“የጽድቅንም ጥሩር ልበሱ”/ኤፌ.፮.፲፬/

ክፍል አንድ

በእንዳለ ደምስስ

መንፈሳዊ ሰው ርስት መንግሥተ ሰማያትን ይወርስ ዘንድ፣ ራስን ለእግዚአብሔር ማስገዛት፣ ትእዛዙንም መፈጸም ይጠበቅበታል፡፡ ከኃጢአት ወደ ጽድቅ ለመሸጋገርም አንድ ክርስቲያን መንፈሳዊ የተጋድሎ መሣሪያዎችን ይዞ መገኘት ይገባዋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች በጻፈው መልእክቱ “እንግዲህ ወገባችሁን በእውነት ታጥቃችሁ ቁሙ፣ የጽድቅንም ጥሩር ልበሱ” እንዲል/ኤፌ.፮.፲፬/፡፡

ሃይማኖትን፣ መልካም ምግባርን፣ ፍቅርን፣ የንስሓ ሕይወትን፣ ወዘተ የያዘ ሰው ራሱን ከዲያብሎስ ውጊያዎች ለመከላከል መንፈሳዊ የተጋድሎ መሣሪያዎችን መያዝ ወይም መታጠቅ ያስፈልገዋል፡፡ እነዚህም፡- ጾም፣ ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በዚህ ጽሑፍ እነዚህን በቅደም ተከተል በጥቂቱ የምናቀርብ ይሆናል፡፡

ጾም

ጾም ክርስቲያን የሆነ ሰው ሁሉ ከሰባት ዓመት የሕፃንነት ዕድሜው ጀምሮ ለተወሰነ ጊዜና ሰዓት ከእህል፣ ከውኃ ተከልክሎ መቆየት ማለት ነው፡፡ በዚህ ወቅት ከወተት፣ ከሥጋ፣ ከቅቤና፣ ከእንቁላል የአጽዋማቱ ሳምንታት እስኪጠናቀቁ ድረስ የምንከለከልበት ነው፡፡ /ፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ ፲፭/፡፡

ጾም ዓይን ክፉ ከማየት፣ ጆሮ ክፉ ከመስማት፣ አንደበት ክፉ ከመናገር፣ እጅ ክፉ ከመሥራት በአጠቃላይ የኃጢአት ሥራ ከመሥራት መከልከል ማለት ነው፡፡ /ቅዱስ ያሬድ/

ጾም የአዋጅ እና የግል/የፈቃድ/ ጾም ተብሎ በሁለት ይከፈላል፡፡

. የአዋጅ ጾም፡ ይህ ጾም በቤተ ክርስቲያናችን ምእመናን ሁሉ በሥውር ሳይሆን በይፋ የሚጾሙት ጾም ነው፡፡ ይህም መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት ያለው ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢዩኤል “በጽዮን መለከትን ንፉ፣ ጾምንም ቀድሱ፣ ጉባኤውንም አውጁ” በማለት እንደተናገረው (ኢዩ 2፡፲፭)፡፡

በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የደነገገቻቸው የአዋጅ አጽዋማት ሰባት ሲሆኑ፣ እነዚህም እንደሚከተለው ተዘርዝረዋል፡-

፩. የነቢያት ጾም                          ፭. የሐዋርያት ጾምየገሃድ ጾም                ፮. ጾመ ድኅነት (ረቡዕና ዓርብ)

2. የነነዌ ጾም                            ፯. ጾመ ፍልሰታ ናቸው፡፡

፬. ዐቢይ ጾም

. የግል/ፈቃድ/ ጾም፡  የግል ጾም ስንል አንድ ሰው በሠራው ኃጢአት ምክንያት ወደ ንስሓ አባቱ በመቅረብ  በጸጸትና በተሰበረ ልብ ሁኖ ኃጢአቱን በመናገር የሚሰጠው የንስሓ ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም በፈቃድ የሚጾም ሲሆን አንድ ሰው ስለ በደሉ፣ ስለደረሰበትና በእርሱ ላይ ስለሆነ ነገር፣ እንዲሁም ስለሚፈልገው ጉዳይ እግዚአብሔር ተገቢውን መልስ እንዲሰጠው የሚጾመው ጾም ነው፡፡ ለምሳሌ ነቢዩ ዳዊት የልጁን መታመም በሰማ ጊዜ ጾሟል፡፡ /2ኛ.ሳሙ.፲2፡፲2/፡፡ ነገር ግን በግል ጾም ጊዜ ጾሙ ይፋ ስላልሆነ ራስን መሠወር እንደሚያስፈልግ ታዟል፡፡ ይህንንም አስመልክቶ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ሲል ተናግሯል፡፡ “ስትጾሙም እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፣ እነርሱ እንደ ጾሙ ለሰው ይታዩ ዘንድ መልካቸውን ይለዋውጣሉና፣ እውነት እላችኋላሁ ዋጋቸውን ተቀብለዋል፡፡ እናንተስ በምትጾሙበት ጊዜ  ራሳችሁን ቅቡ፣ ፊታችሁንም ታጠቡ፡፡ በሥውር ለሚያይ ለአባታችሁ እንጂ ለሰዎች እንደ ጾማችሁ እንዳትታዩ በሥውር የሚያያችሁ አባታችሁም ዋጋችሁን በግልጥ ይሰጣችኋል” ብሏል፡፡(ማቴ.፮፡፲፮-፲፰)፡፡ በዚህ መሠረት የግል ጾምን ከጿሚው ሰው እና ከእግዚአብሔር ውጪ ማንም ሊያወቅ አይገባም፡፡

2. ጾም ለምን ያስፈልጋል?

ጾም ያስፈለገበት ምክንያት የሥጋን ፍላጎት በመግታትና ከኃጢአት ሥራዎች የሚጠብቀን በመሆኑ ነው፡፡ ሰው እንደፈለገው የሚበላና የሚጠጣ፣ ሁል ጊዜ ሳይጾም የሚኖር ከሆነ በኃጢአት ይወድቃል፡፡ ይህንንም አስመልክቶ በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ “ሥጋዊ ፍትወትን ያደክም ዘንድ ጾም ታዘዘ” እንዲል፡፡ ጾም ረኀብን፣ ችግርን እንድናውቅ፣ ለተራቡና ለተጠሙ በአጠቃላይ ለተቸገሩ ሁሉ እንድናስብና እንድናዝን፣ ባለን አቅም ሁሉ እንድንረዳ ያደርገናል፡፡ “ጿሚ ሰው የረኀብን ችግር ያውቅ ዘንድና ለተራቡ ይራራ ዘንድ ጾም ታዘዘ” ይላል፡፡(ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭)

ስለዚህ ጾም ለተራቡ፣ ለጠጠሙ እንዲሁም ለተቸገሩ ሁሉ መራራትን፣ በጎ ማድረግን በማስተማር የምግባር፣ የትሩፋት፣ የትሕርምት ሰዎች ያደርገናል፡፡ ይህም በእግዚአብሔር ፊት የጽድቅ ሥራ ሆኖ መንግሥተ ሰማያትን ያወርሰናል፡፡

ቀድሞ እግዚአብሔር አዳምንና ሔዋንን ካዘዛቸው ትእዛዛት መካከል “መልካምንና ክፉን ከሚያሳየውና ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፣ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና” /ዘፍ.2.፲፮///////// ብሎ ሥርዓት ቢሠራላቸውም አዳምና ሔዋን ግን ከእግዚአብሔር ጋር የገቡትን ቃል አፈረሱ፣ ገነትን ከሚያህል ሥፍራም ተሰደዱ፡፡ ለመሰደዳቸው ምክንያት የሆነው ይጾሙት ዘንድ የተሠራላቸውን ሥርዓት በማፍረሳቸው፣ ዕፀ በለስንም በመብላታቸው ነው፡፡ መብል ከእግዚአብሔር አንድነት የሚለይ ከሆነ ጾም ደግሞ ለእግዚአብሔር ትእዛዛት እንድንገዛ፣ መንግሥቱንም እንድንወርስ ድርሻ እንዳለው ያመለክተናል ማለት ነው፡፡ “ጾምስ በሕግ ውስጥ በታወቀው ጊዜ የሰው ከምግብ መከልከል ነው፡፡ በደሉን ለማስተሥረይ፣ ዋጋውን ለማብዛት፣ እርሱን ወዶ ሕግን ለሠራለት እየታዘዘ የፈቲውን ኃይል ያደክም ዘንድ፣ ለነባቢት ነፍስም ትታዛዝ ዘንድ” እንዲል /ፍትሐ ነገ. አንቀጽ ፲፭/፡፡

አምላካችን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም “ስለ ጽድቅ ብለው የሚራቡና የሚጠሙ ንዑዳን ክቡራን ናቸው፣ እነርሱ ይጠግባሉና” /ማቴ ፭.፮/ ሲል ተናግሯል፡፡ ስለዚህ መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ ጾም ድርሻ እንዳለው ያመለክተናል፡፡

ጾም በሀገር ላይ የታዘዘ መቅሠፍትን ያርቃል፡ መጽሐፍ ቅዱስ በሀገር ላይ ሊመጣ ያለውን መቅሰፍት በጾም አማካይነት እንደሚርቅ ያስተምረናል፡፡ ለዚህም እንደ ምሳሌ የነነዌ ሰዎችን መመልከት እንችላለን፡፡ የነነዌ ሰዎች የዮናስን ትምህርት መሠረት በማድረግ ሕፃናቱን ጨምሮ እንስሳቱ ሁሉ ለሦስት ቀናት ጾመዋል፡፡ እግዚአብሔርም ሊመጣ የነበረውን መቅሰፍት አርቆ ለእነርሱ የታዘዘው እሳት የዛፉን ጫፍ አቃጥሎ ተመልሷል፡፡ (ዮና.፫)፡፡ “አምላካችሁም እግዚአብሔር መሓሪና ይቅር ባይ፣ ቁጣውም የዘገየ፣ ምሕረቱም የበዛ ለክፋትም የተጸጸተ ነውና” እንዲል /ኢዩ.2.፲፫///፡፡

ጾም ሰይጣንን ድል የምንነሣበት መንፈሳዊ መሣሪያ ነው፡- ከላይ እንደተጠቀሰው ጾም ፈቃደ ሥጋችንን ለነፍሳችን የምናስገዛበት፣ ለመልካም ነገር የምንነሳሳበትና ክፉውን የምናርቅበት መሣሪያ በመሆኑ ዲያብሎስ በእኛ ላይ አይሠለጥንም፡፡ ክፉ ከማሰብ፣ ክፉ ከማድረግ እንድንቆጠብም ያደርገናል፣ ለመንፈሳዊ ተጋድሎም ያዘጋጀናል፡፡ ሥጋዊ ፍላጎታችንን እየገታን ለመንፈሳዊ ሕይወታችን እንበረታለን፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ነፍሴ በቅቤና በስብ እንደሚጠግቡ ትጠግባለች፣ ደስተኞች ከንፈሮቼም ስምህን ያመሰግናሉ” በማለት እንደተናገረው፡፡(መዝ.፷፪፥፭)፡፡

በተቃራኒው ደግሞ ባለመጾማችንና ለመንፈሳዊ ተጋድሎ ራሳችንን ባለማዘጋጀታችን ዲያብሎስ እንዲሠለጥንብን፣ ለኃጠአት እንድንሣሣና ከእግዚአብሔር እንድንለይ ያደርገናል፡፡ “እንዲህ ዓይነት አብሮ አደግ ጋኔን ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም” /ማቴ.፲፯፤፳1/ ሲል ጌታችን በቅዱስ ወንጌል እንደተናገረው ሰይጣንን ድል መንሳት የምንችለው በጾምና በጸሎት እንደሆነ ያስረዳናል፡፡

ጾምፈተና እና መከራ ያድናል፡- ፈተና እና መከራ በገጠመን ጊዜ ሱባኤ ይዘን እንጾማለን፣ እንጸልያለን፤ ነገር ግን ብዙዎቻችን ፈተና ወይም መከራ በራቀልን ጊዜ ደግሞ ጾም ጸሎት እናቆማለን፡፡ የምንሻውን ነገር እስክናገኝ፣ ከደረሰብንና ሊደርስ ካለብን ፈተና ለመዳን እንጨነቃለን፣ እንጠበባለን፡፡ ይህ ከክርስቲያኖች የሚጠበቅ አይደለም፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እንጾምባቸው ዘንድ የደነገገችልን የአዋጅ አጽዋማት እንዳሉ ሁሉ የግል/የፈቃድ/ ጾምም እንዳለ ማወቅ ተገቢ ነው፡፡ ክርስቲያን በቀን ውስጥ ሊጸልይባቸው የሚገቡ ሰዓታት እንደተወሰኑ ሁሉ ጾምም አስፈላጊና ዋነኛው ነው፡፡ ሊመጣ ካለው ፈተናም የምንጠበቀው በጾምና ጸሎት ነው፡፡ “ማቅ ለብሼ በአመድም ላይ ሆኜ ስጾም፣ እጸልይና እለምን ዘንድ ፊቴን ወደ ጌታ ወደ አምላክ አቀናሁ” (ዳን.9.፫) እንዲል ነቢዩ፡፡

በጾም ኃጢአት ይሠረያል፡- ቅዱስ ያሬድ “በጾም ወበጸሎት ይሠረይ ኃጢአት፣ በጾምና በጸሎት ኃጢአት ይሠረያል” እንዳለ ጾም ትልቅ ኃይል አለው፡፡ የነነዌ ሰዎች የዮናስን ትምህርት መሠረት በማድረግ ሦስት ቀን ጾመው ጸልየው ኃጢአታቸው ተሠርዮላቸዋል፡፡/ዮና.፫/፡፡ነቢዩ ዳንኤል በጾም ከአፈ አናብስት /ከአንበሶች አፍ/ የዳነው በጾምና በጸሎት ነው፡፡ /ዳን.፮/፡፡  ሶስናም በጾም ከሐሰት ምስክሮች ድናለች፡፡ /ሶስ.1/ ሌሎችም ቅዱሳን በጾም ከፈተና እና ከመከራ ድነዋል፡፡

ጾም ከላይ የተዘረዘሩት ብቻ ሳይሆን በርካታ ጥቅሞች አሉት፡፡ ኃጢአት በመብል አማካይነት ወደ ዓለም እንደገባ በጾም ደግሞ ዲያብሎስን ድል እናደርጋለን፡፡ ዲያብሎስም ወደ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀርቦ “አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህስ እነዚህ ድንጋዮች ዳቦ እንዲሆኑ እዘዝ” አለው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መልሶ “ሰው የሚኖረው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣው ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ እንዳይደለ ተጽፏል” /፬.፬/ አለው እንዲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዲያብሎስን በገዳመ ቆሮንቶስ አርባ ቀንና ሌሊት ጾሞ ድል ነስቶታልና እኛም እርሱን አርአያ አድርገን በመጾም በመንፈሳዊ ሕይወት በመጽናት ድል ልናደርገው ይገባል፡፡

ይቆየን፡፡

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *