ጾመ ነቢያት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ኅዳር ፲፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

እግዚአብሔር አምላካችን ዓለምን ለማዳን ሲል የሰውን ሥጋ መልበሱን፣ ከእናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ጋር ወደ ግብጽ ግብር መሰደዱን፣ በባሕረ ዮርዳኖስ መጠመቁን፣ በትምህርቱ ብርሃንነት ጨለማውን ዓለም ማብራቱን፣ ለሰው ልጆች ድኅነት ሲል ልዩ ልዩ ዓይነት መከራ መቀበሉን፣ መሰቀሉን፣ መሞቱን፣ ከሙታን ተለይቶ መነሣቱን፣ ማረጉንና ዳግም ለፍርድ የሚመጣ መኾኑን በአጠቃላይ የማዳን ሥራውን በየዘመናቱ የተነሡ ቅዱሳን ነቢያት በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝተው አስቀደመው በትንቢት ተናግረዋል፡፡ ትንቢቱ ተፈጽሞ ለመመልከትም ‹‹አንሥእ ኃይለከ ፈኑ እዴከ፤ ኃይልህን አንሣ፤ እጅህን ላክ›› እያሉ በጾም በጸሎት ተወስነው አምላክ ሰው ኾኖ ዓለምን የሚያድንበትን ጊዜ በቀናት፣ በሳምንታት፣ በወራትና በዓመታት እያሰሉ ሲጠባበቁ ቆይተዋል፡፡ የእግዚአብሔርን ሰው መኾን ሲጠባበቁ የኖሩት የነቢያት ትንቢትና ጸሎትም በእግዚአብሔር ሰው መኾን ፍጻሜ አግኝቷል፡፡

ይህን ምሥጢር በማሰብ በየዓመቱ ከኅዳር ፲፭ ቀን ጀምሮ እስከ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት ዋይዜማ ድረስ እንድንጾም አባቶቻችን መምህራነ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሠርተውልናል፡፡ ይህ ጾም፣ ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ ሲኾን፣ በስያሜም ‹‹ጾመ ነቢያት (የነቢያት ጾም)›› እየተባለ ይጠራል፡፡ ወቅቱ ለአዳም የተነገረው የድኅት ተስፋ የተፈጸመበት ስለ ኾነም ‹‹ጾመ አዳም (የአዳም ጾም)›› ይባላል፡፡ ስለ እግዚአብሔር ሰው መኾን በስፋት ትምህርተ ወንጌል የሚሰጥበት ወቅት በመኾኑም ‹‹ጾመ ስብከት (የስብከት ጾም)›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ የጾሙ መጨረሻ (መፍቻ) በዓለ ልደት በመኾኑ ደግሞ ‹‹ጾመ ልደት (የልደት ጾም)›› በመባል ይታወቃል፡፡ በተጨማሪም ‹‹ጾመ ሐዋርያት››  እየተባለ ይጠራል፡፡ ምክንያቱም ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹በዓለ ትንሣኤን ዐቢይ ጾምን ጾመን እናከብረዋለን፤ በዓለ ልደትንስ ምን አድርገን እናከብረዋለን?›› በማለት ነቢያት በጾሙበት ማለት ከልደተ ክርስቶስ በፊት ባለው ወቅት ጾመዋልና፡፡

በሌላ አጠራር ይኸው ጾመ ነቢያት ‹‹ጾመ ፊልጶስ (የፊልጶስ ጾም)›› በመባል ይታወቃል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ፊልጶስ በአፍራቅያ እና አውራጃዋ ዅሉ እየተዘዋወረ በጌታችን አምላካችንና ድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ወንጌልን በማስተማር፣ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን በማድረግ ብዙዎችን ወደ አሚነ እግዚአብሔር ሲመልስ ቆይቶ ትምህርቱን በማይቀበሉ የአፍራቅያ ሰዎች አማካይነት በሰማዕትነት ዐርፏል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ሥጋውን ሊቀብሩ ሲሉም ተሰወረባቸው፡፡ በዚህ ጊዜ በዓት ዘግተው፣ ሱባዔ ገብው፣ በጾም በጸሎት ተወስነው የሐዋርያውን ሥጋ ይመልስላቸው ዘንድ እግዚአብሔርን ቢለምኑት ልመናቸውን ተቀብሎ ሱባዔ በያዙ በ፫ኛው ቀን የቅዱስ ፊልጶስን ሥጋ (በድን) መልሶላቸው በክብር አሳርፈውታል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ የሐዋርያውን ሥጋ ካገኙ በኋላ እስከ ጌታችን ልደት ድረስ ጾመዋል፡፡ ስለዚህም ጾመ ነቢያት፣ ‹‹ጾመ ፊልጶስ›› እየተባለ ይጠራል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ወልደ አምላክ ክርስቶስን በግብረ መንፈስ ቅዱስ እንደምትፀንሰው፣ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ካበሠራት በኋላ ‹‹ሰማይና ምድር የማይወስኑትን አምላክ ፀንሼ ምን ሠርቼ እወልደዋለሁ?›› በማለት ጌታችንን ከመውለዷ አስቀድማ እመቤታችን ጾማዋለችና ይህ ጾም ‹‹ጾመ ማርያም›› በመባልም ይታወቃል፡፡ በአጠቃላይ በዚህ በጾመ ነቢያት፣ ነቢያትም ሐዋርያትም፣ ቀደምት አባቶቻችንም ጾመው በረከት አግኝተውበታል፡፡ እኛ ምእመናንም የነቢያት፣ የሐዋርያት፣ የጻድቃንና የሰማዕታት አምላክ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ሐዋርያት በረከት እንዲያሳትፈን በዚህ በጾመ ነቢያት ወቅት በጾም በጸሎት ተወስነን እግዚአብሔርን ልንማጸነው ይገባናል፡፡ 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡ 

ምንጭ፡ 

  • ፍትሐ ነገሥት ንባቡና ትርጓሜው፣ አንቀጽ ፲፭፡፡ 
  • ጾምና ምጽዋት (፳፻፩ ዓ.ም)፣ ዲያቆን ቃኘው ወልዴ፤ ገጽ ፵፯ – ፶፡

‹‹በመንገድ ላይ እንዳላጠፋህ በፊትህ መልአክ እሰዳለሁ፤›› (ዘፀ. ፴፫፥፫)፡፡

በመምህር ኢዮብ ይመኑ 

ኅዳር ፲፪ ቀን ፳፻፲ ዓ.

በረኃብ ምክንያት ከከነዓን ወደ ግብጽ የተሰደዱት የያዕቆብ ቤተሰቦች፣ በአባታቸው በያዕቆብ ምርቃት በግብጽ ምድር ቍጥራቸውም እጅግ እየበዛ መጣ፡፡ መብዛታቸውም ከ፲፪፻፹ – ፲፬፻፵፭ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ የተነሣውን፣ ዮሴፍን የማያውቀውን ንጉሥ አስፈራው (ዘፀ. ፩፥፰)፡፡ ንጉሡም ጠላት ይኾኑብናል ያም ባይኾን ጠላት ቢነሣብን አብረው ይወጉናል በሚል ፍርኃት፣ አገዛዙን አጸናባቸው፡፡ በከባድ ሥራ እየጠመደ በጭካኔ ጡብ እያስገነባ ፊቶም፣ ራምሴ፣ ዖን የተባሉ ታላላቅ ከተሞችን አሠራቸው፡፡ ኖራ እያስወቀጠ፣ ጭቃ እያስረገጠ በሥራ ደክመው ልጅ እንዳይወልዱ ጉልበታቸውን አደከማቸው፡፡ በጅራፍ እየገረፈ መከራ አጸናባቸው፡፡ ይህን ቢያደርግም ጉልበታቸው እየበረታ፣ ከእርሱ መከራ የአባቶቻቸው ምርቃትና ቃል ኪዳን እየረታ አሁንም በዙ፡፡ ንጉሡም ወንድ ሲወለድ በመግደል እስራኤልን ለመቆጣጠር ሞከረ፡፡ ነገር ግን የመከራው ብዛት የሕዝቡም ጩኸት የራሔልም ዕንባ የሕዝቡን መከራ ቅድመ እግዚአብሔር እንዲደርስ አደረገው፡፡

በግብጽ ምድር በመከራ የኖሩት እስራኤላውያን፣ በፈርዖንና በሠራዊቱ ላይ ከደረሱ ፱ መቅሠፍቶች፣ ፲ኛ ሞተ በኵር እና ፲፩ኛ ስጥመተ ባሕር በኋላ በእግዚአብሔር ፈቃድ፣ በቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነትና በሙሴ ጸሎት በተአምራት ከግብጽ ምድር ወጥተው ወደ ርስታቸው ከነዓን ገብተዋል፡፡ ‹‹በመንገድ ላይ እንዳላጠፋህ በፊትህ መልአክ እሰዳለሁ፤›› (ዘፀ. ፴፫፥፩-፫) ተብሎ እንደ ተጻፈው፤ ከመከራ የወጡትን እስራኤል በጉዟቸው ከሚገጥማቸው መሰናከል እየጠበቀ፣ በመንገድ ላይ እንዳይጠፉ እያማለደ፣ በምሕረት እየታደገ፣ ከጠላት ጋር ሲዋጉም አብሮ እየቀደመ፣ ከዲያብሎስ ተንኮል እየሰወረ እግዚአብሔር ወዳዘጋጀላቸው ሥፍራ ያስገባቸው የእግዚአብሔር መልአክ የቅዱስ ሚካኤል መታሰቢያ በዓል በየዓመቱ ኅዳር ፲፪ ቀን በቤተ ክርስቲያናችን ይከበራል፡፡

እግዚአብሔር የሰው ልጆችን ድካም የሚያውቅ አምላክ ነው፡፡ የሰው ልጅ ደግሞ የእግዚአብሔርን ውለታ የሚዘነጋ፣ የተደረገለትንም የሚረሳ፣ ፊቱ ባለ ነገር ላይ ብቻ የሚጨነቅ፣ ነገ በሚመጣው ብቻ የሚጠበብ እንጂ የትናንትና ታሪኩን አስቦ እግዚአብሔርን የሚያመሰግን ባለመኾኑ፣ የተደረገለትን ውለታ እንዳይረሳ ይልቁን እግዚአብሔርን እንዲያመሰግን እንደዚሁም ያለፉት ሥራዎቹ እንዳይረሱ መታሰቢያን ሰጥቶናል፡፡ የቅዱሳን በመታሰቢያ በዓላት እኛን እንድንድን ለመርዳትና ለማገዝ የተሠሩ ሥርዓቶች ናቸው፡፡ መጽሐፍ ‹‹መታሰቢያህም ለልጅ ልጅ ነው … ይህ ለሚመጣ ትውልድ ይጻፍ፡፡ የሚፈጠርም ሕዝብ ለእግዚአብሔር ዕልል ይላል›› (መዝ. ፻፩፥፲፪) እንዳለ የቅዱሳን በዓል መታሰቢያነቱ የእግዚአብሔርን ሥራ ለማድነቅ ለማመስገን ነው፡፡ ተጠቃሚዎቹ ደግሞ እኛ ምእመናን ነን፡፡ ከዚህም ባሻገር መጪውን ትውልድ ወደ እግዚአብሔር ማቅረቢያ፣ ለነገ መንፈሳዊ ሕይወት ማዘጋጃ፣ የበረከትም ማግኛ ይኾናል – መታሰቢያ፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ እንደ ተመዘገበው የዮርዳኖስን የሞላ ውኃ በእግዚአብሔር ተአምራት ተቋርጦ በደረቅ መሻገራቸው ለማሰብ ኢያሱ እስራኤላውያንን ‹‹በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ታቦት ፊት ወደ ዮርዳኖስ መካከል እለፉ፡፡ ከእናንተም ሰው ዅሉ በእስራኤል ልጆች ነገድ ቍጥር በጫንቃው ላይ አንድ አንድ ድንጋይ ከዚያ ይሸከም፡፡ ይህም በመካከላችሁ ምልክት ይኾናል ልጆቻችሁም በሚመጣ ዘመን ‹የእነዚህ ድንጋዮች ነገር ምንድር ነው?› ብለው ሲጠይቁአችሁ እናንተበእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ታቦት ፊት የዮርዳኖስ ውኃ ስለ ተቋረጠ ነው፤ እነዚህ ድንጋዮች ለእስራኤል ልጆች ለዘለዓለም መታሰቢያ ይኾናሉ› ትሏቸዋላችሁ፤›› ብሏቸዋል (ኢያሱ ፬፥፬-፯)፡፡ ይህም መታሰቢያ ዕለታት ወይም በዓላት ወይም ምልክቶች ጥቅም እንዳላቸው ያስረዳናል፡፡ በእነዚህ ዕለታት፣ ሰው እግዚአብሔርን አመስግኖ፣ ከቅዱሳኑ በረከት አግኝቶ፣ ራሱን በቅድስና ሥፍራ አውሎ፣ ቅድስናን ተምሮ ለቅድስና የሚያበቃውን በረከት ያገኛል፡፡  እግዚአብሔር አምላካችን ሥራ የሠራበት፣ በጽኑ ተአምራት ሕዝቡን የታደገበት መንገድ እንደ ቀላል በዝምታ የሚታለፍ ሳይኾን መታሰቢያ የሚደረግለት በዓል ነው፡፡ ‹‹ተዝካረ ገብረ ለስብሐቲሁ፤ ለተአምራቱ መታሰቢያአደረገ፤›› (መዝ. ፻፲፥፬) ተብሎ እንደ ተጻፈ፡፡

ስለዚህም ኅዳር ፲፪ ቀን እግዚአብሔር በታላላቅ ተአምራት ሕዝቡን ነጻ ያወጣበት ዕለት በመኾኑ የመታሰቢያ በዓል ኾኗል፡፡ እግዚአብሔር በባሕርዩ የእርሱ ለኾኑት ቅዱሳን ክብርና ሞገስ የሚሰጥ አምላክ ነው፡፡ ሰዎች የእርሱ የኾኑትን እንዲያከብሩለት የሚፈልግ አምላክም ነው፡፡ ለዚህም ነው ‹‹እነሆም መጥተው በእግሮችህ ፊት ይሰግዱ ዘንድ እኔም እንደወደድኹህ ያውቁ ዘንድ አደርጋቸዋለሁ፤›› በማለት የተናገረው (ራዕ. ፫፥፱)፡፡ ወዳጆቹን ማክበር እግዚአብሔርን ማክበር ነው፡፡ እነርሱን ማሰብም እርሱን ማሰብ ነውና ነው፡፡ ‹‹የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሯችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ፡፡ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነት ምሰሏቸው›› ተብሎ እንደ ተጽፏልና (ዕብ. ፲፫፥፯)፡፡

ቅዱሳኑን መመልከት እግዚአብሔርን መመልከት ነው፡፡ ስለዚህም ይህ የከበረ ዕለት፣ እስራኤል በመንገድ ላይ እንዳይጠፉ በቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት፣ ጥበቃና መሪነት ወዳዘጋጀላቸው ሥፍራ መግባታቸውን የምናስብበት በዓል ነው፡፡ ቤቱ የእርሱ ቢኾንም መታሰቢያነቱን ለወዳጆቹ፣ ደስ ላሰኙት ቅዱሳኑ እግዚአብሔር ይሰጣል (ኢሳ. ፶፮፥፬)፡፡ ልዩ ከኾነው ስሙ ጋር ስማቸው አብሮ እንዲነሣ ያደርጋል፡፡ አድሮባቸው ሥራ ሠርቷልና እንዲሁ አይተዋቸውም፤ እንዲታሰቡለት ያደርጋል እንጂ፡፡ በቤቱም በፊቱም እነርሱ ሲታሰቡና ሲከብሩ ደስ ይሰኛል፡፡ ምንጩም ፈቃጁም እርሱ ራሱ ነውና፡፡ ‹‹እግዚአብሔርን ለሚፈሩ፣ ስሙንም ለሚያስቡ የመታሰቢያ መጽሐፍ በፊቱ ተጻፈ፤›› እንዳለ ነቢዩ (ሚል. ፫፥፲፮)፡፡ ቅዱሳኑ ስሙን በፍጹም አስበዋልና እግዚአብሔር ደግሞ ስማቸው በሌሎች (በእኛ) እንዲታሰብ ፈቅዷል፡፡ ከዚህ አኳያ ከእስራኤል ዘሥጋ ነጻ መውጣት ጋር ‹‹ስሜ በእርሱ ስለ ኾነ›› (ዘፀ. ፳፫፥፳) የተባለለት ቅዱስ ሚካኤል፣ በየዓመቱ ኅዳር ፲፪ ቀን መታሰቢያው ይከበራል፡፡

‹‹የእግዚአብሔር ሠራዊት አለቃ ኾኜ አሁን መጥቼአለሁ›› (ኢያሱ ፭፥፲፬) በማለት መልአኩ እንደ ተናገረው ኢያሱና እስራኤላውያንን የረዳቸው፣ ያጸናቸው እርሱ ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡ ዲያብሎስ በተንኮል የሙሴን መቃብር አሳይቶ ሕዝቡን በአምልኮ ጣዖት ሊጥል ሲያደባ በጣዖት ወድቀው እግዚአብሔርን በድለው እንዳይጠፉ ከፊታቸው ቀድሞ ከዲያብሎስ ስውር ሤራ የጠበቃቸው ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡ ‹‹የመላእክት አለቃ ሚካኤል ግን ከዲያብሎስ ጋር በተከራከረ ጊዜ ስለ ሙሴ ሥጋ ሲነጋገር ‹ጌታ ይገሥፅህ› አለው እንጂ የስድብን ፍርድ ሊናገረው አልደፈረም፤›› እንዲል (ይሁዳ፣ ቍ. ፱)፡፡ ዳግመኛም ቀኑን በደመና ዓምድ ከበረኃው ዋዕይ እየጋረደ፣ ሌሊቱን በብርሃን ዓምድ ጨለማውን እያስወገደ፣ ከመሰናክል እያዳነ ከመከራ እየጠበቀ እስራኤልን ነጻ አውጥቷቸዋልና ለቅዱስ ሚካኤል መታሰቢያ በዓል ተደርጎለታል (ዘፀ. ፳፫፥፳፤ መዝ. ፴፫፥፯)፡፡

በዘመነ ኦሪት የሶምሶንን አባት እና እናት ልጅ እንደሚወልዱ ባበሠራቸው ጊዜ ማኑሄ፣ ‹‹ነገርህ በደረሰ ጊዜ እንድናከብርህ ስምህ ማን ነው?›› (መሣ. ፲፫፥፲፯) በማለት የእግዚአብሔርን መልአክ መጠየቁ በምስጋና፣ በደስታ ቀናቸው ይህን ተአምራት ያሳያቸውን መልአክ ለማክበርና መታሰቢያ ለማድረግ ነበር፡፡ ይህም የቅዱሳንን በዓል የማበክበር ትውፊት ከጥንት ጊዜ ጀምሮ መኖሩን በሚገባ ያሳያል፡፡ የደስታ፣ የምስጋና ቃል የሚሰማበት ቀን ደግሞ ‹በዓል› ይባላል፡፡ መጽሐፍ ‹‹በዓል የሚያደርጉ ሰዎች የደስታ የምስጋና ቃል አሰሙ›› ይላልና (መዝ. ፵፩፥፭)፡፡ እግዚአብሔር በላያቸው ላይ አድሮ ሥራ የሠራባቸውን፣ ተአምራቱን የገለጸባቸውን ቅዱሳን መላእክት፣ ጻድቃንና ሰማዕታትን የመታሰቢያ በዓል እኛም በዚህ ዘመን በደስታና በምስጋና ማክበራንም ፍጹም አምላካዊና መንፈሳዊ መንገድ መኾኑን አምነን እንመሰክራለን፡፡ ‹‹ቀንን የሚያከብር ለጌታ ብሎ ያከብራል›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሮሜ. ፲፬፥፮)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዘመነ ጽጌ

በዶክተር ታደለ ገድሌ

ጥቅምት ፳፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ መሠረት ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭ ቀን ያለው ወቅት ‹ዘመነ ጽጌ፤ ወርኀ ጽጌ› ተብሎ ይጠራል፡፡ በግእዝ ቋንቋ ‹ጸገየ› ማለት ‹አበበ፤ አፈራ፤ በውበት ተንቆጠቆጠ፤ በደም ግባት አጌጠ፤ የፍሬ ምልክት አሣየ› እንደ ማለት ነው፡፡ ከዚሁ ግስ ላይ ‹ጽጌያት› ብሎ ስም ማውጣት ሲቻል አበባማ፣ ውበታማ፣ አበባ የያዘና የተሸከመ ለማለት ደግሞ ‹ጽጉይ› ይላል፡፡ በተለይም ዘመነ ጽጌ (ወርኀ ጽጌ) የምትከበረው በሀገራችን ከወቅቶች ሁሉ በጣም በሚወደደው የመፀው ወቅት ነው፡፡ በዚህ ምድር በልምላሜና በውበት በምትንቆጠቆጥበት ወቅት በየሳምንቱ እሑድ ከመንፈቀ ሌሊት ጀምሮ ማኅሌተ ጽጌ የሚቆሙትና ሰዓታት የሚያደርሱት ካህናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በአበባ፣ በትርንጎ፣ በሮማን፣ በእንጆሪ … እየመሰሉ ለፈጣሪ መዝሙርና ምስጋና ያቀርባሉ፡፡

በዘመነ ጽጌ ‹‹ጊዜ ገሚድ በጽሐ ቃለ ማዕነቅ ተሰምዓ በምድርነ፤ ተመየጢ ተመየጢ ወንርዓይ ብኪ ሰላመ፤ እንዘ ተሐቅፊዮ ለሕፃንኪ፤ ክበበ ጌራ ወርቅ ጽሩይ በዕንቈ ባሕርይ ዘየኀቱ፤ አክሊለ ጽጌ ማርያም፤ ንዒ ርግብየ ወንዒ ሠናይትየ፤ እንተ ሐዋርያት ይሴብሑኪ መላእክት ይትለአኩኪ፤ ንዒ እምሊባኖስ ሥነ ሕይወት፤ ቡራኬሁ ለሴም፤ ተናግዶቱ ለአብርሃም መዓዛሁ ለይስሐቅ ወሰዋስዊሁ ለያዕቆብ ወናዛዚቱ ለዮሴፍ …›› ይህን የመሳሰሉ ኃይለ ቃላትን እያነሡ ሊቃውንቱና ምእመናኑ እግዚአብሔርንና እመቤታችንን ያመሰግናሉ፡፡

ይህም ማለት ‹‹… በአበባው ወቅት መሆን የሚገባው ነገር ሁሉ ደረሰ፡፡ የአዕዋፍ ውዳሴ ቃልም በምድራችን ተሰማ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ! በአንቺ ሰላምን ማየት እንችል ዘንድ መመለስን ተመለሺ፡፡ ልጅሽን እንዳቀፍሽ፤ ክበቡ ያማረ ወርቅ እንደ ተጎናጸፍሽ የአበባ አክሊል ማርያም ርግቤ፣ ደጌ ሆይ! ነይ፡፡ ሐዋርያት የሚያመሰግኑሽ፤ መላእክት የሚላላኩሽ፤ የሕይወት መሠረት ከሊባኖስ ነይ፡፡ የሴም በረከቱ፤ የአብርሃም መስተንግዶው፤ የይስሐቅ ሽቶው፤ የያዕቆብ መሰላሉ፤ የዮሴፍ አጽናኙ …›› በሚሉና በሌሎችም የዜማ ስልቶች ካህናትና ዲያቆናት፤ ደባትር (ደብተሮች) በቅኔ ማኅሌት ውስጥ ጧፍ እያበሩና እየዘመሩ፤ ከበሮ እየመቱ፤ ጸናጽል እያንሹዋሹ፤ በመቋሚያ አየሩን እየቀዘፉና መሬቱን እየረገጡ፤ እየወረቡ ሌሊቱን ሙሉ ለእግዚአብሔር ምስጋና ያቀርባሉ፡፡

ሰዓታት የሚያደርሱ ካህናትም፡- ‹‹ትመስሊ ምሥራቀ፤ ወትወልዲ መብረቀ፤ ወታገምሪ ረቂቀ፡፡ ትመስሊ ፊደለ፤ ወትወልዲ ወንጌለ፤ ወታገምሪ ነበልባለ፡፡ ትመስሊ ጽጌ ረዳ፤ ወትወልዲ እንግዳ፤ ወታድኅኒ እሞተ ፍዳ … ሐረገ ወይን ሐረገ ወይን ዐፀደ ወይን አንቲ ማርያም›› ማለት፡- ‹‹በምሥራቀ ፀሐይ የምትመሰየሚው፤ እንደ መብረቅ ኃያል የሆነውን ጌታን የወለድሽ፤ ረቂቅ ምሥጢርን የምትችዪ፤ እንደ ፊደል ባለ ብዙ ዘር (ሆሄያት) የሆንሽ፤ ወንጌልን የወለድሽ፤ ነበልባለ እሳትን (ክርስቶስን) የተሸከምሽ፤ በጽጌ ረዳ አምሳል የምትመሰየሚው ቅድስት ማርያም ሆይ! የዓለሙን እንግዳ ፈጣሪን የወለድሽ፤ ከፍዳ ሞት የምታድኚ፤ የወይን ሐረግ የወይን ዐፀድ (ተክል) አንቺ ነሽ …›› እያሉ ያመሰግናሉ፡፡

‹‹እምግብጽ ጸዋዕክዎ ለወልድየ ለክብረ ቅዱሳን፤ ለቅዱሳን ክብር ልጄን ከግብጽ ጠራሁት›› በማለት ነቢዩ ሆሴዕ በምዕራፍ ፲፩ ቍጥር ፩ እና ፪ ላይ አስቀድሞ እንደ ተናገረው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በልጅነቱ ወደ ምድረ ግብጽ (ምስር) የተሰደደው የነቢያት ትንቢት ይፈጽም ዘንድ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሕፃናትን በመፍጀት ከሚታወቀው ከአረመኔው ንጉሥ ከሄሮድስ ለማምለጥ ነው፡፡ አምላካችን ክርስቶስ ያለጊዜው (ዕለተ ዓርብ) ደሙ አይፈስምና፡፡ ስለዚህም ‹‹ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ምድረ ግብጽ ሽሽ፤ ሄሮድስ ሕፃኑን ለመግደል ይፈልጋልና›› ብሎ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለዮሴፍ በነገረው ቃል መሠረት ሕፃኑንና እናቱን ይዞ በሌሊት ወደ ግብጽ ምድር ተሰደደ፡፡ ይህንን ስደት አስመልክቶ ሰቆቃወ ድንግል የሚባለውን ቃለ እግዚአብሔር ካህናቱ በሚያሳዝን ዜማ ያደርሳሉ፤ ያቀርባሉ፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በይሁዳ ግዛት በቤተልሔም በንጉሥ ሄሮድስ ዘመን በተወለደ ጊዜ በሄሮድስ ላይ ቅንዓት አድሮበት ነበር፡፡ ‹‹ከአንተ የሚበልጥና የሚልቅ ንጉሥ በቤተልሔም ይወለዳል›› የሚል ትንቢት ይሰማ ነበር፡፡ ‹‹ወአንቲነ ቤተ ልሔም ምድረ ኤፍራታ ኢትቴሐቲ እምነገሥተ ይሁዳ እስመ እምኔኪ ይወፅዕ ንጉሥ፤ አንቺ የኤፍራታ ምድር ቤተልሔም ሆይ! ብዙ ነገሥታት ከነገሡባት ከይሁዳ አታንሺም፤ የዓለም ንጉሥ የሚሆን ከአንቺ ይወጣልና›› የሚለው የነቢያት ትንቢት ሄሮድስን አስጨነቀው፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ ሰብአ ሰገል (የጥበብ ሰዎች) ‹‹የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ የት አለ? የምሥራቅ ኮከብ እየመራን መጥተናል፡፡ እንሰግድለት ዘንድ አመላክቱን›› ብለው ወደ ኢየሩሳሌም ብዙ መብዓ ይዘው መምጣታቸውን ሄሮድስ ሲሰማ ዓይኑ ፈጠጠ፤ ሰውነቱም ደነገጠ፡፡ ስለዚህም ጌታችንን ሊገድለው ወደደ፡፡

ለሥልጣን ስሱ የነበረው ሄሮድስ ‹‹ከእኔ በላይ ሌላ ምን ንጉሥ አለ?›› ብሎ ተቆጣና የካህናትን አለቆችና የሕዝቡን ጻፎች (ፈሪሳውያንን) አስጠርቶ በመሰብሰብ ‹‹ክርስቶስ የተወለደው የት ነው?›› ብሎ አፈጠጠባቸው፡፡ በኋላም አንደበቱን አለሰለሰና ‹‹እውነት ከሆነ እኔም እሰግድለት ዘንድ ፈልጉልኝ›› አለ ብልጡ ንጉሥ፡፡ ካህናቱም ከልቡ መስሏቸው ‹‹‹አንቺ ቤተልሔም የይሁዳ ምድር ከይሁዳ ገዢዎች ከቶ አታንሽም፤ ሕዝቤን እስራኤልን የሚጠብቅ መስፍን ከአንቺ ይወጣልና› ተብሎ በተጻፈው መሠረት ጌታችን የተወለደው በይሁዳ በቤተልሔም ነው፡፡ ሰብአ ሰገልም አምኃ (እጅ መንሻ) ለማቅረብ የሚሔዱት ወደዚያው ነው›› ብለው እቅጩን ነገሩት፡፡ ሄሮድስም መንገደኞቹን ሰብአ ሰገልን ጠራና ‹‹ወገኖቼ አደራችሁን ለተወለደው ልጅ መብዓ አድርሳችሁ በእኔ በኩል ተመለሱ፡፡ እኔ ደግሞ ሒጄ እሰግድለት ዘንድ ሁኔታውን ትነግሩኛላችሁ›› ብሎ አሰናበታቸው፡፡

እነርሱም ‹‹ኧረ ግድ የለም ንጉሥ ሆይ!›› ብለው የምሥራቁ ኮከብ እየመራቸው፤ ሕፃኑ ባለበት ቦታ ላይ ደርሰው፤ ወደ ቤትም ገብተው፤ ወድቀው ለሕፃኑ ሰገዱለት፡፡ ሳጥኖቻቸውንም ከፍተው እጅ መንሻ ወርቅና ዕጣን፣ ከርቤም አቀረቡለት፡፡ ሲመለሱ በሌላ መንገድ እንዲሔዱ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በሕልም ነግሯቸው ነበርና በሌላ መንገድ ወደ ሀገራቸው ተጓዙ፡፡ ሄሮድስ ይህን በመሰማ ጊዜም የበለጠ ቅንዓት አደረበትና ሕፃኑን ለመግደል ይበልጥ ተነሣሣ፡፡ በሐሳብ የተጨነቀው ንጉሥ ጉዳዩን ለመጠንቁል (ለጠንቋይ) አማከረ፡፡ ጠንቋይ መቼም እበላና እወደድ ባይ ነውና ‹‹‹እስከ ሁለትና ሦስት ዓመት ዕድሜ ለአላቸው ወንድ ሕፃናት ቀለብ ልሠፍርላቸው አስቤአለሁና ተሰብሰቡ› ብለው አዋጅ ያስነግሩ፡፡ ሕፃናቱን ሲሰበሰቡልዎም ያን ጊዜ ሁሉንም ይግደሏቸው፡፡ ከዚያ ውስጥ የእርስዎ የወደፊት ጠላት አብሮ ይሞታል›› ብሎ መከረው፡፡ በዚህ መሠረት በመቶ ሺሕ የሚቆጠሩ ሕፃናትን ሄሮድስ አስፈጅቷል፡፡ ‹‹ድምፅ በራማ ተሰማ፤ ለቅሶና ብዙ ዋይታ፡፡ ራሔል ስለ ልጆቿ አለቀሰች፡፡ መጽናናትም አልወደደችም፤ የሉምና›› የሚለው ትንቢትም ተፈጸመ፡፡

ከሦስት ዓመት ከመንፈቅ የግብጽ ስደት በኋላ ሊቃውንቱ፡- ‹‹ተመየጢ ማርያም ሀገረኪ ናዝሬተ፣ በላዕሌኪ አልቦ ዘያበጽሕ ሁከተ፣ ወኢትጎንድዪ በግብጽ ከመ ዘአልብኪ ቤተ፣ ዘየኀሥሦ ለወልድኪ ይእዜሰ ሞተ፣ በከመ ነገሮ መልአክ ለዮሴፍ ብሥራተ›› እያሉ ከስደት መመለሷን ያበሥራሉ፡፡ ትርጉሙም፡- ‹‹ማርያም ሆይ! ወደ ሀገርሽ ወደ ናዝሬት ተመለሺ፡፡ በአንቺ ላይ ሁከት የሚያመጣ ማንም የለም፡፡ ቤት እንደሌለሽ ሁሉ በግብጽ አትቆይ፡፡ ለዮሴፍ በሕልሙ መልአክ እንደ ነገረው የሕፃኑን ነፍስ የፈለገው (ጠላት ሄሮድስ) ሞቷልና›› ማለት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን በዐርባው ቀን (በዘመነ ጽጌ) ወቅት የማርያምን የሽሽትና የመመለስ (የሚጠት) ታሪክ እያነሡ ውዳሴ የሚያቀርቡትና ማኅሌት የሚቆሙት በዚሁ ምክንያት ነው፡፡ በዚህ ወቅት ለእመቤታችን ክብር ሲባል የፈቃድ ጾም የሚጾሙ ምዕመናንና ምዕመናትም ብዙዎች ናቸው፡፡

መምህር ክፍሌ ወልደ ጻድቅ ‹የጽጌ ዚቅ› በሚለው፣ ዓመተ ምሕረት በሌለውና በእጅ ጽሑፍ ተዘጋጅቶ በታተመው መጽሐፋቸው ከገጽ 1 – 75 እንደ ገለጹት ከበዓለ ጽጌ ጋር የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፤ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፤ የቅዱን መላእክት፤ የቅዱሳም ጻድቃን እና የቅዱሳን ሰማዕታት በዓላት አብረው ይከበራሉ፡፡ ለአብነትም የሥላሴ፤ የአማኑኤል፤ የዐርባዕቱ እንስሳ፤ የሩፋኤል፤ የኪዳነ ምሕረት፤ የመጥምቀ መለኮት ዮሐንስ (ፅንሰቱ)፤ የእስጢፋኖስ፤ የወንጌላውያኑ ማቴዎስና የማርቆስ፤ የዘብዴዎስ ልጆች የያዕቆብና የዮሐንስ፤ የቶማስ ዘህንደኬ፤ የሐና፤ የአቡነ አረጋዊ፤ የቂርቆስ፤ የአባ ኤዎስጣቴዎስ፤ የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ፤ የአብርሃ አጽብሐ ነገሥትና የሌሎችም ቅዱሳን በዓላት ተጠቃሾች ናቸው፡፡

በአጠቃላይ በዘመነ ጽጌ ዘወትር እሑድ፣ እሑድ በመላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ማኅሌት በመቆም ታላቅ በዓል ይደረጋል፡፡ የዐርባ ቀኑ ዘመነ ጽጌ (ወርኀ ጽጌ) መታሰቢያነቱ ለቅድስት ድንግል ማርያምና ለጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እመቤታችን ልጇን ይዛ ከሰሎሜና ከዮሴፍ ጋር ወደ ምድረ ግብጽ በተሰደዱ ጊዜ የደረሰባትን ጭንቅና ውኃ ጥም፤ ግፍና እንግልት ለማስታወስና ከግብጽ ወደ ሀገሯ ናዝሬት መመለስዋን (ሚጠቷን) ለመዘከር ሲባል በዘመነ ጽጌ የደመቀ አገልግሎት ይከናወናል፡፡ በዚህ ወቅት የሚቆመው የሰንበት ማኅሌቱ፣ መዝሙሩና ቅዳሴው እንደዚሁም የሚቀርበው የክብር ይእቲና የዕጣነ ሞገር ቅኔ ሁሉ በዘመነ ጽጌ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ተዝካሩን አውጥቶ ክርስቶስን የተከተለ ሐዋርያ

ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ

በዲያቆን ዘክርስቶስ ጸጋዬ

ጥቅምት ፲፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

አንድ ሰው ከቅፍርናሆም ገበያ ወደ ገሊላ ባሕረ ወደብ በሚወስደው ዐቢይ መንገድ ዳር ቁጭ ብሎ ነጋዴዎችን ቀረጥ ያስከፍል ነበር፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚያ ሲያስተምር ቀረጥ ከሚሰብስብበት ቦታ ጠርቶ ‹‹ተከተለኝ›› አለው፡፡ እርሱም ሥራውን ርግፍ አድርጎ ትቶ ተከተለው፡፡ ለሐዋርያነት በተጠራ ጊዜ በቤቱ ድግስ አዘጋጅቶ ለጌታችን ግብዣ አቅርቦ፣ ለድሆች መጽውቶ፣ የቁም ተዝካሩን አውጥቶ ክርስቶስን ተከተለው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ (ማቴ. ፱፥፲-፲፫)፡፡

ማቴዎስ ማለት ‹የእግዚአብሔር ስጦታ፣ ኅሩይ እመጸብሓን (ከቀራጮች መካከል የተመረጠ)› ማለት ነው፡፡ አባቱ ዲቁ እናቱ ደግሞ ክሩትያስ ይባላሉ፡፡ አባቱ (ዲቁ) በሌላ ስም ‹እልፍዮስ› (Aliphaeus) እየተባለ ይጠራል፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ ብሔረ ሙላዱ (የተወለደበት አገር) ናዝሬት፤ ነገዱም ከነገደ ይሳኮር ነው፡፡ የቀድሞ ስሙ ‹ሌዊ› ነበር (ማር. ፪፥፲፬)፡፡ በዕብራውያን ዘንድ በሁለት ስሞች መጠራት የተለመደ ሲኾን ሌዊ ከቀድሞ ጀምሮ ይጠራበት የነበረ፤ ማቴዎስ ደግሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከተከተለ በኋላ የተጠራበት ስሙ እንደ ኾነ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ያስረዳሉ፡፡

የቅዱስ ማቴዎስ ለሐዋርያነት መጠራት

ቅዱስ ማቴዎስ በቅዱሳን ሐዋርያት የስም ዝርዝር ላይ በራሱ ወንጌል በስምንተኛ፤ በማርቆስና በሉቃስ ወንጌል ደግሞ በሰባተኛ ቍጥር ተጠቅሷል (ማቴ. ፲፥፫)፡፡ በቀድሞ ሥራው ቀራጭ (የሮማውያን ግብር ሰብሳቢ) ነበር፡፡ የቀራጭነት ሥራውን ይሠራ የነበረውም በገሊላው ገዥ በሄሮድስ አንቲጳስ ሥር የነበረ ሲኾን ቦታውም በገሊላ ባህር አጠገብ በምትገኘው ደማቋ ከተማ ቅፍርናሆም ነበር፡፡ ዛሬ ይኼ ቦታ በእሾኽ ታጥሮ የጥንቱን የገበያ ምልክት ይዞ ይገኛል፡፡ የእልፍዮስ ልጅ ሌዊ በዚህ የመቅረጫ ቦታ ተቀምጦ የዓሣ እና የሌላም ነገር ንግድን እየተቆጣጠረ የቀራጭነት ሥራውን ይሠራ ነበር፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚቀርጥበት ቦታ ጠጋ ብሎ ‹‹ተከተለኝ›› አለው፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ ሲጠራ ቤት፣ ንብረት የነበረው ታዋቂ ባለ ሥልጣን ነበር፡፡ ጌታችን ‹‹ተከተለኝ›› ሲለው ድሆችን በነጻ የሚያበላ፣ ድውያንን በነጻ የሚፈውስ አምላክ መኾኑን ተረድቶ ሥራውን ርግፍ አድርጎ ትቶ ተከተለው፡፡ የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዝሙር መኾኑን በቤቱ ለጌታችንና ለተከታዮቹ ግብዣ በማድረግ ግልጥ አደረገ (ሉቃ. ፭፥፳፱)፡፡ ለጌታችና ለተከታዮቹ ግብዣ ያቀረበበት ቤቱም በቅፍርናሆም የሚገኝ ሲኾን ዛሬ ላቲኖች ቤተ ክርስቲያን ሠርተውበታል፡፡

የሐዋርያው አገልግሎት

ተዝካሩን ያወጣው ሐዋርያ ከክርስቶስ ጋር በነበረበት ጊዜ ከዋለበት እያዋለ፣ ካደረበት እያደረ፣ እንዲሁም በትንሣኤና በዕርገቱ ጊዜ በበዓለ ኀምሳ ደግሞ ለደቀ መዛሙርት መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ጊዜ አብሮ ነበር (ማቴ. ፲፥፩-፭፤ ሉቃ. ፲፰፥፴፩)፡፡ ከዚያም ሰባቱ ዲያቆናት እስከ ተመረጡበትና እስጢፋኖስም እስከ ተገደለበት ቀን ድረስ ከዚያም በኋላ ለተወሰነ ጊዜ በኢየሩሳሌም ከሐዋርያት ጋር አብሮ ነበር፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት ዓለምን በዕጣ ሲከፋፈሉም ለእርሱ በደረሰው ሀገረ ስብከት በምድረ ፍልስጥኤም ገብቶ ጌታ ከፅንስ ጀምሮ ያደረጋቸውን ተአምራት፣ ያስተማረውን ትምህርት፣ የሠራውን ትሩፋት ቢነግራቸው ብዙዎች ከሕገ ኦሪት ወደ ሕገ ወንጌል፣ ከገቢረ ኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ ተመለሰው፣ በክርስቶስ አምነው ተጠምቀዋል፡፡

 በካህናት አገር ወንጌልን መስበኩ

ቅዱስ ማቴዎስ በደመና ተጭኖ በጌታችን ትእዛዝ ወደ ሀገረ ካህናት እንደ ተወሰደ በገድለ ሐዋርያት እና በመጽሐፈ ስንክሳር ተመዝግቦ እናገኛለን፡፡ በዚያም ወደ ከተማው መግቢያ ደጅ በደረሰ ጊዜ አንደ ወጣት ብላቴና አገኘ፡፡ ወደ ከተማው ለመግባት እንዴት እንደሚችል ቢጠየቀው ወጣቱ ብላቴናም ‹‹እራስኽንና ጺምኽን ካልተላጨኽ፣ በእጅህም ዘንባባ ካልያዝኽ መግባት እትችልም›› ሲል መለሰለት፡፡ ይህም ነገር ለሐዋርያው ማቴዎስ አስጨንቆት ሲያዝን አስቀድሞ ያነጋገረው ያ ወጣት ብላቴና ዳግም በስሙ ጠራው፡፡ ሐዋርያውም ‹‹ወዴት ታውቀኛለህ?›› አለው፡፡ እርሱም ‹‹እኔ ጌታህ ኢየሱስ ነኝ፤ አሁንም እንደ ነገርኹኽ አድርግ፡፡ እኔም ካንተ ጋር አለሁ፡፡ ካንተም አልርቅም›› አለው፡፡

ከዚያን በኋላ ጌታችን እንዳዘዘው አድርጎ ወደ ካህናት አገር ገባ፡፡ በዚያም ከጣዖቱ ካህናት አለቃ ከአርሚስ ጋር ተገናኘ፡፡ ከእርሱም ጋር ስለ አማልክቶቻቸው ተነጋገረና ‹‹ራሳቸውን ማዳን የልቻሉ ሌላውን እንዴት ያድናሉ?›› ብሎ ድንቅ ተአምራትን በማድረግ ጣዖቶቻቸውን አቃጠላቸው፡፡ በዚያን ጊዜም ከአርሚስ ጋር ብዙዎች ሰዎች አመኑ፡፡ ቅዱስ ማቴዎስም አጠመቃቸው፡፡ ከሰማይ ምግብ አውርዶም መገባቸው፡፡

የአገሩም ንጉሥ የሐዋርያውን ድንቅ ስራ በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጥቶ ከአርሚስ ጋር ሐዋርያውን ወደ እሳት በጨመረው ጊዜ ጌታችን ከእሳቱ አዳናቸው፡፡ ከዚያን በኋላ በሚያሰቃያቸው ነገር ሲያስብ ንጉሡ ልጁ መሞቱን ሰማ፡፡ በዚህም እያዘነ ሳለ ሐዋርያው ማቴዎስ ‹‹ልጅህን እንዲያስነሡት ወደ አማልክትህ ለምን አትለምንም?›› አለው፡፡ ንጉሡም ‹‹አማልክት የሞተ ማንሣት እንዴት ይችላሉ?›› ብሎ መለሰ፡፡ ቅዱስ ማቴዎስም ‹‹ብታምንስ የእኛ አምላክ ልጅኽን ከሞት ማስነሣት ይችላል›› አለው፡፡ ንጉሡም ‹‹ልጄ ከሞት ከተነሣ እኔ አምናሁ›› አለው፡፡ በዚያን ጊዜ ሐዋርያው ክብር ይግባውና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸለየና የንጉሡንም ልጅ ከሞት አስነሣው፡፡ ንጉሡም በጌታችን አመነ፡፡ የአገሩ ሰዎችም ዂሉ አመኑ፡፡ የቀናች ሃይማኖትንም አስተምሮ ክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው፡፡ የጣዖቱ ካህን የነበረው አርሚስንም ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾመላቸው፡፡

የማቴዎስ ወንጌል

ጎርጎርዮስ ዘእንዚናንዙ የቅዱሳት መጻሕፍትን ቀኖና በጠቀሰበት ጽሑፉ ቅዱስ ማቴዎስ ከአይሁድ ወደ ክርስትና ለተመለሱ ዕብራውያን ወንጌሉን እንደ ጻፈው ሲገልጽ ‹‹ማቴዎስ ለዕብራውያን ተአምራተ ኢየሱስን ጻፈ›› በማለት ተናግሯል፡፡ በመቅድመ ወንጌል ትርጓሜ ላይም እንዲህ ይላል፤ ‹‹ምድረ ፍልስጥኤም ለማቴዎስ በዕጣ ደረሰችው፡፡ ከዚያ ገብቶ ጌታ ከፅንስ ጀምሮ ያደረገውን ተአምር፣ ያስተማረውን ትምህርት፣ የሠራውን ትሩፋት ቢነግራቸው እስራኤል ናቸውና ከኦሪት ወደ ወንጌል፣ ከገቢረ ኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ ተመለሱ፤ አመኑ፤ ተጠመቁ፡፡ ትምህርት ካልደሰበት ለማዳረስ ወጥቶ በሚሔድበት ጊዜም ‹በቃል ያለ ይረሳል፤ በመጽሐፍ ያለ ይወረሳል› ብለውት ጽፎላቸዋል››፡፡

የሐዋርያው አገልግሎት በኢትዮጵያ 

አውሳብዮስ ዘቂሣርያ እና ሩፊኖስ የጻፏቸው ማስረጃዎች እንደሚያስረዱት ቅዱስ ማቴዎስ በእስራኤል፣ በኢትዮጵያ፣ በፋርስ፣ በባቢሎን፣ በዓረቢያ፣ በግሪክ፣ በፍልስጥኤም እና በብሔረ ብፁዓን ወንጌልን አስተምሯል፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት ቅዱስ ማቴዎስ በአገራችን ኢትዮጵያ በትግራይ አካባቢ ከዓድዋ አውራጃ በስተምዕራብ ልዩ ስሙ ናዕይር በተባለው ቦታ ወንጌልን አስተምሯል፡፡

ሐዋርያው በብሔረ ብፁዓን

ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ ብሔረ ብፁዓን በደመና ተጭኖ ሔዶ ማስተማሩን ገድለ ዞሲማስ (ዘሲማስ) ያስረዳል፡፡ ከቅዱስ ማቴዎስ በኋላ በብሔረ ብፁዓን ስለሚኖሩ ወገኖች አኗኗር በጥልቀት በቀሲስ ዞሲማስ የተዘረዘረ ሲኾን ለእነዚህ ወገኖች ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ቅዱስ ማቴዎስም ወንጌልን እንዳስተማሯቸው በመጽሐፈ ገድሉ ተጠቅሷል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዂልጊዜ በየበዓላቸው ወደ ብሔረ ብፁዓን መሔዱ፣ ቅዱስ ማቴዎስም ከቅዱሳን መላእክት እና ሄሮድስ ካስገደላቸው አንድ መቶ ዐርባ አራት ሺሕ ሕፃናት ጋር እግዚአብሔርን ማመስገኑ ተገልጿል፡፡

የሐዋርያው ተጋድሎና የምስክርነቱ ፍጻሜ

የቅዱስ ማቴዎስ ተጋድሎውና የምስክርነቱ ፍጻሜ ሲቃረብ ወደ አንዲት ከተማ ገብቶ አስተማረ፡፡ በዚያም ብዙዎችንም አሳመነ፡፡ አገረ ገዢውም ይዞ ከወኅኒ ቤት ጨመረው፡፡ በወኅኒ ቤቱም አንድ እጅግ የሚያዝን እስረኛ አገኘና ስለ ሐዘኑ ጠየቀው፡፡ እርሱም ብዙ የጌታው ገንዘብ ከባሕር እንደ ሰጠመበት ነገረው፡፡ ሐዋርያው ማቴዎስም እስረኛው የጠፋበትን ገንዘብ የሚያገኝበትን የባሕር ዳርቻ ጠቆመው፡፡ እስረኛውም ሐዋርያው በነገረው መሠረት የጠፋውን ገንዘብ አግኝቶ ለጌታውም ሰጠው፡፡ ጌታውም ከየት እንዳገኘው ቢጠይቀው ከወኅኒ ቤት ባገኘው በሐዋርያው ማቴዎስ ጥቆማ የጠፋውን ገንዘብ ሊያገኘው መቻሉን ነገረው፡፡ ጌታው ግን ሊያምነው አልቻለም ነበር፡፡

ይልቁንም እጅግ ተቆጥቶ ሐዋርያውን ከእስር ቤት አስወጥቶ ወደ ንጉሡ ወሰደው፡፡ ንጉሡም ተዝካሩን አውጥቶ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የተከተለውን ሐዋርያ ቅዱስ ማቴዎስን ወዲያው በሰይፍ ራሱን እንዲቆርጡት፣ ሥጋውንም ለሰማይ ወፎች እንዲጥሉት አዘዘ፡፡ የንጉሡ ወታደሮችም በታዘዙት መሠረት ጥቅምት ፲፪ ቀን በ፷ ዓ.ም የሐዋርያውን አንገት በሰይፍ ቆርጠው ራሱን ለብቻ፣ ሰውነቱን ለብቻ አድርገው አሞሮች እንዲበሉት ጥለውት ሔዱ፡፡ ምእመናንም ራሱንና ቀሪው ሰውነቱን በአንድ አድርገው ካባቶቹ መቃብር እንዲቀበር አደረጉ፡፡ ያ ሐዘንተኛ እስረኛም የቅዱስ ማቴዎስን መገደል ሲሰማ ለሦስት ቀናት እያዘነ አለቀሰ፡፡ ከቅዱስ ማቴዎስ ሞት በኋላ አምስት ቀናት ቆይቶ እርሱም ዐረፈ፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን! እኛንም ተዝካሩን አውጥቶ፣ ሥልጣኑንና ሥራውን ትቶ፣ የሚበልጠውን ሰማያዊ መንግሥት ሽቶ ክርስቶስን በተከተለው ሐዋርያ በቅዱስ ማቴዎስ ጸሎት ይማረን፡፡ በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡- የጥቅምት ፲፪ ቀን ስንክሳር እና ገድለ ሐዋርያት፡፡

ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌላዊ

ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌላዊ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ጥቅምት ፲፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም 

የጌታችን፣ አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አምላካዊ ትእዛዝ ተቀብለው ወንጌልን ለመላው ዓለም በማብሠር መምለክያነ ጣዖትን ወደ አሚነ እግዚአብሔር፣ አሕዛብን ወደ ክርስትና ከመለሱ ቅዱሳን ሐዋርያት መካከል ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ አንደኛው ነው፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ አገሩ ናዝሬት፣ የዘር ሐረጉም ከይሳኮር ነገድ ሲኾን አባቱ እልፍዮስ (ዲቁ)፣ እናቱ ደግሞ ካሩትያስ ይባላሉ፡፡ ለደቀ መዝሙርነት ከመመረጡ በፊት ‹ሌዊ› ይባል ነበረ፤ ከተጠራ በኋላ ግን ‹ማቴዎስ› ተብሏል፡፡ ‹ማቴዎስ› ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ‹ጸጋ እግዚአብሔር (የእግዚአብሔር ስጦታ)› ማለት ሲኾን ስሙን ያወጣለትም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ለወንጌል አገልግሎት የተጠራውም በቅፍርናሆም ከተማ ከቀራጭነት ሥራ ላይ ነው (ማቴ. ፱፥፱-፲፫፤ ሉቃ. ፭፥፳፯-፴፪)፡፡

ቅዱስ ማቴዎስ ቍጥሩ ከ፲፪ቱ ሐዋርያት ሲኾን ከ፬ቱ ወንጌሎች አንደኛውን የጻፈው እርሱ በመኾኑ ‹ወንጌላዊ› እየተባለ ይጠራል፡፡ ወንጌሉን የጻፈውም ጌታችን ባረገ በ፰ኛው ዓመት መጨረሻ በ፵፩ (፵፪) ዓ.ም፣ ቀላውዴዎስ ቄሣር በነገሠ በመጀመሪያው ዘመን ነው፡፡ ወንሉን የጻፈበት ቋንቋ ዕብራይስጥ ሲኾን ጽሕፈቱንም በፍልስጥኤም አገር ጀምሮ በህንድ ፈጽሞታል (ማቴ. ፳፰፥፳)፡፡

ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌሉን የጻፈበት ምክንያትም በሀገረ ስብከቱ በፍልስጥኤም ጌታችን ከፅንስ ጀምሮ እስከ ዕርገቱ ድረስ ያደረጋቸውን ተአምራት፣ ያስተማረውን ትምህርትና የሠራቸውን ትሩፋቶች ሲያስተምራቸው ብዙ አሕዛብ ከኦሪት ወደ ወንጌል፤ ከገቢረ ኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ ተመልሰዋል፡፡ እነዚህ ምእመናን ‹‹በቃል ያለ ይረሳል፤ በመጽሐፍ ያለ ይወረሳልና ያስተማርኸንን ጻፍልን›› ብለውት፤ አንድም እንደ አባትነቱ ከራሱ አንቅቶ (አመንጭቶ)፤ አንድም አይሁድ ክርስቲያኖችን ‹‹ክርስቶስ ወልደ ዳዊት ወልደ አብርሃም መኾኑን ሠፍራችሁ፣ ቈጥራችሁ አስረዱን›› ቢሏቸው ለማስረዳት የዕውቀት ማነስ ነበረባቸውና እርሱ ጽፎላቸዋል፡፡

መምህራነ ቤተ ክርስቲያን እንደሚስተምሩት የማቴዎስ ወንጌል በውስጡ ከ፻፶ በላይ የብሉይ ኪዳን ጥቅሶችን ማካተቱ አይሁድን ለማሳመን የተጻፈ ለመኾኑ ማስረጃ ነው፡፡ የማቴዎስ ወንጌል ከኦሪታዊ ይዘቱ አኳያ በመጀመሪያ ተቀመጠ እንጂ የተጻፈው ግን ከማርቆስ ወንጌል ቀጥሎ እንደኾነም መምህራኑ ያስረዳሉ፡፡ ወንጌሉን ከጻፈ በኋላም ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሶ አፓንጌ በሚባል አገር ወንጌልን በመስበክ ብዙዎችን በክርስቶስ አሳምኗል፡፡ የማቴዎስን ወንጌል ወንጌላዊው (ሐዋርያው) ዮሐንስ በእልአንሳን፣ በህንድና በኢየሩሳሌም አገሮች እየተረጐመ አስተምሮታል፡፡ የእርሱ ስብከት በመጽሐፍ ቅዱስ አለመጠቀሱም መላ ሕይወቱን ለክርስቶስ አገልግሎት የሰጠ ሐዋርያ መኾኑን እንደሚያሳይ መምህራን ይመሰክራሉ፡፡

ቅዱስ ማቴዎስ በወንጌሉ ‹‹ወልደ ዳዊት፣ ወልደ አብርሃም›› በማለት የክርስቶስን ምድራዊ ልደት (ሰው መኾን) ጽፏልና ከአራቱ የኪሩቤል ገጽ መካከል በአንደኛው በገጸ ሰብእ ይመሰላል፡፡ የኤፌሶን ወንዝ ፈለገ ሐሊብ ይባላል፤ ርስትነቱም ለሕፃናት ነው፡፡ ቅዱስ ማቴዎስም በዘር የሚወለዱ አበውን ልደት ጽፏልና፤ ዳግመኛም ሄሮድስ ስላስፈጃቸው ሕፃናት ተናግሯልና በኤፌሶን ወንዝ ይመሰላል፡፡

ወንጌልን አስተምሮ ብዙዎችን ወደ አሚነ እግዚአብሔር ከመለሰ በኋላ ጌታችን ወደ ካህናት አገር እንዲሔድና የካህን ልብስ ለብሶ፣ ፀጉሩንና ጺሙን ተላጭቶ፣ በቀኝ እጁ ዘንባባ ይዞ ወደ አገሩ ቅፅር እንዲገባ ስላዘዘው በደመና ተጭኖ ሔዶ ወደ ቤተ ጣዖታቱ ገብቶ በጸለየ ጊዜ መብረቅ የመሰለ ብርሃን ወረደ፡፡ የአምላክን ከሃሊነት ለመግለጥ በተከሠተው ርዕደ መሬትም የአገሩ ጣዖታት ዂሉ ወድቀው ተሰባበሩ፡፡ አርሚስ የሚባለው የጣዖቱ ካህንም ካየው አምላካዊ ብርሃንና ድንቅ ተአምር የተነሣ በክርስቶስ አምኖ ከተጠመቀ በኋላ የቅዱስ ማቴዎስ ረድእ ኾኗል፡፡

ይህ ክሥተትም በአጭር ጊዜ ውስጥ ብዙዎችን በክርስቶስ እንዲያምኑ አድርጓቸዋል፡፡ ያማኞች ቍጥርም ፬ ሺሕ እንደ ነበረ በገድለ ሐዋርያት ተጠቅሷል፡፡ ከዚህ በኋላ የንጉሡ ልጅ በሞተ ጊዜ ቅዱስ ማቴዎስ ወደ እግዚአብሔር ጸልዮ ከሞት ቢያስነሣው ንጉሡ፣ ቤተሰቦቹና የአገሩ ሰዎች በኢየሱስ ክርስቶስ አምነው አጵሎን የተባለውን ጣዖት በእሳት አቃጥለው ቤተ ጣዖቱን የአምልኮተ እግዚአብሔር መፈጸሚያ ሥፍራ አድርገውታል፡፡ ቅዱስ ማቴዎስም አርሚስን ኤጲስ ቆጶስ በማድረግ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾሞላቸዋል፡፡

በገድለ ሐዋርያት እንደ ተጠቀሰው ቅዱስ ማቴዎስ ከማረፉ በፊት በደመና ተነጥቆ ብሔረ ብፁዓን ገብቷል፤ በዚያም ሄሮድስ በግፍ በጨፈጨፋቸው ሕፃናት ክብረ በዓል ጌታችን ወደ እነርሱ ሲመጣ፣ መላእክትም በዙሪያው ከበው ሲያመሰግኑት ያይ ነበር፡፡ ከዚያ ተመልሶም በየአገሩ እየዞረ ወንጌልን አስተምሯል፤ ካስተማረባቸው አገሮችም ፍልስጥኤም፣ ፋርስ፣ ባቢሎን፣ ኢትዮጵያና ዓረቢያ ይጠቀሳሉ፡፡ የማስተማር ተልእኮው የተከናወነውም በታንሿ እስያ ውስጥ ነው፡፡ ግሪካውያን አሕዛብ ‹‹አምላካችንን ሰደበብን›› ብለው አሥረውት በነበረ ጊዜም ወኅኒ ቤት ኾኖ ወንጌልን ይሰብክ ነበር፡፡

ቅዱስ ማቴዎስ በ፵ ዓ.ም በአገራችን በኢትዮጵያ እየተዘዋወረ ወንጌልን እንደ ሰበከና በዘመኑ የነበሩ ኦሪታውያን ነገሥታትን ጨምሮ በርካታ አሕዛብን አስተምሮ በማጥመቅ ወደ ክርስትና ሃይማኖት እንደ መለሰ፤ እንደዚሁም ለምጻሞችን በማንጻት፣ አንካሶችን በማርታት፣ ሕሙማንን በመፈወስ፣ ሙታንን በማስነሣት ድንቅ ድንቅ ተአምራትን እንዳደረገ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትና በትግራይ ክልል በማኅበረ ጻድቃን ዴጌ ገዳም የሚገኙ የብራና መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡

ወንጌላዊው በአገልግሎቱ መጨረሻም በትርያ በምትባል አገር ሲያስተምር አገረ ገዥው አሠረው፡፡ በወኅኒ ቤቱም ጌታው ለንግድ የሰጠውን ገንዘብ ማዕበል ወስዶበት በዕዳ ምክንያት የሚያለቅስ አንድ እሥረኛ አገኘና አጽናንቶ መኰንኑ ገንዘቡን ከሕዝቡ ለምኖ እንዲከፍለው በመሻት ከእሥር እንደሚፈታው፤ ከባሕር ዳርቻም የወደቀ ወርቅ የተሞላ ከረጢት እንደሚያገኝ፤ ያንንም ለጌታው ከሰጠ በኋላ ከዕዳና ከእሥር ነጻ እንደሚኾን አስረዳው፡፡ ሰውየውም ቅዱስ ማቴዎስ የተናገረው ዂሉ ስለ ተፈጸመለት ‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ አምናለሁ›› እያለ፤ ለቅዱስ ማቴዎስ እየሰገደ በኢየሱስ ክርስቶስ ማመኑን ተናገረ፤ ደስታውን ገለጸ፡፡

ይህንን ድንቅ ተአምር የሰሙ ብዙ አሕዛብም በጌታችን አምነዋል፡፡ በዚህ ምክንያት አርያኖስ በሚባል ንጉሥ ትእዛዝ ጥቅምት ፲፪ ቀን አንገቱን በሰይፍ ተቈርጦ በሰማዕትነት ዐርፏል፤ ምእመናንም ሥጋውን በክብር ቀብረውታል፡፡ ትርጓሜ ወንጌል ደግሞ ብስባራ በምትባል አገር በደንጊያ ተወግሮ በሰማዕትነት ካረፈ በኋላ የቂሣርያ ክፍለ ዕጣ በምትኾን በቅርጣግና መቀበሩን ይናገራል፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን፡፡ እኛንም በሐዋርያው በቅዱስ ማቴዎስ ጸሎት ይማረን፤ በረከቱም ይደርብን፡፡

ምንጮች፡

  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ጥቅምት ፲፪ ቀን፤
  • የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት፤
  • የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፤
  • የማቴዎስ ወንጌል አንድምታ ትርጓሜ፤
  • ገድለ ሐዋርያት፡፡

ዘመነ ጽጌ  

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፳፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም 

በቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ በአገራችን በኢትዮጵያ የወቅቶች ሥርዓተ ዑደት መሠረት ከመስከረም ፳፮ ቀን ጀምሮ እስከ ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ፺ ቀናትን የሚያጠቃልለው ጊዜ ‹ዘመነ መጸው› ይባላል፡፡ ‹መጸው› ማለት ‹ወርኀ ነፋስ› (የነፋስ ወቅት) ማለት ሲኾን ይኸውም ‹መጸወ ባጀ፤ መጽለወ ጠወለገ› ካለው የግእዝ ግስ የተገኘ ነው፡፡ ዘመነ መጸው ከዘመነ ክረምት ቀጥሎ የሚብት (የሚገባ) የልምላሜ፣ አበባ፣ የፍሬ ወቅት ነው፡፡ በውስጡም አምስት ንዑሳን ክፍሎችን የሚያካትት ሲኾን እነዚህም፡- ዘመነ ጽጌ፣ ዘመነ አስተምህሮ፣ ዘመነ ስብከት፣ ዘመነ ብርሃን እና ዘመነ ኖላዊ ናቸው (ያሬድና ዜማው፣ ገጽ ፵፰-፵፱)፡፡

ከአምስቱ የዘመነ መጸው ክፍሎች መካከልም የመጀመሪያው ክፍል ‹ዘመነ ጽጌ› ተብሎ ይጠራል፡፡ ይህም ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፮ ቀን ድረስ ያሉትን ፵ ቀናት ያጠቃልላል፡፡ ‹ጽጌ› ቃሉ ‹ጸገየ አበበ› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን ትርጕሙም አባባ ማለት ነው፡፡ ‹ዘመነ ጽጌ› ደግሞ ‹የአበባ ወቅት፣ የአበባ ጊዜ፣ የአበባ ዘመን› ማለት ነው፡፡ ይህ ወቅት ዕፀዋት በአበባ የሚያጌጡበት፣ ምድር በአበቦች ኅብረ ቀለማት የምታሸበርቅበት፣ ወንዞች ንጹሕ የሚኾኑበት፣ ጥሩ አየር የሚነፍስበት፣ አዕዋፍ በዝማሬ የሚደሰቱበት፣ እኛም የሰው ልጆች ‹‹አሠርጎካ ለምድር በሥነ ጽጌያት፤ አቤቱ ምድርን በአበቦች ውበት አስጌጥሃት›› እያልን የዘመናት አስገኚ እና ባለቤት የኾነውን ልዑል እግዚአብሔርን የምናመሰግንበት፤ ከዚህም ባሻገር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከተወደደ ልጇ ጋር ከገሊላ ወደ ግብጽ ምድር መሰደዷን የምናስብበት ወቅት ነው፡፡

ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተ ልሔም በተወለደ ጊዜ የዘመኑ ንጉሥ ሄሮድስ ሥልጣኔን ይቀማኛል በሚል ቅናት ተነሣሥቶ ጌታችንን ለማስገደል አሰበ፡፡ ጌታችንም በተአምራት መዳን ሲቻለው የትዕግሥት፣ የትሕትና አምላክ ነውና በለበሰው ሥጋ በእናቱ በቅድስት ድንግል ማርያም ጀርባ ታዝሎ በመልአኩ ተራዳኢነት፣ በአረጋዊው ዮሴፍ ጠባቂነትና በሰሎሜ ድጋፍ ከገሊላ ወደ ግብጽ ተሰዶ ሄሮድስ እስኪሞት ድረስ ቆይቷል፡፡ ሄሮድስም ጌታን ያገኘሁ መስሎት በቤተ ልሔምና በአውራጃዋ የሚገኙ የሁለት ዓመት ከዚያ በታች የኾኑ አንድ መቶ ዐርባ አራት ሺሕ ሕፃናትን በሰይፍ አስጨርሷል፡፡

መምህራነ ቤተ ክርስቲያን እንደሚያስተምሩን የጌታችን እና የእመቤታችን የስደት ወቅት በወርኀ ግንቦት ነው፡፡ ነገር ግን ዘመነ ጽጌ የአበባ፣ የፍሬ ወቅት በመኾኑ እመቤታችንን በአበባ፣ ጌታችንን ደግሞ በፍሬ እየመሰሉ ለማመስገንና ለማወደስ በሚያስችል ምሥጢር ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የስደቱ ጊዜ ከመስከረም እስከ ኅዳር ባለው ጊዜ ውስጥ እንዲዘከር አድርገዋል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለዘለዓለሙ የማይደርቀውን የሕይወት ፍሬ ኢየሱስ ክርስቶስን ያስገኘችልን ንጽሕት የማትጠወልግ አበባ ናትና፡፡ ይህ የእመቤታችን አበባነትና የጌታችን ፍሬነትም እንደ ቅዱስ ያሬድ፣ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫና አባ ጽጌ ድንግል ባሉ ሊቃውንት ድርሰቶች በስፋት ተገልጧል፡፡ በተለይ በአባ ጽጌ ድንግል ድርሰት በማኅሌተ ጽጌ በጥልቀት ተመሥጥሯል፡፡

በአጠቃላይ በዘመነ ጽጌ በማኅሌትና በቅዳሴ ጊዜ የሚቀርቡ መዝሙራትና የሚሰጡ ትምህርቶችም ይህንኑ ምሥጢር የሚመለከቱ ናቸው፡፡ በዚህ ወቅት በሚገኙ ሰንበታት ሊቃውንቱ ሌሊቱን ሙሉ ስለ እመቤታችን አበባነትና ስለ ጌታችን ፍሬነት የሚያትት ትምህርት የያዙትን ማኅሌተ ጽጌና፣ ሰቆቃወ ድንግልን ከቅዱስ ያሬድ ዚቅ ጋር በማስማማት ሲዘምሩ፣ ሲያሸበሽቡ ያድራሉ፡፡ ቅዳሴውም በአባ ሕርያቆስ የተደረሰውና ምሥጢረ ሥጋዌን፣ ምሥጢረ ሥላሴንና ነገረ ማርያምን በጥልቅ ትምህርተ ሃይማኖት የሚያትተው ቅዳሴ ማርያም ነው፡፡ ምንባባቱም ከዚሁ ጋር ተዛማጅነት ያላቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ናቸው፡፡

በተአምረ ማርያም እና በማኅሌተ ጽጌ ተጽፎ እንደሚገኘው ጌታችን በግብጽ ምድር በስደት ሳለ ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን አድርጓል፡፡ ከእነዚህ መካከልም እናቱን እመቤታችንን የዘለፏትን ትዕማንና ኮቲባ የሚባሉ ሴቶችን ከሰውነት ወደ ውሻነት መቀየሩ፤ ውኃ በጠማቸው ጊዜ ውኃ እያፈለቀ ማጠጣቱና ይህንንም ውኃ ክፉዎች እንዳይጠጡት ማምረሩ፤ ለችግረኞችና ለበሽተኞች ግን ጣፋጭ መጠጥና ፈዋሽ ጠበል ማድረጉ፤ ‹‹የሄሮድስ ጭፍሮች ደርሰው ልጅሽን ሊገድሉብሽ ነው›› ብሎ የዮሴፍ ልጅ ዮሳ እመቤታችንን በማስደንገጡ እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ ድንጋይ ኾኖ እንዲቆይ ማዘዙ፤ መንገድ ላይ የተራዳቸው ሽፍታ ሰይፉ በተሰበረች ጊዜ ሰይፉን በተአምራት እንደ ቀድሞው ማደሱ፤ እንደዚሁም የግብጽ ጣዖታትን በአምላክነቱ ቀጥቅጦ ማጥፋቱ ተጠቃሾች ናቸው፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ጋር በተሰደደች ጊዜ የደረሰባትን መከራ በማስታወስ ዘመነ ጽጌን በፈቃዳቸው የሚጾሙ ካህናትና ምእመናን ብዙዎች ናቸው፡፡ ኾኖም ግን የጽጌ ጾም የፈቃድ ጾም እንጂ ከሰባቱ አጽዋማት ጋር የሚመደብ ስላልኾነ ጽጌን የማይጾሙ አባቶች ካህናትንና ምእመናንን ልንነቅፋቸው አይገባም፡፡ የጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ፣ የእናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ በሄሮድስ እጅ በግፍ የተሠዉ ሕፃናት በረከት አይለየን፡፡ አምላካችን በአበባ የሚመሰለው ሰውነታችን የጽድቅ ፍሬን ሳያፈራ እና ንስሐ ሳንገባ በሞት እንዳንወሰድ መልካም ፈቃዱ ይኹንልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ብዙኃን ማርያም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፳ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በቤተ ክርስቲያናችን ከሚዘከሩ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ክብረ በዓላት መካከል መስከረም ፳፩ ቀን የሚውለው በዓል ብዙኃን ማርያም በመባል ይታወቃል፡፡ በዓሉ በሁለት ዐበይት ምክንያቶች ይከበራል፤ የመጀመሪያው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሃይማኖታዊ ውሳኔ ለማዘጋጀት ከሩቅም ከቅርብም የተሰባበሰቡት ቀን፤ ሁለተኛው ደግሞ ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ዕፀ መስቀል በግሸን ደብረ ከርቤ የተቀመጠበት ዕለት መኾኑ ነው፡፡ ሁለቱንም ታሪኮች ከዚህ ቀጥለን እንመለከታቸዋለን፤

በ፫፻፳፭ ዓ.ም አርዮስ የሚባል መናፍቅ የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት አልቀበልም በሚል ክህደት እርሱ ተሰናክሎ ለሌሎችም መሰናክል ኾነ፡፡ ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት አርዮስ ክህደቱን እንዲተው ቢመክሩትም ሊመለስ አልቻለም፡፡ ይህ የአርዮስ ክህደትም በሊቃውንቱ መካከል መለያየትን ፈጠረ፡፡ ጊዜው ታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ‹‹አብያተ ጣዖታት ይትአጸዋ አብያተ ክርስቲያናት ይትረኀዋ፤ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ! አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ!›› የሚል ዐዋጅ የነገረበት ወቅት ነበርና ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ በአርዮስ ክህደት ምክንያት በኒቅያ የሃይማኖት ጉባኤ እንዲካሔድ በየአገሩ ላሉ ሊቃውንት መልእክት አስተላለፈ፡፡

በዚህም መሠረት ከሚያዝያ ፳፩ ቀን ጀምሮ እስከ መስከረም ፳፩ ቀን ድረስ ፳፫፻፵፰ (ሁለት ሺሕ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንት) ሊቃውንት በኒቅያ ተሰበሰቡ፡፡ ኒቅያ ለዚህ ጉባኤ የተመረጠችበት ምክንያትም ጳጳሱን ከማኅበረ ካህናቱ፤ ንጉሡን ከሠራዊቱ ጋር አጠቃላ ለመያዝ የምትችል ሰፊና ምቹ ቦታ ከመኾኗ ባሻገር ለኹሉም አማካይ ሥፍራ ስለነበረች ነው፡፡ በጉባኤው ከተሰበሰቡ ሊቃውንት መካከልም እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ሙታንን ያስነሡ፣ ለምጽ ያነጹ፣ አንካሳ ያረቱ፣ የዕውራንን ዓይን ያበሩ ድውያንን የፈወሱ፣ ሌላም ልዩ ልዩ ተአምር ያደረጉ፤ እንደዚሁም ስለ ርትዕት ሃይማኖታቸው በመጋደል ዓይናቸው የፈረጠ፣ እጃቸው የተቈረጠ አበው ይገኙበታል፡፡

ሊቃውንቱ ሱባዔ ይዘው በጸሎት ከቆዩ በኋላ ኅዳር ፱ ቀን በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሊቀ መንበርነት፣ በእለእስክንድሮስ አፈ ጉባኤነት ጉባኤው ተጀመረ፡፡ ንጉሡ ሊቃውንቱን ‹‹ስማችሁን፣ አገራችሁንና ሃይማኖታችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ›› ባላቸው ጊዜም ከ፳፫፻፵፰ቱ መካከል ፫፻፲፰ (ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ) ሊቃውንት ሃይማኖታቸውን ሲገልጹ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ፤ ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በመለኮት፣ በሥልጣን፣ በፈቃድ፣ በህልውና አንድ ነው›› ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ንጉሡም ‹‹ሃይማኖት እንደ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት ይኹን›› ብሎ ዐዋጅ አስነግሯል፡፡

፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በጉባኤው አርዮስን አውግዘው በመለየት ‹‹ነአምን በአሐዱ አምላክ፤ በአንድ አምላክ እናምናለን›› የሚለውን የሃይማኖት ጸሎት (የሃይማኖት መሠረት) እና ሌሎችንም የሃይማኖት ውሳኔዎች ደንግገዋል፡፡ ሊቃውንቱ ጉባኤውን ያካሔዱት ኅዳር ፱ ቀን ይኹን እንጂ በአንድነት የተሰባሰቡት መስከረም ፳፩ ቀን ስለ ነበረ ይህ ዕለት ብዙኃን ማርያም እየተባለ ይጠራል፡፡ ብዙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ለሃይማኖታዊ ጉባኤ የተሳባሰቡበት ዕለት ነውና፡፡ እነዚህ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በኦሪት ዘፍጥረት የተጠቀሱት የአብርሃም ብላቴኖች ምሳሌዎች ናቸው (ዘፍ. ፲፬፥፲፬)፡፡

በሌላ በኩል መስከረም ፳፩ ቀን የጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በአምባሰል ተራራ በግሸን ደብረ ከርቤ የገባበትና በዓሉ የከበረበት ዕለት ነው፡፡ ታሪኩም በአጭሩ የሚከተለው ነው፤

ዐፄ ዳዊት መንፈሳዊና ደግ ንጉሥ ነበሩ፡፡ በዘመናቸው በኢትዮጵያ ቸነፈር ተከሥቶ ሕዝቡ ስለ ተሰቃየባቸው እጅግ አዘኑ፤ በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ቢያመለክቱም ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላኩ ባሕታዊ መጥተው ‹‹የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል አስመጥተህ በአገርህ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አሠርተህ ብታስቀምጥ ረሃቡ፣ ቸነፈሩ ኹሉ ይታገሥልሃል›› አሏቸው፡፡ ዐፄ ዳዊትም ከብዙ ገጸ በረከት (ስጦታ) ጋር ‹‹የጌታችንን መስቀል ላኩልኝ›› የሚል መልእክት አስይዘው መልእክተኞችን ወደ ኢየሩሳሌም ሰደዱ፡፡ መልእክተኞቹም በታዘዙት መሠረት መስቀሉን ይዘው መምጣታቸውን ዐፄ ዳዊት ሲሰሙ ‹‹ክተት ሠራዊት ምታ ነጋሪት›› ብለው አሳውጀው መስቀሉን ለመቀበል ጉዞ ጀመሩ፡፡

ዐፄ ዳዊት ስናር (ሱዳን) ደርሰው ከመልእክተኞቹ ጋር ተገናኝተው መስቀሉን በክብር አጅበው ወደ መካከል ኢትዮጵያ ለማስገባት ሲነሡም ከበቅሏቸው ወድቀው ጥቅምት ፱ ቀን ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፤ በዚህም ሠራዊታቸው ተደናግጠው የጌታችንን መስቀል እዚያው ትተው የዐፄ ዳዊትን አስከሬን ይዘው ተመለሱ፡፡ መስቀሉ በስናር ከቆየ በኋላ የዐፄ ዳዊት ልጅ ዘርዐ ያዕቆብ ሲነግሡ ወደ መሃል ኢትዮጵያ አምጥተው ቤተ ክርስቲያን አሠርተው ለማስቀመጥ ቢያስቡም ምቹ ቦታ ግን ሊያገኙ አልቻሉም ነበር፡፡ ንጉሡና ሠራዊታቸው ምቹ ቦታ ሲፈልጉ መስቀሉን በኤረር ተራራ፣ በደብረ ብርሃን፣ በመናገሻ ማርያም ዓምባ፣ በእንጦጦ ጋራ ብዙ ጊዜ አስቀምጠውት ቆይተዋል፡፡

መስቀሉ በእንጦጦ ጋራ ሳለ እግዚአብሔር አምላክ ‹‹አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል፤ መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አስቀምጥ›› የሚል ቃል ለንጉሡ በራእይ ነገራቸው፡፡ መስቀሉን ወደወሎ ሀገረ ስብከት እንዲወስዱትም አዘዛቸው፡፡ ንጉሡና ሠራዊታቸው በእግዚአብሔር መሪነት መስቀሉን ይዘው ወሎ ሲደርሱም ጌታችን ወደ አምባሰል እያመለከተ ‹‹አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል፤ መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አስቀምጥ›› ይላቸው ነበር፡፡ ንጉሡ መስቀሉን ይዘው ወደ ቦታው ሲያመሩ መስቀለኛው የግሸን ተራራን አገኙ፤ በዚያም ቤተ ክርስቲያን አሠርተው በ፲፬፻፵፮ (1446) ዓ.ም የጌታችንን መስቀል በክብር አስቀምጠውታል፡፡

ከዚህ በኋላ ንጉሡ ‹‹መካከሏ ገነት፤ ዳሯ እሳት ይኹን! የበረረ ወፍ፣ የሠገረ ቆቅ አይታደንባት! በድንገት ሰው የገደለ፣ ቋንጃ የቈረጠ ወንጀለኛ አይያዝባት!›› ብለው ዐዋጅ አስነግረዋል፡፡ የእመቤታችን ጽላትም አብሮ በግሸን ደብረ ከርቤ እንዲቀመጥ አድርገዋል፡፡ ስለዚህም መስከረም ፳፩ ቀን በየዓመቱ በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡ ኀጢአታቸውን ለካህን ተናዘው፣ ንስሐ ገብተው በዚህ ዕለት ወደ ግሸን ደብረ ከርቤ በመሔድ የሚጸልዩና የሚማጸኑ ምእመናን ኹሉ እስከሰባት ትውልድ ድረስ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደሚያገኙም ጤፉት በተባለችው መጽሐፍ ተጠቅሷል፡፡ የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ፣ የእመቤታችን አማላጅነት፣ የክርስቶስ የመስቀሉ ኃይል፣ የአባቶቻችን ሊቃውንትና ነገሥታት በረከት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ / አፈወርቅ ተክሌ፤ ፳፻፭ .ም፣ አዲስ አበባ፤ ገጽ ፫፻፶፬፫፻፶፮፡፡

ተአምረ ማርያም በጼዴንያ

በዝግጅት ክፍሉ

መስከረም ፲ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ መስከረም ፲ ቀን ከሚዘከሩ በዓላት መካከል የእመቤታችን በዓል አንደኛው ሲኾን ይኸውም ጼዴንያ በምትባል አገር ከሥዕሏ ተአምር የተደረገበት ዕለት ነው፡፡ በተአምረ ማርያም እና በመጽሐፈ ስንክሳር እንደ ተመዘገበው ቅዱስ ሉቃስ ከሣላት ሥጋ የለበሰች ከምትመስል የእመቤታችን የሥዕል ሠሌዳ ቅባት ይንጠፈጠፍ ነበር፡፡ ከዚህች የእመቤታችን ሥዕል የተገለጠው ተአምርና ታሪክም በአጭሩ የሚከተለው ነው፤

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን የምትወድና በሚቻላትም ዂሉ የምታገለግላት፣ ቤቷንም ለእንግዳ ማደሪያ ያደረገች አንዲት ማርታ የምትባል ሴት ነበረች፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አባ ቴዎድሮስ የሚባሉ መነኵሴ ከእርሷ ዘንድ በእንግድነት አድረው በማግሥቱ ከቤቷ ሲወጡ ማርታ የሚሔዱበትን አገር በጠየቀቻቸው ጊዜ  እርሳቸውም ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው ቅዱሳት መካናትን እንደሚሳለሙ ነገሯት፡፡ ማርታም ከእርሷ ገንዘብ ወስደው የእመቤታችንን ሥዕል ገዝተው ይዘውላት እንዲመጡ ለመነቻቸው፡፡ መነኵሴውም በራሳቸው ገንዘብ ሥዕሉን ገዝተው እንደሚያመጡላት ቃል ገቡላት፡፡ አባ ቴዎድሮስ ኢየሩሳሌም ደርሰው ቅዱሳት መካናትን ከተሳለሙ በኋላ ሥዕሏን ሳይገዙ ወደ አገራቸው ተመለሱ፡፡ ያን ጊዜም ‹‹ሥዕል መግዛትን ለምን ረሳህ?›› የሚል የሚያስደነግጥ ቃልን ሰምተው ወደ ገበያ ተመልሰው መልኳ ያማረና የተወደደ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል ገዝተው በሐርና በንጹሕ ልብስ ጠቅልለው ይዘው እየተጓዙ ሳሉ ከሚያስፈራ ዱር ውስጥ ደረሱ፡፡ በዚያም ወንበዴዎች ተነሡባቸውና ከእነርሱ ሊሸሹ ሲሉ ‹‹መንገድህን ሒድ›› የሚል ቃል ከሥዕሏ ወጣ፤ መነኵሴውም መንገዳቸውን በሰላም ተጓዙ፡፡ ሁለተኛም አንበሳ ሊበላቸው በተነሣባቸው ጊዜ ከዚያች ሥዕል የሚያሥፈራ ድምፅ ወጥቶ አንበሳውን አባረረላቸው፡፡

አባ ቴዎድሮስ ይህን ዂሉ ድንቅ ተአምር ባዩ ጊዜም ያቺን ሥዕል ለማርታ ከመስጠት ይልቅ ወደ አገራቸው ሊወስዷት ወደዱ፡፡ በመርከብ ተሳፍረው በሌላ አቅጣጫ ሲሔዱም ታላቅ ነፋስ ተነሥቶ ወደ ማርታ አገር ወደ ጼዴንያ ወሰዳቸው፡፡ ከመርከብም ወርደው ከብዙ እንግዶች ጋር ወደዚያች መበለት ቤት ደረሱ፡፡ ነገር ግን ማንነታቸውን ለማርታ አልገለጡላትም፤ እርሷም አላወቀቻቸውም ነበር፡፡ በማግሥቱም ተሠውረው ወደ አገራቸው ሊሔዱ ሲሉ የቅፅሩ ደጃፍ ጠፍቶባቸው ሲፈልጉ ዋሉ፡፡ በመሸባቸው ጊዜም ወደ ማደሪያቸው ተመለሱ፡፡ ማታ ማታ በሩን ያዩታል፤ ነግቶ መሔድን ሲሹ ግን የበሩ መንገድ ይሠወርባቸዋል፡፡ እንዲህም ኾነው እስከ ሦስት ቀን ድረስ ቆዩ፡፡ ማርታም ‹‹አባቴ ሆይ አእምሮህ ተነክቷልን? ስትቅበዘበዝ አይሃለሁና ምን ኾነህ ነው?›› ሰትል ጠየቀቻችው፡፡ እርሳቸውም ከእመቤታችን ሥዕል የተደረገውን ተአምር እና ሥዕሏን ይዘው ለመጥፋት ያደረጉትን ጥረት ዂሉ ነግረው፣ ራሳቸውን ገልጠው ሥዕሏን ሰጧት፡፡ እርሷም የእመቤታችንን ሥዕል ተቀብላ የተጠቀለለችበትን ልብስ በፈታችው ጊዜ ወዝ ከሥዕሊቱ ሲንጠፈጠፍ አገኘች፡፡ ከደስታዋ ብዛት የተነሣም የአባ ቴዎድሮስን እጃቸውንና እግራቸውን ሳመች፡፡

ከዚህም በኋላ ያቺን ሥዕል ወደ ጸሎት ቤቷ ወስዳ በታላቅ ክብር አኖረቻት፡፡ ማንም እንዳይዳስሳትም የነሐስ መስኮትን ሠራችላት፡፡ በቀንና በሌሊትም የሚያበሩ መቅረዞችን በፊቷ ሰቀለች፤ ከመቅረዞች ውጭም የሐር መጋረጃን ጋረደች፡፡ ከሥዕሊቱ በታችም እየተንጠፈጠፈ የሚወርደው የወዝ ቅባት የሚጠራቀምበት ከዕብነ በረድ የተሠራ ወጭት አኖረች፡፡ እኒያ መነኰስም እስከሚሞቱበት ቀን ድረስ የእመቤታችን ድንግል ማርያምን ሥዕል እያገለገሉ ኖሩ፡፡ የአገሩ ሊቀ ጳጳስም የእመቤታችን ሥዕል ሥጋ የለበሰች ኹና ባገኙና ተአምሯንም በተመለከቱ ጊዜ ከዚህ አምላካዊ ግብር የተነሣ አደነቁ፡፡ ከሥዕሏ ከሚንጠባጠበው ቅባት ቀድተው ለበረከት ሲካፈሉም ወዲያውኑ በወጭቱ ውስጥ መላ፡፡ ሥዕሊቱን ወደ ሌላ ቦታም ሊወስዷት በፈለጉ ጊዜም ንውጽውጽታ ኾኖ ብዙዎች በድንጋጤ ወደቁ፡፡ ሥዕሊቱም እስከ ዛሬ ድረስ በዚያች አገር (በጼዴንያ) ትገኛለች፡፡

‹‹እግዚአብሔር በቅዱሳኑ ላይ ድንቅ ነው›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፷፯፥፴፭) እግዚአብሔር አምላካችን በልዩ ልዩ መንገድ ለሰው ልጅ ተአምራቱን ይገልጣል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ተመዝግቦ እንደምናገኘው እግዚአብሔር ከዓለት ላይ ውኃ እያፈለቀ ሕዝቡን ያጠጣል፡፡ እንደዚሁም ቅዱሳን ሐዋርያት በቃላቸውም፣ በልብሳቸውም፣ በጥላቸውም ሙታንን በማስነሣት፤ ሕሙማንን በመፈወስ ተአምራትን ያደርጉ ነበር፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ጴጥሮስ በጥላው፤ ቅዱስ ጳውሎስም በልብሱ ቅዳጅ ያደርጓቸው የነበሩ ተአምራትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከግዑዝ ዓለት ውስጥ ውኃ የሚያፈልቅ አምላክ ከሥጋዋ ሥጋ፤ ከነፍሷ ነፍስ ተዋሕዶ ካከበራት ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ወዝ እንዲፈስ ቢያደርግ ምን ይሳነዋል? ሐዋርያት ከእግዚአብሔር ዘንድ በተሰጣቸው ጸጋ በልብሳቸውና በሰውነታቸው ጥላ ተአምራትን ማድረግ እንደ ተቻላቸው ዂሉ አምላክን በማኅፀኗ የተሸከመችው ወላዲተ አምላክ ቅድስት ድንግል ማርያምም በሥዕሏ ወዝ ብዙ ሕሙማንን መፈወስ ይቻላታል፡፡ ከቅዱሳን ልብስና ጥላ የእርሷ ሥዕል ይከብራልና፡፡ ስለዚህም ነው በየዓመቱ መስከረም ፲ ቀን በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት የሚከበረው፡፡

የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፤ የልጇ፣ የወዳጇ የጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቸርነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የኢትዮጵያ ዘመን አቈጣጠር

በዲያቆን ኃይለ ኢየሱስ ቢያ

መስከረም  ፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የዘመን አቈጣጠር ዓመታትን፣ ወራትን፣ ሳምንታትን፣ ዕለታትን፣ ደቂቃን እና ድቁቅ ሰዓታትን በየሥፍራቸው (በየመጠናቸው) የሚገልጽ፤ የሚተነትን፤ የሚለካ የቤተ ክርስቲያን የቍጥር ትምህርት ነው፡፡ እነዚህ ዅሉ ተመርምረው፣ ተመዝነው፣ ተቈጥረው ሲያበቁ ምድብና ቀመር ተሰጥቷቸው የሚገኙበትን ውሳኔና ድንጋጌ የሚያሳውቅ የዘመን አቈጣጠር – ‹ሐሳበ ዘመን› ይባላል፡፡ ዓመታት፣ ወራት፣ ሳምንታት፣ ዕለታትና ሰዓታት የሚለኩት (የሚሠፈሩት፣ የሚቈጠሩት) በሰባቱ መሥፈሪያና በሰባቱ አዕዋዳት ነው፡፡ ሰባቱ መሥፈርታት የሚባሉትም፡- ሳድሲት፣ ኃምሲት፣ ራብዒት፣ ሣልሲት፣ ካልዒት፣ ኬክሮስ እና ዕለት ሲኾኑ ሰባቱ አዕዋዳት ደግሞ፡- ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅ፣ ዐውደ ዓመት፣ ዐውደ ፀሐይ፣ ዐውደ አበቅቴ፣ ዐውደ ማኅተም እና ዐውደ ቀመር ናቸው፡፡

  • ዐውደ ዕለት – ከእሑድ እስከ ቅዳሜ ያሉት ሰባቱ ዕለታት ሲኾኑ፤ አውራኅን (ወራትን) ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
  • ዐውደ ወርኅ – በፀሐይ ፴ ዕለታት፣ በጨረቃ ፳፱ ወይም ፴ ዕለታት ናቸው፤ ዓመታትን ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
  • ዐውደ ዓመት – በፀሐይ ቀን አቈጣጠር ፫፻፷፭ ቀን ከ፲፭ ኬክሮስ፤ በጨረቃ አቈጣጠር ፫፻፶፬ ቀን ከ፳፪ ኬክሮስ ነው፡፡ እነዚህ ሦስቱ በዕለት፤ አራቱ ደግሞ በዓመት ይቈጠራሉ፡፡ ዘመናትን ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
  • ዐውደ ፀሐይ – ፳፰ ዓመት ነው፤ በዚህ ዕለትና ወንጌላዊ ይገናኙበታል፡፡
  • ዐውደ አበቅቴ – ፲፱ ዓመት ነው፤ በዚህ ፀሐይና ጨረቃ ይገናኙበታል፡፡
  • ዐውደ ማኅተም – ፸፮ ዓመት ነው፤ በዚህ አበቅቴና ወንጌላዊ ይገናኙበታል፡፡
  • ዐውደ ቀመር – ፭፻፴፪ ዓመት ነው፤ በዚህ ዕለትና ወንጌላዊ፣ አበቅቴም ይገናኙበታል፡፡

የዘመናት (የጊዜያት) ክፍል እና መጠን

አንድ ዓመት በፀሐይ ፫፻፷፭ ቀን ከ፲፭ ኬክሮስ፤ በጨረቃ ፫፻፶፬ ቀን ከ፳፪ ኬክሮስ ነው፡፡ አንድ ወር በፀሐይ ፴ ዕለታት አሉት፤ በጨረቃ ፳፱ ወይም ፴ ዕለታት አሉት፡፡ አንድ ዕለት ፳፬ ሰዓት፤ አንድ ቀን ፲፪ ሰዓት፤ አንድ ሰዓት ፷ ደቂቃ ነው፡፡ አንድ ደቂቃ ፷ ካልዒት፤ አንድ ካልዒት ፩ ቅጽበት ነው፡፡ ኬክሮስ ማለት የክፍለ ዕለት ሳምንት (የዕለት ፩/፷ ወይም ፩/፳፬ኛ ሰዓት) ነው፡፡ አንድ ዕለት ፳፬ ሰዓት ወይም ፷ ኬክሮስ ነው፡፡

ክፍላተ ዓመት (የዓመት ክፍሎች)

የዓመት ክፍሎች፡- መጸው፣ በጋ፣ ፀደይ እና ክረምት ናቸው፡፡

  • ከመስከረም ፳፮ እስከ ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ክፍለ ዓመት መጸው ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት ሌሊቱ ረጅም፣ ቀኑ አጭር ነው፡፡
  • ከታኅሣሥ ፳፮ እስከ መጋቢት ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ክፍለ ዓመት በጋ ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት የቀኑና የሌሊቱ ርዝመት እኩል ነው፡፡
  • ከመጋቢት ፳፮ እስከ ሰኔ ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ወቅት ፀደይ ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት ቀኑ ይረዝማል፤ ሌሊቱ ያጥራል፡፡
  • ከሰኔ ፳፮ እስከ መስከረም ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ክረምት ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት የቀኑና የሌሊቱ ርዝመት እኩል ነው፡፡

የዘመናት አከፋፈል በአራቱ ወንጌላውያን እና ዘመን የሚለወጥበት ሰዓት

  • ማቴዎስ ዘመኑን ከምሽቱ ፩ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከሌሊቱ ፮ ሰዓት ይፈጽማል፡፡
  • ማርቆስ ዘመኑን ከሌሊቱ ፯ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከጠዋቱ ፲፪ ሰዓት ይፈጽማል፡፡
  • ሉቃስ ዘመኑን ከጠዋቱ ፩ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከቀኑ ፮ ሰዓት (በቀትር) ይፈጽማል፡፡
  • ዮሐንስ ዘመኑን ከቀኑ ፯ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከቀትር በኋላ ከምሽቱ ፲፪ ሰዓት ይፈጽማል፡፡

የወራት፣ የሌሊትና የቀን ሥፍረ ሰዓት

  • መስከረም – ሌሊቱ ፲፪፤ መዓልቱም (ቀኑ) ፲፪ ሰዓት ነው፡፡
  • ጥቅምት – ሌሊቱ ፲፫፤ መዓልቱ ፲፩ ሰዓት ነው፡፡
  • ኅዳር – ሌሊቱ ፲፬፤ መዓልቱ ፲ ሰዓት ነው፡፡
  • ታኅሣሥ – ሌሊቱ ፲፭፤ መዓልቱ ፱ ሰዓት ነው፡፡
  • ጥር – ሌሊቱ ፲፬፤ መዓልቱ ፲ ሰዓት ነው፡፡
  • የካቲት – ሌሊቱ ፲፫፤ መዓልቱ ፲፩ ሰዓት ነው፡፡
  • መጋቢት – ሌሊቱ ፲፪፤ መዓልቱ ፲፪ ሰዓት ነው፡፡
  • ሚያዝያ – ሌሊቱ ፲፩፤ መዓልቱ ፲፫ ሰዓት ነው፡፡
  • ግንቦት – ሌሊቱ ፲፤ መዓልቱ ፲፬ ሰዓት ነው፡፡
  • ሰኔ – ሌሊቱ ፲፱፤ መዓልቱ ፲፭ ሰዓት ነው፡፡
  • ሐምሌ – ሌሊቱ ፲፤ መዓልቱ ፲፬ ሰዓት ነው፡፡
  • ነሐሴ – ሌሊቱ ፲፩፤ መዓልቱ ፲፫ ሰዓት ነው፡፡

የበዓላት እና አጽዋማት ኢየዐርግ እና ኢይወርድ (ከፍታ እና ዝቅታ)

  • ጾመ ነነዌ ከጥር ፲፯ ቀን በታች፤ ከየካቲት ፳፩ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ዐቢይ ጾም ከየካቲት ፩ ቀን በታች፤ ከመጋቢት ፭ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ደብረ ዘይት ከየካቲት ፳፰ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፪ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ሆሣዕና ከመጋቢት ፲፱ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፳፫ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ስቅለት ከመጋቢት ፳፬ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፳፰ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ትንሣኤ ከመጋቢት ፳፮ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፴ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ርክበ ካህናት ከሚያዝያ ፳ ቀን በታች፤ ከግንቦት ፳፬ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ዕርገት ከግንቦት ፭ ቀን በታች፤ ከሰኔ ፲፱ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ጾመ ሐዋርያት ከግንቦት ፲፮ ቀን በታች፤ ከሰኔ ፳ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ጾመ ድኅነት ከግንቦት ፲፰ ቀን በታች፤ ከሰኔ ፳፪ ቀን በላይ አይውልም፡፡

የተውሳክ አወጣጥ

፩. የዕለት ተውሳክ

የዕለት ተውሳክ በቅዳሜ ይጀምራል፡፡ የቅዳሜ ተውሳክ ፰፤ የእሑድ ተውሳክ ፯፤ የሰኞ ተውሳክ ፮፤ የማክሰኞ ተውሳክ ፭፤ የረቡዕ ተውሳክ ፬፤ የሐሙስ ተውሳክ ፫፤ የዓርብ ተውሳክ ፪ ነው፡፡

፪. የአጽዋማትና የበዓላት ተውሳክ

የነነዌ ተውሳክ አልቦ (ባዶ)፤ የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬፤ የደብረ ዘይት ተውሳክ ፩፤ የሆሣዕና ተውሳክ ፪፤ የስቅለት ተውሳክ ፯፤ የትንሣኤ ተውሳክ ፱፤ የርክበ ካህናት ተውሳክ ፫፤ የዕርገት ተውሳክ ፲፰፤ የጰራቅሊጦስ ፳፰፤ የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ ፳፱፤ የጾመ ድኅነት ተውሳክ ፩ ነው፡፡

በዓላት እና አጽዋማት የሚውሉባቸው ዕለታት

  • ጾመ ነነዌ፣ ዐቢይ ጾም እና ጾመ ሐዋርያት – ሰኞ፡፡
  • ደብረ ዘይት፣ ሆሣዕና፣ ትንሣኤ እና ጰራቅሊጦስ – እሑድ፡፡
  • ስቅለት – ዓርብ፡፡
  • ርክበ ካህናት እና ጾመ ድኅነት – ረቡዕ፡፡
  • ዕርገት – ሐሙስ ቀን ይውላል፡፡

መጥቅዕ እና አበቅቴ

መጥቅዕ እና አበቅቴ ከየት መጣ ቢሉ፣

የመጀመሪያው – የፀሐይና የጨረቃ ቀን አቈጣጠር ልዩነት ነው፡፡ አንድ ዓመት በፀሐይ ፫፻፷፭ ቀን ከ፲፭ ኬክሮስ፤ በጨረቃ ፫፻፶፬ ቀን ከ፳፪ ኬክሮስ ነው፡፡ የሁለቱ ልዩነት (፫፻፷፭ – ፫፻፶፬ = ፲፩) አበቅቴ ይባላል፡፡

ሁለተኛው – የቅዱስ ድሜጥሮስ ሱባዔ ውጤት ነው፡፡ ቅዱስ ድሜጥሮስ በዓላትና አጽዋማት የሚውሉበት ቀን በጥንተ ዕለቱ እንዲውል ለማድረግ ይመኝ ነበርና ከሌሊቱ ፳፫ ሱባዔ፤ ከቀኑ ፯ ሱባዔ ገብቷል፡፡ ፳፫×፯ = ፻፷፩ ይኾናል፡፡ ፻፷፩ ለ፴ ሲካፈል ፭ ይደርስና ፲፩ ይተርፋል፤ ይህን ቀሪ አበቅቴ አለው፡፡ ፯ በሰባት ሲባዛ ፵፱ ይኾናል (፯×፯ = ፵፱)፡፡ ፵፱ ለ፴ ሲካፈል (፵፱÷፴) ፩ ደርሶ ፲፱ ይቀራል፤ ይህን ቀሪ መጥቅዕ አለው፡፡

ዓመተ ዓለምን፣ ወንጌላዊን፣ ዕለትን፣ ወንበርን፣ አበቅቴን፣ መጥቅዕን፣ መባጃ ሐመርን፣ አጽዋማትን እና በዓላትን ለይቶ ለማወቅ ሒሳባዊ ሰሌቱ እንዲሚከተለው ነው፤

ዓመተ ዓለምን ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ኵነኔ ሲደመር ዓመተ ምሕረት ሲኾን፣ ውጤቱ ዓመተ ዓለም ይባላል፡፡ ለምሳሌ ፶፭፻ + ፳፻፲ = ፸፭፻፲ (5500 + 2010 = 7510)፤ ፸፭፻፲ (7510) ዓመተ ዓለም ይባላል፡፡

ወንጌላዊን ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ዓለምን ለአራት ማካፈል ነው፡፡ ዓመተ ዓለሙ ለአራት ተካፍሎ ፩ ሲቀር ዘመኑ ማቴዎስ፤ ፪ ሲቀር ማርቆስ፤ ፫ ሲቀር ሉቃስ፤ ያለ ቀሪ ሲካፈል ዮሐንስ ይኾናል፡፡

ዕለቱን (ለምሳሌ መስከረም ፩ ቀንን) ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ዓለም ሲደመር መጠነ ራብዒት (ለአንድ ወንጌላዊ የደረሰው) ሲካፈል ለሰባት ነው፡፡ ዓመተ ዓለም እና መጠነ ራብዒት ተደምሮ ለሰባት ተካፍሎ ፩ ሲቀር ማክሰኞ፤ ፪ ሲቀር ረቡዕ፤ ፫ ሲቀር ሐሙስ፤ ፬ ሲቀር ዓርብ፤ ፭ ሲቀር ቅዳሜ፤ ፮ ሲቀር እሑድ፤ ያለ ቀሪ እኩል ሲካፈል ሰኞ ይኾናል፡፡

ተረፈ ዘመኑን (ወንበሩን) ለማግኘት ዓመተ ዓለም ለሰባት ተካፍሎ የሚገኘው ቀሪ ተረፈ ዘመን (ወንበር) ይባላል፡፡ ከቀሪው ላይ ስለ ተጀመረ ተቈጠረ፤ ስላልተፈጸመ ታተተ (ተቀነሰ) ብሎ አንድ መቀነስ ስሌቱ ሲኾን ቀሪው ወንበር ይባላል፡፡

አበቅቴን ለማግኘት ወንበር ሲባዛ በጥንተ አበቅቴ (፲፩) ሲካፈል ለ፴ ኾኖ ቀሪው አበቅቴ ይባላል፡፡ መጥቅዕን ለማግኘት ወንበር ሲባዛ በጥንተ መጥቅዕ (፲፱) ሲካፈል ለ፴ ኾኖ ቀሪው መጥቅዕ ይባላል፡፡

ከዚህ ላይ አዋጁን (መመሪያውን) እንመልከት፤ አዋጁም መጥቅዕ ከ፲፬ በላይ ከኾነ መጥቅዕ በመስከረም ይውላል፤ የመስከረም ማግስት (ሳኒታ) የካቲት ይኾናል፡፡ ፲፬ ራሱ መጥቅዕ መኾን አይችልም፡፡ መጥቅዕ ከ፲፬ በታች ከኾነ በጥቅምት ይውላል፤ የጥቅምት ማግስት (ሳኒታ) ጥር ነው፡፡ መጥቅዕ ሲደመር አበቅቴ ውጤቱ ዅልጊዜ ፴ ነው፡፡ መጥቅዕ አልቦ (ዜሮ) ሲኾን መስከረም ፴ የዋለበት የቀኑ ተውሳክ መባጃ ሐመር ይኾናል፡፡

መባጃ ሐመርን ለማግኘት የዕለት ተውሳክ ሲደመር መጥቅዕ ሲካፈል ለሠላሳ ነው (የዕለት ተውሳክ+መጥቅዕ÷፴ = መባጃ ሐመር)፡፡ ቍጥሩ ለሠላሳ መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወሰዳል፡፡

የአጽዋማት እና የበዓላት ተውሳክ አወጣጥ

ጾምን ለማግኘት ስሌቱ መባጃ ሐመር ሲደመር የጾም ተውሳክ ሲካፈል ለሠላሳ ነው (መባጃ ሐመር+የጾም ተውሳክ÷፴ = ጾም)፡፡ ቍጥሩ ለሠላሳ መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወሰዳል፡፡ በዓላትን ለማግኘት ስሌቱ መባጃ ሐመር ሲደመር የበዓል ተውሳክ ሲካፈል ለሠላሳ ነው (መባጃ ሐመር+የበዓል ተውሳክ÷፴ = በዓል)፡፡ ቍጥሩ ለሠላሳ መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወሰዳል፡፡ በዚህ ሒሳብ መሠረት በየዓመቱ የሚመላለሱ በዓላት እና አጽዋማት የሚዉሉበትን ቀን ማወቅ ይቻላል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዝክረ ዐውደ ዓመት

በዶክተር ታደለ ገድሌ

መስከረም ፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የዓለም ሕዝብ በየዓመቱ በታላቅ ደስታ ከሚያከብራቸውና ከሚዘክራቸው በዓላት መኻከል አንዱ የዘመን መለወጫ በዓል ነው፡፡ ዕለታት እየበረሩ፣ ወራት እየተቀመሩ አልፈው አዲስ ዘመን በባተ ቍጥር ሕዝብ ዅሉ ፍሥሐ ያደርጋል፡፡ ሰላምን፣ ብልጽግናን፣ ጤንነትን፣ ፍቅርን፣ … ለወዳጅ ዘመድ ይመኛል፡፡ አዲሱ ዓመት ዘመነ ሰላም፣ ዘመነ ጥጋብ … እንዲኾን መልካም ምኞቱን ይገልጻል፡፡ አዲስ የሥራ ዕቅድና ምኞትን በስሜቱ ያሠርፃል፡፡ ወደ ተግባርም ለመተርጐም ሌት ተቀን ይፋጠናል፡፡ በአገራችን ኢትዮጵያ የዘመን መለወጫ በዓል መስከረም ፩ ቀን ይከበራል፡፡ ‹‹ለመኾኑ በኢትዮጵያ መስከረም የአዲስ ዓመት መባቻ ኾኖ የተመረጠው ለምንድን ነው? በአራቱ ወንጌላውያንና በአራቱ እንስሳ (ኪሩቤል) መካከል ያለው የስያሜ ትሥሥርስ ምሥጢሩ ምንድን ነው?›› የሚሉና የመሳሰሉ ጥያቄዎች በአእምሯችን ሊመላለሱ ይችላሉ፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢ ለነበሩት አለቃ አያሌው ታምሩ በአንድ ወቅት እነዚህን ጥያቄዎች አቅርበንላቸው (የካቲት መጽሔት፣ 15ኛ ዓመት ቍጥር 1፤ መስከረም 1984 ዓ.ም፣ ገጽ 4 – 7 እና 34)፤ ኢትዮጵያውያን አዲስ ዓመትን በመስከረም የሚያከብሩት ከኖኅ በፊትና በኋላ በተዘረጋው ስሌተ ዘመን እንደ ኾነ በማስረዳት የሚከተለውን ትምህርት ሰጥተዋል፤

የኢትዮጵያ ይዞታ መሠረተ ባሕርይ ከጥንት ጀምሮ ሃይማኖት ሲኾን በጽሑፍም በአፈ ታሪክም እየተወራረሰ የመጣ ነገር ነው፡፡ በሰው ፍልስፍና ወይም በመንግሥት ለውጥ ምክንያት የተናወጠ ነገር የለም፡፡ ለውጦች ጦርነቶችና ግጭቶች፣ በተለያዩ የመንግሥት መሪዎች ቢፈራረቁም መሠረተ እምነትን አልነኩም፡፡ የአገሪቱን ባህልና ታሪክ የሚነካ ለውጥ አልደረሰም፡፡ ነገር ግን ባለ ሥልጣናት በሹም ሽር ሲቀያየሩ በምርጫ የመንበረ መንግሥት መቀመጫ ቦታ ልውውጥም ሲደረግ መጥቷል፡፡ አዲስ ዓመት ከጥንት ከአዳም ጀምሮ የነበረ በዓል ነው፡፡ ከአዳም ጀምሮ የመጣውን የቍጥር ዘመን በጽሑፍ ያስተላለፈው ሄኖክ ነው፡፡ ይኸውም ሳምንታት በፍጥረት ከእሑድ እስከ ቅዳሜ ሰባት፣ የዕለት ሰዓት ሃያ አራት፣ የወር ቀናት ሠላሳ፣ የዓመት ቀናት ሦስት መቶ ስልሳ አራት ሲኾኑ ስልሳ አምስተኛዋ መዛወሪያ ቀን ናት፡፡ ጳጕሜን አምስት ቀን ስትኾን የሚዘለው ስድስተኛው ቀን ሠግር (የወር መባቻ) ይኾናል፡፡

የኢትዮጵያ ዘመን አቈጣጠር ከጥፋት ውኃ በፊት ሦስት ትውልዶችን አሳልፏል፡፡ እነርሱም ሄኖክ፣ ላሜህና ኖኅ ናቸው፡፡ ኖኅ የሰው ልጆች ዅሉ አባት እንደ ኾነው እንደ አዳም የሚቈጠር ከጥፋት ውኃ በመጨረሻ የተረፈ አባት ነው፡፡ ኖኅ ከአባቶቹ የተቀበለውን ጥበብ ዅሉ ለልጆቹ አስተላለፈ፡፡ ለአብነትም ዛሬ የምንጠቀምበት የኮሶ መድኃኒት የኖኅ ተረፈ ጥበብ ነው፡፡ ኖኅ በሰኔ ወር ከመርከብ በወጣ ጊዜ የበግ መሥዋዕት ሠውቶ ሰውን ከእግዚአብሔር ጋር አስታረቀ፡፡ እግዚአብሔርም ያን ጊዜ ከኖኅ ጋር አዲስ ቃል ኪዳን መሠረተ፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ልቡ ምንም ክፉ ቢኾንና ቅጣትም የማይቀርለት ቢኾን ጨርሶ እንደማያጠፋው ለኖኅ ቃል ገባለት፡፡ ምልክቱንም የቀስቱን ደጋን ወደራሱ፣ ገመዱን ደግሞ ወደ ሰው ልጆች አድርጐ በደመና ላይ ቀስት ስሎ አሳይቶታል፡፡ 

ጌታ ‹‹መዓልትና ሌሊት፣ በጋና ክረምት፣ ብርድና ሙቀት፣ ዘርና መከር ጊዜያቸውን ጠብቀው ሲፈራረቁ ይኖራሉ፡፡ በምድር ላይ ይህ አይቀርም›› በማለት እንደ ተናገረው በቃሉ መሠረት ክረምት ገባ፡፡ ክረምቱ ካለፈ በኋላ የዓመት መሥፈሪያ ሦስት መቶ ስልሳ አምስት ቀናት በመኾናቸው መስከረም አንድ ቀን የአዲስ ዓመት መባቻ ኾነ፡፡ አዲስ ዓመት ሥራውን ጨርሶ በሔደ ቍጥር፣ ዕለት ግን በየጊዜው እየታደሰ ይሔዳል፡፡ እስከ አዲስ ኪዳን መጀመሪያ ድረስ አበው በልዩ ልዩ ጊዜያት የተገለጹላቸውን ምልክቶች በመያዝ የየዘመናትን ብተት (መግቢያ) የእግዚአብሔርን ዙፋን ተሸካሚ በኾኑ በኪሩቤል መላእክት እያመሳሰሉ ገጸ ሰብእ፣ ገጸ ላህም (ላም) ገጸ ንሥር (አሞራ)፣ ገጸ አንበሳ እያሉ ዓመታትን ይመድቡ ነበር፡፡ ከስብከተ ሐዲስ በኋላ ግን ይህ ተሽሮ ወንጌልን በጻፉት አርድእት ስም ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስ፣ ዮሐንስ ስም ተሰየመ፡፡ ወንጌላውያኑ ወንጌልን ሲጽፉ ዕለት ተቀደም (በቅደም ተከተል) ነውና ተራቸውን ጠብቀው በየዓመቱ ይመላለሳሉ፡፡ ይህም ማለት ዘመኑ ዘመነ ምሕረት መኾኑን ለማብሠርና ድኅነት (መዳን) የሚሰበክበት ዘመን መምጣቱን ለመግለጽ ነው፡፡

በገጸ ሰብእ የተተካው ማቴዎስ ነው፡፡ ምሥጢሩም ‹‹ጌታ ከሰማይ ወረደ፤ ሰው ኾነ›› ብሎ ማስተማሩን የሚያመለክት ነው፡፡ በገጸ አንበሳ የተተካው ማርቆስ ነው፡፡ ይኸውም አሕዛብ በግብጽ (ምሥር) በላህም (በላም)፣ በጣዕዋ (ጥጃ) አምሳል ጣዖት አሠርተው ያመልኩ ስለ ነበር ያንን አምልኮ አጥፍቶ፣ ሽሮ በክርስቶስ እንዲያምኑ ስላደረገ ነው፡፡ በገጸ እንስሳ (ላህም) የተተካው ሉቃስ ነው፡፡ ምሳሌነቱም የጌታን መሥዋዕትነት ስለሚያስተምር ነው፡፡ በገጸ ንሥር የተተካው ዮሐንስ ነው፡፡ ንሥር ከአዕዋፍ ዅሉ መጥቆ ይሔዳል፡፡ መሬትም ላይ ምንም ኢ ምንት ነገር ብትወድቅ አትሠወረውም፡፡ ዓይኑ ጽሩይ (ብሩህ) ነው፡፡ ይህም ማለት ቅዱስ ዮሐንስ ዓለም ሳይፈጠር፣ ዘመን ሳይቈጠር ወደ ነበረው ኹኔታ በሕሊናው ርቆ በመሔድ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ቀዳማዊ ቃል መኾኑን፤ እግዚአብሔርም ዓለሙን የፈጠረው በእርሱ ቃል እምነት መኾኑን፤ ያም ቃል ሰው መኾኑን ስለሚያስተምር ነው ገጸ ንሥር የተባለው፡፡ የሦስቱ ወንጌላውያን ትምህርት ታሪክ ጠቀስ ኾኖ ለሰሚዎችና አንባቢዎች ዅሉ በቶሎ ሲረዳ፣ የዮሐንስ አስተምህሮ ግን ጥልቅ የአእምሮ ብስለትና ምርምርን ይጠይቃል፡፡

ዘመን በተለወጠ ቍጥር ከሰው ልጆች ስሜት ጋር አብሮ የሚንቀሳቀስ ተስፋ አለ፡፡ በጥፋት ዘመን ሰማይ በደመና ተሸፍኖ፣ ከላይ ዝናም፣ ከታች የሚፈልቀው ጎርፍ የኖኅ ሰዎችን አስጨንቋቸው ነበር፡፡ በኋላ ግን ምድር ላይ ለውጥ ታየ፡፡ ነፋስ ነፈሰ፡፡ ብርሃን ፈነጠቀ፡፡ አበባ አበበ፡፡ የኖኅ መልእክተኛ የኾነችው ርግብም ‹‹ማየ አይህ ነትገ፤ የጥፋት ውኃ ጐደለ›› እያለች ርጥብ ቄጠማ በአፏ ይዛ መጥታ ስታበሥረው የኖኅ ሰዎች ከመርከቧ ወደ መሬት ሲወርዱ በመጀመሪያ አበባ፣ እንግጫ፣ ቄጠማ፣ የለመለመ ሣር … አገኙ፡፡ እግዚአብሔርንም በአንቃዕድዎ ልቡና አመሰገኑና በዓላቸውን አከበሩ፡፡ በዚህም አምሳል ክረምት አልፎ መሬት በምታሸበርቅበት በምታብበት ከመስከረም አንድ ቀን ጀምሮ አዲስ ዓመታችንን እናከብራለን፡፡ ሰውም ከመሬት የተገኘ በመኾኑ እንደ ዕፀዋትና እንደ አበቦች ዅሉ በመስከረም ወር በተስፋ ስሜት ይለመልማል፡፡ ያጣው አገኛለሁ፣ የታመመው እድናለሁ ብሎ በቁርጥኝነት ይነሣሣል፡፡ በዘልማድም እምነቶች ይገለጻሉ፤ ‹‹በዮሐንስ እረስ፣ በማቴዎስ እፈስ … ጳጕሜ ሲወልስ ጎታህን አብስ … ጳጕሜ ሲበራ ስንዴህን ዝራ›› እያሉ ገበሬዎች ይናገራሉ፤ ይተነብያሉ፡፡ ገበሬዎች ገና በግንቦት ወር የክረምቱን አገባብ ለይተው የሚዘሩትን ዘር ደንብተው የሚያውቁ ሜትሮሎጂስቶች (የአየር ጠባይዕ ትንበያ ባለሙያዎች) ናቸው፡፡

አለቃ አያሌው እንዳስተማሩት ዐውደ ዓመት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባሕረ ሐሳብ መሠረት የሚከበርና መንፈሳዊ ምሥጢር ያለው ሃይማኖታዊም አገራዊም በዓል ነው፡፡ በቅዱስ ዮሐንስ በዓል በቤተ ክርስቲያን ከሚፈጸመው መንፈሳዊ አገልግሎት ባሻገር በአዲሱ ዓመት ዋይዜማ በየቤቱ ጨፌና ቄጠማ ይጎዘጎዛል፡፡ አበባ በሥርዓቱ እየተዘጋጀ በየቦታው ይቀመጣል፡፡ ልጆችና አረጋውያን አዳዲስ ልብሳቸውን ለብሰው በደስታ ይፈነድቃሉ፡፡ አመሻሽ ላይ ችቦ አቀጣጥለው ‹‹ኢዮሃ አበባዬ መስከረም ጠባዬ … ኢዮሃ የበርበሬ ውኃ … በሸዋ በጎንደር፣ በትግራይ በወሎ፣ በሐረርጌ፣ በሲዳሞ … ያላችሁ እንዴት ከረማችሁ? እንኳን ከዘመን ዘመን ከጨለማ (ሰኔ፣ ሐምሌ፣ ነሐሴ) ወደ ብርሃን (መስከረም) በሰላም አሸጋገራችሁ! … እንጉሮ ገባሽ በያመቱ ያምጣሽ …›› እያሉ ያቀጣጠሉትን ችቦ በአየር ላይ እየወረወሩ ደስታቸውን ሲገልጹ፣ የምሽቱም የችቦ እሳት ርቀት እስከሚወስነው አድማስ ድረስ ከቀዬ ቀዬ፣ ከአድባር እስከ አድባር፣ ከመንደር እስከ መንደር … ሲንቀለቀልና ሲንቦገቦግ መሬት የእሳት ላንቃዋ ተከፍቶ ነበልባል የምትተፋ ትመስላለች፡፡ የአየር ላይ ወጋገኑን ሲመለከቱት ደግሞ እግዚአብሔር ከመንበረ ጸባዖቱ ወርዶ የብርሃን አክሊል ደፍቶ ቀይ መጐናጸፊያ ተጎናጽፎ ጨለማውን እየገፈፈ በጠፈር (በአየር) ላይ እየተንሳፈፈ ወደ መሬት የሚወርድባት የመጨረሻዋን የምጽአትን ቀን ታስታውሳለች – የዕንቍ ጣጣሽ ሌሊት፡፡

አባቶች የችቦ ብርሃን ላሰባሰበው ሕዝብ ቡራኬና ምርቃት ያደርጋሉ፡፡ ‹‹የተዘራውን እኽል እኽለ በረከት፣ የዘነመውን ዝናም ዝናመ ምሕረት፣ ዘመኑን የሰላም ዓመት ያድርግልን፡፡ እኽል ይታፈስ፤ ይርከስ፡፡ ሳቢ በሬውን፣ አራሽ ገበሬውን ይባረክ፣ ቁንጫ፣ ተባይ ተምች፣ አንበጣ … ፀረ ሰብል ዅሉ እንደ ችቦው ተቀጣጥለው ይንደዱ …›› እያሉ ይመርቃሉ፡፡ እናት አባት በልጆቻቸው፣ በወዳጅ ዘመዶቻቸው የተበረከተላቸውን የእንግጫ ጉንጉን በራሳቸው፣ በእንጀራ ማቡኪያና መሶቡ፣ ከቤቱ ምሰሶ ላይ … ያሥራሉ፡፡ ይህ በአበባ የተዘጋጀ የእንግጫ ጉንጉን የመስቀል ደመራ ዕለት ከእሳቱም ከዐመዱም ላይ ይጣላል፡፡ ተምሳሌቱም እንደ ቁንጫ ዅሉ ቁርጥማቱ ራስ ምታቱ፣ ምችጎንፍ ቁርጠቱ፣ ምቀኛ፣ ሸረኛ፣ ሰላቢው፣ ሌባ፣ ቀማኛ ቀጣፊው … እንዲቃጠልና እንዲጠፋ ነው፡፡ በቤቱም (በአባወራው ቤት) በረከትና ሞገስ (አግሟስ) እንዲቀርብም ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡