‹‹በመስቀሉ አርኀወ ገነተ፤በመስቀሉ ገነትን ከፈተ››ድጓ ዘቅዱስ ያሬድ

በመ/ር ለይኩን አዳሙ ባሕር ዳርማእከል
  ክፍል -፩
ሊቅነትን ከትሕትና ምናኔን ከቅድስና ከአምላኩ እግዚአብሔር የተቸረው ማኀሌታዊው የሊቃውንቱ አባት የመንፈስ ቅዱስ ዕንዚራ የሆነው ሙራደ ስብሐት ቅዱስ ያሬድ ረቂቃን የሆኑ ሰማያውያን መላእክትን በምስጋና መስሎ እንደ ሰማያውያን መላእክት እግዚአብሔርን በአመሰገነበት የዜማ ድርሰቱ ክርስቶስ ጽኑዕ በሆነ ክንዱ መንጥቆ ሲኦልን በርብሮ ነፍሳትን ነጻ ካወጣ በኋላ ለ5500 ዘመን የሰው ልጆችን ስትውጥ የነበረችን ሲኦልን ዘግቶ በአዳም አለመታዝ የተዘጋችን ገነት በመስቀሉ ቁልፍነት በሥልጣኑ ከፈተ በማለት መስቀሉ ዲያብሎስ ድል የተነሣበት ገነት የተከፈተበት መሆኑን በሚገባ ተናገረ ፡፡
ይህ የተዘጋች ገነት የተከፈተባት መስቀል ለሰማያውያን መላእክት የድላቸው ምልክት የቅዱሳን አባቶቻችን የተጋድሏቸው አርማ ነው፡፡ይህ መስቀል ጎልጎታ ላይ የተተከለ መፍቀሬ ሃይማኖት ለሆነው ለቆስጠንጢኖስ በሰማይ የታየ ለሚፈሩትና ለሚያመልኩት ለኢትዮጵያ ምልክት ሆኖ የተሰጠ የሃይማኖት አርማ ነው፡፡በአዳም በደል ምክንያት ገነት ተዘግታ በኪሩቤል ሰይፍ ትጠበቅ እንደነበረና የዓለም መድኃኒት የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ተሰቅሎ ጥንተ ርስታችን ገነትን ከፈተልን ‹‹ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ የሚለውን የምሥራችም አሰማን›› (ሉቃ ፳፫÷፵፫) ቅዱስ ያሬድም ይህን መነሻ አድርጎ ከላይ በርእስነት የጠቀስነውን ቃል በበዓለ መስቀል በሚዘመረው ድጓ ላይ ዘምሮት እናገኘዋለን፡፡
፩. የመስቀል ትርጒም
መስቀል ማለት‹‹ሰቀለ፣ ሰቀለ›› ካለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ምሥጢራዊ ትርጒሙ ወይም ፍችው መስቀያ፣መሰቀያ መከራ ማለት ነው፡፡ኢትዮጵያዊው ሊቅ እንዲህ ሲል ይተረጉማል ‹‹መስቀል ብሂል ዕፀ ሕይወት ብሂል፤መስቀል ማለት የሕይወት ዛፍ ማለት ነው››፡፡በማለት ሊቁ ክርስቶስ ዙፋኑ ያደረገውን ዓለም የዳነበትን ቅዱስ መስቀል የሕይወት ዛፍ በማለት ተርጒሞታል፡፡ አዳምና ሔዋን የበሉት ዕፀ በለስ ሞትና ውርደትን ፍርሃትና መቅበዝበዝን ወደ ዓለም ቢያመጣም ዳግማይ አዳም ክርስቶስ የተሰቀለበት ዕፀ መስቀል ግን ሕይወትን ሰላምንና አንድነትን ክብርን ለአዳምና ለልጆቹ ያጎናጸፈ ስለሆነ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ የሕይወት ዛፍ በማለት ድንቅ በሆነ አገላለጽ ተርጒሞታል፡፡
                                                                                                   መስቀል በብሉይ ኪዳን
መስቀል ከልደተ ክርስቶስ በፊት ወይም በብሉይ ኪዳን የዐመፀኞች፣የወንጀለኞች፣መቅጫ እንደ ነበረ የታሪክ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ሰውን ለመጀመሪያ ጊዜ በመስቀል ላይ መቅጣት የተጀመረው ፋርስ ወይም ኢራን ተብላ በምትጠራ ሀገር ውስጥ ነው፡፡ በፋርስ ወይም በኢራን ሀገር የነበሩ ሰዎች የመሬት አምላክ ወይም ኦርዝሙድ የተባለውን ጣዖት ያመልኩ ስለነበረ በሀገራቸው ሰው ወንጀል ሲፈጽም ቅጣቱን በመሬት ላይ የተቀበለ እንደሆነ ደሙ ፈሶ ኦርዝሙድ ጣዖታቸውን የሚያረክሰው ስለሚመስላቸው ቅጣቱን በመስቀል ላይ ይፈጽሙበት ነበር፡፡
በእስራኤል ሀገር ሰው በደል ሠርቶ ሕግ ተላልፎ የሞት ፍርድ ከተፈረደበት በኋላ ሬሳው ለማስጠንቀቂያ ከዛፍ ላይ ይሰቀል እንደነበረ እስትንፋሰ እግዚአብሔር የሆነው ቅዱስ መጽሐፍ ሕያው ምስክር ነው፤ ዘዳ ፳፩÷፳፫፡፡ በብሉይ ኪዳን ሙሴ የፈርዖንን መሰግላን (ጠንቋዮች) ድል ያደረገባት በትር የመስቀል ምሳሌ ነው፡፡

፪.መስቀል በሐዲስ ኪዳን
የሐዲስ ኪዳኑ መስቀል መድኃኒት አልባ ለሆነው ዓለም መድኃኒት ሊሆን ወደዚህ ዓለም የመጣ አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰውነቱ ክፋት በአንደበቱም ሽንገላ ሳይኖርበት እንደበደለኛ ተቆጥሮ ከበደለኞች ጋር በደልን በተመሉ በአይሁድ እጅ ተይዞ በግፍ በተሰቀለ ጊዜ አካሉ ያረፈበት የሰላም እግሮቹ የተቸነከሩበት የፍቅር እጆቹ የተዘረጉበት ጎኑ በጦር ተወግቶ ክቡር ደሙ የፈሰሰበት የፍቅር ዙፋን ነው፡፡
በመሆኑም የሐዲስ ኪዳኑ መስቀል አምላክ በክብሩ ያከበረው በቅድስናው የቀደሰው ስለሆነ ለደከሙት ኃይልን ለታመሙት ፈውስን ላዘኑት መጽናናትን ለዕውሮች ብርሃንን ማሰጠቱ ይታወቃል፡፡ የአምላክ ኃይሉና ጥበቡ ማዳኑ የተገለጠበት የፍቅር ዐደባባይ ነው፡፡

በልብ መታሰቡ በቃልም መነገሩ ከፍ ከፍ ይበልና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን በገዛ ሥልጣኑ ድል አድርጎ ከተነሣ በኋላም ድውይ በመፈወስ ሙት በማስነሣት ብርሃን ለሌላቸው ብርሃንን በመስጠት ድንቅ የሆነ ማዳኑንና ተአምራቱን የገለጸው በአከበረውና በቀደሰው መስቀል ነው፡፡ በዕለተ ዓርብ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከጲላጦስ ተካሰው ክርስቶስን በሐዲስ መቃብር ከቀበሩት በኋላ ከዚያው ከመቃብሩ አጠገብ አስቀምጠውት ነበር፡፡ ይህ መስቀልም ሙት የሚያነሣ ዕውር የሚያበራ ለምጻም የሚያነጻ በመሆኑ አይሁድ ለደካሞች ኃይልና ጉልበት ለነፍስ ቤዛ መድኃኒት በሆነው መስቀል ላይ በጠላትነት ተነሥተው የሕሙማን መዳን ያላስደሰታቸው ምቀኞች ስለሆኑ ጉድጓድ ቆፍረው ቀበሩት፡፡

፫. አይሁድ መስቀሉን የመቅበራቸው ምክንያት ምን ነበር?
ሙታንን እያስነሣ ዕውራንን እያበራ ጎባጣን እያቀና የአምላክን ጥበብና ድንቅ ድንቅ ተአምራቱን በመግለጡ ግፍን የተመሉ ሕዝበ አይሁድ በኃጢአት በፈረጠመ ክንዳቸው የሰው ልጆች እንዳይድኑ ጉድጓድ ምሰው መስቀሉን ቀበሩት፡፡ ሕዝበ አይሁድ መስቀሉን የቀበሩት በሦስት ምክንያት ነው፡፡
፩ኛ መድኅነ ዓለም ክርስቶስ በሞተ ጊዜ ከተቀበረበት መቃብር ተነሥቶ እንዳይሄድ በሚል ሰቅለው የገደሉት አይሁድ ታላቅ ድንጋይ ከመቃብሩ አፍ ላይ አድርገውና መቃብሩን የሚጠብቁ ዘበኞችን ቀጥረው ማንም ሰው ወደ መቃብሩ እንዳይደርስ ወደ መቃብሩ የቀረበውን የቀረበ በድጋይ ወግረው እንዲገሉት ትእዛዝ ሰጥተው ነበር፡፡እመቤታችን ድንግል ማርያም ግን ክርስቶስ ከተቀበረበት ቀን ጀምሮ ዘወትር ወደ ልጇ መቃብር እየሄደች ስትጸልይ አይሁድ ይመለከቱ ነበርና በእርሷ አመላካችነት ከነገሥታት አንዱ መጥቶ በክርስቶስ ላይ ስለደረሰው መከራ ሁሉ ይጠይቀናል የተሰቀለበትንም መስቀል ስጡኝ ብሎ ይጣላናል በሚል ፍራቻ የክርስቶስን መስቀል እንዲሁም በግራና በቀኝ የተሰቀሉትን የሁለቱን ሽፍቶች መስቀል፣ ጎኑን የተወጋበትን ጦር፣ ከራሱ ላይ፣ የደፉትን የሾህ አክሊልና የተቸነከረባቸውን ችንካሮች በአንድ ላይ ምድርን ቆፍረው የቀበሩበት አንዱ ምክንያት ነው፡፡
፪ኛ ንጹሓን ቅዱሳን ሐዋርያት በኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ መስቀል ርኵሳን አጋንንት ሲያወጡ ሙታንን ሲያስነሡ ለምጻሞችን ሲያነጹ መስማት የተሳናቸው መስማት እንዲችሉ ሲያደርጉ ጎባጣዎችን ሲያቀኑ ዓይነ ሥውራንን ሲያበሩና ወንጌልን ሰብከው በማስተማር ብዙ አሕዛብን በስመ ሥላሴ አሳምነው ሲያጠምቁ ልጅነት ሲያሰጡ በማየታቸው ተሰብስበው ክፉ ምክርን መክረው የሰው ልጆች መዳን ያላስደሰታቸው አይሁድ መስቀሉን ቆፍረው ቀበሩት ሁለተኛው ምክንያት ይህ ነው፡፡
፫ኛ. ድንቅ የሆነው አምላካችን በመስቀሉ ላይ አድሮ የሚደነቅ ተአምራቱን ሲገልጽ ያዩ ሰዎች ቅናተ ሰይጣን ስላደረባቸውና የኦሪትን ሕግ ምክንያት በማድረግ ምድር ቆፍረው ቀበሩት ፡፡ ይሁንም እንጂ እንደ ክፉዎቹ አይሁድ ሳይሆን በዕፀ መስቀል ተሰቅሎ የሞተው ክርስቶስ ቅዱስ ነው፡፡ የተሰቀለበት መስቀልም ቅዱስ ነው፡፡ ክፉዎች አይሁድ ቅዱስ መስቀሉን ከቀበሩት በኋላ በተቀበረው መስቀል ላይ ከታናሽ እስከታላቅ በአንድነት ጥርጊያ ለመድፋት ተማማሉ፡፡ ለከተማው ሰው አዋጅ ነገሩ፡፡ የመስቀሉ ስም አጠራር ከሰው አዕምሮ እንዲጠፋ እንዲረሳ ለማድረግ ጌታ የተሰቀለበትን ሕሙማን የዳኑበትን መስቀል ከሥር ጥጦስና ዳክርስ የተሰቀሉበትን ከላይ አድርገው ቀብረው የከተማውን ጥራጊ እያመጡ ይደፉበት ጀመር፡፡የደፉት ቆሻሻም ተራራ እንዳከለ የታሪክ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ዲያብሎስ ተዋርዶ አዳምና ልጆቹ የከበሩበት ሕሙማን የተፈወሱበት ገነት የተከፈተበት ቅዱስ መስቀል ጉድጓድ ውስጥ ተቀብሮ ለሁለት መቶ ዓመታት ያህል በመቆየቱ ክርስቲያኖችም በጥጦስ ወረራ ከተማቸውን ለቀው በመሰደዳቸው የከተማዋ መልክአ ምድርም ተለውጦ ስለነበረ መስቀሉ የተቀበረበት ቦታ የት እንደሆነ የሚያውቀው አልነበረም፡፡
ይሁን እንጂ ጌታ በወንጌል “እስመ አልቦ ክዱን ዘኢይትከሠት ወአልቦ ኅቡዕ ዘኢይትዐወቅ፤ የማይገለጥ የተከደነ የማይታወቅ የተሠወረ ምንም የለም” በማለት አስቀድሞ እንደ ተናገረው ሁሉ(ማቴ፲÷፳፮፣ሉቃ.፲፪÷፪) ከሰዎች ኃይል የእግዚአብሔር ኃይል ከሰዎች ጥበብ የእግዚአብሔር ጥበብ ይበልጣልና እነርሱ ተሸፍኖ ወይም ተዳፍኖ ይቀራል ያሉት እግዚአብሔር የተሠወረው ተገልጦ እንዲወጣ ፈቃዱ ነበርና በሃይማኖት የጸናች በምግባር ያጌጠች የመስቀሉ ፍቅር ያላት አይሁድ በምቀኝነት እንደቀበሩት ትሰማ የነበረች ቅድስት ዕሌኒንና ልጅዋን ቆስጠንጢኖስን አስነሣ፡፡
…………….. ይቆየን !

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *