፲፰ኛው የአሜሪካ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤ ተካሔደ።

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአሜሪካ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል ፲፰ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በሲያትል ዋሺንግተን ቅዳሜ ግንቦት ፳ እና እሑድ ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ተካሔደ።

በጉባኤው ወደ ፬፻ የሚደርሱ የማእከሉ አባላት፤ የዲሲና የአካባቢው እንዲሁም የካሊፎርንያና ምዕራብ አሜሪካ አህጉረ ስብከት ተወካዮችና የሥራ አስፈጻሚ አባላት፤ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎችና ካህናት፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።

ጉባኤው በጸሎተ ኪዳን በተጀመረበት ቅዳሜ ግንቦት ፳ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የማእከሉ ሰብሳቢ ዶ/ር ሕልምነህ ስንሻው የእንኳን ደኅና መጣችሁና የመክፈቻ ንግግር ካደረጉ በኋላ በማእከሉ የተተገበሩ ዋና ዋና የአገልግሎት ሥራዎችን ዘገባ አቅርበዋል። የዲሲ እና የአካባቢው ሀገረ ስብከት ዋና ጸሐፊ መልአከ ሰላም ቀሲስ ዶ/ር መሥፍን ተገኝም የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የብፁዕ አቡነ ፋኑኤልን መልእክት ለጉባኤው ካስተላለፉ በኋላ በመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሽፈራው “ሥራ የበዛበት ትልቅ በር” /፩ኛቆሮ. ፱፥፲፮/ በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

በመቀጠል የማእከሉ የአገልግሎት ክፍሎች ዓመታዊ ጠቅላላ ሪፖርትና የቀጣይ ዓመት ዕድቅ ለጉባኤው ቀርቧል፡፡ በቀረበው ሪፖርትም በንዑሳን ማእከላት በርካታ ትምህርታዊ ጉባኤዎች እንደተካሔዱ፣ በልዩ ልዩ ከተሞች የማኅበረሰብ ቴሌቪዥን ፕሮግራም እንደተጀመረ፣ ለገዳማት እና አብነት ትምህርት ቤቶች፣ እንዲሁም ኢአማንያንን ለማስተማርና ለማስጠመቅ ለተዘረጋው የስብከተ ወንጌል ፕሮጀክት ከአባላት እና ከምእመናን የተሰበሰበ የእርዳታ ገንዘብ ወደ ዋናው ማእከል እንደተላከ ተገልጿል።

የማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል ተወካይ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም የዋናውን ማእከል መልእክት እና ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት ከጉባኤው ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ከመስጠታቸው በተጨማሪ የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴና ወቅታዊ ጉዳዮችን በማስመልከት ሰፊ ማብራሪያ አቅርበዋል።

በሁለቱ ቀናት ጉባኤ ላይ በሲያትል ንዑስ ማእከል የአቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ውዳሴ ማርያምና ሰዓታት በንባብና በዜማ፤ የጸሎተ ቅዳሴ ተሰጥኦና ምስባክ፤ እንደዚሁም የአብነት ትምህርትን አሰጣጥና ሒደት የሚያሳይ ሥርዓተ ማኅሌት፣ ቅኔ፣ የመጻሕፍት ትርጓሜ እና የተለያዩ መንፈሳዊ ዝግጅቶችን አቅርበዋል።

በተጨማሪም የሲያትል ንዑስ ማእከል የአገልግሎት ተሞክሮዉን ለጉባኤው ያካፈለ ሲኾን፣ የማእከሉ የአገልግሎት ክፍሎች የበጀት ሪፖርትም ለጉባኤው ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። ከስድስት ወር በኋላ የማእከሉ የዕቅድ ክለሳ እንደሚደረግም በጉባኤው ተገልጿል።

እንዲሁም ዝክረ አበው በሚል መርሐ ግብር የሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ሰባተኛ ዓመት የዕረፍት መታሰቢያ በማስመልከት የተዘጋጀ ፊልም ለእይታ በቅቷል።

በዕለቱ ላለፉት ሁለት ዓመታት ማዕከሉን ይመራ የነበረው የሥራ አስፈጻሚ የሥራ ዘመን በመፈጸሙ፣ ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት ማእከሉን በሥራ አስፈጻሚነት የሚመሩ ፲፫ አባላት በጸሎትና በዕጣ ተመርጠዋል።

በጉባኤው ማጠቃለያ በማእከሉ ፲፰ኛ ጠቅላላ ጉባኤ አዘጋጅ ኮሚቴ የዝግጅቱ ሒደትና በሲያትል ከተማ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የሰበካ ጉባኤ አባላት፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ምእመናን በልዩ ልዩ መንገድ ያበረከቱት ከፍተኛ አገልግሎት በዝርዝር የቀረበ ሲኾን ይህ አሳታፊነትና ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ጋር በቅንጅት የመሥራት ልምድ ለሌሎች ንዑሳን ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች ያለው አርአያነት የጎላ መኾኑ ተገልጿል።

በመጨረሻም ፲፱ኛው የማእከሉ ጠቅላላ ጉባኤ በቦስተን፣ ፳ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ደግሞ በቨርጂንያ እንዲካሔድ ተወስኖ ጠቅላላ ጉባኤው በዝማሬ እና በጸሎት ተጠናቋል።

የቅዱስ ያሬድን ፲፭፻፫ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የቅኔ ውድድር ተካሔደ፡፡

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በጎንደር ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤተፐች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በጎንደር ማእከል አዘጋጅነት ግንቦት ፲፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የቅዱስ ያሬድን ፲፭፻፫ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ በጎንደር ከተማ በርእሰ አድባራት ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ ውድድር ተካሔደ፡፡

የውድድሩ ተሳታፊ ጉባኤ ቤቶች፡- የደብረ ፀሐይ ቍስቋም ማርያም፣ የደብረ ምሕረት አቡን ቤት ቅዱስ ገብርኤል፣ የቀዳሜ አድባራት አበራ ጊዮርጊስ፣ የመካነ ሕይወት ፊት አቦ እና የደብረ ገነት አዘዞ ቅዱስ ሚካኤል ቅኔ ጉባኤ ቤቶች ሲኾኑ፣ መምህራኑ የመረጧቸው ደቀ መዛሙርትም ጉባኤ ቤቶቹን ወክለው ለውድድር ቀርበዋል፡፡

ውድድሩን በዳኝነት የመሩትም መምህር ፍቅረ ማርያም የመንበረ መንግሥት መድኃኔ ዓለም የ፬ቱ ጉባኤያት ምክትል መምህር፣ ሊቀ ብርሃናት ኤልያስ አድማሴ በዐቢየ እግዚእ ኪዳነ ምሕረት የብሉይ ኪዳን መምህር እና መምህር ቃለ ሕይወት በመካነ ነገሥት ግምጃ ቤት የሐዲስ ኪዳን መምህር ሲኾኑ የውድድሩ መሥፈርቶችም አንደኛ የቅኔው ምሥጢር፣ ሁለተኛ የዜማው ልክ፣ ሦስተኛ ገቢር ተገብሮ አገባብ፣ አራተኛ የቃላት አመራረጥ እና አምስተኛ የጊዜ አጠቃቀም ናቸው፡፡ እያንዳንዱ መሥፈርት ፳፣ ባጠቃላይም ፻ ነጥቦችን የያዘ ሲኾን ለእያንዳንዱ ተወዳዳሪም የ፲፭ ደቂቃ የማቅረቢያ ጊዜ ተሰጥቶታል፡፡

በውድድሩ ከአንደኛ አስከ ሦስተኛ ደረጃ የያዙት የወንጌል አንድምታ ትርጓሜ መጻሕፍትን፤ አራተኛና አምስተኛ የወጡት ደግሞ የትንቢተ ኢሳይያስን አንድምታ ትርጓሜ መጽሐፍ ተሸልመዋል፡፡ ይኸውም ቅኔ ተምረናል በቃን ብለው እንዳያቆሙ እና ቀጣይ መጻሕፍትን እንዲማሩ ለማሳሰብ ነው፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የማእከሉ ሰብሳቢ መምህር ዓለማየሁ ይደግ እንደተናገሩት የውድድር መርሐ ግብሩ የተዘጋጀበት ዓላማ በጉባኤ ቤቶች መካከል መልካም የሆነ የውድድር መንፈስ እንዲኖር፣ ተማሪዎቹ ራሳቸውን እንዲፈትሹ ለማድረግ፣ የቅኔ ትምህርት በማኅበረሰቡ ዘንድ እንዲታወቅ፣ የበታቾቻቸውን ለማነሣሣት እና በዋናነት ቅዱስ ያሬድን ለመዘከር ነው፡፡

የጎንደር ከተማ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቀ ካህናት ሊቀ አእላፍ ጥበበ አወቀ በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው እንደዚህ ዓይነቱ መርሐ ግብር እየቀዘቀዘ የመጣውን የአብነት ትምህርት በተለይ የቅኔ ትምህርት እንደሚያጠናክር ጠቅሰው ይህም ማኅበረ ቅዱሳንን እንደሚያስመሰግነው ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም ለደቀ መዛሙርቱ አባቶቻችን ይህን ትምህርት በእግዚአብሔር ኃይል ጸንተው፣ ኮቸሮ በልተው፣ በውሻ ተበልተው አቆይተውናል፤ እኛም ጠብቀን ለትውልድ ማቆየት ይኖርብናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ በስድስቱም ጉባኤ ቤቶች የሚገኙ በርካታ የአብነት ተማሪዎች እና በርካታ ምእመናን የተገኙ ሲኾን፣ ከምእመናኑም ይህ የቅኔ ትምህርት እንዲስፋፋ ሰፊ ትኩረት ተሰጥቶት ሊሠራ እንደሚገባው አስተያየት ተሰጥቷል፡፡

የጎንደር ማእከል መዘምራንም ቅዱስ ያሬድን የሚዘክሩ የሰማይ ምስጋና የሚል የንስሐ መዝሙር እና ያሬድ ማኅሌታይ ለእግዚአብሔር ካህኑ የሚል ወረብ አቅርበዋል፡፡

የመርሐ ግብሩ መምህር በጽሐ ዓለሙ በመንበረ መንግሥት መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን የ፬ቱ ጉባኤያት ምክትል መምህር በአብነት ትምህርት ቤት ሦስት ዓይነት ተማሪ አለ፤ እነሱም፡- እግረ ተማሪ፣ ልብሰ ተማሪ እና ልበ ተማሪ ናቸው ካሉ በኋላ ኹላችንም ልበ ተማሪን ኾነን ትምህርታችንን በሚገባ መማር አለብን ብለዋል፡፡

በመጨረሻም በአባቶች ጸሎት መርሐ ግብሩ ተጠናቋል፡፡ ይህ መርሐ ግብር በፋና ኤፍ ኤም 98.1 የሬድዮ ጣቢያም የሚዲያ ሽፋን ማግኘቱ የሚታወስ ነው፡፡

የአዳማ ማእከል የሕክምና አገልግሎት ሰጠ፡፡

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአዳማ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ለሚገኙ አባቶችና እናቶች መነኮሳት እንዲሁም ለአብነት ተማሪዎች ግንቦት ፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የሕክምና አገልግሎት ሰጠ፡፡

በሕክምና አገልግሎቱም በአዳማ ማእከል፣ በደብረ ዘይት ወረዳ ማእከልና በአዱላላ ግንኙነት ጣቢያ የሚገኙ ስፔሻሊስት ሐኪሞች፣ ሜዲካል ዶክተሮች፣ የጤና መኮንኖች፣ የላቦራቶሪ ቴክኒሻኖች እና የአዳማ ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ግቢ ጉባኤ የሕክምና ተማሪዎች በአጠቃላይ ፴፰ የሕክምና ባለሞያዎች ተሳትፈዋል፡፡

በሕክምና አገልግሎቱም ለገዳሙ መነኮሳት እና አብነት ተማሪዎች ሙሉ የጤና ምርመራና የመድኃኒት ድጋፍም ተደርጓል፡፡ ለአባቶች መነኮሳትና ለእናቶች መነኮሳይያት የስኳር፣ የደም ግፊት እና የዓይን ምርመራ ተደርጎላቸዋል፡፡ የመድኃኒት አቅርቦቱም ከዋናው ማእከል ቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል እና ከአንድ በጎ አድራጊ ወንድም የተገኘ ነው፡፡ የአዳማ ኢዮር ክሊኒክ የመድኃኒትና የሕክምና መመርመሪያ መሣሪያ ከማቅረቡ ባሻገር የክሊኒኩ ስፔሻሊስት ሐኪሞችም ከፍተኛ አገልግሎት ፈጽመዋል፡፡

በዕለቱ ሕክምና የተደረገላቸው አባቶች መነኮሳት፣ እናቶች መነኮሳይያትና የአብነት ተማሪዎች ከ፪፻፶ የሚበልጡ ሲኾን፣ ከሕክምናው በተጨማሪ ለአብነት ተማሪዎች የግልና የአካባቢን ጤና አጠባበቅ የተመለከተ ሥልጠና በጤና ባለሞያዎች ተሰጥቷቸዋል፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ በአዳማ ማእከል የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ለአብነት ተማሪዎች የተዘጋጀው አልባሳት፣ የገላና የልብስ ሳሙና በገዳሙ በኩል ለአብነት ተማሪዎቹ እንዲከፋፈል ተደርጓል፡፡

የገዳሙ አባቶች፣ እናቶች መነኮሳትና እና የአብነት ተማሪዎቹ በተደረገላቸው የሕክምና፣ የአልባሳት እና የጤና መጠበቂያ ድጋፍ እጅግ መደሰታቸውን ገልጸው ማኅበረ ቅዱሳን በገዳማት ላይ እየሠራ ያለው አገልግሎት የሚያስመሰግነው መኾኑንና ይህንንም ሁልጊዜ ሲያስታውሱት እንደሚኖሩ በመጥቀስ ማኅበሩ በገዳማት ላይ የሚያደርገውን አገልግሎት አጠናክሮ እንዲቀጥል በማሳሰብ ማኅበሩን ያስፋልን ይጠብቅልን በማለት መርቀው የሕክምና ቡድኑን በቡራኬና በጸሎት አሰናብተዋል፡፡

አምስተኛው ዐውደ ርእይ በሰላም ተጠናቀቀ፡፡

ግንቦት ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ማኅበረ ቅዱሳን የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ በሚል መሪ ቃል ከግንቦት ፲፯-፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለስድስት ቀናት በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ያዘጋጀው አምስተኛው ዐውደ ርእይ ግንቦት ፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ 4፡00 በሰላም ተጠናቀቀ፡፡

ዐውደ ርእዩ ከተጀመረበት ዕለት እስከ ተጠናቀቀበት ሰዓት ድረስ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በብዙ ሺሕ ምእመናን፣ በመንግሥት ባለ ሥልጣናትና በሌሎች ቤተ እምነት ተከታዮችም ተጎብኝቷል፡፡

በዐውደ ርእዩ ከተሳተፉ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የሰቲት ሑመራ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ይህ ዛሬ ያየነው በማኅበረ ቅዱሳን የተዘጋጀ ትልቅና አስደናቂ ዐውደ ርእይ ነባሩን ኢትዮጵያዊ ሥርዓት፣ ቅርስ፣ ታሪክና ትውፊት የሚገልጽ ዐውደ ርእይ ነው፤ በመኾኑም በጣም የሚወደድ፣ የሚከበርና የሚደነቅ ነው ብለዋል፡፡ አክለውም ይህንን ነባር ሥርዓት ለማጥፋት የሚጥሩ ብዙ ሐሳውያንን ስላሉ ኹላችንም ከመንበረ ፓትርያርክ ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ጠንክረን መሥራት ይኖርብናል፤ ዐውደ ርእዩም እስከ ወረዳ ድረስ መታየት ይገባዋል ካሉ በኋላ በርቱ፤ ጠንክሩ፡፡ ኹሉም ነገር ለሰላም፣ ድህነትን ለማጥፋት፣ አንድነትን ለማጽናት፣ በአጠቃላይ ድንቁርናን ለማስወገድ መኾን ይኖርበታል በማለት አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋና የደቡብ ኦሞ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የሲኖዶስ አባል ደግሞ ይህንን የመሰለ ያማረ ጉባኤ ሳይ በጆሯችን የሰማነውን በዓይኖቻችንም ያየነውን እንመሰክራለን ተብሎ እንደተጻፈ የሰማሁትንና ያየሁትን መመስከር ግድ ይለኛል፡፡ ልጆቻችንን በዚህ ደረጃ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ያበቋቸው ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ናቸው፡፡ ብፁዕነታቸው እኔ ለኩሸዋለሁ፤ እናንተ አንድዱት የሚል ቃል ተናግረው ነበር፡፡ በእውነትም እርሳቸው የለኮሱት መንፈሳዊ ሕይወት፣ መንፈሳዊ አገልግሎት ነዷል፡፡ ከኢትዮጵያም ተርፎ በመላው ዓለም ተዳርሷልና ይህንን በማየታችን እጅግ በጣም ደስ ብሎናል ሲሉ የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም እግዚአብሔር የሚቋረጥ ሥራ አይወድምና በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የአባቶቻቸውን አደራ እንደ ጠበቁ ልጆች ማኅበረ ቅዱሳንም የአባታችሁን የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስን አደራ በመጠበቅ አገልግሎታችሁን ልትቀጥሉ፤ ፈተናዎችንም በመወያየትና በመነጋገር ልታልፏቸው ይገባል የሚል አባታዊ ምክር ለግሰዋል፡፡

በሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የኾኑት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤልም የዚህ ታላቅ ማዕድ ተካፋይ በመኾኔ እጅግ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡ በእናንተ በልጆቻችንም መንፈሳዊ ኩራት ይሰማናል፡፡ ልበ አምላክ ዳዊት በአባቶች ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ እንዳለው ኹሉ ተዋሕዶ እምነታችን እንደዚህ ለሃይማኖታችሁ የምትቆረቆሩ የምታስቡ ልጆች በማግኘቷና እኛም እንደዚህ ዓይነት ትውልድ ባለበት ሰዓት በመነሣታችን እጅግ ደስ ይለናል ሲሉ ስሜታቸውን ከገለጹ በኋላ ማኅበሩ የሠራው ሥራ የሚያስመሰግነው ቢኾንም በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈው እኛ ለጌታ የማንጠቅም ባሪያዎች ነን ማለት እንደሚገባውም ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም ይህ ሥራ የመጨረሻችሁ ሳይኾን የመጀመሪያችሁ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ከእናንተ ጋር ናቸው፡፡ ከአባቶቻችሁ መመሪያ እየተቀበላችሁ ከዚህ የበለጠ እንድታገለግሉ አደራ እላለሁ የሚል አባታዊ ምክር ሰጥተዋል፡፡

ሌሎች ብፁዓን አበውም ማኅበረ ቅዱሳንን አስነሥቶ ሕዝበ ክርስቲያኑን በዚህ መልኩ እንዲሰባሰብና ስለ ቤተ ክርስቲያኑ፣ ስለ ሃይማኖቱ እንዲማር በማድረጉ እግዚአብሔርን አመስግነዋል፤ በማኅበሩ ሥራ መደሰታቸውንም ገልጸዋል፡፡ ለወደፊትም ከአባቶች ጋር በመመካከር ከዚህ የበለጠ መትጋት እንደሚገባ አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡

አንዳንድ ያነጋገርናቸው ምእመናን እንደገለጹልን በዝግጅቱ ከመደሰታቸው የተነሣ ከቤተሰቦቻቸውና ከልጆቻቸው ጋር በመኾን ስድስቱን ቀን በሙሉ በዐውደ ርእዩ ተሳትፈዋል፡፡ በዐውደ ርእዩ መሳተፍ የሚኖረውን ጠቀሜታ አስመልክቶ ቃለ መጠይቅ ያደርግንላቸው ምእመናንም ዐውደ ርእዩ ኹሉም ምእመን ስለ ሃይማኖቱ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያኑና ስለ አገሩ ታሪክ እውቀት እንዲኖረው ከማድረጉ በተጨማሪ ራሱን እንዲያይና ድርሻውን በማወቅ የሚጠበቅበትን ሓላፊነት እንዲወጣ የሚያስችል ግንዛቤ ያስጨብጠዋል ብለዋል፡፡

ከአስተያየት መስጫ መዛግብት ላይ ከሰፈሩ ዐሳቦች ውስጥም ዐውደ ርእዩ በጣም አስተማሪ መኾኑን ገልጸው፣ የአዘጋጆቹን፣ የአስተናጋጆቹንና የገላጮቹን ጥንካሬ በማድነቅ እንደዚህ ዓይነቱ ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ከተማ ብቻ ሳይኾን፣ በየክፍለ ሀገሩና በየወረዳው መዘጋጀት እንደሚገባው፤ ትዕይንቶቹም ቀለል ባለ መልኩ በብሮሸርና በሲዲ መልክ ለምእመናን መዳረስ እንደሚኖርባቸው አስተያየት የሰጡ ሰዎችን ዐሳብ በአብዛኛው አንብበናል፡፡ በተጨማሪም ማኅበሩ በዐውደ ርእዩ ላይ የበጎ አድራጎት ማኅበራት ሥራዎች እንዲተዋወቁ ማድረጉ ያስመሰግነዋል፤ ለወደፊቱ እንደዚህ ዓይነት ዐውደ ርእይ ሲያዘጋጅ ከቤተ ክህነትና ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ጋር በጋራ ቢሠራ ደግሞ የበለጠ ውጤታማ ይኾናል የሚሉና ሌሎችም አስተያየቶች ተሰጥተዋል፡፡

በአንጻሩ የዐውደ ርእዩ ጊዜ ጠባብ መኾኑ፣ ማኅበሩ ኤግዚብሽን ማዕከሉ ውስጥ ለታዳሚዎች የሚኾን ምግብ ቤት ስላልተዘጋጀ፣ እንደዚሁም በትዕይንቶቹ አዳራሾች ውስጥ ጎብኝዎቹ ስለሚደራረቡና የልዩ ልዩ ትዕይንቶች ገላጮች ድምፅ ስለሚቀላቀል ለወደፊቱ ሰፊ ዝግጅት ያስፈልገዋል ብለዋል፡፡ ከዚህ በተለየ ደግሞ ማኅበሩ ራሱን የሚያስተዋውቅበት የትዕይንት ክፍል ማዘጋጀት ነበረበት የሚል አስተያየት በጽሑፍም በቃልም ተነሥቷል፡፡

ከውጪ አገር ከመጡ ጎብኝዎች መካከል ማርቆስ ሀይዲኛክና ባለቤቱ አገራቸው ቡልጋርያ በሃይማኖታቸውም የምሥራቅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባል መኾናቸውን ጠቅሰው በዚህ ዐውደ ርእይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክና ሥነ ጽሑፋዊ ጥበብ፣ የክርስቲያኖቹን ትጋትና መንፈሳዊ ሕይወት እንደዚሁም የአገሪቱን ሕዝብ ባህል እንደተረዱበት ለዝግጅት ክፍላችን ገልጸዋል፡፡

ከሌላ ቤተ እምነት ከመጡ ግለሰቦች መካከልም ማርሺያ ሲንግልተን የምትባል አንዲት አሜሪካዊት የፕሮቴስታንቲዝም እምነት ተከታይ በዚህ ዐውደ ርእይ በመሳተፏ እድለኛ መኾኗን ጠቅሳ በጉብኝቱም የኢትዮጵያ ኦርቶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በታሪክ የበለጸገና በመጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ ላይ የተመሠረተ መኾኑን ከገለጸች በኋላ ዐዲስ እውቀት እንዳገኝ ስላደረጋችኹኝ አመሰግናለሁ የሚል አስተያየቷን በእንግሊዝኛ ቋንቋ አስፍራለች፡፡

በተያያዘ ዜና አንድ ጣልያናዊ ጎልማሳ የእስልምና ሃይማኖት ተከታይ በዐውደ ርእዩ የኢትየጵያን ታሪክና የክርስትናን አስተምህሮ እንደተረዳበትና በመታደሙም ደስተኛ እንደኾነ ገልጾ፣ ዐውደ ርእዩ በርካታ ምሁራን የተሳተፉበት መኾኑን ከትዕይንቶቹ ይዘት መረዳቱን ከተናገረ በኋላ ማኅበሩንና አዘጋጆቹን አመስግኗል፡፡

በመጨረሻም በትናንትናው ዕለት ከምሽቱ 4፡00 ዐውደ ርእዩ ሲጠናቀቅ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚዎች፣ የዝግጅቱ አስተባባሪዎች፣ የትዕይንት ገላጮች፣ የአብነት ተማሪዎችና ሌሎችም ድጋፍ ሰጪ አካላት በኤግዚብሽን ማዕከሉ ግቢ ውስጥ ተሰባስበው ንሴብሖ ለእግዚአብሔር ስቡሐ ዘተሰብሐ እያሉ በሰላም ያስፈጸማቸውን ልዑል አግዚአብሔርን በዝማሬና በዕልልታ አመስግነዋል፡፡

አምስተኛው የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል

ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ከፍ ብሎ የሚሰማው የመዝሙር ድምፅና በማዕከሉ መግቢያ በር ላይ የተለጠፉ መንፈሳውያን ማስታወቂያዎች አካባቢው አንዳች ብርቱ ጉዳይ እንዳለበት ይመሰክራሉ፡፡ ብዙ የቆሙ መኪኖች፣ በሺሕ የሚቈጠሩ ምእመናን መንገዱን አጨናንቀውታል፡፡

ከዐዲስ አበባ ከተማ ብቻ ሳይሆን ከልዩ ልዩ የኢትዮጵያ ክፍላተ አህጉር የሚመጡ ምእመናንና ምእመናት ከግንቦት 17 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ እግሮቻቸውን ወደ አንድ አቅጣጫ አድርገዋል፤ ወደ ዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል፡፡ የጉዟቸው ምክንያት ደግሞ የማኅበረ ቅዱሳን አምስተኛው ዙር መንፈሳዊ ዐውደ ርእይ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን ዐውደ ርእይ ለማዘጋጀት ከዓመታት በፊት ዓቅዶ ሠርቷል፤ ዐውደ ርእዩ ለምእመናን ሊቀርብ የነበረውም ከመጋቢት 15-21 ቀን 2008 ዓ.ም የነበረ ቢኾንም ዳሩ ግን በሰዓቱ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ባይኾን ግልጽ ባልነበረ ምክንያት ዐውደ ርእዩ መታገዱ ሲሰማ ብዙ ምእመናን ተደናገጡ፡፡

የማኅበሩ ሥራ አመራር አባላትም፡- አይዟችሁ አትደንግጡ፤ ኹሉም በጊዜው ይኾናል፡፡ እግዚአብሔር በፈቀደበት ጊዜ ዐውደ ርእዩን እናሳያችኋለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ግን በትዕግሥት ኾነን እንጠባበቅ፤ ወዘተ እያሉ ዐውደ ርእዩን በጉጉት ሲጠባበቁ የነበሩትን ምእመናን እያጽናኑ ከሚመለከታው አካላት ጋር ውይታቸውን ቀጠሉ፡፡

እግዚአብሔር ሥራውን የሚሠራበት ጊዜ ሲደርስ በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት፣ በአባቶችና በእናቶች ጸሎት የማኅበሩና የተባባሪዎቹ ጥረት ተሳክቶ ዐውደ ርእዩ የሚታይበት ቀን ደርሶ እነሆ ከግንቦት 17 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለተመልካቾቹ ይፋ ኾነ፡፡

መስቀል ዐደባባይን በማቋረጥ ከሰሜን ወደ ምዕራብ አቅጣጫ ከፍ ብሎ ወደሚገኘው ቅፅር ግቢ ውስጥ ሲገሰግሱ የኢትዮጵያውያንን ባህል ገላጭ የኾነውንና ጠቢባኑ የተካኑበትን በረጅሙ ቆሞ ከርቀት የሚታየውን በኅብረ ቀለማት ያጌጠውን መሶብ ያገኛሉ፡፡

ይህንን መሶብ አለፍ እንዳሉ በግዙፉ መግቢያ በር ላይ አምስተኛው ዙር የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል፣ ከግንቦት 17-22 ቀን 2008 ዓ.ም የሚሉ ማስታዎቂያዎች በረጅም ብራና ቁልቁልና አግድም ተለጥፈው ይነበባሉ፡፡

ከታች ደግሞ የጸጥታ ባለሙያዎች ተመልካቾችን በጥንቃቄ እየፈተሹ ወደ ኤግዚብሽን ማዕከሉ ቅፅር እንዲገቡ ያደርጋሉ፡፡ የዐውደ ርእዩ ታዳሚዎችም በሩ ውስጥ የተመደቡትን የቲኬት ሽያጭ አስተባባሪዎች ፈቃድ ካገኙ በኋላ ወደ አዳራሾቹ ጥቂት እንደተጓዙ ከአስፋልቱ በስተቀኝ በኩል ተንጣሎ የሚታየውን ቍጥር አንድ አዳራሽን ያገኛሉ፡፡ ይህ አዳራሽ በቍጥር የመጀመሪያው ይሁን እንጂ በዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ግን የመጨረሻው ነው፡፡

በአስተባባሪዎች መሪነት ወደ ሰሜን ምዕራብ አቅጣጫ ጥቂት ተጉዘው ጊዜያዊ የእንግዶች ማረፊያ ድንኳን ውስጥ ቁጭ ብለው በድምፅና በምስል የታገዙ ልዩ ልዩ መንፈሳውያን መረጃዎችን ሲከታተሉ ከቆዩ በኋላ በተራ ቅደም ተከተላቸው መሠረት ወደ ትዕይንቱ አዳራሾች ያመራሉ፡፡

የኤግዚብሽን ማዕከሉ በስተሰሜን በኩልም ተጨማሪ የመግቢያ በር ያለው ሲኾን፣ እንደዋናው በር ኹሉ የመግቢያ ቅድመ ኹኔታዎችን ካሟሉ በኋላ ወደ ደቡብ አቅጣጫ ሲያመሩ በዋናው በር ከገቡ ታዳሚዎች ጋር በአንድ ድንኳን ውስጥ አብረው እንዲቆዩ ይደረጉና ወደ ትዕይንቶች ይገሰግሳሉ፡፡

ይህ መንፈሳዊ ዐውደ ርእይ በአባቶች ጸሎት ከተከፈተበት ዕለት ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በርካታ ምእመናን እየተመለከቱት ሲኾን፣ የምእመናኑ ቍጥርም ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ ነው፡፡

የዐውደ ርእዩ አዘጋጆችና አስተባባሪዎቹ ምእመናኑ ረጅም ሰዓት በመቆም እንዳይጉላሉ በማሰብ የሚቻላቸውን ኹሉ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ ስለዚህም ከኤግዚብሽን ማዕከሉ አዳራሾች በተጨማሪ ሰፋፊ ድንኳኖችን በማዘጋጀት ተጨማሪ መመልከቻ ቦታዎችን አመቻችተዋል፡፡

ትዕይንታተ ዐውደ ርእይ

ዐውደ ርእዩ በሦስት መንገድ ይጎበኛል፤ ይኸውም በገላጮች ማብራሪያ፣ በባነሮች (ብራናዎች) ላይ በተቀመጡ ጽሑፎችና መረጃዎች እንደዚሁም በድምፅ ወምስል በመታገዝ ነው፡፡ የዐውደ ርእዩ ዐበይት አርእስትም አራት ሲኾኑ እነዚህም፡-

የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት፤ ሁለተኛው የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ፤ ሦስተኛው የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ፤ አራተኛው ደግሞ ምን እናድርግ የሚሉ ናቸው፡፡ የእያንዳንዳቸውን ጭብጥ ለማስገንዘብ ያህል የአርእስቱን ዐሳብ በአጭሩ እንመልከት፤

ትዕይንት አንድ፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት

ይህ ትዕይንት ሀልዎተ እግዚአብሔር፣ ነገረ ድኅነት፣ ነገረ ማርያም፣ ነገረ ቅዱሳን እና ነገረ ቤተ ክርስቲያን የተካተቱበት ክፍል ነው፡፡ ሀልዎተ እግዚአብሔር በሚለው ርእስ እግዚአብሔር አምላክ በጊዜና በቦታ የማይወሰን፣ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው፣ የፍጥረታት ኹሉ አስገኝ፣ ከመሥፈርትና ከአመለካከት ውጪ፣ እርሱ በገለጠው መጠን ብቻ የሚታወቅ እንጂ ባሕርዩ ተመርምሮ ሊደረስበት እንደማይቻል እንደዚሁም መልዕልተ ኵሉ (የኹሉ የበላይ) ኾኖ ሳለ በፈቃዱ የትሕትና ሥራ መሥራቱን ያስረዳል፡፡

ነገረ ድኅነት ደግሞ በአዳምና በሔዋን ምክንያት የዘለዓለም ሞት ተፈርዶበት የነበረው የሰው ልጅ ከሦስቱ አካላት አንዱ በኾነው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀልና ሞት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መቻሉን፤ ንደዚሁም እምነት፣ ምግባር እና ምሥጢራተ በቤተ ክርስቲያንን መፈጸም የሰው ልጅ ለመዳን የሚያስፈልጉት ነገሮች መኾናቸው በዚህ ርእስ ሥር ተካቷል፡፡

ትዕይንት ሁለት፡- የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ

በዚህ ትዕይንት የሐዋርያነትና የሐዋርያዊ አገልግሎት ትርጕም፣ ዓላማና አመሠራረትን ጨምሮ ስብከተ ወንጌል አንዴት እንደተስፋፋና እስከ ዛሬ ድረስ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሱ ፈተናዎችን እንደዚሁም መልካም አጋጣሚዎችን በማካከተት ልዩ ልዩ መረጃዎችና ትምህርቶቸ ቀርበውበታል፡፡

ትዕይንት ሦስት፡- የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ

ይህ ትዕይንት ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን ለማስፋፋት ያሳለፈችውን ተጋድሎ፣ የመናፍቃንን ተፅዕኖና የሰማዕታትን ታሪክ፣ የተዋሕዶ ሃይማኖትን አስተምህሮ ለማስጠበቅ የተደረጉ ልዩ ልዩ ዓለም ዓቀፍና አገር ዓቀፍ ጉባኤያትን በዝርዝር ይዟል፡፡

ትዕይንት አራት፡- ምን እናድርግ?

ይህ ትዕይንት ደግሞ ምእመናን በዐውደ ርእዩ ከተመለከቷቸውና ከሰሟቸው እውነታዎች በመነሣት የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ከመጠበቅና ድርሻን ከማወቅ አኳያ ልዩ ልዩ ችግሮችን ለመቅረፍ ወደፊት ምን ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው የሚያስረዱ መረጃዎችን አካቷል፡፡

ዐውደ ርእዩ ከነዚህ ዐበይት ትዕይንቶች በተጨማሪ የሕፃናት ትዕይንትም የተካተተበት ሲኾን፣ በዚህ ትዕይንት ለሕፃናት አእምሮ የሚመጥኑ መንፈሳውያን ትምህርቶች ተዘጋጅተውበታል፡፡ ሕፃናቱም ክፍሉ ውስጥ እየዘመሩ ይማራሉ፤ ይደሰታሉ፡፡

ከሁሉም በተለየ መንገድ ደግም የሁሉም ገባኤያት (የንባብ፣ የዜማ/የድጓ፣ የቅዳሴ፣ የቅኔ፣ የአቋቋም፣ የመጻሕፍትና የአቡሻሕር ጉባኤ ቤቶች) ሊቃውንት (መምህራን) ደቀ መዛሙርታቸውን ሲያስተምሩ እስከ ጎጆዎቻቸውና እስከሚጠቀሙባቸው ዕቃዎች ድረስ በተግባር ይታያሉ፡፡ የብራና መጻሕፍት አዘገጃጀትም በባለሙያ አባቶች ይብራራል፡፡

የማኅበረ ቀዱሳንን ልዩ ልዩ ክፍሎች፣ እንደዚሁም የጽርሐ ጽዮንና የደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳውያን ማኅበራት አገልግሎት የሚቃኝባቸው ክፍሎችም የትዕይንቱ አካላት ናቸው፡፡ በማኅበሩ የሚዘጋጁ ንዋያተ ቅድሳትና መጻሕፍትም በሽያጭና በዕጣ መልክ ቀርበዋል፡፡

ማኅበረ ጽዮን የጉዞ ማኅበር፣ መቄዶንያ የአረጋውያንና የአእምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል፣ ዮድ አቢሲንያ አስጎብኚና የጉዞ ወኪል ስለሚሰጧቸው ተግባራት የሚገልጹባቸው ክፍሎችም ተካተዋል፡፡

ትዕይንቶቹን ተመልክተው የሚወጡ ምእመናንም ኾኑ የሌሎች እምነት ተከታዮች ለሚያነሷቸው ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን መውጫው በር ላይ ተሠይመዋል፡፡

የዐውደ ርእዩ ታዳሚዎች ጉብኝቱን ጨርሰው ሲወጡ ደግሞ የተሰማቸውን ስሜት ወይም ደግሞ ቅሬታ የሚያሰፍሩባቸው የአስተያየት መስጫ መዛግብት በብዛት ተደርድረዋል፤ ጎብኝዎቹም ስሜታቸውን እየጻፉ ወደየመጡበት ይመለሳሉ፡፡

ከዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ጎን ለጎንም ከግንቦት 17 ቀን 2008 ጀምሮ የአብነት ትምህርቶችን የተመለከቱ ጥናቶችና መንፈሳውያን ተውኔቶች እንደዚሁም መዝሙራት ከቀኑ 11፡00 እስከ ምሽት ድረስ ለጎብኝዎቹ በመቅረብ ላይ ይገኛሉ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለአምስተኛ ጊዜ ያዘጋጀው ይህ ዐውደ ርእይ መታየት ከጀመረ እነሆ ዛሬ አምስተኛውን ቀን ያስቈጠረ ሲኾን፣ እጅግ በሚማርክ ኹኔታ በአባቶች ካህናትና በምእመናን ብቻ ሳይኾን በሌሎች ሰዎችም እየተጎበኘ ይገኛል፡፡

ትናንትናና ዛሬም በርካታ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በዐውደ ርእዩ ተገኝተው አባታዊ ቡራኬ ሰጥተዋል፤ ማኅበሩ እየሠራ ያለውን ተግባር በማድነቅም ስሜታቸውን መዝገብ ላይ አስፍረዋል፡፡

ለዐውደ ርእዩ ድምቀት ከሰጡ ክሥተቶች መካከልም የሰንበት ት/ቤት ዘማርያን የመዝሙር ልብስ ለብሰው እየዘመሩ፤ እንደዚሁም በዛሬው ዕለት (ግንቦት 21 ቀን 2008 ዓ.ም) ጋብቻቸውን የፈጸሙ ጥንዶች ከአጃቢዎቻቸው ጋር በመኾን በዐውደ ርእዩ መታደማቸው ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡

ዐውደ ርእዩ ከተከፈተበት ቀን ጀምሮ በአስተያየት መስጫ መዛግብቱ ላይ የሰፈሩትን አስተያየቶች ስናነብና ቃለ መጠይቅ ስናደርግ ብዙ ምእመናን በዐውደ ርእዩ ራሳቸውን እንዳዩበትና ስለሃይማኖታቸው በቂ ግንዛቤ እንዳስጨበጣቸው እንደዚሁም የድርሻቸውን ለመወጣት እንዳነሣሣቸው ተረድተናል፡፡

በተጨማሪም ዐውደ ርእዩ በዐዲስ አበባ ብቻ ሳይኾን በየአገሩ ቢታይ፣ ትዕይንቶቹ በብሮሸርና በሲዲ መልክ ቢሠራጩ፣ ከጠቅላይ ቤተ ክህነትና ከሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ጋር በጋራ በመኾን ማቅረብ ቢቻል መልካም ነው የሚሉና የመሳሰሉ አስተያየቶች ተሰጥተዋል፡፡

በአንጻሩ በትዕይንቶቹ ገላጮችና በምስል ወድምፅ ዝግጅቶች መካከል የድምፅ መጋጨት እንዳይኖር ጥንቃቄ ቢደረግ፤ ግቢው ውስጥ በማኅበሩ የተዘጋጁ ምግቦችና መጠጦች ለሽያጭ ቢቀርቡ፤ ትዕይንቶቹ ሰፊ ጊዜ ተሰጥቷቸው በስፋት ቢተነተኑ፤ አዳራሾቹ ውስጥ ረጅም ሰዓት መቆየት ባይኖር፤ ወዘተ የመሰሉ በርካታ አስተያየቶችንም ከአንዳንድ ጎብኝዎች ለመረዳት ችለናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስን ጉባኤ መጀመር አስመልክቶ ከቅዱስ ፓትርያሪኩ የተሰጠ መግለጫ

ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች፣ እንደሚታወቀው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በዛሬው ዕለት ተጀምሯል፤ ቅዱስ ፓትርያሪኩ ጠዋት ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ለጋዜጠኞች የሰጡትን ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ወዓዲ እብለክሙ ለእመ ኀብሩ ክልኤቱ አው ሠለስቱ እምኔክሙ በውስተ ምድር በእንተ ኵሉ ግብር ዘሰአሉ ይትገበር ሎሙ በኀበ አቡየ ዘበሰማያት እስመ ኀበ ሀለዉ ክልኤቱ ወሠለስቱ ጉቡአን በስምየ ህየ እሄሉ አነ ማእከሎሙ፤ ዳግመኛም ከእናንተ ሁለቱ ወየም ሦስቱ በምድር ላይ ስለሚለምኑት ሥራ ሁሉ ቢተባበሩ፣ በሰማያዊ አባቴ ዘንድ ይደረግላቸዋል፤ ሁለቱ ወይም ሦስቱ በስሜ ተሰብስበው ካሉበት፣ እኔ ከዚያ በመካከላቸው እገኛለሁና /ማቴ.፲፰፥፲፱-፳/፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ከጌታችን፣ ከአምላካችንና ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተሰጠንን ዓቢይ ተልእኮ ወይም ሐዋርያዊ አገልግሎት በየተሠማራንበት ሀገረ ስብከት ስናከናውን ቆይተን፣ በዓለ ትንሣኤውን ካከበርን በኋላ፣ በቀኖና ሐዋርያት ድንጋጌ መሠት፣ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን ጉዳዮች ለመነጋገር በዚህ በረክበ ካህናት ዓመታዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አንድ ላይ ስለሰበሰብን፣ አምላካችን እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማይታበል ቃሉ እንዳስተማረን፣ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የገባው ቃል ኪዳን አለ፤ እርሱም ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር የተፈጸመ ጽኑ ቃል ኪዳን ነው፡፡ ቃል ኪዳኑም፡- ሁለቱ ወይም ሦስቱ በስሜ በተሰበሰቡበት፣ እኔ ከዚያ በመካከለቸው እገኛለሁ ይላል፡፡ በሁሉም ዘንድ እንደሚታወቀው፣ ቃል ኪዳን በሁለት ወገኖች መካከል የሚፈጸምና ለቃል ኪዳኑ መከበር የሁለቱንም የቃል ኪዳን አካላት ኃላፊነት በግልጽ የሚያስቀምጥ ነው፤በዚህ ሁኔታ እግዚአብሔር ከጥንት ጀምሮ ከቅዱሳን አበው ጋር ቃል ኪዳን መሥርቶ እንደነበረ በቅዱስ መጽሐፍ በየቦታው ተጽፎ እናገኛለን፡፡

ይሁንና በዘመነ ሐዲስ ጌታችን ቃል ከገባባቸው ዓበይት ነገሮች አንዱ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ነው፡፡ በዚህ ቃል ኪዳን ውስጥ ቅዱስ ሲኖዶስ በስመ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲሰበሰብ ሓላፊነት ተሰጥቶታል፡፡ ጌታችንም በስሙ በሚደረግ ጉባኤ እንደሚገኝ ቃል ገብቶአል፡፡

በመሆኑም የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በርእሰ መንበርነት፣ ቅዱስ ፓትርያርክ በመሪነት፣ ሊቃነ ጳጳሳት በአባልነት የሚገኙበት ዓቢይ ጉባኤ ነው፡፡ ቅዱስ ወይም ልዩ ጉባኤ የሚያሰኘውም ቅሉ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በርእሰ መንበርነት የሚገኝበት በመሆኑ ነው፡፡ ይህ ጉባኤ ጌታችን እስከ ዓለም ፈጻሜ ድረስ እንደማይለየው ሲገልጽ፡- ወናሁ አነ እሄሉ ምስሌክሙ እስከ ኅልቀተ ዓለም፤ እነሆ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ እኔ ከናንተ ጋር ነኝ ብሎ በቃሉ አረጋጦአል /ማቴ.፳፰፥፳/፡፡

እንግዲህ በየጊዜው ስመ እግዚአብሔርን ጠርተን በስሙ፣ ስለስሙ ብለን የምናካሂደው ቅዱስ ጉባኤ ወይም ቅዱስ ሲኖዶስ ይህን ያህል ታላቅ ክቡርና ጽኑ የሆነ አምላካዊ ቃል ኪዳን ያለው እንደመሆኑ መጠን፣ ለደረጃው በሚመጥን ክብርና ልዕልና መካሄድ ይኖርበታል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ጌታችን፣ አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን በአደራነት ያስረከበ ለዚህ ጉባኤ እንደሆነ በውል የሚታወቅ ነው፡፡

ይህ ቅዱስ ጉባኤ የእግዚአብሔር መንግሥት ወኪል እንደመሆኑ መጠን ድንበር የለውም፤ ምክንያቱም የእግዚአብሔር መንግሥት ድንበር የለውምና፡፡ ይህ ጉባኤ ገደብ የለሽ መንፈሳዊ ሥልጣን ከሕያው አምላክ ሲሰጠው፣ ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፤ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ ከሚል ትእዛዝ ጋር መታዘዙ የቅዱስ ሲኖዶስ መንፈሳዊ ሥልጣን ድንበር የማይገድበው መሆኑን በግልጽ ያሳያል /ማር.፲፮፥፲፭/፡፡

በመሆኑም የዚህ ቅዱስ ጉባኤ ሥራና ሓላፊነት ዓለም አቀፋዊ ይዘት ያለው መሆኑ ሊሠመርበት ይገባል፡፡ ይህም በመሆኑ ነው ዛሬ ቤተ ክርስቲያናችን በሁሉም ክፍላተ ዓለም አብያተ ክርስቲያናትን ከፍታ ሐዋርያዊ ተልእኮዋን በማካሄድ ላይ የምትገኘው፡፡

ይሁንና አሁን የምንገኝበት የሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ወቅት፣ የሴኩላሪዝም አስተሳሰብ ያየለበት፤ የዓለም ሉላዊነት የበረታበት፣ የጽንፈኝነትና የሽብርተኝነት መንፈስ የተስፋፋበት፣ እነዚህ ሁሉ በየፊናቸው ተሰልፈው በሃይማኖት ላይ ከባድ ተጽዕኖ የፈጠሩበት ዘመን ነው፡፡ ዓለም በዚህ ሥጋዊ ፍልስፍና እና ቁሳዊ አምሮት ቤተ ክርስቲያንን ለመውጋት ስትዘጋጅ እኛ የክርስቶስ ወኪሎች እንዲሁ ዝም ብለን የምናይበት ኅሊና ሊኖረን አይችልም፡፡

ቀደምት አበው እሾህን በእሾህ ብለው እንደተናገሩት፣ የዓለምን ጥበብ በክርስቶስ ጥበብ ለመቋቋም፣ በዓለም እየሆነ ያለውን ነገር ሁሉ መከታተልና ማወቅ፣ ለወደፊትም ሊያስከትለው የሚችለውን ሃይማኖታዊ፣ ማኅበራዊ፣ ሰብአዊና ባህላዊ ቀውስ አስቀድሞ በመተንበይ፣ ሕዝቡን በእግዚአብሔር ቃል ኃይል መጠበቅና መንከባከብ ከእኛ ይጠበቃል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

በሃይማኖት ዙሪያ ያንዣበቡ እነዚህ ዓለም አቀፍ ተፅዕኖዎች እጅግ አስጊ ቢሆኑም፣ እነርሱን ለመከላከል ብሎም ለመቀልበስ አሁንም ቢሆን ጊዜው አልመሸም፡፡ በተለይም በሀገራችን ያለው ሕዝብ፣ አሁንም ምርጫው እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን እንደሆነ በተጨባጭ የምናውቀው ሐቅ ነው፡፡ ይህንን ሕዝብ በሚገባ ማገልገል ከተቻለ፣ ችግሩን በሚገባ መቋቋም ይቻላል፡፡

ስለሆነም ሕዝበ ክርስቲያኑን በአግባቡ ለማገልገልና ለመጠበቅ፣ ከሁሉም በፊት የሕዝቡን ጥያቄ ማወቅ ያስፈልጋል፤ ቀጥሎም ለጥያቄው ተገቢ የሆነ መልስ በመስጠት ፍጹም መግባባት መፍጠር ይገባል፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑ ከሃይማኖት መሪዎችና ከአገልጋይ ካህናት የሚጠብቀውን ሁለንተናዊ አገልግሎት በሚገባ ካገኘና በሃይማኖቱ እንዲኮራ የሚያስችል ሁኔታ ከተመቻቸለት፣ ለተጠቀሱ ዓለም ዓቀፍ ተፅዕኖዎች ተንበርካኪ አይሆንም፡፡ ስለሆነም የኛው የጥበቃ ስልት መቀየስ ያለበት በዚሁ መንፈስ አቅጣጫ ነው፡፡

ሕዝበ ክርስቲያኑ በአሁኑ ጊዜ የሚጠይቃቸው ብዙ ነገሮች አሉ፤

ሕዝቡ፣ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና ለሃይማኖት መጠበቂያ ብሎ በእምነት የሚለግሰው ገንዘብና ንብረት ከምዝበራ ተጠብቆ ለታለመለት ዓላማ ብቻ እንዲውል ይፈልጋል፤

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መልካም አስተዳደር ሰፍኖ አድልዎ፣ ጭቅጭቅ፣ ንትርክ፣ መለያየት በአጠቃላይ ከሃይማኖቱ መርሕ ጋር የማይጣጣም ኋላ ቀር አሠራርና አስተሳሰብ ተወግዶ የተስተካከለ ሥርዓትን ማየት ይፈልጋል፤

ስለሃይማኖት ክብርና ህልውና ከልብ የሚቆረቆሩ፣ መልካም የሆነ ሥነ ምግባርና የተስተካከለ ሰብእና ያላቸው እንደዚሁም በኑሮአቸው ሁሉ ለሕዝበ ክርስቲያኑ እንደ ሞዴል የሚጠቀሱ ውሉደ ክህነትና ሠራተኞች እንዲመሩት ይፈልጋል፤

ሕዝቡ ቤተ ክርስቲያን በሁሉም መስክ ጠንካራ ዓቅምን ገንብታ እንደዚሁም ለሕዝበ ክርስቲያኑ መንፈሳዊና ማኅበራዊ ችግር ደራሽና አለሁላችሁ ባይ ኾና ማየት እንደሚፈልግ ከሚያነሣው ጥያቄ ማወቅ ይቻላል፡፡

ብፁዓን ሊቃ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

የእኛ ተልእኮ እግዚአብሔርንና ሕዝብን ማገልገል ከሆነ፣ የሕዝቡ ጥያቄም ከሞላ ጎደል የሚታወቅ ከሆነ፣ በተሰጠን አደራና ሓላፊነት መሠረት የሕዝበ ክርስቲያኑን ጥያቄ በጽሞና አዳምጠንና ተቀብለን፣ በቅዱስ መጽሐፍ አስተምህሮ፣ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ድንጋጌና ባሉን የቤተ ክርስቲያን ሕጎች ማእከልነት፣ ጥያቄውን የማስተናገድ ክርስቶሳዊ ግዴታ አለብን፡፡

ከሕግ የወጣ የሥራ አፈጻጸም ሲኖርም፣ ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ በወቅቱ ማረም ያስፈልጋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቱያናችን የመጨረሻ ውሳኔ ሰጭ አካል እንደመሆኑ መጠን፣ የቤተ ክርስቲያናችንን መልካም አስተዳደር ለማስፈን የሚያስችሉ ሕጎችን፣ ልዩ ልዩ ደንቦችን፣ መመሪያዎችን፣ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በማዘጋጀትና በማጽደቅ፣ እንደዚሁም በአፈጻጸማቸው ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ፣ ሕዝበ ክርስቲያኑን እሰየው የሚያሰኝ አሠራር ማረጋገጥ አለብን፡፡ ይኸ ሲሆን ብቻ ነው ሕዝቡን ከቁሳዊው ዓለም ማዕበል መታደግ የምንችለው፡፡

በመጨረሻም

ይህ የተቀደሰ ክርስቶሳዊና ሐዋርያዊ ጉባኤ ከልዩ ልዩ የቤተ ክርስቲያናችን አመራር አካላትና ከጉባኤው የሚቀርቡትን ሃይማኖታዊ ሀገራዊ ጉዳዮችን በጥልቀት በመፈተሽና በመመርመር እንደዚሁም ሕጋዊና ቀኖናዊ መፍትሔ በማስቀመጥ የተሳካ ውጤት ያስመዘግብ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እየጸለይንና ከልብ እየተመኘን የ፳፻፰ ዓ.ም የረክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ዛሬ መከፈቱን እናበሥራለን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤

አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም

ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን አምስተኛው ዙር ዐውደ ርእይ ተጀመረ፡፡

ዐውደ ርእዩ ለስድስት ተከታታይ ቀናት ከጠዋቱ 2፡00 እስከ ምሽቱ 1፡30 ድረስ ለተመልካቾች ክፍት ኾኖ ይቆያል፡፡

ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በማኅበረ ቅዱሳን የተዘጋጀውና በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው አምስተኛው ዙር መንፈሳዊ ዐውደ ርእይ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ የማኅበሩ ሥራ አመራር አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ እንደዚሁም የዐውደ ርእዩ ተመልካቾች በተገኙበት በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማእከል ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በአባቶች ጸሎት ተጀምሯል፡፡

በጸሎተ ወንጌሉ የተሰበከው ምስባክ፡- ጥቀ ዐቢይ ግብርከ እግዚኦ ወኵሎ በጥበብ ገበርከ መልዐ ምድረ ዘፈጠርከ፤ አቤቱ ሥራህ እጅግ ታላቅ ነው፡፡ ሁሉን በጥበብ አደረግህ፡፡ የፈጠርኸውም ፍጥረት ምድርን ሞላ፤ /መዝ.፻፫፥፳፬/ የሚለው ትምህርት ሲኾን፣ የተነበበው የወንጌል ክፍልም ሉቃ. ፲፥፳፩-፳፬ ያለው ኃይለ ቃል ነው፡፡

ጸሎተ ወንጌሉና ኪዳኑ እንደ ተፈጸመ ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ የመክፈቻ ንግግር ካደረጉ በኋላ ዐውደ ርእዩ በይፋ ለተመልካች ክፍት ኾኗል፡፡

የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ በሚል መሪ ቃል በተዘጋጀው በዚህ ዐውደ ርእይ የቤተ ክርስቲያን ማንነትና ሐዋርያዊ ተልዕኮ በዓለም፣ በአፍሪካና በኢትዮጵያ፣ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ፈተናዎችና ከምእመናን የሚጠበቁ ጉዳዮች የትእይንቱ አርእስት ኾነው ይቀርቡበታል፡፡

ዐውደ ርእዩ ከግንቦት ፲፯-፳፪ ቀን ፳፻፰ (17-22 ቀን 2008) ዓ.ም፣ ከጠዋቱ 2፡00 እስከ ምሽቱ 1፡30 ድረስ ለስድስት ተከታታይ ቀናት ለተመልካቾች ክፍት ኾኖ ይቆያል፡፡

ከመጋቢት ፲፭-፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለተመልካች ሊቀርብ የነበረው ይህ ዐውደ ርእይ ለጊዜው ግልጽ ባልነበረ ምክንያት ታግዶ ቢቆይም፣ ማኅበረ ቅዱሳን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ባደረገው ውይይት እገዳው ተነሥቶ ለእይታ በቅቷል፡፡

ተዋሕዶ የአይፎን አፕሊኬሽን ተሻሽሎ አገልገሎት መስጠት ጀመረ::

አፕሊኬሽኑ ለሁሉም የአፕል ስልኮችና አይፓዶች በሚኾን መልኩ ተሻሽሎ ቀርቧል፡፡

ትምህርቶችን፣ ጸሎታትን፣ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶችን፣ የየዕለቱን ምንባባትና የአብያተ ክርስቲያናት መረጃዎችን ይዟል፡፡

ግንቦት ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

Tewahedoappበሰሜን አሜሪካ ማእከል

በእጅ ስልክ አማካይነት ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ትምህርቶችን፣ ስብከቶችን፣ መዝሙራትንና ጸሎታትን በቀላሉ ማግኘት የሚያስችለው ተዋሕዶ የአይፎን አፕሊኬሽን ተሻሽሎ አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ተገለጠ፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የሰሜን አሜሪካ ማእከል ሙያ አገልግሎትና ዐቅም ግንባታ ክፍል ለዝግጅት ክፍላችን በላከው መረጃ እንደገለጠው፤ በማእከሉ ታቅፈው ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በሞያቸው በሚያገለግሉ አባላት ቀደም ሲል የተዘጋጀው አፕሊኬሽኑ ለምእመናን ሰፊ አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡

ከተጠቃሚዎች በተሰጡ አስተያየቶችና በባለሞያዎቹ ምክርና ጥረት ለሁሉም የዓፕል ስልኮችና አይፓዶች በሚኾን መልኩ ተሻሽሎ ቀርቧል፡፡ በአዲስ መልክ የተሸሻለው ይህ አፕሊኬሽን ከበርካታ ትምህርቶች፣ ጸሎታት፣ መዝሙራት፣ ኪነ ጥበባዊ ዝግጅቶች በተጨማሪ የኢትዮጵያን ካላንደር (በዓላትና አጽዋማት ማውጫ)፣ በየዕለቱ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባትን እንዲሁም በአሜሪካ፣ በካናዳና አውሮፓ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትን አድራሻና መሠረታዊ መረጃዎችን ያካተተ ነው፡፡

በተጨማሪም አፕሊኬሽኑ ልዩ ልዩ ዓመታዊ በዓላት እና አጽዋማት ሲደርሱ ለተጠቃሚዎቹ ማስታወሻ እንዲልክ ኾኖ ተዘጋጅቷል፡፡ የማእከሉ ሙያና ዐቅም ማጎልበቻ ክፍል ምእመናን ይህንን አፕሊኬሽን እዚህ ላይ በመጫን እንዲገለገሉ፣ ላልሰሙትም እንዲያሰሙ ሲል ያበስራል፡፡

የሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ ሰባተኛ ዓመት የዕረፍት ቀናቸው ተዘከረ

በዕለቱ ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት በሚል ርእስ በ፲፱፻፺፮ ዓ.ም ባዘጋጁት መጽሐፋቸው ላይ የዳሰሳ ጥናት ቀርቧል፡፡

ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ በስእለት መልክ ለእግዚአብሔር መሰጠታቸውን እኅታቸው ተናግረዋል፡፡

ወጣቱ ትውልድ የእርሳቸውን ፈለግ ተከትሎ ቤተ ክርስቲያንን መጠበቅ ከቻለ አባ አበራ ሕያው ናቸው እንጂ አልሞቱም ተብሏል፡፡

ግንቦት ፲፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የሊቀ ገባኤ አባ አበራ በቀለ (ስመ ጥምቀታቸው ኃይለ መስቀል) ሰባተኛ ዓመት የዕረፍት ቀናቸው መታሰቢያ ቤተሰቦቻቸው፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራሮችና አባላት በተገኙበት ግንቦት ፲፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በማኅበሩ ሕንፃ ተዘክሯል፡፡

በዕለቱ ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት በሚል ርእስ በ፲፱፻፺፮ ዓ.ም ባዘጋጁት መጽሐፋቸው ላይ የዳሰሳ ጥናት ያቀረቡት ዲያቆን አሻግሬ አምጤ እንደገለጹት አባ አበራ ባለ ፬፹፬ ገጽ በሆነው በዚህ መጽሐፋቸው መግቢያ ላይ ክርስትና የፍቅር ሃይማኖት መሆኑንና የሃይማኖታችን ታሪክ በፍቅር ተጀምሮ በፍቅር መፈጸሙን አስረድተዋል፡፡ እንደዚሁም የሰው ልጅ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ ሦስት ዐበይት ነጥቦች እንደሚያስፈልጉና እነዚህም ማመን፣ መጠመቅና ትእዛዛትን መጠበቅ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡

በትምህርተ ሃይማኖት መቅድማቸውም ሃይማኖት ከእግዚአብሔር ለሰው የተሰጠ መሆኑን አስረድተው እምነት የሁሉ ነገር መሠረት እንደሆነ በማብራራት መሠረት ሕንፃዎችን ሁሉ እንደሚሸከም እምነትም ምግባራትን ሁሉ እንደምትይዝ፣ ሕንፃ ያለመሠረት እንደማይቆም ምግባርም ያለ ሃይማኖት እንደማይጸና የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን ትምህርት ጠቅሰው አስተምረዋል፡፡

በዳሰሳ አቅራቢው እንደተብራራው መጽሐፉ በክፍል አንድ አንቀጹ ሠለስቱ ምእት በኒቅያው ጉባኤ የደነገጉትን ጸሎተ ሃይማኖት እና በጉባኤ ቍስጥንጥንያ የተሰበሰቡ ፻፶ ሊቃውንትን ውሳኔ መጽሐፍ ቅዱስንና ሊቃውንትን መሠረት በማድረግ ያብራራል፡፡ ባጠቃላይም ስለ ሃይማኖት በመመስከር ላይ እንደሚያተኩር እና ሰይጣንን ክዶ የክርስቶስ ተከታይ ስለመሆን እንደሚያትት የጥናቱ አቅራቢ ዲያቆን አሻግሬ አስረድተዋል፡፡ ክፍለ ሁለት የክርስቶስ የማዳን ሥራና ጸጋ እውን የሚሆነው ቃሉን በመስማትና ምሥጢራትን በመፈጸም መሆኑን እንደሚያስረዳ፣ ክፍል ሦስት ደግሞ ክርስቲያናዊ ሕይወትና ምግባር በእምነት፣ በተስፋና በፍቅር መገለጡ ተብራርቶበታል፡፡

ምእመናን የመዳን ተስፋችን እውን እንዲሆን በሥስቱ አርእስተ ሃይማኖት ማለትም በእግዚአብሔር ፍቅር፣ በክርስቶስ ጸጋ እና በመንፈስ ቅዱስ ኅብረትና ረድኤት መመሥረት እንደሚገባን ይናገራል፡፡ በተጨማሪም አባ አበራ ፍቅርን አንደኛ እግዚአብሔር ለሰው ያለው ፍቅር፣ ሁለተኛ ሰው ለእግዚአብሔር ያለው ፍቅር እና ሦስተኛ ትእዛዛቱን መጠበቅ (አምላክህንና ባልንጀራህን ውደድ የሚሉትን) በማለት በሦስት ክፍል አቅርበውበታል፡፡ ይህም የአባ አበራ መጽሐፍ በዚህ ዓመት በማኅበረ ቅዱሳን እንደገና ታትሞ ገበያ ላይ ውሏል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም በሕይወት በነበሩበት ወቅት ያስተማሩት ትምህርትና ያደረጉት ንግግር በቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩምና በዲያቆን ሙሉዓለም ካሣ አስተባባሪነት በድምፅና ምስል ተቀናብሮ ለመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች የቀረበ ሲሆን ቀጥሎም ቤተሰቦቻቸውና በቅርብ የሚያውቋቸው ወዳጅ ዘመዶቻቸውና የመንፈስ ልጆቻቸው አባ አበራ ፍቅርን፣ መንፈሳዊነትን፣ ደግነትን፣ ቅንነትን እና ትሕትናን የተላበሱ፣ ከስስትና ከፍቅረ ንዋይ የራቁ አባት እንደነበሩ መስክረውላቸዋል፡፡

ታናሽ እኅታቸው ወ/ሮ ጸዳለ በቀለ አባ አበራ ሕፃን እያሉ ጥቅምት ፳፰ ቀን ወላጅ እናታቸው አዝለዋቸው በመንገድ ሲጓዙ በዘመኑ ታዳጊ ወንዶች ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ሽፍቶች ባገኗቸው ጊዜ እናታቸው አባቴ አማኑኤል ሆይ ልጄን ከነዚህ ሽፍቶች ብታድንልኝ የአንተ አገልጋይ ይሁን ብለው በስእለት መልክ ለእግዚአብሔር ሰጥተዋቸው ነበር፤ ይህም ሕይወታቸውን በሙሉ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት እንዲኖሩ አድርጓቸዋል ብለዋል፡፡

መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁንም ከሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ጋር በመሆን በስብከተ ወንጌልም በአስተዳደርም ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሲያገለግሉ መኖራቸውን አውስተው በተለይ ለወላጅ እናታቸው ልዩ ፍቅርና አክብሮት እንደነበራቸው ተናግረዋል፡፡ አክለውም የጻድቅ ሰው መታሰቢያ ለዘለዓለም ይኖራል የሚለውን ኃይለ ቃል መነሻ በማድረግ ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ራሳቸውን መሥዋዕት አድርገውና ልዩ ልዩ ፈተናዎችን ተቋቁመው ያሰቡትን መንፈሳዊ ዕቅድ ሁሉ አሳክተው ያለፉ አባት መሆናቸውን ጠቅሰው ወጣቱ ትውልድ የእርሳቸውን ፈለግ ተከትሎ ቤተ ክርስቲያንን መጠበቅ ከቻለ አባ አበራ ሕያው ናቸው እንጂ ሞቱ አይባልም ሲሉ መልእክታቸውን አጠቃለዋል፡፡

ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ በበኩላቸው አባ አበራ በአገር ውስጥም፣ ከአገር ውጪም በሚገኙ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት እየተዘዋወሩ ብዙ ዕውቀት መቅሰማቸውን ገልጸው፣ አክለውም ለሚሰማቸው ብቻ ሳይሆን ለሚመለከተቻውም አስተማሪ ሕይወት እንደነበራቸው፣ በሕይወት ከኖሩበት ጊዜ በላይ ካረፉ በኋላ ለብዙ ሰዎች ምሳሌ እንደሚሆኑና ሁሉም ሊማርባቸውና ሊያስታውሳቸው እንደሚገባ ገልጸው እኒህን አባት ለመዘከር ያመች ዘንድ በስማቸው የሚሰየም አንድ ስኮላርሺፕ ቢኖረን መልካም ነውና ሁላችንም ብናስብበት ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

በተጨማሪም ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ፣ ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ፣ አቶ ኤርምያስ ዓለሙ እና አቶ ሙሉጌታ ምትኩ ስለ አባ አበራ መንፈሳዊ ሕይወት ተመሳሳይ አሳብና አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

ከጽርሐ ጽዮን ማኅበር አባላት አንዷ የሆኑት ወ/ሮ ሙሉእመቤት በላቸውም፡- ክርስትና ማለት ራስን መካድ መሆኑን የተማርሁት ከአባ አበራ ነው፡፡ ሁላችንም አንረሳቸውም፡፡ እኛ ጊዜያችን እያለቀ ነው፡፡ እናንተ ወጣቶች ትግሉን እንደእርሳቸው ታገሉት፤ ትጥቁን እንደእርሳቸው ታጠቁት፡፡ የአባ አበራን ፈለግ ተከትላችሁ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ የሚመጣባችሁን ሁሉ ፈተና በጸጋ ተቀብላችሁ ወንጌልን ስበኩ ሲሉ እናታዊ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

በመጨረሻም በአባቶች ምክርና ጸሎተ ቡራኬ በስማቸው የተዘጋጀው ጸበል ጸሪቅ ከቀረበ በኋላ ከምሽቱ 2፡30 ገደማ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

ክቡር ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ ከአባታቸው ከግራ አዝማች በቀለ መኩሪያ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ በሸዋምየለሽ ድፋባቸው ከዐዲስ አበባ በስተምሥራቅ አቅጣጫ የረር አካባቢ በሚገኘው ልዩ ስሙ ቡኢ በተባለ ሥፍራ በዕለተ ስቅለት ሚያዝያ ፪ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም ተወልደው በ፸፫ ዓመታቸው ሚያዝያ ፭ ቀን ፳፻፩ ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው ይታወሳል፡፡

ለአርባ አምስት ዓመታት ያህል ቅድስት ቤተ ክርስቲያንንና ሀገራቸውን በፍጹም ፍቅር ሲያገለግሉ የቆዩት ሊቀ ጉባኤ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት ካበረከቱት ከፍተኛ አተዋጽዖ በተጨማሪ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነውን በውኃ እንፋሎት የሚንቀሳቀስ መኪና የሠሩ ጥበበኛም ነበሩ፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም እኒህ ታላቅ አባት ለቤተ ክርስቲያንና ለአገር ያበረከቱትን አስተዋጽዖ ግምት ውስጥ በማስገባት የሰባተኛ ዓመት የዕረፍት ቀናቸው እንዲዘከር አድርጓል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን አዘጋጅነት ሁለት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀረቡ

ግንቦት ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

ዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በጸሎተ ሃይማኖት *ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ* የሚለው ንባብ *በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሆነ* ተብሎ መስተካከል አለበት ተብሏል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዕቃ ቤትና በቅዱሳት መካናት አማካኝነት የቅርስ ቤተ መዛግብት እንደሆነች ተገልጿል፡፡

ወጣቱ ትውልድ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የመጠበቅና የማስጠበቅ ኃላፊነት እንዳለበት ተነግሯል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማዕከል አዘጋጅነት *የአርዮስና መንፈቀ አርዮሳውያን ተጽዕኖ በቤተ ክርስቲያን ላይ* እና *የቤተ ክርስቲያን ተንቀሳቃሽ ቅርሶችን የመጠበቅ ሒደት በአድባራትና ገዳማት* በሚሉ ዐበይት አርእስት የሚመለከታቸው ምሁራንና ተሳታፊ ምእመናን በተገኙበት ቅዳሜ ግንቦት ፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በማኅበሩ አዳራሽ ሁለት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡

*የአርዮስና መንፈቀ አርዮሳውያን ተጽዕኖ በቤተ ክርስቲያን ላይ* በሚለው ርእሰ ጉዳይ ላይ ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡት ቀሲስ ዶክተር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል ሲሆኑ በጥናታቸውም የአርዮስ የኑፋቄ ትምህርት የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት የሚቃወም መሆኑን ጠቅሰው አርዮስና ኑፋቄዉ በ፫፻፲፰ ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት በ፫፳፭ ዓ.ም በኒቅያ በተደረገው ጉባኤ ቢወገዝም ትምህርቱ ግን እስከ ዛሬ ድረስ ቤተ ክርስቲያንን እየተፈታተናት እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡

አያይዘውም በጉባኤ ኒቅያ በተወሰነው የሃይማኖት መሠረት (ጸሎተ ሃይማኖት) ውስጥ *ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ* የሚለው የግእዝ ንባብ *በመለኮቱ ከአብ ጋር የሚተካከል* ተብሎ መተርጐሙ ትክክል አለመሆኑን መረጃ በማስደገፍ ገልጸው ይህ ሐረግ *በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሆነ* ተብሎ መስተካከል እንዳለበትና የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትም ይህንን ምሥጢር ለምእመናን ማስረዳት እንደሚገባቸው ተናግረዋል፡፡

*የቤተ ክርስቲያን ተንቀሳቃሽ ቅርሶችን የመጠበቅ ሒደት በአድባራትና ገዳማት* በሚለው ርእስ ላይ ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡት ዲያቆን አለባቸው በላይ ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዕቃ ቤትና በቅዱሳት መካናት አማካኝነት በቅርስ ቤተ መዛግብትነት የምትገኝ መሆኗን ጠቅሰው ወጥ የሆነ መመሪያና ዕቅድ አለመኖር፣ የቅርስ አጠባበቅና ክብካቤ ችግር፣ ወዘተ የመሰሉ ተግዳሮቶች እንዳሉባት በጥናታቸው ጠቁመዋል፡፡

በጥናታቸው ማጠቃለያም ቤተ ክርስቲያናችን የእምቅ ተንቀሳቃሽ ቅርሶች ባለቤት መሆኗን ገልጸው የዕቅድና ወጥ መመሪያ ዝግጅት፣ የአስተዳደርና የዓቅም ግንባታ ሥራ፣ ለምእመናን ስለቅርሶች ግንዛቤ መስጠትና የባለቤትነት ስሜት እንዲያድርባቸው ማድረግ፣ ወዘተ የመሰሉ ተግባራት ለቅርስ አጠባበቅ ችግር መፍትሔ ሊሆኑ እንደሚችሉ በዝርዝር አስረድተው *ሁላችንም ይህንን በመረዳትና የተጀመሩ መልካም አጋጣሚዎችን በመጠቀም ለወደፊት የተሻለ መሥራት ይጠበቅብናል* ብለዋል፡፡

በዐውደ ጥናቱ ላይ ከተገኙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከል አንዱ የሆኑት መልአከ ታቦር ተሾመ ዘርይሁን አስተያየት በሰጡበት ወቅት፣ *ትልቁ ነገር የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች መመለስ ነው፤ ማኅበረ ቅዱሳን መምህራንን በመጋበዝ እንደዚህ ዓይነት ጥናታዊ ውይይት ማካሔዱ ለአባቶች ተገዢ መሆኑን አመላካች ተግባር ነው* ብለዋል፡፡ በተጨማሪም *ቤተ ክርስቲያናችን፣ Living Church of Living Faith and Ever Growing Church – ዘለዓለማዊት፣ የዘለዓለማዊው ሃይማኖት መሪ የሆነች እና ዘለዓለም የምታድግ ናት፤ ስለሆነም ወጣቱ ትውልድ የዚህችን ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ የመጠበቅና የማስጠበቅ ኃላፊነት አለበት* ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በመጨረሻም በሁለቱም ጥናቶች ላይ ከተሳታፊዎች ለተነሡ ጥያቄዎች በአቅራቢዎቹ ምላሽ ተሰጥቶ ሲያበቃ የውይይቱ መሪ ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ የማጠቃለያ ንግግር ካደረጉ በኋላ በአባቶች ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡