ክርስቶስ ተከፍሎአልን ? (፩.ቆሮ.፩፥፲፪)

ዲን ታደለ ፈንታው( ዶ/ር)

                           

ክፍል  ሁለት

 

 የሰው ልጆች በክርስትና አስተምህሮ

 

የሰው ልጅ አንድ ሆኖ ተፈጥሮ ሳለ በቦታ ምክንያት አንዱ ወደ ቀኝ ሌላው ወደ ግራ ወይም ደግሞ አንዱ ወደ ሰሜን ሌላው ወደ ደቡብ ይጓዛል፡ በዚያም በሚኖርበት ስፍራ እንደ መጽሐፍ ቃል ይባዛል፤ ምድርንም ይሞላታል፡፡ ከዚህም የተነሣ በተለያየ መልክ፣ ቋንቋ፣ ባህል፣ ወግ፣ ሥርዓት፣ እምነት  መኖሩ የተለመደ ሆነ፡፡ ይህንንም ብዝኃነት ክርስትና የሚቀበለው እንጂ የሚቃወመው አይደለም፡፡

ከመጀመሪያው አንድ ሆኖ የተፈጠረ የሰው ልጅ በቋንቋ፣ በባህል፣ በኑሮ፣ በአስተሳሰብ፣ በሥልጣኔ፣ በአኗኗር የተለያየ ቢሆንም መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባሕርያችንን ነሥቶ ሰው ሲሆን፤ በመስቀሉም ጥልንና ሞትን አጥፍቶ በከበረ ደሙ ፈሳሽነት አንድ አድርጎናል፡፡ የሰው ልጅ በጥንተ ተፈጥሮ አንድ ሆኖ የተፈጠረ በዘመኑ ፍጻሜም በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ሆኗል፡፡

ነገር ግን የሰው ልጅ ከውድቀት በኋላ በእርሱ ዘንድ ባለች የኃጢአት ዝንባሌ ምክንያት ልዩነትን እንደ ውበት ሳይሆን እንደ ቅራኔ መነሻ ለመለያያ እሳቤ ሲጠቀምበት ይስተዋላል፡፡ ይህም ልዩነት የመጣላት፣ የመገፋፋት ምንጭ በመሆን እያደገ እና እየሰፋ መጥቶ በወንድማማቾች መካከል እንኳን እስከ መገዳድል የሚያደርስ ሆኗል፡፡ ይህ ደግሞ ከሃይማኖታዊ (ከኦርቶዶክሰዊ) አስተምህሯችን ጋር ፈጽሞ የሚቃረን ነው፡፡ ስለሆነም “ክፉውን ከመካከላችሁ አስወግዱት” ተብሎ እንደተፃፈ በክርስትና ሕይወታችን ውስጥ ቆርጠን ልንጥለው ይገባል፡፡

ስለ ሰው ልጆች ክብር የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ምን ይላል?

የሰው ልጅ ባሕርይ አንድ ከሆነ ክብሩም በሁሉም የሰው ልጀች ዘንድ አንድ እንጂ ሌላ አይሆንም፡፡ እኩልነት እና ወንድማማችነት የዚሁ ተመሳሳይ ባሕርይ ክብር እንጂ ችሮታ ወይም ግኝት ወይም የፖለቲከኞች ይሁንታ አይደለም፡፡

አስቀድመን ያነሣናቸው እሳቤዎች በስቶክ ፍልስፍና እሳቤ ውስጥ ሳይቀር የሚነሣ ቢሆንም እውነተኛ ቅርጽ እና ትርጉም፣ መሠረት፣ ፍኖት ጥንካሬን የሰጠው ግን ክርስትና ነው፡፡ በርግጥ ሐዋርያው እንዳለው የሰው ልጆች የሚበላለጡ ከሆነ የሚበላላጡት እግዚአብሔር በሚሰጣቸው ጸጋ ነው፡፡ ምክንያቱም የጸጋ ልዩ ልዩ ነው፡፡ “እግዚአብሔርም በሰጠን ጸጋ መጠን ልዩ ልዩ ስጦታ አለን” እንዲል፡፡ መንፈስ ግን አንድ ነው፡፡ አገልግሎትም ልዩ ልዩ ነው፡፡ ጌታም አንድ ነው፡፡ አሠራርም ልዩ ልዩ ነው፡፡ ሁሉን በሁሉ የሚያደርግ እግዚአብሔር ግን አንድ ነው፡፡… አካልም አንድ እንደሆነ ብዙም ብልቶች እንዳሉበት ነገር ግን የአካል ብልቶች ሁሉ ብዙዎች ሳሉ አንድ አካል እንደሆኑ ክርስቶስ ደግሞ እንዲሁ ነው፡፡ አይሁድ ብንሆን የግሪክ ሰዎች ብንሆን ባሪያዎች ብንሆን ጨዋዎችም ብንሆን  እኛ ሁላችን በአንድ መንፈስ፣ አንድ አካል እንድንሆን ተጠምቀናልና ሁላችን አንዱን መንፈስ ጠጥተናል፡፡(፩ኛ ቆሮ.፥፲፩፥፲፯-፴፪)

የሰው ልጆች በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስመ ክርስትና ሀብተ ወልድና ያላቸው ክርስቲያኖች አንድ አባት አብ፣ አንድ ጌታ መድኅን ክርስቶስ፣ አንድ ሕያው መንፈስ መንፈስ ቅዱስ፤ አንድ ተስፋ እርሱም ዘላለማዊ ሕይወት አላቸው፡፡ ይህ ሰው በመሆን ተከፍሎ የለበትም፡፡ አንድ የመኖሪያ ስፍራ እርሱም አምልኮአቸውን የሚፈጽሙባት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አለቻቸው፡፡

ይቀጥላል

 

 

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *