“በምንም አትጨነቁ” (ፊል.፬፥፮)
በሕይወታችን ለሚገጥመን ማንኛውም ችግር ከእግዚአብሔር ዘንድ መፍትሔ ይኖረዋል፡፡ በእርሱ አምነንና ታምነን እስከኖርን ድረስ ከመከራና ከሥቃይ ያወጣናል፡፡ ሰዎች በተለያዩ ጊዜያት በሕይወታቸው ውስጥ ችግር ሊገጥማቸው ይችላል፡፡ የሚረዳቸው ቤተሰብም ሆነ ዘመድ ከሌላቸው ደግሞ ችግራቸውን ስለሚያባብሰው ወደከፋ መከራ ውስጥ ሲገቡ ሰምተንም ሆነ ተመልክተን ይሆናል፡፡ ነገር ግን አምላካችን እግዚአብሔር ሰውን የሚፈትነው ለበጎ እንደሆነ በማወቅና በመረዳት የነገን ተስፋ አድርጎ መኖር ይኖርብናል እንጂ ተስፋ መቁርጥ ወይም ማማረር አይገባም፡፡ በተቻለው መጠን ለኑሯችን ተሯሩጠን የዕለት ጉርሻችን መሙላት እንዲሁም ወደ ተሻለ ሕይወት መትጋት ይገባል፡፡