ወለርሑቃን ፈውሰ ወጥዕምተ ገብራ (ሰቈቃወ ድንግል)

ቀሲስ ዐቢይ ሙሉቀን

ክፍል ሁለት

. ሥርዐቱ

ሕጉን ጠብቀው፣ እንደ ሥርዓቱ ተጉዘው ሰማያዊውን ርስት ለመውረስ ለሚመኙት እግዚአብሔር ያስቀመጠልን ሕግና ሥርዓት የሚመች፣ የሚጥም ነው። ነገር ግን መሠረታዊ ዓላማቸው ይህ ላልሆነው፣ ጽድቁን ቢያስቡም ያለመከራ ለሥጋዊ ምኞታቸው ቅድሚያ በመስጠት ለመጽደቅ ለሚያስቡት ሕጉና ሥርዓቱ ላይመቻቸው ይችላል። ሕግና ሥርዓት ለእውነተኛ ሰው አይጎራብጥም፤ የሚጎራብጠው እውነትን መከተል ለማይፈልግ፣ ከእውነት ጎዳና አፈንግጦ በራሱ ሐሳብና ምኞት ለሚጓዝ ግን አይመችም። ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት “ሕግህ ለእግሬ መብራት ለመንገዴም ብርሃን ነው” (መዝ.፻፲፰፥፻፭) በማለት የገለጸው ለእውነተኞች የእግዚአብሔር ሕግ የሕይወት መሠረት ስለሆነ ነው። በአንጻሩ በሕግ መኖር ለማይፈልግ ግን ይመረዋል፤ ይጠፋበታልም።

. መንፈሳዊ ተጋድሎ

ሰው በልዩ ልዩ ምክንያቶች አብሮት ከሚኖረውም ሆነ ከማይኖረው ጋር ይጋጫል፣ ይጋደላል። ለምድራዊ ርስት፣ ለምድራዊ ሀብት ንብረት ብሎ የሚጛደል ይኖራል። ለመንፈሳዊው ርስት ብሎ ደግሞ ከሚታየውም ከማይታየውም ጋር ይጋደላል። ምድራዊውን ርስት ፈጽሞ አያስፈልግም ባይባልም ሰማያዊውንነ ርስት አስቦ የሚታየውን ዓለም በማይታየው ዓለም ለውጦ የሚያደርጉት ተጋድሎ መንፈሳዊ ተጋድሎ ተብሎ ይጠራል። ይህ መንፈሳዊ ተጋድሎ የሚጥማቸውም የማይጥማቸውም አካላት አሉ።

. የሚጣፍጣቸው

ቅዱሳን አባቶቻችን እውነተኛውንና መንፈሳዊውን ተጋድሎ በተግባር ፈጽመው አሳይተውናል። እየጣፈጣቸውም ተቀብለውት አልፈዋል። በሃይማኖት ጸንተው የሚቀበሉት መከራ ዘለዓለማዊ ሕይወትን የሚያስገኝ ክብርን የሚያጎናጽፍ በመሆኑ ይጣፍጣል። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ምእመናን በላከው መልእክቱ “ስለዚህም ቢሆን በብዙ ራእይ እንዳልታበይ ሰውነቴን የሚወጋ እርሱም የሚጎስመኝ የሰይጣን መልእክተኛ ተሰጠኝ። ስለዚህም ከእኔ ያርቀው ዘንድ ጌታዬን ሦስት ጊዜ ማለድሁት። እርሱም ጸጋዬ ይበቃሃል፤ ኀይልስ በደዌ ያልቃል አለኝ፤ የክርስቶስም ኃይል በእኔ ላይ ያድር ዘንድ በመከራዬ ልመካ ወደድሁ። ስለዚህም ስለ ክርስቶስ መከራ መቀበልን፣ መሰደብን፣ መጨነቅን፣ መሰደድን፣ መቸገርንም ወደድሁ፤ መከራ በተቀበልሁ ጊዜ ወዲያውኑ እበረታለሁና። (፪ቆሮ ፲፪፥፰) በማለት በእርሱ ላይ ያደረው ደዌ በፈቃደ እግዚአብሔር እንደሆነና ለምንም እንደተሰጠው ሲናገር በመከራው (በደዌው) ምክንያት የሚያገኘው ጸጋ እንዳለ ያስረዳል። ስለዚህ ጸጋ የሚያስገኝ መከራ ይጣፍጣል።

በሃይማኖት ጸንተን ምግባራችንን አቅንተን እየኖርን የሚመጣብን ቅጣት ክብር የሚያሰጥ ነው። ሐዋርያው ያዕቆብ “በመከራ የሚታገሥ ሰው ብፁዕ ነው፤ ተፈትኖ እግዚአብሔር ለሚወዱት ተስፋ ያደረገላቸውን የሕይወት አክሊል ይቀበላልና።” (ያዕ.፩፥፲፪) በማለት እንዳስተማረን መከራችን፣ ተጋድሏችን ሰማያዊ ክብርን የሚያሰጥ፣ ዘለዓለማዊ ደስታን የሚያጎናጽፍ ነው። ስለዚህ እንደዚህ ያለውን ተጋድሎ ባንጋደል ሰማያዊው ክብር ይቀርብናል። ይህ መንፈሳዊ ተጋድሎ የማያልፈውን፣ የማይጠፋውን፣ ዘለዓለማዊ ክብር የሚያሰጠን ስለሆነ በዚህ መንፈሳዊ ተጋድሎ አለመጽናታችን የምናስበውንና የምንመኘውን ክብር እንዳናገኝ ያደርገናል።

ሊቁ ቅዱስ ያሬድ “ሞዕዎ ለእኩይ ኅሊና በእምነቶሙ እስመ ሠናየ ገድለ ተጋደሉ፤ መልካሙን ገድል ተጋድለዋልና በእምነታቸው ክፉውን ሐሳብ ድል አደረጉት” በማለት እንደገለጸው ይህ መንፈሳዊ ተጋድሎ ክፉውን ሐሳብ ጥቅምት/ ፳፻፲፫ ዓ.ም 12 ትምህርተ ሃይማኖት ፲፪ ድል የምናደርግበት ነውና እጅግ ይጥማል። ቅዱሳኑም ሰማያዊውን ዓለም እያሰቡ ተጋድሎውን ሳይሳቀቁት ይልቁንም እየጣፈጣቸውና እየተመቻቸው መከራውን በመቀበላቸውም እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ተግባራዊ ክርስትናን አሳይተውናል።

. የሚመራቸው፡

ከላይ የተገለጸው መንፈሳዊ ተጋድሎ ለእነ ቅዱስ ጳውሎስ እንደጣማቸው ለነዴማስ አልጣማቸውም። እነ ቅዱስ ጳውሎስ “አማን መነኑ ሰማዕት ጣዕማ ለዛ ዓለም ወከዐዉ ደሞሙ በእንተ እግዚአብሔር ወተዐገሡ ሞተ መሪረ በእንተ መንግሥተ ሰማያት፤ ሰማዕታት በእውነት የዚችን ዓለም ጣዕም ናቁ ስለ እግዚአብሔር ደማቸውን አፈሰሱ፣ ስለመንግሥተ ሰማያትም መራራ ሞትን ታገሡ” (ውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ) እንደተባለው በመከራው ሲደሰቱ እነዴማስ ግን እንዲህ ዓይነቱን ሕይወት ሳይሆን የተሰሎንቄን ከተማ መረጡ። ስለዚህ በመልካም ተጋድሎ መንግሥተ ሰማያትን መውረስ መቻልን፣ ወይም መንፈሳዊውን ተጋድሎ በጸጋ መቀበልንና በሕይወት መተርጎምን ከሩቅ ለመጡት ጣፋጭ ለቅርብ ሰዎች ግን መራራ አደረገው ማለት በተጋድሎ ሰማያዊውን ዓለም እንደሚወርሱ የተሰበከላቸው የእግዚአብሔር ሕዝቦች የተባሉት እስራኤል ጸንተው መቀበል ሲያቅታቸው ከአሕዛብ ወገን የነበሩት ግን አምነው መልካሙን ተጋድሎ ተጋድለው ይህ ዓይነት ሕይወትም ጣፍጧቸው እንደተጠቀሙበት ለመግለጽ ነው።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በመዋዕለ ስብከቱ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ ቀራጮችና አመንዝሮች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በመግባት ይቀድሟችኋል” (ማቴ.፳፩፥፴፩) በማለት የተናገረው ትንቢቱ የተነገረላቸው ሱባኤው የተቈጠረላቸው አምነው መቀበል ሲቸገሩ ትንቢት ያልተነገረላቸው ሱባዔ ያልተቈጠረላቸው አሕዛብ አምነው በመቀበላቸው ለክብር መብቃታቸውን ያስረዳናል።

. ንስሓው

ንስሓ ሰው ከእግዚአብሔር ጋር የሚታረቅበት፣ ከቅዱሳን ኅብረት አንድ የሚሆንበት ታላቅ ስጦታ ነው። የመልካም አባት ስጦታ፣ የፍቅር ስጦታ እየተባለም በሊቃውንት ዘንድ ይነገራል። ይህን ታላቅ ስጦታ ተረድተውት ለሚጠቀሙበት የሚጣፍጥ ነው። ለማይጠቀሙበት ግን ፍርድን ያስከትላል። ኃጢአታቸውን እያሰቡ ያለቀሱት፣ ዘመናቸውን በአግባቡ የተጠቀሙትን ለምሳሌ ብንጠቅስ አዳም፣ ዳዊት፣ ቅዱስ ጴጥሮስ፣ በቀኝ የተሰቀለው ሽፍታ እናገኛለን። ይሁን እንጂ የንስሓ ዕድሜ ተሰጥቷቸው ያልተጠቀሙበት ደግሞ እንደ ይሁዳና ሌሎችም የይሁዳን መንገድ የተከተሉትን መጥቀስ ይቻላል።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቃሉን አምነው ባለመቀበላቸውና ንስሓም ባለመግባታቸው እንዲህ ይወቅሳቸው ነበር። “ኮራዚ ወዮልሽ ቤተ ሳይዳ ወዮልሽ በእናንተ የተደረገ አምራት በጢሮስና በሲዶና ተደርጎ ቢሆን ማቅ ለብሰው አመድም ነስንሰው አስቀድመው ንስሓ በገቡ ነበር። ነገር ግን እላችኋለሁ በፍርድ ቀን ከእናንተ ይልቅ ጢሮስና ሲዶና ዕረፍትን ያገኛሉ። ቅፍርናሆም አንቺም እስከ ሰማይ ከፍ ከፍ ብትዪ እስከ ሲኦል ትወርጃለሽ፤ በአንቺም የተደረገው ተአምራት በሰዶም ተደርጎ ቢሆን እስከ ዛሬ በኖረች ነበር። ነገር ግን እልሻለሁ በፍርድ ቀን ከአንቺ ይልቅ የሰዶም ምድር ዕረፍትን ታገኛለች።” (ማቴ.፲፩፥፳፩-፳፬)

ይህ ኀይለ ምንባብ የሚያስረደሳን መድኅነ ዓለም ክርስቶስ በአካል ተገልጦ ቢያስተምራቸው አንመለስም ብለው የንስሓ ሕይወትን ገንዘብ አለማድረጋቸውን ነው። አባ ጽጌ ድንግም “ለሀገሩ ሰዎች መራራ አደረጋት” ብሎ የገለጸው እንዲህ ያለውን በቅርብ የተገኘ ጸጋ በአግባቡ አለመጠቀምን ሲያስረዳን ነው።

. ሥጋ ወደሙ

በሰው ልጅ ሕይወት የሚገድልም የሚያድንም ምግብ አለ። አዳም ከአንዲት ዕፀ በለስ በቀር በገነት ያለው ሁሉ ሲፈቀድለት ዕፀ በለስን ግን ተከልክሏል። የተፈቀደለት ነገር በሕይወት እንዲኖር የሚያስችለው ሲሆን የተከለከለው ግን ሞትን የሚያመጣበት ነበር። የተፈቀደለት ነገርና የተከለከለው ዕፀ በለስ እንዳለ ሆኖ ብላም አትብላም የሚል ትእዛዝ ያልተላለፈበት ዕፀ ሕይወትም ነበረ። አትብላ የተባለውን ዕፀ በለስን ሲበላ ሞት ተፈረደበትና ዕፀ ሕይወትን ተከለከለ። “አሁንም እጁን እንዳይዘረጋ ደግሞም ከሕይወት ዛፍ ወስዶ እንዳይበላ ለዘለዓለምም ሕያው ሆኖ እንዳይኖር ስለዚህ የተገኘባትን መሬት ያርስ ዘንድ እግዚአብሔር አምላክ ደስታ ከሚገኝባት ገነት አስወጣው” (ዘፍ.፫፥፳፪-፳፫) እንዲል።

አዳም አትብላ የተባለውን ዕፀ በለስን በመብላቱ ዕፀ ሕይወትን ተከለከለው። በአዳም ሕይወት ዕፀ በለስ የሚገድል ዕፀ ሕይወት ደግሞ ዘለዓለማዊ ሕይወትን የሚያስገኝ ነበር። በሐዲስ ኪዳን ላለን ምእመናን በዕፀ ሕይወት ፈንታ የታደለን ሥጋ ወደሙ ነው። ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም እመቤታችን ቅድስት ማርያምን ባመሰገነበት በውዳሴ ማርያም ድርሰቱ “ ከፈለነ ንብላዕ እም ዕፀ ሕይወት ዘውእቱ ሥጋሁ ለክርስቶስ ወደሙ ክቡር በእንተ ፍቅረ ዚአነ፤ ከሕይወት እንጨት እንበላ ዘንድ አደለን ይኸውም ሰውን ስለመውደዱ ያደለን ሥውና ደሙ ነው” (ውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ) በማለት እንደገለጸው ሕይወትን የሚሰጠን ዘለዓለማዊ ሕይወትን ገንዘብ አድርገን እንድንኖር የተሰጠን ሥጋውና ደሙ ነው።

የተለያዩ ነገሮች የተለያየ ጠባይና ተፈጥሮ መኖራቸው ላያስደንቅ ይችላል። ዕፀ በለስና ዕፀ ሕይወት የሞትና የሕይወት እንጨት መሆናቸው ብዙ ላይገርመን ይችላል። ነገር ግን አንዱ ዕፀ ሕይወት ለአንዱ ሕይወትን የሚያድል ለሌላው ደግሞ ሞትን የሚያመጣ መሆኑ የረቀቀ ምሥጢር። ሥጋ ወደሙ ሕይወትን የሚያድላቸው እንዳሉ ሁሉ ሞትን የሚያመጣባቸው ወገኖች አሉ። እነርሱ እንማን ናቸው? የሚለውን እንመለከታለን።

. የሚጣፍጣቸው

ፈቅደውና ወደው ንስሓ ገብተው የሚችሉትን ዝግጅት አድርገው ለሚቀበሉት ሕይወት መድኃኒት ነው። ሊቁ አባ ሕርያቆስም በቅዳሴው “እሳት ማሕየዊ ለርቱዓነ ልብ ለእለ ይገብሩ ፈቃዶ፤ ፈቃዱን ለሚፈጽሙ የሚያድን እሳት ነው” (ቅዳሴ ማርያም) በማለት እንደገለጸው በእግዚአብሔር ፈቃድ ለሚመላለሱት እንድንበታለን ብለው አምነው ለሚቀበሉት ሕይወት መድኃኒት ነው። ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋውንና ደሙን አስፈላጊ እንደሆነ ብቻ ሳይሆን ያለዚያ ሰማያዊ መንግሥትን መውረስ እንደማይቻልም አስተምሮናል። “እውነት እውነት እላችኋለሁ የሰውን ልጅ ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ የዘለዓለም ሕይወት የላችሁም። ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው፤ እኔም በኋለኛይቱ ቀን አነሣዋለሁ። ሥጋዬ እውነተኛ መብል ደሜም እውነተኛመጠጥ ነውና” (ዮሐ.፮፥፶፫-፶፭)

. የሚመራቸው

ሥጋዬን ብሉ ደሜን ጠጡ ብሎ ሲያስተምር በእምነት መቀበል የተቸገሩት አይሁድ “ይህ እንበላ ዘንድ ሥጋውን ሊሰጠን እንዴት ይችላል? ብለው እርስ በእርሳቸው ተከራከሩ” (ዮሐ.፮፥፶፪) በእርግጥም አምነው ለማይቀበሉት፣ ሳይገባቸው ለሚቀበሉት የማይቻል ነው። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ምእመናን በላከላቸው መልእክቱ “አሁንም ሳይገባው ይህን ኅብስት የበላ ይህንም ጽዋ የጠጣ የጌታችን ሥጋውና ደሙ ስለሆነ ዕዳ አለበት” (፩ቆሮ.፲፫፥፳፯) በማለት ሳያምኑበትና ያድነኛል ሳይሉ ንስሓም ሳይገቡ ለሚቀበሉት ዕዳ እንደሚሆናቸው፣ እንደማይመቻቸው ያስረዳል። ሊቁ አባ ሕርያቆስም መድኃኒትነቱን ብቻ ሳይሆን የሚያጠፋ መሆኑንም “እሳት በላዒ ለአማጽያን ለእለ ይክህዱ ስሞ” ስሙን ለሚክዱት ለአመጸኞች የሚባላ እሳት ነው። በማለት ከማን አንሼ ብለው፣ እገሌ ሲቈርብ አየን ብለው የሚቀበሉት እንዳልሆነ በእንደዚህ ያለ ሁኔታ ላይ ሆነው ቢቀበሉት ደግሞ መፈራረጃ እንደሚሆን አስረድቷል።

በአጠቃላይ በማይመረመር ጥበቡና በልዩ ፍቅሩ የፈጠረን እግዚአብሔር አምላካችን የሚሰጠን ሁሉ መልካም ነው። ይሁን እንጂ የተሰጠንን ነገር በአግባቡ ባለመጠቀማችን ስንጎዳበት እንስተዋላለን። አንዳንዶቹ በቤቱ እየኖሩ፣ በክህነት አገልግሎት እየተመላለሱ፣ ግን ለቤቱ የሚገባና የሚመች አገልግሎት ባለመፈጸማቸው ሲጠፉበት ይስተዋላሉ። በአንጻሩ ደግሞ ከውጭ ሆነው እግዚአብሔርን በመፍራትና በመንቀጥቀጥ የሚኖሩ ግን ለእግዚአብሔር እንጂ ለሰው መንፈሳዊ ማንነታቸው የማይገለጥ በርካታ ሰዎች አሉ። ለዚህ ነው “ከሩቅ ለመጡት የሚጣፍጥ ለሀገሩ ሰዎች ደግሞ መራራ አደረጋት” በማለት አባ ጽጌ ድንግል የገለጸልን። በቤቱ ኖረን ለቤቱም የሚገባውን ክብር በመስጠት አገልግሎታችንን ፈጽመን ሰማያዊውን ዓለም እንዲያወርሰን እግዚአብሔር ይፍቀድልን አሜን።

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *