ለሰላም በሰላም እንሥራ!

 

ለሜሣ ጉተታ

ዛሬ በሀገራችን ሰላም የሚያደፈርሱ ብዙ ችግሮች ያሉ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ የተሳሳቱ የታሪክ ትርክቶች፤ ወገንተኛ መሆን፤ አክራሪነት፣ የኢኮኖሚ፣ የሃይማኖት፣ የፖለቲካና፣ የሥልጣን የበላይነትን መፈለግ፤ የሐሳብ ልዩነትን አለማክበር፣ ያለመደማመጥ፣ ያለመግባባት፣ ጽንፈኛ ብሔርተኛ መሆን፣ ዘረኝነትና የሥልጣን ጥማት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ ለዚህ መፍትሔ በዋናነት ታላላቆች  ለትውልዱ አርአያና ምሳሌ ሊሆኑ ይገባል፡፡ ከራሳችን የግልና የቡድን ጥቅም/ፍላጎት በላይ ሕዝብንና ሀገርን ማስቀደም የግድ ይላል፡፡

በተለይም ክርስቲያን ከሁሉም ሰው ጋር በሰላም፣ በአንድት፣ በፍቅር፣ በመግባባት፣ በመደማመጥ፣ በመቻቻል፣ ችግሮችን በውይይት መፍታት ለሌሎችም አርአያና ምሳሌ በመሆን ልዩነትን በማጥፋት የተጣሉትን በማስታረቅ ሊኖር ይገባል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹የሚያስታርቁ ብዑዓን ናቸው›› ይላልና፡፡ በሌላም በኩል “ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ” (ሮሜ.12፤18) መባላችን ሰላም የሁሉም ነገር መሠረት መሆኑን ያሳያል፡፡ ክርስቲያኖች ሁላችን ባለንበት ቦታ ሁሉ ሰላምን ሊያጠፉ ከሚችሉ ክፉ ተግባራት ሁሉ መራቅ አለብን፡፡ ነገሮችን በትዕግሥት፣ በጥበብና በማስተዋል ልናልፍ ይገባል፡፡ ካላስፈላጊ ክርክርና ሙግትም ልንርቅ ይገባል፡፡ ሰላምን መፈለግ፣ ነገርን መተው፣ ለይቅርታ መሸነፍ ይገባል፡፡ ይቅር ባይነትና ይቅርታን መጠየቅ አስተዋይነት እንጂ ተሸናፊነት አይደለምና፡፡ ይህ ደግሞ የክርስቲያን ቁልፍ መለያው ነው፡፡

እኛ ክርስቲያኖች በትንሹም በትልቁም፣ በሥራ ቦታ፣ በትምህርት ቤት፣ በማኅበራዊ ሕይወታችን ላይ የሰላም፣ የአንድነት፣ የፍቅርና የእርቅ ምክንያት እና ተምሳሌቶች መሆን አለብን እንጂ የግጭት፣ የልዩነት፣ የክርክር፣ የጠብ እና የጥል መንስኤ መሆን የለብንም፡፡ ፍቅር የነበራቸው፣ ታሪክ የነበራቸውና ድሆዎችን ሲረዱ የነበሩ ነገር ግን ዛሬ ስማቸውና ታሪካቸው እንዳልነበረ የሆኑ በርካቶች ናቸው፡፡ በማሳያነት ሶርያን፣ ሊቢያንና ሱዳንን ልናስታውስ ይገባል፡፡ ከምድረ ገጽም ለመጥፋት የተቃረቡም አሉ፡፡ ዜጎቻቸው ሰላምን  በማጣት በየሀገራቱ የተበተኑባቸው አሉ፡፡ የየመንና የሶሪያ ዜጎች በሰላም እጦት ምክንያት ከተደላደለ ሕይወታቸው ወጥተው ብዙዎቹ ሕይወታቸው አልፏል፤ በየሀገራቱ በስደት ተቅበዝባዥ ሁነዋል፣ በአዲስ አበባ ጎዳናዎች ላይ እንኳን ሳይቀር በልመና መሰማራታቸውን ጭምር እያስተዋልን ነው፡፡ ይህ ሁሉ ከሰላም እጦት የመጣ ችግር ነው፡፡  ከዚህ ውጪ የብዙ  ሀገራት ዜጎች ሰላምን በማጣት ሀገራችንን መጠለያ አድርገዋታል፤ ይህ ደግሞ ለእኛ ትልቅ ትምህርት ሊሆነን ይገባ ነበር፡፡

ሰላምን ለማግኘት በጎ ሥራን መሥራት ከክፋት ከተንኮል መራቅ እንዳለብን ብሎም ሰላምን መሻትና መፈለግን ተግባራችን መሆኑን መርሳት የለብንም፡፡ ሰላምን የሚሰጠው እግዚአብሔር ነው፡፡ ይህ የሚሆነው ደግሞ እኛ ሰላማዊ ስንሆን ነው፡፡ ሰላምን የማይፈልጉት ክፉዎች ብቻ ናቸው፡፡ እነርሱ ደግሞ ተንኮለኞች፣ በወንድማማች መካከልም ጥልንና ክርክርን የሚዘሩ፣ በእግዚአብሔር ዘንድም የማይወደዱ፣ የተጠሉም ጭምር ናቸው፡፡ የልዩነትና የጦርነት እንክርዳድን፣ ጥርጣሬንና ሐሜትን የሚዘሩ ናቸው፡፡ የፍቅር፣ የአንድነት እና የሰላም እንቅፋቶች ናቸው፡፡ ከዜጎች መካከል ፍቅርን፣ አንድነትን፣ መቻቻልን፣ መደጋገፍን መደማመጥን የሚያጠፉ ናቸው፡፡ ይህ እኩይ ተግባር ደግሞ በእግዚአብሔር ዘንድ አስጸያፊ ነው፤ በሥጋ መጎዳት ብቻ ሳይሆን በነፍስ ላይም ጭምር ሞትን ያስፈርዳል፡፡

የሀገር ፍቅር ያለው ሰው መገለጫው የሰላም ሰው መሆን ብቻ ነው፡፡ የሀገር ፍቅር ያለው እርቅን የሚፈልግ የይቅርታ ልብ ያለው ሰው ነው፡፡ እግዚአብሔር ጥልን የሚዘሩትን ይጸየፋል፡፡ ፍቅር የሌላቸው ክፉዎች ከእግዚአብሔር መንግሥት የተለዩ፣ ከእርሱም ጋር አንድነት ኅብረት የሌላቸው የጨለማው ልጆች ናቸው፡፡ ለጊዜው ሰላማዊ፣ ደስተኞች ሊመስሉ ይችላሉ፤ ነገር ግን ውስጣቸው ክፋታቸውን ስለሚነግራቸው በሰላም መኖር ወጥቶ መግባት፣ ተኝቶ መነሳት፣ ደስተኛ የሆነ ሕይወትን መኖር አይችሉም፡፡ ‹‹ለክፉዎች ሰላም የላቸውም›› ሊኖራቸውም አይችልም፡፡ በአንጻሩ  ደግሞ ‹‹በጎ ሥራ ለሚያደርጉ ሁሉ ምስጋናና ክብር ሰላምም ይሆንላቸዋል›› ተብሏል (ሮሜ.2፡10)፡፡ እናም ሁላችን ለሰላም በሰላም እንሥራ፤ እንጸልይ፤ ለሀገራችን ሰላምን፣ ፍቅርን፣ አንድነትን፣ መግባባትንና መቻቻልን እንዲያድለን የአምላካችን መልካም ፈቃድ ይሁንልን አሜን !

 

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *