“በሃይማኖት ጽኑ” (፩.ቆሮ. ፲፮፡፲፫)

መ/ር ቢትወደድ ወርቁ

“ሃይማኖት” የሚለው ቃል ሃይመነ፣ አሳመነ ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም፦ ማመን መታመን፣ አመኔታ ማለት ነው። ይኸውም ቅድመ ዓለም ከሁሉ በፊት የነበረ ፍጥረታትን የፈጠረ፤ ዓለምን ፈጥሮ የሚገዛ፤ ዓለምንም አሳልፎ የሚኖር፤ ለእርሱ ግን አስገኝ አሳላፊ የሌለው፤ በአንድነት በሦስትነት ያለ ሁሉን ቻይ አምላክ እንዳለ ማመን ነው። (ሮሜ ፲፥፱)

አንዳንድ ሰዎች “ሃይማኖት አያድንም”፣ “ጌታን በግልህ አምልከው”፣ “መጽሐፍ ቅዱስን እንደፈለግህ በገባህ መንገድ አንብበህ ተረዳ” እያሉ መጮህን ልማድ አድርገውታል፡፡ በዚህም ስብከታቸው ግላዊነትን፤ በነጻነት ስም ልቅነትንና ዋልጌነትን ተቋም አልባ እምነት አስፋፍተው ትውልዱን ከሃይማኖት ለማስወጣት ጥረት ሲያደርጉ ይታያል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ግን ግላዊነትንና ገደብ የለሽነትን አያስተምረንም፡፡ ይህን በሚገባ ለመረዳት ሐዋርያው ቅዱስ ይሁዳ በመልእክቱ የጻፈልንን በጥቂቱ አፍታተን እንመልከተው፡፡ ከዚህ ከሐዋርያው መልእክት የሚከተሉትን መንፈሳዊ መልእክቶችን እንረዳለን፡-

ሃይማኖት የተሰጠው ለድኅነት መሆኑን

ከሰባ ሁለቱ አርድእት አንዱ የሆነው የያዕቆብ ወንድም ይሁዳ በመልዕክቱ “ወንድሞች ሆይ ስለ ሁላችን መዳን እጽፍላችሁ ዘንድ በሁሉ ተፋጠንሁ፤ እጅግ ተግቼ እጽፍላችኋላሁና ለቅዱሳን የተሰጠችውንም ሃይማኖት ትጋደሉላት ዘንድ እማልድላችኋለሁ፡፡” በማለት ይናገራል፡፡ (ይሁ. ፩፡፫) ይላልና በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ሃይማኖት፡ የእግዚአብሔር የአካል ሦስትነት፣ የባሕርይ፣ የሕልውና፣ የመፍጠር፣ የመስጠት፣ የመንሣት፣ መለኮታዊ አንድነት፣ የክርስቶስን በፍጹም ተዋሕዶ ሰው ሆኖ መገለጥ፣ መከራ መቀበል፣ መሞት፣ መነሣት፣ ማረግና ዳግም መምጣትን ማመን፤ ያለ ጥምቀት፣ ያለ እርሱ ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም ሕይወት እንደሌለ መቀበልና በፍጻሜም ሰው ከሞተ ከፈረሰ ከበሰበሰ በኋላ ይነሣል ብሎ ጽኑዕ ተስፋን መያዝ ማለት ነው፡፡ (ዘፍ. ፩፥፳፮፤ ፫፥፳፪፣ ኢሳ. ፯፥፲፬፤ ፱፥፮፤ ሚክ. ፭፤፩፣ መዝ፣ ፵፱፥፪፤ ኢሳ. ፵፥፲፤ ራእ. ፳፪፥፲፪፤ ዮሐ. ፫፥፭፤ ማር. ፲፮፥፲፮፤ ዮሐ. ፮፥፶–፶፱፤ ማቴ. ፳፮፥፳፮፤ ኢሳ. ፳፮፥፲፭-፲፮፤ ዳን. ፲፪፭፪)

ይህ ባይሆን ቅዱሳን ሐዋርያት ደጋግመው “በሃይማኖት ጽኑ”፤ “በሃይማኖት ቁሙ” ፤ “ሃይማኖታችሁን ጠብቁ” በማለት ባላስተማሩን ነበር፡፡(ቆላ. ፩፳፮-፳፯፤ ፩ቆሮ. ፲፮፥፲፫፤ ቆላ. ፪፥፯፤ ይሁ. ፩፥፳፤ ሐዋ. ፮፥፯፤ ፲፬፥፲፯)፡፡

ሃይማኖት የተሰጠው ለቅዱሳን እና አምነው በስሙ ለተጠሩት መሆኑን፡-

ሃይማኖት ለቅዱሳን የተሰጠ ስለሆነ ሐዋርያው “ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ስለተሰጠ” አለን፡፡ የክርስትና ሃይማኖት የተሰጠ መሆኑን ሲያጠይቅ፡፡ ቅዱሳን ስንል መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያስተምረን:-

  • ቅዱሳን መላእክትን (ማቴ. ፳፭፥፴፩፤ ዳን. ፬፥፵፪)
  • ቅዱሳን ነቢያትን(፪ጴጥ. ፩፥፳፩፤ ፫፥፴፪)
  • ቅዱሳን ሐዋርያትን(፪ጴጥ. ፫፥፪)
  • ቅዱሳን ጻድቃንና ሰማዕታትን ነው (ሉቃ ፩፥፮፤ ፪ጴጥ. ፪፥፯-፰፤ ዕብ. ፲፥፩-፴፬)
  • እንዲሁም አምነው በስሙ ለተጠሩት እና በስሙ ለሚጋደሉ ሁሉ የተሰጠ ነው፡፡ (፩ቆሮ. ፩፥፪-፫፤ ሮሜ. ፰፳፰-፴)

ስለዚህ ሃይማኖት ለቅዱሳን የተሰጠ ነው ስንል ለቅዱሳን መላእክት፣ ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ ጻድቃንና ሰማዕታት፣ እንዲሁም በስሙ ልጅነትን አግኝተው ጸንተው ለተጋደሉ ሁሉ የተሰጠ ነው ማለታችን ነው፡፡ እኛ የክርስትና ሃይማኖት ተቀባዮች እንጂ ጀማሪዎች አይደለንምና ሌላ እንመሥርት፤ ይህን እንጨምር፣ ያን እንቀንስ የማለት መብቱም ዕውቀቱም ፈቃዱም የለንም፡፡ “በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፡፡” እንዲል፡፡ (ኤፌ. ፪፥፲፱-፳) ሃይማኖት የምንጨምርበት የምንቀንስበት የምንቀጥልበት የላብራቶሪ ውስጥ ቁስ፣ የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም፣ የአስተዳደር ሥርዓት ወይም የፋሽን አይደለምና፡፡ “ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትናና ዛሬ እስከ ዘላለምም ያው ነው፡፡” እንዲል፡፡ (ዕብ. ፲፫፥፯)

የክርስትና ሃይማኖት በባሕርይው ማኅበራዊ እንጂ ግላዊ አይደለም፡፡ “በግልህ አምልክ”፤ “በግልህ ብቻ ጸልይ” ወዘተ የሚሉ መራዥ ንግግሮች በሐዋርያት ትምህርት ቦታ የላቸውም፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት፣ ቅዱሳን ጽኑ፣ ጹሙ፣ ጸልዩ፣ ተሰብሰቡ ብለው የክርስትና ሃይማኖትን ትክክለኛ ጠባይ እኛ እንጂ እኔ እንደማይባልበት ነግረውናል፡፡ አንድነታችንን እንድናጸናና ግለኝነትንም እንድናርቅ ሰብከውናል፡፡ (፩ቆሮ. ፩፥፲፪፤ ዕብ. ፲፥፳፭፤ ሐዋ. ፬፥፵፪፤ ሐዋ. ፪፥፵፯)

ፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለምን፣ ዓለም በዝና ከፍ አድርጋ የሰቀለቻቸውን ሰዎች ንግግር ወይም አቋም፣ እንዲሁ ሳንመረምር የተቀበልነውን ነገር በመያዝ የማንም መንጋ ወይም ተከታይ ሳንሆን ነቢያት ሐዋርያት ያስተማሩንን ትምህርት በመቀበል የክርስቶስ መንጋዎች ልንሆን ይገባል፡፡ (ሐዋ. ፵፥፵፰፤ ዮሐ. ፲፥፳፯)

የክርስትና ሃይማኖት ፍጹም መሆኑን

ቤተ ክርስቲያን ስለ እግዚአብሔር በአካል ሦስት፣ ባሕርይ አንድ ስለ መሆኑ፣ ስለ ጥምቀት፣ ስለ ቁርባን፣ ስለ ሙታን ትንሣኤ፣ ስለ ቅዱሳን ክብር የምታስተምረው ትምህርት ፍጹም ነው፡፡    “ፈጽሞ ስለተሰጠ ሃይማኖት” መባሉን ልብ በሉ፡፡ ስለዚህም በቤተ ክርስቲያን ሆኖ በኃጢአት፣ በዝሙት፣ በስካር፣ በገንዘብ ፍቅር፣ ሆድንና ሥልጣንን በመውደድ ከእግዚአብሔር አንድነትና ፈቃድ የራቀን ሰውነት በንስሓ በማደስ ወደ ፍጹምነት ለማድረስ መጋደል እንጂ ፍጽምት የሆነች የክርስትና ሃይማኖትን ላድስ ማለት ወደ ከፋ የክሕደት፣ የጥፋትና የሞት መንገድ ይወስዳል፡፡(ማቴ. ፭፥፭፰፤ ዘፍ. ፮፥፱፤ ፩ጴጥ. ፭፥፲፩) የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ጉድለትንም የክርስትና ሃይማኖት ጉድለት ከማድረግ እንቆጠብ፡፡

ሃይማኖት የተሰጠው አንድ ጊዜ መሆኑን

ወደ ሕይወት የሚወስድ አንድ መንገድ እንጂ ብዙ ወይም አቋራጭ መንገዶች አይደሉም፡፡ (ኤር. ፮፥፲፮፤ ማቴ. ፯፥፲፫-፲፬) ወደ ሥልጣን፣ ወደ ባለጠግነት፣ ወደ ዕውቀት የሚያደርሱ ብዙ መንገዶች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ወደ እግዚአብሔር የሚወስደው መንገድ (ሃይማኖት) ግን አንድ ብቻ መሆኑን ከላይ የተጠቀሱትን ኃይለ ቃላት በማስተዋል ማንበብ እና በቅንነት መረዳት ይቻላል፡፡ “አንድ ጌታ፤ አንድ ሃይማኖት፤ አንዲት ጥምቀት” እንዲል ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡፡ (ኤፌ. ፬፥፬)

በአንጻሩም እጅግ በሰፋ የምግባር ብልሹነትና ልክ በሌለው የሥጋ ፈቃድ የተሞሉ የጥፋት መንገዶች እንዳሉ እነርሱም ለሰው ቅን እንደሚመስሉ ተነግሮናል፤ የሚያብረቀርቅ ሁሉ ወርቅ አይደለምና፡፡ (ምሳ. ፲፬፥፲፪፤ ማቴ. ፯፥፲፫-፲፬) ከአዳም ጀምሮ የተነሡ ቅዱሳን በሙሉ ወደ እግዚአብሔር የደረሱት በአንድ እምነት ተጉዘው እንጂ በተለያየ መንገድ ሄደው አይደለም፡፡ ሰው በፈለገው መንገድ ለመጓዝ ነጻ ፈቃድ ከተጠያቂነት ጋር እንደተሰጠውም አንዘንጋ፡፡ በሃይማኖት እየኖሩ መጋደል እንደሚገባ ሐዋርያው በዚህ መልእክቱ በክርስትና ሃይማኖት አምነን ከእርሱ   ጋር ስንኖር ፈተና እንዳለና ፈተናውንም ሁሉ በመቋቋም መጋደል እንደሚገባ አስተምሮናል፡፡ ተጋድሎውም ከሥጋውያን ከደማውያን ሰዎች ጋር ሳይሆን በሰዎች ላይ አድረው ከሚመጡ ክፉዎች መናፍስትና ርኩሳን አጋንንት ጋር ነው፡፡ “መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፡፡” እንደተባለ፡፡ (ኤፌ. ፮፥፲፩-፲፮)

የቤተ ክርስቲያን ውጊያ ከሰዎች ጋር አይደለም፤ ድሉም የትግል ስልቱም ማሸነፊያ መሣሪያውም ሥጋዊ አይደለም፡፡ ማሸነፊያው ቃለ እግዚአብሔርን መማር፣ በጾምና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር መጮህ፣ የየራሳችንንም መንፈሳዊ ድርሻ በመንፈሳዊ መንገድ መወጣት፣ እያንዳንዳችንም ራሳችንን መመርመርና ንስሓ መግባት ቅድስናን በመለማመድና ገንዘብ በማድረግ ነው፡፡ (ማቴ ፲፯፥፳፩፤ ኤፌ. ፮፥፲፯፤ ፪ቆሮ. ፲፫፥፭) ስለዚህም ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እስከ ምጽአተ ክርስቶስ ፈተና እንደማይለያት ጠንቅቀን እንወቅ፡፡ በሃይማኖትም ጸንተን እንኑር፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት የእናታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን በረከት   አይለየን!!

ጽዮን ማርያም

“እግዚአብሔር ጽዮንን መርጦአታልና፥ ማደሪያውም ትሆነው ዘንድ ወድዶአታልና፥ ይህች ለዘለዓለም ማረፊያዬ ናት መርጫታለሁና በዚህች አድራለሁ።” (መዝ. ፻፴፩፥፲፫-፲፬) እንዲል ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት በመዝሙሩ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አማናዊት የእግዚአብሔር ማደሪያ የሆነችውን የእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ዓመታዊ በዓል ኅዳር ፳፩ ቀን በድምቀት ታከብራለች፡፡

“ጽዮን” ማለት “አምባ፣ መጠጊያ” ማለት ነው፡፡ “ሰው እናታችን ጽዮን ይላል፤ በውስጥዋም ሰው ተወለደ” (መዝ. ፹፮፥፭) በማለት መዝሙረኛው ዳዊት እንደተናገረ አዳምና ልጆቹ በበደል ምክንያት ለአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ከተፈረደባቸው የሲኦል እሥራት ነጻ ይወጡ ዘንድ እግዚአብሔር ወልድ ከዳዊት ዘር በተገኘችው ቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን አደረ፡፡ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ማኅፀኗን ዙፋን አድርጎ ተወለደ፡፡ እኛም ኦርቶዶክሳውያን የእግዚአብሔር ማደሪያ፣ አምባ መጠጊያ የሆነችውን ድንግል ማርያምን የድኅነታችን መሠረት ናትና እናከብራታለን፣ እናመሰግናታለን፣ ከፍ ከፍም እናደርጋታለን፣ በዓሏንም እናከብራለን፡፡

ታቦተ ጽዮን በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትመሰላለች፡፡ ኅዳር ፳፩ ቀን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ዓመታዊ በዓል በተለየ መልኩ የምናከብርበት ምክንያት በርካታ ቢሆኑም በዋነኛነት ታቦተ ጽዮን በፍልስጤማውያን ተማርካ በነበረበት ወቅት ዳጎን የተባለውን ጣኦት የሰባበረችበትና ልዩ ልዩ ተአምራት የፈጸመችበትን መሠረት አድርገን ነው፡፡

ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከእግዚአብሔር በታዘዘው መሠረት ሁለት ጽላት ቀርጾ፣ የእንጨት ታቦትንም ሠርቶ ወደ ተራራ ወጣ፤ “ከማይነቅዝ እንጨትም ታቦትን ሠራሁ፤ እንደ ፊተኞቹም ሁለት የድንጋይ ጽላት ቀረጽሁ፤ ወደ ተራራም ወጣሁ፤ ሁለቱም ጽላት በእጄ ነበሩ፤ እግዚአብሔርም በተራራው ላይ በእሳት መካከል የተናገራችሁን ዐሥርቱን ቃላት ቀድሞ ተጽፈው እንደነበረ በጽላቱ ላይ ጻፈ፤ እግዚአብሔርም እነርሱን ለእኔ ሰጠኝ፡፡” (ዘዳ. ፲፥፩-፬) በማለት እንደተናገረው የቃል ኪዳኑን ታቦት ይዘው ወደ ምድረ ርስት ተጉዘዋል፡፡

ወደ ትርጓሜው ስንመጣ ታቦተ ጽዮን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ስትሆን፣ በውስጡዋ የያዘችው የሕጉ ጽላት የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ታቦቷ ከማይነቅዝ እንጨት መሠራቷ የጌታን እናት ንጽሕናን የሚያመለክት ሲሆን በውጪም በውስጧም በጥሩ ወርቅ መለበጡዋ የቅድስናዋና ድንግል በሕሊና ወድንግል በሥጋ መሆኗን የሚያስረዳን ነው፡፡ እስራኤላውያንም በፊታቸው ታቦተ ጽዮንን ይዘው የሚገዳደሯቸውን ሁሉ ድል ይነሡ ነበር፡፡

ፍልስጤማውያን ለጦርነት በእስራኤላውያን ተነሡ፤ በአንድነትም ተሰብስበው እስራኤላውያንን ወጉአቸው፣ እስራኤላውያን ያለ ቃል ኪዳኑ ታቦት ተሰልፈዋልና በፍልስጤማውን ድል ተነሡ፡፡ የእስራኤል ሽማግሌዎችም “ዛሬ እግዚአብሔር በፍልስጤማውያን ፊት ስለ ምን ጣለን? በፊታችን እንድትሄድ ከጠላቶቻችንም እንድታድነን የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳኑ ታቦት ከሴሎ እናምጣ” አሉ፡፡ ነገር ግን ቀድሞ እስራኤላውያን በድለዋልና ለፍልስጤማውያን አሳልፎ ሰጣቸው፤ ታቦተ ጽዮንም ተማረከች፡፡ (፩ኛ ሳሙ. ፬፥ ፩-፲፩) ፍልስጤማውያን እግዚአብሔርን የቃል ኪዳኑ ታቦት ወስደው ወደ ዳጎን ቤት አስገብተው ከዳጎን አጠገብ አኖሩ፡፡ በነጋም ጊዜ ዳጎን በእግዚአብሔር ፊት በግንባሩ ወድቆ አግኝተውታል፡፡

በሆነው ነገር ግር ቢሰኙም መልሰው ዳጎኑን አንስተው በስፍራው አቁመው በሩንም ዘግተው ሄዱ፡፡ በነጋም ጊዜ ግን ሲገቡ ዳጎን በግንባሩ ወድቆ ራሱ እና ሁለቱ እጆቹ ተቆርጠው ወድቀው አገኙአቸው፡፡ የእግዚአብሔርም እጅ በአዛጦን ሰዎች ላይ ከበደ፤ የአውራጃዎቿ ሰዎችም በእባጭ በሽታ ተመቱ አይጦችም በከተሞቻቸው ፈሰሱ፤ በከተማውም ላይ ታላቅ መቅሰፍት ሆነ፡፡ የቃል ኪዳኑ ታቦትም ጠንክራብናለች በማለት ከከተማቸው አውጥተው ወደ አስቀሎና ላኳት፤ የአስቀሎናም ሰዎች እጅግ ታወኩ፡፡ “እኛንና ሕዝባችንን ልታስገድሉን የእስራኤልን አምላክ ታቦት ለምን አመጣችሁብን?” ብለው ሰደዱአት፡፡ የእግዚአብሔርም ታቦት በፍልስጤማውያን ዘንድ ለሰባት ወር ቆየች፡፡ ምድራቸውም አይጦችን አወጣች፡፡ ከሕዝቡም ብዙዎች ተቀሰፉ፡፡ በመጨረሻም ከከተማቸው አውጥተው በኮረብታው ላይ ወደ አሚናዳብ ቤት ወሰዷት፤ በዚያም ለሃያ ዓመታት ቆየች፡፡

ከሃያ ዓመት በኋላም እግዚአብሔር ለዳዊት ፍልስጤማውያንን በእጁ አሳልፎ ሰጠው ድልም አደረጋቸው፡፡ “አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦት” እንዲል ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት የእግዚአብሔር ታቦትን ይዘው በእልልታና በዝማሬ በክብር ወደ እስራኤል ተመለሰች፡፡ ዳዊትም በተከላት ድንኳን ውስጥ አኖራት፡፡

ከዚህ ታሪክ በተጨማሪ ከላይ የኅዳር ጽዮንን በዓል የሚከበርበት ምክንያት፡-

፩. ነቢዩ ዘካርያስ ጽዮንን በተቅዋመ ማኅቶት አምሳል ያየበት፣

፪. ቀዳማዊ ምኒልክ ታቦተ ጽዮንን ይዞ አክሱም የገባበት፣

፫. በዮዲት ጉዲት ዘመን በዝዋይ ደሴት ቆይታ ሰላም ሲሆን ተመልሳ አክሱም የገባችበት፣

፬. አብርሀ እና አጽብሐ በአክሱም ከተማ ከ፫፻፴፫-፫፻፴፱ ዓ.ም ቤተ መቅደሱን ሠርተው ቅዳሴ ቤቱን ያከበሩበት ዕለት ስለሆነ ኅዳር ፳፩ ቀን ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በዓሉን በድምቀት ታከብራለች፡፡ (መድብለ ታሪክ፤ ገጽ ፻፶፪)፡፡  በታቦተ ጽዮን ከተመሰለችው ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ያሳትፈን፡፡ አሜን፡፡

 

 

 

 

 

 

“ጾም የነፍስን ቊስል ትፈውሳለች” (ቅዱስ ያሬድ)

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከሚከናወኑ ዐበይት ክርስቲያናዊ ምግባራት መካከል ጾም አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ ጾም “ጾመ” ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ተከለከለ፤ ተወ፤ ታቀበ፤ ታረመ ማለት ነው፡፡ (ጾም እና ምጽዋት ገጽ ፰)

የቤተ ክርስቲያናችን የሕግና የሥርዓት መጽሐፍ የሆነው ፍትሐ ነገሥት ደግሞ በአንቀጽ ፲፭ ላይ ጾምን “ጾምሰ ተከልኦተ ብእሲ እመብልዕ በጊዜ ዕውቅ በውስተ ሕግ፤ ጾምስ በታወቀው ዕለት፤ በታወቀው ሰዓት ከምግብ መከልከል ነው” በማለት ይተረጕመዋል፡፡

እንግዲህ በሃይማኖታዊ ትርጉሙ ጾም ማለት ራስን ከእህል፤ ከውኃ ብሎም አምላካችን እግዚአብሔር ከሚጠላቸው እኩይ ምግባራት ሁሉ ራስን በመከልከል የሥጋን ፈቃድ ለነፍስ በማስገዛት መቆየት ማለት ነው፡፡

ጾም በብሉይ ኪዳንም ሆነ በሐዲስ ኪዳን የታወቀ፣ በነቢያት የነበረ፣ በክርስቶስ የጸና፣ በሐዋርያት የተሰበከ እና የተረጋገጠ መንፈሳዊ ሕግ፤ ፈጣሪን መለመኛ መንፈሳዊ መሣሪያ ነው፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴ የእግዚአብሔርን ጥሪ ተከትሎ ወደ ተራራ በወጣ ጊዜ ለአርባ ቀንና ሌሊት ምግብና ውኃ እንዳልቀመሰ ይነግረናል፡፡ሁለቱን የድንጋይ ጽላት፥ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር የተማማለባቸውን የቃል ኪዳን ጽላት፥ እቀበል ዘንድ ወደ ተራራ በወጣሁ ጊዜ፥ በተራራው ዐርባ ቀንና ዐርባ ሌሊት ተቀምጬ ነበር እንጀራ አልበላሁም፥ ውኃም አልጠጣሁም” ተብሎ እንደተጻፈ። (ዘዳ.፱፥፱) ነቢዩ ዕዝራም በአምላካችን ፊት ራሳችንን እናዋርድ ዘንድ ከእርሱም የቀናውን መንገድ ለእኛ እና ለልጆቻችን ለንብረታችንም ሁሉ እንለምን ዘንድ በዚያ በአኅዋ ወንዝ አጠገብ ጾም አወጅሁ (ዕዝ. ፰፥፳፩) በማለት ራስን ዝቅ በማድረግ ለአምላክ ፈቃድ መገዛት እንደሚገባ ያስተምረናል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊትም “ጉልበቶቼ በጾም ደከሙ፤ ሥጋዬም ቅባት በማጣት ከሳ” በማለት መጾሙን እንረዳለን፡፡ (መዝ ፻፰፥፳፬)

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ስለ መብልና መጠጥ ከንቱነት እንዲህ በማለት አስተምሮናል፡፡ ራሳችሁን ጠብቁ፤ በመብልና በመጠጥ፤ በመቀማጠልና የዓለምን ኑሮ በማሰብ ልባችሁን አታደንድኑ፤ ያቺ ቀንም በድንገት ትደርስባችኋለች፡፡(ሉቃ.፳፩፥፴፬) እንዲል፡፡ ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ ሳይሆን ልዑል እግዚአብሔር የመሠረተው፣ ከእግዚአብሔር ለሰው ልጅ የተሰጠ የመጀመሪያው ትእዛዝ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እከብር አይል ክቡር፣ እነግሥ አይል ንጉሥ፣ እጸድቅ አይል ጽድቅ የባሕርዩ የሆነ አምላክ ነው፡፡ ለእኛ አርአያ ቤዛ ሊሆነን፣ እናንተም ብትጾሙ ብትጸልዩ አጋንንትን ድል ትነሳላችሁ ሲለን፣ ጾምን ለመባረክና ለመቀደስ፤ በመብል ምክንያት ስተን ስለ ነበር ስለ እኛ ኀጢአት እና በደል ሲል ዐርባ ቀንና ሌሊት ጾሟል፡፡

ጾም ከመንፈሳዊ ተጋድሎ አንዱ ነው፤ ለሥጋም መንፈሳዊ ልጓም ነው፡፡ አንድ ክርስቲያን ፈቃደ ሥጋውን እየገታ ነፍሱን የሚያለመልምበት መንፈሳዊ ስንቅ ነው፡፡ “ጾም ቊስለ ነፍስን የምትፈውስ፤ ኃይለ ፍትወትን የምታደክም፤ የበጎ ምግባራት ሁሉ መጀመሪያ፤ ከእግዚአብሔር ጸጋን የምታሰጥ፤ የወንጌል ሥራ መጀመሪያ፤ የጽሙዳን ክብራቸው፤ የደናግል የንጽሕና ጌጣቸው፤ የዕንባ መፍለቂያዋ፤ አርምሞን (ዝምታን) የምታስተምር፤ ለበጎ ሥራ ሁሉ የምታነቃቃ፤ ሰውነትን በእግዚአብሔር ፊት በማዋረድ ትሕትናን ገንዘብ ለማድረግ የምትረዳ መድኃኒተ ነፍስ ናት፡፡ ” (ማር ይስሐቅ አንቀጽ ፬ ምዕ. ፮)

በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ መሠረት ጾም በሁለት ይከፈላል፤ የአዋጅ እና የግል ጾም በማለት፡፡ በዚህም መሠረት የአዋጅ አጽዋማት የምንላቸው  ሰባት ሲሆኑ እነርሱም፡-

  1. የነቢያት ጾም
  2. የገሀድ ጾም
  3. የነነዌ ጾም
  4. ዐቢይ ጾም
  5. የሐዋርያት ጾም
  6. ጾመ ድኅነት (ረቡዕና ዓርብ)
  7. ጾመ ፍልሰታ

እነዚህ አጽዋማት በቤተ ክርስቲያናችን በአዋጅ ጊዜ እና ወቅት ተሰጥቷቸው፣ ሥርዓትም ተበጅቶላቸው ከሰባት ዓመት ሕፃናት እስከ አረጋውያን ለተወሰነ ሰዓት ከምግብ እና ከውኃ በመከልከል በጸሎትና በበጎ ምግባራት በትጋት የሚጾሙት ነው፡፡

የግል ጾም የምንለው ደግሞ አንድ ሰው በሠራው ኃጢአት ምክንያት ለንስሓ አባቱ ተናግሮ የሚሰጠው የንስሓ ጾም ሲሆን እንዲሁም አንድ ሰው ስለደረሰበትና በእርሱ ላይ ስለሆነ ነገር ስለሚፈልገው ጉዳይ እግዚአብሔር ተገቢውን መልስ እንዲሰጠው የሚጾመው ጾም ነው፡፡ ነገር ግን በግል ጾም ጊዜ ጾሙ የሁሉ ስላልሆነ ራስን መሰወር እንደሚያስፈልግ ታዟል፡፡

ይህንንም አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ሲል ተናግሯል፡፡ “ስትጾሙም እንደ ግብዞች አትጠውልጉ ለሰዎች ሊታዩ እንደ ጾመኛ ፊታቸውን ያጠወልጋሉና አንተ ግን ስትጾም ለሰዎች እንዳትታይ ራስህን ተቀባ በስውር የሚያይህ አባትህ በግልጥ ይከፍልሃል” (ማቴ.፮፥፲፮-፲፰) እንዲል፡፡ በዚህም መሠረት የግል ጾምን ከጿሚው ሰው እና ከእግዚአብሔር ውጭ ማንም ማወቅ የለበትም፡፡

የጾም ጥቅም፡-

ቅዱስ ያሬድ የጾምን ጥቅም እንዲህ በማለት ይገልጸዋል፡- “ጾም ትፌውስ ቊስለ ነፍስ፤ ወታጸምም ኵሎ ፍትወታተ ዘሥጋ ፤ ትሜህሮሙ ጽሙና ለወራዙት፤ ጾም የነፍስን ቊስል ትፈውሳለች፤ የሥጋን ፍትወታት ሁሉ ታጠፋለች፤ ለወጣቶችም ትሕትናን ታስተምራለች፡፡” በማለት፡፡

ጾም በቅዱሳት መጻሕፍት እንደ ተገለጸው የሚከተሉት ጥቅሞች አሉት፤ ጥቂቶቹን ስንመለከት፡- የሥጋን ምኞት ያጠፋል፤ የነፍስ ቍስልን ያደርቃል፤ ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ያስገዛል (ፍት.ነገ.፲፭፥፭፻፷፬)፤ መላእክትን መስሎ ለመኖር ያስችላል፤ ልዩ ልዩ መከራን ያቃልላል፤ አጋንንትን ያስወጣል (ኢያ.፯፥፮-፱)፤ ሰማያዊ ክብር እና ጸጋን ያስገኛል (፩ኛነገ.፲፱፥፰)፤ በመንግሥተ ሰማያት ለመኖር የሚያስችል ምግባርን ያሠራል (ሉቃ.፮፥፳፩)፤ ከእግዚአብሔር ዘንድ ይቅርታ እና ምሕረትን ለማግኘት ይረዳል፤ አጋንንትን ድል ለማድረግ ያግዛል (ማቴ.፬፥፲፩፤ አስ.፯)፤ ፈቃደ እግዚአብሔርን ለመፈጸም ይረዳል (፩ኛነገ.፲፱፥፩)፤ ከእግዚአብሔር ቍጣ ለመዳን ያስችላል (ዮና.፫፥፩)፤ የተደበቀ ምሥጢርን ይገልጣል (ዳን.፲፥፲፬)፤ ከቅዱሳን በረከት ያሳትፋል፤ መንፈሳዊ ኃይልን ያሰጣል (፩ኛሳሙ.፯፥፭)፤ ጥበብን ይገልጣል (ዕዝ. ፯፥፮፤ ዳን.፱፥)/፤ ዕድሜን ያረዝማል፤ ትዕግሥትን ያስተምራል፤ ወዘተ፡፡

ጾም ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ በማስገዛት ከኃጢአት ለመራቅ ይረዳናል፡፡ የሥጋ ፍላጎት በቀዘቀዘ ቊጥር ነፍስ ትለመልማለች፤ ለአምላክ ሕግና ትእዛዛት ሁሉ ተገዢ ትሆናለች፡፡ ስለዚህ እኛም አሁን የጀመርነውን የነቢያት ጾም በሥርዓት በመጾምና በመጸለይ ለክርስቲያን የሚገቡ ምግባራትንም በመፈጸም ከአምላካችን ምሕረትን ቸርነትን እናገኝ ዘንድ እንትጋ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ቀኖቹ ክፉዎች ናቸውና ዘመኑን ዋጁ።” (ኤፌ. ፭፥፲፮)

ዲ/ን በረከት አዝመራው

መግቢያ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረን “ቤተ ክርስቲያን ከዓለም ናት፤ በዓለም ውስጥም ትኖራለች፤ ነገር ግን ዓለማዊ አይደለችም”፡፡ (ዮሐ.፲፯፥፲፮) ለመሆኑ ጌታ ከቤተ ክርስቲያን በተቃራኒ ያቆማት “ዓለም” ምንድር ናት? ኦርቶዶክሳዊ ክርስትናችን ከዓለም ጋር የሚቃረንባቸው ዕሴቶቹ ምን ምን ናቸው? በዓለም ስንኖር ክርስትናችንን ሳንጎዳ ለመኖር ምን እናድርግ? በዚህ ጽሑፋችን እነዚህን ነጥቦች በአጭሩ ለማየት እንሞክራለን፡፡

ሀ. ዘረኝነትን በጽናት መቃወም፡-

ዘረኝነት የሰውን ልጅ ድንቅ እና ክቡር ተፈጥሯዊ አንድነት የሚያስክድ እና ከክርስትና በተፃራሪ የቆመ አስተሳሰብ ነው። ልዩ ልዩ ቋንቋዎች፣ ቀለሞች፣ ታሪኮች እና ባህሎች በሰው ልጆች መካከል ቢኖሩም ክርስትና ግን ከዚህ ሁሉ ከፍ ባለ በአዲስ ተፈጥሮ ሰውን አንድ የሚያደርግ ነው። (ራእ.፭፥፱) በአሁኑ ዓለም የተፈጥሮ ሀብትን እና ሥልጣንን ለመቀራመት የሚፈልጉ አካላት ዘረኝነትን እንደ መሣሪያ እየተጠቀሙ በመሆናቸው ክርስቲያኖችን እርስ በእርስ የሚያባላ መጥፎ በሽታ ሆኗል። እኛ ክርስቲያኖች ግን ከዚህ ወጀብ በተቃራኒ በመቆም የሰውን ልጅ ሁሉ በመስቀሉ ወደ አንዲት ዘለዓለማዊት መንግሥቱ የሚሰበስበውን የአምላካችን ክርስቶስን ፈቃድ መፈጸም ይገባናል። (ዕብ.፲፪፥፳፪)

ለ. ዓለማዊነት (Secularism) በብስለት መምራት፡-

“ዓለማዊነት (Secularism)” ማለት ይህን የሚታየውን ዓለም መዳረሻ አድርጎ መኖር ነው፡፡ ዓለማዊነት እግዚአብሔርን መጥላት እና የሚታየውን እና ጊዜያዊውን ተድላ ደስታ መውደድ ነው፡፡ ዓለማዊነት ፍጥረታትን ወድዶ ፈጣሪያቸውን መጥላት ነው፡፡ (፩ኛዮሐ. ፪፥፲፭፣ ያዕ.፬፥፬) ይህ ዓለም በራሱ የእግዚአብሔር ፍጥረት ስለሆነ ክፉ ነገር አይደለም፡፡ (ዘፍ. ፩፥፴፩) ፍጥረታትን በራስ ወዳድነት መበዝበዝ (Utilitarianism) እንጂ እንጠቀምባቸው ዘንድ እግዚአብሔር የፈጠረልንን ፍጥረታት በሥርዓት ከምስጋና ጋር በፍቅር መጠቀም ዓለማዊነት አይደለም፡፡ በአጭር አገላለጽ ዓለማዊነት ማለት በሥጋዊ ፈቃድ የዓለምን መሻት በመፈጸም በኃጢአት ውስጥ መኖር ነው፡፡

እግዚአብሔርን እንኳ ለዚህ ዓለም ብቻ ተስፋ አድርገው ‘ሊበዘብዙት’ የሚሞክሩ “’መንፈሳውያን’ ዓለማውያን (‘Spiritual’ Seculars)” እንዳሉ ይታወቃል፡፡ (፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፲፱) ከላይ በዘረዘርናቸው ምክንያቶች ዓለማዊነት በልቡ ውስጥ ያደረበት ሰው ለኃጢአት ሁሉ የተጋለጠ ነው፡፡ ለኃጢአት የተጋለጠ መሆን ብቻም ሳይሆን ኃጢአትን ማስተባበልንም እና ራሱን ትክክል አድርጎ መቁጠርም ይጠናወተዋል፡፡ በዚህ ምክንያት ዓለማዊነት ከክርስትና እሴቶች ጋር የሚጋጭ አስተሳሰብ በመሆኑ ቅዱሳት መጻሕፍት ራሳችንን ከዓለማዊነት እንድንጠብቅ ደጋግመው ይመክሩናል፡፡ (፩ኛዮሐ.፪፥፲፭፣ ያዕ.፬፥፬)

ሐ. በኦርቶዶካሳዊ ክርስትናችን መጽናት፡-

ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ያልተበረዘ ያልተከለሰ ጥንታዊ እና ርቱዕ (ቀጥ ያለ) ክርስትና ማለት ነው፡፡ ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ስንል ሰዎች በዕውቀታቸው ልክ ያላጠበቡት፣ ለሥጋ ድካማቸው እንዲመች አድርገው ያላሻሻሉት መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረው፣ ሐዋርያት የሰበኩት ቅዱሳን ሊቃውንት አበው የጠበቁትን ንጹሕ ክርስትና ማለታችን ነው፡፡ ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና “አንድ ጊዜ ለቅዱሳን ፈጽማ የተሰጠች” ሃይማኖት ናት፡፡(ይሁዳ ቁ.፱)

ኦርቶዶክሳዊነት እውነተኛ ሃይማኖት፣ እውነተኛ አምልኮ እና እውነተኛ አኗኗር የተካተቱበት ነው፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው እኔ ኦርቶዶክስ ክርስቲያን ነኝ ሲል የሐዋርያትን ሃይማኖት፣ የሐዋርያትን ሥርዓተ አምልኮ እና ሐዋርያት የኖሩትን እና በጽሑፍም በቃልም ያስተማሩትን ክርስቲያናዊ አኗኗር እከተላለሁ እያለ ነው፡፡ (ገላ ፩፥፰፣፪ኛተሰ.፪፥፲፭)

ሐዋርያት የኖሩበት እና በጽሑፍም በቃልም አስተምረውት ለእኛ በትውልድ ቅብብል የደረሰው ክርስቲያናዊ አኗኗር ምን ዓይነት ነው? ሐዋርያት ያስተማሩን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አርዓያነቱን እና ትምህርቱን ተከትሎ በተግባር መፈጸም፣ በኃጢአትና በክሕደት ላለመያዝ ራስን ገዝቶ መኖር፣ ከምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ዘወትር መሳተፍ፣ ይህ ዓለም ለሚመጣው ዓለም መሻገሪያ እንጂ መጨረሻ አለመሆኑን አምኖ በሰማያዊ ልቡና እና በአምላካዊ ተስፋ መኖር ተገቢ ነው፡፡

ማንኛውም በዚህ ዓለም ያለ ነገር ከዚህ እምነታችን እና አኗኗራችን ካናወጠን እና መሰናክል ከሆነን ዓለማዊነት እያጠቃን ነው እንላለን፡፡ ምንም እንኳ ዓለማዊነት በየዘመናቱ ያለ ቢሆንም በተለይ በዘመናችን ለዓለማዊነት እንድንጠቃ የሚያደርጉን ከዘመኑ ተግዳሮቶች (challenges) መካከል ከሳይንስ እና ቴክኖሎጂ መስፋፋት ጋር የሚመጡ ተግዳሮቶች፣ በሉላዊነት (Globalization) ምክንያት እንግዳ የሆኑ አስተሳሰቦች መስፋፋት፣ ኃጢአትን የተለማመደ የባህል ወረራን መፍትሔያቸውንም እየጠቆምን እንመለከታለን፡፡

መ. ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ  ያመጣቸውን ተግዳሮቶች መቋቋም፡-

ሳይንስና ቴክኖሎጂ በራሱ መልካም የሆነ እና ኑሮን የሚያቀል የሰው ልጆች ውጤት በመሆኑ ሊመሰገን ይገባዋል፡፡ ነገር ግን ከሳይንስና ቴክኖሎጂ መስፋፋት የተነሣ ክርስትና የሚፈተንባቸው አጋጣሚዎች ደግሞ በርካታ ናቸው፡፡

ይህንም በሁለት መንገድ ማየት እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው ፈተና በሳይንስና በቴክኖሎጂ ላይ ብዙ ተስፋ በመጣል ሳይንስና ቴክኖሎጂን እንደ አዳኝ (Savior) መቁጠር ነው፡፡ ይህ በምዕራቡ ዓለም ትልቅ ፈተና እየሆነ መጥቷል፡፡

በርግጥ የሳይንስን ታሪክ እና ፍልስፍና ያጠኑ ምሁራን እንደሚጠቁሙት ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዋናው ጥቅሙ የሰውን ልጅ የዕለት ተዕለት ኑሮ ለማቅለል እና ለማሳለጥ እንደሆነ እና ከዚያ ያለፈ በሳይንስ ላይ የተጣለ ተስፋ ባለፉት ፬፻ ዓመታት እንዳልተሳካ ነግረውናል፡፡

በመጀመሪያዎቹ የ’አብርሆት’ ዘመናት (በ፲፮ኛው መ/ክ/ዘመን አካባቢ) ሳይንስ የሰውን ልጅ ሕይወት በእጅጉ እንደሚቀይር እና ምድርን ገነት የሚያደርግ እንደሚሆን ይገመት ነበር፡፡ ነገር ግን እንደተባለው አልሆነም፡፡ ይልቁንም ከዚያ በኋላ በቴክኖሎጂ የታገዙ ሁለቱ ታላላቅ የዓለም ጦርነቶች ያደረሱት የሚሊዮኖች ሞትና ሥቃይን ነው፡፡ በዓለም ላይ የተከማቸው እና በማንኛውም ጊዜ ሊፈነዳ የሚችለው የኒዩክሌር የጦር መሣሪያዎች ክምችት (Nuclear Arsenal) ሳይንስና ቴክኖሎጂ በአግባቡ ካልተጠቀምንበት የጥቅሙን ያህል ጉዳቱ ብዙ እና አደገኛ እንደሆነ ያስገነዝበናል፡፡

ከዚህም በተጨማሪ ሳይንስ ለጥናት የሚጠቀምበት ዘዴ (Scientific Method) በእግዚአብሔር መንፈስ የተቃኙት የቅዱሳት መጻሕፍትን አስተምህሮ ባለማካተቱ ሳይንስ ገና ከጅማሬው በሕይወት ትርጉም ያልሰጠ (Life Values) የተገደበ እና ጉድለት ያለበት ነበር፡፡ በመሆኑም የሰውን ልጅ የዕለት ተዕለት ኑሮ ከማቅለል ውጭ የሕይወት ትርጉም ያላቸውን ዘላለማዊ ጥያቄዎቹን ሊመልስ መንፈሳዊ ዕሴቶቹንም ሊያስቀጥል አልቻለም፤ ወደፊትም አሁን ከሚሄድበት መንገድ የተሻለ የመንፈሳዊ ሕይወት ሊኖረው አይችልም፡፡

ይህም የሳይንስን ፍልስፍና በሚያጠኑ እውነተኛ ምሁራን ዘንድ የታወቀ ቢሆንም በተራው የሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ዘንድ ግን ብዙ ጊዜ ሳይንስ ካቅሙ በላይ የሆነ ተስፋ ሲጣልበት እናያለን፡፡ ይህ ያለአግባብ ተስፋ ብዙ ሰዎች እግዚአብሔርን መፈለጋቸውን እንዲተዉ እና ሳይንስን ሃይማኖት አድርገው እንዲያዩ አድርጓቸዋል፡፡ እኛ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ይህን ማወቅ እና ራሳችን ከዚህ አስተሳሰብ መጠበቅ ይገባናል፡፡ ካልሆነ ግን “በሰው የሚታመን፣ ሥጋ ለባሽንም ክንዱ የሚያደርግ፣ ልቡም ከእግዚአብሔር የሚመለስ ሰው ርጉም ነው” የሚለው ቃል ይደርስብናል፡፡ (ኤር. ፲፯፥፭)

ሌላው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ፈተና ሰውን በክፉ ምኞት ማማለሉ እና በቀላሉ ከኃጢአት ጋር የሚገናኝ ማድረጉ ነው፡፡ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን የመቀያየር አባዜ ተጠናውቷቸው የሚናውዙ ብዙዎች ናቸው፡፡ በኢንተርኔት የዝሙት ምስሎችን (Pornography) በመመልከት እንዲሁም በማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች (Facebook እና የመሳሰሉት) ያለአግባብ ብዙ ጊዜ የሚያጠፉ እና አእምሯቸውን እና ኅሊናቸውን የሚያበላሹትም ጥቂቶች አይደሉም፡፡

እኛ እንደ ኦርቶዶክስ ክርስቲያንነታችን ቴክኖሎጂን በአግባቡ እና በሚያስፈልግበት ጊዜ እና ቦታ መጠቀምን መልመድ ይኖርብናል፡፡ ካልሆነ ግን ከክርስትና እና ከዘላለማዊ ሕይወታችን የሚነጥለን የዘመኑ የዓለም ወጥመድ ይሆናል፡፡

ሠ. ከሉላዊነት እንግዳ አስተሳሰቦችን መዋጋትን መዋጋት፡-

ከሉላዊነት ጋር ተያይዞ በዓለም ላይ ብዙ “እንግዳ” አስተሳሰቦች ይደርሱናል፡፡ ብዙዎቹ አስተሳሰቦች አዲስ ባይሆኑም በመረጃ ሉላዊነት የተነሣ በሌላው የዓለም ክፍል አዲስ ያልሆኑት እኛ ዘንድ አዲስ የሚሆኑበት ጊዜ ብዙ ነው፡፡ እነዚህ አስተሳሰቦች አእምሮውን አምታተውበት ራሱን  ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚያርቅ ይኖራል፡፡

እኛ ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ግን ልቡናችንን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ ማጽናት አለብን፡፡ ሐዋርያው “ልዩ ልዩ በሆነ በእንግዳ ትምህርት አትወሰዱ፤ ልባችሁ በጸጋ ይጽና” እንዳለው አዲስ ነገር በሰማን ቁጥር የምንደነግጥ እና የምንደናበር መሆን የለብንም፡፡ (ዕብ. ፲፫፥፱) ልባችን በጸጋ እንዲጸና ምን ማድረግ አለብን? ኦርቶዶክሳዊ ክርስትናን በሚገባ ለመረዳት መጣር፣ ራስን ከኃጢአትና ከክፉ ምኞት ለመጠበቅ መጋደል፣ በንስሓ ውስጥ ሆኖ ከቅዱስ ቊርባን አለመራቅ፣ ጸሎትን ማዘውተር የመሳሰሉትን መንፈሳዊ ጥረቶች ማድረግ አለብን፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ “ዓለምን የሚያሸንፈው እምነታችን ነው” እንዳለው እምነታችን በጸጋ እግዚአብሔር ማጽናት ይገባናል፡፡ (፩ኛዮሐ.፭፥፭)

ረ. ኃጢአትን የተለማመደ መጤ ባህል መስፋፋትን መግታት፡-

ባለንበት ዘመን ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ተግዳሮት ከሚሆኑ ነገሮች በዘመናዊነት ስም እየተስፋፋ ያለው የክፉ ባህል ወረርሽኝ አንዱ ነው፡፡ እውነተኛ ዘመናዊነት በዘመን ላይ መሠልጠን እንጂ ዘመን ያመጣው መጥፎ ነገር ሰለባ መሆን አይደለም፡፡

በዚህ ዘመን ልንሸሻቸው ከሚገቡን ክፉ ነገሮች አንዱ እየተስፋፋ ያለውን ኃጢአትን የተለማመደ ባህል ነው፡፡ የእኛ የኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ባህላችን ክርስቲያናዊ ነው፡፡ አሁን ግን እንግዳ የሆነ እና ኃጢአት ትክክል ሆኖ የሚቆጠርበት ባህል አኗኗራችን እየተፈታተነው ይገኛል፡፡ ይህ እያጠቃቸው ያሉ ደግሞ ለመገናኛ ቴክኖሎጂ እና “ለዘመናዊነት” ቅርብ የሆኑ በከተማ የሚኖሩ ወጣቶችን ነውና እንቅስቃሴውን ልንገታው ይገባል፡፡

ወጣቶች ልንገነዘበው የሚገባው ኃጢአት ዘመናዊነት እንዳልሆነ ነው፡፡ ይህም ማለት ከማኅበረሰባዊ ዕሴቶቻችንና ከሃይማኖታችን አስተንህሮ ባፈነገጠ የመጤ ባህል ተፅዕኖ ሥር ነውደቅ በኃጢአት ወጥመድ ውስጥ መውደቅ እንጂ መዘመን (ዘመናውያን መሆን) አይደለም፡፡ ለዚህም ነው ኃጢአት ዘመናዊነት አይደለም ምንለው፡፡ ዘመናዊነት ዘመን የወለዳቸውን የሳይንስና ቴክኖሎጂ ውጤቶችን ዘመኑን ለዋጀ አገልግሎት ማዋል ነው፡፡ ሁል ጊዜ የማያረጀው ዘመናዊነት እና አዲስነት ከእግዚአብሔር ጋር መኖር ነው፤ ሁል ጊዜ አዲስ ሆኖ የሚኖር እና የማይለወጥ እግዚአብሔር ብቻ ነውና፡፡ (መዝ. ፻፩፥፳፭-፳፰፣ ራእይ. ፳፩፥፭) የአካል መቆሸሽ በምንም አመክንዮ ዘመናዊነት እንዳልሆነ ሁሉ በኃጢአት መቆሸሽም ዘመናዊነት ሊሆን አይችልም፡፡ ዲያብሎስ ኃጢአትን ከጥንት ጀምሮ ብዙ ጭምብል አልብሶ ያመጣል፤ በዘመናችን ደግሞ የሥልጣኔን ጭምብል ለብሶ ነው የመጣው፡፡ ምንም ቢሆን ግን ኃጢአት ከኃጢአትነቱ ሊወጣ አይችልም፡፡

ከእኛ ከክርስቲያኖች የሚጠበቀው ግን ባህልን መቀደስ እንጂ በክፉ ነገር መወሰድ አይደለም፡፡ ጌታችን “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፤ … እናንተ የምድር ጨው ናችሁ” ማለቱ እኛ ዓለምን ወደ እግዚአብሔር ማቅረብ እንደሚገባን ሲነግረን ነው፡፡ ለዚህም ከእኛ በኩል ጥረት ይፈለጋል፤ ከእግዚአብሔር ዘንድ ደግሞ ኃይል ይገኛል፡፡ (ማቴ. ፭፥፲፫-፲፬፣ ዮሐ. ፲፭፥፭)

እንግዲህ ከላይ የዘረዘርናቸውን ነገሮች በክርስትና ትዕዛዛት እየመረመርን መልካሙን በመያዝ፣ ክፉውን በመተው ዘመኑን መዋጀት ይጠበቅብናል፡፡ ጌታችን በወንጌል እንዳስተማረን እኛ ዓለምን ወደ ብርሃን ማምጣት ይገባናል እንጂ ዓለም ወደ ጨለማው የሚጎትተን ልንሆን አይገባም፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በራስህ ጥበብ አትደገፍ (ምሳ. ፫፥፭)

መ/ር ቢትወደድ ወርቁ

በወጣትነት ዘመናችን እጅግ ከምንቸገርባቸው ጉዳዮች መካከል አንዱ ራስን ዐዋቂ አድርጎ ማሰብ ነው፡፡ ይህም በራስ ጥበብ የመደገፍ አንዱ ችግር ነው፡፡ ለሚፈጠርና ሊፈጠር ላለ ችግር “እንዲህ የሆነው እንዲህ ስለሆነ ነው፤ በዚህ ምክንያት እንዲህ ሊሆን ነው፤ እንደዚህ ያለው ለዚህ ይመስለኛል፡፡” በማለት ራስን ዐዋቂ አድርጎ ማቅረብ በራስ የመደገፍ ፍላጎትን ከፍ ያደርጋል፡፡ እንዲሁም አንድ ድርጊት ከተፈጸመ በኋላ ለምን የሚል ጥያቄ ሲነሣ “ደስ ስላለኝ ነው፤ ስለ መሰለኝ ነው” የሚሉ መልሶች እየበዙ መምጣታቸው በራስ ጥበብ የመደገፋችንን ግዝፈት የሚያመለክቱ ናቸው፡፡

ይህ አስተሳሰብ አደገኛ የሚያደርገውም የሕይወት ልምድ በሌለበት እንኳን በሕይወትና በኑሮ በጽንሰ ሐሳብ ደረጃም ቢሆን የጠለቀ ዕውቀትን ገንዘብ ባላደረግንበት ጊዜ መሆኑ ነው፡፡ ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ ወጣቶች “ለራሴ የማውቀው ራሴ ነኝ፣ በሕይወቴ ጣልቃ አትግቡ…” እና የመሳሰሉ ሐሳቦችን በማንሣት ወላጆቻቸውንና ታላላቆቻቸውን ሲከሱና ሲያስጠነቅቁ ይስተዋላሉ፡፡ የሚያሳዝነው ግን እንዲህ የሚሉ ወጣቶች ራሳቸውን በሚጎዳ፣ የቤተሰቦቻቸውን አንገት በሚያስደፋ፣ ማኅበረሰባዊ ዕሴትን በሚንድ እና ጤናን በሚያናጋ ተግባር ላይ ተሰማርተው ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ፍፃሜአቸው አስከፊ ይሆናል፡፡

ትልቅ ተቋም የሚባለውን ትዳር መሥርተው እንኳን የትዳር አጋራቸውን ምንም የማያደምጡ በቤታቸውና በትዳራቸው ጉዳዮች ሁሉ “እኔ አውቃለሁ፤ እንዲህ ነው መሆን ያለበት” በማለት  በራሳቸው ጥበብ ብቻ በመደገፍ የሚወስኑ ሰዎችም ቁጥር ቀላል አይደለም፡፡ እኔ ትክክል ነኝ ብለው ስለሚያስቡም በራሳቸው ጥበብ ላይ ብቻ በመንጠላጠል ከሌላው አካል የሚቀርብላቸውን ሐሳብ ለማድመጥ ፈቃደኛ ሳይሆኑ ይቀራሉ፡፡

ለዚህ ዓይነቱ ጠባይ መዳረግን የሥነ ልቡናው ዘርፍ እንደ አንድ ትልቅ እክል እንደሚመለከተው የታወቀ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ቃል ያልተመረመረ፣ ታላላቅ ሐሳብ ባላቸው ታላላቅ አባቶችና ወንድሞች ያልተፈተሸ የራስ ጥበብ ወደ ወድቀት ይመራል፡፡ እናታችን ሔዋንና አባታችን አዳም ከእግዚአብሔር የተነገራቸውን “በገነት ካለው ዛፍ ሁሉ ብላ፣፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያሳየውና ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና” የሚለውን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ (ዘፍ. ፪፥፲፮-፲፯) ተላልፈው በራሳቸው ጥበብ በመመካት እና አምላክ የመሆን ፍላጎታቸው አይሎ ለውድቀት ተዳርገዋል፡፡

በወጣትነት ዕድሜ ይቅርና በጉልምስናም ዕድሜ ቢሆን ራስን ብቻ ለራስ አዋቂ አድርጎ መቁጠር ብዙ ዋጋ ያስከፍላል፡፡ ሰው እንደመሆናችን መጠን አያሌ ክፍተቶች ይኖሩብናል፡፡ የዕይታ አድማሳችንም ቢሆን ፍጹም አይደለም፡፡ በራስ ጥበብ ብቻ መደገፍ የትዕቢትም መገለጫ ነው፡፡ በራስ ጥበብ መደገፍ በማንኛውም መመዘኛ ስንመዝነው ትክክል ሊሆን አይችልም፡፡ ለምን? ቢሉ መጽሐፍ “መንገዳችንን እንመርምርና እንፈትሽ” በማለት እንደገለጸው ማንኛውም አስተሳሰብ እና ዕውቀት በእግዚአብሔር ቃል መመዘንና መፈተሽ ተገቢ ነው፡፡ (ሰቆ. ኤር. ፫፥፵)

መንገዳችንን እንመርምር ከተባለ በምን እንመርምረው? የሚል ጥያቄ መነሣቱ ግድ ነው፡፡ ልበ አምላክ ክቡር ዳዊት “ጎልማሳ መንገዱን በምን ያነፃል?” ብሎ ይጠይቅና “ቃልህን በመጠበቅ ነው” በማለት ደግሞ ይመልሳል፡፡ (መዝ. ፩፻፲፰፥፱) በእግዚአብሔር ቃል የተገራ፣ በኑሮ ልምድ የተፈተነ፣ በዕውቀትና በጥበብ የተደራጀ ማስተዋል ያለው ሰው መንገዱ ይቀናለታል፣ እሾህና አሜኬላውን በአሸናፊነት ይሻገራል፡፡

በራስ ዕወቀትና አስተሳሰብ መደገፍ ብዙዎችን ሲጥል ተመልክተናል፡፡ ይህንንም ከሮብአም መማር ይቻላል፡፡ ሮብአም በነገሠበት ዘመን የእስራኤል ጉባኤ በአንድነት ተሠብስበው “አባትህ ቀንበር አክብዶብን ነበር አሁንም አንተ ጽኑውን የአባትህን አገዛዝ በላያችንም የጫነውን የከበደውን ቀንበር አቃልልን እኛም እንገዛልሀለን” ብለው ተናገሩት፡፡

እርሱም መክሬ እስክወስን ከሦስት ቀን በኋላ ተመለሱ አላቸው፡፡ እርሱም ታላላቆቹን የሀገሩን ሽማግሌዎች ሰብስቦ “ለዚህ ሕዝብ እመልስለት ዘንድ በዚህ ዙሪያ ምን ትመክሩኛላችሁ?” አላቸው፡፡ ሽማግሌዎቹም “ለዚህ ባሪያ ብትሆን ብትገዛላቸውም መልሰህም በገርነት ብትናገራቸው በዘመኑ ሁል ባሪያዎች ይሆኑልሃል፡፡” ብለው መልካሙን ምክር መከሩት፡፡ እርሱ ግን ይህንን የሽማግሌዎቹን ምክር ትቶ ከእርሱ ጋር ካደጉት ብላቴኖች ጋር በነገሩ ላይ ተመካከረ፡፡ እነርሱም “አባትህ ቀንበር አክብዶብናል አንተ ግን አቃልልን ለሚሉህ ሕዝብ፡- ታናሺቱ ጣቴ ከአባቴ ወገብ ትወፍራለች፡፡ አሁንም አባቴ ቀንበር ጭኖባችኋል እኔ ግን በቀንበራችሁ ላይ እጨምራለሁ፤ አባቴ በአለንጋ ገርፎአችኋል እኔ ግን በጊንጥ እገርፋችኋለሁ፡፡” በላቸው ብለው ማስተዋል የጎደለው ትዕቢትና ዕብሪት የተጫነው ክፉ ምክር መከሩት፡፡ እርሱም እነዚህ ብላቴኖች እንዳሉት አደረገ፡፡ ይህንም በማድረጉ ሕዝቡ ተነሥተውበት በድንጋይ ደብድበው ገደሉት፡፡ በራስም ሆነ በእግዚአብሐር ቃል ባልተቃኘ ጥበብ መደገፍ ፍፃሜው እንዲህ  ነው፡፡ (፩ነገ. ፲፪፥፩-፲፱)

በራስ ጥበብ መደገፍ ስንጀምር ሁሉንም ነገር በራስ ዕውቀት ልክ ለመመዘንና ለመተንበይ እንጥራለን፡፡ ሰው እንደ ግዙፍ ተራራ ከፊቱ የገጠመውን ተግዳሮት በራሱ ዕውቀትና የዕይታ መነጽር ብቻ የሚመለከት ከሆነ በእግዚአብሔር መታመንን ያጣል፡፡ ለዚህ ነው ጠቢቡ ሰሎሞን “በፍጹም ልብህ በእግዚአብሔር ታምነህ ኑር፤ በራስህም ጥበብ አትደገፍ” በማለት የመከረን፡፡ (ምሳ. ፫፥፭) ችግር ሁሉ በሰው ዕውቀትና የማስተዋል ልክ ይመርመር ከተባለ ይወሳሰባል፤ መከራ ሁሉ ይከብዳል፤ ኀዘን ሁሉ ይጸናል፤ ስለሆነም በራስ ማስተዋል ከመደገፍ በእግዚአብሔር መታመን ይበልጣል፡፡

የራሳችን ማስተዋል ክፋቱ ክፉውን በክፉ መመለስ አቻ የማይገኝለት አማራጭ አድርጎ ማቅረቡ ነው፡፡ ክፉውን በክፉ መመለስ ክፋትን አያጠፋም፡፡ በወጣትነት ዘመናችን ለብስጭታችን ሱሰኝነትን፤ ለኀዘናችን ቁዘማን እንደ መፍትሔ መውሰድ ለበለጠ ስቃይና መከራ ይዳርገናል፡፡

ስለሆነም ጥበባችን እውነተኛ ጥበብ እንዲሆን በእግዚአብሔር ቃል እንመዝነው፡፡ በታላላቆች ምክርም እንገምግመው፡፡ ተግባራችን በሌላውም ላይ ሆነ በራሳችን ላይ ሌላ ችግር እንዳያስከትል በራሳችን ጥበብ መደገፍን አቁመን በእግዚአብሔር እንታመን፣ እንደገፍም፡፡

እውነተኛ ጥበብ መመዘኛው ምንድነው? ለሚል ሰው መጽሐፍ እንዲህ ይላል “ከእናንተ ብልህና አስተዋይ ማን ነው? ከጠባዩ ማማር የተነሣ ሥራውን በቅንነትና በማስተዋል ያሳይ፡፡ ነገር ግን መራራ መቀናናትና መከዳዳት በልባችሁ ካለ አትመኩ፤ በእውነትም ላይ አትዋሹ፡፡ ይህቺ ጥበብ ከላይ የምትወርድ አይደለችም፤ ነገር ግን የምድር ናት፡፡ መቀናናትና መከዳዳት ባሉበት ሥፍራ ሁሉ በዚያ ሁከትና ክፉ ሥራ አሉና፡፡ ላይኛይቱ ጥበብ ግን በመጀመሪያ ንጽሕት ናት፤ በኋላም ታራቂ ገር እሺ ባይ ምሕረትና በጎ ፍሬ የሞላባት ጥርጥርና ግብዝነት የሌለባት ናት፡፡ የጽድቅም ፍሬ ሰላምን ለሚያደርጉት ሰዎች በሰላም ይዘራል፡፡”(ያዕ.፫፥፲፫-፲፰)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዘመነ ጽጌ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የወቅቶች አቆጣጠር መሠረት ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭ ቀን ያለው ወቅት ዘመነ ጽጌ ተብሎ ይጠራል፡፡ በግእዝ ቋንቋ “ጸገየ” ማለት “አበበ፤ አፈራ፤ በውበት ተንቆጠቆጠ፤ አጌጠ፤ የፍሬ ምልክት አሣየ” ማለት ነው፡፡

ዘመነ ጽጌ ምድር በልምላሜ የምትንቆጠቆጥበት ወቅት ሲሆን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ልጇን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሊገድለው ከሚሻው ከሄሮድስና ከጭፍሮቹ ለማዳን ወደ ምድረ ግብጽ የተሰደደችበት ወቅት የሚታሰብበት ነው፡፡ ይህንንም መሠረት በማድረግ ካህናት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ምእመናን በየሳምንቱ እሑድ ከምሽቱ ጀምሮ ማኅሌተ ጽጌ ይቆማሉ፤ ሰዓታት ያደርሳሉ፡፡ በዚህ ጊዜ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በአበባ፣ በትርንጎ፣ በሮማን፣ … እየመሰሉ ለፈጣሪ መዝሙርና ምስጋና ያቀርባሉ፡፡

በይሁዳ ክፍል በቤተ ልሔም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደ ጊዜ ሰብአ ሰገል ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም “ኮከቡን ከምሥራቅ አይተን እንሰግድለት ዘንድ መጥተናልና የተወለደው የአይሁድ ንጉስ ወዴት ነው?” እያሉ መጡ፡፡ በዘመኑ ንጉሡ ሄሮድስ ከእርሱ ሌላ እስራኤልን የሚገዛ እንደሌለ ይመካ ነበርና የጌታችን መድኀኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስ መወለድ በሰማ ጊዜ ደነገጠ፤ ኢየሩሳሌምም በመላዋ ከእርሱ ጋር ደነገጠች፡፡” (ማቴ. ፪፥፩-፫)

አንቺ የኤፍራታ ምድር ቤተ ልሔም ሆይ! አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ነገር ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘላለም የሆነ በእስራኤል ላይ ገዢ የሚሆን ከአንቺ ይወለዳል፡፡” የሚለው የነቢያት ትንቢት ሄሮድስን አስጨነቀው፡፡ ስለዚህም ጌታችንን ሊገድለው ወደደ፡፡ (ማቴ. ፪፥፩-፪) እውነቱንም ሲረዳ ሰብአ ሰገልን በስውር አስጠርቶ “ኮከቡ የታየበትን ዘመን ከእነርሱ ተረዳ፡፡ “ሄዳችሁ የዚያን ሕፃን ነገር ርግጡን መርምሩ፤ ያገኛችሁትም እንደሆነ እኔም መጥቼ እሰግድለት ዘንድ በእኔ በኩል ተመልሳችሁ ንገሩኝ ብሎ ወደ ቤተ ልሔም ሰደዳቸው፡፡” (ማቴ. ፪፥፬-፰)

ሰብአ ሰገልም ወደ ቤተልሔም ሲሄዱ በምሥራቅ ያዩት ኮከብ ሕፃኑ ባለበት ቦታ ላይ ደርሶ እስኪቆም ድረስ ይመራቸው ነበር፡፡ በከብቶች ማደሪያ ግርግም እንስሳት በትንፋቸው እያሟሟቁት ሕፃኑን ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም ጋር አገኙት፤ ወድቀውም ሰገዱለት፡፡ ሳጥኖቻቸውንም ከፍተው ወርቅና ዕጣን፣ ከርቤም እጅ መንሻ አቀረቡለት፡፡

ከዚህ በኋላ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በሕልም ለአረጋዊው ዮሴፍ ተገልጦ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ምድረ ግብጽ ሽሽ፤ ሄሮድስ ሕፃኑን ለመግደል ይፈልጋልና ብሎ ነገረው፤ ሕፃኑንና እናቱን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ይዞ በሌሊት ወደ ግብጽ ምድር ተሰደደ፡፡ (ማቴ.፪፥፲፫)

እመቤታችን ልጇን አዝላ ከአረጋዊው ዮሴፍ እና ከሰሎሜ ጋር የአሥራ አምስት ዓመት ብላቴና ስትሆን ረሃቡንና ጥሙን ተቋቁማ ልጇን ከሄሮድስ እጅ ለማዳን ወደ ግብጽ በረሃ ለመሰደድ ተገደደች፡፡

 እግዚአብሔር በነቢዩ ሆሴዕ ላይ አድሮልጄን ከግብጽ ጠራሁት እንዲል አስቀድሞ እንደ ተናገረው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በልጅነቱ ወደ ምድረ ግብጽ የተሰደደው የተነገረው የነቢያት ትንቢት ይፈጽም ዘንድ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ አምላካችን ክርስቶስ ያለ ጊዜው (ዕለተ ዓርብ) ደሙ አይፈስምና ሊገድለው ከሚፈልገው ክፉ ንጉሥ ከሄሮድስ ለማምለጥ ነው፡፡ (ሆሴ. ፲፩፥ ፩-፪)፡፡

ሰብአ ሰገል ለጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወርቅ ዕጣን እና ከርቤ አቅርበው ወደ ሀገራቸው ሲመለሱ ንጉሡ ሄሮድስ ወደ እርሱ መጥተው ሕፃኑ ያለበትን እንዲነግሩት ባሳሰባቸው አልተመለሱም፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በሕልም ነግሯቸው ስለነበር በሌላ መንገድ ወደ ሀገራቸው ተመለሱ፡፡

ሄሮድስም ሰብአ ሰገል ወደ እርሱ እንዳልተመለሱና እንደዘበቱበት በተረዳ ጊዜ እጅግ ተቆጣቶ በቤተ ልሔምና በአውራጃዎችዋ ያሉትን ከሁለት ዓመት እና ከዚያም በታች የሆናቸውን ሕፃናት አስገደለ፡፡ ያን ጊዜ በነቢዩ ኤርምያስ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመ፡፡ እንዲህ ሲል፡- “ራሔል ስለ ልጆችዋ ስታለቅስ ብዙ ልቅሶና ዋይታ በራማ ተሰማ፤ መጽናናትንም እንቢ አለች፣ ልጆችዋ የሉምና፡፡” እንዲል፡፡ (ማቴ. ፪፥፩-፲፰)

ከሦስት ዓመት ከመንፈቅ የግብጽ ስደት በኋላም ሄሮድስ በመሞቱ የእግዚአብሔር መልአክ ለአረጋዊው ዮሴፍ በግብጽ ሀገር በሕልም ታየው፡፡ እንዲህ ሲል፡- “የሕፃኑን ነፍስ የሚሹ ሙተዋልና ተነሥተህ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ” አለው፡፡ እርሱም ተነሥቶ ሕፃኑንና እናቱን ይዞ ወደ እስራኤል ምድር ገባ፡፡ (ማቴ. ፪፥፲፱-፳፩)

የቅድስት ቤተ ክርሰቲያናችን ሊቃውንት ይህንን መሠረት አድርገው ተመየጢ ማርያም ሀገረኪ ናዝሬተ፣ በላዕሌኪ አልቦ ዘያበጽሕ ሁከተ፣ ወኢትጎንድዪ በግብጽ ከመ ዘአልብኪ ቤተ፣ ዘየኀሥሦ ለወልድኪ ይእዜሰ ሞተ፣ በከመ ነገሮ መልአክ ለዮሴፍ ብሥራተ፤ ማርያም ሆይ! ወደ ሀገርሽ ወደ ናዝሬት ተመለሺ፤ በአንቺ ላይ ሁከት የሚያመጣ ማንም የለም፡፡ ቤት እንደሌለሽ ሁሉ በግብጽ አትቆይ፡፡ ለዮሴፍ በሕልሙ መልአክ እንደ ነገረው የሕፃኑን ነፍስ የፈለገው (ጠላት ሄሮድስ) ሞቷልና በማለት ሊቃውንቱ በማሕሌት ሲያመሰግኑ ያድራሉ፡፡

በአጠቃላይ በዘመነ ጽጌ ዘወትር እሑድ፣ እሑድ በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ማኅሌት በመቆም ታላቅ በዓል ይደረጋል፡፡ እመቤታችን ልጇን ይዛ ከሰሎሜና ከዮሴፍ ጋር ወደ ምድረ ግብጽ በተሰደዱ ጊዜ የደረሰባትን ጭንቅና ውኃ ጥም፤ ግፍና እንግልት ለማስታወስና ከግብጽ ወደ ሀገሯ ናዝሬት መመለስዋን ለመዘከር ሲባል በዘመነ ጽጌ የደመቀ አገልግሎት ይከናወናል፡፡

በዚህ ወቅት የሚቆመው የሰንበት ማኅሌቱ፣ መዝሙሩና ቅዳሴው እንደዚሁም የሚቀርበው የክብር ይእቲና የዕጣነ ሞገር ቅኔ ሁሉ በዘመነ ጽጌ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ እመቤታችን ስደት በረከት ያገኙ ዘንድ የፈቃድ ጾም የሚጾሙ ምእመናንም ብዙዎች ናቸው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ትንሣኤ ምንድን ነው?

መምህር በትረማርያም አበባው

ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን…….በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን

አሰሮ ለሰይጣን……..አግዓዞ ለአዳም

ሰላም….….እምይእዜሰ

ኮነ…….ፍሥሓ ወሰላም

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ

ትንሣኤ፡- ትንሣኤ ተንሥአ ተነሣ ከሚለው የግእዝ ቃል የወጣ ሲሆን ትርጉሙ መነሣት ማለት ነው፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ሞቶ ሥጋው ፈርሶ በስብሶ እንደማይቀር እና በዳግም ምጽአት ጊዜ እንደሚነሣ የሚያመለክት ነው፡፡ የሰው ልጅ ከፈጣሪ የተሰጠውን ትእዛዝ ባለመጠበቁ ምክንያት የሞት ሞት ተፈርዶበት ነበረ፡፡ “እንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ፣ አትንኩትም” ተብሎ ነበርና፡፡ (ዘፍ.፫፣፫) በዚህም ምክንያት ከአቤል ጀምሮ እስከ እለተ ምጽአት ድረስ የሰው ልጅ በሥጋ የሚሞት ሆኗል፡፡ ነገር ግን እንደሞትን አንቀርም፡፡ ሁላችንም ትንሳኤ አለን፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በመነሣት የትንሣኤያችን በኩር ሆኖናልና፡፡(፩ኛ ቆሮ.፲፭፣፳፩)፡፡

“ሞት በሰው በኩል ስለመጣ ትንሳኤ ሙታን በሰው በኩል ሆኗል›› እንዲል፡፡ ዘለዓለማዊ ሞታችን እና ፈርሶ በስብሶ መቅረት የቀረልን አካላዊ ቃል ሥጋችን ተዋሕዶ ሰው ሆኖ ሞትን በሞቱ ድል ከነሣልን በኋላ ነው፡፡ ሊቁ ሱኑትዩ በሃይማኖተ አበው “ሞተ ክርስቶስ በሞተ ዚኣነ ከመ ይቅትሎ ለሞት በሞቱ፤ ሞትን በሞቱ ያጠፋልን ዘንድ ክርስቶስ በተዋሐደው ሥጋ የእኛን ሞት ሞተ ብሎ እንደገለጠው፡፡ (ዮሐ.፲፩፣፳፭)

“ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ” ያለ ጌታ በጥንተ ትንሣኤ መጋቢት ፳፱ ቀን በዕለተ እሑድ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ መልአኩም ማር.(፲፮፣፮) “አትደንግጡ የተሰቀለውን የናዝሬቱን ኢየሱስ ትሻላችሁን? ተነሥቷል” ብሎ ለቅዱሳት አንስት ነግሯቸዋል፡፡ (ሉቃ.፳፬፣፮)፡፡

የክርስቶስ ትንሣኤ ከአልዓዛር ትንሣኤ የተለየ ነው፡፡ አልዓዛርን ያስነሣው ራሱ ክርስቶስ ሲሆን ትንሣኤውም መልሶ ሞት ነበረበት፡፡ ክርስቶስ ግን የተነሣው በራሱ ሥልጣን ነው፡፡ ዳግመኛ ሞትም የለበትም፡፡(ዮሐ.፪፥፲፱፤ ፲፥ ፲፰)”ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት በሦስት ቀንም አነሧዋለሁ” ካለ በኋላ እርሱ ግን ይህንን የተናገረው ቤተ መቅደስ ስለተባለ ሰውነቱ ነበር ይለዋል፡፡ በሌላም የወንጌል ክፍል “እናንተ በሰቀላችሁት እግዚአብሔርም ከሙታን ባስነሣው በናዝሬቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ሥም… ይላል፡፡(ሐዋ.፬፣፲) በሃይማኖተ አበው ደግሞ መንፈስ ቅዱስ አስነሳው የሚል ይገኛል፡፡ ይህን ቢል ሦስቱ አካላት አንዲት ግብረ ባሕርይ ስላላቸው ያችን ለእያንዳንዱ አካላት አድሎ መናገሩ ነው፡፡ አብ አምላክ፣ ወልድ አምላክ፣ መንፈስ ቅዱስ አምላክ ቢል ሦስት አምላክ አንልም፡፡ አንድ አምላክ እንላለን እንጂ፡፡ (ዮሐ.፲፥፴) “እኔና አብ አንድ ነን”(ዮሐ.፲፥፱) እንዲል፡፡ ማስነሣት ሦስቱ አካላት አንድ የሚሆኑበት ግብር ስለሆነ አብ አስነሣው፣ በራሴ ሥልጣን ተነሣሁ፣ መንፈስቅዱስ አስነሣው ቢል አንድ ነው፡፡

የትንሣኤ ዓይነቶች

በዳግም ምጽአት ጊዜ ሙታን ሲነሡ ሁለት ዓይነት ትንሣኤ ይነሣሉ፡፡ አንደኛው ትንሣኤ ዘለክብር ሲሆን ሁለተኛው ትንሣኤ ዘለኀሣር ነው፡፡ ትንሣኤ ዘለክብርን የሚነሡ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ የፈጸሙ ቅዱሳን ናቸው፡፡ ትንሣኤ ዘለኀሣርን የሚነሡት ደግሞ የእግዚአብሔርን ሕግ ያልፈጸሙ ኃጥአን ናቸው፡፡ (ማቴ.፳፭፥፵፮) “እነዚያም (ኃጥአን) ወደ ዘለዓለም ቅጣት ጻድቃን ግን ወደ ዘለዓለም ሕይወት ይሄዳሉ” ተብሎ እንደተገለጠ፡፡ ትንሣኤ ዘለክብርን የተነሡ ጻድቃን ለዘለዓለም በመንግሥተ ሰማያት በተድላ በደስታ ይኖራሉ፡፡ ትንሣኤ ዘለኀሣርን የተነሡ ኃጥአን ደግሞ ለዘለዓለም በገሃነመ እሳት በሥቃይ በሰቆቃ ይኖራሉ፡፡

የትንሣኤ ምሳሌዎች

፩. ፀሐይ፡-

ፀሐይ የመውጣቷ የመወለዳችን ምሳሌ ነው፡፡ ፀሐይ ጠዋት ወጥታ ስታበራ እንድትውል እኛም ተወልደን በዚች ምድር ለመኖራችን ምሳሌ ነው፡፡ በሠርክ ፀሐይ መግባቷ የመሞታችን ምሳሌ ነው፡፡ መልሳ ጠዋት መውጣቷ የትንሣኤያችን ምሳሌ ናት፡፡ (ሃይ.አበ.፶፰፥፭)

፪. ዖፈ ፊንክስ፡-

ይህ ወፍ የሚሞትበት ቀን እንደደረሰ ባወቀ ጊዜ ብዙ ጭቃ ሰብስቦ ወደ ግብጽ ይሄዳል፡፡ በጭቃው ላይ ቆሞ ክንፉን በደረቱ ባማታው ጊዜ ከአካሉ እሳት ወጥቶ ሥጋውን አጥንቱን ሁሉ ያቃጥለዋል፡፡ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ዝናም የያዘ ደመና መጥቶ ዝናም ይዘንማል፡፡ እሳቱንም ያጠፋዋል፡፡ ከዚያ ከአመዱ ትንኝ ይገኛል፡፡ክንፍም ይበቅልለታል፡፡ ቡላል አህሎ ያድራል፡፡ በሦስተኛው ቀን እንደቀደመ አካሉ ይመለስለታል፡፡

የራሳችን ፀጉርም ከተላጨ በኋላ መልሶ ሌላ አዲስ ፀጉር ይበቅልልናል፡፡ የእጅ ጥፍርም እንዲሁ ከተቆረጠ በኋላ አዲስ ጥፍር ይወጣል፡፡ ይህ ሁሉ ምሳሌ ዘየሐጽጽ ነው፡፡ እኛ በምንነሣበት ጊዜ ይዘነው የምንነሣው ሥጋ የማይራብ የማይጠማ ሥጋን ነው፡፡ በምስጋና እና በጸጋ ላይ ጸጋ እየተጨመረለት የሚሄድ ሥጋን ይዘን ነው የምንነሣው፡፡ ሌላው እና ዋናው ግን በኃጢአት የወደቅን ሰዎች በንስሓ ተነሥተን አዲስ ልብን ገንዘብ ማድረግ ይገባናል፡፡ ይህም ትንሣኤ ልቡና ይባላል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

 

 

 

“ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይችላል?” (ዮሐ. ፫፥ ፬)

በእንዳለ ደምስስ

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በቅዱስ ያሬድ አማካይነት ከዓመት እስከ ዓመት ሳምንታቱን በወቅት፣ በጊዜ ከፋፍላ አገልግሎት ትፈጽማለች፡፡ በዚህም መሠረት የዐቢይ ጾም ስምንቱን ሳምንታት በቅዱስ ያሬድ አስተምህሮ መሠረት ዜማውንና ምንባባቱን ሁሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ተመሥርታ ሥርዓቱን ታከናውናለች፡፡

በዚህም መሠረት የዐቢይ ጾም ሰባተኛ ሳምንት የአይሁድ መምህር በነበረውና ሌሊት ሌሊት በጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግር ሥር ቁጭ ብሎ ወንጌል ይማር በነበረው በኒቆዲሞስ ይጠራል፡፡

የአይሁድ አለቆች ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን “ተአምራት አሳየን” እያሉ ጥያቄ ያቀርቡለት ነበር፡፡ ተአምራቱንም ድውያንን በመፈወስ፣ አንካሳውን እያቀና፣ ዲዳውን እያናገረ፣ የሥውራን ዐይን እያበራ ሲያዩት ደግሞ “ሕጋችንን ሻረ” እያሉ ይከሱት ነበር፡፡

ኒቆዲሞስ ግን የአይሁድ አለቃቸውና መምህራቸው ሲሆን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታላላቅ ተአምራትን ሲያደርግ ተመልክቶ እንደ አይሁድ መምህርነቱ ከመቃወም ይልቅ ከአይሁድ ተደብቆ በሌሊት ወደ እርሱ እየመጣ ከእግሩ ሥር ቁጭ ብሎ ይማር እንደነበር መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ “ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነ ኒቆዲሞስ የተባለ አንድ ሰው ነበረ፡፡ እርሱም በሌሊት ወደ ጌታችን ኢየሱስ መጥቶ እንዲህ አለው፡- መምህር ሆይ ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን፤ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርገውን ይህን ተአምር ሊያደርግ የሚችል የለምና” ብሎታል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የኒቆዲሞስን ምስክርነት መሠረት አድርጎም “እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ያልተወለደ ሰው የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም” ሲል መልሶለታል፡፡ በጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ንግግር ግራ የተጋባውና ምሥጢሩ የረቀቀበት ኒቆዲሞስ ግን እንግዳ ለሆነበት አገላለጽ ምላሽ ይሰጠው ዘንድ በመሻት “ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይችላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?” ሲል ጠየቀ፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ የአይሁድ መምህር ቢሆንም ምሥጢር ተሰውሮበታልና በቅንነት ለጠየቀው ጥያቄ ምላሽ ሳይሰጠው አላለፈም፡፡ “እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነውና፣ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና፡፡ ስለዚህ ዳግመኛ ልትወለዱ ይገባችኋል ስላልኩህ አታድንቅ” በማለት ለጥያቄው መልስ ሰጥቶታል፡፡

ኒቆዲሞስም ምንም እንኳን የኦሪት መምህር ቢሆንም ይበልጥ የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መልስ እጅግ ረቀቀበት፡፡ አላዋቂነቱን አምኖ ያልገባውን ምሥጢር ከአምላኩ ጠይቆ ለመረዳት ወደ ኋላ ባለማለትም “ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል?” ሲል ለአእምሮው የረቀቀበትን ምሥጢር ገልጾ ያስረዳው ዘንድ መልሶ ጥያቄውን አቅርቧል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም “አንተ የእስራኤል መምህራቸው ነህ ነገር ግን እንዴት ይህን አታውቅም? እውነት እውነት እልሃለሁ የምናውቀውን እንናገራለን፤ ያየነውንም እንመሰክራለን፤ ነገር ግን ምስክርነታችንን አትቀበሉም፡፡ በምድር ያለውን ስነግራችሁ ካላመናችሁኝ በሰማይ ያለውን ብነግራችሁ እንዴት ታምኑኛላችሁ? ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም” በማለት አስረድቶታል፡፡

ኒቆዲሞስ አሁንም ግልጽ ይሆንለት ዘንድ በመፈለግ የተከፈለበትን ምሥጢር ይረዳ ዘንድ ከአይሁድ ተደብቆ በሌሊት ወደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመገስገስ የቃሉን ትምህርት በመማር ተጋ፡፡

ኒቆዲሞስ ከቀኑ ክፍለ ጊዜ ይልቅ ሌሊቱን ለምን መረጠ? ብለን ስንጠይቅ ስለ ተለያዩ ምክንያቶች ሌሊቱን መርጧል፡፡ እነርሱም፡-

ኒቆዲሞስ የአይሁድ መምህራቸው ስለነበር፤ መምህር ሲሆን ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ እግር ሥር በቀን ቁጭ ብሎ ሲማር ቢያዩት መምህር መባሌ ይቀርብኛል ሲል ከንቱ ውዳሴን ሽቶ፤ ሌላው ኒቆዲሞስ አይሁድ እንዳያዩት ፈርቶ፤ ሦስተኛው ከቀን ይልቅ ሌሊት አእምሮ ስለሚረጋጋ፣ በሙሉ ልብ በማስተዋል መማርን ፈልጎ ነው፡፡

ሌሊት ጨለማ ነው፤ ብርሃንም የለም፡፡ ጨለማ ደግሞ የኃጢአት ምሳሌ ነው፡፡ ኒቆዲሞስም ስለ ኃጢአቱ ንስሓን ሽቶ ወደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ በሌሊት መጥቷል፡፡ እንዲሁም ሌሊት የብሉይ ኪዳን ምሳሌ ነው፡፡ ኒቆዲሞስም የኦሪት መምህርነቱን አምኖ ወንጌልን ከአንተ እማር ዘንድ ይገባል ሲል ወደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ በሌሊት መጥቶ መማሩን ያመለክተናል፡፡

እኛም ክርስቲያኖች ከኒቆዲሞስ ሕይወት ልንማር ያስፈልገናል፡፡ ቃለ እግዚአብሔርን ከአባቶችና ከመምህራን እግር ሥር ቁጭ ብሎ መማር ሕይወታችንን እንድንመረምር፣ ከገቢረ ኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ እንድንመለስ፣ ስለ በደላችንም ንስሓ እንድንገባ ስለሚያደረገን በጾም በጸሎት ተወስነን እንደ ኒቆዲሞስ በትጋትና በቅንነት ልንመላለስ ይገባል፡፡ እንደ ቃሉ ተመላልሰን የመንግሥቱ ወራሾች ያደርገን ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን ፡፡ አሜን፡፡

ጾም

መ/ር በትረ ማርያም አበባው

፩. ጾም ምንድን ነው?

ጾም ማለት ለተወሰነ ሰዓት ከምግብ መከልከል፣ ለተወሰኑ ቀናት ከጥሉላት መከልከል፣ ለዘለዓለሙ ደግሞ ከኃጢኣት መከልከል ማለት ነው። ስለ ጾም ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ በሰፊው ይናገራል። “ጾምሰ ተከልዖተ ብእሲ እመብልዕ በጊዜ ዕውቅ በውስተ ሕግ እንዘ ይትኤዘዝ ለዘሐገጎ፤ የጾምን ሕግ ለሠራው ጌታ እየታዘዙ ለተወሰኑ ሰዓታት ለተወሰኑ ቀናት ከምግብ መከልከል ነው።”

ቅዱስ ያሬድ በድጓው “ዓይን ይጹም እዝንኒ ይጹም እምሰሚአ ኅሡም” ብሏል። ይህም ማለት ጆሮ ክፉ ከመስማት ዓይን ክፉ ከማየት ይከልከል ማለት ነው። አጠቃላይ ሕዋሳቶቻችን ክፋትን ከማድረግ ይከልከሉ ማለት ነው። ይህ ዓይነት ጾም እስከ እለተ ሞታችን ድረስ የምንጾመው ጾም ነው። ጾም በብሉይ እና በሐዲስ የነበረ ሕግ ነው “ጾምን ቀድሱ” ብሏል  (ኢዮ. ፩፥፲፬)፡፡

“ጉልበቶቼ በጾም ደከሙ፤ ሥጋዬም ቅቤ በማጣት ከሳ” (መዝ. ፻፱፥፳፬) እንደ ተባለው በጾም ወቅት ከጥሉላት ምግቦች ማለትም ከሥጋ፣ ከወተት፣ ከቅቤ እና ከመሳሰሉ ምግቦች መከልከል ይገባል። ፍትሐ ነገሥቱም አንቀጽ ፲፭ ቁጥር ፭፻፷፭ “ወኢይትበላዕ ቦሙ ሥጋ እንስሳ ወኢ ዘውእቱ እምእንስሳት፤ የእንስሳት ሥጋ አይበላ ከእንስሳት የሚገኙ ቅቤ ወተትም አይበላ” ይላል። ነቢይት ሐና “በጾምና በጸሎት ሌሊትና ቀን እያገለገለች ከመቅደስ አትለይም ነበር” ተብላለች። ይህ ጾሟ፣ ጸሎቷ ደግሞ የእስራኤልን መድኃኒት ጌታን ለማየት አብቅቷታል። (ሉቃ. ፪፣፴፯)

ቅዱስ ጳውሎስም ጾምን “በመትጋትና በመጾም፣ በንጽሕናና በዕውቀት፣ በምክርና በመታገሥ፣ በቸርነትና በመንፈስ ቅዱስ አድልዎ በሌለበት ፍቅር፣ በእውነት ቃል በእግዚአብሔር ኃይል ለቀኝና ለግራ በሚሆን የጽድቅ የጦር እቃ” ብሎታል። (፪ኛ ቆሮ. ፮፥፭-፰)

፪. ጾም ለምን ይጠቅማል?

ሀ. እግዚአብሔርን በረድኤት ለመፈለግ፡- ይህም ማለት በሥጋም በነፍስም ይረዳን ዘንድ እንጾማለን። (፪ኛ ዜና.መዋ. ፳፥፫)፡፡ “ኢዮሳፍጥም ፈራ እግዚአብሔርንም ሊፈልግ ፊቱን አቀና በይሁዳም ሁሉ ጾም ዐወጀ” ይላል። እግዚአብሔርን በረድኤት ለመፈለግ ኢዮሳፍጥ ያደረገው ጾምን ማወጅ ነበረ። “የነነዌም ሰዎች እግዚአብሔርን አመኑ፤ ለጾም አዋጅ ነገሩ። ከታናሹም ጀምሮ እስከ ታናሹ ማቅ ለበሱ፡፡” የነነዌ ሰዎች በበደላቸው ምክንያት ሀገራቸው ልትጠፋ ነበር። ነገር ግን ጾም አውጀው ሁሉም ሰው ከጾመ በኋላ ሀገሪቱ ከጥፋት ድናለች። (ኢዮ. ፪፣፲፪)

“አሁንስ ይላል እግዚአብሔር በፍጹም ልባችሁ በጾምም በልቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ” ይላል እግዚአብሔር። ይህም ኃጢኣታችንን በደላችንን አምነን በጾም በልቅሶ ወደ እግዚአብሔር ብንመለስ ከጥፋት እንደምንድን ማሳያ ነው።

ለ. የቀናውን መንገድ ለማግኘት፡- “በአምላካችን ፊት ራሳችንን እናዋርድ ዘንድ ከእርሱም የቀናውን መንገድ ለእኛና ለልጆቻችን ለንብረታችንም ሁሉ እንለምን ዘንድ በዚያ በአኅዋ ወንዝ አጠገብ ጾም አወጅሁ” ይላል (ዕዝ. ፰፥፳፩)  ቁጥር ፳፫ ላይ ደግሞ የጾምን ውጤት እንዲህ ብሎ ያስቀምጠዋል “ስለዚህም ነገር ጾምን ወደ እግዚአብሔርም ለመንን። እርሱም ተለመነን” ይላል። ዕዝራ ጾምን ያወጀበትን ምክንያት ተናግሯል ለእኛ ለልጆቻችን እና ለንብረታችን የቀናውን መንገድ ፈጣሪ ይሰጠን ዘንድ ነው በማለት።

ሐ. ለፈውሰ ሥጋ ወነፍስ፡- ጾም ከአጋንንት እስራት ነጸ ለመውጣት ለሥጋዊ ፈውስ እና ኃጢኣትን ለማስተስረይ ይጠቅማል። ጌታም ደቀ መዛሙርቱ ሊፈውሱት ያልቻሉትን በሽታ በምን እንደሚፈወስ ሲነግራቸው “ይህ ወገን በጸሎትና በጾም ካልሆነ በምንም ሊወጣ አይችልም” ብሏቸዋል።(ማር.፱፥፳፱)

ቅዱስ ያሬድም በድጓው ይህንኑ የሚያጠናክር ቃል ተናግሯል “ጾም ትፌውስ ቊስለ ነፍስ ወታጸመም ኲሎ ዘሥጋ ፍትወታ፤ ጾም የነፍስን ቁስል ታድናለች የሥጋን ፍትወትም ታጠፋለች” ብሏል። የነፍስ ቁስል የተባለ ኃጢኣት ነው። ጾም የነፍስን ቁስል ታድናለች ማለት ኃጢኣትን ታስተሰርያለች ማለት ነው።

ሠለስቱ ምእትም በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ቁጥር ፭፻፷፬ “ለሥርየተ አበሳ ኃጢኣቱ ሊሠረይለት፤ ወብዝኀ እሴት፤ ዋጋው ሊበዛለት፣ ከመ ያድክም ኃይለ ፍትወት፤ የፈቲውን ጾር ያደክም ዘንድ፣ ወትትአዘዝ ለነፍስ ነባቢት፤ ሥጋ ለነባቢት ነፍስ ትታዘዝ ዘንድ ለክርስቲያን ሁሉ ጾም የታዘዘ ነው እንዲል፡፡

፫. ተቀባይነት የሌለው ጾም፡- ጾም ከጸሎት እና ከፍቅር ጋር እንዲሁም ከሌሎች መልካም ሥራዎች ጋር ካልሆነ ተቀባይነት የለውም። ይህንንም እግዚአብሔር እንዲህ ይለናል “ስለምን ጾምን አንተም አልተመለከትኽንም” ይላሉ። እነሆ በጾማችሁ ቀን ፈቃዳችሁን ታደርጋላችሁ። ሠራተኞቻችሁንም ሁሉ ታስጨንቃላችሁ። እነሆ ለጠብና ለክርክር ትጾማላችሁ። እኔ ይህንን ጾም የመረጥሁ አይደለም። ይህ ጾም በእግዚአብሔር ዘንድ የተመረጠ አይደለም” ተብሏል (ኢሳ.፶፰፥፫-፭)

ሰውን እየበደልን እኛ ብንጾም ጾማችን በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት የለውም። ሰው ጿሚ ነህ ይበለኝ ብለን በሌሎች ሰዎች ለመወደስ የምንጾመው ጾምም ተቀባይነት የለውም። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “አንተ ግን ስትጦም በስውር ላለው አባትህ እንጂ እንደ ጦመኛ ለሰዎች እንዳትታይ ራስህን ተቀባ ፊትህን ታጠብ። በስውር የሚያይ አባትህ በግልጥ ይከፍልሃል” ብሎ ተናግሯል።(ማቴ.፮፥፲፯-፲፰)

በእርግጥ ይህ ቃል የተነገረው ከአዋጅ ጾም ውጭ ለምንጾመው የፈቃድ ጾም ነው እንጂ የአዋጅ ጾምስ በአዋጅ የሚጾም በሁሉ የሚታወቅ ስለሆነ ከንቱ ውዳሴ የለበትም። በስውር ጹም የተባለ ከአዋጅ አጽዋማት ውጭ ከንስሓ አባታችን ቀኖና ተቀብለን በምንጾመው እና እኛው በፈቃዳችን በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ ለማግኘት ብለን በምንጾመው ጾም ጊዜ ማንም የትሩፋት ጾም እንደምንጾም ሊያውቅ አይገባም።

፬. የአዋጅ አጽዋማት

በብሉይ ኪዳንም በተለየ የሚጾሙ ቀናት ነበሩ። ይህንንም “የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። የአራተኛው ወር ጾም የአምስተኛውም የሰባተኛውም የአሥረኛውም ወር ጾም ለይሁዳ ቤት ደስታና ተድላ የሐሴትም በዓላት ይሆናል”(ዘካ. ፰፥፲፱) ከዚህ የምንረዳው በተጠቀሱት ወራት የሚጾም ጾም እንደነበረ ነው። በሐዲስ ኪዳንም ሁሉም ክርስቲያን ሊጾማቸው የሚገቡ ሰባት የአዋጅ አጽዋማት አሉ። እነዚህም የሚከተሉት ናቸው፡-

ሀ. ጾመ ኢየሱስ፡- ይህ ጾም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገዳመ ቆሮንቶስ የጾመውን አስበን የምንጾመው ጾም ነው። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ   እንደተጠመቀ ልዋል ልደር ሳይል ከጥር ፲፩ ጀምሮ እስከ የካቲት ፳፩ ድረስ በቆሮንቶስ ገዳም ገብቶ ጾሟል (ማቴ.፬፥፩) የዚህ ጾም የመጀመሪያው ሳምንት ዘወረደ ይባላል። እስከ ፲፪ ሰዓት ይጾማል። ሁለተኛው ሣምትን ቅድስት፣ ሦስተኛው ሣምንት ምኲራብ፣ አራተኛው ሣምንት መጻጉዕ፣ አምስተኛው ሣምንት ደብረ ዘይት፣ ስድስተኛው ሣምንት ገብር ኄር፣ ሰባተኛው ሣምንት ኒቆዲሞስ፣ ስምንተኛው ሣምንት ሆሣዕና ይባላል። ከቅድስት ጀምሮ እስከ ኒቆዲሞስ አርብ እስከ ፲፩ ሰዓት ይጾማል። ከሆሣዕና ጀምሮ እስከ ትንሣኤ ያለው ሰሙነ ሕማማት ይባላል። እስከ ምሽቱ ፩ ሰዓት ይጾማል። ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ቁጥር ፭፻፷፭።

ለ. ጾመ ድኅነት፡- ይኸውም ከበዓለ ሃምሳ ውጭ እና ጥምቀትና ልደት ረቡዕ እና አርብ ካልዋለ በሌላው ጊዜ መጾም ነው። ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ቁጥር ፭፻፷፮። ረቡዕ እና አርብ የሚጾሙትም እስከ ዘጠኝ ሰዓት ነው።

 ሐ. የነነዌ ጾም፡- ይህም ለጊዜው የነነዌ ሰዎች ከጥፋት ድነውበታል። (ትንቢተ ዮናስን ይመልከቱ)። እኛም መቅሰፍት እንዳይደርስብን እንደ ነነዌ ሰዎች እንጾመዋለን። (ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ቁጥር ፭፻፷፯)፡፡

 መ. የገሃድ ጾም፡- ይህም የልደት እና የጥምቀት ዋዜማ በሚውለው ዕለት የሚጾም ነው። ጥምቀት ጌታ አንድነቱን ሦስትነቱ የገለጠበት ሲሆን ልደት ደግሞ የማይታየው በሥጋ የተገለጠበት የታየበት ስለሆነ ገሃድ ማለት መገለጫ ማለት ነው። (ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ቁጥር ፭፻፷፯)፡፡

ሠ. የነቢያት ጾም፡- ይኸውም በአራቱም ዘመናት ከኅዳር ፲፭ ጀምሮ እስከ ልደት ያለው ነው። ነቢያት ጌታ ይወርዳል ይወለዳል እያሉ የጾሙት ጾም ነው። ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ቁጥር ፭፻፷፰)፡፡

ረ. የሐዋርያት ጾም፡- ይህ ደግሞ ከጰራቅሊጦስ ጀምሮ እስከ ሐምሌ ፭ የሚጾመው ጾም ነው። ሐዋርያት በዕጣ ተከፋፍለው ወደየሀገረ ስብከታቸው ከመሄዳቸው በፊት አገልግሎታቸው የሠመረ ይሆን ዘንድ የጾሙት ጾም ነው(ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ቁጥር ፭፻፷፱)፡፡

ሰ. ጾመ ማርያም፡- ከነሐሴ ፩ ጀምሮ እስከ ነሐሴ ፲፮ ያለው ነው። ሐዋርያት ሥጋ ማርያምን ለማግኘት ሱባኤ የገቡበትና ጌታም ከአጸደ ገነት አምጥቶ ሰጥቷቸው ገንዘው ከቀበሯት በኋላ ነሐሴ ፲፮ ተነስታ አርጋለች። የዚያ መታሰቢያ ነው። ሰባቱ የአዋጅ አጽዋማት የሚባሉት እነዚህ ናቸው። ከዐቢይ ጾም ውጭ ያሉት ሌሎች አጽዋማት እስከ ፱ ሰዓት ነው የሚጾመው። በጾም ወቅት እሑድ ቅዳሜ ከጥሉላት ብቻ ተከልክለን እንውላለን እንጂ እንደሌለው እስከዚህ ሰዓት ጹም የሚል የላቸውም። ቀዳም ስዑር ብቻ ይጾምባታል። በሌላው ግን የለም። ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ቁጥር ፭፻፸፪ ፡፡ “ወኢይጹሙ በዕለተ እሑድ ወበሰንበት ዘእንበለ ጥሉላት” እንዲል።

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን።

“ጽጌ እንተ ኢትትነገፍ፤ የማትረግፍ አበባ” (ቅዱስ ያሬድ)

በዲ/ን ሕሊና በለጠ

በቤተ ክርስቲያናችን ከመስከረም ሃያ ስድስት እስከ ኅዳር አምስት ያለው ዓርባ ቀናትን የያዘው ጊዜ ዘመነ ጽጌ፣ ወርኃ ጽጌ በመባል የሚታወቅ ነው። ከዋክብትን ለሰማይ ውበት የፈጠራቸው አምላካችን እግዚአብሔር አበቦችን ደግሞ ምድርን ያስጌጧት ዘንድ ፈጥሯቸዋል። አበቦች ለመጀመሪያ ጊዜ በምድር ላይ መታየት የጀመሩት በዕለተ ሠሉስ፣ በሦስተኛው የፍጥረት ዕለት ነው። ይህንን የመዘገበልን ሙሴ በኦሪት ዘፍጥረት ላይ እንዲህ ይለናል፡ ‹‹ምድርም ዘርን የሚሰጥ ሣርንና ቡቃያን እንደ ወገኑ ዘሩም ያለበትን ፍሬን የሚያፈራ ዛፍን እንደ ወገኑ አበቀለች። እግዚአብሔርም ያ መልካም እንደ ሆነ አየ››። (ዘፍ.፩፡፲፪)።

ጊዜን በወቅቶች ከፍሎ፡ በየትኛው ጊዜ ምን ዓይነት ምስጋናን ማቅረብ እንደሚገባን ሥርዓትን በመጻሕፍቱ የሠራልን ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ፡ በዚህ የሙሴ ቃል ላይ ተነሥቶ በድጓ ዘጽጌ እንዲህ ይለናል፡- ‹‹በቀዳሚ ገብረ እግዚአብሔር ሰማየ ወምድረ ወሤሞ ለፀሐይ ውስተ ጠፈረ ሰማይ ወርእየ ከመ ሠናይ ወካዕበ ይቤ ለታውፅዕ ምድር ጽጌያተ ዘበድዱ ወፍሬያተ ዘበበዘመዱ – በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን ሠራ፤ ፀሐይንም በጠፈር ላይ አሠለጠነው፤ የሠራው ሁሉ መልካም እንደ ሆነ እግዚአብሔር አየ። ዳግመኛ ምድር አበቦችን በየግንዱ ፍሬዎችን በየነገዱ ታውጣ እንዳለ››። (ድጓ ዘጽጌ)። እግዚአብሔር ሰውን በዕለተ ዓርብ የፈጠረው ሰማይን በከዋክብት፣ ምድርን በዕፅዋት አስጊጦ ከፈጸመ በኋላ ነው። ቅዱስ ያሬድ በዚሁ በጽጌ ድጓው እንዳለውም ‹‹ወወሀበ ገነተ ምስለ ጽጌያት – ገነትንም በአበቦች እንዳሸበረቀች ሰጠው›› እንዲል።

አንድ ደጋሽ ምግቡን አዘጋጅቶ፣ መጠጡን አሰናድቶ፣ ቤቱን አስውቦ የከበረ እንግዳውን በመጨረሻ እንደሚጠራው፡ እግዚአብሔር አምላክም ከፍጥረታት ይልቅ የከበረውን ሰው ሁሉን አሰናድቶ ከፈጸመ በኋላ ፈጠረውና በሁሉ ላይ ሾመው። አዳም ይኖርባት ዘንድ የተሰጠችው ገነትም ያማረችና የተዋበች ነበረች። ለዚህ ነው አምላካችን ‹‹ወይቤሎ ለአዳም ወሀብኩከ ርስተ ገነተ ትፍሥሕት በጽጌ ሥርጉተ ወበፍሬ ክልልተ- ለአዳም ‹አዳም ሆይ በፍሬ የተከበበች በአበባ የተሸለመች የደስታ ገነትን ለአንተና ለልጆችህ ርስት ትሆንህ ዘንድ ለርስትነት ሰጠሁህ›› በማለት ገነትን ‹‹የደስታ ገነት›› ብሎ የሰጠው። (ድጓ ዘጽጌ)። አዳም በበደለ ጊዜ ግን ባሕርይው ጎሰቆለ። ከገነት ወጣ፤ ስደተኛ ሆነ፤ ምድርም በአዳም ምክንያት ተረገመች። ዕፀ በለስን በመብላት መዋቲነትን መረጠ። ምንም እንኳን ለዘላለም ሕይወት ቢፈጠርም በበደሉ ምክንያት የሚሞት ሆነ። እንደ አበባ ሊያብብ ቢፈጠርም ባለመታመኑ ምክንያት ጠወለገ። አበባ እሳት ሲያቃጥለው፣ ፀሐይን ሲያጣ ወይም ሙቀቷ ሲበረታበት፣ ውኃን ሲጠማ፣ ውጫዊ ኃይል ሲያርፍበትና ከግንዱ ሲለይ ይጠወልጋል፣ ይረግፋል። አዳምም ከጕንደ ወይኑ ከእግዚአብሔር ተለይቶ ጠወለገ፤ ሥጋው በመቃብር ነፍሱ በሲኦል ረገፈ። መልሶ እንዲያብብ ‹‹የሕይወት ውኃ›› የተባለ ‹‹ፀሐየ ጽድቅ›› ክርስቶስ ያስፈልገው ነበር። ለዚህ ደግሞ ለድኅነቱ ምክንያት የሆነችው ንጽሕት እመቤት ድንግል ማርያም ታስፈልገው ነበር። ለዚህ ነው ቅዱስ ያሬድ እንዲህ ሲል የገለጻት፡- ‹‹እስመ ርእየ ሕማማ ለአመቱ ወገብረ ኃይለ በመዝራዕቱ… መዝገቡ ለቃል ጽጌ እንተ ኢትትነገፍ መድኃኒተ ሕዝብ – የባርያይቱን መዋረድ አይቷልና ኃይልን በክንዱ አደረገ፤ የማትረግፈውን አበባ የዓለም መድኃኒት የቅዱሳን መዓዛ እንድትሆን አደላት›› (ድጓ ዘጽጌ)።

ቅዱስ ያሬድ ‹‹የማትረግፈው አበባ›› ያላት የማይረግፍ ዘላለማዊ ክብርና ቅድስና ያላትን እመቤታችንን ነው። ስለ እርሷ ‹የማይረግፍ አበባነት› ከማየታችን በፊት ግን፡ ሊቁ በአበባ ከመሰላቸው መካከል ከእመቤታችን ጋር ዐቢያን አምሳላት የሚባሉት መስቀሉ እና ቤተ ክርስቲያንም ይህ ”ጽጌ እንተ ኢትትነገፍ፤ የማትረግፍ አበባ” ዐውደ ስብከት ዲ/ን ኅሊና በለጠ ቅዱስ ያሬድ ጥቅምት/ ፳፻፲፫ ዓ.ም 5 ቅጽል ይገባቸዋልና የእነርሱንም ‹የማይረግፍ አበባነት› በጥቂቱ ልናይ ይገባናል። ይልቁንስ ከጠቀስናቸው ከሦስቱም ይልቅ በአበባ ከሚመሰሉት ከዐራቱ ዐቢያን አንዱ የሆነው ጌታችን፡ ‹‹የማይረግፍ አበባ›› ነው፤ ሌሎቹም ይህን ጸጋ ያገኙት ከእርሱ ሥር ተጠልለው ነውና ከሁሉ አስቀድሞ የእርሱን አበባነት ማየቱ ተገቢ ነው። የጌታችን አበባነት ነቢዩ ኢሳይያስ በትንቢቱ ‹‹ከእሴይ ግንድ በትር ይወጣል፥ ከሥሩም ቍጥቋጥ ያፈራል›› ሲል የጌታችንን ከእመቤታችን መወለድ ገልጾአል። (ኢሳ. ፲፩፡፩)። ‹‹በትር›› የተባለችው ያለ ዘር የጸነሰችውና ከእሴይ የዘር ሐረግ ሥር የተገኘችው ድንግል ማርያም ስትኾን ከበትሩ ላይ ያቆጠቆጠው አበባ ደግሞ ጌታችን ነው። ይህንን ሲያስረዳ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ትወፅዕ በትር እምሥርወ ዕሴይ ወየዐርግ ጽጌ እምኔሃ… ይእቲ በትር አምሳለ ማርያም ቅድስት ይእቲ ወጽጌ ዘወፅአ እምኔሃ አምሳሉ ለወልድ – ከእሴይ ሥር በትር ትወጣለች፤ አበባም ከእርሷ ያቆጠቁጣል፤ ይህች በትር ቅድስት ማርያም ናት፤ ከእርሷ የወጣው አበባም የወልድ ምሳሌ ነው››። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የማርያም አበባ ነው። ከእርሷ በትርነት የተገኘ አበባ ነው።

ጠቢቡ ሰሎሞን በመኃልየ መኃልይ ‹‹እኔ የሳሮን ጽጌ ረዳ የቈላም አበባ ነኝ›› ማለቱን ሊቃውንት ከጌታችን ጋር አያይዘው ተርጉመውታል። (መኃ.፪፡፩)። ሳሮን (Sharon) በይሁዳ የሚገኝ ሸለቆ ነው። ብዙ ውኃ ያለበትና መለምለም የሚችል ሥፍራ ነው። ነገር ግን በግብፅና በሶሪያ መካከል እንደ መንገድ የሚጠቀሙበት ጠባብ ሥፍራ በመኾኑ አበቦች የሉበትም። ‹‹እኔ የሳሮን ጽጌ ረዳ የቈላም አበባ ነኝ›› በሚለው ጥቅስ ላይ ሳሮን የሕዝበ እስራኤል፣ ቆላ ደግሞ የአሕዛብ ምሳሌ ናቸው። በእስራኤልም ሆነ በሕዝብ መካከል ፍሬ ድኅነት አልተገኘባቸውም ነበር፤ ድኅነትን የሚሰጠውን አበባ፣ ማለትም ክርስቶስን አላገኙም ነበርና። የማርያም አበባ የሆነው ጌታችን በተወለደ ጊዜ ግን በሳሮን ለተመሰሉት ለእስራኤላውያን ጽጌረዳ፣ በቆላ ለተመሰሉት አሕዛብም አበባ ሆነላቸው። ያውም በጊዜ ብዛት የማያልፍና የማይጠወልግ፣ የማይረግፍም አበባ። ‹‹እኔ የሳሮን ጽጌ ረዳ የቈላም አበባ ነኝ›› ያለው ጌታችን በጠቢቡ አንደበት ቀጥሎም ‹‹በእሾህ መካከል እንዳለ የሱፍ አበባ፥ እንዲሁ ወዳጄ በቈነጃጅት መካከል ናት›› ይላል። (መኃ.፪፡፪)።

ይህን ያብራሩ ሊቃውንት ‹‹እርሱ የቆላ አበባ እንደ ሆነው ሁሉ የሚወዳቸው ሁሉ የእርሱን ምሳሌነት ተከትለው አበባ እንዲኾኑ ይፈልጋል። ማለትም የእርሱን መንገድና ምሳሌነት የሚከተል ነፍስ ሁሉ አበባ ይኾናል›› ይላሉ። በእሾህ እንደ ተከበበች የሱፍ አበባ ወዳጄ ብሎ የገለጻት የሰው ነፍስን ነው። ይህን ክፍል በተረጎመበት ትምህርቱ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ‹‹ነፍስ ወደ መሲሁ የምትናፍቅ አበባ ናት፤ የዚህን ዓለም ፈተና ሁሉ ድል አድርጋ ወደ እርሱ የምትጓጓ አበባ ናት›› ይላል። (A Patristic Commentary on The Song of Songs; Fr. Tadros Y. Malaty;) የቅዱስ መስቀሉ አበባነት አበው ‹‹በሴት ጠፋን በሴት ዳን›› እንደሚሉት ሁሉ ‹‹በዕፅ ጠፋን በዕፅ ዳን››ም ይላሉ። ያጠፋን ዕፅ ዕፀ በለስ ሲኾን ያዳነን ዕፅ ደግሞ ዕፀ መስቀሉ ነው። የመስቀሉ ጠላቶች የሚበሰብስ መስሏቸው ዕፀ መስቀሉን ከመሬት ሥር ለሦስት መቶ ዓመታት ቀብረውት ቢቆዩም ‹‹የማይረግፈው አበባ›› መስቀሉ ግን ምንም ሳይኾን በቅድሰት ዕሌኒ ምክንያት ተገኝቷል።

ዛሬም ማዕተብና መስቀሉ የሚወክለው ክርስትናን ጨርሶ ለመቅበር የሚጥሩ ሰዎች የማይሳካላቸው መስቀሉ ‹‹የማይረግፍ አበባ›› ስለ ሆነ ነው። ውኃ የማይጠጣ ተክል ይጠወልጋል፤ መስቀሉ ግን ‹‹እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ሁሉ ግን ለዘላለም አይጠማም፥ እኔ የምሰጠው ውኃ በእርሱ ውስጥ ለዘላለም ሕይወት የሚፈልቅ የውኃ ምንጭ ይሆናል እንጂ›› ያለውን የክርስቶስን ደም ‹ጠጥቶ› ስለ ለመለመ የሚጠወልግ አይደለም – የማይረግፍ አበባ ነው እንጂ። (ዮሐ.፬፡፲፬)። ቅዱስ ያሬድም ‹‹በከመ ይቤ ሰሎሞን በእንተ ማርያም ንዑ ንትፈጋዕ ወኢይኅልፈነ ጽጌ ደመና መስቀል ዘዮም አብርሃ በሥነ ማርያም – ሰሎሞን ስለ ድንግል ማርያም ሲናገር እነሆ ክረምቱ አልፎ በረከት ተተካ እንዳለ የክርስቶስ መስቀል ከድንግል ማርያም ባሕርይ በተገኘው (በተወለደው በክርስቶስ) ዛሬ አብርቷልና የበረከት አበባ ሳያልፈን ኑ እንደሰት›› ይላል። (ድጓ ዘጽጌ)። ለዚህም ነው መዘምራን የመስቀል በዓል ሲደርስ ‹‹መስቀል አበባ ነህ ውብ አበባ አደይ አበባ ነህ ውብ አበባ›› እያሉ የሚዘምሩት። የቤተ ክርስቲያን አበባነት ቅዱስ ያሬድ የቤተ ክርስቲያንን አበባነት ሲመሰክር እንዲህ አለ፡- ‹‹ልዑለ ረሰዮ ለመሠረትኪ አረፋትኪ ዘመረግድ ደቂቅኪ ምሁራን በኀበ እግዚአብሔር…- የተለየሽ ጽዮን ቤተ ክርስቲያን ሆይ መሠረትሽን ከፍ ከፍ አደረገው። ግድግዳዎችሽን በመረግድ በወርቀ ደማቸው። ልጆችሽ በእግዚአብሔር ዘንድ የሠለጠኑ ናቸው። በምድረ በዳ እንዳለች የሱፍ አበባ ለጋ የሆነ የወይን አበባ ሽታን ትሸቻለሽ። የበረከትንም ፍሬ ታፈሪያለሽ››። ዳግመኛም በዚሁ በድጓ ዘጽጌው ‹‹ሐረገ ወይን እንተ በምድር ሥረዊሃ ወበሰማይ አዕፁቂሃ እንተ በሥሉስ ትትገመድ ወታፈሪ ለነ አስካለ በረከት ሲሳዮሙ ለቅዱሳን – ሥሯ በምድር ጫፏ በሰማይ የሆነች በፈቃደ ሥላሴ ተገርዛ የምትለቀም የበረከት ፍሬን የምታፈራልን የወይን ሐረግ የተለየች ጽዮን ቤተ ክርስቲያን ናት›› ይላል። ቤተ ክርስቲያን ‹‹ፍሬ›› የተባለ የክርስቶስን ሥጋ ወደሙን ዘወትር የምትሰጠን የማትረግፍ አበባ ናት። ብዙዎች ሊያረግፏትና ሊያጠወልጓት ለዘመናት ቢዘምቱባትም፣ ዲያቢሎስ ጦሩን ሁሉ ቢወረውርባትም፡ ልክ ለምለም አበባ በረጅም ሥሩ ውኃን ከመሬት እየሳበ የበለጠ እንደሚያብበው ‹‹የውኃ ግድግዳ የደም መሠረት›› እያልን የምንዘምርላት ቤተ ክርስቲያንም የበለጠ አበበች እንጂ አልጠወለገችም። አትጠወልግምም።

የእመቤታችን አበባነት ‹‹የማኅጸንሽ ፍሬ ቡሩክ ነው›› ለተባለው ለእውነተኛው ፍሬ መገኛ የሆነችው እመቤታችን የማትረግፍና ዘወትር የምታብብ አበባ ናት። እመቤታችን በማይጠወልግና በለምለም ተክል መመሰሏ ነገረ ማርያምን ለተማረ ሰው አዲስ አይደለም። ሙሴ በሲና ተራራ ላይ እሳቱ ሐመልማሉን ሳያቃጥለው፣ ሐመልማሉም እሳቱን ሳያጠፋው ያየው ምሥጢር ለእሳተ መለኮትና ለትሥብእት ተዋሕዶ ምሳሌ ነው። ‹‹የእግዚአብሔርም መልአክ በእሳት ነበልባል በእሾህ ቍጥቋጦ መካከል ታየው እነሆም ቍጥቋጦው በእሳት ሲነድ ቍጥቋጦውም ሳይቃጠል አየ››። (ዘፀ. ፫፡፪)። እሳት ተዋሕዶት ያልጠወለገው ሐመልማል ለእመቤታችን ምሳሌ እንደ ሆነ ሊቁ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ሲያስረዳ ‹‹ጌታችን ክርስቶስን በወለደችው ጊዜ ከእርሷ ወደ ሰው ሕይወት የበራው የመለኮት ብርሃን ሐመልማሉን አላቃጠለውም። በተመሳሳይም በእርሷ ውስጥ ያለው የድንግልናዋ አበባም አምላክን በወለደችው ጊዜ አልረገፈም›› ይላል። ሌሎች እናቶች ሲያገቡና ሲወልዱ ጽጌ ድንግልናቸው ይወገዳል፤ የማትረግፈው አበባ ድንግል ማርያም ግን ወልዳም ጽጌድንግልናዋ አልተለወጠም። የኢየሩሳሌምን ጥፋት እንዳያይ እግዚአብሔር በእንቅልፍ ምክንያት የሠወረው አቤሜሌክ፡ ከቀጠፋት ከስልሳ ስድስት ዓመት በኋላ ሳትጠወልግና ሳትደርቅ ወተቷ ሲንጠባጠብ የተገኘችው የበለስ ቅጠል ምሳሌነቷ ለእመቤታችን እንደ ሆነ ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት አመሥጥረው ያስረዳሉ። (ተረ. ባሮ. ፫)። ይህች ቅጠል ተቀጥፋ ከስልሳ ስድስት ዓመታት በኋላም ከነ ልምላሜዋ መገኘቷ የእመቤታችንን ዘላለማዊ ድንግልና፣ ንጽሕናና ቅድስና የሚያሳይ ነው።

“የማኅጸንሽ ፍሬ ቡሩክ ነው” ለተባለው ለእውነተኛው ፍሬ መገኛ የሆነችው እመቤታችን የማትረግፍና ዘወትር የምታብብ አበባ ናት። የካህኑ አሮን የደረቀ በትር መለምለሙም ለእመቤታችን ሌላው ምሳሌ ነው። ‹‹እንዲህም ሆነ በነጋው ሙሴ ወደ ምስክሩ ድንኳን ውስጥ ገባ እነሆም፥ ለሌዊ ቤት የሆነች የአሮን በትር አቈጠቈጠች፥ ለመለመችም፥ አበባም አወጣች፥ የበሰለ ለውዝም አፈራች››። (ዘኁ. ፲፯፡፰)። ይህም አስቀድመን እንዳየናቸው ምሳሌዎች ሁሉ መጠቀስ የሚችል ነው። ‹‹በሰላመ ገብርኤልን›› አዘውትሮ የሚጸልይና ለእመቤታችን ልዩ ፍቅር የነበረው አንድ አስቴራስ የተባለ ዲያቆን ነበር። ይህም ዲያቆን ወደ ሩቅ አገር እየሔደ ሳለ ጨካኞች በመንገድ አገኙትና ገድለውት ሳይቀብሩት ከመንገድ ዳር ትተውት ሔዱ። ነገር ግን ሌሎች መንገደኞች ሲያልፉ አይተውት ከዚያው ከመንገዱ ዳር ቀብረውት ሔዱ። ከሦስት ቀንም በኋላ በዚያ አቅራቢያ ባለ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለሚያገለግል አንድ መልካም ዲያቆን እመቤታችን በራእይ ትገለጣለች። ጓደኞቹን አስተባብሮም የዲያቆን አስቴራስን አስከሬን ከመንገዱ ዳር በማውጣት በቤተ ክርስቲያን ግቢ እንዲቀብሩት ታዛቸዋለች። ዲያቆኑም እመቤታችን እንዳዘዘችው ሌሎች ዲያቆናትን ይዞ ወደ ቦታው በመጓዝ አስከሬኑን ቢያወጡት ርሔ እንደሚባል ሽቱ መዓዛው እጅግ ደስ የሚያሰኝ ከአስከሬኑ የበቀለ የጽጌሬዳ አበባን አገኙ። በዚህም እየተደነቁ አስከሬኑን በክብር ገንዘውት በታዘዙት ሥፍራ ቀበሩት። ይህን የተአምረ ማርያም ታሪክ አባ ጽጌ ድንግል እንዲህ ተቀኝቶበታል፡- “ጽጌ አስተርአየ ሠሪጾ እምዐፅሙ፣ ለዘአምኀኪ ጽጌ ለገብርኤል ምስለ ሰላሙ፣ ወበእንተዝ ማርያም ሶበ ሐወዘኒ መዓዛ ጣዕሙ፣ ለተዐምርኪ አሐሊ እሙ፣ ማሕሌተ ጽጌ ዘይሰመይ ስሙ። ትርጉም፡- የክርስቶስ እናቱ የሆንሽ ድንግል ማርያም ሆይ መልአኩ ገብርኤል ደስ ይበልሽ እያለ ካቀረበልሽ ሰላምታ ጋር አበባን ይዞ እጅ ከነሣሽ ሰው ዐፅም የጽጌሬዳ አበባ በቅሎ ታየ ስለዚህም የተአምርሽ ዜና ባስደሰተኝ ጊዜ ስሙ ማኅሌተ ጽጌ የሚባል ምስጋናን አመሰግንሻለሁ። (ማኅሌተ ጽጌ) (ሊቀ ጠበብት አስራደ ባያብል፣ የማሕሌተ ጽጌ ትርጉምና ታሪክ፣ ፳፻፬፣ ፳)፡፡

አንድ ሌላ የእመቤታችን ወዳጅ የሆነ ዲያቆንም እንዲሁ በግፍ ተገድሎ በተቀበረ በአራተኛ ቀኑ፡ በመቃብሩ ላይ ፈርከሊሳ የተባለ አበባ ይበቅላል። የአበባው ቅጠል ላይም ዲያቆኑ በሕይወት እያለ ዘወትር ይጸልየው የነበረው ‹‹በሰላመ ገብርኤል›› ጸሎት ተጽፎበት ተገኝቷል። አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም በመልክአ ውዳሴው፡- ማርያም ጽጌ ዘትምዕዚ እምፈርከሊሳ፣ ይማዖ ጽድቀ ዚአኪ ለዘዚአየ አበሳ፣ ከመአራዊተ ይመውእ አንበሳ። ትርጉም፡- ፈርከሊሳ ከምትባል የሽቱ እንጨት መዓዛ ይልቅ አንበሳ አራዊትን እንደሚያሸንፍ ጽድቅሽ፣ መዓዛ ቅድስናሽ የኔን በደል ያጥፋው። (መልክአ ውዳሴ) በማሕሌተ ጽጌም ይህንና ይህን የመሰለውን ሁሉ በማንሣት እመቤታችንንና ጌታችንን በአበባ እየመሰሉ ካህናቱና ምዕመናኑ ሲያመሰግኑ ያድራሉ። ማጠቃለያ፡- የዚህ ዓለም ሀብትና ጊዜ እንደ ጤዛ የሚረግፉ፣ እንደዚህ ዓለም አበባ የሚጠወልጉ ናቸው። የሰው ልጅ በዚህ ምድር ቢያዝን ኀዘኑ ዘላለማዊ አይደለም። ቢደሰትም የዚህ ምድር ደስታና ፈንጠዝያ የሚያልፍ ነው።

የሰው የጉብዝና ዘመንና የምድር ሕይወት እንኳን የሚረግፍ ነው። ነቢዩ የሰው ልጅን እንደ ሣር መጠውለግ ሲገልጽ ‹‹የማጽናናችሁ እኔ ነኝ፥ የሚሞተውን ሰው እንደ ሣርም የሚጠወልገውን የሰው ልጅ ትፈራ ዘንድ አንተ ማን ነህ?›› ይላል። (ኢሳ.፶፩፡ ፲፪)። የሰው ልጅ ከሚጠወልግ ከዚህ ምድር ሕይወቱ ይልቅ ዘላለማዊውን የማይረግፍ ሕይወት ያገኝ ዘንድ ‹‹የማይረግፉ አበቦች›› ያልናቸውን ሊጠጋ ይገባዋል። የጌታችንን ሥጋውን ሊበላ ደሙን ሊጠጣ፣ ጌታችን ራስ ለሆነላት ለአካሉ ለቤተ ክርስቲያን ብልት ለመኾን ሊፋጠን፣ በእመቤታችን አማላጅነትና በመስቀሉ መማጸኛነት አምኖና ተመርኩዞ መንፈሳዊ ሕይወቱን ሊያበረታ ይገባዋል። ይህን በማድረግም ‹‹የክርስቶስ አበባ›› የተባለች ነፍሱን ከመጠውለግና ከመርገፍ ይታደጋታል። ‹‹ጽጌ እንተ ኢትትነገፍ – የማትረግፍ አበባ›› ብሎ ቅዱስ ያሬድ የጠራት እመቤታችን ሁላችንንም ከመከራ ትጠብቀን። አሜን፡፡

ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት ጥቅምት ፳፻፲፪ ዓ.ም