በትዳር ሕይወት የወላጆች ኃላፊነት

                                                                  ዲ/ን ተመስገን ዘገየ
መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር አምላክ ሰውን በአርአያውና በአምሳሉ ፈጠረው ይለናል (ዘፍ፪-፳፮) አዳም ብቻውን ይሆን ዘንድ ያልፈቀደውና ብቻውን ቢሆን መልካም እንዳልሆነ የሚያውቅ አምላካችን የምትረዳውን ሔዋንን ከጎኑ አጥነት ፈጥሮለታል፡፡እግዚአብሔር ወንድና ሴት አድርጎ መፍጠሩ ለበረከት፤ለመባዛት በመሆኑ”ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሉአት” በማለት ሕገ በረከትን ሰጥቷአቸዋል፡፡ስለዚህ ጋብቻ በሰው ፍላጎት ብቻ የተገኘ አይደለም፡፡ስለ ጋብቻ በኦሪትም በወንጌልም ሕግ ተሰርቷል፡፡የአዳምና የሔዋን ጋብቻ የሕጋዊ ጋብቻ መሠረት ነው፡፡ጋብቻን ያከበሩ በሕጋዊ ጋብቻ የነበሩ ደጋግ ቅዱሳን በሕገ ልቡና እንደነበሩ ሁሉ በሕገ ኦሪትም ነበሩ፡፡ለምሳሌ የኢያቄምና የሐና ጋብቻ ቅዱስ ጋበቻ ነበር፡፡የተቀደሰ ጋብቻ በመሆኑ የቅድስት ድንግል ማርያም ወላጆች የአምላካችን የመድኀኒታችን አያቶች ለመሆን በቅተዋል፡፡
እንዲሁም የዘካርያስና የኤልሣቤጥ ጋብቻ የተባረከ ጋብቻ ነበር፡፡ ቡሩክና ሕጋዊ በመሆኑም መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስን ማግኘት ችለዋል፡፡ጋብቻ የቅድስና ሕይወትን በሥርዓት የሚመሩበት የቤተሰብ መንግሥት በመሆኑ ክብሩና ልዕልናው ሊጠበቅ ይገባዋል፡፡ወላጆች ልጆችን መተካት አለባቸው ሲባል“መውለድ” ብቻ ማለት አለመሆኑን በሚገባ መረዳት ይገባል፡፡ቅዱስ ዳዊትም “ናሁ ጸጋሁ ለእግዚአብሔር ውሉድ ዕሤተ ፍሬሃ ለከርሥ፤ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ናቸው (መዝ፻፳፮፥፫) ልጆች ማደግ ያለባቸው በእግዚአብሔር ትእዛዝና መንገድ ነው፡፡ክቡር የሆነው የሰው ልጅ ቀርቶ አራዊትም እንኳን ልጆቻቻውን በሥርዓት ያሳድጋሉ፡፡ ለምሳሌ፤አናብስትና አናብርት አዳኝ የዱር እንሰሳት ልጆቻቻውን እንዴት እያደኑ ማደግ እንዳለባቸው ያስተምራሉ፡፡
ጠቢቡ ሲራክ “የሰው አነዋወሩ በልጆቹ ይታወቃል”ይላል (ሲራ፲፩፥፳፰) በ፳፩ኛው ክፍለ ዘመን የወጣቱ ሥነ-ምግባር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየዘቀጠ መምጣቱ እውነት ነው፡፡ለዚህም ዋናው መሠረታዊ ችግር ሕዝቡ ከእግዚአብሔር ጋር ያለው ግንኙነት በተለያየ ምክንያት እየዛለ መምጣ ነው፡፡ወላጆች ልጆቻቸውን ማስተማር ያላባቸው ቀዳሚ ትምህርት“እግዚአብሔርን መፍራት“ነው፡፡(ምሳ፩፥፯) ልጆች ለሚጠይቁት ጥያቄ እንደ ዐቅማቸው ማስረዳት ይገባል፡፡ ሕፃናትን የሚያስተምሩ ሰዎች በፍቅርና በደስታ ማቅረብ ይኖርባቸዋል፡፡ልጆች ከጣፈጭ ምግብ ይልቅ የሚረኩት ከወላጆች በሚያገኙት ፍቅር ነው፡፡ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “አባቶች ሆይ ልባቸው እንዳይዝል ልጆቻችሁን አታበሳጩ”ይላል (ቈላ፫፥፳፪) ልጆችን በፍቅር እንጂ በስድብ ፤በመደብደብ ፤በማበሳጨት፤በማስፈራራት ለማስተማር መሞከር እንደማይገባን ሐዋርያው አስተምሮናል፡፡
ሲራክ“የሰው አኗኗሩ በልጆቹ ይታወቃል (ሲራ፲፩፥፳፰) የላኪው ማንነት በተላከው እንደ ሚታወቅ የወላጆች ምንነት ማሳያ ልጆች ናቸው፡፡የኢትዮጵያ ሕዝብ ሥነ ምግባር የማይታይበት ልጅ ሲያጋጥማቸው”አሳዳጊ የበደለው” ይላሉ፡፡ስለዚህ ልጆችን በሥነ ምግባር ኮትኩቶ ማሳደግ ለነገ የማይባል ተግባር ነው፡፡አሁን አሁን በልጆቹ የሚደሰትና የሚጠቀም ወላጅ ሳይሆን በወለዷቸው ልጆች የሚያዝኑና የሚያለቅሱ ኢትዮጵያውያን ይበዛሉ፡፡ሲራክ “በሱ ጥፋት አንተ እንዳታፍር ልጅህን አስተምረው ያገለግልሃል”(ሲራ፴፥፲፫) ልጅን በሚገባ አስተምሮ ማሳደግ በጣም አስፈላጊ መሆኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ያሰተምሩናል፡፡ የካህኑ የዔሊ ልጆች ፊንሐስና አፍኒን በታቦተ ጽዮን ድንኳን ሥር ያመነዝሩ ነበር ያሳፍራል፡፡ ዔሊ ልጆቹ ይህን የመሰለ ኃጢአት መፈጸማቸውን እያወቀ ባለመገሰጹ ቅጣት ተቀብሏል፡፡ልዑል እግዚአብሔር ዔሊን “ከእኔ ይልቅ ልጆችህን ለምን አከበርክ?(፩ኛሳሙ፪፥፳፱) በማለት ተቆጣው፡፡ሁለት ልጆቹንም ቀሰፋቸው፡፡ቅጣቱ በልጆቹና በእሱ ብቻ ተወስኖ አልቀረም፡፡ለሌላም ተረፈ አንጂ፡፡
ወላጆች ሆይ ልጆቻችንን እንዴት እናሳድጋቸው?
የነገው ትወልድ ሀገሩንና ቤተሰቡን የሚጠቅም በሥነ- ምግባር የታነጸ በሥራው የተመሰገነ ይሆን ዘንድ ዛሬ ያሉትን ልጆች በአግባቡ መያዝ ልዩ እንክብካቤ ማድረግ ይገባል፡፡ወላጆች ከማንም በላይ ሕፃናትን መልካሙንና ክፉንም በማሰተማር ቅርብ ናቸው፡፡እናትና አባት ከትምህርት ቤት ሲመለሱ ስለተማሩት ትምህርት መጠየቅ አለባቸው፡፡ልጆችም እንደሚጠየቁ ስለሚያውቁ ትኩረት ሰጥተው ይከታተላሉ፡፡ጥሩ ነገር በሠሩ ጊዜ ጥሩ ወጤት ባመጡ ጊዜ ሽልማት ማዘጋጀት ይገባል፡፡ወላጆች በቤት ውስጥ በቃል ሳይሆን በተግባር በክፉነት ሳይሆን በደግነት እያስተማሩ ሊያሳድጉ ይገባል፡እንዲህ ከሆነ የክፉ ምግባር ቦይ አይሆኑም፡፡አንድ ሰው በቅሎ ጠፋችበትና ወዲያ ወዲህ እየተንከራተተ ሲፈለግ በበቅሎ ሌብነት የሚጠረጠረው ሰው አብሮ ያፋልገው ጀመር፡፡ዘመድ መጥቶ “በቅሎህ ተገኘችልህ ወይ”ብሎ ቢጠይቀው አፈላላጊዬ የበቅሎዬ ሌባ ስለሆነ እንደምን አድርጌ በቅሎዬን ላገኛት እችላለሁ አለ ይባላል፡የልጆችን አእምሮዊ ዕድገት ለማሟላት ከሚደረጉ እንክብካቤዎች የሚከተሉት ይጠቀሳሉ
ተገጣጣሚ መጫዎቻዎችን በመጠቀም የቁጥር ስሌት እንዲያውቁ ማድረግ፤የቋንቋ ችሎታቸውን የሚያሳድጉ መንፈሳዊ ጹሑፎችን እንዲያነቡ ደጋግመው መንገርና ዕድሎችን ማመቻችት፡፡ወላጆች (ባልና ሚስቱ) በአንድነት ሁነው የቤተሰቡ መሪ በመሆናቸው ሊወስዱት የሚገባ ተግባር ይኖራል፡፡ልጆቻችንን በምግባር በማሳደግ የሚኖሩበትን ቤት የዕለት ከዕለት እንቅሰቃሴ እየተከታተሉ መሥመር በማስያዝ አገልጋዮች የሆኑ የቤት ሠራተኞችን ሳያማርሩ ሥራ ሳያበዙ በማሠራት መኖር ይጠበቅባቸዋል፡፡ወላጆች ይህንን ከባድ የቤተሰብ ኃላፊነት ሲወጡ በሚከተሉት ነጥቦች ቢመሩ መልካም ነው፡፡
፩.. በፍቅር፤ ልጆች ፍቅርን እንክብካቤን ከወላጆችና ከመምህራን ይፈልጋሉ፡፡የወላጆቹን ፍቅር እያገኘ ያደገ ልጅ መንፈሰ ጠንካራ፤ለሰው የሚያዝንና ታዛዥ ይሆናል፡፡አንዳንድ ወላጆች የቤተሰቡ ራስ መሆናቸውን በቊጣ በዱላ በመግለጽ ልጆቻቸውን በኃይል ብቻ ለመግዛት የሚሞክሩ አሉ ፡፡ይህ የተሳሳተ መንገድ ነውና ከስሕተት ጎዳና መመለስ ይኖርባቸዋል፡፡
፪..ትኩረት በመስጠት፣ ልጆች ከፍተኛ የሆነ ክትትልና ትኩረት ይፈልጋሉ፡፡የሚያከናውኑትን እያንዳንዱን ተግባራት እየተመለከተ በጎውን በጎ የሚላቸው ሲሳሳቱ የሚያርማቸው ይሻሉ፡፡ ልጆችን በንቃት መከታተል የወላጆችና የመምህራን ግዴታ ነው፡፡ወላጆች በዕረፍት ጊዜ ከልጆቻቸው ጋር መወያየት፣መመካከር፣የወደፊት ዕቅዳቸውን ምኞታቸውን በተመለከተ በግልጽነት መረዳት ይገባቸዋል፡፡
፫. በማስተማር፤ ንግሥት ዕሌኒ ቆስጠንጢኖስን በሥርዓት ኮትኩታ በማሳደጓ የሀገረ መሪ ለመሆን በቃ፡፡አሁንስ እኛ ልጆቻችንን እንዴት እያሳደግናቸው ነው? ሰው በሕፃንነቱ ተክል ማለት ነው፡፡ተክል የሚሆነውን ሁሉ ሊሆን ይችላል፡፡ቀጥ ብሎ ያድጋል ተወላግዶም ያድጋል የተወላገደውን ለማቃናት ብዙ ዋጋ ያስክፍላል፡፡ወላጆች በልጆቻቸው ዕድገት ትኩረት ሊሰጡት የሚገባ አንዱና ዋነኛው የልጆቻቸውን ተፈጥሮዊ ተሰጥኦ ማበልጸግ ነው፡፡ወላጆች ልጆችን የማሳደግ ክህሎት ለማዳበር ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ ይኖርብናል፡፡ከእኛ ቤት ሲገባ ግን መጸሕፍት ይኖር ይሆን? በተለያዩ የቤተሰብና የልጆች ነክ ጉደዮች በመሳተፍ ከተቻለ የሥነ ልቡና ባለሙያና የአብነት መምህራንን በማማከር የተሻለ ዕውቀት መጨመር ይቻላል፡፡
የልጆችን ተሰጥኦ ከልጅነታቸው ጀምሮ መረዳትና እውቅና መስጠት ለወላጆች ትልቅ ስኬትና አበረታች ነገር ነው፡፡ወላጆችና የአብነት መምህራን ልጆች ችሎታቸውን የሚያወጡበትን አማራጮችና ዕድሎችን ማመቻችት ይገባቸዋል፡፡በእኛ ሀገር ደረጃ ጥረህ ለፍተህ ብላ ኑር ነው እንጂ አማራጭ አንሰጥም ይህ ዘመንን አለመዋጀት ነውና መስተካከል ይኖርብናል፡፡የልጆችን እንቅስቃሴ በመከታተል የልጆችን ፍላጎት ማወቅ ይገባል፡፡ወላጆች ከትምህርት ስኬት ባሻገር የልጆቻቸውን ማኀበራዊ መንፈሳዊና ሥነ-ልቦናዊ ሕይወት መረዳት አለባቸው፡፡ወላጆችና መምሀራን ልጆችን ሲያናግሩ ሙሉ ትኩረት መስጠት አለባቸው፡፡
ልጆችን በልዩ ልዩ እንቅስቃሴዎች ማሳተፍ ይገባል
ወላጆች ልጆቻቸውን ሲያሳድጉ በትምህርታቸው ብቻ ስኬታማ ሆነው ትምህርታቸውን አጠናቀው እንዲመረቁ ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ በመንፈሳዊ ሕይወታቸውም ስኬታማነት እንዲ ዘጋጁ የማደረግ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ልጆችን ከትምህርት ቤት መልስ በተለያዩ ተግባራት እንዲሳተፉ ማድረግ የሚከተሉት ጠቀሜታዎች ይኖሩታል፡፡
ቴሌቪዥን በመመልከትና ጌም በመጫዎት የሚያሳልፉትን ጊዜ በመገደብ በሠርክ ጉባኤና በሰንበት ትምህርት ቤት ከመደበኛው ከትምህርት ውጭ የሆኑ ተግባራት ሲሳተፉ ወሳኝና ለወደፊት ሕይወታቸው ከፍተኛ ጠቀሜታ ያላቸው ማኀበራዊ ክህሎቶችን እንዲያዳብሩ ይረዳቸዋል፡፡ በውኃ ውስጥ መዋኘትም ለልጆች የሚመች የእንቅስቃሴ አይነት ነው፡፡በሳምንት ሁለት ጊዜ (ቅዳሜና እሑድ) ቢዋኙ አካላዊ ብቃታቸውን ያሻሽላል፡፡የመተንፈስ እንቅስቃሴ በማሻሻል ሂደት ለልጆች ጤንነት የአካል ብቃት የላቀ አስተዋጽኦ አለው፡፡ከትምህርት ቤት መልስም ሆነ በዕረፍት ቀናት የእግር ኳስ እንቅስቃሴ ማድረግ ወላጆች አብረው በመጫወት ካልተቻለም ልጆች ሲጫወቱ በመከታተል ,.በተግባር በማሳየት፣ልጆች ከሚሰሙት ይልቅ በሚያዩት ይሸነፋሉ፡፡ ከተነገራቸው ይልቅ የተመለከቱት በእነርሱ ኀሊና ትልቅ ቦታ አለው፡፡ ወላጆች ተግባራዊ የሆነ ሕይወትን ለልጆቻቸው ሊያስተምሩ ይገባል፡፡አሁን በየቤታችሁ ልጆች ምንድን ነው የሚያዩት አንዳንድ ወላጆች ልጆቻቸውን እንዳይጠጡ እየመከሩ እነርሱ ጠጥተው የሚገቡ አሉ፡፡አሁን የዚህ ሰውየ ልጅ ምን ይሆናል? ልቡ ባዶ ቅርጫት ራሱ ባዶ ቤት እየሆነ ነው፡፡ ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ በማስገዛት ልጆችን መልካም የሆኑ ነገሮችን ማስተማር አለብን አንድ ወቅት ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ “ራሱን ያሸነፈ የጎበዝ ጎበዝ ነው ሌለውን ያሸነፈ ተራ ጎበዝ ነው” ብለው ነበር፡፡ በዘመናችን ራስን ማሸነፍ ሰማዕትነት ነው፡፡
• ልጆች ማኅበራዊ ሚዲያዎችን በአግባቡ መጠቀም ይኖርባቸዋል
የመረጃ ልውውጥ ከማደረግ (በጎን መጥፎውንም) ማኅበራዊ ግንኙት ከማጠናከር (የጠፉ ጓደኞችን) ከማገናኘት አንጻር በአግባቡ ከተጠቀሙበት ትልቅ አስተዋጽዖ አለው፡፡የማኅበራዊ ሚዲያዎች ጉዳት ተመልሶ የማይገኝ ጊዜን ያባክናል፡፡አጠቃቀማችን በአግባቡ ካልሆነ ለትዳር ጠንቅ ነው ራሳቸውን አግዝፎ ለማሳየትና ማኅበራዊ ሚዲያዎችን ለዝሙት የሚጠቀሙ አሉ፡፡ በዘመናችን ችግሩን መናገር በራሱ ችግር ነው እንጂ ቴክኖሎጂው እየተራቀቀ ሲመጣ የትውልዱም ጥያቄ እንዲሁ እየተበራከተ ይመጣል፡፡የ፳፩ኛውን ክ/ዘመን ትውልድ ሥነ ልቡና በመረዳት ወላጆች እንደ እባብ ብልህ በመሆን ትውልዱ ያለበትን ሁኔታ ቀድመው ምን እየመጣ እንደሆነ መመልከት ይኖርባቸዋል፡፡
የመረጃ ቴክኖሎጂ ዓለምን ወደ አንድ መንድር እየተቀረ በመምጣቱ ሀገራችንም የዚሁ ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ በመሆኑ አደጋ አለው፤በአግባቡ መጠቀምና መቆጣጠር አለመቻል መሠረታዊ ችግር ነው፡፡ልጆቻችን ውጤታማና ስኬታማ እንዲሆኑ ለማድረግ የመረጃ ቴክኖሎጂ አጠቃቀማቸውን መገደብና መቆጣጠር የወላጆች ኃላፊነት ነው፡፡ልጆች በቪዲዮ ጌም መጫወት ካለባቸው በወላጆች በጥንቃቄ የተመረጡ፣አዝናኝና የልጆችን የፈጠራ ችሎታ የሚያበለጽጉ ፣ለዕድሜአቸውና ለሥነ-ልቡናቸው የሚመጥኑ ቁጣና ጥቃት ያልበዛባቸው መሆን እንዳለባቸው ባላሙያዎች አበክረው ይመክራሉ፡፡የሚያስፈሩ ቪዲዎችና ጌሞችን የሚጫወቱ ልጆች የበለጠ ቍጣና ጥላቻ የሚያሳዩ ይሆናሉ፡፡ልጆች ያለ ገደብ ቴክኖሎጂ ከተጠቀሙ የአእምሮ ዕድገታቸው ይጎዳል፡፡የትምህርት አቀባባል ድክመት ያጋጥማቸዋል፡፡ላልተፈለገ የሰውነት ውፍረት ያጋልጣል፡፡ ለማሰታወስ ችግር ያጋጥማችዋል፡፡የቴክኖሎጂ ሱሰኛ ያደርጋል፣የእንቅልፍ እጦት ያጋጥማቸዋል፡፡
የልጆች ሥነ- ምግባርና መንፈሳዊ ሕይወት በምን ምክንያት ሊበላሽ ይችላል-?
በቂ ቁጥጥር ካለማድረግና ወላጅ ልጆቹን ሥነ-ምግባር ስለማያስተምር ታላላቆቻቸው እና ቤተሰቦቻቸው ሥነ-ምግባርን በማስተማር ረገድ ደከሞች በመሆናቸው፡፡ ሕፃናቱ አብረው የሚውሉት አብረው የሚማሩት ሰው ማንነት እንዲሁም የሚውሉበት አካባቢ መጥፎ መሆን ለእነርሱ የማይገቡ የማይመጥኑአቸውን ፊልሞችና ድርጊቶች ስለሚመለከቱ አንዳንድ ትምህርት ቤቶች ሥነ- ምግባርን አስመልክቶ የሚያስተላልፉት መልእክት አነሳ መሆን የሚያስፈልጋቸውን ነገሮች ባለማግኘት ምክንያት አግባብነት ወደ ሌላቸው ቦታዎች ሊሄዱ በመቻላቸው ምክንያት ነው፡፡ ልጆቻችን መከራ እንዲቋቋሙ አድርገን እናሰልጥናቸው ችግር ሲመጣ የሚቋቋሙ አናድርጋቸው፡፡ሕፃናት በማይጠቅሙ ዓለማዊ ፊልሞች ጨዋታዎች ድራማዎች፤ፍቅር ሰጥመው ካደጉ በኋ ክፉ ነገር ተው ብንል እንዴት ይቻላል? ልጆቻቸውን በሥርዓት ያስተማሩና ከቅጣት ያዳኑ ደጋግ አባቶች ነበሩ፡፡መጽሐፍ “ከእግዚእበሔር ሕግ እንዳይወጡ ሴት ልጆቻቸውንና ወንድ ልጆቻቸውንም፡አስተምረው ነበርና፤የሚቀርባቸው ክፉ ጠላት አልነበረም (፩መ.መቃቢያን፲፱፥፲፫)

 ወላጆች ለልጆቻቸው የእግዚአብሔርን ድንቅ ተኣምራት ፤የጻድቃንና የሰማዕታት ገድልና የሀገራቸውን ታሪክ በሚገባቸው መጠን እያስጠኑ የማሳደግ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ከወላጅ ወደ ልጆች መተላለፍ የነበረበት የቃል ትምህርት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየደበዘዘ በመምጣቱ በትውልዱ ዘንድ ክፍተቱ እየበዛ መጥቷል፡፡በጥንቱ ባሕል መሠረት ልጆች ወላጆቻቸውን ቁመው ማብላት ነበረባቸው፡፡በእራት ጊዜ የእንጨት መብራት ይዞ ያበላ ነበር፡፡ይህም ቢሆን ልጅ ለወላጅ ያለውን አክብሮት ለመግለጽ የሚደረግ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጥንተ መሠረት ያለው ነው፡፡(ሉቃ፲፯፥፰፤፳፪፥፳፯)
ወላጆች ልጆቻቸውን በሥነ-ምግባር ኮትኩተው በሥነ ሥርዓት አስተምረው የማሳደግ ኃላፊነት እንዳለባቸወ ሁሉ ልጆችም ወላጆቻቸውን የመታዘዝ፤የማክበር ግዴታ አላባቸው፡፡ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ”ልጆች ሆይ ይህ ለጌታ ደስ የሚያሰኝ ነውና ለወላጆቻችሁ ታዘዙ”ይላል( ቈላ፫፥፳)ከሁሉ በፊት እናትና አባቱን የሚያከብር ልጅ ዕድሜው ይረዝማል(ዘጸ፳፥፲፪) ምክንያቱም ይመረቃልና፡፡ወላጆቹ የመረቁት ልጅ በእግዚአብሔር ዘንድም የተወደደ ነው፡፡ በመንፈሳዊና በምድራዊ ሀብት የበለጸገ ይሆናል፡፡”ምርቃት ትደርስህ ዘንድ ቢጠራህ አቤት ቢልክህ ወዴት ብለህ አባትህን አክብረው “(ሲራ፫፥፱) በታዛዥነታቸው፤በትሕትናቸው በወላጆቻቸው ከተመረቁት መካከል ያዕቆብንና ርብቃን ለአብነት ማንሳት ይበቃል (ኩፋ፳፥፷፭፤ዘፍ፳፬፥፷ ፤ኩፋ ፲፬፥፴፱)
ዲድስቅልያ አንቀጽ ፲፩፥፩ ”እናንትም አባቶች የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ይጠብቁ ዘንድ የክርስቶስን ጎዳና ይከተሉ ዘንድ ልጆቻችሁን አስተምሯቸው እጅ ሥራ አገልግሎት ይማሩ ዘንድ እዘዟቸው ሥራ ፈት ሁነው እንዳይቀመጡ”ይላል፡፡ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ ሚያዝያ 23 ቀን 1982 ዓ.ም በሻሸመኔ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ሲያሰተምሩ ”ልጆቻችሁ ከመዝሙር ጋር ደግሞ ሃይማኖታቸውን ፤ሥነ ምግባራቸውን እንዲማሩ ያስፈልጋል፡፡ወደ ቤተ ክርስቲያን ስትመጡ ልጆቻችሁን ይዛችሁ ኑ ብቻችሁን ከመጣችሁ የምተሠሩትን አያውቁም፤ወደየት እንደ ሄዳችሁም አያውቁም፡፡ወራሾቻችሁም አይሆኑም ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን ስትመጡ ልጆቻችሁን ይዛችሁ ኑ፤ሥዕሉን ይሳሙ፤ቅዳሴ ጠበሉን ይጠጡ ፡በእምነቱ አሻሹአቸው መስቀል እንዲሳለሙ አስተምሯቸው ዕጣኑንም ያሽትቱ የሚታጠነውን፤ሥጋወደሙን ይቀበሉ፤ቃጭሉን ይስሙ፤ደወሉ ሲደወል ይስሙ፤ቄሳቸው ማን እንደሆነ ቤተ ክርስቲያናቸው ማን እንደሆነች በውስጧም ምን ምን እንደሚሠራ ያጥኑ ፤ይማሩ፡፡ ወደ ሰንበቴም ስትሄዱ ይዛችኋቸው ግቡ ወደ ሰንበቴም ዳቦውን ተሸክመው ይምጡ እነርሱም ነገ ይህንን እንዲወርሱ የነገ ባለ አደራዎች መሆናቸውን እንዲያውቁ፡፡መመካት አይገባም የሚገባ ቢሆን እኛ ከዓለም ሁሉ የበለጠ መመካት ይገባን ነበር፡፡ምከንያቱም አባቶቻችንና እናቶቻችን ሥርዓታችንንና እምነታችንን ሁሉ ሰፍረው ቆጥረው ያስቀመጡልን ስለሆነ፤ይህ ትውልድ ይህንን ከቀበረ በኋላ ይህንን ካጠፋ በኋላ እንደገና ቤተ መዘክር እንዳይሄድ ነው ሃይማኖቱን ፍለጋ፤ታሪኩን ፍለጋ፤ስለዚህ እምነታችሁን፤ሥርዓታችሁንና መንፈሳዊ ውርሳችሁ እንድትጠብቁ አደራዬ የጠበቀ ነው”ብለው ነበር፡፡

ምንጭ፤ሐመር መጽሔት ፳፮ኛዓመት ቊ ፮ ጥቅምት ፳፻፲ወ፩ ዓ.ም