ማኅበረ ቅዱሳን የጠራው ሰልፍ እንደሌለ አስታወቀ

ጥቅምት 7 ቀን 2007 ዓ.ም.

በተለያዩና ባልታወቁ አካላት ለማኅበሩ አጋርነት ለማሳየት በመጪው እሑድ በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሰልፍ ለማድረግ በማኅበራዊ ሚዲያው የሚሽከረከረውን አስመልክቶ ከአባላቱ ለቀረበለት ጥያቄ የሚያውቀው ነገር እንደሌለና ማኅበሩም ምንም ዓይነት ጥሪም እንዳላካሔደ የማኅበረ ቅዱሳን የሕዝብ ግንኙነት ክፍል አስታወቀ፡፡

ማኅበሩ በአገልግሎቱ ሂደት ላይ ፈተናዎችና የስም ማጥፋት ዘመቻዎች እያጋጠሙት እንደሆነ ባይሸሽግም ችግሮቹን ለመፍታት ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት በአድራሻና ለብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በግልባጭ አመልክቶ ውሳኔውን መጪው ረቡዕ ጥቅምት 12 ቀን 2007 ዓ.ም. ከሚጀምረው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እየተጠባበቀ ከመሆኑ በቀር ምንም ዓይነት ጉባኤም ሆነ ሰልፍ አለመጥራቱን አስታውቋል፡፡

ማኅበሩ ገጽታውን ለማበላሸት ሆን ብለው በሐሰት ስሙን የሚያጠፉትን ግለሰቦች በሕግ እንደሚጠይቅ ማሳወቁም የሚታወስ ነው፡፡