ስግደትና ሰላምታ በሰሙነ ሕማማት

በሊቀ ማእምራን ብርሃነ መስቀል አጠና 

የሊቃውንት ጉባኤ አባል

መጋቢት ፳፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ሰሙነ ሕማማት ሰሙነ ስቅለትም ይባላል፡፡ ይኸውም ከሆሣዕና ማግስት (ከሰኞ) ጀምሮ እስከ ዓርብ ስቅለት ያለው ክፍለ ጊዜ ሲኾን ይህም ከጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐበይት በዓላት መካከል አንዱ ነው፡፡ ‹‹እርሱ ግን በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ፤ ሕማማችንንም ተሸከመ፡፡ ስለ እኛም ታመመ፡፡ እኛም እንደ ታመመ፣ እንደ ተገረፈ ቈጠርነው፡፡ እርሱ ግን ስለ ኃጢአታችን ቈሰለ፤ ስለ በደላችንም ታመመ፡፡ የሰላማችንም ተግሣፅ በእርሱ ላይ ነበረ፡፡ በእርሱም ቊስል እኛ ተፈወስን፤›› በማለት ነቢዩ ኢሳይያስ እንደ ገለጸው (ኢሳ. ፶፫፥፬-፭)፣ ሰሙነ ሕማማት የክብርና የሥልጣን ዅሉ ባለቤት፣ ዅሉን ቻይ፣ ኃያል የኾነው አምላክ እኛን ከመውደዱ የተነሣ የእኛን ዕዳ ለመክፈል በመስቀል እስከ መሞት ድረስ እጅግ ከባድና አሰቃቂ የኾነ መከራ በፈቃዱ የተቀበለበት ሰሙን ከመኾኑም ባሻገር እኛ ፍጹም ድኅነትን ያገኘንበት ጊዜ ነው፡፡

ስግደት የአምልኮ ስግደት እና የአክብሮት ስግደት ተብሎ በሁለት ይከፈላል፡፡ እኛ ኢያሱ ለመልአኩ እንደ ሰገደ ዮሐንስ፤ ወንጌላዊም እንደዚሁ ለመልአኩ መላልሶ እንደ ሰገደ እግዚአብሔር አምላክ ላከበራቸው ቅዱሳን መስገድ ያከበራቸው እግዚአብሔርን ማክበር መኾኑን አውቀን የአክብሮት ስግደት ስንሰግድላቸው ያልገባቸው ሰዎች ከኢያሱና ከዮሐንስ በላይ ለእግዚአብሔር አምልኮት ተቈርቋሪ በመምሰል ይዘብቱብናል፤ ባይገባቸው ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎችም እንደዚሁ ‹‹በሰሙነ ሕማማት ሌሎች በዓላት ተደርበው ሲውሉ ስግደት አይገባም፤›› እያሉ ሕዝቡን በየጊዜው ያደናግራሉ፡፡ በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ‹‹በጌታችን በዓል፣ በእመቤታችን በዓል ሥጋ ወደሙ ከተቀበሉ በኋላ ሰጊድ አይገባም፤›› ይልና በጌታ በዓል አድንኖ፤ በእመቤታችን በዓል አስተብርኮ በቅዱሳን በዓል ሰጊድ ይላል፡፡ ነገር ግን ይህ ሐተታ ለየትኛው ስግደት እንደ ተነገረ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

አንደኛ የሕማማት ዝርዝር ኹኔታ የተጻፈው በአንቀጸ ጾም ነው፤ ይህ ሐተታ ግን የሚገኘው በአንቀጸ ጸሎት ነው፡፡ ከሕማማት ጋር ፈጽሞ ግንኙነት የለውም፡፡ ሁለተኛ ፍትሕ መንፈሳዊ በአንቀጽ ፲፭ ሐተታውን ሲጀምር ‹‹ወዘይጼሊ ቅድመ ይስግድ ወበዘይበጽሕ ዝክረ ሰጊድ ለእግዚአብሔር ልዑል በጊዜ ጸሎት›› በማለት የሚጸልይ ሰው አስቀድሞ (በመጀመሪያ) አንድ ጊዜ ወይም ሦስት ጊዜ ሰጊድን ከሚያነሣ አንቀጽ ላይ ሲደርስ፣ ለአብነትም ‹‹ንሰግድ ለከ ዘለከ ይሰግድ ኵሉ ብርክ፤ ንስግድ ሎቱ ወንሰብሖ ምስለ አብ ወወልድ፤ ንሰግድ ለከ ክርስቶስ፤ እሰግድ ለአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐተ ስግደተ፤ እሰግድ ለእግዝእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ፤ እሰግድ ለመስቀለ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ›› የመሳሰለ ንባብ ሲያጋጥም መስገድ እንደሚገባ ያዛል፡፡

ስለዚህ በግል ጸሎት ጊዜና በንስሓ ወቅት ስለሚሰገደው ስግደት ወይም አንድ ባሕታዊ ፆር እንዳይነሣብኝ ብሎ፤ ምእመናን ክብር ለማግኘት ብለው ስለሚሰግዱት ስግደት የተወሰነውን ሥርዓት ከሕማማት በዓል አከባበር ጋር ያለ ስፍራው ማምጣት ስሕተት ነው፡፡ ምክንያቱም ሰሙነ ሕማማት ዓርብ ስቅለትን ጨምሮ ከጌታችን ዐበይት በዓላት አንዱ ነው፡፡ በዓሉ ደግሞ የሚከበረው በማኅሌት፣ በቅዳሴ ሳይኾን ባለቤቱ በመሠረተው በኀዘን፣ በጸሎት፣ በልቅሶ፣ በስግደት ነውና፡፡ ስለኾነም ማንኛውም በዓል የዓመትም ይኹን የወር በዓል ከሕማማት ጋር ቢገጥም እንኳ አልፎ ከፋሲካ በኋላ ይከበራል እንጂ በሕማማት ውስጥ አይከበርም፡፡ ስግደትም አይከለከልም፡፡ ታዲያ በዓሉ ቦታውን ለቆ ሒዶ እያለ የሕማማትን ስግደት እንዴት ያስቀራል?

መጽሐፉ በጌታችን በዓል ‹አድንኖ›፤ በእመቤታችን በዓል ‹አስተብርኮ› ብሎ በቅዱሳን በዓል ‹ስግደት› ነው የሚለው፡፡ እንኳን በሰሙነ ሕማማት የቅዱሳን በዓላት በሚውሉባቸው ሌሎች ዕለታትም ስግድት መስገድ አይከለከልም፡፡ እነዚያ በግምት የሚነጉዱ ሰዎች ግን ‹‹የቅዱሳን በዓል በሕማማት ሲውል አይሰገድም፤›› እያሉ ችግር ሲፈጥሩና ‹‹እገሌ በበዓል ጊዜ ይሰግዳል ይላል፡፡ መናፍቅ ነው፤›› እያሉ የእውነተኞችን መምህራን ስም ሲያጠፉ ይስተዋላሉ፡፡ ስለዚህ የሚመለከተው አካል ተዉ ሲላቸው ካልተመለሱ ጥብቅ ትምህርት ሊሰጣቸው ይገባል፡፡

በመሠረቱ ሰላምታ በቁሙ ፍጹም ጤና፣ ዕረፍት፣ ፍቅር፣ አንድነት፣ ደኅንነት፣ ተድላ፣ ደስታ፣ ሰላምታ፣ ቡራኬ፣ የምርቃት ቃል፣ ሰው ሲገናኝ ወይም ሲለያይ የሚናገረው የሚፈጽመው ተግባር ነው (መጽሐፈ ሰዋስው ዘኪዳነ ወልድ)፡፡ ስለኾነም ሰላም በየትኛውም ቦታ፣ በማንኛውም ጊዜ ለዅሉ የሚበጅ፤ ከዅሉም በላይ እጅግ ጠቃሚ ተግባር ነው፡፡ ጎጂና በጣም ክፉ ወይም አደገኛ ኾኖ የተገኘው የጥፋት ልጅ የተባለው የይሁዳ ሰላምታ ነው፡፡ ‹‹ይህንንም ሲነግራቸው ሕዝቡ ደረሱ፤ ከዐሥራ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት አንዱ ይሁዳ ይመራቸው ነበር፡፡ ወደ ጌታችን ኢየሱስም ቀርቦ ሳመው፤ የሰጣቸው ምልክት ይህ ነበር፡፡የምስመው እርሱ ነውና አጽንታችሁ ያዙት፤አላቸው፡፡ ጌታችን ኢየሱስምይሁዳ! የሰውን ልጅ በመሳም ታስይዘዋለህን? ልታስገድለው አይደለምን?› አለው›› (ሉቃ. ፳፪፥፵፯-፵፰፤ ማቴ. ፳፮፥፵፯-፶፮፤ ማር. ፲፬፥፫-፶፤ ዮሐ. ፲፰፥፫-፲፪)፡፡

ጌታችን በዚህ ኹኔታ ከተያዘ በኋላ ነው እስከ ሞት ድረስ ያን ዅሉ መከራ የተቀበለው፡፡ ስለኾነም ከሰሙነ ሕማማት እስከ በዓለ ትንሣኤ (ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን) እስከሚባል ድረስ መስቀል ወይም መጽሐፍ መሳለም እንዳይገባ ‹‹ወኢይትአምኁ በበይናቲሆሙ ዘእንበለ በዕለተ ፋሲካ ወኢየአምኁ መስቀለ ወወንጌለ፤ ያለ ፋሲካ ቀን እርስ በእርሳቸው አይሳሳሙ፤ መስቀልንና ወንጌልንም አይሳለሙ፤›› ተብሎ ተደንግጓል (ፍት.መን. ገጽ ፪፻፳፯)፡፡ ጸዋትወ ዜማም ‹‹ይሁዳ ኢየሱስ ክርስቶስን ስለ ሳመው ወይም በመሳም ስላስያዘው እርስ በርሳቸው አይሳሳሙ፤ ወንጌልንና መስቀልንም አይሳለሙ፡፡ የሞቱትንም ሰዎች አይፍቱ፤›› ይላል (ገጽ. ፺፬-፺፯)፡፡

በግብረ ሕማማት ገጽ ፵፯ እና ፭፻፺፭ ‹‹ወኢይትአምኁ በበይናቲሆሙ ወኢይአምኁ ወንጌለ ወመስቀለ በእንተ ዘአምኆ ይሁዳ ወኢይዝክሩ ሰሞሙ ለእለ ኖሙ ቅዱሳን አበው ወኢይበሉ ሐዳፌ ነፍስ›› ይላል፡፡ ይህ ትእዛዝ በእነዚህ ዅሉ መጻሕፍት እየተደጋገመ መጠቀሱ ለአጽንዖተ ነገር ነው፡፡ በሰሙነ ሕማማት እርስበርስ መሳሳም ከይሁዳ ሰላምታ ጋር የተያያዘ ስለ ኾነና የይሁዳ ተባባሪ ስለሚያሰኝ እስከ ትንሣኤ ድረስ መሳሳምም ኾነ ወንጌልንና መስቀልን መሳለም ተከልክሏል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምሥጢረ ሆሣዕና

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፳፪ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የዐቢይ ጾም ስምንተኛው ሳምንት ‹‹ሆሣዕና›› ተብሎ ይጠራል፡፡ ይኸውም ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ላይ ተቀምጦ በክብር፣ በምስጋና፣ በዝማሬ ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱን የምንዘክርበት በዓል ነው፡፡ በዚህ ዕለት ከዋይዜማው ጀምሮ በመንፈቀ ሌሊት፣ በነግህ እና በሠርክ ጌታችን ወደ ኢሩሳሌም የመግባቱን ምሥጢር፣ ከሕዝቡ የቀረበለትን ምስጋና እንደዚሁም ኢየሩሳሌም በግርማው መደንገጧን የሚያስረዳ ቃለ እግዚአብሔር በቤተ ክርስቲያናችን በሰፊው ይነገራል፡፡

ይህ ምሥጢርም በቅዱሳት መጻሕፍት በልዩ ልዩ መንገድ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ በዚህ ዝግጅት፣ በማቴዎስ ፳፩፥፩-፲፩፤ በማርቆስ ፲፩፥፩-፲፤ በሉቃስ ፲፱፥፳፰-፵ እና በዮሐንስ ፲፪፥፲፪-፲፭ በተጻፈው ኃይለ ቃል መሠረት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያዘጋጁትን አንድምታ ትርጓሜ መነሻ በማድረግ ምሥጢረ ሆሣዕናን (ጌታችን በአህያ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም የመግባቱን ምሥጢር) የሚያስገነዝብ ትምህርት ይዘን ቀርበናል፡፡ ትምህርቱን ትከታተሉ ዘንድ በአክብሮት ጋበዝናችሁ!

ክብር ይግባውና ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው በልዩ ልዩ አገሮች እየተዘዋወረ ቃሉን በማስተማር ሕገ ወንጌልን መሥርቷል፤ ብዙዎችንም ለመንግሥቱ አቅርቧል፡፡ ቃሉን ለመስበክ ከተዘዋወረባቸው ቦታዎች አንዷ ደግሞ ኢየሩሳሌም ናት፡፡ የመሲሑን መምጣት ማለትም የእግዚአብሔርን ሰው መኾን የሰሙና ያመኑ እስራኤላውያን ክርስቶስን በዓይነ ሥጋ ለማየት ይጓጉ፣ መምጣቱንም ይጠባበቁ ነበር፡፡

አመጣጡ ግን እነርሱ በጠበቁት ልዩና ተአምራዊ መንገድ ሳይኾን በትሕትና ተፈጸመ፡፡ ሲወለድ በከብት በረት፤ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባም በአህያ ተቀምጦ ለእስራኤል ተገለጠ፡፡ ሰማይ ዙፋኑ፣ ምድር የእግሩ መረገጫ የኾነ ጌታ መላእክቱን አስከትሎ፣ በመባርቅትና በነጐድጓድ ታጅቦ ይመጣል ተብሎ ሲጠበቅ የትሑታን ጌታ መኾኑን ለማጠየቅ በአህያ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ፡፡ በዚህ ጊዜ ኢየሩሳሌም ተረበሸች፤ ደነገጠች፡፡ አምላክን ባልጠበቀችው አኳኋን ተገልጦ አይታዋለችና፡፡

ወደ ጥንተ ነገሩ እንመለስና ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ሊገባ በተቃረበ ጊዜ ከደቀ መዛሙርቱ መካከል ሁለቱን በፊታቸው ወደሚገኝ አገር ሔደው ከውርንጫዋ ጋር ታሥራ የሚያገኟትን አህያ ፈተው እንዲያመጡለት አዘዛቸው፡፡ የሰው ልጅ ከማዕሠረ ኀጢአት (ከኀጢአት ማሠሪያ) የሚፈታበት ጊዜ ደርሷልና፡፡ ይኸውም አምላካችን የመጣው የዓለምን ኀጢአት ለማስወገድ መኾኑን የሚያጠይቅ ነው፡፡ ‹‹ነዋ በግዑ ለእግዚአብሔር ዘየአትት ኃጢአተ ዓለም፤ የዓለምን ኀጢአት የሚያስወግድ እነሆ የእግዚአብሔር በግ!›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዮሐ. ፩፥፴፮)፡፡

አህያዋንና ውርንጫዋን ‹‹ለምንድን ነው የምትፈቷቸው?›› ብሎ የሚጠይቅ ካለም ‹‹‹ጌታቸው ይሻቸዋልበሉ፤ ያንጊዜ ያሰናብቷችኋል (ይተዋችኋል)›› አላቸው፡፡ በተፈጥሮ ጌታቸው ነውና ማለትም ፈጥሯቸዋልና ‹‹ጌታቸው›› አለ፡፡ ደግሞም እርሱ እናቶችን ብቻ ሳይኾን ልጆችን ጭምር ወደ ቤቱ ማቅረብ ይፈልጋልና፡፡ ይህም ጌታችን በኀጢአት ማሠሪያ የተያዙ ኀጢአተኞችን ለመፍታት ከፈቀደ ‹‹ለምን ይህን ታደርጋለህ?›› ብሎ የሚቃወመው አለመኖሩን ያስገነዝባል፡፡

አህያዪቱንና ውርንጫዋን በተመለከተ ማቴዎስ ሁለቱንም፤ ማርቆስ ደግሞ ውርንጫዋን ብቻ ነው የጠቀሱት፡፡ የማቴዎስን አጻጻፍ መከተል ለታሪኩ እንደሚያመች፣ ይህም እንደማይጣላና የምሥጢር ተፋልሶ እንደማያመጣ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን ይተረጕማሉ፡፡ ለዚህ ማስረጃ ሲያቀርቡም ማርቆስ አንድ ማለቱ (ውርንጫዋን ብቻ መጠቀሱ) ለመናገር በቂ ነው ብሎ በማሰቡ እንደ ኾነ፤ አንድም ማቴዎስ የሕዝብም (ያመኑ) የአሕዛብም (ያላመኑ) መምህር በመኾኑ ሁለቱንም (አህያዬቱንና ውርንጫዋን) እንደ ጠቀሰ፤ ማርቆስ ግን የአሕዛብ እንጂ የሕዝብ መምህር ስላልኾነ የአሕዛብን ምሳሌ ብቻ (ውርንጫን) እንደ አወሳ ሊቃውንቱ ያስረዳሉ (ማር. ፲፩፥፫)፡፡

ይህ ዂሉ የተደረገውም ማለት ጌታችን በአህያዪቱና ውርንጫዪቱ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ለመግባት የፈቀደውም ‹‹አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ፥ እጅግ ደስ ይበልሽ፤ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ፥ እልል በዪ፤ እነሆ፥ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ኾኖ በአህያም፥ በአህያዪቱም ግልገል በውርንጫዪቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል፤›› ተብሎ የተነገረው ቃለ ትንቢት የሚፈጸምበት ጊዜ ስለ ደረሰ ነው (ዘካ. ፱፥፱)፡፡ ትርጓሜ ወንጌል በሐተታው ወለት (ልጅ) የተባለች እስራኤል፤ ጽዮን ደግሞ ኢየሩሳሌም መኾኗን ያብራራል፡፡ አንድም ወለትን (ልጅን) እንዳለ መስሎ ጽዮን የተባለች ሕግ መኾኗን ይጠቅሳል፡፡ የምሳሌዉን ትርጕም ሲያስረዳም እናት ልጆቿን ሠርታ፣ ቀጥታ እንድታሳድግ ሕግም ሕዝቡን ሠርታ፣ ቀጥታ እንደምታኖር ይናገራል (ማቴ. ፳፩፥፬-፭)፡፡

ወደ ታሪኩ ስንመጣ ደቀ መዛሙርቱም እንደ አዘዛቸው አህያዬቱንና ውርንጫዋን ፈተው ለጌታችን አመጡለት፡፡ ልብሳቸውንም በጀርባዋ ላይ ጐዘጐዙለት፡፡ ኮርቻ ይቈረቍራል፤ ልብስ አይቈረቍርም፡፡ ጌታችንም የማትቈረቍር ሕግ (ሕገ ወንጌልን) መሥራቱን ለማጠየቅ ልብስ ጐዘጐዙለት፡፡ አንድም ልብስ ነውርን ይሠውራል፤ እርሱም ከባቴ አበሳ (በደልን በሥውር ይቅር የሚል) አምላክ ነውና ልብስ ጐዘጐዙለት፡፡ ጌታችንም በጥበቡ በሁለቱም አንድ ጊዜ ተቀምጦባቸዋል፡፡

በትርጓሜ ወንጌል እንደ ተጠቀሰው ከኢየሩሳሌም እስከ ቤተ መቅደስ ያለው ርቀት ዐሥራ ስድስት ምዕራፍ ይኾናል፡፡ ጌታችን ዐሥራ አራቱን ምዕራፍ በእግሩ ተጕዞ፤ ሁለቱን በአህያዋ ጀርባ ላይ ተቀምጦ ሔዷል፡፡ በውርንጫዋ ላይ ተቀምጦ ደግሞ ቤተ መቅደስን ሦስት ጊዜ ዞሯል፡፡ ይህም የሦስትነቱ ምሳሌ ነው፡፡ ዐሥራ አራቱን በእግሩ መሔዱም ዐሥሩ፣ የዐሠርቱ ትእዛዛት፤ አራቱ የአራቱ ኪዳናት ማለት የኪዳነ ኖኅ (የኖኅ ኪዳን)፣ የክህነተ መልከ ጼዴቅ (የመልከ ጼዴቅ ክህነት)፣ የግዝረተ አብርሃም (የአብርሃም መገረዝ) እና የጥምቀተ ዮሐንስ (የዮሐንስ ጥምቀት) ምሳሌዎች ናቸው፡፡ አንድም አምስት ሺሕ አምስት መቶዉን ዓመት በአራት በአራት መቶ ቢከፍሉት ዐሥራ አራት ሊሞላ አንድ መቶ ይጐደለዋል፡፡ ዐሥራ አራቱ ምዕራፍ፣ ይህ ዘመን (አምስት ሺሕ አምስት መቶዉ) ሲፈጸም አምላክ ሰው እንደ ኾነ ያጠይቃል፡፡

ጌታችን በአህያ መቀመጡ ስለ ምን ነው ቢሉ ትንቢቱ፣ ምሳሌው ሊፈጸም ነው፡፡ እርሱ ባወቀ (በአምላካዊ ጥበቡ) ትንቢቱን አስቀድሞ አናግሯል፤ ምሳሌውንም አስመስሏል፡፡

  • ትንቢቱ፡- ‹‹ሠረገላዉንም ከኤፍሬም፥ ፈረሱንም ከኢየሩሳሌም ያጠፋል፤›› ተብሎ አስቀድሞ ተነግሯል (ዘካ. ፱፥፲)፡፡ የትንቢቱ ፍጻሜ ሲደርስ ጌታችን በፈረስና በሠረገላ ሳይኾን በአህያ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ፡፡
  • ምሳሌው፡- ቀድሞ ነቢያቱ ዘመነ ጸብዕ (የጦርነት ዘመን) የሚመጣ እንደ ኾነ በፈረስ ተቀምጠው፣ ዘገር ነጥቀው (የጦር ትጥቅ ይዘው)፤ ዘመነ ሰላም የሚመጣ እንደ ኾነ ደግሞ በአህያ ተቀምጠው፣ መነሳንስ ይዘው ይታያሉ፡፡ ጌታችን የሰላም አምላክ ነውና የሰላም ዘመን መድረሱን፣ ሰላምን ይዞ መምጣቱን ሲያስረዳ በአህያ ላይ ተቀምጦ ታየ፡፡

ምሥጢሩስ ምንድን ነው ቢሉ በአህያ ላይ የተቀመጠ ሸሽቶ ማምለጥ፣ አሳዶ መያዝ አይችልም፡፡ ጌታችንም ለሚፈልጉት (ለሚያምኑበት) እንደሚገኝ፤ ለማይፈልጉት (ለሚክዱት) እንደማይገኝ ሲያመላክት በአህያ ላይ ተቀምጦ ታየ፡፡ አንድም በንጹሓን መሃይምናን ላይ አድሮ እንደሚኖር ሲያጠይቅ ነው፡፡

አህያ፣ የእስራኤል ምሳሌ ነው፤ አህያ፣ የሠረገላ ቀንበር መሸከም እንደምትችል እስራኤልም ሕግ መጠበቅ የለመዱ ናቸውና፡፡ ውርንጫ፣ የአሕዛብ ምሳሌ፤ ውርንጫ፣ ቀንበር መሸከም እንደማትችል አሕዛብም ሕግ መጠበቅ ያልለመዱ ናቸውና (አልለመዱምና)፡፡ በሌላ በኩል አህያ፣ የኦሪት፤ ውርንጫ የወንጌል ምሳሌዎች ናቸው፡፡ አህያ የሠረገላ ቀንበር መሸከም እንደ መልመዷ ኦሪትም በዘመኑ የተለመደች ሕግ መኾኗን፤ ውርንጫ ቀንበር መሸከም እንዳለመልመዷ ወንጌልም በዘመኑ ያልተለመደች (አዲስ) ሕግ መኾኗን ያመላክታል፡፡

ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ብዙ ሕዝብ ‹‹እንኳን አንተ፣ ተቀመጥህባት አህያም መሬት መርገጥ አይገባትም›› ሲሉ ልብሳቸውን በጎዳናው ላይ አንጥፈውለታል፡፡ ሌሎችም ቅጠል እየቈረጡ ከመንገድ ያነጥፉ ነበር፡፡ እግዚአብሔርን መያዝ እንደዚህ ያስከብራል፡፡ ከእርሱ መለየት (እርሱን መካድ) ግን ያዋርዳል፡፡ እርሱን በሕይወታችን ላይ ካስቀደምን በእርሱ ምክንያት ብዙዎች ያከብሩናል፡፡

ሕዝቡ ለጌታችን ልብስና ቅጠል ማንጠፋቸው ከኢዩ የንግሥና ታሪክ ጋር ተመሳሳይ ኾኖ ይጠቀሳል፡፡ ኢዩ ከእስራኤል ነገሥታት አንዱ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድ ለንግሥና ሲመረጥ ቅብዐ መንግሥት የተቀባው በድንገት ነው፡፡ ታሪኩም እንዲህ ነው፤ ነቢዩ ኤልሳዕ ከደቂቀ ነቢያት አንዱን ጠርቶ ‹‹ቀርነ ቅብዑን ይዘህ ሒድ፤ ኢዩን ቀብተህ አንግሠውና ፈጥነህ ና፤ ከሰው ጋር አትነጋገር›› ብሎ ላከው፡፡ መልእክተኛውም የኤልሳዕን ትእዛዝ ተቀብሎ ወደ ኢዩ ሔደ፡፡ ኢዩንም በአደባባይ ተቀምጦ ከባልንጀሮቹ ጋር ሲጫወት አገኘውና መልእክት እንዳለው ነገረው፡፡ ኢዩም ‹‹ከእኛ ነው ከሌላ?›› ብሎ ቢጠይቀው ‹‹መልእክት እንዳደርስ ወደ አንተ ተልኬ መጥቻለሁ›› አለው፡፡

በዚህ ጊዜ ወደ እልፍኝ ይዞት ገባ፡፡ በዚያም ‹‹ከመዝ ይቤ አምላከ እስራኤልቀባዕኩከ ትንግሥ ላዕለ ሕዝብየ እስራኤል፤ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤በሕዝቤ እስራኤል ላይ ትነግሥ ዘንድ ቀባሁህ›!›› ብሎ የንግሥና ቅብዓትን ቀብቶት ተመለሰ፡፡ ኢዩ ወደ ባልንጀሮቹ በሔደ ጊዜም ‹‹መልእክተኛው ምን አለህ? ነገረን?›› ብለው አፋጠጡት፡፡ እርሱም ‹‹ትነግሣለህ ብሎ ቀብቶኝ ሔደ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹እኛስ ሌላ ምን እንሻለን?›› ብለው ከፊሉ ምንጣፍ አንጥፈውለታል፤ ከፊሉ መጋረጃ ጋርደውለታል (፪ኛ ነገሥት ፱፥፩-፲፩ )፡፡

ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባም በዚህ አምሳል እስራኤላውያን ልብሳቸውን በጎዳናው ላይ አንጥፈዋል፡፡ ቅጠል እየቈረጡ ያነጠፉም ነበሩ፡፡ ቅጠሉ ሰሌን ከኾነ አብርሃም ይስሐቅን፣ ይስሐቅ ያዕቆብን፣ በወለዱ ጊዜ፤ እስራኤል ከግብፅ በወጡ ጊዜ፤ ዮዲት ሆሎሆርኒስን ድል ባደረገች ጊዜ ሰሌን ቈርጠው ይዘው ማመስገናቸውን ያስታውሳል፡፡ ደግሞም ሰሌን እሾኽ እንዳለበት ዂሉ ጌታችንም የኃይል፣ የማሸነፍ ምልክት (ሥልጣን) ያለው አምላክ መኾኑን ያመላክታል፡፡ ሰሌንን እሳት አይበላውም፤ ለብልቦ ይተወዋል እንጂ፡፡ ይህም የጌታችን መለኮታዊ ባሕርይ የማይመረመር መኾኑን ያስገነዝባል፡፡

ቅጠሉ ተምር ከኾነ ተምር ልዑል (ትልቅ)፤ ፍሬው አንድና በእሾኽ የተከበበ እንደ ኾነ ዂሉ ‹‹አንተም ልዑለ ባሕርይ (በባሕርይህ ከፍ ከፍ ያልህ) ነህ፤ ባሕርይህ አንድ ነው፤ አይመረመርም›› ሲሉ የተምር ቅጠል አንጥፈውለታል፡፡ ቅጠሉ ዘይት ነው ያሉ እንደ ኾነ ዘይት ጽኑዕ (የጸና)፣ ብሩህ (የሚያበራ)፣ መሥዋዕት ነው፡፡ እስራኤል የዘይት ቅጠል ማንጠፋቸውም ጌታችን ጽኑዐ ባሕርይ (ባሕርዩ የጸና)፣ ብሩህ እንደ ኾነ እንደዚሁም ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ዓለምን እንደ አዳነ ያመላክታል፡፡ በዕለተ ሆሣዕና በቤተ ክርስቲያን የዘንባባ ቅጠል የሚታደለውም ይህንኑ ምሥጢር ለማስታወስ ነው፡፡

ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ በገባባት በዚያች ዕለት በእስራኤል የነበረው ደስታ የተለየ ነበር፡፡ ሕፃናት ሲመሩ አረጋውያን እየተከተሉ፤ አረጋውያን ሲመሩ ሕፃናት እየተከተሉ፤ ነቢያት ሲመሩ ሐዋርያት እየተከተሉ፤ በዐሥር ሺሖች የሚቈጠር ሕዝብ ጌታችንን ከፊትና ከኋላው ከበውት፤ ጻድቃን በቀኙ፣ ተነሳሕያን (ንስሐ የሚያስፈልጋቸው) በግራው አጅበውት እነዚህ ዂሉ ‹‹ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት ቡሩክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር ሆሣዕና በአርያም፤ ለዳዊት ልጅ መድኀኒት መባል ይገባዋል፤ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ (አምላክነቱን ገልጦ) በእግዚአብሔር ስም የመጣ እርሱ (ክርስቶስ) መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሌለበት፤ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን የሚያድል በሰማይ ያለ መድኀኒት እርሱ ነው›› እያሉ አመስግነውታል (መዝ. ፻፲፯፥፳፬-፳፮)፡፡

ከፈሪሳውያንና ከሕዝቡ መካከልም በዚህ ልዩ ምስጋና እና ደስታ ተበሳጭተው ‹‹መምህር ሆይ፥ ደቀ መዛሙርትህን ተቈጣቸው›› አሉት፡፡ ጌታችንም እነርሱ ዝም ቢሉ ድንጋዮች አፍ አውጥተው የሚያመሰግኑት አምላክ መኾኑን ነግሮ አሳፍሯቸዋል፡፡ በዕለተ ሆሣዕና ሕዝቡ ዂሉ ለጌታችን የቀረበዉን ምስጋና እና የነበረዉን ደስታ ዓይተው ተገረሙ፡፡ ከተማዪቱም ‹‹በዚህ አኳኋን የተገለጠ ይህ ማነው?›› ብላ፤ አንድም የፊቱ ብርሃን ፀሐይን ሲበዘብዝ (ከፀሐይ በላይ ደምቆ ሲያበራ) አይታ፤ የሕፃናትን ምስጋና ሰምታ ተረበሸች፤ ታወከች፤ ደነገጠች፡፡

በቀር እርሱን ዓይቶ ማን ተረጋግቶ ይቆምና! ጌታችን በትሕትና በተገለጠ ጊዜ ግርማው ይህን ያህል ካስደነገጠ በግርማ መለኮት፣ በክበበ ትስብእት ዳግም ለፍርድ ሲመጣ እንዴት ያስፈራ ይኾን? ያን ጊዜ የቅጣት ፍርድ ከመስማትና ከመደንገጥ እንድን ዘንድ ከኀጢአት ተለይተን በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን እንኑር፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ኒቆዲሞስ እና አዲሱ ልደት – የመጨረሻ ክፍል

በዲ/ ታደለ ፈንታው

መጋቢት ፳ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

‹‹ኢየሱስም መለሰ፤ እንዲህ ሲል፡- እውነት እውነት እልሃለሁሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም››

ጌታ ይህንን እውነት ዝቅ አድርጎ እንዳይመለከተው በማሰብ አስቀድሞ የተናገረውን ነገር ደገመለት፡፡ በእርግጥ የእግዚአብሔር ቃል አዎ አይደለም ከሚለው አፍአዊ ነገር በዘለለ መልስን የሚጠይቅ ነው፡፡ ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ ከመረዳት አቅሙ በላይ ቢኾንም ጌታ እንደ ገና መወለድ ትምህርቱ ላይ ጠንከር ብሎ ሔዷል፡፡ ያለዚህ ልደት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየትም ለመግባትም የሚያስችል መንገድ የለም፡፡ ሰው ከውኃና ከመንፈስ መወለድ አለበት ይላል፡፡ ስለምን ውኃን ይጠቀማል? ውስጣዊ የመንፈስ መታጠብን ለማመልከት ነው (ሕዝ. ፴፮፥፳፭፤ ፩ኛ ቆሮ. ፮፥፲፩፤ ቲቶ. ፫፥፭)፡፡ ይህ ውስጣዊ የመንፈስ መታጠብ በመንፈስ ቅዱስ የሚፈጸም ነው፡፡ እርሱ ብቻ ያጥባል ያነጻል ውስጣዊ ልባችንን አዲስ ያደርጋል፡፡ ጌታ በሰርግ ቤት ተገኝቶ ውኃውን ወደ ወይን በመቀየር በሰርጉ ቤት ለነበሩ ዕድምተኞች ደስታን እንደ ሰጠ በመንፈሱ የሰጠው ውጫዊ የሰውነት መታጠብ አይደለም፡፡

ይህ ውኃ ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣ ይጠጣ በማለት ለሳምራዊቷ ሴት የነገራት የሕይወት ውኃ ነው፡፡ በያዕቆብ ጉድጓድ ውስጥ እንዳለው ውኃ አይነት አይደለም ያዕቆብ፣ ልጆቹና፣ ከብቶቹ የጠጡት ውኃ የሚያረካው የሥጋን ጥማት ነው፡፡ ጌታችን የሚሰጠን ውኃ ግን የነፍስን ጥማት የሚያረካ ነው፡፡ አዲሱ ልደት በውኃ ውስጥ ብቅ ጥልቅ እየተባለ መፈጸሙ ሞትን የመቀበልና ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር የመቀበር ምልክት ነው፡፡ ከእርሱ ጋር እንነሣ ዘንድ የግድ ያስፈልገናልና፡፡ ‹‹እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደ ተነሣ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ፡፡ ከሞቱ ጋር አንድ እንኾን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን›› እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ፡፡€

ከውኃና ከመንፈስ መወለድ የአሮጌውን ሰው መሞትና የአዲሱን ሰው ትንሣኤ ይጠይቃል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ የኾነውን አዲስ ሕይወትም መቀበል ነው፡፡ እርሱም የትንሣኤ መንፈስ ነው፡፡ ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር የሚያደርገንን አዲሱን ሰው የመፍጠር ሒደት ነው፡፡ በፈጣሪያችን መልክ የተፈጠረውን አዲስ ሰው መመልከት ነው፡፡ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አምነው መስቀሉን ሊሸከሙ የሚወዱ ወገኖች በአብ፣ በወልድ እና በመንፈስ ቅዱስ ስም መጠመቅ አለባቸው፡፡ ‹‹የጌታ ቃል ትርጕም ለኒቆዲሞስ ምንድን ነው?›› ብሎ ለሚጠይቅ ምላሹ ‹‹ጌታ ከሥጋ ትውልድ ወጣ ብሎ መንፈሳዊውን ትውልድ እንዲያስብ ሳበው›› የሚል ነው፡፡

ጌታችን ለኒቆዲሞስ እንዲህ በማለት የነገረው ይመስላል፤ ‹‹ኒቆዲሞስ ሆይ እየነገርሁህ ያለሁት ስለ ሌላ ልደት ነው፡፡ ስለምን ነው ንግግሬን ወደ ምድራዊ ነገር የምታወርደው? የምነግርህ ነገር ስለምን በተፈጥሮ ሕግ እንዲገዛ ታደርጋለህ? ይህ ልደት በሥጋ (በምጥ) ከሚደረገው ትውልድ የተለየ ነው፡፡ አጠቃላይና የተለመደ ከኾነ ልደት ራስህን አውጣ፡፡ እኔ ሌላ ልደትሚገኝበት መንፈሳዊ ዓለም ሾሜሃለሁና፡፡ ሰዎች ዂሉ ከዚህ አዲስ ልደት እንዲወለዱ እወዳለሁ፡፡ አዲስ ዓይነት ልደትን ይዤ ወደ ምድር መጥቻለሁ፡፡ ሰውን የፈጠርሁት ከምድር አፈርና ከውኃ ነበር፡፡ ይህ ያገለግለኛል ብዬ የፈጠርሁት ምርጥ ዕቃ የተፈጠረበትን ዓላማ ዘንግቶ አግኝቸዋለሁና እንደገና ከአፈርና ከውኃ ልሠራው አልፈቅድም እንደገና በውኃና በመንፈስ እንዲወለድ እፈቅዳለሁ እንጂ፡፡››

ከመካከላችን እግዚአብሔር ‹‹ሰውን እንዴት ከውኃ ፈጠረው?›› ብሎ ሊጠይቅ ይችላል፡፡ ምላሹን የሚያገኘው ግን የሚከተሉትን ጥያቄዎች መመለስ ሲቻል ነው፤ ‹‹ሰውን እንዴት ከምድር አፈር አበጀው? ጭቃን እንደምን አድርጋችሁ ወደ ተለያየ ክፍል ትከፋፍሉታላችሁ? አጥንት፣ ነርቭ፣ የደም ሥር፣ የደም ቧንቧ ከየት ተሠሩ? ቆዳ፣ ደም፣ ጉበት ከየት ተሠሩ? ይህ ታላቅ ሥራ ለምን የተከናወነ ይመስላችኋል? የተለያየውስ ቀለም? እነዚህ ዂሉ ዓይነቶች ውሁዶች ከየት ተገኙ?›› እነዚህ ዂሉ ነገሮች የምድርም የጭቃም አካል አይደሉምና፡፡

ምድር ዘርን ስትቀበል እንዴት አድርገው ሥር ይሰዳሉ? ነገር ግን በእኛ አካል ውስጥ ሲኾኑ እነዚህ ዘሮች ይፈጫሉ፡፡ ምድር ዘርን ምን መግባ ዘር ፍሬ እንዲያፈራ ታደርጋለች? እንደ ገናስ ሰውነታችን እንዴት በእነዚህ ዘሮች ይገነባል? ምድር ውኃን ትቀበላለች፤ ወደሚያፈራ ወይንም ትቀይረዋለች፡፡ የእኛ ሰውነት ግን ወይንን ተቀብሎ ወደ ውኃ ይቀይረዋል፡፡ በአሳብ የምትሰጠው ፍሬ ሁሉ የእርሷ ውጤት መሆኑን በምን በምን በምን መንገድ ነው የሚለውን ግን ማስረዳት ቀላል ነገር አይደለም፡፡ ምድር በፍሬዋ ሰውነታችንን ታጠግባለች፤ በእግዚአብሔር ላይ ያለን እምነት ብቻ ነው እነዚህ ዂሉ ነገሮች የምድር ውጤቶች ናቸው ብለን እንድቀበል የሚያደርገን፡፡

እነዚህ ዂሉ ዓይነት ተጨባጭ ነገሮች በየቀኑ የሚከሠቱ ስለ ኾነ እምነት የሚይጠይቁ ናቸው፡፡ መንፈሳዊ የኾነው ጉዳይ በቂ ትኩረትና ቅድምና ማግኘት እንደሚኖርበት እንገነዘባለን፡፡ የማይንቀሳቀሰው ምድር ለእግዚአብሔር ፈቃድ መልስ ይሰጣል፡፡ ምድር የምትሸከመው ይህ ዂሉ ነገር የተገኘው ለዚህ ፈቃድ ነውና፡፡ በተመሳሳይ ኹኔታ ከመረዳታችን በላይ የኾነ ጽንፍ የያዘ ብዙ ምልክት ይፈጠራል፡፡ ከመካከላችን አንዱ፡- ‹‹ውኃ ለዳግም ልደት ለምን ያስፈልጋል?›› ብሎ ቢጠይቅ ምላሹ ‹‹ይህ ልደት አምላካዊ ጠቀሜታ አለው›› የሚል ነው፡፡ መቃብር፣ መቀበር እምነት፣ ሕይወትና፣ ትንሣኤ እነዚህ ዂሉ ምሥጢራት በጥምቀት ጊዜ የሚከናወኑ ናቸው፡፡ ጭንቅላታችንን ውኃ ውስጥ እንነክራለን፤ ወደ መቃብር እንደምንወርድ ዂሉ አሮጌውን ሰውነታችንን እንቀብር ዘንድ ጭንቅላታችንን ስናነሣ አዲሱ ሰው በተመሳሳይ ኹኔታ ይገኛል፡፡‹‹ከመንፈስ የሚወለድ እርሱ ማነውእንደሚያታልል ምኞት የሚጠፋውን አሮጌውን ሰው አስወግዶ በአእምሮው መንፈስ ከሚታደስ ሰው በስተቀር፤››€ተብሎ እንደ ተጻፈ (ኤፌ. ፬፥፳፫)፡፡

በእርግጥ ይህ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ እንደ ገና የተወለደው ሰው ነው፡፡ ይህ በዘላለማዊ ሕይወት የመተማመን ውጤት ነው፡፡ ይህም በጥምቀት አማካኝነት የሚፈጸም ነው፡፡ በእርግጥም እንዲህ ዓይነት ሰው እንደ ምሕረቱ መጠን በአዲስ ልደት በሚኾነው መታጠብም በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ መንፈሳዊ ልጅነትን የተቀበለ ነው፡፡ በሌላ ንባብ ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ ይላል፤ ‹‹በመንፈስ ቅዱስ ስም ትጠመቃላችሁ›› (ሐዋ. ፲፩፥፲፮)፡፡ ከውኃና ከመንፈስ ከተወለደ ወገን ውጭ በመንፈስ ቅዱስ የተጠመቀ ማነው? ለዚህም ነው ጌታችን ‹‹… ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለዳችሁ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት አይቻላችሁም›› በማለት በጥምቀት የምናገኘውን ልጅነትና ዘለዓለማዊ መንግሥት የነገረን፡፡

በምሥጢረ ጥምቀት የኀጢአት እሥራት ይፈታል፡፡ ስለዚህም ሕፃናት ሳይቀሩ ይጠመቃሉ፡፡€ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ይገባ ዘንድ አይቻለውምና፡፡ ጥምቀት ኀጢአታችን ዂሉ ያጥባል፡፡ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ መቅደስ እንድንኾን ያደርገናል፡፡ ሰማያዊ ተፈጥሮአችንን ያድሳል፡፡ ይህም በመንፈስ ቅዱስ ግብር የሚፈጸም ነው፡፡ በጥምቀት ሰው ከሰይጣን ኀይል ነጻ ይኾናል፤ ይህም በመንፈስ ቅዱስ የሚከናወን ነው፡፡ የተጠመቀውን ሰው የሚቀድስና የሚያነጻ መንፈስ ቅዱስ ነውና፡፡ በእንደዚህ ዓይነት ሰው ላይ ሰይጣን የወደደውን ያደርግበት ዘንድ አቅሙ አይኖረውም፡፡ ሰው በጥምቀት ከክርስቶስ ጋር አንድነትን ሲፈጥር እንደ ገና ከመወለዱ ባሻገር ክርስቶስን በዂለንተናው ይለብሰዋል (ገላ. ፫፥፳፯)፡፡ ይህ ምሥጢር በንባብ ብቻ የምንረዳው አይደለም፡፡ የፍቅር መግለጫ ነውና፡፡ ይህንን የምንረዳው ጌታ ሥጋችንን ተዋሕዶ እኛን ለማዳን ሲል በእኛ መጠን በመወለዱ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ኒቆዲሞስ እና አዲሱ ልደት – ሦስተኛ ክፍል

በዲ/ ታደለ ፈንታው

መጋቢት ፲፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

‹‹ኢየሱስም መልሶ እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም አለው››€

ኒቆዲሞስ ምልክትን ማድረግ ለክርስቶስ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደሆነ ለማመኑ ማሣያ አድርጎ ቆጥሮ ነበር፡፡ ምክንያቱም የአይሁድ ረበናት እምነትን ምልክት ከመሥራት ጋር አያይዘውታልና፡፡ ስለ ክርስቶስ ማንነት ለመመስከር ከዚህ ወንዝ ባሻገር ያቋረጠው የለም፡፡ ስለዚህ ጌታን በጎነት ያለው መምህር፣ የእግዚአብሔር ሰው አድርጎታል፡፡ እግዚአብሔር ይስሐቅን ‹‹አትፍራ፤ እኔ ከአንት ጋራ ነኝና›› (ዘፍ. ፳፮፥፳፬) እንዳለው ሰው ዓይነት አድርጎ ገምቶት ነበር፡፡ ወይም እንደ መበለቲቱ ልጅ ‹‹ኢያሱ ከሙሴ ጋር እንደ ነበርሁ ከአንተም ጋር እሆናለሁ›› (ኢያ. ፩፥፭) ያለው ዓይነት ነቢይ ነበር ጌታ ለኒቆዲሞስ፡፡ ሌሎች ብዙ አለቆችና ነቢያት ተመሳሳይ ልምድ ነበራቸው፤ ነገር ግን ኒቆዲሞስ ምንም እምነትን ይዞ ቢመጣም ከፈሪሳውያን ጠባብ አስተሳሰብ ልጓም እንዳይወጣ የሚያደርግ አእምሮ ነበረው፡፡ የተማረውም ይኼንን እውነታ ነው፡፡ በጌታና በኒቆዲሞስ መካከል የነበረው ውይይት የሚከተሉት ነጥቦች የትኩረት አቅጣጫዎቹ ነበሩ፤

፩. የዳግም ልደት አስፈላጊነት እርሱም ውስጣዊው ዓለም የተሻለ እንደ ኾነ የሚያሳይ ነው፤ ይኸውም የእግዚአብሔር መንግሥት ነው፡፡ ይህ አባባል በቅብጥ፣ በሶርያ፣ በላቲን በመጀመሪያይቱ ቤተ ክርስቲያን አባቶች ጽሑፍ የተካተተ ነው፡፡ ዮስጢኖስ፣ ቀሌምንጦስ ዘእስክንድርያ፣ ጠርጡለስ፣ አውግስጢኖስና፣ ዠሮም ለአብነት ይጠቀሳሉ፡፡ ጌታችን ኒቆዲሞስን እንደ ገና እንዲወለድ እንደጋበዘው ተረድቷል፡፡ ይህ አስደነቀው፡፡ አሳቡ በልቡ ውስጥ መዳህ ጀምሯል፡፡ ስለዚህም ‹‹ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል?›› አለ፡፡

፪. አዲሱ ልደት ከላይ ነው ሰማያዊ ነው፡፡ ይህ ድርጊት በቅዱሱና በሰማያዊው የእግዚአብሔር መንፈስ ብቻ የሚፈጸም ነው፡፡ የሰውን አሳብ ዂሉ ያለፈ ስጦታ ነው፡፡

፫. አዲሱ ልደት የሚፈጸመው በውኃና በመንፈስ ነው፡፡

፬. ይህ ልደት በኀይል ያለ በነፍስ የተመሰለ ነው፡፡ ስለዚህ ማንም ምሥጢሩን ሊገነዘበው አይችልም፡፡

በአይሁድ ጽሑፍ እውነት የሚለው ቃል መደገሙ በእውነት ቅዱስ ከሚለው ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ጌታችን የሚናገረው ነገር በጣም ጠቃሚና ትኩረት የሚያሻው መኾኑን ለመናገር ይጠቀምበታል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በርጋታ ለኒቆዲሞስ የገለጸለት ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ዘንድ መምህር መኾኑን ማመን ብቻውን በቂ አለመኾኑን፣ ተአምራቱንም ማድነቅና የተለዩ መኾናቸውን ማወቅ በራሱ ግብ አለመኾኑን ነው፡፡ በእርግጥም የሚያስፈልገው እንደ ገና መወለድ ነው፡፡ እርሱም ሰማያዊ የኾነ ልደት ነው፡፡ ሰማያዊ መንፈሳዊ የኾኑ ጉዳዮችን ለማየት ያስችላልና፡፡ በእናቱ ማኅፀን ያለ ፅንስ በዚህ ዓለም እየኾነ ስላለው ነገር የሚያውቀው ነገር የለም፡፡

በተመሳሳይ ኹኔታ አንድ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት መመልከት አይቻለውም፡፡ እንደ ገና ከተወለደ ብቻ ነው የአዲሱን ዓለም ብርሃን መመልከት የሚችለው፡፡ ሊያይ የሚለው ጌታችን አጽንዖት ሰጥቶ የተናገረው ግሥ ለእውነተኛ ክርስቲያን አስፈላጊ ነው፡፡ አዲሱን ልደት ያጣጥም ዘንድ ስለ ተወለደ እንዲመካ አይደለም የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊመለከት ለመንግሥቱም እንደሚገባ ሊመላለስ ይገባዋል እንጂ፡፡ ይህ ማለት አእምሮውና ልቡ ሰማያዊ በኾነ ነገር ላይ ማተኮር አለበት ማለት ነው፡፡ ከሰማያዊ ሕግ ጋር አብሮ የሚሔድ ሕግን ያለማወላወል ሊከተል ይገባዋል፡፡ አዲስ ግብ፣ አዲስ ተስፋ አዲስ ኀይልን ገንዘብ አድርጎ፡፡

በአዲሱ ልደት ክርስቲያን በዓይነቱ የተለየ ኑሮን መኖር ይጀምራል፤ አሮጌውን የሰውነቱን ሕንጻ አፍርሶ መሠረቱ ክርስቶስ የኾነውን አዲስ ሕንጻ በማነጽ አሮጌው ሰዎችን ተወግዶ የክርስቶስን መልክ የያዘው አዲሱ ሰው ሊታይ ይገባዋል፡፡ አስቀድመን ኀጢአት ጥንተ ተፈጥሮአችንን ስላጠፋው፣ የልባችንም ጥልቅ በኀጢአት ተይዞ ስለ ኖረ፣ ሥጋውያን በሥጋ ሕግና ፈቃድም የምንመራ ኾነናል፡፡ የምንመራውም የመልካም ነገር ጠላት በኾነ በዲያብሎስ ነበረ፤ ስለዚህ አዲሱ ልደት ልንሸሸው የማይገባ ጠቃሚ ጉዳይ ኾኖ ቀርቧል፡፡ ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ›› የሚለው የጌታ ቃል ለዚህ እውነት ማሳያ ነው፡፡

የእግዚአብሔር መንግሥት ምንድን ነው? ከሰማያዊው መሲሕ ሌላ መመልከት እንደሌለብን የምታሳስብ መንግሥት አይደለችምን? በእኛ መካከል መንግሥቱን መሥርቶ ይኖራል፡፡ ከእርሱ ጋር አንድነትን ፈጥረን የምናየው፣ የምንኖረው ዂሉ ለዚህ ሕይወት እንደሚገባ ነው፡፡ እርሱ ቅዱስ ስለ ኾነ እኛም ቅዱሳን እንኾናለን፡፡ በእኛ የሚኖረው የእግዚአብሔር መንግሥት ትክክለኛ ትርጕምም ይኼው ነው፡፡ ጌታ ‹‹መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ›› አለ (ማቴ. ፬፥፲፯)፡፡ እንደ ገናም በእግዚአብሔር መንግሥት ያለንን ሥፍራ ሲናገር ‹‹መንግሥተ ሰማያት በመካከላችሁ ናት›› ብሏል (ሉቃ. ፲፯፥፳፩፤ ራእ. ፩፥፮)፡፡

ይህ መንግሥት ከጌታችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ኅብረትን የምንፈጥርበት መንግሥት በመኾኑ እንዲህ ተብሏል፤ ‹‹የእግዚአብሔር መንግሥት ጽድቅና ሰላም በመንፈስ ቅዱስም የኾነ ደስታ ናት እንጂ መብልና መጠጥ አይደለችም›› (ሮሜ. ፲፬፥፲፯)፡፡ ይህ መንግሥት ለዘላለማዊ ሕይወት ዋስትና ነው፡፡ ወደ ሰማይ እንድንጓዝ ጌታ በጌትነቱ ሲመጣ አስደናቂውን ክብር እንድንካፈል ያደርገናል፡፡ ከምንም በላይ አሳባችንን ከፍ ከፍ አድርጎ ውስጣዊ ነፍሳችንን የመጨረሻውን ቀን እንድትመለከት ጌታ ሲመጣ ሰማያዊ ዘውድን ደፍተን ያለ ፍርሃት በፊቱ እንቆም ዘንድ የሚያስችለንን ጸጋ እንይዝ ዘንድ ያስችለናል፡፡

የጌታን ቃል እንደ ገና በሌላ አባባል እንግለጠው ብንል ‹‹ዳግመኛ ካልተወለድህ ከመንፈስ ጋር ኅብረት ካልፈጠርህበጥምቀት ልጅነትን ካላገኘህ፣ እኔን በተመለከተ ትክክለኛ የኾነውን አሳብ አታገኝም›› የሚል ይኾናል፡፡ ኒቆዲሞስም ‹‹ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል? ሁለተኛ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን?›› በማለት ጠየቀ፡፡ የኒቆዲሞስ ጥያቄ የእውቀት ድካሙን ይገልጣል፡፡ ጌታ የሚናገረው በመንፈሳዊ ቋንቋ ነው፡፡ የኒቆዲሞስ ልብ ነገሮችን የሚያገናኘው ቁሳዊ ዓለማዊ ከኾኑ ነገሮች ጋር ነው፡፡ ቁሳዊ ነገሮችን ከልቡናው ከአእምሮው ካላወጣ መንፈሳዊና ሰማያዊ የኾኑ ምሥጢራትን እንደምን ሊገነዘብ ይችላል? ያኔ ነው ወደ እውነት መድረስና በእግዚአብሔር መንፈስ አዲስ መንፈሳዊ ጉልበትን ይዞ ምሥጢርን መረዳት የሚቻለው፡፡

ይህ ዂሉ ነገር እያለ ኒቆዲሞስ ጀርባውን ለጌታ አልሰጠም፤ እርሱ የጎደለው አንድ ነገር እንዳለ አምኖ ትምህርቱን ቀጥሏል፡፡ በግብሩ ምንም እንኳን መምህርና አለቃ ቢኾንም በትሕትና እውነተኛ የኾነ ነገርን ለመማር የተዘጋጀ መኾኑን ገልጧል፡፡ ነገር ግን ጌታ የሚለው አዲስ ልደት የማይቻል እንደ ኾነ ገምቷል፡፡ አስደናቂ ሰው ነው፡፡ ረጅም ዘመን የትምህርትና የአመራር ልምድ ያለው ሰው ከጌታ እግር ሥር ተንበርክኮ አዲስ ነገርን ሲማር መመልከት ያስደንቃል፡፡ ለእውነተኛ አለቃ ጌታ የሰጠው ምሳሌ አስቸጋሪ ሊኾንበት ይችላል፡፡ አሁን ኒቆዲሞስ ስለ ትምህርትና ስለ አመራር ልምዱ ሲመካ አንመለከተውም፡፡ እስከ መጨረሻው እስትንፋሱ ድረስ ሲማር እንጂ፡፡ አምብሮስ እንዲህ ይላል፤ ‹‹የኒቆዲሞስኔታ የሚያሳየን መማር የማያስፈልገው እግዚአብሔር ብቻ መኾኑን ነው፡፡››

ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ መጣ፤ ከፍ ያሉ ነገሮችን አዳመጠ፡፡ እንዲህ ዓይነት ጉዳዮች ተራ ሰው የሚገልጣቸው አይደሉም፡፡ ማንም ሰውም ከዚህ አስቀድሞ ሰምቷቸው አያውቅም፡፡ በቅፅበት ኒቆዲሞስ ወደ ከፍታ ወጣ፤ ነገር ግን መረዳቱ ጨለማ ነበር፡፡ ነገር ግን በራሱ ማስተዋል ገና የቆመ በመሆኑ ሊሸከማቸው ስላልቻለ ወደቀ፤ የጌታን ቃል እንዴት ሊሆን ይችላል? በማለት ጠየቀ፡፡ ጌታ የተናገረውን ነገር እንዲያብራራለት ሰው ከሸመገለ በኋላ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን በማለት ማብራሪያ ጠየቀ፡፡ ኒቆዲሞስ ስለ መንፈሳዊ ልደት ሰምቷል፡፡ ነገር ግን በመንፈስ አልተለማመዳቸውም (አያውቀውም)፡፡ የተማመነውም ቁሳዊ መረጃ ላይ ነው፤ ይህን ትልቅ ምሥጢር ለመረዳትና ለመተርጐም ምሳሌ አድርጎ ያቀረበው የሰውን የሥጋ ልደት ነው፡፡ ይህን ኹኔታ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ በማለት ይገልጠዋል፤ ‹‹ለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም፡፡ በመንፈስም የሚመረመር ስለ ኾነ ሊያውቀው አይችልም›› (፩ኛ ቆሮ. ፪፥፲፬)፡፡

በዚህ ዂሉ ነገር ኒቆዲሞስ ክብርና ጉጉት ይታይበታል፡፡ ጌታ የነገረው ነገር አላስቆጣውም፡፡ ነገር ግን ይህ ኹኔታ የማይቻል መኾኑን አስቦ ጥያቄ ጠይቆ ዝም አለ፡፡ ሁለት ነገሮችን ተጠራጥሯል፡፡ ምን ዓይነት እንደ ገና መወለድ እና የእግዚአብሔር መንግሥት፡፡ አይሁድ በየትኛውም ጊዜ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት የተናገሩት ነገር የለም፡፡ ስለ ዳግም ልደትም እንዲሁ፡፡ ስለነዚህ ነገሮች ሰምተውም አያውቁም፡፡ ኒቆዲሞስን ያስደነቀውም ነገር ይህ ነው፡፡

ቅዱስ አውግስጢኖስ እንደተ ተናገረው ይህ ሰው ከአዳምና ከሔዋን የሚደረግ ልደትን ሰምቷል፤ ከእግዚአብሔርና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስለሚደረገው ልደት ግን አያውቅም፡፡ የሚያውቀው ዘርን የሚተኩ ወላጆች በሞት ፍጻሜያቸውን እንደሚያገኙ ነው፡፡ ነገር ግን ሕይወትን ስለሚሰጠው ስለ አዲሱ ልደት ያለው ግንዛቤ ከመረዳት በታች ነው፡፡ ንብረታቸውን የሚወርሱ ልጆችን የሚወልዱ ቤተሰቦች ያውቃል፡፡ ነገር ግን ዘወትር የሚኖሩ ልጆችን የሚወልዱ የማይሞቱ ወላጆችን በተመለከተ እውቀት የለውም፡፡ ሁለት ዓይነት መወለድ አለ፡፡ አንደኛው በምድር የሚደረግ ሁለተኛው ሰማያዊ፡፡ የመጀመሪያው ከሥጋና ከደም ሁለተኛው ከውኃና ከመንፈስ፤ የመጀመሪያዎቹ ለሞት የተጋለጡ ናቸው የኋለኞቹ ዘላለማውያን ናቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ የተወለዱት ከወንድና ከሴት የኋለኞቹ ከእግዚአብሔርና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ኒቆዲሞስን በተመለከተ የሚያውቀው አንድ ልደትን ብቻ ነው፡፡

ይቆየን

ኒቆዲሞስ እና አዲሱ ልደት – ሁለተኛ ክፍል

በዲ/ ታደለ ፈንታው

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ ዘንድ እየሔደ የመማሩ አምስተኛው ምክንያት ለካህናት አለቆች ወሬው ሊደርስ ይችላል ብሎ ከፍርሃት የተነሣ ነው፡፡

ስድስተኛው ደግሞ ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ ዘንድ መድረሱን አይሁድ ቢያውቁ ጌታችንን ለመዋጋት ቁጣቸውን ይጨምርላቸዋል፡፡ ኒቆዲሞስን ራሱን ለመጉዳት አይሁድ ፈሪሳውያን ሊነሣሡበት ይችላሉ፡፡ ምንም እንኳን በጌታ ትምህርት ቢማረክም በቀን እንዳይሔድ እምነት አንሶት ሊሆን ይችላል፡፡

ሰባተኛው ምክንያት ከምንም በላይ ጌታ የዓለም ብርሃን መኾኑን በእርግጠኝነት አለመረዳቱ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ የአይሁድ አለቃ ነው፤ የእስራኤል መምህር ነው፡፡ ሰማያዊውን ደስታ ገንዘብ ያደርግ ዘንድ አዲስ ልደት የሚያስፈልገው ሰው ነው፡፡ በምሽት ሲመጣ ደካማ የሆነ እምነትን ይዞ ነበር የመጣው፤ ነገር ግን የጌታ በር ተከፍቶ አገኘው፡፡ ጌታ ስሜቱን ሊጎዳው አልወደደም፡፡

ዂሉ ነገር የሚቆጠረው እምነት እንደ ሰናፍጭ ቅንጣት ቀስ በቀስ በልቡ ውስጥ እንደሚያድግ ነበር፡፡ ጌታ የፈለገው ያች ቅንጣት አብባ፣ አፍርታ፣ ጌታ በሚሰቀልበት ጊዜ ትልቅ ዛፍ ትኾን ዘንድ ነበረ፡፡ እንደዚያ ሲኾን ነው በዚያ እምነት ደረጃ ላይ ሲደርስ ነው በድፍረት የጌታን ሥጋ የቀበረው፡፡

ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር በተገናኘ ጊዜ የአይሁድ ድካም በእርሱም ላይ ይንጸባረቅ ነበር፡፡ አስቀድመን እንዳልነው በብርሃን ሳይኾን በጨለማ የመምጣቱም ምክንያት ይህ ነበር፡፡ ነገር ግን መሐሪው አምላክ አልጠላውም፤ ትምህርቱንም አልከለከለውም፡፡ ከዚህ በተቃራኒው ከጌታው ጋር በፍቅር ለመነጋገር ቻለ፡፡ ጌታችንም ከፍ ያለውን ምሥጢር ገለጠለት፡፡ ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ ከአይሁድ የተለየ ቢኾንም ጌታን የቆጠረው ሰው አድርጎ ነው፡፡ ይናገረው የነበረው እንደ ነቢይ ነው፡፡ ያደረገውን ምልክት እያደነቀ ነበር የጠየቀው፡፡ ‹‹መምህር ሆይከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን … እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከኾነ በስተቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና›› ነበር ያለው፡፡

ኒቆዲሞስ ጌታ በተናገረው አዲስ ልደት ተደንቋል፡፡ ልክ እንደ ሌሎች አይሁድ ዘመዶቹ የአብርሃም ዘር በመኾኑ የሚመካ ነው፡፡ ጌታ ደግሞ እንደ ገና ተወለድ እያለው ነው፡፡ አይሁድ ለእግዚአብሔር የተመረጡና የተወደዱ አድርገው ራሳቸውን ይቆጥሩ ነበር፡፡ በነቢያትና በተስፋው ቃል ኪዳን የተቀደሱ ሕዝቦች ነን ይሉ ነበር፡፡ ከምንም በላይ እግዚአብሔር ከእነርሱ አባቶች ጋር ቃል ኪዳን ገብቶ ነበር፡፡ ልዩ መቅደስና መሥዋዕትም ነበራቸው፡፡

ኒቆዲሞስ እስራኤላዊ ብቻ አልነበረም፤ ፈሪሳዊም ጭምር እንጂ፡፡ ምን ዓይነት ከዚህ የበለጠ ልደት ጌታ ይሰጠኛል ብሎ ሊያስብ ይችላል? አይሁድ መሲሑ ሲመጣ የእስራኤል መንግሥት እንደሚያምንበት እንደ ገናም እንደሚወለዱ ይገምታሉ፡፡ ነገር ግን አስቀድሞ በነበራቸው ኩራትና ትምክህት አንጻር ሲመዝኑት ይህ የሚኾን አይመስላቸውም ነበር፡፡ እነርሱ አሁን ከያዙት የአብርሃም ልጅነት የከበረ ልደት ያለ መስሎ አይታያቸውም ነበር፡፡ ስለ ትውልድ አገራቸው ይመኩ ነበር፤ ስለዚህ ሌላ ልደት መስማት የሚኾንላቸው አይደለም፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ኒቆዲሞስን ‹‹ኒቆዲሞስ ሆይ፥ ስለ ምን በምስጢር በምሽት መጣህ? ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣ የእግዚአብሔር የሆነውንም ነገር እንደሚናገር እያወቅህ፡፡ ስለምን ከእርሱ ጋር ነገሮችን በግልጽ አልተወያየህም?›› ዓይነት ጥያቄዎችን አልጠየቀውም፡፡ አልወቀሰውምም፡፡ ነቢዩ እንዲህ ይላል፤ ‹‹አይጮኽም፤ ቃሉንም አያነሣም፡፡ ድምፁንም በሜዳ አያሰማም፡፡ የተቀጠቀጠ ሸምበቆን አይሰብርም፤ የሚጨስንም ክር አያጠፋም›› (ኢሳ. ፵፪፥፫)፡፡ ጌታ ራሱ እንዲህ ብሏል፤ ‹‹ዓለሙን ላድን እንጂ በዓለሙ ልፈርድ አልመጣሁም›› (ዮሐ. ፲፪፥፵፯)፡፡

የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትሕትና ተመልከቱ! ‹‹እኔ ዂሉን በራሴ ማድረግ ይቻለኛልና የማንም ርዳታ አያስፈልገኝም፡፡ እኔ ራሴ እግዚአብሔር ነኝ፡፡ የያዝኩት ኀይል የአባቴን ኀይል ነው …›› አላለም፡፡ ይህንን ቢል ለሚያዳምጡት ወገኖች ቃሉን መቀበል ከባድ በኾነ ነበር፡፡

ነገር ግን ድርጊቱን ሲፈጽም በተመሳሳይ መንገድ አልነበረም፤ ምልክትን ሲያደርግ በኀይል ነው፤ ስለዚህም እንዲህ አለ፤ ‹‹ልትነጻ እወዳለሁ›› (ማቴ. ፰፥፫)፤ ‹‹ጣቢታ ተነሽ›› (ማር. ፭፥፬)፤ ‹‹እጅህን ዘርጋ›› (ማር. ፫፥፭) ‹‹ኀጢአትህ ተሰረየችልህ›› (ማቴ. ፱፥፪) ‹‹ፀጥ በል›› (ማር. ፬፥፴፱) ‹‹አልጋህን ተሸከምና ሒድ›› (ማቴ. ፱፥፮)፤ ‹‹አንተ ርኩስ መንፈስ ከዚህ ሰው ውጣ›› (ማር. ፭፥፰)፤ ‹‹ማንም ስለምን እንዲህ ታደርጋላችሁ ቢላችሁለጌታ ያስፈልገዋል› በሉት›› (ማር. ፲፩፥፫)፤ ‹‹ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትኾናለህ›› (ማር. ፳፫፥፵፫)፤ ‹‹ለቀደሙትአትግደል› እንደተባለ ሰምታችኋል፡፡ የገደለም ፍርድ ይገባዋል፡፡ እኔ ግን እላችኋለሁበወንድሙ ላይ የሚቆጣ ዂሉ ፍርድ ይገባዋል›› (ማቴ. ፭፥፳፩)፤ ‹‹ተከተለኝ፤ ሰውን አጥማጅ አደርግሃለሁ›› (ማቴ. ፩፥፲፯)፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የጌታችንን አምላክነትና ትሕትና ሲያስረዳ እንዲህ ይላል፤ ‹‹ስለዚህ ነው ጌታ ኒቆዲሞስን በግልጥ ያናገረው፤ ነገር ግን የአብ የባሕርይ ልጅነቱን በመግለጽ አልጀመረም፤ ምልክት የሚያደርገው በተመሳሳይ ሥልጣን መኾኑን አልገለጠለትም፡፡›› 

በማንኛውም ኹኔታ የጌታችንን ታላቅ ሥልጣን እንመለከታለን፡፡ አምላካዊ ሥራን ሲሠራ ማንም ወገን በእርሱ ላይ ስሕተትን ማግኘት አይቻለውም፡፡ ነገር ግን ሊያጠምዱበት የሚቻላቸው በአንድ መንገድ ብቻ ነው እርሱም በንግግሩ ብቻ ነው፤ ማለት ንግግሩን በተሳሳተ መንገድ በመተርጐም፡፡ ኒቆዲሞስ በስሙ ከሚያምኑ ከጌታ ጋር ግን ግንኙነት ከሌላቸው ወገኖች አንዱ ነበረ፡፡ ስለዚህ በምሽት ወደ ጌታ ዘንድ መጣ፡፡ የመጣው ወደ ብርሃን ቢኾንም በጨለማ መጣ፡፡ ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ የመጣው ወደ ጌታ ቢኾንም የመጣው በምሽትና የሚናገረው በጨለማ ነፍሱ ነበር፡፡ ስለዚህ በሰው ዂሉ ላይ የሚያበራውን ብርሃን የሚናገረውን መልእክት ሊረዳው አልተቻለውም፡፡

ኒቆዲሞስ መምህር ነበረ፡፡ ወደ እውነተኛው ብርሃን በጨለማ የመምጣቱ ምሥጢርም ምናልባት ለክብሩ ተጠንቅቆ ይኾናል፡፡ የሚያናግረውን ጌታ አምላክነት ገና አላወቀም ነበርና ፈራ፡፡ ኒቆዲሞስ በምሽት ወደ ጌታ የመጣው ለመጠመቅ አልነበረም፡፡ ለመማርና የጌታ ደቀ መዝሙርም ለመኾንም አይደለም፡፡ በአይሁድ ትውፊት መሠረት ማንም ወገን በምሽት ወደ አይሁድ እምነት፣ ለመገረዝ ወይም ለመጠመቅ አይመጣም፡፡ ይህ ሕግን መተላለፍ ነው፡፡ እንደ ተማሪ ከጌታ ሥር ቁጭ ብሎ ለመማር ሳይኾን የጌታን አሳብ ለማወቅና በጎዳናውም ይጓዝ ዘንድ ነው፡፡

የአይሁድ መምህር ‹‹ረቢ›› ብሎ ጌታን መጥራት ቀላል ነገር አይደለም፡፡ የሕዝብ አለቃ ነኝ ብሎ የሚያስብ ሰው በትሕትና ረቢ ብሎ ሲናገር መመልከት በእርግጥም ያስደንቃል፡፡ ኒቆዲሞስ ጌታን የጠየቀው ነፍሱ ስለምትድንበት ኹኔታ ብቻ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ ስለ ጌታ አንድ ነገር ያውቃል፤ ጌታ በአይሁድ ምሁራን ወይም በታወቀ የአይሁድ ትምህርት ቤት ገብቶ የተማረ አይደለም፡፡ ትምህርቱ ከሰማይ ነው፡፡ ጌታ የያዘው የእውነትን ኀይል እንጂ የሰይፍን ኀይል አለመኾኑን ተገነዘበ፡፡ ከምድራዊው ጥበብ ባለፈ ፍጹም መለኮታዊ ጥበብ እንደሚናገርም ተገንዝቧል፡፡ የሚያደርገው ምልክት በመለኮታዊ ኀይል መኾኑን አስተውሏል፡፡

በጣም አስደናቂው ንግግሩ ደግሞ ‹‹መምህር ሆይከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን›› የሚለው ነው፡፡ ምናልባት ከእርሱ ጋር ሌሎች ሰዎች እንዳሉ ያመለክታል፤ ወይም ፈሪሳውያንን ወክሎ እየተናገረ ይኾናል፡፡ ምክንያቱም ምግባቸውም መጠጣቸውም ወሬአቸውም ክርስቶስ ኾኗልና፡፡ ከእነርሱ መካከል ኒቆዲሞስ የሚያምነውን እምነት የሚያምኑ ፈሪሳውያን ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ከእነርሱ መካከል ጌታን በግልጥ ወይም በስውር ሊያገኘው የፈለገ ወገን የለም፡፡

ይቆየን

ኒቆዲሞስ እና አዲሱ ልደት – የመጀመሪያ ክፍል

በዲ/ ታደለ ፈንታው

መጋቢት ፲፯ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ሦስት ብዙ አሕዛብ ወደ ክርስትና እምነት የተቀላቀሉበትን ምሥጢር የሚያስረዳ ምዕራፍ ነው፡፡ ድኅነትን በትጋት ለመፈጸም የሚታገሉ ክርስቲያኖች ይኼንን ምዕራፍ ሲያነቡ ከኒቆዲሞስ ጎን መቆማቸው የሚያጠራጥር አይኾንም፤ ከጌታ ጋር ምሥጢራዊ የኾነ ውይይትን መቀጠል ይፈልጋሉ፡፡ በሕይወታቸው የተከፈተ የአዲስ ኪዳን መንገድ እንዳለ ሲገነዘቡም ጌታን ይከተላሉ፡፡ ከእርሱ ጋር ከቅዱስ መንፈሱም ጋር አንድ ይኾናሉ፡፡ አዲስ ልደትን ያገኛሉ፤ ይህም በጥምቀት የሚገኝ የሥላሴ ልጅነት ነው፡፡

ይህ ምዕራፍ መልካም ሥነ ምግባር በነበረው ፈሪሳዊ ሕያውና መንፈሳዊ በኾነው ምንጭ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መካከል የነበረውን ውይይት ይዟል፡፡ ኒቆዲሞስ እንደ ፈሪሳዊ በአይሁድ ትውፊትና በብሉይ ኪዳን ትምህርት የታጠቀ ነው፡፡ ጠንካራ ሞራል እንደ ገነባ ሰው ወደ ጽድቅ የሚወስደውን ትውፊት የሚያውቅ ሰው በፈቃዱ መታዘዝ እንዳለበት የሚያምን ነው፡፡ ይህ የሚኾነው ደግሞ ሰው በሚያደርገው ጠንካራ ትግል እንደ ኾነ ያምናል፡፡ ይህ ትግል በሰው በጎ ፈቃድና ሕጉን በደረቁ በመተርጐም እንደሚገኝ ያምናል፡፡ ኒቆዲሞስ ጌታን ያገኘው ሕጉን የሚቃወም ኾኖ ሳይኾን ሕጉን በጥልቀት የሚተረጕም አይሁዳዊ ኾኖ ነው፡፡ ስለዚህም ነው ወደ መድኀኒታችን ከተሳቡ ወገኖች መካከል ወንጌላዊው የኒቆዲሞስን ጉዳይ በትኩረት የጻፈው፡፡

ወንጌላዊው እንደ ነገረን ኒቆዲሞስ ጌታ ከእግዚአብሔር እንደ መጣ አወቀ፤ አመነም (ዮሐ. ፫፥፪)፡፡ ነገር ግን ምናልባት ኒቆዲሞስ ጌታ ትምህርቱን ማኅበራዊ ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚያስተምር ሊያስብ ይችላል፡፡ የሕጉን ጥሬ ትርጕም እንጂ ፍካሬያዊ ትርጕም አልተገነዘበም፡፡ የአይሁድን ኑሮ ሊያሻሽል የመጣ ነው ብሎም ሊያስብ ይችላል፡፡ የኒቆዲሞስ አመለካከቱና ልምዱ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለውን አዲስ ሕይወት ለመቀበል አያበቃውም፡፡ በአዲሱ ልደት የሚገኘው የጸጋ ልጅነት አይገነዘበውም፡፡ የመንፈሳዊው ሕግ ጥቅም ግን ይህ ነበር፡፡ ሥጋዊውን ከመንፈሳዊ ምድራዊውን ከሰማያዊ መለየት ያስችላል፡፡ ጌታ የኒቆዲሞስን አሳቡን፣ ልቡን፣ ስሜቱን፣ ዕውቀቱን ዂሉ ወደ ሰማያዊ ነገር እንዲያሸጋግረው ፈቀደ፡፡ ይህን በማድረግ ከሰማይ የወረደው እርሱም በሰማይ የነበረው እንደ ኾነ ይገነዘባል፡፡ ወደ ሰማይ መውጣትም የሚቻለው እርሱ ነው፡፡ በእርሱ የሚያምኑ ወገኖችን ከፍ ከፍ የሚያደርጋቸው፤ ከፍ ያለውንም ነገር እንዲመለከቱ የሚያደርጋቸው እርሱ ነው፡፡

የኒቆዲሞስና የጌታ ግንኙነት ትኩረታችንን ወደ ክርስቶስ እንድናደርግ ያደርገናል፡፡ ለእያንዳንዱ የሰው ልጅ ነፍስ መዳን ምን ያህል ትኩረት እንደሚሰጥ ከእያንዳንዱም ወገን ጋር ሲነጋገር ያለውን ትሕትናም እንገነዘባለን፡፡ ከኒቆዲሞስ ጋር ሲወያይ የአዲሱን ልደት ጠባይ ዘርዝሯል፡፡ ኒቆዲሞስ የእግዚአብሔርን መንግሥት ማወቅ ፈልጓል፤ ይኼንን መንግሥት ለማወቅ በውኃና በመንፈስ ይጠመቅ ዘንድ ግድ መኾኑን ያስረዳል፡፡ ይህ ኹኔታ አስፈላጊ ነው፤ ክርስቲያን ዘወትር የእግዚአብሔር ልጅ ኾኖ እንዲኖር ያስችለዋልና ይጠመቅ ዘንድ የግድ ነው፤ በመንፈሱም እንዲኖር ያደርገዋል፡፡ በዚህ ምዕራፍ ጌታ ከምድራዊ ነገሮች ያወጣና አሳባችን ሰማያዊ በኾነው ጉዳይ እንዲያዝ ያደርጋል፡፡ ይህንን ማድረግ የምንችለው ከሰማያዊው ጋር ኅብረት ስንፈጥር መኾኑን ይነግረናል፡፡

ጌታ ጥምቀቱን ከመስቀሉ ጋር አያይዞታል፡፡ እግዚአብሔር አብ ለሰው ልጆች ዂሉ ያለውን እውነተኛ ፍቅር የገለጠበት፣ የባሕርይ ልጁን ወደ ዓለም በመላክ ዓለሙ ዘላለማዊ ሕይወትን ያገኝ ዘንድ ልጁ ከፍ ከፍ ያለበትም የነገሠበትም ዙፋኑ ነውና፡፡ አዲሱን ልደትን በማንሣት ጌታ ከፍርሃት ባርነት አውጥቶ መለኮታዊ የኾነውን ብርሃን እንድንመለከት ያደርገናል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ጌታ ሲጠመቅ የነበረውን ኹኔታ ሲነግረን ለሚያምኑ ወገኖች ያለውን አንድምታም ሲገልጽ ደስታው ፍጹም ነበር፡፡ ወንጌላዊው ዮሐንስ በወንጌሉ ከሰጠው ትምህርት መካከል ከምዕራፍ ፩ – ፫ ስለ አዲሱ ልደት ማብራሪያ ይሰጣል፡፡

ከፈሪሳውያንም ወገን የአይሁድ አለቃ የኾነ ኒቆዲሞስ የሚባል አንደ ሰው ነበረ፡፡ ‹ኒቆዲሞስ› የአይሁድ ስም ሲኾን ትርጓሜው ‹ሕዝብን ያሸነፈ› ማለት ነው፡፡ ኒቆዲሞስ የአይሁድ አካል የሰንሃድሪን አይሁድ ሸንጎም አባል ነው፡፡ የክርስቶስ መለኮታዊ ጥሪ መላውን የሰው ልጆች ያካተተ ነው፡፡ የመደብ ልዩነት አልተደረገበትም፡፡ ነገር ግን በከፍተኛ ሓላፊነት ከነበሩ የመንግሥትና የሃይማኖት መሪዎች መካከል ለዚህ ጥሪ መልስ የሰጡ ጥቂቶች ነበሩ፡፡ ከፈሪሳውያን መካከል እጅግ ጥቂቶች፤ ከጥቂቶቹ አንዱ ኒቆዲሞስ ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ በአይሁድ ሸንጎ የተከበረ ሰው ነበረ፡፡ ጌታ ግን ይህችን አንዲት ለመዳን የወሰነች ነፍስ ዝቅ አላደረጋትም፤ ሞትን የተቀበለው ስለእያንዳንዱ ነፍስ ነውና፡፡

ፈሪሳውያን ለመለኮታዊው እውነት የሰጡት መልስ ጥላቻና የዐመፅ መንፈስን የተመላ ነው፡፡ ነገር ግን ከተማሩ አይሁድ መካከል ጌታን ለማግኘት የቸኮሉ በሩም ተከፍቶ የጠበቃቸው ጥቂቶች ነበሩ፡፡ የእግዚአብሔር ጸጋ በተማሩም ባልተማሩም ወገኖች ላይ ይሠራል፡፡ በተራውም ሕዝብ፣ በአለቃውም፣ በየዋሁም፣ በዐመፀኛውም ላይ ይሠራል፡፡ ኒቆዲሞስ ደረጃው ከዐመፀኞቹ ቢኾንም ወደ ጌታ መጣ፤ ጊዜው ሲደርስ የቻለውን ያህል ይጠይቅና ያውቅ ዘንድ ሞከረ፡፡ በጥያቄ ላይ እንደ ነበረ ታሪኩ ያስረዳል፡፡ ጊዜው ሲደርስ ለደቀ መዛሙርቱ ያልተቻለው ለዚህ ሰው ተቻለ፡፡ ከጲላጦስ አስፈቀዶ አዲስ ባሳነጸው መቃብር ላይ እንዲቀበር አደረገ፡፡

ቤን ረጊን በአይሁድ ታሪክ መጽሐፍ ስለ ኒቆዲሞስ ሲናገር ይህ ሰው በጣም ሀብታም ከመሆኑ የተነሣ በኢየሩሳሌም የነበሩ ብዙዎችን ለብዙ ዓመታት ይረዳ እንደ ነበር ይናገራል፡፡ እርሱም በሌሊት ወደ ኢየሱስ መጥቶ ‹‹መምህር ሆይ፥ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከኾነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለም፡፡ መምህርነህ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን›› አለው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ኒቆዲሞስን በብዙ ቦታዎች ጠርቶታል፡፡ ጌታን ማታ ማታ ይጐበኝ እንደ ነበረም ገልጧል፤ ይህ ኹኔታ ሦስት ጊዜ ያህል ተጠቅሷል (ዮሐ. ፫፥፪፤ ፱፥፴፱፤ ፯፥፶)፡፡

ኒቆዲሞስ ስለ ምን ወደ ጌታ በምሽት መጣ

የመጀመሪያው ምክንያት ጌታችን በአደባባይ የሚያስተምረውን ትምህርት ከሰዎች መስማቱ ብቻውን በቂ አይደለም፡፡ ከምንም በላይ ጌታ በአደባባይ የሚያደርገውን ምልክት በሕዝብ መካከል በግልጽ መጥቶ ማየት አልወደደም፡፡ ድኅነትና ነፍስን የሚመለከቱ ጉዳዮችን በጥሞና ከጌታ ሥር ቁጭ ብሎ መነጋገር ልቡ ፈቅዷል፡፡ ‹‹ቃሌስ በቅንነት ለሚሔድ በጎ አያደርግምን?›› (ሚክ. ፪፥፯) ተብሎ እንደ ተጻፈ ኒቆዲሞስ የቅንነትን መንገድ መርጦ ወደ ጌታ ቀርቧል፡፡ ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር ይነጋገር ዘንድ ወደደ፡፡ ጌታ እንኳን ከሕዝቡና ከደቀ መዛሙርቱ ተለይቶ ከአብ ጋር ሲነጋገር የሚያድርበት ጊዜ ነበር፡፡ እኛማ ሌሊቱን በሙሉ ከእግዚአብሔር ጋር እንደምን መነጋገር ይገባን ይኾን? በተለይ በሌሊት ዂሉንም ነገር ትተን ከጌታ ጋር መገናኘት ይጠበቅብናል፡፡ አዲሱን ሕይወትና የዚህን ሕይወት ባሕርይ፣ በዚህ ሕይወትም ውስጥ ካለች ከመንፈስ ኅብረት ተካፋዮች እንኾን ዘንድ ይገባናል፡፡

ሁለተኛው ምክንያት ምናልባት ጥበብን ለመማር የማታው ጊዜ የተሻለ እንደ ኾነ በመረዳቱ ነው፡፡ ጌታ ቀን ቀን ሕዝቡን ሲያስተምር እንደሚውል ያውቃል፡፡ ስለዚህም ኒቆዲሞስ ጌታን በምሽት ጠብቆ ለማግኘትና ለማግኘትና የድኅነትን ትምህርት ለመማር ወደደ፡፡

ሦስተኛው ምክንያት አንዳንድ ምልክቶችን ከተመለከተ በኋላ ጌታን ለማግኘት የመጀመሪያውን ዕድል በምሽት ማግኘቱ ነው፡፡ ዂሉም ሰው ሲተኛ ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር መንፈሳዊ ምሽትን ማሳለፍ ፈልጓል፡፡ ምናልባትም እንዲህ ዓይነት ዕድል ወደፊት ሊገጥመው እንደማይችል ሥጋት አድሮበት ሊኾን ይችላል፡፡

አራተኛው እንደ ነቢዩ ዳዊት ምሳሌውን ሊከተል ፈልጎ ነው፡፡ ዳዊት ሌሊቱን ለምስጋና ይጠቀምበት ነበርና (መዝ. ፴፮፥፮፤ ፻፲፱፥፻፵፰)፡፡

ይቆየን

የጌታችን ልደት እና የመላእክት አገልግሎት

በዲያቆን አለልኝ ጥሩዬ

ታኅሣሥ ፳፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን በዓለም ላይ ሠልጥኖ የነበረውን ጨለማ ያስወግድ ዘንድ እግዚአብሔር አምላክ ሰው ኾነ፡፡ ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው አማናዊው ብርሃን ፀሐየ ጽድቅ ክርስቶስ በሥጋ ተገለጠ፡፡ ‹‹ብርሃን ዘበአማን ዘያበርህ ለኵሉ ሰብእ ለእለ ይነብሩ ውስተ ዓለም፤ በጨለማ ውስጥ ለሚኖር ሕዝብ ታላቅ ብርሃን ወጣላቸው›› እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴው (ኢሳ. ፱፥፪)፡፡ ቀዳሚ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ሰው በኾነ ጊዜም ቅዱሳን መላእክት በቤተ ልሔም ተገኝተዋል፡፡ ይህንም ቅዱስ ሉቃስ ‹‹ወግብተ መጽኡ ብዙኃን ሐራ ሰማይ፤ የሰማይ መላእክት በድንገት መጡ›› በማለት ገልጾታል (ሉቃ. ፪፥፲፫)፡፡ በድንገት መባሉም አመጣጣቸው ግሩም በመኾኑ ነው፡፡ ቅዱሳን መላእክት ቀድሞ አመጣጣቸው ጻድቃንን ለመርዳት፣ ሰማዕታትን ከስለት ለመታደግ፣ የተቸገረውን ለማጽናት ነበር፡፡

ዛሬ ግን ስለ ሰው ፍቅር ከሰማይ የወረደውን፣ በጎል (በበረት) የተጣለውን፣ በጨርቅ የተጠቀለለውን አምላክ ከሰው ልጅ ጋር በአንድነት ለማመስገን መጡ፡፡ ‹‹ዮም አሐደ መርዔተ ኮኑ መላእክት ወሰብእ ከመ ይሰብሕዎ ለክርስቶስ ንጉሥ፤ ሰውና መላእክት፣ ንጉሥ ክርስቶስን ያመሰግኑ ዘንድ ተባበሩ›› እንዲል፡፡ መላእክት በተፈጥሯቸው የማይሞቱ (ሕያዋን) ሲኾኑ ሰው ደግሞ ሟች ነው፤ ሞት ይስማማዋል፡፡ በጌታችን ልደት ግን መላእክትና የሰው ልጆች በአንድ ማኅበር፣ በአንድ ቃል ‹‹ስብሐት ለእግዚአብሔር›› እያሉ እግዚአብሔርን አመስግነዋል፡፡ በአዳም ኀጢአት ምክንያት ፈርሶ የነበረው የመላእክትና የሰው ልጆች ማኅበር ከተቋረጠ ከብዙ ዘመን በኋላ በኢየሱስ ክርስቶስ ልደት እንደ ገና ተጀመረ፡፡ ይህ የምስጋና ኅብረትም ምድር እንደ ልብስ ተጠቅልላ ስታልፍ ወደ ፊት በምትመጣዋ በአዲሲቷ ዓለም፣ በአዲሱ ሰማይ፣ በአዲሱ ቤተ መቅደስ ይቀጥላል (ራእ. ፳፩፥፩-፬)፡፡

አንድነታችን እንደማያቋርጥና በሰማይም እንደሚቀጥል አረጋዊ መንፈሳዊ ሲገልጥም ‹‹እሉሂ ወእልክቱሂ በአሐዱ ኁባሬ አልቦ ማዕከሌነ ወማዕከሌሆሙ፤ በእኛ በደቂቀ አዳም እና በቅዱሳን መላእክት መካከል ልዩነት የለም›› ይላል፡፡ ይህም የኾነው በጌታችን መወለድ ምክንያት ነው፡፡ በጌታችን ልደት ምክንያት እኛም ዳግመኛ ተወለድን፡፡ የጌታችን ልደት የእኛም የክርስቲያኖች ዅሉ ልደት ነው፡፡ ከሦስቱ የቀጰዶቅያ አባቶች (The three Cappadocian Fathers) አንዱ፣ ታላቁ የቤተ ክርስቲያን አባት ሊቁ ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ ይህን ምሥጢር ሲገልጥ ‹‹The nativity of Christ is the birthday of the whole human race – የክርስቶስ ልደት የመላው ሰው የልደት ቀን ነው›› ሲል መስክሯል (Hyman of praise to the mother of God)፡፡

ሊቃውንት እንዳስተማሩን እግዚአብሔር አምላክ ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ዓለምን ያዳነበት ጥበቡ ይበልጣል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበት እና ዓለምን ያዳነበት ምሥጢር ከምሥጢራት ዅሉ በላይ ነው፡፡ ይህን ምሥጢር ከማድነቅ ሌላ ሊናገሩት አይቻልም፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም በመገረም ይህን ጥበብ እንዲህ ሲል ይገልጸዋል፤ ‹‹ምን እላለሁ? ምንስ እናገራለሁ? ከዘመን አስቀድሞ የነበረው እርሱ ሕፃን ኾኗልና፡፡ እኔ ፈጽሜ አደንቃለሁ፡፡ ከሰማየ ሰማያት በላይ የሚኾን፣ በዘለዓለማዊ ዙፋን የሚኖር እርሱ በበረት ተጣለ፡፡ ከሥጋዌ አስቀድሞ አይዳሰስ የነበረ አንዱ እርሱ በምድራውያን እጅ ተዳሰሰ፡፡ ኀጢአትን የሚያስተሰርይ እርሱን በጨርቅ ጠቀለሉት፡፡ ይህን ወዷልና፤›› (ሃይማኖተ አበው ዘዮሐንስ አፈ ወርቅ፣ ፷፮፥፲፯)፡፡ ቅዱስ ዲዮስቆሮስም በቅዳሴው የእግዚአብሔርን ሰው የመኾን ምሥጢር እንዲህ በማለት ገልጾታል፤ ‹‹በጐለ እንስሳ ተወድየ አሞኀ ንግሡ ተወፈየ ወከመ ሕፃናት በከየ እንዘ ይስእል እምአጥባተ እሙ ሲሳየ፤ በእንስሳት በረት ተጨመረ፡፡ የንጉሡንም እጅ መንሻ ተቀበለ፡፡ ከእናቱ ጡቶች ምግብን እየለመነ እንደ ሕፃናት አለቀሰ፤›› (ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ ቍ. ፲፯)፡፡

በዚህ ታላቅ በዓላችን የምናደንቀው ሌላው ምሥጢር እግዚአብሔር ወልድ በቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን፣ በኅቱም ድንግልና ተፀንሶ በኅቱም ድንግልና የመወለዱ ረቂቅ ምሥጢር ነው፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይህን ድንቅ የሥጋዌ ምሥጢር ግሩም፣ ዕፁብ እያሉ ያደንቁታል፡፡ ሐዋርያውያን አበውን ተከትለው ከተነሡ የቤተ ክርስቲያን ጠባቆች (Apologists) መካከል አንዱ ቅዱስ ሄሬኔዎስም ፩ኛ የእመቤታችን ዘለዓለማዊ ድንግልና፣ ፪ኛ ድንግል ማርያም አማኑኤል ጌታን መውለዷ እና ፫ኛ የማይሞተው አምላክ መሞት በእግዚአብሔር የዝምታ ሸማ የተጠቀለሉ ሦስት ምሥጢሮች መኾናቸውን ይናገራል፡፡ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ የተባለው አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም በመጸሐፈ አርጋኖን ድርሰቱ ይህን ድንቅ የተዋሕዶ ምሥጢር በሚከተለው መልኩ ይገልጠዋል፤

‹‹ሦስቱን ደጆች ያልከፈተ የአብን ልጅ ጥበብ አደንቃለሁ፤ ያለ መለወጥ በኅቱም ድንግልና በመወለዱ፣ የመቃብሩን ደጅ ሳይከፍት በመነሣቱ፣ ደቀ መዝሙርቱ ተሰብስበው ወዳሉበት ቤት በተዘጋ ቤት በመግባቱ እና በሩን ሳይከፍት በመውጣቱ ስለነዚህም ሦስት ደጆች ልቤ አደነቀች፡፡ ከሁለቱ ይልቅ የመጀመሪያው እጅግ ያስደንቀኛል፡፡ ምክንያቱም ሁለቱን ከዚህ በፊት በመጽሐፍ ቅዱስ አውቃቸዋለሁ፡፡ የመቃብሩን ደጅ የሚመስለው ነገር አለ (ዮሐ. ፳፥፲፱)፡፡ ብልጣሶር የተባለ ዳንኤልን በአንበሶች ጕድጓድ ውስጥ በጣሉት ጊዜ ጕድጓዱን በታላቅ መዝጊያ ዘጉት፡፡ ዳንኤልም በረሃብ እንደ ተጨነቀ ልዑል እግዚአብሔር ባየ ጊዜ መልአኩን ወደ ነቢዩ ዕንባቆም ላከ (ዳን. ፮፥፲፮-፲፯)፡፡ በራሱም ፀጕር አንሥቶ ተሸክሞ ወስዶ ዳንኤል ወዳለበት ጕድጓድ አገባው፡፡ ዳንኤልና ዕንባቆም እንጀራውንና ንፍሮውን በልተው እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ ዕንባቆምም ደጅ ተዘግቶ ሳለ ወጣ፡፡ ስለ ቤቱ ደጅም የሚመስል ነገር አለ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ ወርዶ ጴጥሮስን ከግዞት ቤት እንዳወጣው በሐዋርያት ሥራ ተጽፏል፡፡ ጴጥሮስንም ካወጣው በኋላ ደጁ ተቈልፎ ዘበኞች በዅሉ ወገን ይጠብቁ ነበር (ሐዋ. ፲፪፥፮)፡፡  ለእነዚህ ለሁለቱ ደጆች ለቅዱሳን የተገኘውን ምክንያት አገኘሁ፡፡ ስለ ድንግልናሽ ደጅ እጠናለሁ፤ ግን ምክንያት አላገኘሁም፡፡ በድንግልና የኖረች ሴትም አላየሁም፡፡ እንደዚህ ዓይነት ነገር ኾኖ አያውቅም፡፡ ኢኮነ እምቅድመ ዝ ወኢኮነ እምድኅረ ዝ – ከዚህ በፊት አልተደረገም፤ ከዚህ በኋላም አይደረግም፤›› (አርጋኖን ዘቀዳሚት)፡፡

በአጠቃላይ በዓለ ልደት፣ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል እርቅ የተፈጸመበት በዓላችን ነው፡፡ ለሞት ከመገዛት የዳንበት፤ ጨለማው ተወግዶልን የብርሃን ልጆች የኾንበት፤ የእባብ ራስ የተቀጠቀጠበት፤ ከምድር ወደ ሰማይ ያረግንበትና ከመላእክት ጋር ኾነን ለእግዚአብሔር ምስጋና ያቀረብንበት፤ ከነቢያት ኅብረት ጋር አንድ የኾንበት በዓል ነው፡፡ ድንቅ የተዋሕዶ ምሥጢር የተፈጸመበትን ይህን ልዩ በዓል በመንፈሳዊ ሥርዓት ማክበር ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር፡፡

ለብርሃነ ልደቱ መዘጋጀት

በዲያቆ ዘላለም ቻላቸው

ታኅሣሥ ፳፯ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

አዳም የድኅነት ቃል ኪዳንን ከእግዚአብሔር ዘንድ ከተቀበለ ከአምስት ሺሕ ዓመታት በኋላ የአዳምን በደል ካሣ ከፍሎ ከራሱ ጋር ሊያስታርቀው እግዚአብሔር ወልድ ወደዚህ ዓለም መጥቶ በተዋሕዶ ሰው ኾነ፡፡ እግዚአብሔር ሰው ከመኾኑ አስቀድሞ የነበሩ የቃል ኪዳን ዓመታት አምላካችን የፈጸመዉን የድኅነት ሥራ (ሥጋዌ፣ ሞት፣ ትንሣኤ …) የሰው ልጆች እንዲረዱ ለማስቻል ዝግጅት የተደረገባቸው ዘመናት ናቸው፡፡ በእነዚህ ዘመናት እግዚአብሔር የራሱ የኾኑ ሕዝቦችን እና ሰዎችን በመምረጥና ከእነርሱ ጋር ቃል ኪዳን በመግባት፣ ለእነዚህ ሕዝቦች ተአምራትን በማድረግና ከጠላቶቻቸው በማዳን፣ ከዚህም ባሻገር ነቢያቱን ልኮ ሕዝቡን በማስተማር፣ ትንቢት በማስነገርና ተስፋ በመስጠት (በማጽናናት)፣ ሱባኤም በማስቈጠር አምላነቱንና ዓለምን ለማዳን ያቀደውን ዕቅድ ቀስ በቀስ፣ በጥቂት በጥቂቱ ገልጧል፡፡ በየዘመኑ የተነሡ ነቢያትም ምንም እንኳን አምላክ ይህን ዓለም እንዴት እንደሚያድነው በግልጽ ባይረዱትም እግዚአብሔር ዓለሙን የሚያድንበትን ቀን እንዲያቀርበው እንዲህ እያሉ ይማፀኑ ነበር፤ ‹‹አቤቱ ሰማዮችን ዝቅ ዝቅ አድርጋቸው፤ ውረድም … እጅህን ከአርያም ላክ …›› (መዝ. ፻፵፫፥፯፤ ኢሳ. ፷፬፥፩)፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ በሁለተኛው መልእክቱ እንደ ገለገጸልን በመንፈስ ቅዱስ እየተመሩ ስለሚመጣው ነገር ዅሉ ትንቢት ተናግረዋል፤ ሱባዔ ቈጥረዋል፤ ሕዝቡም የጌታን ማዳን በተስፋ እንዲጠብቅ አስተምረዋል፡፡ ጌታ ሰው ኾኖ የተወለደው ከዚህ ዅሉ ዝግጅት በኋላ ነው፡፡ የአዳኙ መሲሕ የክርስቶስ መወለድ በጉጉት ይጠበቅ ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ከእስራኤል መካከል ቅን የነበሩትና በእግዚአብሔር መንገድ የተጓዙት ‹‹መሲሑን አገኘነው … ሙሴ በሕግ መጻሕፍት፣ ነቢያትም ስለ እርሱ የጻፉለትን የናዝሬቱን ኢየሱስን አገኘነው፤›› እያሉ ተከትለውታል (ዮሐ. ፩፥፵፩-፵፭)፡፡ እንግዲህ ይህ ታሪክ ከተፈጸመ ጌታችንም ከተወለደ እነሆ ፳፻፲ ዓመታት ተቈጥረዋል፡፡ እኛም የተደረገውን ዅሉ በትውፊት ተቀብለን በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ተሳትፈን በዚህ በድኅነት ጉዞ የተሰጡንን ጸጋዎች ተካፍለን ክርስቲያኖች ኾነናል፡፡

‹‹በሞቱም እንመስለው ዘንድ ከእርሱ ጋር በጥምቀት ተቀበርን፤ እርሱ ክርስቶስ በአባቱ ጌትነት ከሙታን እንደ ተነሣ እኛም እንደ እርሱሐዲስ ሕይወት እንኖራለን፤›› (ሮሜ. ፮፥፬) በማለት ቅዱስ ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ እንዳስተማረው ክርስትና፣ በጥምቀታችን ሞተን እንደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞት ተነሥተን በትንሣኤው ብርሃን በአዲስ ሕይወት የምንመላለስበት፤ የእግዚአብሔርን ፍቅር እየቀመስን፣ ያደረገልንን ዅሉ እያደነቅን፣ ጸጋውን ዕለት ዕለት እየተቀበልን የምንኖረው ኑሮ ነው፡፡ በዚህ ክርስቲያዊ ሕይወት ስንኖር አምላካችን ለእኛ ብሎ የፈጸመውን የማዳን ሥራ (ልደቱን፣ ጥምቀቱን፣ ጾሙን፣ መከራውን፣ ስቅለቱን፣ ትንሣኤዉንና ዕርገቱን እንደዚሁም ዳግም ምጽአቱን) ዘወትር ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ በአጠቃላይ ሕይወታችን ጌታችን የፈጸመዉን ተግባር ዅሉ በማስታወስ፣ በማሰብ እና በመካፈል ላይ የተመሠረተ መኾን ይኖርበታል፡፡ ስለዚህም ቤተ ክርስቲያን በነገረ ድኅነት ውስጥ ትልቅ ቦታ ያላቸውን የጌታችን ድርጊቶች ቢያንስ በዓመት አንድ ጊዜ እንድናስባቸው አድርጋለች፡፡ የልደትን፣ የጥምቀትን፣ የስቅለትን፣ የትንሣኤን፣ የዕርገትን … በዓላት የማክበራችን ዋናው ምክንያትም ይኸው ነው፡፡

ዳሩ ግን በጥምቀት የተቀበልነውን አዲስ ሰውነት በኀጢአት በማቆሸሻችንና ራሳችንን ከጸጋ እግዚአብሔር በማራቃችን፣ እንደዚሁም በልዩ ልዩ ሥጋዊ ጉዳዮች ተጠምደን በወከባ በመኖራችን ይህን ማድረግ ይክብድብናል፡፡ እነዚህን በዓላት ስናከብር ከሚያስጨንቁንና ሕሊናችንን ከሞሉት ሥጋዊ ጉዳዮች ተመልሰን በአንድ ጊዜ ወደ መንፈሳዊ ዐሳብና ተመስጦ መምጣት ስለምንቸገር ቤተ ክርስቲያን ከበዓላቱ በፊት የዝግጅት፣ የማንቂያ ጊዜያት እና አጽዋማት እንዲኖሩም አድርጋለች፡፡ በእነዚህ ወቅቶች ሕሊናችንን ቀስ በቀስ ወደ መንፈሳዊው ዐሳብ እና ወደ በዓሉ ጉዳይ ተመልሶና በዓሉን በናፍቆት ጠብቀን በተገቢው ሥርዓት እንድናከብረውም ታዝዛለች፡፡ በዚህም ምክንያት አብዛኞቹ በዓላት ከመከበራቸው በፊት አጽዋማት ይኖራሉ፤ ሥጋ ወደሙን ከመቀበላችንም በፊት እንጾማለን፡፡ ሌሎቹም ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ከመፈጸማቸው በፊት የጾምና የዝግጅት ወቅቶችን ማሳለፍ ጥንታዊ የቤተ ክርስቲያን ትውፊት ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን የጌታችንና የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል እንዲከበር ያደረገችው ከእነዚህ ዘወትር ልናስባቸው ከሚገቡ ነገሮች አንዱ የኾነዉን ብርሃኑንና ዘወትር ልናየው የሚገባውን የጌታችንን ልደትን ቢያንስ በዓመት አንድ ጊዜ በተመስጦ እንድናስበውና ብርሃኑን እንድናየው ነው፡፡ ይህችን በዓመት አንድ ጊዜ የምትመጣዋን በዓልም ቢኾን ከማክበራችን በፊት ዐርባ ሦስት ቀናትን በመጾም እንዘጋጃለን፡፡ በመጾም ብቻ ሳይኾን እነዚህ ዐርባ ሦስት ቀናት ተከፋፍለው የልደት በዓልን በተገቢው መንገድ እንድናከብር የሚያዘጋጁ ትምህርቶችን እንማርባቸዋለን፡፡ በተለይም ከልደት በዓል በፊት ያሉት ሦስት ሳምንታት ይህ ዓላማ አላቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን የጌታችንን የልደቱን ብርሃን ለማየት እንዘጋጅ ዘንድ እነዚህን ሦስት ሳምንታት የጌታችንን ልደት በናፍቆት በመጠበቅ እንደ ብሉይ ኪዳን ሰዎች ኾነን እንድናሳልፍ ታደርጋለች፡፡

በእነዚህ ሳምንታት (በተለይም በእሑዶቹ) የብሉይ ኪዳን ነቢያት የአዳኙን መምጣትና የጌታን ቀን መገለጥ በመናፈቅ ስላሳለፏቸው ጊዜያት ደጋግመን በመማር እነዚያን የጨለማ ዘመናት እንድናስታውስና እኛም በእነርሱ መንፈስ ተቃኝተን ብርሃነ ልደቱን ለማየት እንናፍቃለን፤ በዓሉን ለማክበርም እንዘጋጃለን፡፡ በዓሉን የምናከብረውም እንዳለፈ ታሪክ ለማሰብ አይደለም፡፡ ልክ በዚያች በልደቱ ቀን ከሰብአ ሰገልና ከእረኞች ጋር እንደ ተገኘን ኾነን እናከብረዋለን እንጂ፡፡ ለዚህም ነው የልደትን በዓል ስናከብር ‹‹ዮም ፍስሐ ኮነ በእንተ ልደቱ ለክርስቶስ፤ ዛሬ በክርስቶስ ልደት ደስታ ሐሤት ኾነ›› እያልን የምናመሰግነው፡፡ ‹‹ዮም፣ ዛሬ›› ማለትም በዓሉ የልደት መታሰቢያ ብቻ ሳይኾን በዚያ በልደት ቀን እንደ ነበርን አድርገን የምከብረው በዓል መኾኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ከልደተ በዓል በፊት ያሉት ሦስቱ የጾመ ነቢያት ሳምንታት ስብከት፣ ብርሃን እና ኖላዊ ተብለው ይጠራሉ፡፡ እነዚህ ሳምንታት፣ ነቢያቱ፣ አምላክ ይህን ዓለም እንዲያድን ያላቸውን ናፍቆት የገለጡባቸውና ነገረ ድኅነትን አስመልክተው ያስተማሩባቸው ሳምንታት ናቸው፡፡

፩. ስብከት

ስብከት ማለት ማስተማር ማለት ነው፡፡ ይህ ሳምንት ከሙሴ ጀምሮ የነበሩ ነቢያት በሙሉ አዳኝ (መሲሕ) እንደሚመጣ ማስተማራቸው፣ ጌታችንም ነቢያት ይመጣል ብለው ያስተማሩለት አምላክ እርሱ መኾኑን መግለጡ የሚታሰብበት ነው፡፡ ሙሴ ለጊዜው የጌታችን ምሳሌ ለሆነው ለኢያሱ ፍጻሜው ግን ለጌታችን በኾነው ትንቢቱ ‹‹አምላክህ እግዚአብሔር ከወንድሞችህ እንደ እኔ ያለ ነቢይ ያስነሣልሃል፤ እርሱንም ስሙት፤›› ብሎ ለሕዝበ እስራኤል ነግሯቸው ነበር (ዘዳ. ፲፰፥፲፭)፡፡ ጌታችንም ይህ ትንቢት በእርሱ መፈጸሙን ሲያመላክት ‹‹ሙሴ እና ነቢያት ዅሉ ስለ እኔ ይናገራሉ›› እያለ አስተምሯል፡፡ ትንቢቱን ያውቁ የነበሩ በእግዚአብሔር መንገድ የሚጓዙ እስራኤላውያንም በቃሌ አምነው ተከትለውታል፡፡ ሐዋርያትና ሌሎች አባቶችም ከጌታችን ሞትና ትንሣኤ በተለይ የተነገሩትን ትንቢቶች ዅሉ ያውቁ ለነበሩት እስራኤላውያን ያስተማሩት እነዚህን የነቢያት ትምህርቶች እና ትንቢቶች እያጣቀሱ ነበር፡፡

ለምሳሌ ቅዱስ ጴጥሮስ በቤተ መቅደስ እንዲህ ብሎ አስተምሯል፤ ‹‹አሁንም ወንድሞቼ ሆይ፥ አለቆቻችሁ እንዳደረጉ ይህን ባለ ማወቅ እንዳደረጋችሁት አውቃለሁ፡፡ እግዚአብሔር ግን ክርስቶስ መከራን እንዲቀበል በነቢያት ዅሉ አፍ እንደ ተናገረ እንዲሁ ፈጸመ፤›› (ሐዋ. ፫፥፲፯-፲፰)፡፡ በሁለተኛው መልእክቱ ደግሞ ‹‹ወንድሞች ሆይ፥ የቀደሙ ቅዱሳን ነቢያት የተናገሩትን ቃልና ለእኛ ለሐዋርያትም ያዘዘውን የመድኀኒታችንና የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ትእዛዝ ታስቡ ዘንድ … ዕወቁ፤›› (፪ኛ ጴጥ. ፫፥፩-፫)፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በዕብራውያን መልእክቱ ስለ እግዚአብሔር መገለጥ እንዲህ ሲል አስተምሯል፤ ‹‹ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዐይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናገረ፤ በኋላ ዘመን ግን ዅሉን ወራሽ ባደረገው፥ ዅሉን በፈጠረበት በልጁ ነገረን፤›› (ዕብ. ፩፥፩-፪)፡፡

፪. ብርሃን

ነቢያት የአምላክን ማዳን ከጠበቁባቸው እና ከገለጡባቸው መንገዶች አንዱ ብርሃን ነው፡፡ ዘመነ ብሉይ መከራ ሥጋ፣ መከራ ነፍስ የፀናበት፣ ሁሉ ነገር አስጨናቂ የሆነበት፣ ሰው ብርሃን ከሆነው አምላክ ጋር የተራራቀበት ስለነበር ያሉበትን ዘመን «ጨለማ» ብለው በመግለጥ ይህንን ጨለማ የሚያስወግድና ወደ ትክክለኛው መንገድ የሚመራ ብርሃን እንዲመጣ እንዲህ እያሉ ይፀልዩ ነበር፡፡ ‹‹ብርሃንህንና ጽድቅህን ላክ፤ እነርሱም ይምሩኝ፡፡ አቤቱ ወደ መቅደስህ ተራራና ወደ ማደራያህ ይውሰዱኝ፤›› (መዝ. ፵፪፥፫)፡፡ ጌታችንም ወደዚህ ዓለም በመጣ ጊዜ ‹‹እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ›› በማለት ለዚህ ጸሎት ምላሽ ሰጥቷል (ዮሐ. ፰፥፲፪)፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ስለ ብርሃንነቱ መስክረዋል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ስለ ጌታችን ሰው መኾን (ምሥጢረ ሥጋዌ) በተናገረበት በወንጌሉ የመጀመሪያ ክፍል ጌታችንን ብርሃን ብሎታል፡፡ ‹‹ሕይወት በእርሱ ነበረ፤ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረ፡፡ ብርሃንም በጨለማ ያበራል፤ ጨለማም አላሰነፈውም፤›› (ዮሐ. ፩፥፬-፭)፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ጌታችን በሚያንጸባርቅ ብርሃን አምሳል እንደ ተገለጠበት ተናግሯል፡፡ ‹‹እኩል ቀን በኾነ ጊዜ በመንገድ በሔደ ከፀሐይ ይልቅ የሚበራ መብረቅ በእኔና ከእኔ ጋር ይሔዱ በነበሩት ላይ ከሰማይ ሲያንጸባርቅ አየሁ … አንተ የምታሳድደኝ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ አለኝ፤›› (ሐዋ. ፳፮፥፲፫)፡፡

፫. ኖላዊ

ኖላዊ ማለት እረኛ ማለት ነው፡፡ ነቢያቱ ራሳቸውን እና ሕዝበ እስራኤልን ብሎም ዓለምን እረኛቸው እንደ ተዋቸው እና እንደ ተቅበዘበዙ በጎች በመቍጠር እንዲሰበስባቸውና እንዲያሰማራቸው እንዲህ እያሉ ይማጸኑ ነበር፤ ‹‹ዮሴፍን እንደ መንጋ የምትመራ የእስራኤል ጠባቂ (እረኛ) ሆይ፥ አድምጥ፤ በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ ተገለጥ፤›› (መዝ. ፸፱፥፩)፡፡ ጌታችንም ለዚህ ጥያቄ እንዲህ ሲል ምላሽ ሰጥቷል፤ ‹‹ቸር ጠባቂ (እረኛ) እኔ ነኝ፡፡ ቸር ጠባቂ ስለ በጎቹ ነፍሱን ይሰጣል፤›› (ዮሐ. ፲፥፲፩)፡፡

ማጠቃለያ

ዛሬም እኛ በኀጢአት ስንዋከብ ዘወትር ልናየውና ልንመላለስበት የሚገባን ብርሃነ ልደቱ ተሰውሮብናል፣ ከቸር እረኛችን የራቅን የተቅበዘበዝን በጎች ኾነናል፡፡ አንዳንዶቻችን በምናስበው ዐሳብ፣ በምንሠራው ሥራ ውስጥም የአምላክን ሰው የመኾን ምሥጢር ረስተነዋል፡፡ የምንኖረው ልክ ክርስቶስ እንዳልተወለደ ነው፡፡ ስለዚህ ያጣነውን ይህን ጸጋ ለማግኘትና ብርሃነ ልደቱን ለማየት፣ በዚያ ውስጥም ለመመላለስ የክርስትናችንን እና የመንፈሳዊነታችንን ጥልቀት ለመጨመር መሻት አለብን፡፡ ስለዚህ እስኪ እኛም በእነዚህ ሳምንታት የብሉይ ኪዳን ሰዎች የነበሩበትን ኹኔታ እየዘከርን፣ ያለንበትን አኗኗር እየመረመርን፣ ስላጣነው ብርሃን ለማሰብ፣ ያጣነውን መልሰን ለማየትና ለማግኘት እንትጋ፡፡ መጻሕፍትን ለማንበብ፣ በጉዳዩ ላይ በተመስጦ ለማሰብ እና ለመወያየት ጊዜ እንስጥ፡፡ ብርሃነ ልደቱን ለማየት እንዲያበቃንም ‹‹አቤቱ ብርሃንህንና ጽድቅህን ላክ፤ ቸሩ እረኛችን ሆይ፥ ተቅበዝብዘናልና እባክህ ሰብስበን›› እያልን እግዚአብሔርንእንማጸነው፡፡ ሰው ከነኀጢአቱ ወደ እግዚአብሔር ብርሃን ሊቀርብና ብርሃኑን ሊያይ አይቻለውምና በንስሐ ራሳችንን እናጽዳ፡፡ እነዚህን ቤተ ክርስቲያን ያስቀመጠችልንን የዝግጅት ጊዜያት በሚገባ ከተጠቀምን ትርጕም ያለው፣ በሕይወታችንና በመንገዳችን ላይ ለውጥ የሚያመጣ ልዩ የልደት በዓል እናከብራለን፡፡ አምላካችን ብርሃነ ልደቱን እንድንመለከት ቅዱስ ፈቃዱ ይኹንልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ኖላዊ ኄር

በመሪጌታ ባሕረ ጥበባት ሙጬ

ታኅሣሥ ፳፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

‹‹ኖላዊ ኄር›› የሚለው ሐረግ ‹ኖላዊ› እና ‹ኄር› ከሚሉ ሁለት ቃላተ ግእዝ የተዋቀረ ነው፡፡‹ኖላዊ› ማለት ‹እረኛ፣ ጠባቂ› ማለት ሲኾን፣ ‹ኄር› ደግሞ ‹መልካም፣ ቸር ርኅሩኅ፣ አዛኝ› የሚል የአማርኛ ትርጕም አለው፡፡ ስለዚህ ‹ኖላዊ ኄር› ማለት ‹መልካም እረኛ› ማለት ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ቅዱስ ያሬድ ባዘጋጀው ስያሜ መሠረት ከታኅሣሥ ፳፩-፳፯ ያለው ሳምንት ‹ኖላዊ› ተብሎ ይጠራል፡፡ ሳምንቱ ካልጠፉት ዘጠና ዘጠኝ መንጋዎች ይልቅ የጠፋውን አንዱን በግ ፍለጋ የመጣው የእረኞች አለቃ፣ መልካሙ እረኛ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚታሰብበት ሳምንት ነው፡፡ ቸር ጠባቂያችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መልካም እረኝነት የባሕርዩ ነው፡፡ ‹‹አነ ውእቱ ኖላዊ ኄር ዘበአማን፤ እውነተኛ ቸር ጠባቂ እኔ ነኝ፤›› በማለት እንደ ተናገረው (ዮሐ. ፲፥፲፩)፡፡ ጌታችን ይህን መለኮታዊ ሥልጣኑን ለቅዱሳን በጸጋ አድሏቸዋል፡፡ ‹‹… ግልገሎቼን አሰማራ፤ ጠቦቶቼን ጠብቅ፤ በጎቼን አሰማራ›› በማለት ለቅዱስ ጴጥሮስ የሰጠው ሥልጣን ለዚህ ማሳያ ነው (ዮሐ. ፳፩፥፲፭-፲፯)፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ስለ መንጋቸው ራሳቸውን አሳልፈው የሰጡትን ታላላቅ መልካም እረኞችን የመረጣቸው ከበግ እረኝነት ነው፡፡ አምላካችን ለሕዝቡ የሚራራ ቸር ጠባቂ ነውና የጦር ስልት ከሚያውቁ ኃያላን የጦር ዐርበኞች በግ ጥባቂዎችን ለእረኝነት ይመርጣል፡፡ ቀድሞም ለበግ ጥበቃ በትረ ሙሴ እንጂ የጦር መሣሪያ መቼ ያስፈልግና? መልካም እረኞች የበጎችን ጠባይዕ ያውቃሉ፡፡ ለበጎች ምን እንደሚያስፈልጋቸውም ይረዳሉ፡፡ መልካም እረኞች ለበጎች ይራራሉ፤ ስለዚህም ወደ ለመለመ መስክ፣ ወደ ንጹሕ ምንጭ ይመሯቸዋል። የተሰበሩትን ይጥግኗቸዋል፤ የደከሙትንም ያበረቷቸዋል፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም በጎችን ከአንበሳ መንጋጋ፣ ከተኩላ ንጥቂያ ይከላከላሉ፡፡

ከበግ እረኝነት ወደ ታላቅ የሕዝብ መሪነት ከተመረጡት አንዱ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ነው። ለሙሴ በእግዚአብሔር ዓይን ሞገስ ያስገኘለት የቤተ መንግሥት ኃያልነት፤ ዐርበኝነት እና የልዑልነት ማዕረግ ሳይኾን ለእግዚአብሔር መታመኑና ለ፵ ዓመታት በምድያም ተራራዎች፣ በሲና በረሃዎች በሎሌነት ያሳለፈው የበግ እረኝነት ተግባሩ ነበር፡፡ እግዚአብሔር አምላክም ሙሴ ከግብፅ ያመጣውን ትጥቅ አልፈለገውምና ‹‹ኢትቅረብ ዝየ ፍታሕ አሣዕኒከ እምእገሪከ እስመ መካን እንተ አንተ ትቀውም ባቲ ምድር ቅድስት ይእቲ፤ የቆምኽባት ምድር የተቀደሰች ናትና ጫማኽን ከእግርኽ አውጣ፤›› በማለት አዝዞታል (ዘፀ. ፫፥፭)፡፡ የቃል ኪዳኗ ምድር የምትወረሰው በእረኛ በትር እንጅ በልዑላን ሰልፍ አይደለምና፡፡ ሙሴ ከሕፃንነት እስከ ጕልምስና የሚያውቀው የፈርኦንን ሕግ እንጅ ስለ እረኞች አልነበረም፡፡ ለመቶ ዓመታት በባርነት ስቃይና ከሞት ጋር ሲተናነቅ ለኖረ ሕዝብ የፈርኦናውያን ሕግ ምን ለውጥ ያመጣለታል?

ክንደ ብርቱው ሙሴ ከቤተ መንግሥት ልዑልነት ይልቅ ወደ ሎሌነት ወርዶ፣ ሥጋዊ ሓላፊነትን ንቆ፣ የቤተ መንግሥት ዝናሩን አውልቆ፣ ከእግዚአብሔር ዘንድ በተሰጠው የእረኝነት ሥልጣን የኃያልነት ዝናርን ታጥቋል፡፡ ለበጎቹ ሲልም በሲና በረሃ እሳት ነዶበታል። በእረኝነቱም ሕዝቡን ከጥፋት ለመታደግ ከበረሃ አውሬዎች ጋር ታግሏል፡፡ በእረኝነት ተግባር ብቻ ሳይኾን በየዋህቱም አርአያ ኾኗል፡፡ በመከራ እና በስቃይ የኖረ ሕዝብ የቃል ኪዳኗን ምድር ለመውረስ የሚጓዘው ሙሴ በረኝነት በነበረበት የበረሃ ምድረ አቋርጦ ነው፡፡ ጉዞው የሚወስደው ጊዜ ደግሞ ዐርባ ዓመታትን ነው፡፡ መንጋውን ለመምራት ለ፵ ዓመት የበረሃውን ሕይወት ከሚያውቀው ከሙሴ በቀር ማን ይችላል? ለዚህም ነው ቀን በደመና ሌሊት በብርሃን ዓምድ ውኃ እያፈለቀ፣ መና እያወረደ የቃዴስን ሐሩር ያሳለፋቸው፡፡ የእግዚአብሔር ቁጣ  በእስራኤል ልጆች ላይ በነደደች ጊዜ እንኳን ራሱን ስለ እነርሱ አሳልፎ የሚሰጥ መልካም እረኛ ኾኖ ተገኝቷል – ነቢዩ ሙሴ፡፡ ‹‹ወይእዜኒ እመ ተኀድግ ሎሙ ዘንተ ኃጢአተ ኅድግ ወእመ አኮሰ ደምስስ ኪያየኒ እመጽሐፍከ ዘጸሐፍከኒ፤ ሕዝብኽን ይቅር የማትላቸው ከኾነ እኔን ከጻፍኸው መጽሐፍኽ ደምስሰኝ›› በማለት መማጸኑም ስለዚህ ነው፡፡ የዚህ መልካም እረኛ ጸሎትም በእግዚአብሔር ፊት ሞገስን አግኝቷል (ዘፀ. ፴፪፥፴፪)፡፡

‹‹ረከብክዎ ለዳዊት ወልደ ዕሴይ ብእሴ ምእመነ ዘከመ ልብየ፤ ዘይገብር ኵሎ ፈቃድየ፤ ፈቃዴን ዅሉ የሚያደርግ የዕሴይን ልጅ ዳዊትን አገኘሁ›› (ሐዋ. ፲፫፥፳፪) ብሎ እግዚአብሔር የመሰከረለት ቅዱስ ዳዊት የተጠራውም ከበግ ጠባቂነት ነው፡፡ ለንጉሥ ሳኦል በወታደርነት የሚያገለግሉት የጦርነት ልምድ ያላቸው፣ በሰውኛ ዓይን ለቅብዐ መንግሥት ይበቃሉ ተብለው የሚታሰቡት ታላላቆቹ የዕሴይ ልጆች የነቢዩ ሳሙኤልን ቀርነ ቅብዕ ሲጠባበቁ ታናሹ ብላቴና ዳዊት ግን ያባቱን በጎች በዱር ይጠብቅ ነበር፡፡ እግዚአብሔርም ስለ ብጎቹ ሲል ከአንበሳ ጋር የሚተናነቀውን ታናሹን ብላቴና ዳዊትን መረጠ፡፡ እግዚአብሔር ዳዊትን ለንግሥና እንደ መረጠው የተረዳው ነቢዩ ሳሙኤልም መልእክተኛ ልኮ ዳዊትን አስጠርቶ ቅብዐ መንግሥትን ቀብቶ አነገሠው፡፡ የእግዚአብሔርም መንፈስ ከዚያን ቀን ጀምሮ በዳዊት ላይ አደረ (፩ኛ ሳሙ. ፲፮፥፲፪-፲፫)፡፡

ስለ መልካም እረኛ ሲነሣ በአብነት ከሚጠቀሱ የቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከል በረከታቸው ይደርብንና ኢትዮጵያዊው ሰማዕት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ አንደኛው ናቸው፡፡ ጠላት አገራችንን በወረረበት፣ በመንጋው ላይ መከራ እና ችግር በጸናበት፣ እንደዚሁም የንጹሐን ደም በግፍ በፈሰሰበት በዚያ በፈተና ወቅት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ለቤተ ክርስቲያንም ለአገርም የሚያስቡ መልካም እረኛ እንደ ነበሩ የታሪክ መዛግብት ማስረጃዎች ናቸው፡፡ ሰማዕቱ አቡነ ጴጥሮስ ከዐርበኞች ጋር ኾነው ሕዝቡ ለጠላት እጁን እንዳይሰጥና ሃይማኖቱን እንዳይለውጥ ከማስተማራቸው፣ ከማጽናናታቸው ባሻገር በጠላት ፊት ለፍርድ በቀረቡበት ጊዜም መልካም እረኝታቸውን በዐደባባይ መስክረው፣ ለሕዝብ፣ ለቤተ ክርስቲያንና ለአገር በመቆርቆራቸው በጥይት ተደብድበው በሰማዕትነት አልፈዋል፡፡

ክብር ይግባውና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረን ወደ በጎች ስፍራ በበሩ የማይገባ፥ በሌላም በኩል የሚገባ ሌባ፥ ወንበዴም ነው፡፡ በበሩ የሚገባ ግን የበጎች ጠባቂ ነው፡፡ ለእርሱ በረኛው ይከፍትለታል፤ በጎቹም ቃሉን ይሰሙታል፤ እርሱም በጎቹን በየስማቸው ይጠራቸዋል፤ አውጥቶም ያሰማራቸዋል፡፡ ምንደኛ (ቅጥረኛ) እረኛ ግን ለበጎቹ አይጨነቅም፤ በጎቹም አያውቁትም (ዘካ. ፲፩፥፬-፭፤ ዮሐ. ፲፥፩-፲፪)፡፡ ዛሬም በእናት ቤተ ክርስቲያናችን የተሾሙ አባቶች እንደነሙሴ፣ እንደነዳዊት፣ እንደነብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ለቤተ ክርስቲያንም ለአገርም የሚጨነቁ ሊኾኑ ይገባል፡፡ እኛ ምእመናንም እግዚአብሔር አምላካችን መልካም እረኞችን እንዳያሳጣን መለመን ይኖርብናል፡፡ እንደዚሁም ራሳችንን ለሃይማኖታችን ማስገዛት፣ መልካም እረኞችንም አብነት ማድረግና መከተል ይጠበቅብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ክርስቲያናዊ ኑሮ በዘመነ አስተምሕሮ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ታኅሣሥ ፲ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በቤተ ክርስቲያናችን የወቅት አከፋፈል ሥርዓት ከኅዳር ፮ እስከ ታኅሣሥ ፯ ቀን የሚገኘው ወቅት ‹ዘመነ አስተምህሮ› ይባላል፡፡ ቀጣዩ ወቅት (ዘመነ ስብከት) ዕለተ ሰንበትን ጠብቆ የሚገባ በመኾኑ ይህ ወቅት አንዳድ ጊዜ እስከ ታኅሣሥ ፲፫ ቀን የሚዘገይበት ጊዜም አለ፡፡ ‹ዘመነ አስተምህሮ› የሚለው ሐረግ ትርጕሙም በሃሌታው ‹ሀ› (‹አስተምህሮ› ተብሎ) ሲጻፍ የቃለ እግዚአብሔር ማስተማሪያ ማለትም የትምህርተ ወንጌል ዘመን ማለት ነው፡፡ ሥርወ ቃሉም ‹‹መሀረ/አምሀረ – አስተማረ፤ ለመምህር ሰጠ፤  መራ፤ አሳየ፤ መከረ፤ አለመደ›› ወይም ‹‹ተምህረ – ተማረ፤ ለመደ›› የሚለው የግእዝ ግስ ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፭፻፸፱)፡፡ 

ይኸውም የእግዚአብሔርን ቸርነት፣ ርኅራኄ፣ ትዕግሥትና የማዳን ሥራውን የሚመለከት ትምህርት በስፋት የሚቀርበበት ጊዜ ነው፡፡ ቃሉ በሐመሩ ‹‹ሐ›› (‹አስተምሕሮ› ተብሎ) ሲጻፍ ደግሞ የምሕረት፣ የይቅርታ ዘመን ማለት ነው፡፡ ሥርወ ቃሉም ‹‹መሐረይቅር አለ፤ ዕዳ በደልን ተወ›› ወይም ‹‹አምሐረ – አስማረ፤ ይቅር አሰኘ፤ አራራ፤ አሳዘነ›› የሚለው የግእዝ ግስ ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፭፻፹፬)፡፡

ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው ዘመነ አስተምሕሮ ስለ እግዚአብሔር ቸርነትና ርኅራኄ፤ እርሱ በደላችንን ዅሉ ይቅር እንደሚለን እኛ ምእመናንም እርስበርስ ይቅር መባባል እንደሚገባን ትምህርት የሚሰጥበት ጊዜ ነው፡፡

በቅዱስ ያሬድ የዜማ መጻሕፍት እንደ ተቀመጠው በዘመነ አስተምሕሮ ውስጥ የሚገኙ ሰንበታት (እሑዶች) አስተምሕሮ፣ ቅድስት፣ ምኵራብ፣ መጻጉዕ እና ደብረ ዘይት ተብለው ይጠራሉ፡፡ ከመጀመሪያው ሳምንት (ከአስተምሕሮ) በቀር የአራቱ እሑዶቹ ስያሜ ከዐቢይ ጾም ሰንበታት ጋር አንድ ዓይነት ነው፡፡ የሰንበታቱ ስያሜ ከዐቢይ ጾም ሰንበታት ጋር ተመሳሳይ ይኹን እንጂ በእነዚህ ሳምንታት ሌሊት የሚዘመሩ መዝሙራት፣ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ ምንባባትና የሚቀርቡ ትምህርቶች ግን በምሥጢር ይለያያሉ፡፡

ትምህርቶቹ ይለያያሉ ስንልም በዚህ ወቅት የሚነገረው ምሥጢርና ይዘት በወቅቱ ላይ የሚያተኵር መኾኑን ለመግለጽ ነው እንጂ በየትኛውም ጊዜ በቤተ ክርስቲያናችን የሚቀርበው ትምህርት አንዱ የእግዚአብሔር ቃል ብቻ ነው። ሳምንታቱን በዚህ መልክ የከፋፈለውም ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ ይህንንም ከመጽሐፈ ድጓው መመልከት ይቻላል (ድጓ ዘአስተምህሮ)፡፡

ከዚህ ቀጥለን በእያንዳንዱ የዘመነ አስተምህሮ (አስተምሕሮ) ሳምንት የሚቀርበውን ትምህርት በቅደም ተከተል በአጭሩ እንመለከታለን፤

፩. አስተምሕሮ

የመጀመሪያው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት አስተምሕሮ ይባላል፤ ይህም ከኅዳር ፮–፲፪ ያሉትን ሰባት ቀናት ያካትታል፡፡ በዕለቱ (እሑድ) የሚቀርበው የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ‹‹ኢተዘኪሮ አበሳ ዚአነ ኢኀደገነ ፍጹመ ንማስን …. ኀጢአታችንን አላሰበብንም፤ እንጠፋ ዘንድም ፈጽሞ አልተወንም ….›› የሚለው ሲኾን፣ በተጨማሪም ‹‹ፈጽም ለነ ሠናይተከ እንተ እምኀቤነ …. በአንተ ዘንድ ያለችውን በጎነት ፈጽምልን ….›› የሚለውም እንደ አማራጭ ሊዘመር ይችላል፡፡ ምስባኩ ‹‹ኢትዝክር ለነ አበሳነ ዘትካት ፍጡነ ይርከበነ ሣህልከ እግዚኦ እስመ ተመንደብነ ፈድፋደ፤ የቀደመውን በደላችንን አታስብብን፡፡ አቤቱ ምሕረትህ ፈጥኖ ያግኘን፡፡ እጅግ ተቸግረናልና፤›› የሚለው የዳዊት መዝሙር ነው (መዝ. ፸፰፥፰)፡፡

ወንጌሉ ማቴዎስ ፮፥፭-፲፮ ሲኾን፣ ይኸውም ፊትን በማጠውለግና ጸሎተኛ በመምሰል ሳይኾን በፍጹም ፍቅርና ትሕትና መጾም መጸለይ እንደሚገባን የሚያስተምረው የወንጌል ክፍል ነው፡፡ እንደዚሁም ከእግዚአብሔር ዘንድ ይቅርታን ለማግኘት በመጀመሪያ እርስበርሳችን ይቅር መባባል ማለትም የበደሉንን ይቅር ማለት እንዳለብን ይህ የወንጌል ክፍል ያስረዳናል፡፡ ቅዳሴውም ቅዳሴ እግዚእ (የጌታችን ቅዳሴ) ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ነገረ ድኅነትን ከምሥጢረ ቍርባን ጋር በማስማማት የተዘጋጀውና ብዙ ምሥጢራትን ያካተተው ቅዳሴ ነው፡፡

በዚህ ሳምንት (በአስተምሕሮ) እግዚአብሔር አምላካችን ከአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዓመት የመርገምና የጨለማ ዘመን ዓለምን ማውጣቱ፤ ቸርነቱ፣ ርኅራኄውና ትዕግሥቱ፤ ምእመናንን ከሞተ ሥጋ ከሞተ ነፍስ ማዳኑ በሰፊው ይመሠጠርበታል፡፡ በየጊዜው እንደምንማረው እግዚአብሔር አምላካችን ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከቅድስት ደንግል ማርያም ተወልዶ በአዳም በደል (የውርስ ኀጢአት) ምክንያት ከመቀጣት ማለትም ከሞተ ነፍስ (ከቁራኝነት) አድኖናል፡፡ ድነናል ስንልም ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከፈለው መሥዋዕትነት በቀደመው የአዳም በደል አንጠየቅም ማለታችን ነው፡፡

ይኹን እንጂ በየራሳችን በደል እንደምንጠየቅ መዘንጋት የለብንም፡፡ ስለዚህም ‹‹በጸጋው ድነናል›› እያሉ ከጽድቅ ሥራ ተለይተው በዘፈቀደ ምድራዊ ኑሮ ማለፍ ከሚፈልጉ አንዳንድ ሰዎች የተሳሳተ ትምህርት መራቅ ይጠበቅብናል፡፡ ከዚሁ ዂሉ ጋርም ‹‹ድነናል›› ብለን ብቻ መቀመጥ ሳይኾን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንችል ዘንድ በየጊዜው ከሠራነው ኀጢአት በንስሐ መመለስ እንደሚገባንም መረዳት ይኖርብናል፡፡ ይኸውም (ምሥጢረ ንስሐ) እግዚአብሔር አምላካችን ለእኛ ለምእመናን የሰጠን ልዩ ጸጋ ነው፡፡

ይህን ያህል ጸጋ ከተሰጠን ለመኾኑ በምን ዓይነት ሕይወት እየኖርን ነው? በመንፈሳዊ ወይስ በዓለማዊ? በፈሪሃ እግዚአብሔር ወይስ በአምልኮ ባዕድ? በጽድቅ ወይስ በኀጢአት ሥራ? ጥያቄውን ለየራሳችን እንመልሰው፡፡ በፈቃዱ ከሞት ወደ ሕይወት የመለሰንን አምላክ በክፉ ግብራችን እንዳናሳዝነው ልንጠነቀቅ ያስፈልጋል፡፡ በመልካምታችን ከዂሉም በፊት የምንጠቀመው እኛው ራሳችን ነንና፡፡

ስለዚህ በዚህ ወቅት እግዚአብሔር ያደረገልንን ዘለዓለማዊ ውለታ በማሰብ ይቅርታውን፣ ቸርነቱን ከማድነቅና እርሱን ከማመስገን ባሻገር በጽደቅ ሥራ ልንበረታ ይገባናል፡፡ ጊዜው የአስተምሕሮ ማለትም የምሕረት፣ ይቅርታ፣ የስርየተ ኀጢአት እንደዚሁም የምስጋና ጊዜ ነውና፡፡

፪. ቅድስት

ከኅዳር ፲፫–፲፱ ያሉትን ሰባት ቀናት የሚያካትተው የዘመነ አስተምሕሮ ሁለተኛው ሳምንት ቅድስት ይባላል፤ ቅድስት የተባለበት ምክንያትም ዕለተ ሰንበትን ለቀደሰ፣ ለመረጠ፣ ላከበረ ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ማቅረብ እንደሚገባ የሚነግርበት ሳምንት በመኾኑ ነው፡፡ በዚህ ዕለት (እሑድ) ‹‹ሎቱ ስብሐት ወሎቱ አኰቴት ለዘቀደሳ ለሰንበት …. ሰንበትን ላከበራት ለእርሱ ክብር ምስጋና ይኹን (ምስጋና ይድረሰው፤ ምስጋና ይገባዋል) ….›› የሚለው የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ይቀርባል፡፡ በቅዳሴ ጊዜም ‹‹ኵሎ ዘፈቀደ ገብረ እግዚአብሔር በሰማይኒ ወበምድርኒ በባሕርኒ ወበኵሉ ቀላያት፤ በሰማይና በምድር፣ በባሕርና በጥልቆችም ዅሉ እግዚአብሔር የወደደውን ዅሉ አደረገ፤›› የሚለው ምስባክ ይሰበካል (መዝ. ፻፴፬፥፮)፡፡

የዕለቱ ወንጌል ዮሐንስ ፭፥፲፮-፳፰ ሲኾን፣ ይኸውም ስለ ሰንበት ክብር፣ እግዚአብሔር የሰንበት ጌታ ስለመኾኑና ሰንበትን ለሰው ልጆች ዕረፍት ስለ መፍጠሩ ያስረዳል፡፡ በዚህ ሳምንት ሰንበትን ስለ ቀደሰ እግዚአብሔር ቅድስና እና ሰንበት ቅድስት ስለመኾኗ ሰፊ ትምህርት ይቀርባል፡፡ በዕለቱ የሚቀደሰው ቅዳሴ አትናቴዎስም ነገረ ድኅነትን ከምሥጢረ ሥጋዌና ምሥጢረ ቍርባን ጋር በማስማማት የሚያትትና ክብረ ሰንበትን የሚያስረዳ ቅዳሴ ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድ ‹‹ሰንበት ተዐቢ እምኵሉ ዕለት ወሰብእ ይከብር እምኵሉ ፍጥረት፤ ከዕለታት ሰንበት ትበልጣለች፤ ከምድራውያን ፍጥረታትም የሰው ልጅ ይከብራል›› በማለት እንደ ዘመረው ዕለተ ሰንበት ከሳምንቱ ዕለታት ዂሉ ትበልጣለች፡፡ የሰው ልጅም ከምድራውያን ፍጥረታት የከበረ ነው፡፡ ሰንበት ስንል ሁለቱን ዕለታት (ቀዳሚት ሰንበት እና እሑድ ሰንበትን) ማለታችን ነው፡፡ የመጀመሪያዋ ሰንበት እግዚአብሔር ከሥራው ዂሉ ስላረፈባት፤ ሁለተኛዋ (እሑድ) ሰንበት ደግሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ተፀነሰባት፣ ከሙታን ተለይቶ ስለ ተነሣባት ከዕለታት ዂሉ ይበልጣሉ፡፡ ስለዚህም ከሌሎች ዕለታት አስበልጠን እናከብራቸዋለን፡፡

የሰው ልጆችም በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ እንደ መፈጠራችን ከፍጥረታት ዂሉ እንደምንከብር ቅዱሳት መጻሕፍት ይነግሩናል፡፡ ኾኖም ብዙዎቻችን እግዚአብሔር የሰጠንን ክብር በራሳችን ኀጢአት ዝቅ አድርገነዋል፡፡ ማለትም በእግዚአብሔር አምሳል ከተፈጠረ፣ ለእግዚአብሔር ማደሪያነት ከተመረጠ ክቡር ሰው በማይጠበቅ ክፉ ግብር ወድቀናል፡፡ በዝሙት፣ እርስበርስ በመከፋፈል፣ በመገዳደል፣ በመተማማትና በሐሰት በመካከሰስ በጥቅሉ ለሰይጣናዊ ግብር በፈቃዳችን በመገዛት ራሳችንንና ሌሎችን የምንበድል፣ እግዚአብሔርንም የምናሳዝን ሰዎች ጥቂቶች አይደለንም፡፡ እግዚአብሔር ይቅር ብሎ ወደ ክርስቲያናዊ ሕይወትና ወደ መንፈሳዊ ሰብእና ይመልሰን እንጂ፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት፣ ይህን ዂሉ የሰው ልጅ በደል ሲያመላክት ‹‹ሰብእሰ እንዘ ክቡር ውእቱ ኢያእመረ ወኮነ ከመ እንስሳ ዘአልቦ ልብ ወተመሰሎሙ፤ ሰው ግን ክቡር ኖ ሳለ አያውቅም፡፡ እንደሚጠፉ እንስሶች መሰለ፤›› በማለት ይናገራል (መዝ. ፵፰፥፲፪)፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንት በትርጓሜአቸው ‹‹ዳዊት አክብሮ አጓዶ ተናገረ፡፡ ዕዝራ ግን ‹እንስሳት ይኄይሱነ፤ እነስሳት ይሻሉናል› ብሎታል›› በማለት ይህንን ኃይለ ቃል ያመሠጥሩታል።

ምሳሌውን ሲያብራሩም ‹‹እንስሳ ከገደል አፋፍ ኖ ሲመገብ ከገደሉ ሥር ለምለም ሣር፣ ጥሩ ው ቢያይ የረገጠው መሬት ከአልከዳው (ከአልተናደበት) በስተቀር ወርጄ ልመገብ፣ ልጠጣ አይልም፡፡ ሰው ግን ጽድቅ እንዲጠቅም ኀጢአት እንዲጎዳ እያወቀ ጨለማን ተገን አድርጎ ሊሠርቅ፣ ሊቀማ፣ የጎልማሳ ሚስት ሊያስት ይሔዳል›› ሲሉ ያብራሩታል (ትርጓሜ መዝሙረ ዳዊት)፡፡

በዚህ ዓይነት ኀጢአት ራሳችንን ያስገዛን ዂሉ፣ ከዚህ ክፉ ግብራን በመለየት በንስሐ ወደ እግዚአብሔር መመለስ ከፍጥረታት ከከበርን ከሰው ልጀች ይልቁንም ከክርስቲያኖች ይጠበቃል፡፡ ስለዚህም አሁኑኑ ወደ ይቅር ባዩ አምላካችን ቀርበን ይቅርታን፣ ስርየትን እንለምን፡፡ ጊዜው ዘመነ አስተምሕሮ (የይቅርታ ዘመን) ነውና፡፡

፫. ምኵራብ

ሦስተኛው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት ምኵራብ የሚባል ሲኾን ይህም ከኅዳር ፳–፳፮ ያሉትን ሰባት ቀናት የሚያካትት ሳምንት ነው፡፡ በዚህ ሳምንት ጌታችን፣ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምኵራበ አይሁድ ሕዝቡን እየሰበሰበ ማስተማሩ፤ ባሕርና ነፋሳትን መገሠፁ፤ አጋንንትን ከሰዎች ማውጣቱ ይነገራል፡፡

በዕለቱ (እሑድ) የሚቀርበው መዝሙር፡- ‹‹አምላክ ፍጹም በህላዌሁ ዘሀሎ እምቅድመ ይትፈጠር ዓለም …. ዓለም ከመፈጠሩ አስቀድሞ የነበረው አምላክ (እግዚአብሔር) በህልውናው (አነዋወሩ) ፍጹም ነው ….››  የሚለው ሲኾን፣ ምስባኩም፡- ‹‹ቅረቡ ኀቤሁ ወያበርህ ለክሙ ወኢይትኀፈር ገጽክሙ ዝንቱ ነዳይ ጸርሐ ወእግዚአብሔር ሰምዖ፤ ወደ እርሱ ቅረቡ፤ ያበራላችሁማል፡፡ ፊታችሁም አያፍርም፡፡ ይህ ችግረኛ ጮኸ፤ እግዚአብሔርም ሰማው፤›› የሚል ነው (መዝ. ፴፫፥፭-፮)፡፡ ወንጌሉም ከማቴዎስ ፰፥፳፫ እስከ መጨረሻው ድረስ ነው፡፡ ቅዳሴውም ቅዳሴ እግዚእ ነው፡፡

የዕለቱ ወንጌል ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመርከብ ውስጥ ሳለ መርከቢቱ እስክትናወጥ ድረስ ታላቅ ማዕበል መነሣቱን፤ ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹ጌታ ሆይ እንዳንጠፋ አድነን?›› እያሉ በመተማጸኑት ጊዜ ጌታችን ነፋሱንና ባሕሩን በመገሠፅ ጸጥታን፣ ሰላምን፣ መረጋጋትን ማስፈኑን የሚናገረው ክፍል ነው፡፡

በባሕሩ ዓለም ውስጥ የምትገኘው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሰዎች በፈቃደ ሥጋቸው ተሸንፈው ባመጡት ጥላቻ፣ ኑፋቄ፣ ክህደት፣ ፍቅረ ንዋይ፣ በአጠቃላይ በልዩ ልዩ የኀጢአት ማዕበልና ሞገድ እየተናወጠች ናት፡፡ ይህን ማዕበልና ሞገድ ጸጥ በማድረግ ፍቅርን፣ አንድነትን፣ ሰላምንና ጽድቅን ማስፈን የሚቻለውን መድኀኒታችን ክርስቶስን እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት በአንድነት ኾነን ‹‹ጌታ ሆይ እንዳንጠፋ አድነን?›› እያልን እንማጸነው፡፡

የሰላሙ ዳኛ፣ የሰላሙ መሪ፣ የሰላሙ ጌታ፣ የሰላሙ ንጉሥ፣ የሰላሙ ባለቤት እርሱ ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምን፣ መረጋጋትን፣ ፍቅርን፣ አንድነትን ካወጀ በቤተ ክርስቲያናችን ፍቅር፣ አንድነት ሰላም ይሰፍናልና፡፡

፬. መጻጕዕ

ከኅዳር ፳፯ እስከ ታኅሣሥ ፫ ያሉ ሰባት ቀናትን የሚያጠቃልለው አራተኛው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት መጻጕዕ ይባላል፡፡ የቃሉ ፍቺ ‹በደዌ ዳኛ፣ በአልጋ ቍራኛ የተያዘ በሽተኛ ማለት ነው፡፡ ዕለቱ መጻጕዕ ተብሎ መሰየሙም ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዕውር ኾኖ የተወለደውን ጐበዝ ዓይን ያበራበትን ዕለት ለማስታወስ ነው፡፡

የዕለቱ (እሑድ) መዝሙር ‹‹ይቤሉ እስራኤል ኢርኢነ ወኢሰማዕነ ዘዕውሩ ተወልደ ወተከሥተ አዕይንቲሁ በሰንበት …. ዕውር ኾኖ ተወልዶ ዓይኖቹ በሰንበት የበሩለትን ሰው እስራኤልአላየንም፤ አልሰማንምአሉ ….›› የሚለው የእስራኤላውያንን በክርስቶስ ተአምር አለማመን የሚገልጸው የቅዱስ ያሬድ ድርሰት ነው፡፡

ምስባኩም ‹‹ደቂቀ ዕጓለ እመሕያው እስከ ማእዜኑ ታከብዱ ልበክሙ ለምንት ታፈቅሩ ከንቶ ወተሐሱ ሐሰተ አእምሩ ከመ ተሰብሐ እግዚአብሔር በጻድቁ፤ እናንት የሰው ልጆች፣ እስከ መቼ ድረስ ልባችሁን ታከብዳላችሁ? ከንቱ ነገርን ለምን ትወዳላችሁ? ሐሰትንም ለምን ትሻላችሁ? እግዚአብሔር በጻድቁ እንደ ተገለጠ ዕወቁ፤›› የሚለው እግዚአብሔር ለጻድቃኑ በሚያደርገው ድንቅ ሥራ ማመን እንደሚገባ የሚያስረዳው የዳዊት መዝሙር ነው (መዝ. ፬፥፪-፫)፡፡

ወንጌሉ ደግሞ ዕውር ኾኖ የተወለደውንና በጌታችን አምላካዊ ኃይል የተፈወሰውን ጐልማሳ ታሪክ የሚተርከው ዮሐ. ፱፥፩ እስከ መጨረሻው ያለው ኃይለ ቃል ሲኾን፣ የዕለቱ ቅዳሴም ቅዳሴ እግዚእ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት መድኀኒታችን የዕውሩን ዓይን ከማብራቱ ባሻገር ሕሙማነ ሥጋን በተአምራቱ፤ ሕሙማነ ነፍስን በትምህርቱ ስለ ማዳኑ የሚያወሳ ቃለ እግዚአብሔር ይቀርባል፡፡

ትምህርቱን ከእኛ ሕይወት ጋር አያይዘን ስንመለከተው፣ ብዙዎቻችን ዓይነ ሕሊናችን የጽደቅ ሥራ ብርሃንን ከማየት በመሰወሩ የተነሣ በልዩ ልዩ ደዌ ተይዘናል፡፡ በሐሜት፣ በኑፋቄ፣ በጥላቻ፣ በዐመፅ፣ በስርቆት፣ በውሸት፣ በዝሙት፣ ወዘተ. በመሳሰሉት ደዌያት የተለከፍን ጥቂቶች አይደለንም፡፡ ለዚህም በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች የምንሰማውና የምናየው በቂ ማስረጃ ነው፡፡

ሰው በሰው ላይ በጠላትነት ሲነሣሣና ወንድሙን፣ እኅቱን በአሰቃቂ ኹኔታ ሲገድል፤ ተመሳሳይ ፆታዎች በሰይጣናዊ ፈቃድ ተሸንፈው ‹ጋብቻ› ሲመሠርቱ፤ አንዳንዶቹ ከሕግ ባሎቻቸውና ሚስቶቻቸው ውጪ ሲዘሙቱ፤ ከዚህ በባሰ ደግሞ እግዚአብሔር ምእመናንን እንዲመሩ የሾማቸው ካህናት ሳይቀሩ ክብረ ክህነትን በሚያስነቅፍ የስርቆትና ሌላም ወንጀል ተሰማርተው የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ገንዘብ ሲመዘብሩ እየሰማን ነው፡፡

ከዚህ የሚበልጥ ደዌ ምን አለ? ከደዌ ሥጋ በጠበልና በሕክምና መፈወስ ይቻላል፡፡ በሽታው ባይድንም እንኳን ሕመሙን ለመቋቋም የሚያስችል መድኀኒት አይጠፋም፡፡ የኀጢአት ደዌ ግን መድኀኒቱ ንስሐ ብቻ ነው፡፡ ስለኾነም ከላይ በተጠቀሱትና በመሳሰሉት ደዌያት የምንሰቃይ ወገኖች ዂሉ ፈውሱ ዘለዓለማዊ ወደ ኾነው ወደ ወደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀርበን እንፈወስ፡፡ እርሱ የነፍስ የሥጋ መደኀኒት ነውና፡፡

፭. ደብረ ዘይት

አምስተኛውና የመጨረሻው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት ‹ደብረ ዘይት በመባል የሚታወቅ ሲኾን የሚያጠቃልለውም ከታኅሣሥ ፬ – ፮ ያሉ ቀናትን ነው፡፡ በዕለቱ (እሑድ) ‹‹ሠርዐ ሰንበተ ለሰብእ ዕረፍተ ለእለ በሰማይ ወለእለ በምድር እግዚአብሔር በሰማይም በምድርም ለሚኖሩ ፍጡራን ሰንበትን ለዕረፍት ሠራ (ፈጠረ) ….›› የሚለው የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ይዘመራል፡፡

‹‹ለነዳያኒሃኒ አጸግቦሙ እክለ ወለካህናቲሃኒ አለብሶሙ ሕይወተ ወጻድቃኒሃኒ ትፍሥሕተ ይትፌሥሑ፤ ባልቴቶቿን እጅግ እባርካቸዋለሁ፤ ድሆቿንም እኽልን አጠግባቸዋለሁ፡፡ ካህናቷንም ደኅንነትን አለብሳቸዋለሁ፡፡ ጻድቃኖቿም እጅግ ደስ ይላቸዋል፤›› የሚለው የዳዊት መዝሙር ደግሞ የዕለቱ ምስባክ ነው (መዝ. ፻፴፩፥፲፭-፲፮)፡፡

በዕለቱ የሚነበበው የወንጌል ክፍልም ሉቃስ ፲፪፥፴፪-፵፩ ሲኾን፣ ቅዳሴው ደግሞ ቅዳሴ አትናቴዎስ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት ሰንበት የዕረፍት ዕለት መኾኗን ከሚያስገነዝቡ ትምህርቶች በተጨማሪ የደጋግ አባቶችን መንፈሳዊ ታሪክ፣ የወረሱትን ሰማያዊ ሕይወትና ያገኙትን ዘለዓለማዊ ሐሤት መሠረት በማድረግ እኛ ምእመናንም እንደ አባቶቻችን ለመንግሥተ ሰማያት በሚያበቃ ክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን መኖር እንደሚገባን የሚያተጋ ቃለ እግዚአብሔር ይቀርባል፡፡

በዕለቱ የሚነበበው የወንጌል ክፍል (ሉቃ. ፲፪፥፴፪-፵፩) የሰው ልጅ ዓለም የሚያልፍበትን ወይም ራሱ የሚሞትበትን ቀን አያውቅምና ዘወትር በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንቶ መኖር እንደሚገባው፤ እንደዚሁም በዚህ ምድር ሳለ ለሥጋው የሚጠቅም ኃላፊ ጠፊ ሀብት ከመሰብሰብ ይልቅ ለነፍሱ የሚበጅ የጽድቅ ሥራን ማብዛትና የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ የሚያበቃ ክርስቲያናዊ ምግባርን መያዝ እንደሚጠበቅበት፤ በዚህም ሰማያዊውን መንግሥት ለመውረስ እንደሚቻለው የሚያስረዳ መልእክት አለው፡፡

እንግዲህ እንደ ታዘዝነው ነገ ለሚያልፍና ለሚጠፋ ምድራዊ ጉዳይ መጨነቃችንንና እርበርስ መገፋፋታችንን ትተን እግዚአብሔር አምላካችን ለፍርድ ሲመጣ ሰማያዊ ዋጋ ለመቀበልና የማያልፈውን መንግሥቱን ለመውረስ በሚያበቃን ክርስቲያናዊ ምግባር እንጽና፡፡ ‹‹ክርስቲያናዊ ኑሮ በዘመነ አስተምሕሮ›› ማለትም ይኸው ነው፡፡

የቀደመ በደላችንን ቈጥሮ ሳያጣፋን ዕድሜ ለንስሐ ሰጥቶ እስከ ዛሬ ድረስ የጠበቀን፤ ይቅርታ፣ ርኅራኄ፣ ቸርነት የባሕርዩ የኾነው አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር እንደ ቸርነቱ ዘለዓለማዊ መንግሥቱን ለመውረስ ያብቃን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡