ታላቅ የምሥራች ለኦርቶዶክሳውያን ምእመናን!

app-01

በማኅበረ ቅዱሳን የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ አገልግሎት ክፍል የተሠራው ‹‹ተዋሕዶ›› የተሰኘው የስልክ አፕሊኬሽን አንድሮይድ (Android) የተባለውን የቴክኖሎጂ ውጤት ለሚጠቀሙ ዘመናዊ ስልኮች እና የኪስ ኮምፒውተሮች አመቺ በኾነ መልኩ እንደገና ተሻሽሎ ቀረበ፡፡

ይህ አፕሊኬሽን በ፳፻፮ ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ ተዘጋጅቶ የነበረ ሲኾን፣ ክፍሉ ከተጠቃሚዎቹ የደረሱትን አስተያየቶች በማካተት ልዩ ልዩ ማሻሻያዎችን አድርጎ ለሁለተኛ ጊዜ እንዲቀርብ አድርጓል፡፡

አፕሊኬሽኑ በውስጡም የጸሎት መጻሕፍትን፣ ወቅታዊ የኾኑ መንፈሳዊ ትምህርቶችን፣ ዜናዎችን እና ልዩ ልዩ መረጃዎችን፤ ያሬዳውያን መዝሙሮችን፣ መንፈሳዊ የኪነ ጥበብ ዝግጅቶችን፤ እንደዚሁም የየዕለቱ ምንባባትን እና የሬዲዮ ሥርጭቶችን፤ የቀን መቍጠሪያዎችን፣ የበዓላትና አጽዋማት ማውጫዎችን፤ በተጨማሪም በሰሜን አሜሪካ፣ በካናዳ እና በአውሮፓ በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የሚከናወኑ መርሐ ግብራትንና ሌሎችንም አርእስተ ጉዳዮች አካቷል፡፡

በልዩ ልዩ የመገናኛ መንገዶችና ገጾች ላይ በሃይማኖት ስም የሚጻፉ የኑፋቄ ትምህርቶች በስፋት በሚለቀቁበት በዚህ ዘመን ይህ የቴክኖሎጂ ውጤት መዘጋጀቱ ለምእመናን ታላቅ የምሥራች ነው፡፡

ስለዚህም አንድሮይድ (Android) የተሰኘውን የቴክኖሎጂ ውጤት መጠቀም የሚችል ዘመናዊ ስልክ ወይም የኪስ ኮምፒዩተር ያላችሁ ምእመናን ዅሉ ከጎግል ፕለይ (Google Play) ውስጥ ተዋሕዶ (Tewahedo) የሚለውን ቃል በመፈለግ በዚህ አፕሊኬሽን እንድትጠቀሙና ኦርቶዶክሳዊ ይዘት ባለው ቃለ እግዚአብሔር ነፍሳችሁን እንድታጠግቡ፣ አእምሯችሁንም በመንፈሳዊ ዕውቀት እንድታጎለብቱ ስንል መንፈሳዊ ግብዣችንን እናቀርባለን፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ አገልግሎት ክፍል ይኼንኑ አፕሊኬሽን አይ ኦ ኤስ (IOS)ን ለሚጠቀሙ የእጅ ስልኮች እና የኪስ ኮምፒውተሮች ከአሁን በፊት ማቅረቡ የሚታወስ ነው፡፡