kidus estifanos

ቅዱስ እሰጢፋኖስ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አስተምህሮ

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
ዳር 17/2004 ዓ.ም

ስለ ቅዱስ እስጢፋኖስ  ክፍል አንድ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ

 

አይሁድን ቀርቦ ለመረመራቸውም አሕዛብ ከሆኑት ከፋርስ ወገን እንደሆኑ እንዲሁም አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ተአምራትን ሳይሻ ለእግዚአብሔር መከራዎቹን ሁሉ ታግሦና ተቋቁሞ የተመላለሰው እንደሆነ እግዚአብሔር ልጁ እንደሚያደርገው፣ እንዲሁም የሁሉ አባት አብርሃም እንዳደረገው የአባቶችን መቃብርና ያለንን ሁሉ በመተው ልንታዘዝ እንደሚገባንም ጠቁሞናል ፡፡

kidus estifanos

የአብርሃም አባትና ዘመዶቹ ምንም እንኳ ረጅም ጉዞ ከአብርሃም ጋር ቢጉዋዙም ከንዓንን ይወርሱ ዘንድ የተገባቸው ካልሆኑ ልጆቹስ ላይ እንዴት ይህ እጣ ፈንታ አይደርስባቸው ይሆን? “ነገር ግን ልጅ ሳይኖረው ለእርሱ ከእርሱም በኋላ ለዘሩ ርስት አድርጎ ይሰጠው ዘንድ ተስፋ ሰጠው፡፡” አለ፡፡ በዚህ የእግዚአብሔርን ድንቅ ስጦታንና የአብርሃምን እምነት ታላቅነት እንመለከታለን፡፡ “ልጅ ሳይኖረው” የሚለው አገላለጽ የእርሱን በእምነት መታዘዝን የሚገልጥ ነው፡፡ “ለእርሱ ከእርሱም በኋላ ለዘሩ ርስት አድርጎ ይሰጠው ዘንድ”የሚለው በድርጊት ከታየው ጋር ስናነጻጽር የተቃረነ መስሎ ይታየናል፡፡ ምክንያቱም አስቀድሞ “በዚችም የእግር ጫማ ስንኳ የሚያህል ርስት አልሰጠውም” እንዲሁም ልጅም አልነበረውም ይለናልና፡፡ እነዚህ ዐረፍተ ነገሮች አብርሃም በእምነቱ ከተሰጠው ጋር የሚጣጣሙ ላይመስሉን ይችላሉ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ሊሰጥ ያሰበውን ያንኑ ነው የሚሰጠው፡፡ በዚህ ቦታ ግን ቃሉና ድርጊቱ የተቃረኑ ይመስሉናል፡፡ ነገር ግን እንደ እኛ አስተምህሮ ፈጽሞ የሚጣረሱ አይደሉም፡፡ እንደውም ፈጽመው የሚጣጣሙ እንጂ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ በዚህ እንደምንደክም ነገር ግን እረፍታችን በላይ በሰማይ እንደሆነ አስተምሮናል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ እስጢፋኖስ እንዲህ አለ፡፡

 

“ስለምን የተስፋው ቃል እንደተፈጸመ እናስባለን ? ስለምን ነገሮችን እናምታታቸዋለን? በዚህም ምድር መከራን ተቀበላችሁን? በድህነት ለመኖር ተገደዳችሁን? አዘናችሁን? በዚህ አትጨነቁ፡፡ ስለ ክርስቶስ ስትሉ በዚህ ምድር የምትቀበሉት መከራ በሚመጣው ዓለም ዕረፍት ያሰጣችኋል፡፡ የዚህ ምድር መከራችሁ ለዘለዓለማዊ ዕረፍታችሁ ምክንያት ነው፡፡ “ይህ ሕመም” ይልና “የእግዚአብሔር ልጅ በእርሱ ይከብር ዘንድ ስለእግዚአብሔር ክብር ነው ለሞት አይደለም”ይለናልና (ዮሐ.11፡ 4) በሚመጣው ዓለም የምንቀበል ከሆነ ፍርዱ ነው፤ ነገር ግን በዚህ ምድር የምንቀበለው መከራ የምንማርበትና የምንታረምበት መከራ ነው፡፡ ፍልሚያው በዚህ ምድር ነው ኃጢአትን ደምን እስከማፍሰስ ደርሶ መዋጋት የእኛ ድርሻ ነው፡፡ ጦርነቱ በዚህ በምድር እንጂ በሰማያት አይደለም፡፡ በውጊያ ላያ ያለ ወታደር ዕረፍትን ሊሻት አይገባም፡፡ በውጊያ ሰፈር እንደንጉሥ የቅምጥልንነት ሕይወትን ሊኖር አይገባውም፣ ሀብትን ለመሰብሰብ ወይም ስለቤተሰቡ በማሰብ ሊጨነቅ አይገባውም፡፡ አንድ ወታደር ውጊያው ላይ ብቻ ሊያተኩር ይገባዋል፡፡ እርሱም በጠላቴ ላይ እንዴት ድልን ልቀዳጅ እችላለሁ የሚለው ነው፡፡ በዚህ ምድር ስንኖር ስንቃችን ይህ ይሁን፡፡ እንዲህ ከሆነ በጠላት ተሸንፈን ከሆነ ተመልሰን ድል እንነሣዋለን፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ሁሉን የጦር ትጥቆች አስታጥቆናል፡፡ ጠላታችንን ዲያብሎስ እንዴት ድል መንሣት እንችላለን የሚለው ብቻ የእኛ ግብ ይሁን፡፡ እንዲህ የምናስብ ከሆነ ልምምዳችንም ይህ ይሆናል፡፡ የእግዚአብሔር ጸጋም ይህን እንድናከናውን የድርሻውን ይወጣል፡፡ ስለዚህም እንዴት የሚረዳንንም የእግዚአብሔር ጸጋ ማቅረብ እንደምንችል እንወቅበት፡፡ እንዲህ ከሆነ “እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ከሆነ ማን ይቃወመናል” (ሮሜ.8፡31) አንድ ነገር ብቻ የእኛ ልምምድ ይሁን እርሱም እግዚአብሔር አምላክ የእኛ ጠላት በመሆን ፊቱን ከእኛ እንዳይመልስ ነው፡፡


መከራን በመቀበላችን ክፉ ደረሰብን ብለን አንመረር፤ ነገር ግን ኃጠአትን በፈጸምን ወቅት መከራ እንደመጣብን እንቁጠር፡፡ ይህ ነው መራሩ መከራ፡፡ እኛ ግን በዚህም ምድር ኑሮአችንን በቅንጦት እያሳለፍን የሚመጣውን ዓለም ሕይወት ለመስበክ አንሻም፡፡ እንዳውም በሚመጣው ዓለም የምንኖረው እንዲህ ዓይነት ሕይወት እንደሆነ እናስተምራለን፡፡ ሕሊናችን እንዴት በኃጢአት እንደተጨማለቀ እስቲ ቆም ብለን እናስብ ፡፡ ይህ ከሌሎች ቅጣቶች ይልቅ አጅግ ከባዱ ቅጣት አይደለምን?

 

በኃጢአት ሕይወት ለሚመላለሱ ወገኖች ምንም እንኳ የራሳቸውን ኃጢአት የማያስተውሉ፣ ስለጽድቅ መከራን ለመቀበል ለሚሰቀቁ ነገር ግን በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ ለሚኖሩ … አንድ ጥያቄ ላንሣ፡፡ በወዲያኛው ዓለም ዕረፍትን ማግኘት ትፈልጋላችሁን? በዚህ ምድር ስለክርስቶስ ስትሉ መከራን ተቀበሉ፡፡ ይህን የመሰለ ዕረፍት ፈጽሞ አታገኙም፡፡ ሐዋርያት ስለክርስቶስ ሲሉ በተቀበሉት መከራ ደስተኞች ነበሩ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህን አስመልክቶ “በጌታ ደስ ይበላችሁ” (ፈልጵ.4፡4) አለ፡፡ እየታሰሩ እየተገረፉ በሸንጎ ፊት እየቀረቡ እንዴት ነው ደስ ሊላቸው የቻለው? ሁሉም ደስተኞች ነበሩ ይላልና፡፡ እንዴት እንዲህ ደስ ሊላቸው ቻለ ብለህ ጠይቅ፡፡ እንዴት ደስ ላይላቸው ይችላል፡፡ ሕሊናቸው እኮ ከኃጠአት ንጹሕ ነው፡፡ ስለዚህ እጅግ ልዩ በሆነ ደስታ ውስጥ ይዋኛሉ፡፡ መከራቸው በበዛ ቁጥር እንዲሁ ደስታቸውም ከመከራቸው እጥፍ ይጨምርላቸው ነበር፡፡

 

አንድ ወታደር በጦር ሜዳ ደጋግሞ ቢቆስልና ወደቤቱ በድል አድራጊነት ቢመለስ ደስታው ታላቅ አይሆንምን? በጦር ሜዳ ስለመዋሉ ቁስሉ በግልጥ አይናገርምን? ለትምክህቱስ ምስክር አይሆኑለትምን? አንተም ልክ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ በደስታ “እኔ የኢየሱስን ማኅተም በሥጋዬ ተሸክሜአለሁ”(ገላ.6፡17) ለማለት የበቃህ እንድትሆን ዘንድ ስለክርስቶስ መከራን ለመቀበል አትሰቀቅ እንዲህ ያደረግህ ከሆነ ደስታህ እጅግ ታላቅ በክብር ያጌጠ ይሆናል፤ በአምላክም ዘንድ የታወቅህ ትሆናለህ፡፡

 

ለክብር የማያበቃህ መከራ የለም ስለዚህም አንድ ሰው በአንተ ላይ በጠላትነት ቢነሣብህ ክርስቶስን አስበህ ክፉ ቃል እንዳትናገር ፍራ፤ እናም የትዕቢትን አገዛዝ በጽናት ተቋቋመው፤ ቁጣንና ሴሰኝነትንም በጽናት ተቃወማቸው፡፡ እነዚህ ለአንተ እንደ ማኅተም ናቸው፡፡ እነዚህ ለአንተ እንደግርፋት ናቸው፡፡ አንድ ነገር ልጠይቃችሁ የትኛውን ነው የከፋው ግርፋት የምትሉት? ነፍስ በገሃነም እሳት የምትገረፉትን መገረፍ አይደለምን? በዚህ ምድር መከራ ብንቀበል በሥጋችን ነው፡፡ ነገር ግን በሚመጣው ነፍሳችንም ሥጋችንም ነው መከራ የሚቀበሉት፡፡

 

ሁሉም ክፋቶች ከነፍስ ይመነጫሉ፡፡ አንድ ሰው ቢቆጣ ቢቀና እኒህን የሚመሰሉ ክፋቶችን ቢፈጽም በነፍሱ ላይ ስቃይን እያመጣ ነው፡፡ ምንም እንኳ እነዚህ ክፋቶች ወደ ድርጊት የተመለሱ ባይሆኑም መቆጣትና ቅናት አንዲሁም እነዚህን የመሰሉ ሁሉ ኃጢአቶች ናቸው፡፡ በእርግጥም ቁጣና ቅናት ነፍስን የሚያቆስሉና የሚጎዱ መከራዎችም ናቸው፡፡ ስለዚህም ተቆጥተህ እንደሆነ በመከራው ውስጥ ራስህን እንደጣልህ ቁጠር፡፡ እንዲህ ከሆነ የማይቆጣ ሰው ራሱን መከራ ውስጥ አልጣለም ማለት ነው፡፡

 

የተሰደበ ሰው መከራን በነፍሱ እየተቀበለ ነው ብለህ ታስባለህን ? አይደለም ነገር ግን ከላይ እንዳስተማርኩት ተሳዳቢው በነፍሱ መከራን እየተቀበለ ነው፡፡ ስለዚህም እነዚህ ነገሮችን መፈጸም አንድ ሰውን ኃጠአተኛ የሚሰኙት ከሆነ መከራ አለበት ማለት ነው፡፡ ስለዚህም መከራ እየተቀበለ ያለው ተሰዳቢው ሳይሆን ተሳዳቢው መሆኑን መረዳት ይቻለናል፡፡

 

አንተ “እርሱን ልጄን ሞኝ ብሎ ተሳድቦአል” ልትል ትችላለህ፤ ነገር ግን አንተ ለስድቡ አጸፌታውን በመመለስ በበደል እርሱን አትምሰለው፡፡ አንድ ነገር እጠይቅሃለሁ ይህ ሰው መልካም ነገር አደረገን? አንተ እርሱ መልካም አድርጎአል አትልም፤ ስለዚህም እርሱ የፈጸመው መልካም ካልሆነ አንተ እርሱ የፈጸመውን ከማድረግ በመከልከል መልካምን አድርግ፡፡ ልጅህ በመሰደቡ ምን ያህል ቁጣ በውስጥህ እንደሚቀጣጠል እረዳለሁ፡፡ ነገር ግን አንተ “ እርሱ ልጄን የሰደበ ከሆነ እንዴት ነው ይህን ሰው እኔንም ከመሳደብ የሚመለሰው? ብለህ ትጠይቅ ይሆናል፡፡ እንዲህ ያደረገውን ሰው በትሕትና ገሥጸው፣ ምከረው ብዬ እመክርሃለሁ፡፡ ትሕትና ቁጣ አንዱ ካንዱ የሚቃረኑ ጠባያት ነው፡፡ በትሕትና ቁጣን ማብረድ ይቻልሃል፡፡

 

በእኛ ላይ ክፉ ስለተፈጸመብን በምላሹ እኛም ክፉን ልንፈጽም አይገባንም ነገር ግን ስለሌሎች መዳን ስንል መልካምን ልናደርግ ይገባናል፡፡ ልጅህ በመሰደቡ ምክንያት ራስህም እንደተሰደብክ አድርገህ አትቁጠር፡፡ በእርሱ ምክንያት አንተ ልትቆጣ ትችላለህ፡፡ ነገር ግን ላትሳደብም ትችላለህ፡፡ ልጅህ በመሰደቡ ምክንያት የአንተም ክብር እንደተነካ ልትቆጥር ትችላለህ፡፡ ነገር ግን ነገሩን ስናስተውለው ልጅህ የሰደበው እንጂ የሚጎዳው ልጅ ወይም አንተ አትጎዱም ክብርህም አይዋረድም፡፡

 

ስለዚህም እንደ ሰይፍ የሰላውን የቁጣ ሰይፍህን ከሰገባው ውስጥ መልሰው፡፡ ነገር ግን የቁጣ ሰይፋችንን ብንመዝና ያለጊዜዋ ብንጠቀምባት በእርሱ ተይዘን እኛም እንጠፋለን፡፡ ነገር ግን ቁጣችንን በውስጣችን ይዘን ትዕግሥትን የተላበስን ከሆነ ግን ቁጣው ይከስምልናል፡፡ ክርስቶስ በእርሱ ምክንያት ወደ ቁጣ እንዳንገባ አሳስቦናል፡፡ ጌታችን ለቅዱስ ጴጥሮስ ምን እንዳለው ስማ “ሰይፍ የሚያነሣ ሁሉ በሰይፍ ይጠፋልና ሰይፍህን ወደ ስፍራው መልስ፡፡”(ማቴ.26፡52) አለ፡፡ አንተ ስለልጅህ መነቀፍ ትቆጣለህን? ስለዚህም ልጅህን ምክንያታዊ እንዲሆን አስተምረው፡፡ ስለእርሱ የደረሰብህን ሕማም ንገረው እንዲህ አድርገህ መምህር ክርስቶስን ምሰለው፡፡

 

እርሱ በደቀመዛሙርቱ ላይ መከራ ያጸኑባቸውን ወገኖች “እኔ እበቀላቸዋለሁ አላለም” ነገር ግን “በእኔ እንዳደረጉት በእናንተም ላይ ይፈጽማሉና በትዕግሥት ተቀበሉ፡፡ እናንተ ከእኔ አትበልጡምና” ነበር ያላቸው፡፡ አንተም ለልጅህ አንተ ከጌታችን አትበልጥም ብለህ ልትነግረው ይገባሃል፡፡

 

ይህ መንፈሳዊ ፍልስፍና የአሮጊቶች ተረት ሊመስለን ይችላል ፡፡ በቃል ሰዎችን ከጥፋት ከመመለስ ይልቅ በድርጊት ሰዎችን መመለስ እጅግ ታላቅ ጥበብ አይደለምን? አሁን አንተ በመሃል ቆመሃል፡፡ መከራ ከደረሰባቸው ወገን እንጂ መከራን ከሚያደርሱት ወገን አትሁን፡፡ መከራ ከሚደርስባቸው ወገን በተግባር ካልሆንክ እነርሱ ከሚያገኙት የድል አክሊል ውጪ ትሆናለህ፡፡

 

እግዚአብሔር አምላክህ ቃየንን ስለ ወንድሙ አቤል እንዴት ብሎ በትሕትና እንደጠየቀውና ቃየንም እግዚአብሔር አምላክህን እንዴት ብሎ በንቀት ቃል እንደተናገረው ተመልከት እርሱ “ወንድምህ አቤል ወዴት ነው” ሲለው ቃየን ደግሞ በምላሹ “አላውቅም እኔ የወንድሜ ጠባቂ ነኝን?” ብሎ ነበር የመለሰው፡፡ (ዘፍ.4፡9)ከዚህ መልስ በላይ እጅግ ጸያፍ የሆነ መልስ ምን አለ? ከእናንተስ መካከል እንዲህ ዓይነት ጸያፍ የሆነ መልስን ልጁ ቢመልስለት የሚታገሥ አባት ማን ነው? ከወንድሙስ ቢሰማ እርሱን እንደ ሰደበው አይቆጥርበትምን ? ጌታችን ግን እንዲሀ አላደረገም ነገር ግን በትሕትና ቃል መልሶ ”ምን አደረግህ? የወንድምህ የደሙ ድምፅ ከምድር ወደ እኔ ይጮኻል፡፡” ብሎ ጠየቀው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ከቁጣ በላይ ነው ልትል ትችላለህ፡፡ ትክክል ብለሃል ነገር ግን እንደ ችሎታህ መጠን በጸጋ አምላክ ትሆን ዘንድ ስለአንተ ሲል የእግዚአብሔር ልጅ ሰው ሆኖአል፡፡

 

ነገር ግን ከእናንተ መካከል አንዱ “እኔ ሰው ነኝ አንዴት አምላክ ልሆን እችላለሁ ?ብሎ ሊጠይቅ ይችላል፡፡ ደህና! ምሳሌ የሚሆኑህን ሰዎች ልጥቀስልህ ስለ ጳውሎስ ወይም ስለ ጴጥሮስ የምናገር አድርገህ አታስብ፡፡ ከእነርሱ በእጅጉ ያነሰውን ሰው እንደምሳሌ አንሥቼ ላስረዳህ ካህኑ ኤሊ የሳሙኤልን እናት ሃናን “ስካርሽ እስከመቼ ነው? የወይን ጠጅሽን ከአንቺ አርቂው፡፡” (1ሳሙ.1፡14) ብሎአት ነበር፡፡ ከዚህ የከፋ የነቀፋ ቃል ምን አለ? ነገር ግን እርሱዋ ምን ብላ መለሰች “ጌታዬ ሆይ አይደለም፣ ጌታ ሆይ እኔ ልቡዋ ያዘነባት ሴት ነኝ” ብላ መለሰችለት በእርግጥ በእርሱዋ ላይ የተሰነዘረው የነቀፋ ቃል እርሱዋ ከምትጓጓለት ጋር የሚሰተካከል አልነበረም፡፡ እርሱዋ ለእውነተኛው መንፈሳዊ ፍልስፍና እናቱ ነበረች፡፡ እቺ ሴት ጣውንት ነበረቻት ነገር ግን እርሱዋን አንድም ቀን ተናግራት አታውቅም ነበር፡፡ ነገር ግን ወደ እግዚአብሔር ተጠጋች፡፡ በፀሎቱዋ ስሙዋን እያነሣች ስለስድቡዋ እግዚአብሔር ይቀጣላት ዘንድ አለመነችውም፡፡ እቺ ሴት አጅግ ድንቅ የሆነች ሴት ነበረች፡፡ እርሰዋን ተመልክተን ወገኖቻችንን በእግዚአብሔር ፊት የምንካሰስ እንፈር፡፡ እንደ ቅናት ብርቱ የሆነ ነገር እንደሌለም አንተ ታውቃለህ ነገር ግን እርሱዋ ቅናት ድል ነስቶአት በጣውንቷ ላይ በጠላትነት አልተነሣችም ነበር፡፡

 

ቀራጩ በፈሪሳዊው ሰው ሲንጓጠጥ እየሰማ እርሱም በምላሹ የስድብን ቃል አልተናገረውም፡፡ እንዲህ ማድረግ አቅቶት ግን አይደለም፡፡ ነገር ግን ልክ እንደ ጥበበኛ ሰው በምስጋና በመቀበል ስለራሱ ግን “አምላክ ሆይ እኔ ኃጢአተኛውን ማረኝ እያለ ደረቱን ይደቃ ነበር፡፡” ለመነ (ሉቃ.18፡13) ሜምፊቦስቴ ምንም ክስና ውንጀላ በባሪያው ቢቀርብበትም በባሪያው ላይ ምንም ክፉ ነገር ወይም ቃል ሊናገርው አልፈቀደም ነበር፡፡ በንጉሥ ዳዊት ፊት እንኳ ሊወቅሰው አልፈቀደም፡፡ (2ሳሙ.19፡26)

 

ድንቅ የሆነ ፍልስፍናን ስለተላበሰችው ስለዘማዊቱዋ ሴት ደግሞ ልንገርህን? ክርስቶስ እግሮቹን በእንባዋ አርሳ በጠጉሮቹዋ ስለአበሰችው ሴት ምን ብሎ አስተማረ “እውነት እላችኋለሁ ቀራጮችና ጋለሞቶች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በመግባት ይቀድሙአቸዋል” (ማቴ.21፡31)ብሎ አላስተማረምን? እርሱዋ የቆመችበትን ቦታ፣ ጽናቱዋን እንዲሁም ኃጢአቱዋን እንዴት አጥባ እንዳስወገደች አታስተውልምን? በፈሪሳዊው ስምዖን እንዴት ተብላ ስትነቀፍ እንደነበር አስተውል፤ ስምዖን “ይህስ ነቢይ ቢሆን ይህች የምትዳስሰው ሴት ማን አንደሆነች እንዴትስ እንደነበረች ባወቀ ነበር፡፡”(ሉቃ.7፡39) ሲላት “ አንተስ ማነህና አንተ ከኃጢአት ንጹሕ ነህን ? ብላ መልስ አልሰጠችውም፡፡ ነገር ግን ራሱዋን በጌታዋ ፊት ይበልጥ አዋርዳ አብዝታ አለቀሰች ትኩስ የሆነው እንባዋንም በጌታዋ እግር ላይ እንዲፈስ ፈቀደች፡፡

 

ሴቶች፣ ቀራጮች፣ አመንዝሮች ጥምቀት ሳትሠራ በፊት እንኳ መንፈሳውያን ፈላስፎች ሆነው ከሆኑ፤ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋዎች የተሰጣችሁ እናንተ እርስ በእርሳችሁ ከአራዊት በከፋ መልኩ እርስ በእርሳችሁ በመፋጀታችሁ፣ አንዱ አንዱን በማሳዘኑና በመምታቱ እንዴት የባሰ ፍርድ አይጠብቃችሁ ይሆን? ከቁጣ በላይ የሚከፋ፣ የሚያዋርድ፣ የሚያስፈራ፣ የሚያሳዝን፣ የሚጎዳም ምንም የለም፡፡

 

ይህን በውጭ ላሉ ሰዎች የምናሳየው ብቻ አይደለም፤ ነገር ግን ሚስታችን ተናገሪ ከሆነች ለእርሱዋም ይህን ትዕግሥት ልናሳያት ይገባናል፡፡ ሚስትህ ለአንተ ቁጣን ከሰውነትህ የምታስወግድባት ትምህርት ቤትህ ትሁን፡፡ ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል? ታጋሽ ሁን ሥጋን ብቻ ለሚጠቅም ነገር ታጋሾች ለመሆን ልምምዶችንና ጽኑ የሆኑ መከራዎችን የምንቀበል ስንሆን ነገር ግን ይህን ትዕግሥት በቤታችን የማንፈጸመው ከሆነ ማን ነው የድሉን አክሊል በራሳችን ላይ ሊደፋልን የሚችለው? ሚስትህ ትሰድብሃለችን? እርሱዋን መልሰህ በመሳደብ አንተው እርሱዋን አትምሰላት፡፡ ራስን ከክብር ማሳነሥ የነፍስ ደዌ ነው፡፡ ሚስት ስትሰድብህ አንተ እርሱዋን መልሰህ መሳደብ የተገባ እንዳልሆነ ልብ በል፡፡ በተቃራኒው አንተ እርሱዋን አየተሳደብኽ እርሱዋ የታገሰች ከሆነም ከዚህ የሚበልጥ ውርደት የለም፡፡ እናም እርሷ አንተን በመስደቡዋ የማይገባና የሚያዋርድ ነገርን በመናገርህ በራስህ ላይ የባስ ፍርድን ታመጣለህን፡፡ እርሷ ስትሳደብ ብትታገሣት ግን ያንተን ጽናት ታላቅነት ማረጋገጥ ትችላለህ፡፡ እንዲህ ስል ግን ሚስቶች ተሳዳቢዎች ይሁኑ ማለቴ ግን አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ይህን ማለትን ከእኔ ያርቅ፡፡ ነገር ግን በሰይጣን ግፊት ይህ ተፈጽሞ እንደሆነ እንዲህ አድርጉ ማለቴ ነው፡፡ የሚስትን ድክመት መሸከም የባል ድርሻ ነው፡፡

 

ሠራተኛህ ከአንተ ጋር ቢጋጭ በጥበብ ታገሠው፡፡ ለእርሱ ማድረግ የሚገባህን ወይም መናገር የሚገባህን አትናገር ማለቴ ግን አይደለም፡፡ ነገር ግን ከአንደበትህ በእርሱ ላይ የነቀፋ ቃል አይውጣ፡፡ ሴትን ልጅ የሚያዋርድ ንግግርን አትናገራት፡፡ አገልጋይ ሠራተኛህን በንቀት ቃል አትጥራው፡፡ እንዲህ ብታደርግ ግን እርሱን እያዋረድካት አይደለህም ራስህን እንጂ፡፡

 

ቁጡ ሰው ሆኖ ራስን ገዝቶ መኖር አይቻልም፡፡ ከተራራ ላይ ቁልቁል እየተምዘገዘገ እንደሚወርድ ውኃ ምንም የጠራ ቢሆን ተንደርድሮ አፈሩን ሲመታው ውኃው ደፍርሶ ከጭቃው ጋር ይቀየጥና የማይጠጣና ቆሻሻ ውኃ እንዲሆን የቁጡ ሰውም እጣ ፈንታ እንዲሁ ነው፡፡ ወዳጅህን በቁጣ ገንፍለህ ልትመታው ኮቱንም ልትቀድበት ትችላለህ፤ ነገር ግን የከፋውን ቅጣት የምትጠጣው አንተው ትሆናለህ፡፡ ያንተ ቡጢ በእርሱ ሥጋ ላይ፣ ቁጣህም በእርሱ ልብስ ላይ አርፎ ይሆናል፤ ነገር ግን በአንተ ነፍስ ላይ ቅጣቱ እንዲሁ ይሆንብሃል፡፡ ከሁለት የምትተረትራት የራስህን ነፍስ ነው፡፡ ስቃይህም በውስጥ ሰውነትህ ውስጥ ይሆናል፡፡

 

አንተ የሰረገላው መሪ ከወንበሩ ላይ ፈንግለህ ጥለኸዋል፡፡ ሰረገላህም ነፍስህን ከምድር ላይ ጥሎ እየጎተታት ነው፡፡ በቁጣ ሰረገላውን የሚመራ ሰው እጣ ፈንታው ነፍሱ ተዋርዳ በመሬት ላይ መጎተት ይሆናል፡፡ ልትገሥጽ ፡ ልትመክር ሌላም ልታደርግ ብትፈልግ ሁሉን ያለቁጣ ከስሜታዊነት ወጥተህ ፈጽም፡፡ለራሱ ሐኪም እያስፈለገው ሌላውን ሊፈውስ እንዴት ይቻለዋል፡፡ ራሱን አቁስሎ ሳለ የሌላውን ቁስል ሊፈውስ የሚጥር ይህ ሰው ራሱን የሚያድነው መቼ ነው? አንድ ሐኪም ሌላውን ለማዳን በሚሄድበት ጊዜ የራሱን እጅ ያቆስላልን? አስቀድሞ የራሱን ዐይን አሳውሮ የሌላውን ዐይን ለማዳን የሚሄድ ሐኪም አለን? እንዲህ ከማድርግ እግዚአብሔር ይጠብቀን፡፡ ቢሆንም ሌላውን ከመገሠጽህና ከመምከርህ በፊት የራስህ ዐይኖች አጥርተው የሚያዩና ንጹሐን ይሁኑ፡፡

 

እእምሮህን ከጭቃው ጋር አትደባልቀው እንዲህ አድርገህ እንደሆነ እንዴት ተብሎ ነው አንተን መፈወስ የሚቻለው?ቁጡና ከቁጣ ንጹሕ መሆን ልዩነታቸው በጭራሽ የሚነጻጸሩ አይደሉም፡፡ ያንተን ጌታ አስቀድመህ ከዙፋኑ ላይ ጥለህና ከጭቃው ጋር ለውሰህ ስታበቃ እንዴት ብለህ ነው ከእርሱ እርዳታን የምትሻው? ዳኞች የዳኝነት ካባቸውን ደርበው ከፍርድ ዙፋናቸው ላይ ከመቀመጥ ይልቅ በአፈር ላይ ይቀመጣሉን? አንተም ነፍስህን የዳኝነት ልብስን አልብሰሃት በተገቢው ቦታዋ ልታስቀምጣት ይገባሃል፡፡ እርሱም የማስተዋል ልብስ ነው፡፡ ነገር ግን “እንዲህ ባደርግ ሠራተኛዬ እኔን ሊፈራኝ አይችልም ትለኝ” ይሆናል፡፡ ይበልጥ ይፈራሃል፡፡ አንተ ሠራተኛህን ለምን እንዲህ እንዲህ አላደረግህ በቀጥታ ብትናገረው ባንተ ላይ ሊቆጣ ይችላል፡፡ ነገር ግን በትሕትና የተናገርኸው ከሆነ በስህተቱ ራሱን ይወቅሳል፡፡ እንዲህ በማደርግህ የመጀመሪያህ ጥቅምህ ምንድን ነው? እግዚአብሔር አንተን ያከብርሃል ከዘለዓለማዊውም በረከቶቹ ተሳታፊ ያደርግሃል፡፡ በጌታችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍቅር ለእግዚአብሔር አብና ለእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ክብር ምስጋና አገዛዝ ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡