በዓለ ግዝረት

ግዝረት ከጌታችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ንዑሳን በዓላት አንዱ ነው፡፡ እነዚህ ንዑሳን በዓላት የሚባሉትም ስብከት፣ ብርሃን፣ ኖላዊ፣ ግዝረት፣ ቃና ዘገሊላ፣ ልደተ ስምዖን፣ ደብረ ዘይት፣ የመጋቢት ፲ መስቀልና የመስከረም ፲፯ መስቀል ናቸው፡፡

ፍቅር ወልድን ከዙፋኑ ስቦት ወርዶ ሥጋ ማርያምን ተዋሕዶ፣ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ማሕፀኗን ዓለም አድርጎ ከቆየ በኋላ ታኅሣሥ ሃያ ዘጠኝ በዘመነ ማቴዎስ ተወለደ፡፡ በተወለደ በስምንተኛ ቀኑ ሥርዓተ ኦሪትን ሊፈጽም ተገረዘ፡፡ ግዝረትን በስምንተኛው ቀን መፈጸሙ፣ በተወለደ በአርባ ቀኑ ወደ ቤተ መቅደስ መሔዱ ሕገ ኦሪትን ሊያጸና፣ ሊፈጽም፣ ምሳሌውን በአማናዊው ሊተካ እንጂ ኦሪትን ሊሽር ላለመምጣቱ እማኝ ምስክር ነው፡፡

ክርስቶስ ዘር ምክንያት ሳይሆነው እንደተፀነሰ፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ማኅተመ ድንግልናዋ ሳይለውጥ እንደተወለደ እንደ ነቢዩ ሕዝቅኤል “ሳይከፈት ገብቶ ሳይከፍት እንደወጣ” ስለት ምክንያት ሳይሆነው፣ በግዝረት ምክንያት ደም ሳይፈስ በተአምራት ተገረዘ፡፡

በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈ በስምንተኛው ቀን እንደ ኦሪቱ ሥርዓት ግዝረት ይፈጸምለት ዘንድ ሕፃኑ ጌታችንን ወደ ቤተ መቅደስ ወሰዱት፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ ሲገረዝ የሊቀ ካህን ልጅ ነው ብለው ሊገርዙት ወደ እርሱ መጡ፡፡ ጌታችን ግን ወደ ምድር የመጣው ለትሕትና ነው እንጂ ለልዕልና አይደለምና ወሰዱት አለ /ትርጓሜ ወንጌለ ሉቃስ/፡፡ ስሙም ገና በሥጋ ሳይፀነስ የእግዚአብሔር መልአክ ባወጣለት ስም “ኢየሱስ” ተብሎ ተጠራ /ሉቃ. ፪፥፳፩-፳፬/፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ጌታ ክርስቶስ በሥጋው ግዝረትን ተቀበለ፡፡ ለአባቶች የተሰጠውን ቃል ኪዳን ይፈጽም ዘንድ” በማለት እንደ ተናገረው /ሮሜ. ፲፭፥፰/፣ የክብር ባለቤት መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ ግዝረት በመግባት የኦሪትን ሕግ ፈጽሟል፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም አረጋዊው ዮሴፍን “እንደ ሕጉ ልጄን እንዲገርዘውና ስሙንም እንድንሰይመው ብልህ የኾነ ገራዥ ሰው አምጣልኝ” አለችው፡፡ ጻድቁ ዮሴፍም እንዳዘዘችው የሚገርዝ ባለሙያ ይዞ መጣ፡፡ ባለሙያውም በእናቱ በንጽሕት ድንግል ማርያም ክንድ ላይ ሕፃኑ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ባየው ጊዜ እንድገርዘው በጥንቃቄ ያዙት” አላቸው፡፡ ጌታ ኢየሱስም “ባለሙያ ገራዥ ሆይ! ደሜ ሳይፈስ ልትገርዘኝ ትችላለህን? በዕለተ ዓርብ በመስቀል ስሰቀል ካልኾነ በስተቀር ደሜ አይፈስምና፡፡ ጐኔን በጦር ሲወጉኝ ያን ጊዜ ውኀና ደም ይፈሳል፡፡ ይኸውም ለአዳምና ለሚያምኑ ልጆቹ መድኀኒት ይኾናል” አለው፡፡

የክብር ባለቤት ጌታችን የተናገረውን ይህን ቃል ባለሙያው በሰማ ጊዜም አደነቀ፡፡ ዕቃውንም ሰብስቦ ተነሣና ከጌታችን እግር በታች ወድቆ ሰገደ፡፡ ያንጊዜም ምላጮቹ በእጁ ላይ እንዳሉ እንደ ውኀ ቀለጡ፡፡ ክብርት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምንም “ከሴቶች ተለይተሽ አንቺ የተባረክሽ ነሽ፡፡ የማኅፀንሽም ፍሬ የተባረከ ነው፡፡ ይህ ልጅሽ ስለ እርሱ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት የሕያው አምላክ ልጅ ነው” አላት፡፡

ጌታችንም ባለሙያውን “እኔ ነኝ! ትገዝረኛለህን ወይስ ተውክ? ወይስ የአባቶቼ አባቶች እንዳደረጉ ላድርግ?” አለው፡፡ ባለሙያውም መልሶ”የአባቶችህ አባቶች እነማን ናቸው?”ሲል ጠየቀው፡፡ ጌታችንም አብርሃም፣ ይስሐቅ፣ ያዕቆብ የሕዝቡ ሁሉ አባት እንደ ሆኑ ካስገነዘበው በኋላ “ለእነርሱም ይህ ግዝረት አስቀድሞ ከአባቴ ዘንድ ተሰጣቸው” በማለት የግዝረትን ሕግ አስረዳው፡፡ ባለሙያውም ይህን ምሥጢር ሲሰማ እኔ ከአንተ ጋር እነጋገር ዘንድ አልችልም፡፡ በአንተ ህልውና መንፈስ ቅዱስ አለና” ብሎ የኢየሱስ ክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት መሰከረ፡፡

በዚህ ጊዜ ጌታችን ዐይኖቹን ወደ ሰማይ አቅንቶ “አባት ሆይ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅ፣ ለያዕቆብ አስቀድሞ ግዝረትን የሰጠሃቸው፤ ያቺን ግዝረት ዛሬ ለእኔ ስጠኝ” አለ፡፡ ያንጊዜም ያለ ሰው እጅ በጌታችን ላይ ግዝረት ተገለጠ (የግዝረት ምልክት ታየ)፡፡ ከዚህ ላይ ጌታችን ወደ አባቱ ወደ እግዚአብሔር አብ ልመና ማድረሱ የለበሰው ሥጋ የአብርሃም፣ የይስሐቅ፣ የያዕቆብ መሆኑንና ጸሎት ማቅረብ የሚስማማው ሥጋን መልበሱን ለማጠየቅ ነው እንጂ በእርሱና በአብ መካከል ልዩነት ኖሮ አይደለም፡፡

ጌታችን ድንግልናዋን ሳያጠፋ ከድንግል ማኅፀን እንደ መውጣቱ ግዝረቱም አይመረመርም፡፡ በተዘጋ ቤት ወደ ሐዋርያት እንደ ገባና እንደ ወጣ ሁሉ እርሱ በሚያውቀው ረቂቅ ጥበብ ከሥጋው ምንም ምን ሳይቈረጥ፣ ምንም ደም ሳይፈሰው መገረዙ ተገለጠ፡፡

ገራዡም የጌታችንን ቃል ከመስማቱ ባሻገር በሥጋው ላይ የተደረገውን ተአምር ባየ ጊዜ እጅግ አደነቀ፡፡ ከክብር ባለቤት ከጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግር በታች ወድቆም ሦስት ጊዜ ሰገደና “በእውነት አንተ የእግዚአብሔር ልጅ፣ የእስራኤልም ንጉሥ ነህ!” በማለት በክርስቶስ አምላክነት አመነ፡፡ ከዚህ በኋላ ያየውንና የሰማውን ሁሉ እየመሰከረ ወደ ቦታው ተመለሰ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡- ቅዱስ ወንጌል

        ስንክሳር ጥር ፮

1 reply
  1. ቀሺ ሃብተሥላሴ
    ቀሺ ሃብተሥላሴ says:

    ሰላም ለናንተ ይሁን የምወዳቹህ እና የማከብራቹህ ማህበረ ቅዱሳን ነርቱ እግዚአብሔር ከናንተ ይሁን

    Reply

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *