‹‹ጾም የነፍስን ቊስል ትፈውሳለች›› (ቅዱስ ያሬድ)  

                                                                                              በብዙአየሁ ጀምበሬ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከሚከናወኑ ዓበይት ክርስቲያናዊ ምግባራት መካከል ጾም አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ ጾም ‹‹ጾመ››  ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ተከለከለ፤ተወ፤ታቀበ፤ታረመ ማለት ነው፡፡ በሱርስትና በዕብራይስጥ ቋንቋዎች ‹‹ጻም›› ሲባል በአረብኛ ቋንቋ ደግሞ ‹‹ጻመ›› በመባል ይታወቃል፡፡ (ጾም እና ምጽዋት ገጽ ፰)

የቤተ ክርስቲያናችን የሕግና የሥርዓት መጽሐፍ የሆነው ፍትሐ ነገሥት ደግሞ በአንቀጽ ፲፭ ላይ ‹‹ጾምሰ ተከልኦተ ብእሲ እመብልዕ በጊዜ ዕውቅ በውስተ ሕግ፤ ጾምስ በታወቀው ዕለት፤በታወቀው ሰዓት ከምግብ መከልከል ነው›› በማለት ጾምን በዚህ መልኩ ይተረጕመዋል፡፡

እንግዲህ በሃይማኖታዊ ትርጉሙ ጾም ማለት ራስን ከእህል፤ከውኃ ብሎም አምላካችን እግዚአብሔር ከሚጠላቸው እኩይ ምግባራት ሁሉ ራስን በመከልከል የሥጋን ፈቃድ ለነፍስ በማስገዛት መቆየት ማለት ነው፡፡‹በዚያም ዐርባ ቀንና ዐርባ ሌሊት በእግዚአብሔር ፊት ነበረ፤ እንጀራም አልበላም፤ ውኃም አልጠጣም፤ በጽላቱም ዐሥሩን የቃል ኪዳን ቃሎች ጻፈ።›› (ዘፀ.፴፬፥፳፰) ሁለቱን የድንጋይ ጽላት፥ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር የተማማለባቸውን የቃል ኪዳን ጽላት፥ እቀበል ዘንድ ወደ ተራራ በወጣሁ ጊዜ፥ በተራራው ዐርባ ቀንና ዐርባ ሌሊት ተቀምጬ ነበር እንጀራ አልበላሁም፥ ውኃም አልጠጣሁም›› ተብሎ እንደተጻፈ። (ዘዳ.፱፥፱)

ከዚህም ባሻገር ጾም ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹ጉልበቶቼ በጾም ደከሙ፤ ሥጋዬም ቅባት በማጣት ከሳ›› በማለት እንደናገረው በዚህ የጾም ወቅት ከጥሉላት መባልዕት ወይም የእንስሳት ተዋጽኦ የሚባሉትን ማለትም እንደ ሥጋ፤ወተት፤ዕንቁላል፤ዐይብ፤ ቅቤ ወዘተ ከመሳሰሉት ቅባትነት ካላቸው ምግቦችና ከሚያሰክሩ መጠጦች ራስን መከልከል መከልከል ያስፈልጋል፡፡ (መዝ ፻፰፥፳፬)

ነቢዩ ዳንኤልም በትንቢት መጽሐፉ ስለ መባልዕት ጥሉላት እንዲህ ብሏል‹‹በዚያም ወራት እኔም ዳንኤል ሦስት ሳምንት ሙሉ ሳዝን ነበርሁ፡፡ ማለፊያ እንጀራም አልበላሁም፤ሥጋና የወይን ጠጅም በአፌ አልገባም››(ዳን.፲፥፪-፫) ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ፤‹‹ሌላ ልዩ ትምህርት አታምጡ፤ ልባችሁ በመብል ያይደለ በጸጋ ቢጸና ይበልጣናል፤ በዚያ ይሄዱ የነበሩ እነዚያ አልተጠቀሙምና፡፡›› ለዕብራውያን ሰዎች በጻፈው መልእክቱ ላይ ወንጌል ሥጋን የሚያደልበውን መብልን እንደማትሰብክና በመብል ብቻ ልባችንን ማጽናት እንደሌለብን ገልጿል (ዕብ. ፲፫፥፱)

የክርስትናችን መሠረት ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ስለ መብልና መጠጥ ከንቱነት እንዲህ በማለት አስተምሮናል፡፡ ‹‹ራሳችሁን ጠብቁ፤ በመብልና በመጠጥ፤በመቀማጠልና የዓለምን ኑሮ በማሰብ ልባችሁን አታደንድኑ፤ ያቺ ቀንም በድንገት ትደርስባችኋለች፡፡››(ሉቃ.፳፩፥፴፬)

የሰው ልጅ አብዝቶ በበላና በጠጣ ጊዜ ከአእምሮው በመውጣት እኩይ ተግባራትን ሊፈጽም ይችላል፡፡ ጥጋብና ስካር የኅሊናን አቅል በማሳጣት ለኃጢአት ይዳርጋሉ፡፡ ‹‹በቀን እንደሚሆን በጽድቅ ሥራ እንመላለስ፤በዘፈንና በስካር፤በዝሙትና በመዳራት አይሁን፤በክርክርና በቅናት አይሁን››(ሮሜ ፲፫፥፲፫)  ስካር ከእግዚአብሔር መንግሥት ያርቃል ‹‹ምቀኝነት፤መግደል፤ስካር፤ዘፋኝነት፤ይህንም የሚመስል ነው፡፡አስቀድሜም እንደ ነገርኋችሁ ይህን የሚያደርግ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም፡፡›› (ገላ.፭፥፳፩) ስካር የሰው አዕምሮን ያጠፋል፡፡(ሆሴ.፬፥፲፩)

ከማንኛውም ክፉ ነገሮች ሁሉ መጠበቅ፤ራስን መግዛት እና መቈጣጠር፤ በንስሓና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር መቅረብ፤ እርሱንም ደጅ መጥናትና ለኃጢአታችን ሥርየትን መለምን ማለት ነው፡፡ ይህንንም ስናደርግ ነቢዩ ዳንኤል ‹‹ማቅ ለብሼ በአመድም ላይ ሆኜ ስጾም እጸልይና እለምን ዘንድ ፊቴን ወደ ጌታ ወደ አምላክ አቀናሁ።›› በማለት እንደተናገረው አምላካችን እግዚአብሔር የሚወደውን የተቀደሰውን ጾም በመጾም ለነፍሳችን መልካም ዋጋን እናገኝ ዘንድ ከሥጋዊ ምቾትና ቅንጦት በመራቅና ራሳችንን ዝቅ በማድረግ ልንጾም ይገባል፡፡(ዳን.፱፥፫)

እንግዲህ ጾም ከመንፈሳዊ ተጋድሎ አንዱ ነው፤ ለሥጋም መንፈሳዊ ልጓም ነው፡፡ አንድ ክርስቲያን ፈቃደ ሥጋውን እየገታ ነፍሱን የሚያለመልምበት መንፈሳዊ ስንቅ ነው፡፡ ‹‹ጾም ቊስለ ነፍስን የምትፈውስ፤ኃይለ ፍትወትን የምታደክም፤ የበጎ ምግባራት ሁሉ መጀመሪያ፤ከእግዚአብሔር ጸጋን የምታሰጥ፤የወንጌል ሥራ መጀመሪያ፤የጽሙዳን ክብራቸው፤የደናግል የንጽሕና ጌጣቸው፤ የዕንባ መፍለቂያዋ፤ አርምሞን (ዝምታን) የምታስተምር፤ ለበጎ ሥራ ሁሉ የምታነቃቃ፤ ሰውነትን በእግዚአብሔር ፊት በማዋረድ ትሕትናን ገንዘብ ለማድረግ የምትረዳ መድኃኒተ ነፍስ ናት፡፡››(ማር ይስሐቅ አንቀጽ ፬ ምዕ. ፮)

እግዚአብሔር አምላክ ሰውን በአምሳሉና በአርአያው ከፈጠረው በኋላ ከማእከለ ምድር (ኤልዳ) ወደ ኤዶም ገነት በመውሰድ ክፉውንና መልካሙን የሚለይበት አስተዋይ ኅሊና ባለቤት አድርጎ አኖረው፡፡ (ኩፋሌ ፬፥፱) በዚህም መሠረት የሰው ልጅ ‹‹ከዚህ አትብላ›› በሚል አምላካዊ ቃል ጾም ኆኅተ ጽድቅ የጽድቅ በር ሆና የተሰጠች የመጀመሪያቱ ሕግ ናት፡፡ ጾም ከምግባረ ሃይማኖት ዋነኛው ነው፤ይህም ለአንድ ክርስቲያን በሕይወት ዘመኑ ሁሉ የማይለየው ምግባር ነው፡፡ ጾም የሰው ልጅ ለአምላኩ ለልዑል እግዚአብሔር ያለውን ፍቅር የሚገልጥበት፤መንፈሳዊ ተጋድሎዎችን የሚያከናውንበት፤ስለራሱና ስለወገኖቹ ኃጢአት የሚያዝንበት፤ የሚያለቅስበትና ወደ ንስሓ የሚመለስበት ታላቅ ሥርዓት ነው፡፡

የጾም አስፈላጊነት በክርስትና ሕይወት እጅግ የጎላ ነው፡፡ በመሆኑም በጾም ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛትና ከሥጋዊ ከንቱ ኃጢአት ለመራቅ ይረዳናል፡፡ ሥጋ በምግብ ሲደነድን ለፍትወትና ለተለያዩ ሥጋዊ ኃጢአቶች ቅርብ ይሆናል፡፡ የሥጋ ፍላጎት በቀዘቀዘ ቊጥር ነፍስ ትለመልማለች፤ ለአምላክ ሕግና ትእዛዛት ሁሉ ተገዢ ትሆናለች፡፡ ማኅሌታዊ ቅዱስ ያሬድ  ስለ ጾም እንዲህ ብሏል፤‹‹ጾም ትፌውስ ቊስለ ነፍስ፤ ወታጸምም ኵሎ ፍትወታተ ዘሥጋ ፤ ትሜህሮሙ ጽሙና ለወራዙት፤ ጾም የነፍስን ቊስል ትፈውሳለች፤የሥጋን ፍትወታት ሁሉ ታጠፋለች፤ ለወጣቶችም ትሕትናን ታስተምራለች፡፡››

ለክርስቲያን የነፍስን ሥራ መሥራት  ከእግዚአብሔር ጋር መተባባርና አንድ ወገን እንደመሆን ያለ ምግባር ነው፡፡‹‹አሁንም ወንድሞቻችን በዚህ በሥጋችን ሳለን ፈቃደ ሥጋችንን ልንሠራ አይገባንም፡፡ ፈቃደ ሥጋቸውን የሚሠሩ ሰዎች ሁሉ በወዲሁ አለን ሲሉ በወዲያው ምውታን ናቸውና፡፡ ፈቃደ ሥጋችሁንስ በፈቃደ ነፍሳችሁ ድል ከነሣችሁት ለዘለዓለሙ ሕያዋን ትሆናላችሁ፡፡ ፈቃደ ነፍስን የሚሠሩ ሰዎች ሁሉ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና፡፡›› (ሮሜ ፰፥፲፪-፲፬) እንዲል፡፡

ጾም የኃጢአት ሥርየትን ለማግኘትና ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ ይረዳል፡፡ አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ወደ እርሱ በጾምና በጸሎት እንድንመለስ በነቢያት አድሮ አሥተምሮናል፡፡ ‹‹በፍጹም ልባችሁ፤በጾምም፤በልቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ፡፡››(ኢዩ.፪፥፲፪)

ጾም በጸጸት መንፈስ ሆነን በንጹሕ ልባችን ወደ ልዑል እግዚአብሔር በንስሓ እንድንመለስ ይረዳናል፡፡ ‹‹ወሀበነ ጾመ ለንስሓ በዘይሰረይ ኃጢአት፤ ኃጢአት የሚሠረይበትን ይቅር የሚባልበትን ጾምን ሰጠን›› ጾም በደልን አምኖና ጥፋትን ተቀብሎ በፍጹም ትሕትና ወደ እግዚአብሔር በመቅረብ በድያለሁ ማረኝ ይቅር በለኝ በማለት የንስሓ ዕንባን በማንባት ከእግዚአብሔር ምሕረትን የምናገኝበት ምግባር ነው፡፡

በመጽሐፍ «የእስራኤልም ልጆች ሁሉ ሕዝቡም ሁሉ ወጥተው ወደ ቤቴል መጡ፤ አለቀሱም፤ በዚያም በእግዚአብሔር ፊት ተቀመጡ፤ በዚያም ቀን እስከ ማታ ድረስ ጾሙ፤ በእግዚአብሔር ፊት የሚቃጠል መሥዋዕትንና የደኅንነት መሥዋዕትን አቀረቡ›› እንደዚሁም ፤«ወደ መሴፋ ተሰበሰቡ፤ ውኃም ቀድተው በእግዚአብሔር ፊት በምድር ላይ አፈሰሱ፤ በዚያም ቀን ጾሙ፤ በዚያም፤ በእግዚአብሔር ፊት በድለናል አሉ፤ሳሙኤልም በእስራኤል ልጆች ላይ በመሴፋ ፈረደ›› (መሳ.፳፥፳፮፤፩ኛሳሙ.፯፥፮)

በቤተክርስቲያናችን ሥርዓተ ጾም መሠረት ጾምን የፈቃድ ጾም (የግል ጾም) እና የዐዋጅ ጾም (የሕግ ጾም) በማለት በሁለት ከፍለን የምንመለከታቸው ሲሆን የግል ጾም የምንለው ምእመናን ለንስሓ በግል የሚጾሙትን የፈቃድ ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም ምእመናን በምክረ ካህናት ወይም ከንስሓ አባታቸው ጋር በመመካከርና ቀኖናን በመቀበል የሚጾሙት ጾም ሲሆን አንዱ ሲጾም ሌላው ማወቅ የለበትም፡፡ የዐዋጅ አጽዋማት የምንላቸው ደግሞ ዕድሜያቸው ሰባት ዓመት ከሞላቸው ሕፃናት ጀምሮ መላው ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን በኅብረት በግልጽ የሚጾሟቸው አጽዋማት ናቸው፡፡

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

“ስለ ወንጌል እተጋለሁ” በሚል ርእስ የተዘጋጀው ዐውደ ርእይ ተከፈተ

                                                                                                                በእንዳለ ደምስስ

በኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን በሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን “ስለ ወንጌል እተጋለሁ” በሚል ርእስ የተዘጋጀው ዐውደ ርእይ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣የማኅበሩ አባላትና ምእመናን በተገኙበት ሰኔ ፲፬ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ስድስት ኪሎ በሚገኘው የስብሰባ ማእከል ተከፈተ፡፡

ዐውደ ርእዩ ከሰኔ ፲፬ – ፲፮ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም የሚቆይ ሲሆን፣ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ እና ኬንያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የአውስትራልያና የኒውዚላንድ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ጸሎተ ወንጌል በማድረስ በይፋ ከፍተውታል፡፡

በዐውደ ርእዩ ክፍል አንድ “ቅዱስ ወንጌል ለሁሉ” በሚል የቀረበ ሲሆን፤ ቤተ ክርስቲያን ማን ናት?የቤተ ክርስቲያን ተቀዳሚ ዓላማ፣ ወንጌል ማስፋፋት ነው፣ የወንጌል መስፋፋት መገለጫዎች፣ እንዲሁም ሌሎች ጉዳዮች ተዳሰውበታል፡፡

የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት በተለይም የግብጽ፣የሕንድና የሩሲያ ተሞክሮ በክፍል ሁለት ቀርቧል፡፡አማኞቻቸውን ማጽናት መቻላቸው፣ ከተከላካይት አልፈው የተሻለ ተቋማዊ አቅም መፍጠር መቻላቸው ዛሬ ለደረሱበት አስተዋጽኦ ማድረጉ እንደ ተሞክሮ መታየት እንደሚገባው ተገልጿል፡፡እንደ ምሳሌም በመገናኝ ብዙኃን  ደረጃ ግብጽ ፲፬ የቴሌቪዥን፣ ፲፻፬፻ ድረ ገጾች፣በሕንድ ፰፣በሩሲያ ፭፻ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች እንዳላቸው የተገለጸ ሲሆን ቤተ ክርስቲያናችን በዚህ ዘርፍ ብዙ መሥራት እንደሚጠበቅባት ያሳየ ነበር፡፡

በዚህም መሠረት ከኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ተሞክሮ አንጻር ከእኛ ምን ይጠበቃል? በሚለው ትእይንት የተጀመሩት የቴሌቪዥንና የድረ ገጽ አገልግሎቶችን ማጠናከርና ማስፋፋት፣ በስብከተ ወንጌል ላይ የሚሠሩ አካላትን ማጠናከር፣ የአስኳላ ትምህርት ቤቶችን በስፋት መከፈትና ትውልድን ማነጽ፣እንዲሁም ሌሎች በስብከተ ወንጌል ዙሪያ የተቀናጀ አገልግሎት ለማበርከት ጥረት ማድረግ እንደሚገባ በትዕይንቱ ለመዳሰስ ተሞክሯል፡፡

“ቤተ ክርስቲያን በመጪው ዘመን ምን መሆን አለባት” የሚለው ትዕይንት ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት የሚያስችሉ መልካም ዕድሎችን፣ ፈተናዎች እንዲሁም መፍትሔ ሰጭ ጉዳዮችን የዳሰሰ ነበር፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በጠረፋማ አካባቢዎች የሚያካሔደውን የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በተመለከተም በደቡብ ኦሞ፣ የቤንች ማጂ እና የመተከል አህጉረ ስብከት እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎች እንደምሳሌ ቀርበዋል፡፡ ከአንድ መቶ ሰባ ሺሕ በላይ አዳዲስ አማንያንን ማስጠመቅ እንደተቻለም ተገልጿል፡፡

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የአውስትራሊያ እና የኒውዚላንድ አህጉረ ስብክት ሊቀ ጳጳስ ዐውደ ርእዩን ከተመለከቱ በኋላ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት መልእክትም “ወንጌል የሚለው ሐሳብ ሰውን ማዳን ነው፡፡ አባላት መሰብሰብ፣ ማብዛት ማለት አይደለም፡፡የሰውን ልብ ማግኘት፣ የእግዚአብሔርንና የሰውን ልብ ማያያዝ፣ በሌላ መልኩ ማዳን ነው፡፡” ብለዋል፡፡

ስለ ዐውደ ርእዩ ብጹዓን አባቶች አስተያየታቸውን በጹሑፍ ሲያስቀምጡ

ብፁዕነታቸው ኦርቶዶክሳዊነት ላይ በማተኮር “ኦርቶዶክሳዊነት ዝም ብሎ በአንድ ጊዜ የሚጠፋ ወይም በአንድ ጊዜ የተገኘ ነገር አይደለም፡፡ ክርስትና ከተመሠረተበት ጊዜ አንስቶ እስካለንበት ጊዜ ድረስ በመንፈሳዊ  ሐረገ ትውልድ ተያይዞ የመጣ ዕንቊ የሆነ ነገር ነው፡፡ ይህንን ትውልዱ መቀበል ከቻለ ዓለምን ማዳን ይችላል፡፡” ብለዋል፡፡

ዐውደ ርእዩ እሰከ ሰኔ ፲፮ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም የሚቆይ ሲሆን፣በየዕለቱ ትምህርተ ወንጌል፣ ጥናታዊ ጽሑፎች፣ ዶክመንተሪ ፊልሞች ይቀርባሉ፡፡

በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

የተከበራችሁ አንባብያን በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን ያለችበትን ሁኔታና በየአካባቢው እና በየክልሉ በቤተ ክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየተፈጸመ ያለውን ጥቃት አስመልክቶ ክፍል አንድን  ማቅረባችን ይታወቃል ክፍል ሁለትን እነሆ ብለናል፡፡

ምዕራባውያንና የእነሱ ጉዳይ አስፈጻሚዎች ቤተ ክርስቲያንን ለማዳከም ይጠቅመናል ብለው ያሰቡትን ሁሉ ፈጽመዋል፡፡ የአሳባቸው አቀንቃኝ ኢትዮጵያዊ “ፈረንጆችንም” አግኝተዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም ሊቃውንቷንም ለመተቸት ያለ ስማቸው ስም ያለ ግብራቸው ግብር በመስጠት ጥላቻውን በመግለጽ አልሜዳ የተባለ ሚሲዮናዊ የፈጠራ ታሪክ ጽፏል፡፡ የእሱን ጥላቻ እየጠቀሱ ቤተ ክርስቲያንን የሚተቹት የግብር ልጆቹ ናቸው፡፡ የእሱን ጥፋት ዳንኤል ክብረት «አልሜዳ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን አምርሮ የሚጠላ ኋላ ቀርና በኑፋቄ የተሞላች አድርጎ የሚፈርጅ ኢየሱሳዊ /ሚስዮናዊ/ ነበር፡፡ በጽሑፎቹ ላይ ይህን ነው ሲያንጸባርቅ የኖረው፡፡ ከዚህ ጠባዩ አንጻርም አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ቢተች የሚጠበቅ እንጂ የሚገርም አይደለም» (ዳንኤል፣ ፳፻፲፩፣፫‐፬) በማለት ገልጦታል፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም ሆነ ተሐድሶአውያን አቡነ ተክለ ሃይማኖትን የሚተቹት የእሱን አሳብ እየጠቀሱ ነው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን መንቀፍና ያለ ግብራቸው ግብር መስጠት ቤተ ክርስቲያንን ለማዳከም ይጠቅመናል ብለው ያስባሉ፡፡ ለኋለኞቹ የቤተ ክርስቲያን ተችዎች ጀማሪና ፊታውራሪያቸው አልሜዳ ነው፡፡ የውጭ ጸሐፊዎች የኢትዮጵያውያንን አእምሮ በመበረዝ ቤተ ክርስቲያን ላይ ትችት እንዲያዘንቡ ምክንያት መሆናቸውን ከአልሜዳ ጽሑፍ መረዳት ይቻላል፡፡ ለመነሻ ያህል ይህን ካቀረብን በየዘርፉ የደረሱትን ችግሮች እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡

ሀ. የቤተ ክርስቲያን መቃጠል፡- በየዘመናቱ፣ በየቦታው አብያተ ክርስቲያናት በአክራሪ ሙስሊሞች፣ በግለኝነት በታወሩ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታዮችና በአጽራረ ቤተ ክርስቲያን ሲቃጠሉ ቆይተዋል፡፡ ይህን የሚያደርጉት የግል ጥላቻና የተለየ ፍላጎት ያላቸው ግለሰቦች ወይም ቡድኖች እንጂ ሁሉም የሌሎች እምነቶች ተከታዮች እንዳልሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ስትቃጠል አብረው የሚያዝኑና የሚያለቅሱ፣ ክርስቲያኖች ሲሳደዱና መከራ ሲደርስባቸው በቤታቸው የሚሸሽጉ ብሎም አብረው መከራ የሚቀበሉ፣ ክርስቲያኖች ኃይላቸውን እያሰባሰቡ አቅማቸውን እያጠናከሩ መልሰው ለመገንባት ሲደክሙ ከገንዘብ እስከ አሳብ ድጋፍ የሚያደርጉ የሌላ እምነት ተከታዮች አሁንም በየቦታው መኖራቸው የሚካድ አይደለም፡፡ በዘመናችንም ክርስቲያኖች በጥብዐት መከራውን ተቋቁመው ክርስትና በሞት፣ በስድት፣ በእሳትና በመከራ የማይፈታ መሆኑን አስመስክረዋል፡፡ በዚሁ አንጻር ግን በመገናኛ ብዙኃን በተለያዩ ቦታዎች የሚቃጠሉትን አብያተ ክርስቲያናት ያልታወቁ ግለሰቦች ያቃጠሏቸው እንደሆነ ቢነገርም ታስቦበት፣ ተጠንቶ፣ ምን ለማግኘትና ምን መልስ ለመስጠት አስቀድሞ እየታሰበ ቃጠሎው መፈጸሙን የሚጠቁሙ ማሳያዎች አሉ፡፡ ፲፱፻፺፫ዓ.ም ሚያዝያ ፲፪ ቀን በአርሲ ሀገረ ስብከት ኮፈሌ ወረዳ ጉች ቀበሌ ገበሬ ማኅበር የሚገኘው የመድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን በአክራሪ እስላሞች ለመቃጠል የቻለው ከተማ ላይ ሊያደርሱት የነበረው አደጋ በመከላከያ ሠሪዊትና በፖሊስ ስለተደናቀፈባቸው ነው፡፡ ገጠር በመግባት የክርስቲያኖችን ቤት እየመረጡ ማቃጠላቸው የታቀደና የተደራጀ ጥቃት መሆኑን ለመረዳት ይቻላል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ሃይማኖታዊ ትንኮሳ ከትላንት እስከ ዛሬ መቀጠሉ ታስቦበት እየተሠራ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ ይህ ድርጊት በአንድ በኩል አጥፊዎች ልብ እንዲገዙ፣ በሌላ በኩል ደግሞ መንግሥት ከትላንት እስከ ዛሬ እየደረሰ ያለውን ጥፋት በመረዳት ለእምነት ቤቶችና ለክርስቲያኖች ልዩ ጥበቃ እንዲያደርግ ሊያነቁ፣ ምእመናንም ራሳቸውን እንዲጠብቁ፣ እንዲደራጁና አዲስ ነገር ሲገጥማቸው ለፍትሕ አካላት እንዲያቀርቡ ትምህርት ሊሆን ይገባል፡፡ ክርስቲያኖች የሚማሩት ከመከራ፣ ቅድስናቸው የሚገለጠው በፈተና መሆኑ የተጻፈ፣ ክርስቲያኖች በተግባር ፈጽመው ያሳዩት ሕይወት ነው፡፡

በጅማ ሀገረ ስብከት ከመስከረም ፲፮ እስከ ጥቅምት ፬ ቀን ፲፱፻፺፱ ዓ.ም ጨጉ ቅዱስ ገብርኤል፣ ቦሬ ቅዱስ ገብርኤልና በሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አብያተ ክርስቲያናት በአክራሪ እስላሞች ተቃጥለዋል፡፡ ንዋያተ ቅድሳት ተዘርፈዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በጅማ፣ በምዕራብ በወለጋና በኢሉባቡር ከ፲፫ በላይ አብያተ ክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት ተዘርፈዋል፡፡ ኅዳር ፮ ቀን ፲፱፻፺፰ዓ.ም በአርሲ ሀገረ ስብከት በኮፈሌ ወረዳ የምትገኘው የአይሻ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ፀረ ክርስትና አቋም ባለው ቡድን ተቃጥላለች፡፡ አገልጋይ ካህናት በቤተ መቅደስ ውስጥ ታርደዋል፣ አሥር ክርስቲያኖች በገጀራ ተገድለው፣ አብያተ ክርስቲያናትና የክርስቲያኖች መኖሪያ ቤቶች ተቃጥለዋል፡፡ ብዙ ንብረት ወድሟል፤ ነዋሪዎች ከቀያቸው ተፈናቅለዋል፡፡ ይህ የሚያሳየው በሀገራችን ሰላም እንዳይሰፍን ሆን ብለው ግጭት የሚፈጥሩ አካላት መኖራቸውን ነው፡፡

በወቅቱ አጥፊዎችን ሊያስተምር የሚችል እርምጃ መወሰድ ሲገባ ጉዳዩ ለሕዝብ ይፋ እንዳይሆን ከመንግሥት አካላት ተጽዕኖ ይደረግ ነበር፡፡ አጥፊዎችን ማስታገስ ሲገባ ጉዳት የደረሰባቸው ክርስቲያኖች ጉዳታቸውን እንዳይናገሩ መከልከል ላይ ያተኮረ እንቅስቃሴ ሲፈጸም መፈጸም በሕግም በሞራልም የሚያስወቅስ ነው፡፡ ይህ በምንም ዓይነት መንገድ ፍትሐዊ ሊሆን አይችልም፡፡ ይህ ለአጥፊዎች ከለላ መስጠትን እንጂ ለፍትሕ መቆምን አያሳይም፡፡ አጥፊዎች ሲያጠፋና ክርስቲያኖችና አብያተ ክርስቲያናት ሲቃጠሉ ዝም ብሎ ማየት ትዕግሥትን ሳይሆን የጥፋት ተባባሪ መሆንን የሚያሳይ ነው፡፡

በወቅቱ የመንግሥት አካላትን ያሳስብ የነበረው የገደሉትንና አደጋ ያደረሱትን አካላት ለመያዝ ሳይሆን አደጋው በተፈጸመበት ወቅት ከቦታው ተገኝተው የዘገቡትን አካላት ለመያዝ ነበር፡፡ ይህ ተግባር አሁንም ስለቀጠለ ቤተ ክስስቲያን እየተገፋች ድምፅ የሚያሰማላት አካል እያጣች ነው፡፡ አጥፊዎች ለስንት ሺህ ዘመናት የኖረ የሀገር ሀብት ሲያወድሙ እንደ ቀልድ እየታለፈ መሆኑ ለዚህ ጥሩ ማሳያ ነው፡፡ በየካቲት ወር መጨረሻና በመጋቢት ወር መጀመሪያ በድሬደዋ ከተማ አጠገብ የሚገኘውን ደን በመመንጠር የቤተ ክርስቲያንን መሬት በመከፋፈል ላይ ሳሉ ሕግ አስከባሪ አካላት ቢደርሱም አልታዘዝንም በማለት ቆመው ሲመለከቱ አጥፊዎች ከቦታው እንዲሸሹ ሲያደርጉ እንደነበር የዐይን እማኞች ገልጠዋል፡፡ በሊሙ ኮሳ ወረዳ በያዝነው ዓመት በተፈጸመው ጥፋት ከወረዳ አመራር ጀምሮ ሥልጣን ላይ የሚገኙ ወገኖች ጥፋቱን ያደረሱት አካላት በእምነት ስለሚመስሏቸው ወደ ሕግ ለማቅረብ አለመቻላቸውን ወረዳ ቤተ ክህነቱ ለሀገረ ስብከቱ የጻፈው የድረሱልኝ ደብዳቤ ያስረዳል፡፡ ምክንያት ተፈልጐ የሚያዙትና ካለ ፍርድ እስር ቤት እንዲቆዩ የሚደረጉትም ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ ይህም ክርስቲያኖች እንዲሞቱ የተፈረደባቸው፣ ለሚደረስባቸው  አደጋ ሁሉ ከለላ የሌላቸው መሆኑን ሲያመለክት አጥፊዎች ደግሞ ሽፋን የሚሰጣቸው ይመስላል፡፡ ይህንም በሐረር ከተማ ጥር ፲፩ ቀን ፲፱፻፺፫ ዓ.ም ለጥምቀት በዓል በወጡ ምእመናን ላይ ለጁምአ ስግደት በአንድ መስጊድ ተሰብስበው የነበሩ ሙስሊሞች በፈጸሙት ትንኮሳ ግጭት ተፈጥሮ የአራት ሰዎች ሕይወት ሲያልፍ በፖሊስ ቊጥጥር ሥር የዋሉት ፲፮ ምእመናን ያለ ምንም ውሳኔ ከስድስት ወራት በላይ መቆየታቸው ማሳያ ነው፡፡ ግጭቱን ማን እንደጀመረው? ዓላማው ምን እንደነበር? አጣርቶ አስቸኳይ ውሳኔ መስጠት፣ አጥፊም በጥፋቱ እንዳይቀጥል ማስተማር ሲገባ ክርስቲያኖችን መርጦ ማሰር መፍትሔ አይሆንም፡፡ ወንጀል የፈጸመ ሰው አይያዝ ባይባልም ክርስቲያኖች ብቻ ተይዘው የሚታሰሩበት፣ ቢታሰሩም ቶሎ ለፍርድ የማይቀርቡበት ምክንያት ሌላ ዓላማ ያለ ያስመስላል፡፡

በአጥፊዎች ላይ ውሳኔ ቢሰጥበትም ቤተ ክርስቲያንን ላቃጠሉ፣ ንዋያተ ቅድሳትን ለዘረፉ አካላት የሚሰጠው ፍርድ አንድ በግ ከሰረቀ ሌባ ጋር ልዩነት የሌለው በነፃ ከማሰናበት ያልተሻለ መሆኑ ለክርስቲያኖችና ለቤተ ክርስቲያን ትኩረት መነፈጉን የሚያሳይ ነው፡፡ መረዳት የሚገባው ቤተ ክርስቲያንን አቃጥለው፣ ቅርሱን አውድመው እስከሚጨርሱ ዝም ከተባለ “ኢትዮጵያን የጎብኝዎች መዳረሻ እናደርጋለን” የሚለው አሳብ የሕልም እንጀራ መሆኑን ነው፡፡ የሚነገረው ቃልም ተፈጻሚነት ሳይኖረው ክርስቲያኖችን በማይሆን ነገር ለማዘናጋት የሚፈጸም መሆኑን የሚያሰገነዝብ ነው፡፡ ይህም በቤተ ክርስቲያን ላይ የተነሡት አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ብቻቸውን ሳይሆኑ በጀርባቸው ሌላ አይዞህ ባይ እንዳላቸው የሚያመለክት ነው፡፡ የክርስቲያኖችና የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ትኩረት እንዳይሰጠው፣ በመገናኛ ብዙኃን ሽፋን እንዳያገኝና ሽፋን የሚያገኘውም ዘግይቶ መሆኑ ሌላ ችግር ይዞ እንዳይመጣ መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ የሚሰጠው አስተያየት እውነት የሚመስለው አጽራረ ቤተ ክርስቲያን የሚፈጽሙት እንዲሸፈን መደረጉ ነው፡፡

 በምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሜኤሶን ወረዳ በሚገኘው የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድስት ሥላሴና አቡነ ሳሙኤል ገዳም የካቲት ፳ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም ከረፋዱ አራት ሰዓት አካባቢ ለከብት ዘረፋ ወደ ገዳሙ ክልል የገቡ የኢሳ ጎሳ አባላትን ለመከላከል የተደረገውን የተኩስ ልውውጥ ተከትሎ ሰደድ እሳት ተቀሰቀሰ፡፡ በወቀቱ የተቀሰቀሰው ሰደድ እሳት ከ፳፻፩ ዓ.ም በኋላ ለሁለተኛ ጊዜ ነበር፡፡ ከአሥራ አምስት ዓመት በፊት ተቀስቅሶ ለ፲፭ ቀናት የቆየው ሰደድ እሳት ከ፲፩ ሺህ ሄክታር በላይ ደን አውድሟል፡፡ እሳቱ በቊጥጥር ሥር የዋለው ከዋናው የገዳሙ ግቢ ለመድረስ ፭፻ ሜትር ያህል ሲቀረው ነበር፡፡ በወቅቱ ከ፴፰ ያላነሱ ከሰል አክሳዮች ለሰደድ እሳቱ መነሣት ምክንያት ናቸው በሚል ተጠርጥረው በቊጥጥር ሥር ቢውሉም ወዲያው በዋስ ተለቀዋል፡፡ ክስ ይመሥረትባቸው አይመሥረትባቸውም የታወቀ ነገር የለም፡፡ ይህ ሁሉ የሚያሳየው በቤተ ክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ ለሚደርሰው ጥፋት ማስተካከያ የሚሰጥ አለመኖሩን ያሳያል፡፡

ይቆየን!

ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከግንቦት ፲፮-፴ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም

በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

በተለያዩ መድረኮች ቤተ ክርስቲያን ከእምነት ውጭ የሆኑትን ለማሰቃየት የክፉ አድራጊዎች ጠበቃ የሆነች የሚያስመስሉ ጽሑፎች ይቀርባሉ፡፡ ድብቅ ዓላማ ያላቸው ወገኖች ቤተ ክርስቲያንንና ክርስቲያኖችን ለማጥፋት ሰበብ በመፈለግ ጥፋተኛ እያስመሰሉ ያቀርባሉ፡፡ በመሠረቱ ይህ አስተሳሰብ ሁለት መሠረታዊ ችግሮች አሉበት፡፡ የመጀመሪያው ታሪክ በመሰነድ፣ ትውልድ በምግባር ኮትኩታ ያቆየች ባለውለታ፣ ቅርሶቿ ለሀገር ልዩ መታወቂያ ጐብኝዎችን ማርኮ የሚያመጣ ሆኖ ሳለ ያለ ስሟ ስም መስጠቱ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ከእውነት የራቀ ሐሳብ ይዘው ጥፋተኛ ሳትሆን፤ ጥፋተኛ ስለሆነችና ከአጥፊዎች ስለተባበረች መጥፋት ይገባታል እንበቀላት የሚለው ነው፡፡ እነዚህ ለማጥፋት ምክንያት ፈላጊ ወገኖች ቤተ ክርስቲያንን እያቃጠሉና ምእመናንን እየገደሉ ለምን ሲባሉ ጥፋተኛ ስለሆነች ይላሉ፡፡ መቼ፣ የት፣ በማን፣ እነማንን ተብለው ሲየጠቁ መልስ የላቸውም፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ማቃጠልና ምእመናንን መግደል የእምነቱ ተከታዮች ራሳቸውን ወደ መከላከል ከዚያም ወደ መጉዳት ሊሸጋገሩ እንደሚችሉ መረዳት ይገባል፡፡ ለተፈጸመው ጥፋት አጸፋውን ቤተ ክርስቲያን ብትመልስ በሀገር ላይ ሊከሠት የሚችለውን ጥፋት አስቀድሞ መረዳትም ይጠቅማል፡፡ ጥናትን ሽፋን አድርጎ ለአጥፊዎች ዱላ የሚያቀብሉ አካላትም ከድርጊታቸው መቆጠብ ይኖርባቸዋል፡፡ መንግሥት አጥፊዎችን ለሕግ ከማቅረብ በተጨማሪ ለክርስቲያኖችና ለቤተ ክርስቲያን ከለላ መስጠት ይኖርበታል፡፡ አጥፊዎችም ክርስቲያኖችን ለማጥፋት የመዘዙት ሰይፍ ወደ ራሳቸው እንዳይዞር እና የእርስ በእርስ መጠፋፋት ሊያስከትል እንደሚችል ደጋግመው ሊያስቡበት ይገባል፡፡ በሃይማኖትና በዘር ምክንያት የተቀሰቀሰ ግጭት መብረጃ እንደሌለው በየሀገራቱ የተፈጸሙትን ጥፋቶች ማየት ይገባል፡፡ ታሪክ መጥቀስ ብቻውን የዕውቀት ባለቤት አያደርግም ከታሪክ መማር እንጂ፡፡

ከ፲፱፻፷፮ ዓ.ም ወዲህ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሰውንና ከዛሬ ነገ እርምት ይወስድበታል በማለት በትዕግሥት ስትጠብቅ መኖሯን ከመግለጻችን በፊት ቤተ ክርስቲያን ለሀገር ያበረከተችውን አስተዋጽኦ በመጠኑ ለመዳሰስ እንሞክራለን፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሰዎችን ለመንግሥተ ሰማያት ስታዘጋጅ፣ በፍቅር ስባ፣ በትምህርት አለዝባ በእምነትም በምግባርም እንዲስተካከሉ በማድረግ ነው፡፡ ከአፍሪካ ሀገራት መካከል ሀገራችን ብቸኛ የራሷ ፊደል ያላት፣ ዘመን ተሻግሮ ከዘመናችን የደረሰ ቅርስ አበርክታ ሀገራችን በመላው ዓለም እንድትታወቅ ያደረች ባለውለታ ናት፡፡ አፍሪካውያን በቅኝ ግዛት ሲማቅቁ ኢትዮጵያውያን የቅኝ ግዛት ቀንበርን ሰብረው ጥለው፣ የነጭን ትምክተኛነት አስተንፍሰው ልጆቻቸው ቀና ብለን እንድንሔድ የመሪነቱን ሚና የተጫወተች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ በውጭ ሀገራት በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ተጽፈው እምነት፣ ዕውቀት፣ ሥነ ምግባር የሚያስተምሩ መጻሕፍት ኢትዮጵያዊ በሆነ ብሂል ተተርጒመው ትውልድ እንዲማርባቸው፣ ሊቃውንቶቿ በአፍሪካ፣ በመካከለኛው ምሥራቅና በአውሮፓ የኢትዮጵያን ባህል፣ ሃይማኖት፣ ታሪክ በማስተዋወቅ የአምባሳደርነት ሚና እንዲጫወቱ ያደረገችው ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ይህን የቤተ ክርስቲያን አስተዋጽኦ ዶክተር አክሊሉ ሀብቴ ‹‹የኢትዮጵያ ምሁራን መነኮሳት በኢትዮጵያ መልክዓ ምድር ክልል ውስጥ ብቻ ሳይሆን ከዚያም ውጭ በመሔድ በታሪክ ሊታወስና ሊጠና የሚገባ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡ በኢትዮጵያ አካባቢ በሱዳንና በግብፅ፣ በየመንና በኢየሩሳሌም፣ በአውሮፓ በመሔድ እነሱም እየተማሩ፣ የውጭውንም ሕዝብ ስለ ኢትዮጵያ ቋንቋና ታሪክ፣ ሃይማኖትና ባህል እንዲያውቅና እንዲፅፍ አድርገዋል›› (አክሊሉ፤፹፩) በማለት ገልጠውታል፡፡

እውነተኞቹ ተመራማሪዎች ያለ ኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ኢትዮጵያን ማሰብ እንደሚከብድ በምርምራቸው አረጋግጠው እውነቱን ከሐሰት፣ ብስሉን ከጥሬ፣ የሚጠቅመውን ከሚጐዳው፣ የተፈጸመውን ካልተፈጸመው ለይተው ከጥንካሬያችን እንድንማር ከስሕተታችን እንድንጠበቅ ያደረጋሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ማዳከም ዓላማችንን ያሳካልናል ብለው የሚያስቡ ወገኖች ደግሞ ኢትዮጵያን ቅኝ ለመግዛት ፈልገው ቅስማቸው ተሰብሮ እንዲመለስ ያደረገችው ቤተ ክርስቲያን መሆኗን ስለተረዱ ስሟን ለማጥፋት፣ ታሪኳን ለመበከል የጻፉትን አሉባልታ እውነት አድርገው በመውሰድ ታሪክ ሲያበላሹ፣ በተቀመጡበት የኃላፊነት ቦታ ጥፋት ሲፈጽሙ ይታያሉ፡፡ ሰውን በሰውነቱ እኩል ማገልገል ሲገባቸው በጎሳ፣ በቋንቋ፣ በጎጥ፣ በቡድንና በባህል በመከፋፈል ሥልጣንን ለክፉ ተግባር ይጠቀማሉ፡፡ ሕዝብን ለማገልገል የተሰጣቸውን ሥልጣን ተጠቅመው ቤተ ክርስቲያንንና ምእመናንን የማሳደድ ተልእኮ ይፈጽማሉ፡፡ ሀገር ሰላም ካልሆነችና ዜጎቿ በሰላም ወጥተው ካለገቡ አጥፊዎችም ችግር እንደሚገጥማቸው አልተረዱትም፡፡

በካናዳ፣ በቫቲካን፣ በጀርመንና በሌሎችም ሀገሮች የኢትዮጵያ ጥናት ተቋማት እንዲከፈቱ፣ ተመርምሮ የማያልቅ ዕውቀት የያዙት የብራና መጻሕፍት ለዓለም እንዲተዋወቁ ያደረጉት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምራ «ሑሩ ወመሀሩ» ብላ ያሰማራቻቸው ሊቃውንት ናቸው፡፡ በሌላ በኩልም ሀገራችን እንግዳ ተቀባይ የሆነችውና ዓለም ፊቱን ያዞረባቸውን የመሐመድ ተከታዮች ሳይቀር መጠጊያ እንድትሆን ያደረጋት ቤተ ክርስቲያን በእምነት ኮትኩታ፣ በምግባር አንፃ ያስተማረቻቸው እነ ንጉሥ አርማህ ርኅሩኆች ብቻ ሳይሆኑ አስጠጉኝ ብሎ የመጣባቸውን አሳልፈው ለመስጠት ሰብአዊነት የተለያቸው ስላልነበሩ ጭምር ነው፡፡

ወርቅ ላበደረ ጠጠር፣ እህል ላበደረ አፈር እንዲሉ ይህን ውሉ ውለታ ለዋለች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተሰጠው መልስ ነው፡፡ የደረሱበት መረጃ ካለ ማስረጃን መሠረት አድርጎ እውነት ማሳወቅ አንድ ነገር ነው፣ ሐሰትን እውነት እያስመሰሉ ማቅረብና ሰውን ለብጥብጥ መጋበዝ ግን ጤነኛ አእምሮ ያለው፣ በእግዚአብሔር የሚያምን ሰው የሚፈጽመው አይደለም፡፡ በየጊዜው ቤተ ክርስቲያንን የሚያቃጥሉት፣ ክርስቲያኖችን የሚገድሉት፣ ንብረታቸውን የሚቀሙትና የሚያሳድዱት ከመጥፎ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ መንግሥት እርምት ይወስዳል ቢባልም ምንም ነገር እንዳልተፈጸመ እየታለፈ፣ የማዘናጊያና የማረሳሻ ተግባር እየተፈጸመ ነው፡፡

ከምዕራባውያን የተኮረጀው ሥርዐተ ትምህርት ባልነበረበት ዘመን የሀገራቸው አምባሳደር የነበሩ፣ የውጭ ዲፕሎማት ሲመጣ አስተርጓሚ ሆነው ሲያገለግሉ የኖሩ ሊቃውንትን ያፈራችን ቤተ ክርስቲያን ከዋለችበት ላለማሳደር፣ ካደረችበት ላለማዋል እየተፈጸመ ያለው ግፍ መቆም አለበት፡፡ የሊቃውንቱን አስተዋጽኦ አክሊሉ ሀብቴ ‹‹ሆኖም እዚያ (ኢየሩሳሌም) የተደራጀው የመነኮሳት ማኅበር ኢትዮጵያን በመወከል ወደ ኢጣሊያም፣ ወደ አርመንም፣ ወደ ቊስጥንጥንያም፣ በመሔድ ግንኙነት ፈጥሮ እንደነበርና ምን አልባትም ከአርመኖች ጋር በነበረው የቅርብ ግንኙነት አርመኖች ፊደላቸውን ሊቀረፁ የቻሉት ከኢትዮጵያ ፊደል እንደሆነም ይነገራል፡፡ ወደ ኢየሩሳሌም በሚመላለሱበት ዘመን እግረ መንገዳቸውንም ከሱዳንና ከግብፅ ክርስቲያኖች ጋር የቅርብ ግንኙነት መፍጠራቸው ይታመናል፡፡ የቀድሞዎቹ የኢትዮጵያ ምሁራን መነኮሳት ፈር ቀዳጅ አስተዋጽኦ እንዲሁ መጠናት የሚገባው ነው›› (አክሊሉ፣ ፷፪) በማለት ገልጠውታል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ልጆቿ ሰው አክባሪ፣ ሀገር ወዳድ፣ የሥራ ፍቅር ያላቸው፣ የራሳቸውን የማያስነኩ፣ የሌላውን የማይፈልጉ አድርጋ ስታሳድጋቸው ጠብ አጫሪነትን፣ በጉልበታቸው የሚመኩ መሆንን እንዲጸየፉ በማድረግ ነው፡፡ ጠላታቸውን በጽናትና በትዕግሥት እንዲቋቋሙ፣ ሀገርና ሃይማኖት ሊያጠፋ የመጣውን የጥፋት ኃይል እንዳያሸንፍ ያደረገች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ይህ ድርጊቷ ያበሳጫቸው ምዕራባውያን በዘመናዊ ትምህርት ሰበብ በየሴሚናሪዎቻቸውና ኮሌጆቻቸው አስተምረው የላኳቸው ወገኖቻችን ነባሩን የኢትዮጵያ ሃይማኖትና፣ የክርስቲያኖች ተጋድሎ የሚያናንቅ፣ መልኩ የእኛ ቢሆንም የነጭ ጉዳይ አስፈጻሚ ሀገሪቱን ለባዕድ አሳልፎ ለመስጠት የባለቤትነት ስሜት የሚያድርበት እንዳይሆን አእምሮውን ለውጠው ሲልኩት ኖረዋል፡፡ በመመረቂያ ጽሑፍ ሰበብ ቤተ ክርስቲያንን ያለ ስሟ ስም፣ ያለ ግብሯ ግብር እየሰጡ የዘመናችን ተመራማሪ ነን ባዮች የግብር አባት ሆኑ፡፡ በዚህ ተግባራቸውም ትውልዱ በሰላም ውሎ እንዳይገባ እንቅልፍ ላጡ ወገኖች መንገድ መሪ የጥፋት ተባባሪ ሆነው አልፈዋል፡፡ ይህን ለማረጋገጥ ራሳቸውን ተሐድሶ ብለው የሠየሙ አካላት በተለያዩ የኅትመትና የብሮድካስት ሚዲያዎች በቤተ ክርስቲያን ላይ የሚያወርዱትን የስድብ ዶፍ መመልከት ይቻላል፡፡ በአካል መግዛት ያልተቻላቸውን ኢትዮጵያውያንን በአእምሮ ለመግዛት መሰሎቻችንንና በሥጋ የሚዛመዱንን አእምሮ እየለወጡ የሚልኩልንንና እነሱም አልፎ ሒያጅ መንገደኞችና ለቤተ ክርስቲያን ጥላቻ ያደረባቸውን ወገኖች እየጠየቁ የጻፉትን አሉባልታ በትክክለኛ ማስረጃ በመሞገት፣ የዕውቀታቸውን ግልብነት፣ የመረጃቸውን ተራነት፣ የትነታኔያቸውን አመክንዮ አልባነት ማሳየት ይኖርብናል፡፡ አጥፊዎች ታጥቀው ሲዘምቱብን ዝም ብሎ ማየት እሳት መቃጠሉን የሰማ የዋህ እኔስ ሣር ውስጥ ተደብቄያለሁ በማለት የመለሰውን የሚያስታውስ ይሆናል፡፡

ቱሪስቶች ሊጐበኙ የሚመጡት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ገዳማት፣ አድባራት፣ ሥዕላት፣ የብራና መጻሕፍትና ንዋያተ ቅድሳት እንዲሁም ክርስቲያን ነገሥታት የገነቧቸውን አብያተ ክርስቲያናት፣ ሐውልቶችና አብያተ መንግሥታት ለመጎብኘት ነው፡፡ ይህን አስተዋጽኦ ያደረገችልን ቤተ ክርስቲያን መደገፍና መጠበቅ ሲገባ ስትጠቃ ዝም ብሎ ማየት ማሯን እንጂ ንቧን አልፈልግም እንደ ማለት ይቈጠራል፡፡ ለጥፋት የተሰለፉ ወገኖች በቤተ ክርስቲያንና በምእመናን ላይ አደጋ ሲያደርሱ የግለሰቦች ጉዳይ እየመሰለ ይቀርባል፡፡ በመገናኛ ብዙኃን ይነገራል፡፡ በሌሎች እምነቶች ላይ የሚፈጸመው ወይም ራሳቸው ፈጽመው ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል የተባለውን ለሚፈጽሙት ግን ከመገናኛ ብዙኃን ጀምሮ የሚሰጠው ሽፋን የሚገርም ነው፡፡ ይህም ክርስቲያኖች ሲገደሉ፣ አብያተ ክርስቲያናት ሲቃጠሉ መረጃው በቶሎ እንዳይነገር ከተቻለም ተዳፍኖ እንዲቀር ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን እንድንጠረጥር የሚያደርግ ነው፡፡ ለምሳሌ በቡኖ በደሌ የተፈጸመውን ሰቆቃ በሥልጣን ላይ የተቀመጡ አካላት ወንጀሉን የፈጸሙት አካላት በእምነት ስለሚመስሏቸው ለማዳፈን ሞክረዋል፡፡ በሰሜን ሸዋና በኬሚሴ በክርስቲያኖችና በአብያተ ክርስቲያን ላይ የደረሰው ጥፋት በመገናኛ ብዙኃን የተነገረው ጥፋቱ ከተፈጸመ ከአራት ቀናት በኋላ መሆኑን ኢትዮጲስ ጋዜጣ በሚያዝያ ፮ ዕትሙ አስነብቧል፡፡ በበሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እና አካባቢው አብያተ ክርስቲያን ተቃጥለውና ምእመናን ተገድለው አጥፊዎችን መያዝ ሲገባ መረጃው ያላቸውን ክርስቲያኖች ለመያዝ ይደረግ የነበረው ወከባ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡

ይቆየን!

ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከግንቦት ፲፮-፴ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም

ለ፲፰ ቀናት የቆየው የ፳፻፲፩ ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ጉዳዮችን ለማስፈጸም ውሳኔዎችን አሳለፈ

በሕይወት ሳልለው

 ከግንቦት ፲፬ እስከ ሰኔ ፫ ፳፻፲፩ ዓ.ም ድረስ የተካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የ፳፻፲ እና ፳፻፲፩ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ጉዳዮች ላይ ውሳኔ ማሳላፉን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በመግለጫቸው አስታወቁ፡፡

በአሁኑ ጊዜ በአብያተ ክርስቲያናት ላይ እየደረሰ ያለውን ጥቃት በመንቀፍ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ኃላፊነቷን ለመወጣት የሚያስችል ውሳኔ መወሰኑን ይፋ አድርገዋል፡፡ ለተቃጠሉት አብያተ  ክርስቲያናት መልሶ ግንባታ የሚሆን ገንዘብ ማሰባሰቡን ፤ ምእመናን ላይ እየደረሰ ያለውን ጥቃትና በሀገር ደረጃ ሰላም፤ፍቅርና አንድነት እንዳይኖር የሚያግዱ ችግሮችን ማውገዙንና ሃይማኖታዊ ሥርዓትን ለማስጠበቅ የሚያስችሉ ውሳኔዎችን ማሳለፋቸውን ቅዱስ ፓትርያርኩ ገልጸዋል፡፡ «በውጭ ሀገር የሚገኙ አህጉረ ስብከቶችን የቤተ ክርስቲያንን በማጠናከር መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ማስፋፋት እንዲቻል ቃለ ዓዋዲው ከየሀገራቱ መንግሥታት ሕግ ጋር የተጣጣመ ደንብ ሆኖ እንዲዘጋጅና ለጥቅምት ፳፻፲፪ ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እንዲቀርብ ተወስኗል» ብለዋል፡፡

በተለይም ከቀናት በፊት ቅዱስ ሲኖዶሱ ስላወገዘው የግብረ ሰዶማውያን እንቅስቃሴም ቅዱስ ፓትርያርኩ አሳስበዋል፡፡ «የሀገራችንን የቱሪስት መስሕብነት ምክንያት በማድረግ ዜጎች በቅድስናና በፈሪሀ እግዚአብሔር ተከብረው የሚታወቁባትን የሀገራችንን ታሪክ የሚቀይር፤ የዜጎችን መልካም ሥነ ምግባር የሚለውጥ፤ ሕገ ተፈጥሮንና የተቀደሰውን ሥርዓተ ጋብቻን የሚያበላሽ፤ በቅዱሳት መጻሕፍት ሁሉ የተወገዘ ግብረ-ሰዶምን በሀገራችን ለማስፋፋት፤ በዚህም የቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ቅድስና የሚጎዳ ሕገ-ወጥ ተግባር ለመፈጸም መቀመጫውን በአሜሪካን ሀገር ያደረገው የግብረ-ሰዶማዊያን አስጎብኚ ድርጅትን በመቃወም ወደ ቅድስት ሀገራችን ኢትዮጵያ እንዳይገባ፤ቅዱሳት መካናትንም እንዳይጎበኝ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤው አውግዟል»

እነዚህንና ሌሎች ችግሮችን ለመፍታት ምልአተ ጉባኤው በውይይቱ ላይ  ፲፭ ዋና ዋና ጉዳዮች ያነሳ ሲሆን በእያንዳንዳቸው ላይ ጥናት በማካሄድና ችግሮቹን በመለየት ዘላቂ መፍትሔ ለማምጣት በሚል ባለሞያዎችንም እንደመደበ አስታውቋል፡፡ በተጨማሪም በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በየሦስት ዓመቱ የሚመረጡ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊን የጠቅላይ ቤ ክርስቲያን ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት፤ ሊቀጳጳስ፤ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ እና ብፁዕ አቡነ ያሬድ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ አድርጎ መሰየሙን አሳውቋል፡፡

በመጨረሻም ከ፳፬ ዓመት በኋላ የቤተ ክርስቲያኗ ታላላቅና ሁለት መለስተኛ ሕንጻዎች በአቤቱታ መመለሳቸውን የሚያረጋግጥ ደብዳቤ ግንቦት ፳፱ ቀን መቀበላቸውን ሊቀ ካህናት ኀይለ ስላሴ ዘማርያም ገልጸው ሰኔ ፫ ቀን ርክክቡ በፊርማ ጸድቋል፡፡

 

 

 

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በጸሎት ተከፈተ!

በሕይወት ሳልለው

በዓመት ፪ ጊዜ የሚካሔደው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ግንቦት ፲፬ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም. በጸሎት ተከፈተ! በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰባት ያለውን ችግር ለመፍታት ከአሁን ቀደም ጸሎተ ምሕላው በአግባቡ ያልተካሔደ መሆኑን በመግለጫቸው ያሳወቁት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት «በአክሱምና በሌሎች ጥቂት ገዳማትና አድባራት በዕንባና በልቅሶ የታጀበ ጸሎተ ምሕላ ቢደረግም፤ በርእሰ ከተማ ከአዲስ አበባ ጀምሮ በብዙ ቦታ ጸሎተ ምሕላው ተጠናክሮ እንዳልተካሄደ ለማወቅ ተችሏል» በማለት አስታውቀዋል፡፡

ሁላችንም ከእህልና ውኃ በመለየት መጸለይና ፈጣሪያችንን  መማጸን እንዳለብንም ቅዱስ ፓትርያርኩ አስገንዝበዋል፡፡ «ሁሉን ማድረግ የሚቻለው፤ ምንም ምን የሚሳነው የሌለ፤ እግዚአብሔር አምላካችን ብቻ ነውና፤ እሱ በመሠረተልን ስልት እጃችንን ወደ እግዚአብሔር እንድንዘረጋ፤ ሕዝቡም ሁሉ፤ ሀገሪቱም በአጠቃላይ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር እንድትዘረጋ፤ እኛም በየሀገረ ስብከታችን ተገኝተን፤ራሳችን መሪዎች ሆነን ጸሎተ ምሕላውን እንድንመራ፤ ትምህርተ ወንጌሉን እንድንሰጥ፤ቂም በቀል እንዲከስም፤ ይቅርታ እንዲያብብ፤ ያለማቋረጥ የሽምግልና ሥራን መሥራት ከሁላችን ይጠበቃል» ሲሉም መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

እንዲሁም አያይዘው በሀገራችን ውስጥ ያለውን ጦርነት በመንቀፍ፤ ቅዱስ ሲኖዶሱ ከሕዝቡ ጋር በመወያየት በሰላማዊ መንገድ ያሉትን ችግሮች ለመፍታት፤ ማንኛውንም አይነት ግጭት በመቃወምና አንድነትን በመፍጠር፤ ዘላቂ መፍትሔ ለማግኘት እንደሚጥር ገልጸዋል፡፡ ከዚህም በአሻገር ተፎካካሪ ፓርቲዎች ኃይለ ቃል ከመጠቀምና ስም ከማጥፋት እንዲታቀቡ በእግዚአብሔር ስም አሳስበዋል፡፡

በመጨረሻም የዚህ ዓመት የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ  በአቤቱታ ከተመለሱት የቤተ ክርስቲያኗ ታላላቅና ሁለት መለስተኛ ሕንጻዎች ማግስት በመከናወኑ ከሌላው ዓመት እንደሚለይ አስታውቀዋል፡፡

 

ምስክርነት

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ

በሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ ፩ ቁጥር ፰ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ የተናገራቸው ቃል «በኢየሩሳሌምና በይሁዳ ሁሉ፤ በሰማርያ እስከ ምድር ዳርቻ ድረስም ምስክሮቼ ትሆኑኛላችሁ» የሚል ነው፡፡

ይሁዳ ኢየሩሳሌምን የሚያጠቃልል ግዛት ነው፤በኢየሩሳሌም የጌታችን ተአምር የተፈጸመበት፤ ብዙ ሰው ስለ እርሱ የሰማበትም ከተማ ነው፡፡ ከኢየሩሳሌም ይልቅ በይሁዳ ስለ ክርስቶስ የሚያውቁም የሚሰሙም ዝቅተኛ ናቸው፡፡ ሌላው ሰማርያ ነው፤ ሳምራውያን ከአይሁድ ጋር በሥርዓት አይተባበሩም፤ በመጽሐፍ ቁጥርም፤ በባህልም፤ በቤተ መቅደስም አይገናኙም፤ አንዱ አንዱን ይጸየፈዋል፡፡

እኛስ በሕይወታችን ውስጥ ለሃይማኖታችን እየመሰከርን ነው? ከሐዋርያት ሥራ እንደምናነበው ቅዱስ እስጢፋኖስ መከራ በተቀበለ ጊዜና በክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ላይ ሰይፍ በተመዘዘ ጊዜ ሁሉም ከኢየሩሳሌም እየወጡ ተጉዘዋል፡፡ ቤተሰቦቻቸውን፤ ቤታቸውንና ሀገራቸውን ትተው ወደ አሕዛብ ሀገር ሄዱ፤ በሔዱበት ቦታ ግን ወንጌል ተሰበከች፤ እነርሱ በሥጋ ቢጎዱ ቤተ ክርስቲያን ግን ተጠቅማለች ፡፡ የእኛ ወገኖች ቻይና፤ ዓረብ፤ አውሮፓና አፍሪካ ገብተዋል፤ ኢትዮጵያዊ ዘር ምናልባት ያልገባበት አንታርቲካ ብቻ ሊሆን ይችላል፤ እነርሱ በሄዱበት ሁሉ  ወንጌል አስተማሩ የሚል መጽሐፍ ተጽፎልናል? ዛሬ ግን ኢትዮጵያ ወንጌል ተሰበከ ሳይሆን የሚሰማው ተጣሉ፤ተበጣበጡ፤ይተማማሉ ይቀናናሉ የሚል ነው፤ ይህ ነው ወንጌል? ወንጌል የሰላም፤ የፍቅርና የደኅንነት ምንጭ ነው፤የብጥብጥ፤ የጦርነት ፤የጭቅጭቅ ግን አይደለም፡፡

ከሐዋርያት ዕጣ ፈንታ በገዛ እጁ በጠፋው በይሁዳ ምትክ ሰው ለመተካት ሐዋርያት ዕጣ ሲጣጣሉ «ከእኛ ጋር አብረው ከነበሩት ከእነዚህ ሰዎች አንዱ የትንሣኤው ምስክር ይሆን ዘንድ ይገባል» ብለዋል፤ በሐዋርያት ሥራ ፩፥፳፪፡፡ ሁለቱን ሰዎች ዕጣ የምንጥለው ለምንድን ነው? ለሚለው የሰጡት መልስ «ከሁለቱ አንዱ ከእኛ ጋር የትንሣኤው ምስክር እንዲሆን» የሚል ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ተወለደ፤ አስተማረ፤ ተያዘ፤ ተገረፈ፤ ተሰቀለ፤ሞተ፤ተቀበረ፤ተነሣ የሚለው ቃል የትንሣኤው ምስክር ነው፡፡

እኛስ የማን ምስክር ነን? ብዙዎቻችን ጥሩ የፊልም ተዋናዮች ነን፤ ስለ እነርሱ ተናገሩ ብንባል የምንናገረውን ስለ ቅዱስ ጳውሎስ ተርኩ ብንባል አንተርክም፡፡ ስለ አንድ ዘፋኝ የምንናገረውን ያህል ስለ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ፤ ስለ ቅዱስ ያሬድ ተናገሩ ብንባል አንናገርም፤ የፊልም ተዋናዮቹንና የዘፋኞቹን ፎቶ ደረታችን ላይ ለጥፈን እየተንጠባረርን የምንሄደውን ያህል የቅዱሳንን ሥዕል በቤታችን ለመስቀል እናፍራለን፡፡ ታዲያ የማን ምስክሮች ነን? ዛሬ ኢትዮጵያውያንን በየቦታው እያጨቃጨቀን ያለው ስለ ምግብ ነው? ይበላል ወይስ አይበላም፤ ያገድፋል ወይስ አያገድፍም፤ የማያገድፍ ነገር በዚህ ምድር ላይ መተው ብቻ ነው፡፡

የሁላችንም ምስክርነት የትንሣኤው መሆን አለበት፤ ለምን የትንሣኤው የሚለውን መረጡ? ኢየሱስ ክርስቶስ ሙስና መቃብርን ድል አድርጎ መነሣቱንና በሞት ላይ፤ በዲያብሎስ ላይ ኀይል እንዳለው፤ የተረዳነው በትንሣኤው ስለሆነ ነው፡፡ የትንሣኤው ምስክር ነው ወይስ ነገ የምንቃጠለውን ቃጠሎ ዛሬ እየመሰከርን ነው?‹‹እነሆ ቀን እንደ እሳት እየነደደ ይመጣል፤ ትዕቢተኞችና ኃጢአትን የሚሠሩ ሁሉ ገለባ ይሆናሉ፤ የሚመጣውም ቀን ያቃጥላቸዋል፤ ሚል.፬፥፩፡፡

ምስክሮቼ ትሆናላችሁ የሚለው ስም ለመጀመሪያ ጊዜ የተሰጠው ለሐዋርያት ነው፤ በኋላ ግን ሃይማኖታቸውን የገለጡ፤ ያስፋፉ፤ የመሰከሩ፤ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ለአሕዛብ የሰበኩ ሁሉ ምስክሮች ተብለዋል፡፡ ጌታም በወንጌል፤ «በሰው ፊት የሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔም በሰማያት በአለው አባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ፤ በሰው ፊት የሚክደኝን ግን እኔም በሰማያት በአለው አባቴ ፊት እክደዋለሁ» ብሏል፤ ማቴ. ፲፥፴፪፡፡ ዛሬ ስለ ምስክሮች ስንሰማ በአእምሮአችን የሚመጡት እነዚህ ስለ እምነት ብለው በፈቃዳቸው መከራን መቀበል የቻሉ ምስክሮች ናቸው፡፡

የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት

በተክለ አብ

በጲላጦስ ዘመን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጅ በገባለት ቃል ኪዳን መሠረት፤ ትንቢቱም ይፈጸም ዘንድ መከራን ተቀበለ፤ ጲላጦስ በ፫ ሰዓት ይሰቅል ዘንድ ሲፈርድበትም፤ ‹‹መስቀሉንም ተሸክሞ በዕብራይስጥ ጎልጎታ ወደ ተባለው ቀራንዮ ወደሚባል ቦታ ወጣ›› (ዮሐ.፲፱፥፲፯) የራስ ቅል ስፍራ ቀራንዮ-ጎልጎታ አዳም ዐጽም የተቀበረበት ቦታ ነበር፡፡ በዚያም የአዳም መቃብር የሆነች ዋሻ አለች፤ የመስቀሉንም እንጨት በዚያ በምድር መካከል አይሁዶች ተከሉት፡፡ የአዳም አጽም ቀድሞ ከአዳም ትውልዶች ሲተላለፍ ከኖኅ ደርሷል፤ ኖኅም ወደ መርከብ እንደታቦት አስገብቶት በኋላ መልከጼዴቅ ቀብሮታል፡፡ ጌታችንም ከአዳም የራስ ቅል በላይ ሊያድነው መስቀል ተሸከሞ ተንገላታ፤ አይሁዶችም የቀራንዮን ዳገት  እየገረፉ ከወደ ጫፍ አደረሱት፤ሁለቱንም እንጨት አመሳቅለው ዐይኖቹ እያዩ እጆቹንና እግሮቹን ቸነከሩት፤ በዕለተ ዐርብ ቀትር ፮ ሰዓት ላይም ተሰቀለ፡፡

ጌታችን የተሰቀለበት ሰዓት ፀሐይ በሰማይ መካከል በሆነ ጊዜ የጥላ መታየት በሚጠፋበት፤ ወደ ሰው ተረከዝም በሚገባበት ነበር፡፤ ከ፮ ሰዓት ጀምሮ እስከ ፱ ምድር ጨለመች፤ ፀሐይ፤ጨረቃ፤ከዋክብት ብርሃናቸውን ከለከሉ፤ ምክንያቱም የፈጣሪያቸውን ዕርቃኑን ይሸፍኑ ዘንድ ነበር፤ ‹‹ቀትርም በሆነ ጊዜ ፀሐይ ጨለመ፤ምድርም ሁሉ እስከ ፱ ሰዓት ድረስ  ጨለማ ሆነ›› ማር.፲፭፥፴፫፡፡

በ፱ ሰዓት በቀኝ የተሰቀለው ወንበዴ ስለ ጌታችን በሰማይ ፫ት በምድር ፬ት ተአምራትን ሲያደርጉ አይቶ በእውነት አምላክ እንደሆነ አመነ፤ ‹‹አቤቱ በመንግሥት በመጣህ ጊዜ አስበኝ›› ባለ ጊዜ በግራ የተሰቀለው ዳክርስ ግን ‹‹እስቲ አምላክ ከሆነ እራሱን ያድን›› ብሎ ተዘባበተ፡፡ ፍያታዊ ዘየማን ግን ‹‹እኛስ በበደላችን ነው የተሰቀልን፤ እርሱ ግን ምንም ሳይበድል ነው፤ እንዴት በአምላክ ላይ ክፉ ነገርን ትናገራለህ›› ብሎ ገሰጸው ፤ፍያታዊ ዘየማንም ጌታችን በጌትነት መንበረ ጸባዖት(መንግሥት) ሆኖ ታየው፤እርሱንም አይቶ ‹‹ተዘከረኒ እግዚኦ በውስተ መንግሥትከ›› ቢለው ጌታችን ‹‹ዮም ትሄሉ ምስሌየ ውስተ ገነት›› ብሎ ደመ ማኅተሙን ሰጥቶታል፤ በኋላ ገነት ሲገባም መልአኩ አንተ ማነህ፤ አዳም ነህ፤ አብርሃም ወይንስ ይስሐቅ? እያለ ጠይቆታል፡፡ መልአኩ ሳያውቅ የጠየቀ ሆኖ አይደለም፤እንኳን በመጨረሻ የጸደቀ ፍያታዊ ቀርቶ በዘመናቸው የኖሩ ጻድቃንን ያውቃል፤ አዳምን ፤አብርሃምን፤ይስሐቅን ሳያውቅ ቀርቶም አይደለም፡፡ ነገር ግን ሊቃውንት ሲተረጉሙት ‹‹አዳም ነህ›› ማለቱ የአዳምን ያህል ሥራ አለህን? አብርሃም ነህ ሲለው ደግሞ የአብርሃምን ያህል ሥራ አለህን? ለማለት ነው፡፡ ‹‹በጌታችን ኢየሱስ መስቀል አጠገብም እናቱ፤ የእናቱም እኅት፤ የቀለዮጳም ሚስት ማርያም፤መግደላዊትም ማርያም ቆመው ነበር›› (ዮሐ.፲፱፥፳፭) ‹‹እነርሱም ማርያም መግደላዊት፤ የታናሹ ያዕቆብ እና የዮሳ እናት ማርያም፤ የዘብዴዎስም የልጆቹ እናት ሰሎሜም ነበሩ›› (ማር.፲፭፥፵)፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ከተናገራቸው የአደራ ቃላት አንዱ እመቤታችን ለቅዱስ ዮሐንስ መሰጠቷ ነው፤ ለወዳጁ ዮሐንስ ከስጦታ ሁሉ ስጦታ የሆነች እናቱን እናት ትሁንህ ብሎ ሰጠው፤‹‹እነኋት እናትህ፤ እነሆ ልጅሽ›› (ዮሐ.፲፱፥፳፮)፡፡ በኋላ ወደ ቤቱ ወስዷት ፲፭ ዓመት ኖራለች፤ በዚህም የዮሐንስ ቤት በአቢዳራ ቤት ተመስላለች፤እመቤታችንም የሚያጽናናትን ወዳጁ ዮሐንስን ሰጥቷታል፡፡ የእመቤታችን ለዮሐንስ መሰጠት ቀድሞ በሙሴ አንጻር ጽላቷ ለሕዝቡ ሁሉ እንደተሰጠች፤በዮሐንስ አንጻርም እመቤታችን ለሁላችን ለምእመናን ተሰጥታናለች፡፡

፱ ሰዓት በሆነ ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ኤሎሄ ኤሎሄ ላማ ሰበቅታኒ፤አምላኬ አምላኬ ለምን ተውከኝ›› ብሎ በታላቅ ቃል ተናገረ፤(ማር.፲፭፥፴፬)፡፡ በዚያም ቆመው የነበሩት ‹‹አምላኬ አምላኬ ለምን ተውከኝ፤›› የሚለውን ድምጽ የሰሙ ኤልያስን ይጣራል እያሉ አሙት፤ ክህደትንም ተናገሩ፤ ያንጊዜ አንዱ ወታደር ሮጦ ሆምጣጤ የመላበት ዕቃ ተቀምጦ ነበርና  በሰፍነግ መልቶ በሂሶጽም አድርጎ በአፉ ውስጥ ጨመረለት፡፡

 በመስቀል ላይ ሳለ ጌታችን ኢየሱስም በታላቅ ድምፅ ሁሉ ተፈጸመ አለ፤ (ማር. ፲፭፥፴፯)፤ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በፈቃዱ ለየ፡፡ አይሁድም እኒህ ሰዎች እንደተሰቀሉ አይደሩ፤ ምክንያቱም ቀጣዩ ቀን ሰንበት ነውና ጭናቸውን ሰብረው ያወርዷቸው ዘንድ ጲላጦስን ጠየቁት፤ እርሱም ፈቀደላቸው፡፡ የሁለቱ ወንበዴዎች፤ ፈያታይ ዘየማንንና ፈያታይ ዘጸጋምን አብረው አወረዷቸው፤ ከጌታችን ዘንድ ቢቀርቡ ፈጽሞ ሞቶ አገኙት፤ በዚህም ጭኑን ሳይሰብሩት ቀሩ፡፡ ሌላው ግን የተመሰለው ምሳሌ ፍጻሜ ሲያገኝ ነው፤ የፋሲካውን በግ ‹‹አጥንቱን ከእርሱ አትስበሩ›› የተባለው አሁን ተፈጸመ፤(በዘፀ.፲፪፥፲)፡፡ ከጭፍሮቹም አንዱ ቀኝ ጎኑን በጦር ወጋው እንዲል ከወታደሮቹ አንዱ የሆነው ለንጊኖስ የጌታችንን ጎን ቢወጋው ትኩስ ደምና ቀዝቃዛ ውኃ ፈሷል፡፡ ለንጊኖስ ጥንተ ታሪኩ አንድ ዐይኑ የጠፋ ሲሆን ጌታችን በተሰቀለበት ጊዜ ወደ ጫካ ሸሽቶ ርቆ ነበር፤ ምክንያቱም ከዚህ ሰው ሞት አልተባበርም በማለት ነው፡፡ አመሻሹ ላይ የአይሁድ አለቆች ሲመለሱ ከመንገድ አገኘቱ፤ስለምን ከመሢሑ ሞት አልተባበርክም አሉት? እርሱም ምንም ስላላገኘሁበት አላቸው፡፡ ከዚያም በኋላ እንደሕጋቸው እንደሚቀጡት ቢነግሩት እየሮጠ ሔዶ የጌታችንን ጎን ሲወጋው ደሙ በዐይኑ ላይ ፈሰሰ፤ ያን ጊዜ ዐይኑ በራለት፤ከጌታችን ጎን የፈሰሰው ደም እንደ ቅርጽ ሆኖ በሁለት ወገን ደምና ውኃ ሆነ፡፡ ከጌታችንም የፈሰሰውን ትኩስ ደም መላእክት በጽዋ ቀድተው በዓለም ላይ ረጩት፤ ይህ መሠረት ሆኖ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን የሚታነጸው የጌታችን ደም የነጠበበት  ነው፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹አሁንም በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ›› ያለው (ሐዋ.፳፥፳፰)፡፡ ከጌታ ጎን የፈሰሰው ውኃ ደግሞ ምእመናን የልጅነት ጥምቀትን ስንጠመቅ ውኃውን ካህኑ ሲባርከው ማየ ገቦ ይሆናል፡፡

ቅዳሜ ከቀድሞው በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል የተሻረችው ቅዳሜ ትባላለች፤ ይህ ቅዳሜ ጌታችን ሥጋው በመቃብር የዋለበት በመሆኑ እኛም እንደ ሐዋርያት የትንሣኤውን ብርሃን ሳናይ እህል አንቀምስም በማለት በጾም ስለምናሳልፈው ነው፡፡ ቄጠማውንም ምእመናን እስከ ትንሣኤው ሌሊት በራሳቸው ላይ ያሰሩታል፤ የቄጠማው አመጣጥና ምሥጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፤ ምድር በጥፋት ውኃ በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሠረችው ቄጠማ ይዛ በመግባት ነው፡፡ ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ኃጢአት ጠፋ፤ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነፃነት ተሰበከና ታወጀ በማለት ካህናቱ ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበስሩበታል፡፡

በዚህች ቅድስት ቅዳሜ፤ ቅዱስ የሆነ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ፤ በዚህች ዕለት ከሥራው ሁሉ ያረፈባት ዕለት ናት፡፡ ጌታችን የተቀበረበትም ስፍራ ለተሰቀለበት ቦታ አቅራቢያ ነበር፤ ዮሴፍ ከኒቆዲሞስ ጋር ሆኖ ጌታችንን እንደፍጡር በሐዘንና በልቅሶ ሲገንዙት የጌታችን ዐይኖች ተገለጡ ‹‹እንደፍጡር ትገንዙኛላችሁን? በሉ እንዲህ እያላችሁ ገንዙኝ፤ ቅዱስ እግዚአብሔር፤ ቅዱስ ኃያል፤ ቅዱስ ሕያው›› አላቸው፡፡

ጸሎተ ሐሙስ

ሆሣዕና በአርያም

በወልደ አማኑኤል

ሆሣዕና በአርያም ማለት በሰማይ ያለ መድኃኒት ነው፡፡ ጌታችን በአህያ ውርንጫ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም የገባበት ዕለት ከዘጠኙ ዐበይት በዓላት አንዱ ስለሆነ የክብረ በዓሉ ምስጋና በዋዜማው ይጀመራል፡፡ ቅዳሜ ከሰዓት በኋላ ካህናቱ ‹‹በእምርት ዕለት በዓልነ፣ በታወቀ የበዓላችን ቀን ከበሮ ምቱ›› በማለት የዋዜማውን ምስጋና ይጀምራሉ፡፡ የዋዜማው የምስጋና ቀለም እጅግ ሰፊ ስለሆነ በዚህ መዘርዘር አይቻልምና ከዋዜማው ፍጻሜ በኋላ ያለውን ሥርዓት እንመልከት፡፡

በሌሊተ ሆሣዕና ማኅሌት ከመቆሙ በፊት በካህኑ ተባርኮ በሰሙነ ሕማማት ሲነበብ፤ ሲተረጎም የሚሰነብተው ግብረ ሕማማት የተባለው መጽሐፍ ሲነበብ ነው፡፡ ‹‹ስቡሕ ወውዱስ ዘሣረረ ኩሎ ዓለመ››፣ ዓለምን ሁሉ የፈጠረ እግዚአብሔር ፍጹም የተመሰገነ ነው፡፡ የምስጋናዎች ሁሉ ርእስ የዕለቱ የማኅሌቱ ምሥጋና በካህናት በሊቃውንት ይፈጸማል፡፡

ከዐብይ ጾም መግቢያ ጀምሮ በዝምታ የሰነበቱት ከበሮና ጸናጽል የምስጋናው ባለ ድርሻዎች ናቸው፡፡ በዚህ የተጀመረው ማኅሌት ሌሊቱን ሙሉ አድሮ መዝሙር በሚባለው ምስጋና በኩል አድርጎ ሰላም በተባለ የምስጋና ማሳረጊያ ይጠናቀቃል፡፡

ሥርዓተ ዑደት ዘሆዕና

ሥርዓተ ማኅሌቱ ተፈጽሞ፤ ሥርዓተ ቅዳሴው ከመጀመሩ በፊት እስከዚያ ሰዓት ከነበረው ሥርዓት ለየት ያለ ነው፡፡ ይሔውም ሊቃውንቱ የዕለት ድጓ እየቃኙ፣ እየመሩና እየተመሩ፣ ዲያቆኑ ከመዝሙረ ዳዊት የዕለቱን በዓል የተመለከተ ምስባክ በዜማ እያሳመረ፣ ካህናቱም በዓሉን የተመለከተ የዕለቱ ተረኛ ካህን በማቴዎስ ወንጌል ፳፩፡፩-፲፫ ላይ ያለውን ኃይለ ቃል በሚያነብበት ወቅት በአራቱም መዓዘን ቤተ መቅደሱን አንድ ጊዜ ይዞሩታል፡፡

ለምሳሌ ከምዕራቡ ወደ ምሥራቅ ባለው በር ፊት ለፊት በመቆም መምህሩ ‹‹አርእዩነ ፍኖቶ ወንሑር ቤቶ፣ ወደ ቤቱም እንገባ ዘንድ መንገዱን አሳዩን፤››የሚለውን ድጓ ይቃኛሉ፡፡ ካህናቱ እየተከተሉ ያዜማሉ ዲያቆኑ ‹‹ዘምሩ ለእግዚአብሔር ዘየይድር ውስተ ጽዮን፤ በጽዮን የሚገለጥ እግዚአብሔርን አመስግኑ›› እያለ የዕለቱ ተረኛ ካህን ያዜማል፡፡ በዚህ ዐይነት መልክ በአራቱም መዓዝነ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ ዑደቱ ይፈጸማል፡፡

ሥርዓተ ቅዳሴ ዘሆዕና

በዕለተ ሆሣዕና አሁንም የቅዳሴው አገባብ ሥርዓት ከሌሎች ዕለታት ለየት ያለ መሆኑን እንመለከታለን፡፡ ዲያቆናቱ ኅብስቱን በመሶበ ወርቅ ወይኑን በጽዋዕ ይዘው በምዕራብ በር በኩል ይቆማል፡፡ ሠራኢው ዲያቆን በዜማ አሰምቶ ‹‹አርኅው ኖኃተ መኳንንት፣ አለቆች ደጆችን /በሮችን/ ክፈቱ›› ይላል፡፡ ካህኑም በመንጦላዕት ውስጥ ሆኖ ‹‹መኑ ውእቱ ዝንቱ ንጉሠ ስብሐት››፣ ይህን የክብር ንጉሥ የኃያላን አምላክ እግዚአብሔር ነው፤ ብሎ ይመልሳል፡፡ ዲያቆኑ ሦስት ጊዜ የክፈቱልኝ ጥያቄያዊ ዜማውን ካዜመ በኋላ ‹‹ይባእ ንጉሠ ስብሐት››  የክብር ንጉሥ ይግባ ብሎ ፈቅዶለት ይገባል፤መዝ. ፳፫፥፯፡፡

ይህንንም አበው እንደሚከተለው ያመሰጥሩታል፤ አንደኛ ቅዱስ ገብርኤልና ወላዲተ አምላክ በምሥጢረ ብስራት ጊዜ የተነጋገሩት እንደሆነና በመጨረሻም ‹‹ይኩነኒ በከመ ትቤለኒ››፣ እንደ ቃልህ ይደረግልኝ ብላ መቀበሏን ያሳያል፡፡ ሁለተኛው ፈያታዊ ዘየማንና መልአኩ ኪሩብ በማእከለ ገነት የተነጋገሩትን በድርጊት ለማሳየት መሆኑን ያስተምራሉ፡፡ ዋናው ምሥጢር ግን ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ ሊገባ ሲል ብዙዎቹ እንዳይገባ ቢፈልጉም ከፊሎቹ ግን እንዲገባ መፍቀዳቸውን ያሳያል፡፡እንደተለመደው ሥርዓተ ቅዳሴው ከተጠናቀቀ በኋላ ‹‹እግዚአ ሕያዋን›› /የሕያዋን ጌታ/ የተሰኘው ጸሎት በካህናት ተደርሶ ለምእመናን ሥርዓተ ፍትሐት ይደረግላቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ሥርዓተ ፍትሐት ስለማይደረግ፤ በሰሙነ ሕማማት የማይከናወኑ ምሥጢራት በዕለተ ሆሣዕና ይከናወናል፡፡

ምእመናኑ ተባርኮ የተሰጣቸውን የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ ወደ እየቤታቸው ያመራሉ፡፡ የዘንባባው ምሥጢር የተጀመረው በታላቁ አባት በአብርሃም ነው፤ ኩፋ. ፲፫፥፳፩፡፡ ይህን የአባታቸውን ሥርዓት አብነት አድርገው እስራኤል የኤርትራን ባሕር ሲሻገሩ፣ ዮዲት ድል ባደረገች ወቅት ዘንባባ እየያዙ እግዚአብሔርን አመስግነውበታል፡፡ ጌታችን በዕለተ ሆሳሣና ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባም ሽማግሌዎችና ሕፃናት የዘንባባ ዝንጣፊ ይዘው እንደተቀበሉት እናነባለን፡፡‹‹ኢትዮጵያዊያን ምእመናንም ክርስቶስ የሰላም ነጻነት የድኅነት አምላክ መሆኑን ለመመስከር ዘንባባውን ይዘው ወደ ቤታቸው ይገባሉ››፤በእጃቸውም እንደ ቀለበት ያስሩታል፡፡

ለበዓለ ሆሣዕና በሰላም ያደረሰን አምላክ ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም እንዲያደርሰን ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን!