“ግቢ ጉባኤ ቤተ ክርስቲያን በወጣትነት ዘመናቸው ልጆቿን አቅፋ የያዘችበት ትልቁ ተቋም ነው” (ዐወቀ አበብሽ ከጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ)

ክፍል አንድ 

በእንዳለ ደምስስ

ዐወቀ አበብሽ ይባላል፡፡ በጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ በሜዲካል ላቦራቶሪ ትምህርት ዘርፍ   ተከታትሎ ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ በ፳፻፲፮ ዓ.ም የዩኒቨርሲቲው ዋንጫና ሜዳልያ ተሸላሚ ለመሆን በቅቷል፡፡ ከትውልድ ቀዬው ጎጃም ወደ ጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ሲመደብ ፍርሃት ነበረው፤ ነገር ግን ጠንክሮ በመማር፣ በግቢ ጉባኤያት ከመሣተፍ አልፎ በአገልግሎትም ከሚፋጠኑ ወንድሞች አንዱ ሆኖ አሳልፏል፡፡

የተወለደው ምሥራቅ ጎጃም ጎንቻ ሰውነቴ ወረዳ ውስጥ ነው፡፡ የሕፃንነት ዘመኑን የቤተሰቡን ከብቶች በመጠበቅ በእረኝነት የጀመረ ሲሆን ሕይወት ለአባቡሽ እንደማንኛውም የገጠር ተማሪ ከባድ ነበር፡፡ ገና በሕፃንነቱ ፊደል መቁጠር ቢጀምርም በኩራዝ (ላምባ) እያጠና በጠዋት ወደ ትምህርት ቤቱ ከሰፈሩ ልጆች ጋር እየሮጠ ይሄዳል፤ ሲመለስም እንዲሁ፡፡ ከትምህርት ቤቱ ርቀት የተነሣ ከአንደኛ እስከ አራተኛ ክፍል ድረስ ርቀት እያስገደደው አራት ትምህርት ቤቶችን ቀያይሯል፡፡ ከአምስተኛ እስከ ስምንተኛ ያሉትን ክፍሎችም ከቦታ ቦታ መቀያየሩ ሳይበግረው የደረጃ ተማሪ እንደነበር ይገልጻል፡፡

የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱንም ከቤተሰቡ በመለየት ከጓደኞቹ ጋር ወደ ከተማ በመሄድ ቤት ተከራይቶ በባሕረ ጊዮርጊስ የመሰናዶ ት/ቤት ትምህርቱን ቀጠለ፡፡ ዐወቀ ለትምህርት በነበረው ጠንካራ ፍቅር የተነሣ በሳምንት ወይም በሁለት ሳምንታት አንድ ጊዜ ወደ ቤተሰብ በመሄድ ለስንቅ የሚያስፈልገውን ጥሬ ምርት ይዞ በመመለስ አዘጋጅቶ መመገብን ለመደ፡፡

የዐሥራ ሁለተኛ ክፍል ውጤቱ ብዙም አስደሳች እንዳልነበረ የሚገልጸው ዐወቀ ዩኒቨርሲቲ ከገባ በኋላ ግን በቁርጠኝነት በመማር በአራት ዓመታት የትምህርት ቆይታው ፫.፱ አጠቃላይ ውጤት  ከዩኒቨርሲቲው ከፍተኛውን ነጥብ በማምጣት በእጅግ ከፍተኛ ማዕረግ ለመመረቅ በቅቷል፡፡

በቤተ ክርስቲያን ጋር የነበረውን ሕይወት በተመለከተም እንደማንኛውም ሕፃን በቤተሰቡ አማካይነት ቤተ ክርስቲያን ሄዶ ከመቁረብ ውጪ አብነት ትምህርትን ለመማር ጥረት አለማድረጉን ይናገራል፡፡ ነገር ግን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ከጓደኞቹ ጋር ወደ ከተማ ሄዶ በመማር ላይ ሳለ ቤተ ክርስቲያን መሄድ፣ መጸለይ፣ የሠርክ ጉባኤ መሳተፍ ጀመረ፡፡ በዩኒቨርሲቲ ቆይታውም ግቢ ጉባኤ ውስጥ በመሳተፍ እንደተማረ፤ ይህም ስለ እምነቱ በሚገባ መረዳቱንና እንደ ዐቅሙ በሚችለው ሁሉ በአገልግሎት ሲሳተፍ እንደቆየም ነግሮናል፡፡

የዝግጅት ክፍላችንም በመማር ላይ ላሉትና ወደፊት ወደ ዩኒቨርሲቲ ገብተው ለሚማሩ ተማሪዎች ተሞክሮውን ያካፍል ዘንድ ጋብዘነዋል፤ ቀጥለን እናቅርበዋለን – መልካም ቆይታ፡፡

  • የልጅነት ዘመንህ እንዴት አለፈ? እስቲ ስለ ልጅነት ሕይወትህ አጫውተን፡፡

እንደማንኛውም ሕፃን ከሰፈር አብሮ አደግ ጓደኞቼ ጋር አፈር እየፈጨን፣ ኳስ እየተጫወትን ብናድግም ዋናው ሥራችን ግን እረኝነት ነበር፡፡ የገጠር ልጅ እንደ መሆኔ ከብቶቻችንን ማሰማራት፣ ወደ ወንዝ መውሰድና መመለስ፣ ለወላጆቼ በመላላክ ነው ያደግሁት፡፡

  • ለመማር በምታደርገው ጥረት ላይ የቤተሰቦችህ ድጋፍ ምን ይመስል ነበር?

የወላጆቼ ድጋፍ ነው ዛሬ ውጤታማ ለመሆን ያበቃኝ፡፡ በትምህርቴ እንድበረታና ውጤታማ እንድሆን በሚችሉት ሁሉ ደግፈውኛል፤ የቤት ኪራይ እየከፈሉ፣ የሚያስፈልገኝን የትምህርት መሣሪያዎችን እየገዙልኝ፣ ቀለቤን ሁሉ ችለው ነው ያስተማሩኝ፡፡

ዘጠነኛና ዐሥረኛ ክፍል ልጅነትም ስላለኝ፣ ከቤተሰብም ተለይቼ ስለማላውቅ ቤተሰቦቼ ስለሚናፍቁኝ በየዐሥራ አምስት ቀን እየሄድኩ እጠይቃቸው ነበር፡፡ እነርሱም ስንቅ የሚሆነኝን ጥሬ ቋጥረው ይልኩኝ ነበር፡፡ ዐሥራ አንድ እና ዐሥራ ሁለተኛ ክፍል ግን ትምህርቱም እየጠነከረ ስለመጣ ትኩረት መስጠት ስላላብኝ ብዙም አልመላለስም ነበር፡፡

  • ወደ ዩኒቨርሲቲ ከገባህ በኋላ ጠንክሮ ለመማር ያደረግኸውን ጥረት ብታካፍለን?

የሄድኩት ወደማላውቀው ቦታ ነው፡፡ ብቀጥልም ባልቀጥልም ሄጄ ማየት አለብኝ ብዬ ነው የሄድኩት፡፡ ነገር ግን ወደ ኋላ ማለት ወደፊት ዋጋ እንደሚያስከፍለኝ ስለተረዳሁ ዕድልን ለመጠቀም ወሰንኩ፡፡ ለጊዜው ሙቀቱ በጣም አስቸግሮኝ ነበር፤ ውስጤ ፍርሃት የነበረ ቢሆንም ወንድሞችና እኅቶች ተቀብለው በጥሩ ሁኔታ ነው ያስተናገዱን፡፡ በግቢ ጉባኤ አቀባበል መርሐ ግብር ላይም ለእኛ የሚጠቅመንን ምክር በመስጠት አበረታቱን፡፡ ለራሴም አንድ ቃል ገባሁ፡- “እዚህ ድረስ ከመጣሁ አይቀር በጥሩ ውጤት መመረቅ አለብኝ፡፡” ብዬ ወሰንኩ፡፡ መደበኛ ትምህርቴን መማር፣ ማጥናት፣ ቤተ ክርስቲያን መሄድ፣ ግቢ ጉባኤ በሚኖረው መርሐ ግብር መሳተፍ ብቻ ነበር ሥራዬ፡፡ ይህንን ደግሞ በተግባር ላይ ለማዋል ጊዜ አልፈጀብኝም፡፡

የመጀመሪያ መንፈቅ ዓመት (ሴሚስተር) ውጤቴ ፫.፱ ነበር፡፡ ከዚህ የተሻለ ውጤት ለማምጣትም ራሴን አሳመንኩት፡፡ ነገር ግን ኮቪድ ገብቶ ስለነበር የትምህርት ሂደቱን ስለገታው ወደ ቤተሰብ ነው የሄድኩት፡፡ ትምህርት ሲጀመርም ቀጥታ ሕክምና ለማጥናት የሚያስችለኝ ውጤት ቢሆንም ስድስትና ሰባት ዓመት አልቆይም ብዬ ሜዲካል ላቦራቶሪ ለማጥናት ወሰንኩኝ፡፡

ጅግጅጋ የተመደብኩት እኔ ብቻ ሳይሆን ከእኔ ጋር የነበረው ጓደኛዬ ጭምር ስለነበር ሁለታችንም ጥሩ ውጤት ለማምጣት የምንችለውን ሁሉ አድርገናል፡፡ ተመሳሳይ አቋም ስለነበረን ሁለታችንም በጥሩ ውጤት ነው የጨረስነው፡፡ የግቢ ጉባኤ ወንድሞችና እኅቶች በምክርም በማበረታታት ስለሚያግዙን በራሳችን ላይ ጫና እንዳንፈጥር ጥረት አድርገናል፡፡

ነገር ግን ወደ መጨረሻዎቹ ዓመታት ትምህርቱ እየከበደ ስለሚመጣ ሊሆን ይችላል ብዙም አይጎበኙንም ነበር፡፡ ካሉት ግቢዎች አንጻር የመርሐ ግብር መደራረብ፣ ትምህርትና የጥናት፣ ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎችን ለመቆጣጠር፣ ለመምከርና ለመስተማር የጊዜ እጥረት ሊገጥማቸው እንደሚችል ቢታወቅም ክትትል ያስፈልጋቸዋልና ይህንን ክፍተት ለመሙላት መጣር ይገባል፡፡

  • በአገልግሎት ደረጃ የነበረህ ተሳትፎ ብታብራራልን?

ወደ አገልግሎት የገባሁት ቆይቼ ቢሆንም በልማት ክፍል ውስጥ አገልግያለሁ፡፡ ብዙ ጊዜ እየተማሩ ግቢ ጉባኤ መሳተፍን አክብደው የሚያዩ ተማሪዎች አሉ ይህ ትክክል አይደለም፡፡ ጊዜያችንን አብቃቅተን የቤተ ክርስቲያንን ትምህርትም መማር እንችላለን፡፡ እኔ ከመደበኛው ትምህርቴ ውጪ ቤተ ክርስቲያንና ግቢ ጉባኤ ውስጥ ነው ሳሳልፍ የነበረው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሄጄ እጸልያለሁ፣ ግቢ ጉባኤ ውስጥ ደግሞ በልማት ክፍል ውስጥ ስብሰባ ሲኖር እንዲሁም የምናከናውናቸው ተግባራት ሲኖሩ እሳተፋለሁ፡፡ ኮርስን በተመለከተ እሑድ እሑድ የሚሰጥ በመሆኑ ከቅዳሴ በኋላ እማራለሁ፡፡

በአገልግሎት መሳተፌ ጠቅሞኛል እንጂ ምንም ያሳጣኝ ነገር የለም፡፡ ቁርጠኛ እንድንሆን ሰዓታችንን በአግባቡ እንድንጠቀም ያደርገናልና እኔ በዚህ ተጠቅሜአለሁ፡፡

ይቆየን፡፡

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *