“መኑ ውእቱ ገብር ኄር፤ ታማኝ አገልጋይ ማነው?” (ማቴ. ፳፬፥፵፭)

በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ መሠረት የዐቢይ ጾም ስድስተኛው ሳምንት ገብር ኄር ይባላል፡፡ ሰያሜውንም የሰጠው ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ ከአምስቱ መጻሕፍቶቹ አንዱ በሆነው ጾመ ድጓ በተባለው መጽሐፍ የዐቢይ ጾም ሳምንታት ስያሜዎች ከነሥርዓተ ማኅሌቱ አዘጋጅቷል፡፡ በዚህም መሠረት በስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው ዝማሬ፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ትምህርት ገብር ኄር ወይም ታማኝ አገልጋይ ላይ ትኩረት ያደርጋል፡፡

ይህንንም ወንጌላው ቅዱስ ማቴዎስ እንዲህ እያለ ይገልጸዋል፡፡ “መንገድ እንደሚሄድ አገልጋዮቹንም ጠርቶ ሊያተርፉበት ገንዘቡን እንደሰጣቸው ሰው እንዲሁ ይሆናልና፤ ለእያንዳንዱ እንደ ችሎታው ለአንዱ አምስት፣ ለአንድ አምስት፣ ለአንዱም አንድ ሰጠና ወዲያውኑ ሄደ፡፡ ያ አምስት መክሊት የተቀበለውም ሄደ፤ ነግዶም ሌላ አምስት መክሊት አተረፈ፡፡ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ፡፡ አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቆፈረና የጌታውን ወርቅ ቀበረ፡፡” (ማቴ. ፳፭፥፲፬-፲፰)

ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ ይቆጣጠራቸው ዘንድ ተመልሶ መጣ፡፡ “ነገር ግን የሰው ልጅ በመጣ ጊዜ በምድር ላይ እምነት ያገኝ ይሆን?” እንዲል በእነዚህ አገልጋዮች አንጻር ምእመናን ለእግዚአብሔር ያላቸውን እምነትና ታማኝነት፣ ታምኖም መኖር ምን ያህል እንደሆነ የሚያመለክት ነው፡፡ (ሉቃ .፲፰፥፰)

አገልጋዮቹም ከጌታቸው የተቀበሉትን መክሊትና ያተረፉትን ይዘው በተራ ቀረቡ፡፡  በቅድሚያም አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና፡- “አቤቱ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ ሌላ አምስት አተረፍሁ፤ ብሎ አምስት መክሊት አስረከበ፡፡ ጌታውም መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂት የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለውም መጥቶ፡- አቤቱ ሁለት መክሊትን ሰጥተኸኝ አልነበረምን? እነሆ ሌላ ሁለት መክሊትን አተረፍሁ አለ፡፡ ጌታውም፡- መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡” ሁለቱም የተሰጣቸውን መክሊት ተጠቅመው ወጥተው ወርደው ሠርተውና አትርፈው ተገኝተዋልና ያገኙትንም ይዘው በመቅረብ ከጌታቸው ዘንድ ሞገስና ክብርን አግኝተዋል፡፡

ጌታው ሠርቶ፣ አገልግሎ ያተርፍበት ዘንድ አንድ መክሊት የተሰጠው አገልጋ ግን ከሁለቱ በተለየ መንገድ ወደ ጌታው ቀረበ፡፡  “አንድ መክሊት የተቀበለውም መጣና እንዲህ አለ፡- አቤቱ አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንህ አውቃለሁ፡፡ ስለ ፈራሁም ሄድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ፤ እንግዲህ እነሆ መክሊትህ” አለው፡፡  ጌታውም መልሶ አለው፡- “አንተ ክፉና ሰነፍ አገልጋይ እኔ ካልዘራሁበት የማጭድ ካልበተንሁበት የምሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንሁ ታውቃለህ? ገንዘቤን ለለዋጮች መስጠት በተገባህ ነበር፤ እኔም ራሴ መጥቼ ገንዘቤን ከትርፉ ጋር በወሰድሁ ነበር፡፡ የቆሙትንም እንዲህ አላቸው፡- ይህን መክሊት ከእርሱ ተቀብላችሁ ዐሥር መክሊት ላለው ስጡት፡፡ ላለው ሁሉ ይሰጡታልና ይጨምሩለታልም፡ ለሌለው ግን ያንኑ ያለውን ይወስዱበታል፡፡ ክፉውን አገልጋይ ግን ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት በውጭ ወደአለ ጨለማ አውጡት፡፡” (ማቴ. ፳፭፥፲፬-፴) አለ፡፡

ባዕለ ጸጋ የተባለው ጌታ ነው፡፡ መክሊት የተባለው ልዩ ልዩ የአገልግሎት ጸጋ ነው፡፡ ያተረፉት በሚገባ በታማኝነት ያገለገሉ ቅዱሳን ሰዎች ናቸው፤ መክሊቱን የቀበረው ደግሞ በታማኝነት በተሰጠው ጸጋ ማገልገል ሲገባው ያላገለገለ ነው፡፡ ጌታቸው ሊቆጣጠራቸው መጣ ማለት በዕለተ ምጽአት ለሁሉም በአገለገለው አገልግሎት ዋጋ ለመስጠት እንደሚመጣ የሚያሳይ ነው፡፡

ያገለገሉትና ታምነው የተገኙት ወደ ጌታህ ደስታ ግባ ማለቱ ታማኝ አገልጋዮች መንግሥተ ሰማያትን እንደሚወርሱ፤ ሰነፎች ደግሞ ጥርስ ማፋጨት፣ ስቃይ፣ ጽኑዕ ጨለማ ባለበት ሲዖል መውረዳቸውን የሚያሳይ ነው፡፡

ነቢያት፣ ጻድቃን ሠማዕታት፣ ቅዱሳን በታማኝ አገልግሎታቸው ፈጣሪያቸውን ደስ አሰኝተው ከብረዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ሊቀ ነቢያት ሙሴ፣ ዮሴፍ፣ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት፣ ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ቅዱስ ጳውሎስን ማንሣት የምንችል ሲሆን፤ ለጌታቸው ያልታመኑት ደግሞ ይሁዳ፣ ሐናንያ፣ ሰጲራ፣ የመሳሰሉት የደረሰባቸውን ጉዳት መጥቀስ ይቻላል፡፡

ለዚህ ነበር ቅዱስ ዳዊት “አቤቱ አድነኝ ደግ ሰው አልቋልና፤ ከሰው ልጆችም መተማመን ጎድሏልና” በማለት የገለጸው፡፡ (መዝ. ፲፩፥፩) ስለዚህ ሁሉም በየአለበት የአገልግሎት መስክ ታማኝ አገልጋይ ሆኖ “አንተ በጎ ታማኝ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሀለሁ” የሚለውን የጌታውን የምስጋና ቃል መስማት ይገባዋል፡፡ መልካም አገልግሎት አገልግለን መንግሥቱን እንድንወርስ፣ “ገብርኄር” እንድንባል አምላካችን ይርዳን፡፡

የዕለተ ሰንበት መዝሙር (ከጾመ ድጓ)

“መኑ ውእቱ ገብር ኄር ወምእመን ዘይረክቦ እግዚኡ በምግባረ ሠናይ ወይሰይሞ ዲበ ኲሉ ንዋዩ፡፡ ካዕበ ይቤሎ እግዚአብሔር ገብር ኄር ወምእመን ዘበውኁድ ወምእመን ዘበውኁድ ምእመነ ኮንከ ዲበ ብዙኅ እሰይመከ ባዕ ውስተ ፍሥሐሁ ለእግዚእከ፡፡

ትርጉም– “ጌታው መልካም ሲሠራ አግኝቶ በገንዘቡ ሁሉ ላይ የሚሾመው ቸርና ታማኝ አገልጋይ ማን ነው? ዳግመኛም እግዚአብሔር በታናሹ የታመንህ ደግና ታማኝ አገልጋይ ሆይ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” አለው፡፡

 መልእክታት

የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ መልእክት፡- (፪ኛጢሞ. ፲፮)

“እንግዲህ፥ ልጄ ሆይ፥ አንተ በክርስቶስ ኢየሱስ ባለው ጸጋ በርታ። ብዙ ሰዎች የመሰከሩለትን ከእኔም የሰማኸውን ሌሎችን ደግሞ ሊያስተምሩ ለሚችሉ ለታመኑ ሰዎች አደራ ስጥ። እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ በጎ ወታደር ሆነህ፥ አብረኸኝ መከራ ተቀበል። የሚዘምተው ሁሉ ለጦር ያስከተተውን ደስ ያሰኝ ዘንድ ትዳር በሚገኝበት ንግድ ራሱን አያጠላልፍም። ደግሞም በጨዋታ የሚታገል ማንም ቢሆን፥ እንደሚገባ አድርጎ ባይታገል፥ የድሉን አክሊል አያገኝም። የሚደክመው ገበሬ ፍሬውን ከሚበሉት መጀመሪያ እንዲሆን ይገባዋል። …”

የሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ መልእክት፡- (፩ኛጴጥ. ፲፪)

“እንግዲህ እኔ፥ ከእነርሱ ጋር ሽማግሌ የክርስቶስም መከራ ምስክር ደግሞም ሊገለጥ ካለው ክብር ተካፋይ የሆንሁ፥ በመካከላቸው ያሉትን ሽማግሌዎች እመክራቸዋለሁ፤ በእናንተ ዘንድ ያለውን የእግዚአብሔርን መንጋ ጠብቁ፤ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በውድ እንጂ በግድ ሳይሆን፥ በበጎ ፈቃድ እንጂ መጥፎውን ረብ በመመኘት ሳይሆን ጐብኙት፤ ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ እንጂ ማኅበሮቻችሁን በኃይል አትግዙ፤ የእረኞችም አለቃ በሚገለጥበት ጊዜ የማያልፈውን የክብርን አክሊል ትቀበላላችሁ። …”

 ግብረ ሐዋርያት፡- (ሐዋ. ፱)

“እነርሱም በተሰበሰቡ ጊዜ ጌታ ሆይ፥ በዚህ ወራት ለእስራኤል መንግሥትን ትመልሳለህን? ብለው ጠየቁት። እርሱም። አብ በገዛ ሥልጣኑ ያደረገውን ወራትንና ዘመናትን ታውቁ ዘንድ ለእናንተ አልተሰጣችሁም፤ ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በወረደ ጊዜ ኃይልን ትቀበላላችሁ፥ በኢየሩሳሌምም በይሁዳም ሁሉ በሰማርያም እስከ ምድር ዳርም ድረስ ምስክሮቼ ትሆናላችሁ አለ። ይህንም ከተናገረ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው።”

ምስባክ፡- (መዝ. ፴፱፰-፱)

ከመ እንግር ፈቃደከ መከርኩ አምላኪየ፤ ወሕግከኒ በማዕከለ ከርሥየ፤ ዜኖኩ ጽድቀከ በማኅበር ዐቢይ፡፡
ትርጉም፦ “አምላኬ ሆይ፥ ፈቃድህን ለማድረግ ወደድሁ፥ ሕግህም በልቤ ውስጥ ነው። በታላቅ ጉባኤ ጽድቅን አወራሁ፡፡”

 ወንጌል (ማቴ. ፳፭፲፬፴፩)

“መንገድ እንደሚሄድ አገልጋዮቹንም ጠርቶ ሊያተርፉበት ገንዘቡን እንደሰጣቸው ሰው እንዲሁ ይሆናልና፤ ለእያንዳንዱ እንደ ችሎታው ለአንዱ አምስት፣ ለአንድ አምስት፣ ለአንዱም አንድ ሰጠና ወዲያውኑ ሄደ፡፡ ያ አምስት መክሊት የተቀበለውም ሄደ፤ ነግዶም ሌላ አምስት መክሊት አተረፈ፡፡ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ፡፡ አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቆፈረና የጌታውን ወርቅ ቀበረ፡፡

ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ ተመልሶ ተቆጣጠራቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና፡- አቤቱ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ ሌላ አምስት አተረፍሁ፤ ብሎ አምስት መክሊት አስረከበ፡፡ ጌታውም መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂት የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለውም መጥቶ ፡- አቤቱ ሁለት መክሊትን ሰጥተኸኝ አልነበረምን? እነሆ ሌላ ሁለት መክሊትን አተረፍሁ አለ፡፡ ጌታውም፡- መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡

አንድ መክሊት የተቀበለውም መጣና እንዲህ አለ፡- አቤቱ አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንህ አውቃለሁ፡፡ ስለ ፈራሁም ሄድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ፤ እንግዲህ እነሆ መክሊትህ፡፡ ጌታውም መልሶ አለው፡- አንተ ክፉና ሰነፍ አገልጋይ እኔ ካልዘራሁበት የማጭድ ካልበተንሁበት የምሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንሁ ታውቃለህ? ገንዘቤን ለለዋጮች መስጠት በተገባህ ነበር፤ እኔም ራሴ መጠቼ ገንዘቤን ከትርፉ ጋር በወሰድሁ ነበር፡፡ የቆሙትንም እንዲህ አላቸው፡- ይህን መክሊት ከእርሱ ተቀብላችሁ ዐሥር መክሊት ላለው ስጡት፡፡ ላለው ሁሉ ይሰጡታልና ይጨምሩለታልም፡ ለሌለው ግን ያንኑ ያለውን ይወስዱበታል፡፡ ክፉውን አገልጋይ ግን ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት በውጭ ወደአለ ጨለማ አውጡት፡፡”

ቅዳሴ: ዘባስልዮስ

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *