ፈተና 

 

                                ክፍል  ሁለት

                     መጋቤ ምሥጢር ቀሲስ ስንታየሁ አባተ (አውስትራልያ)

ፈተና ለምን?

ፈተና ከዬትም አቅጣጫና አካባቢ ወይም ምክንያት ይምጣ በውስጡ ግን ዓላማ ይኖረዋል። ትልቁ ነገር የፈተናው መምጣት ሳይሆን ለፈተናው ዓላማ ዝግጁና ብቁ ኾኖ መገኘቱ ላይ ነው።

  1. ፈተና የኃጢአታችን ውጤት ሊኾን ይችላል:: ምክንያቱም ሰው የዘራውን ያጭዳልና።
  2. ፈተና ሊቀሰቅሰንና ሊያተጋን ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚተላለፍልን ደወል ሊኾን ይችላል።
  3. እምነታችንና ፍቅራችን ሊመዘንበት ሊሰጠን ይችላል።
  4. በፈተና ለተያዙ በኃጢአት ለወደቁ መራራትን እንድንማር ሊሰጠን ይችላል።
  5. ዋጋችንን ሊያበዛልን ልንፈተን እንችላለን።
  6. በእኛ መፈተን ውስጥ ሌሎችን ሊያስተምርበት ሊሰጠን ይችላል።

ከላይ ለመግለጥ እንደተሞከረው የፈተና ምክንያቱ በርካታ ነው። ዋናው ነገር እግዚአብሔር ልጆቹን እንደማይፈትንና ከአቅማችን በላይ ለኾነ ፈተና አሳልፎ እንደማይሰጠን ይልቁንም ከፈተናው ጋር መውጫውን አብሮ እንደሚሰጠን መረዳትና ማመናችን ነው።

ይኽም በቅዱሳት መጻሕፍት “ማንም ሲፈተን፦ በእግዚአብሔር እፈተናለሁ አይበል፤ እግዚአብሔር በክፉ አይፈተንምና፤ እርሱ ራሱስ ማንንም አይፈትንም።”(ያዕ. ፩፥፲፫) እንዲሁም ““ለሰው ሁሉ ከሚሆነው በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም፤ ነገር ግን ከሚቻላችሁ መጠን ይልቅ ትፈተኑ ዘንድ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የታመነ ነው፥ ትታገሡም ዘንድ እንድትችሉ ከፈተናው ጋር መውጫውን ደግሞ ያደርግላችኋል” ተብሏል።( ፩ኛ.ቆሮ.፲፥፲፫)

ሊቁ ቅዱስ ባስልዮስ እንደተናገረው እግዚአብሔር የሰውን ድካም ያውቃል። ስለሚያውቅም ከአቅማችን በላይ በኾነ ፈተና እንድንወድቅበት አይሻም። ስለዚህ በእኛ ስሕተት ሳይሆን ከአእምሯችን ውጪ የኾነ ፈተና ሲገጥመን ተስፋ ልንቆርጥና ታዳጊ እንደሌላቸው ወገኖች ልንኾን አይገባንም። እርሱ ቅዱስ ጳውሎስ “በእስያ ስለ ደረሰብን መከራችን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ታውቁ ዘንድ እንወዳለንና፤ስለ ሕይወታችን እንኳ ተስፋ እስክንቆርጥ ድረስ ከዓቅማችን በላይ ያለ ልክ ከብዶብን ነበር፤ አዎን፥ ሙታንን በሚያነሣ በእግዚአብሔር እንጂ በራሳችን እንዳንታመን፥ እኛ ራሳችን የሞትን ፍርድ በውስጣችን ሰምተን ነበር።

እርሱም ይህን ከሚያህል ሞት አዳነን፥ ያድነንማል፤ እናንተም ደግሞ ስለ እኛ እየጸለያችሁ አብራችሁ ስትረዱን፥ በብዙ ሰዎች በኩል ስለ ተሰጠን ስለ ጸጋ ስጦታ ብዙዎች ስለ እኛ ያመሰግኑ ዘንድ፥ ወደ ፊት ደግሞ እንዲያድን በእርሱ ተስፋ አድርገናል” በማለት እንዳስተማረን የሞት ጥላ ቢከብበን እንኳን ከፈተናው ያድነናል (፪ኛ ቆሮ.፩:፰-፲፩)

ፈተና ሲገጥመን ምን እናድርግ ?

ፈተናን በሥጋዊ ጥበብ ማሸነፍ አይቻልም። በመኾኑም እንደ ኦርቶዶክሳዊነታችን ፈተና ሲገጥመን ፈተናውን በምን ዓይነት መንፈሳዊ ጥበብ መፍታት እንዳለብን ተረጋግተን ማሰብ ይጠበቅብናል።

  1. መጸለይ

ጸሎት ከፈተና ያወጣናል። ወደ ፈተናም እንዳንገባ ይጠብቀናል። ስለዚህ በወንጌል “አቤቱ ወደ ፈተና አታግባን: ከክፉ ኹሉ አድነን እንጂ” ብላችሁ ጸልዩ እንደተባለው ተግቶ መጸለይ ይገባል።  በሌላ አንቀጽም ጌታችን “ወደ ፈተና እንዳትገቡ ተግታችሁ ጸልዩ” ብሎ እንዳስተማረን ከፈተና በፊትም ኾነ ፈተና ውስጥ ሳለን አጥብቀን መጸለይ ተገቢ ብቻ ሳይሆን ግዴታችንም ጭምር ነው።

  1. እግዚአብሔርን ማመስገን

መጽሐፍ በኹሉ አመስግኑ እንዳለን በፈተናችንም እግዚአብሔርን ልናመሰግን ይገባናል። “ሳታቋርጡ ጸልዩ፤ በሁሉ አመስግኑ፤ ይህ የእግዚአብሔር ፈቃድ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ እናንተ ነውና” እንዲል።( ፩ኛ ተሰ.፭፥፲፯-፲፰) ጻድቁ ኢዮብ ሰውነቱን ሀብቱንና አስር ልጆቹን በአንዲት ቀን ባጣበት ወቅት “እግዚአብሔር ሰጠ: እግዚአብሔር ነሣ:: እግዚአብሔር ይመስገን” አለ እንጂ በአፉ የስንፍናን ነገር አልተናገረም። እስቲ እኛስ እንዳናመሰግን የሚያግዱንን ፈተናዎቻችንን ከኢዮብ ፈተና አንፃር እንመዝናቸው።

  1. መጽናት

ፈተና የሚጸናው እንዲጸና ሥጋዊ ፈቃዱን የሚከተለውም ምርጫውን እንዲከተል የሚመጣበት ጊዜ አለ። በፈተና ትእግስታችን ይለካል። በፈተና እምነታችን ይመዘናል። በፈተና ፍሬውና እንክርዳዱ ይለያል። በፈተና ልዩ የእግዚአብሔር ጸጋና በረከት ይገኛል። መፍትሐው በእምነት ልብን አበርትቶ መጽናት ብቻ ነው። ቅዱስ ያዕቆብ “በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፤ ከተፈተነ በኋላ ለሚወዱት ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን የሕይወትን አክሊል ይቀበላልና” ያለውን በፈተና መጽናት የሚያስገኘውን በረከት ያስረዳል (ያዕ.፩፥፲፪)

ቅዱስ ጳውሎስም በፈተና የመታገስን ጥቅም “ይህም ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን መከራ ትዕግሥትን እንዲያደርግ፥ ትዕግሥትም ፈተናን ፈተናም ተስፋን እንዲያደርግ እያወቅን፥ ፭፥፫)   ቅዱስ ያዕቆብም በበኩሉ “ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት” በማለት በፈተናችን ውስጥ እየጸናንና እየተጽናናን መታገስ እንዳለብን መክሮናል (ያዕ.፩፥፪-፫)

  1. ንስሐ መግባት

እግዚአብሔር  ስንረሳው ነፍሳችን በኃጢአት ስትጎሰቁልና ስትሞት ጽድቅ ጠፍቶ ሁሉም በበደል ተገርኝቶ ሲያዝ የራቀውን ሊያቀርብ: የወደቀውን ሊያነሣ: የተፍገመገመውን ሊያጸና  ይገሥጸናል።ለዚኽ መፍትሄው ምክንያት ሳያበዙ ንስሐ መግባት ብቻ ነው።እኛ በንስሐ ወደ ፈጣሪያችን ስንመለስ እርሱ ደግሞ በምሕረቱ ወደ እኛ ይመለሳል።

  1. ካለፈው ልምድ መቅሰም

አንዳንድ ጊዜ እንደግለሰብም እንደቤተ ክርስቲያንም አለያም እንደ ሀገርም መሥራት የሚገባንን ባለመሥራታችን: ኃላፊነታችንን በጊዜው ባለመወጣታችን: ስንፍናን በማብዛታችን: አሠራራችንን ለፈተና ተጋላጭ በማድረጋችን ከግለሰብ እስከ ቤተ ክርስቲያንና እስከ ሀገር ልንፈተን እንችላለን የሚለው ነው።አሁን ያገኘንን ፈተና በንስሐና በእንባ ብንመልሰውም መዘጋጀትና መሥራት በሚገባን ልክ ኾነን ካልተገኘን ድጋሚ በፈተና መያዛችን አይቀሬ ነው። ያ ደግሞ እጅግ አደገኛ ነገር ነው።

ስለዚህ ከእያንዳንዱ ፈተናችን ትምህርት ልንወስድና በርትተን ልንሠራ ይጠበቅብናል።በአሁኑ ጊዜ በቤተ ክርስቲያናችን ላይ እየደረሰ ያለውና የበርካታ ምእመናንን ሕይወት የቀጠፈው ፈተና ለቤተ ክርስቲያናችን አዲሷ ባይሆንም ካለፉት ፈተናዎቻችን ተምረን መሥራት ማደራጀት ማሠልጠን ማንቃት መጠበቅ በሚገባን ልክ ሆነን ስላልተገኘን ነው። በመኾኑም ወጣቶች እንደሚያገሳ አንበሳ ሊውጠን በሚያደባብን ፈተና ሳይረበሹ እያንዳንዷን ፈተና ለመልካም አጋጣሚና ዕድል በመቀየር ራሳችንና ቤተ ክርስቲያናችንን ለሚመጣው ትውልድ ማሸጋገር ይጠበቅብናል።ለዚኽ ደግሞ የአምላካችን ቸርነት የድንግል ማርያም ተራዳኢነት  አይለየን።

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *