስፋ ቃል ተሰጥቷል፡፡

መስቀል በዘመነ ነቢያት እና በዘመነ ነገሥት
መስቀል በዘመነ ነቢያት በዘመነ ነገሥት እንደየሀገሩ ግእዝን /ሁኔታ/ ልዩ ልዩ ተግባራት ሲፈጽሙበት ቆይቷል፡፡ ለምሳሌ፡- ለወንጀለኞች መቅጫነት አገልግሏል በዕርግጥ አሁንም የወንጀለኞች የአጋንንት መቅጫ ነው ለሚያምኑበት ግን የጭንቅ መውጫ የነጻነት መገለጫ ነው፡፡

በተለይ ፋርስ ሰዎችን ሰቅሎ መግደል መገለጫዋ ነበር የተጀመረውም በፋርስ ነው ሰውን በመስቀል ሰቅሎ መግደል የባቢሎን እቶነ እሳት እና አናብስት፣ የሮማውሪያንና የፋርስ ስቅለት የአይሁድ ውግረት  መቅጫቸው ነው፡፡

መርዶክዮስን ሊሰቅል ባዘጋጀው መስቀል የተሰቀለው ሐማ በፋርስ ሕግ ነበር “እነሆ ሐማ ለንጉሡ በጎ ለተናገረው ለመርዶክዮስ ያዘጋጀው አምሳ ክንድ የሆነ ግንድ በሐማ ቤት ተተክሎአል “ንጉሡም በእርሱ ላይ ስቀሉት አለ ሐማንም ለመርደክዮስ ባዘጋጀው ግንድ ላይ ሰቀሉት” አስቴ.7፡9፡፡

በእርግጥም ይህን አልን እንጂ ይህ ሥርዓት ከፋርስ ወደሮማውያን ተላልፎ በመቅጫነት አገልግሎአል፡፡ አይሁድም ብዙ ጊዜ ወንጀለኞችን የሚቀጡት በውግረት በእሳት በማቃጠል ቢሆንም በመስቀልም ይቀጡ ነበር፤ ምክንያቱም መነሻው ኦሪት ነውና የኦሪት መደበኞች ደግሞ ፋርሶች ወይ ሮማውያን ሳይሆኑ እነርሱ ናቸው፡፡

“ርጉም ውእቱ ኩሉ ዘስቁል ዲበ ዕፅ” ዘዳ.21፡23 ሰርቆ ቀምቶ በእንጨት የተሰቀለ የተረገመ ይሁን” ተብሎ የተጻፈው በኦሪት ነው፡፡ ስለዚህ መስቀል የወንበዴ የሌባ መቅጫ የጥፋተኛ መቀጥቀጫ ነበር፡፡ በአይሁድ ሕግ ከፍተኛ ወንጀል የፈጸሙ ሰዎች አይገረፉም በመስቀል ይቀጡ ነበር፡፡ ከተገረፉ ደግሞ አይሰቀሉም፤ የፈጸሙት በደል ለዚያ ርግማን የሚያበቃ አይደለም፡፡ ማለት ነው፡፡

መስቀል በዘመነ ነቢያት በብዙ ኅብረ ትንቢት አሸብርቆ በብዙ ኅብረ አምሳል ደምቆ የመጣ እንጂ፤ እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ ድንገት የተገኘ አይደለም፡፡ ለእስራኤል በ40 ዘመን ጉዟአቸው ውስጥ ተአምራት በማረግ የታዩት የሙሴ በትር እና በምድረ በዳ ሙሴ የሰቀለው አርዌ ብርት የታየበት አላማ የመስቀል ምልክቶች ወይም ምሳሌዎች ነበሩ፡፡

የሙሴ በትር ባሕር ከፍሏል ጠላት ገሏል መና አውርዷል ደመና ጋርዷል ውኃ ከአለት አፍልቋል፤ በግብጻውያን ላይ ድንቅ ድንቅ ተአምራት አድርጓል፡፡ ሙሴም ምሳሌው የሆነለት ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀልም ባሕረ እሳትን ከፍሏል ማየ ገቦን ደመ ገቦን ለመጠጣችን ለጥምቀታችን አስገኝቷል፡፡ ኃይሉን በዲያብሎስና በአጋንንት ላይ አሳይቷል፡፡ ነፍሳትን ከሲዖል ባርነት ከዲያብሎስ ቁራኝነት ነጻ አውጥቷል፡፡ “ወሀደፎሙ በመስቀሉ” በመስቀሉ አሻገራቸው” እንዲል መጽፈሐፈ ኪዳን፡፡ ሙሴ በምድረ በዳ የሰቀለው የነሐስ እባብ ክርስቶስ በመሰቀል የሚፈጽመውን የማዳን ሥራ የሚያሳይ ነበር፡፡

“ሙሴም ስለ ሕዝቡ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ እግዚአብሔርም ሙሴን “የናስ እባብን ሠርተህ በዓላማ ላይ ስቀል እባቡም ሰውን ቢነድፍ የተነደፈው ሁሉ ይመልከተው ይድናልም” ሙሴም የናሱን እባብ ሠርቶ በዓላማ ላይ ሰቀለ እባቡም የነደፊችው ሁሉ የናሱን እባብ ባየ ጊዜ ዳነ” ዘኁ.21፡7፡፡

የነሐሱ እባብ የክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ የነሐሱ አባብ ጽሩይ ነው ክርስቶስም ጽሩየ ባሕርይ ነውና የነሐሱ እባብ መርዝ የለበትም ክርስቶስም መርገመ ሥነጋ መርገመ ነፍበስን የሚያርቅ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን የሚያድል ክፋት ተንኮል የሌለበት ነውና እባቡ የተሰቀለበት ዓላማው ደግሞ ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀልምሳሌ ነበር፡፡

እባብ የነደፈው ሁሉ በተመለከተው ጊዜ ይድን እንደነበር የሰው ልጅ በሙሉ በእባብ ዲያብሎስ መርዝ ተነድፎ ቆስሎ በኃጢአት ተመርዞ ሲኖር በመስቀል በተፈጸመው የቤዛነት ሥራ ድኗልና፡፡
“ወበከመ ሙሴ ሰቀሎ ለአርዌ ምድር በገዳም ከማሁ ሀለዎ ለወልደ እጓለመሕያው ይሰቀል ከመ ኩሉ ዘየአምን ቦቱ ኢይትሐጐል አላ የሐዩ ለዓለም”

ሙሴ እባብን በምድረ በዳ እንደሰቀለው እንዲሁ የሰው ልጅ ይሰቀል ዘንድ ይገባዋል የአመነበት ሁሉ ለዘለዓለም ሕያው ሆኖ እንዲኖር እንጂ እንዳይጠፋ የሰው ልጅ ይሰቀል ዘንድ ይገባዋል” ዮሐ.3፡15፡፡

ከነቢያት ዳዊት እንዲሁም ልጁ ሰሎሞን የመስቀሉን ነገር አምልተው አጉልተው ተናግረዋል፡፡ “ወወሀብኮሙ ትዕምርተ ለእለይፈርሁከ ከመ ያምስጡ እምገፀ ቅሥት”  “ከቀስት ፊት ያመልጡ ዘንድ ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው ወዳጆችህ እንዲድኑ” መዝ.59፡4 ለመዳን የተሰጠ ምልክት ደግሞ መስቀል ነው ለዚህ ነው እኛ ኦርቶዶክሳውያን በአንገታችን የምናስረው በእጃችን የምንይዘው የምንሳለመው የምንባረክበት ምክንያቱም የመዳን ምልክት ነውና፡፡

ጥበበኛው ሰሎሞንም የመስቀሉን ነገር በተናገረበት አንቀጽ እንዲህ ይላል “ሐረገ ወይን ኮነ መድኃኒትየ ዘእምሐሲሦን ይትገዘም ወበጎልጎታ ይተከል” “የወይን ሐረግ /መስቀል/ መድኃኒቴ ሆነ ሐሲሦን ከተባለ ቦታ ይቆረጣል በጎልጎታ ይተከላል” መኃ.3፡44 ግዕዙን ተመልከት፡፡

ዳዊት ለመዳን የተሰጠ መሆኑን ሲገልጽ ልጁ እንጨቱ ከየት ተነቅሎ በየት ቦታ እንደሚተከል እና መድኃኒትነቱን አጉልቶታል ስለዚህ መስቀል በብሉይ ኪዳን ትልቅ ቦታ ይዟል ማለት ነው፡፡
መስቀል በሐዲስ ኪዳን

መስቀል ከብሉይ ኪዳን ይልቅ የመዳን ምልክት መሆኑ የተረጋገጠበት በክርስቶስ ደም የተቀደሰ የጠብ ግድግዳን ያፈረሰ ቅድስና ያለው ክብር ያለው የአበው ተስፋ የተፈጸመበትም ሰው ከውድቀቱ የተነሳበት መሆኑ ተረጋጋጧል፡፡

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚያስተምሩን ጌታችን የተሰቀለበት መስቀል የተዘጋጀው ከሰባት ዓይነት ዕፅዋት ነው፡፡
1.    ሳኦል ከገነት ያስመጣው ዕፅ
2.    ሰሎሞን ቤተ መቅደስን በሠራበት ወቅት ሠረገላ አድርጎ የተጠቀመበት ዕፅ
3.    ከመቃብረ አዳም የበቀለ ፅፀ ሕይወት
4.    ሎጥ በእንባው ያለመለመው ፅፀ ከርካዕ
5.    ታቦተ ጽዮንን ይሸከሙበት የነበረው ሠረገላ
6.    ጌታችን በቢታንያ የረገማት ዕፀ በለስ
7.    ዘኬዎስ ጌታችንን ለማየት የወጣበት ዕፀ ሠግለ /ሾላ/ ከእነዚህ ሰባት ዕፅዋት በተዘጋጀ መስቀል ነው ጌታችን የተሰቀለው /መጽሐፈ ኪዳን ትርጓሜ ተመልከት/ 

ጌታችን ከእነዚህ ዕፅዋት የተዘጋጀ መስቀሉን ተሸክሞ በቀራንዮ አደባባይ በመስቀሉ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍሶ ቀድሶታል በዚህ የተነሣ መስቀል ነዋይ ቅዱስ ነው መስቀል በሐዲስ ኪዳን ሁለት መሠረታዊ ትርጉሞች አሉት፡፡
1.    ጌታችን የተሰቀለበት ከሰባት ዕፅዋት የተዘጋጀውን መስቀለኛ እንጨት /ቅዱስ መስቀል/
2.    ጌታችን ዓለምን ለማዳን የተቀበለው መከራ መስቀል ይባላል መስቀል ስንል እነዚህን ከላይ ያነሳናቸውን ሁለት አበይት ትርጉሞች ማስታወስ የግድ ይላል፡፡

ስለ መስቀል የክርስቶስ ትምህርት
ክብር ይግባውና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ ደጋግሞ ነገረ መስቀልን አስተምሯል፡፡ “ዘኢጻረ መስቀለ ሞትየ ኢይክል ይጸመደኒ” መስቀሉን የማይዝ በኋላዬም የማይከተለኝ የእኔ ሊሆን አይገባውም” ማቴ.10፡38፣ 16፡24፣ ማር.8፡34፣ ሉቃ.9፡23፣ 14፡27፡፡

ጌታችን ይህንን ያስተማረው ከመሰቀሉ በፊት መሆኑ ግልፅ ነው በቃል ካስተማረው በኋላ በተግባር ፈጸመው መስቀሉን እንድንሸከም መከራውን እንድንቀበል አስቀድሞ አስጠነቀቀን መስቀሉ የሌለው የክርስቶስ ሊሆን እንደማይችል አስረግጦ ነገረን፡፡

ከዚህ የተነሣ ክርስቶስ ራሷ የሆነላት ሐዋርየዊት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መስቀሉን በየዓመቱ በየወሩ ታከብረዋለች ትሸከመዋለች፡፡ በመስቀሉ የሚገኘውን መከራ ትቀበላለች በመስቀሉ የሚገኘውን በረከት ታድላለች ክርስቶስን በግብር ትመሰለዋለች በእግር ትከተለዋለች የእርሱ መሆኗ መልክት መስቀሉ ነው፡፡

“በዚያን ጊዜ ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ እንዲህ አለ “እኔን መከተል የሚወድ ቢኖር ራሱን ይካድ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ” ማቴ.16፡24፡፡ “የሰው ልጅ /ክርስቶስ/ ለካህናት አለቆችና ለጻፎች አልፎ ይሰጣል የሞት ፍርድም ይፈርዱበታል ሊዘባበቱበትም ሊገርፉትም ሊሰቅሉትም ለአሕዛብ አሳልፈው ይሰጡታል” ማቴ.20፡18፡፡ መስቀል ስንል ይህን ሁሉ መከራ ያጠቃልላል ይህ ሁሉ መከራ የተፈጸመበት ነዋይ ቅዱስም መስቀል ይባላል፡፡

“ከሁለት ቀን በኋላ ፋሲካ እንዲሆን ታውቃላችሁ የሰው ልጅ ሊሰቀል አልፎ ይሰጣል” ማቴ.26፡1፡፡ ይህ እስከ አሁን ጌታችን በቃል ያስተማረውን ተመልክተናል ተግባሩ እነሆ፡-“የአይሁድ ንጉሥ ሰላም ላንተ ይሁን እያሉ ዘበቱበት ተፉበትም መቃውን ይዘው ራሱን መቱት ከዘበቱበትም በኋላ ቀዩን ልብስ ገፈፉት ልብሱንም አለበሱት ሊሰቅሉት ወሰዱት ሲወስዲትም ስምዖን የተባለ የቀሬና /ሊቢያ/ ሰው አገኙ እርሱንም መስቀሉን ይሸከም ዘንድ አስገደዱት ትርጓሜው የራስ ቅል ስፍራ ወደሚሆን ጎልጎታ ወደሚባለው ሥፍራ በደረሱ ጊዜ ሰቀሉት” ማቴ.27፡29፡፡ መስቀል ማለት ይህን ሁሉ ያጠቃልላል፡፡

ሰሎሞን የወይን ሐረግ መድኀኒቴ ሆነ ከሀሲሦን ይቆረጣል በጎልጎታ ይተከላል” ያለው ተፈጸመ መድኃኒት መስቀል መድኃኒት ክርስቶስን ተሸክሞ ታየ መድኃኒት ክርስቶስ የሚሰቀልበትን መስቀል ተሸክሞ ደፋ ቀና ብሎ መከራን ሲቀበል ተመለከትን መስቀሉን እርሱ ብቻ አይደለም ተከትዮቹ እነስምዖን ቀሬናዊም ተሸከሙት የድካሙ ተካፋይ ሆኑ፡፡ ልዩነቱ እነ ስምዖን ተገደው እኛ ግን ወደን ነው፡፡ እነ ስምዖን በአጋጣሚ እኛ ክርስቲያኖች ግን በዓላማ ክርስቶስን እንመስለው ዘንድ መስቀሉን የማይሸከም ለእኔ ሊሆን አይገባውም ብሎ አስተምሮናልና በተግባርም ፈጽሞ አሳይቶናልና፡፡
ከሰቀሉትም በኋላ እንዲህ ዘበቱበት “የእስራኤል ንጉሥ ከሆነ አሁን ከመስቀል ይውረድ እኛም እናምንበታለን” ማቴ.27፡40-42

“ኢየሱስንም ይዘው ወሰዱት መስቀሉንም ተሸክሞ በእብራይስጥ ጎልጎታ ወደተባለው የራስ ቅል ስፍራ ወደሚሉት ወጣ በዚያም ሰቀሉት” ዮሐ.19፡17፡፡ ራስ ቅል ስፍራ ማለት የአዳም የራስ ቅል የተቀበረበት ቦታ ነው መስቀሉ የተተከለበት ቦታም ይህ ነበር ለአዳምና ለልጅ ልጆቹ የተፈጸመ ካሳ ነውና፡፡

“እግዚአብሔርሰ ንጉሥ ውእቱ እምቅድመ ዓለም ወገብረ መድኃኒተ በማዕከለ ምድር” እግዚአብሔር ከዓለም በፊት ንጉሥ ነው በምድር መካከል መድኀኒትን አደረገ” መዝ.73፡13፡፡ ይህ መድኃኒት ዓለም የዳነበት ቅዱስ መስቀሉ አይደለምን?

“ተፈጸመ ተስፋ አበው በማርያም ድንግል ወበቀራንዮ ተተክለ መድኃኒት መስቀል” የአበው ተስፋ በድንግል ማርያም ተፈጸመ በቀራንዮም መድኃኒት መስቀል ተተከለ” እንዲል ስለሆነም መስቀልን ስናስብ ለእኛ የተከፈለውን የአምላካችንን የቤዛነት ሥራ የተቀበለውን መከራ የተገረፈውን ግርፋት የታሰረበት ሀብል የተሰቀለበትን መስቀል የጠጣውን መራራ ሐሞት እደቹ እና እግሮቹ የተቸነከሩበትን ቅንዋት /ችንካሮች/ ጎኑ የተወጋበትን ጦር የፈሰሰውን ደሙን የተቆረሰ ሥጋውን በጠቅላላው ለእኛ ሲል አምላካችን የተቀበለውን ጸዋትወ መከራ እናስባለን፡፡

ስለ መስቀል የሐዋርያት ትምህርት
ስለ ቅዱስ መስቀል ከክርስቶስ ቀጥሎ ያስተማሩት ቅዱሳን ሐዋርያት ናቸው፡፡ ርዕሰ ሐዋርየት ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ በማለት ያስተምራል፡፡ “ወበእንተ ኃጣውኢነ ውእቱ ተሰቅለ ዲበ ዕፀ በሥጋሁ ከመያውጽአነ እምኃጣውኢነ” ስለ ኃጢአታችን እርሱ በእንጨት /በመስቀል/ ላይ ተሰቀለ በመገረፉ ቁስል ተፈወሳችሁ” 1ጴጥ.1፡24 በማለት በመስቀሉ ክርስቶስ የከፈለልንን ዋጋ ነገረን፡፡
“ወንገረ መስቀሉሰ እበድ ውእቱ በኃበ ህጉላን ወለነሰ ለእለ ድኅነ ኃይለ እግዚአብሔር ወጥበበ እግዚአብሔር ውእቱ” 1ቆሮ.1፡18፡፡ 

“የመስቀሉ ቃል /ትምህርቱ/ ለሚጠፉት ሞኝነት ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚብሔር ኃይል ነው በማለት እግዚአብሔር ኃይሉን የገለጠበት ማዳኑን ያሳየበት ትድግናው የተከናወነበት መሆኑን ያስረዳናል፡፡ ይህን ዓለም አልተቀበለውም አላወቀምና፡፡

“እኛስ የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን” 1ቆሮ.1፡2 ሲል የክርስቶስ መገለጫው መስቀሉ ነው፡፡ ዙፋኑ ነውና ዲያብሎስን የቀጣበት ኃይሉን የሻረበት ነውና ሰው ይህን መቀበል ካልቻለ ሰው መሆኑ ያጠራጥራል፡፡

“እስመ ይቤ መጽሐፍ ርጉም ውእቱ ኩሉ ዘስቁል ዲበ ዕፅ ወለነሰ ተሣሃለነ እመርገማ ለኦሪት” መጽሐፍ በእንጨተ የተሰቀለ ሁሉ ርጉም ይሁን ይላልና እኛን ግን ከኦሪት ርግማን በእንጨት ተሰቅሎ ዋጀን” ገላ.3፡12፡፡

የኦሪትን ርግማን ተቀብሎ በእንጨት መስቀል ተሰቅሎ መርገሙን ወደበረከት ለወጠልን መስቀል የእርግማን ምልክት ሳይሆን የድል፣ የነጻነት፣ የበረከት ምልክት መሆኑን አወጀልን፡፡ እኛም ይህን ተቀብለን መስቀል ኃይላችን ነው መስቀል መድኃኒታችን ነው እንላለን፡፡ በመስቀሉ እንመካለን ጥግ አድርገን ጠላታችንን እንዋጋበታለን፡፡

“በሥጋ መልካም ሆነው ሊታዩ የሚወዱ ሁሉ እንድትገረዙ ግድ አሏችሁ ነገር ግን ስለ ክርስቶስ መስቀል እንዳይሰደዱ ብቻ ነው ገላ.5፡12፡፡ ነገር ግን ዓለም ለእኔ የተሰቀለበት /ከኃጢአት/ የተለየበት እኔም ለዓለም የተሰቀልሁበት /ከኃጢአት የተለየሁበት/ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በቀር ሌላ ትምክህት ከእኔ ይራቅ”

እዚህ ላይ ቅዱስ ጳውሎስ ከኃጢአት የተለየበት ከእግዚአብሔር ጋር የታረቀበት መመኪያው መስቀል እንደሆነ ከመሰከረ እኛስ ከእርሱ አንበልጥም እኔን ምሰሉ ብሎናልና” 1ቆሮ.11፡1፡፡ ስለዚህ ነው በመስቀሉ የምንመካው የምናከብረው ኃይላችን ብለን የምንጠራው መስቀሉን መስቀል የሰላም መሠረት ነው ጥልን /ዲያብሎስን/ የገደለ /ድል የነሣ/ ለሰው ሰላም የተደረገበት ነው፡፡

“ሰላምንም ያደርግ ዘንድ ጥልንም በመስቀሉ ገድሎ በእርሱ ሁለታቸውን /ሕዝብና አሕዛብን/ በአንድ አካል ከእግዚአብሔር ጋር ያስታርቅ ዘንድ ነው” ኤፌ.2፡16፡፡ “ወገብረ ሰላመ በደመ መስቀሉ ለእለ ውስተ ሰማይ ወእለ ውስተ ምድር ወዘታህቴሃ ለምድር በእርሱም በኩል በመስቀሉ ደም ሰላም አድርጎ በምድር ወይም በሰማያት ያሉትን ለራሱ /ከራሱ ጋር/ እንዲያስታርቅ ፈቅዷልና ቆላ.1፡20፡፡ ለዚህ ነው መስቀል ሰላም ነው የሰላም ምልክት ነው የምንለው ሰውና መላእክት ሰውና እግዚአብሔር ሕዝብና አሕዛብ ነፍስና ሥጋ የታረቁበት ነውና፡፡

“በትዕዛዛት የተጻፈውን የእዳ ጽሕፈት ደመሰሰው እርሱንም በመስቀል ጠርቆ አስወግዶታል ቆላ.2፡14፡፡ እንግዲህ የዕዳ ደብዳቤያችን የተሻረበት እኛ ጸጋና ክብርን የተጎናጸፍንበት የዕርቅ የሰላም የመዳን ምልክት ነው መስቀል፡፡

ስለዚህ ብዙዎች መስቀልን ይወዱታል በአንጻሩም ብዙወች ባለማወቅና በክፋት ይጠሉታል ሊቀብሩት ፈለጉ ለምን? ተአምራት በማድረጉ ድውይ በመፈወሱ ሙት በማስነሣቱ፣ እውር በማብራቱ ባለቤቱን ክርስቶስን እንደጠሉት ሁሉ መስቀሉን የጠሉ አይሁድ መስቀሉን ለ300 ዓመታት ቀበሩት መስቀል ገቢረ ተአምራት የሚያደረግ ተቀብሮ ይቀር ዘንድ የማይቻል ነውና በእሌኒ ንግሥት አማካኝነት ከተቀበረበት ወጣ መስቀል በጎልጎታ ብቻ አይደለም የተቀበረው በክርስቶሳውያን ልቡና ጭምር እንጂ ስለሆነም ቀብሮ ማስቀረት አይቻልም ይልቁንም ቤዛነቱን ኃይሉን ተአምራቱን አምኖ መቀበል ነው፡፡

በጥንታውያን ክርስቲያኖች መስቀል ተቀብሮ ከወጣበት ጊዘ ጀምሮ እሌኒ ንግሥት ቤተ መቅደስ ከሠራችለት ጊዜ ጀምሮ በመስከረም አሥራ ሰባት ቀን አሁን በኢትዮጵያ እንደሚከበረው ይከበር ነበር፡፡ ዛሬ ግን በኢትዮጵያ ብቻ በደማቅ ሁኔታ ሲከበር በሌሎች ታስቦ ይውላል፡፡ ይህም የሚያሳየው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቱያን ታሪክን በመጠበቅ ከሌሎች ይልቅ ምን ያህል ብርቱ እንደሆነች ያሳያል፡፡

ለመስቀሉ ጠላቶች የተሰጠ ተግሳጽ
ብዙዎች ለክርስቶስ መስቀል ጠላቶቹ ሆነው ይመላለሳሉና ብዙ ጊዜ ስለ እርሱ አልኳችሁ አሁንም እንኳ እያለቀስኩ እላለሁ መጨረሻቸው ጥፋት ነው ሆዳቸው አምላካቸው ነው ክብራቸው በነውራቸው ነው አሳባቸው ምድራዊ ነው” ፊል.3፡18፡፡

የመስቀሉ በረከት ይደርብን