ሰሚ ያጣው የሕፃናት ጩኸት
በዲ/ን ታደለ ሲሳይ
ቀኑ ወረፋውን ለጨለማው ለመልቀቅ በማመናታት ላይ ያለ ይመስላል፡፡ የአዲስ አበባ ምድርም የፀሐይን ብርሃን በሰው ሠራሽ ብርሃን ለመተካት ፓውዛዎቿን ስልም ቁልጭ እያደረገች ነው፡፡ ሁሉም በየፊናው እየተሯሯጠ ነው፡፡ ጠዋት ሥራ የገባው ወደ ቤቱ ለመመለስ፣ ማታ የሚሠራው ደግሞ በአዲስ መንፈስ ለመሥራት ጥድፊያ ላይ ነው፡፡
ከዐዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ ተነሥቼ በድካም የዛለ ሰውነቴን ለማሳረፍ ወደ ቤቴ እያመራሁ ነው፡፡ ስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ ፊት ለፊት ዋናውን አስፓልት አቋርጬ ቀጥታ በድባብ መናፈሻ አድርጌ የቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ግቢን ትቼ ወደ ታች ስታጠፍ በርቀት የሚስረቀረቅ የሕፃናት ኅብረ ድምፅ ሰማሁ፡፡ ምን እንደሚሉ አይሰማም፤ የድምፃቸው ጣዕመ ዜማ ግን ልብን ሰርስሮ ይገባል፡፡