ማእከላት ለኦዲትና ኢንስፔክሽን ሥራዎች ትኩረት እንዲሰጡ ተጠየቀ

ሚያዚያ 22 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

የማኅበረ ቅዱሳን ኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ክፍል ማእከላት ለኦዲትና ኢንስፔክሽን ሥራዎች ትኩረት እንዲሰጡ የክፍሉ ሓላፊ አቶ የሸዋስ ማሞ አስታወቁ፡፡

በአዲስ አበባ ለሁለት ቀናት ለሀገር ውስጥ ማእከላት ስለ ኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎትና አሠራር ዙሪያ ሚያዝያ 12 እና 13 ቀን 2005 ዓ.ም. በተሰጠበት ወቅት ነበር ማእከላት አገልግሎቱን አጠናክረው መቀጠል የሚገባቸው መሆኑን የተገለጸው፡፡

ማእከላት የሒሳብ ክፍል አሠራራቸውንና የኦዲትና ኢንስፔክሽን ክፍሎቻቸውን ይበልጥ  አጠናክረውና በሰው ኃይል አደራጅተው አገልግሎታቸውን መቀጠል እንዳለባቸው በሥልጠናው ላይ ተገልጿል፡፡

ለማእከላት በርካታ ሥልጠናዎችና የግንዛቤ ማስጨበጫ ዝግጅት እየተደረገ ሲሆን የማእከላቱ የግንዛቤ መጠን መጠነኛ ለውጦችን ማምጣት መቻሉን አቶ የሸዋስ ገልጸው ማእከላቱ ለኦዲትና ኢንስፔክሽን ሥራዎች ትኩረት እንዲሰጡና ክፍሉንም በባለሙያ እንዲያጠናክሩ ጥሪያቸውን ያቀረቡት፡፡ የአገልግሎት ክፍሉ እና የሒሳብ ክፍሉ መጠናከር የጎላ አስተዋጽኦ እንደሚኖረውና ለማእከላት ወጥ የሆነ የሒሳብ አያያዝ ሥርዓትም አዎንታዊ ተጽዕኖ ሊኖረው እንደሚችል አስገንዝበዋል፡፡

የአገልግሎት ክፍሉ የማኅበሩን ስልታዊ ዕቅድ ከማስፈጸም አኳያ የተለያዩ ድጋፎችን ለማእከላት የሚያደርግ መሆኑና በዕቅዱም ዘመን የራሱን የአገልግሎት ስልት ዘርግቶ እንደሚሠራ ነው ከሓላፊው ገለጻ የተረዳነው፡፡ ሚያዝያ 12 እና 13 ቀን 2005 ዓ.ም. በተሰጠው ሥልጠና በሀገር ውስጥ ከሚገኙ ማእከላት ተወካዮች በሥልጠናው መሳተፋቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡