Sinod.JPG

ቅዱስ ሲኖዶስ ሦስት መምሪያዎች በሊቃነ ጳጳሳት እንዲመሩ ውሳኔ ሰጠ

በሻምበል ጥላሁን

በሰኖዶሱ አባላት መካከል የተፈጠረው አለመግባባት በሰላም መፈታቱንም ገለጸ

ከጥቅምት 12 እስከ 19/ 2002 ዓ.ም መደበኛ ስብሰባውን ያደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የሰንበት ትምህርት ቤት ማደረጃ መምሪያን ጨምሮ ሌሎች ሁለት መምሪያዎችን በበላይ የሚመሩ ሦስት ሊቃነ ጳጳሳትን በመምረጥና 10 ነጥቦችን የያዘ የአቋም መግለጫ በማውጣት ተጠ ናቀቀ፡፡

Sinod.JPG

 

 

 

 

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የቅዱስ ፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ የነበሩትን ብፁዕ አቡነ ሳሙኤልን እስከ ግንቦቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ድረስ ልማት ኮሚሽንን እንዲያስተዳድሩም መርጧል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔውን ያሳለፈውና ጋዜጣዊ መግለጫውን የሰጠው ከጥቅምት 12 እስከ 19/ 2002 ዓ.ም ከተወያየ በኋላ ነው፡፡

በውይይቱ መሠረትም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ሥር የሚገኙት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ፣ የስብከተ ወንጌል ሐዋርያዊ ተልእኮና የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ በብፁዓን አባቶች የበላይ አመራር ሰጪነት እንዲተዳደሩ ጉባኤው በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡

ሦስቱን መምሪያዎች በበላይ ተቆጣጣሪነትና አመራር ሰጪነት እንዲመሩ በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የተመ ረጡት ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩና አሁን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መመሪያን በበላይነት በሙሉ ጊዜ የሚያሰተዳድሩ፤ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የምዕራብ ሐረርጌ ሊቀ ጳጳስ የነበሩና አሁን የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያን በሙሉ ጊዜ በበላይነት የሚማሩ፡፡ የምሥራቅ ወለጋ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ያሬድ አሁን በሙሉ ጊዜ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያን በበላይነት እንዲመሩ በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ተመድበዋል፡፡

መምሪያዎቹ በሊቃነ ጳጳሳቱ አመራር ሰጪነት በሙሉ ጊዜ  መመራታቸው የአገልግሎት ክፍሎቹን ለማ ጠናከር ቤተክርስቲያን ቁርጠኛ አቋም መውሰዷን እንደሚያመለክት ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ አስተያየታቸውን የሰጡ ምእመናን ገልጸዋል፡፡

ለውጡ በተለይ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያን በሓላፊነት ይመሩ በነበሩት ቆሞስ አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሳሙኤል እና በማኅበረ ቅዱሳን መካከል ተፈጥሮ የነበረውን አለመግባባት እንደሚፈታውም አስተያየት ሰጪዎቹ ተናግረዋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ በስብሰባው ማጠቃለያ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳመለከተው፤ ለ2002 ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ የሥራ ሪፖርትን ማድመጡንና ለ2002 ዓ.ም የቀረበውን የሥራ በጀት በሙሉ ድምጽ ማጽደቁን ገልጿል፡፡

በተለያየ ምክንያት የሥራ ዝውውር እንዲደረግላቸው ለጠየቁ ስድስት ሊቃነ ጳጳሳት ዝውውሩን ጉባኤው መቀበሉን ያመለከተው መግለጫው፤ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን በተመለከተም ውሳኔ ማሳለፉን ገልጿል፡፡

በውሳኔው መሠረት ሀገረ ስብከቱ ካለው ስፋት አንፃር መልካምና ቀልጣፋ አስተዳደርን ለመገንባት በዞን እንዲከፈል ማድረግ በማስፈለጉ አፈጻጸሙን አባቶች ካልተመደቡላቸው አህጉረ ስብከት ጋር በአጥኝ ኮሜቴ ተመቻችቶ ለግንቦቱ የርክበ ካህናት ጉባኤ ይቀርብ ዘንድ ምልዓተ ጉባኤው ተስማምቶ መወሰኑን መግለጫው ጠቁሟል፡፡

ጉባኤው ከቤተክርስቲያኒቱ ኮሌጆች ተመርቀው ለሚወጡ ደቀ መዛሙርት ሊመደብ ስለሚገባው መነሻ በጀት፣ ጉዳይ ተወያየቶ የበጀቱን ሁኔታ ለሚመለከተው ኮሚቴ ተጠንቶ ለግንቦቱ የርክበ ካህናት ጉባኤ እንዲቀርብ መወሰኑንም ብፁዕ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቀነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት ፕሬዝዳንትና የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዝዳንት የተነበበው መግለጫ አመልክቷል፡፡

የቤተ ክርስቲያኒቱን የሥራ እንቅስቃሴ እንዲያቀላጥፍ በቅዱስ ሲኖዶስ ተመርጦ የነበረው የሊቃነ ጳጳሳት የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ኮሚቴው የሚመራበት የመተዳደሪያ ደንብ በማስፈለጉ ጉባኤው መተዳደሪያ ደንቡ ቃለ ዓዋዲውንና ሕገ ቤተክርስቲያንን መሠረት ያደረገ ሁለት ሊቃነ ጳጳሳት በአስረጂነት ያሉበት ውስጠ ደንብ በሕግ ባለሙያዎች ተዘጋጅቶ ለግንቦቱ ጉባኤ እንዲቀርብ መወሰኑ ንም መግለጫው አመልክቷል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትና የቅዱስ ፓትርያርኩ ረዳት ሊቀጳጳስ የነበሩት የብፁዕ አቡነ ሳሙኤልንም ጉዳይ ውሳኔ ማሳለፉን በቅዱስ ፓትርያርኩ የተነበበው መግለጫ ጠቁመዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል ሊመደቡበት የሚገባ ቦታ ሦስት ሊቃነ ጳጳሳት በሚገኙበት ኮሚቴ እንዲጠና መደረጉን ያመለከተው መግለጫው፤ አጥኚው ኮሚቴው ጠቁሞ ካቀረባቸው አራት ቦታዎች መካከል ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል  ከጥቅምት 20 ቀን 2002 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ግንቦቱ የርክበ ካህናት ጉባኤ ድረስ የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ጊዜያዋ ሓላፊ ሆነው እንዲሠሩ መወሰኑን መግለጫው አስረድቷል፡፡

ሲኖዶሱ ባለፈው ሐምሌ ወር 2001ዓ.ም በድንገት ተፈጥሮ ከነበረው የሥራ አለመግባባት የተነሣ ያልተ ጠበቀ አሳዛኝ ድርጊት ተፈጽሞ መገኘቱ ሁሉንም ያሳዘነ ቢሆንም የሰላም መልእክተኛው ቅዱስ ሲኖዶስ በአባላቱ መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት በዕርቅ እንዲፈታ በማድረግ ጉባኤው በሰላም መካሄዱንም አመልክቷል፡፡

ችግሩ በአባቶች ቀኖናዊ  ዕይታ መፈታቱንም መግለጫው አመልክቶ፤ ለሀገር አንድነትና ደኀንነት ስትጸልይ የኖረችውና የምትኖረው ቅድስት ቤተክርስቲያናችን የራሷን ችግር በራሷ የመፈታት አቅሟን አጎልብታ ባልተጠበቀ ሁኔታ ተከሥቶ የነበረ ውንና ቅዱስ ሲኖዶሱን አሳዘኖ ያለፈውን ችግር በመፍታት እርቅ ሰላ ሙን ለማስፈን መብቃቷንም መግለጫው አብራርቷል፡፡

በመሆኑም ሐምሌ 2001 ዓ.ም ተፈጥሮ የነበረውን ችግር ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደ ፈተና የምትቆጥረው ቢሆንም አባቶች የሰጡትና የሚሰጡት ቃለ ትምህርትና ቃለ ምዕዳን ትኩረትን አግኘቶ ተፈጥሮ የነበረው ጊዜያዊ አለመግባባት ተወግዶ መፍ ትሔ በመገኘቱ ደስታዋን ሁሉም እንዲረዳው በአጽንኦት ማብሰሯንም በቅዱስ ፓትርያርኩ የተነበበው መግለጫ አስረድቷል፡፡
               

ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 17ኛ ዓመት ቁጥር 4/ቅጽ 17 ቁጥር 189 ከኅዳር 1-15 2002 ዓ.ም