አብያተ ክርስቲያናት መቃጠላቸውና መዘረፋቸው ተገለጸ

 

                                                                                                                                                                                                                                                                       በሕይወት ሳልለው     

በሲዳማ ጌዴኦ አማሮና ቡርጂ አህጉረ ስብከት በሁላ ወረዳ ቤተክህነት ሥር ወይም በሁላና ቦና ዙሪያ ወረዳ ፫ አብያተ ክርስቲያናት በጥፋት ኃይሎች መቃጠላቸውና ፪ ደግሞ መዘረፋቸው  ተገለጸ፡፡ከሐምሌ ፲፩ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ጀምሮ ለሦስት ተከታታይ ቀናት በቆየው የሲዳማ ዞን ክልል ይሁንልን ጥያቄ ረብሻ ለአብያተ ቤተ ክርስቲያናት መቃጠልና መዘረፍ መንስኤ መሆኑም ተገልጿል፡፡

መጋቤ ጥበባት ቀሲስ ሞላልኝ መርጊያ፤ የሲዳማ፤ጌዴኦ፤አማሮና ቡርጂ አህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ «ሀገረ ስብከቱ ከወረዳ ቤተክህነት ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ጥበቃቸውን እንዲያጠናክሩና ምእመናንም ተደራጅተው ራሳቸውንና አብያተ ክርስቲያናትን እየጠበቁና እንዲከላከሉ መልእክት የተላለፈ ቢሆንም የጥፋት ኃይሎቹ ከአካባቢው የፀጥታ ኃይልና ከምእመናን አቅም በላይ በመሆናቸው የከፋ ጉዳት ሊያደርሱ ችለዋል» በማለት አስረድተዋል፡፡የደረሰው ቃጠሎ በመጀመሪያ በዶያ ቅዱስ ሚካኤል የ፲፰ አባወራዎችን ንብረት በማጥፋት፤ ፸፪ ንዋያተ ቅዱሳትን ሙሉ በሙሉ በእሳት አውድሟል፡፡ ቤተክርስቲያኗን ለማትረፍ ሲረባረቡ የነበሩትን ፲ ሰዎችም አደጋ እንደደረሰባቸው ታውቋል፡፡

ዶያ ቅዱስ ሚካኤል

በሌላ በኩል በ፳፻፰ ዓ.ም. ተመሥርቶ ከኅዳር ፲ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም. ጀምሮ አገልግሎት መስጠት የጀመረው የጋታማ ገብረ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን በአካባቢው ጥፋት ኃይሎች በእሳት ሙሉ ለሙሉ ተቃጥሏል፡፡ ፵፫ አባወራዎች ንብረታቸው ሲዘረፍና ሲቃጠል፤  በአይነት ፵፯ የሚሆኑ ንዋያተ ቅድሳት ሙሉ በሙሉ በእሳት ተቃጥለዋል፡፡

፵፫ የሚሆኑ አባወራዎች ደግሞ ከቤተሰቦቻቸው ጋር በየሰው ቤት ተጠልለው እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የገታማ ገብረ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን

የሉዳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን የውስጥ ንዋያተ ቅድሳት በእሳት ተቃጥለዋል፡፡ የቤተ  ክርስቲያኑ በር፤መስኮት እና መንበር ሲሰባበር፤ደጀ ሰላሙ ሙሉ በሙሉ ወድሟል፡፡ ሥርዓተ አምልኮ ሲፈጽሙ በነበሩ ምእመናን ላይም የሀብት ዝርፊያ በቤታቸው ተካሔዷል፡፡ አቶ ሽፈራው ማሞ በተባሉት አባት ከፍተኛ የአካል ጉዳትም እንደደረሰ ምንጮች አያይዘው ጠቅሰዋል፡፡

ሉዳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን

የጭሮኔ ቅዱስ አማኑኤል ቤተክርስቲያን ታቦተ ሕጉ እስከ አሁን ያለበት ቦታ አልታወቀም፡፡ ቤተ ክርስቲያኑንና ንዋያተ ቅዱሳቱን ያቃጠሉት ግለሰቦች የካህናትን ልብሰ ተክህኖና የሰንበት ተማሪዎች አልባሳትን ለብሰው፤ ቆብ አጥልቀውና መስቀል ይዘው በመዞር ከጨፈሩ በኋላ ተመልሰው ቤተ  ክርስቲያኗን ማቃጠላቸውን የዐይን እማኞች አብራርተዋል፡፡

ንዋያተ ቅዱሳቱን

በተጨማሪም በ፲፱፻፱ የተመሠረተው የቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን ደግሞ በደረሰው ጥቃት ሙሉ ለሙሉ ተዘርፏል፡፡ አገልግሎት እየሰጡ የነበሩ መቃብር ቤቶች በርና መስኮቶች ተሰባብሯል፡፡

የቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ  ክርስቲያን

ሦስት ኦርቶዶክሳውያን በአሰቃቂ ሁኔት ተገድለዋል፡፡ ፪፻፶ ምእመናን ተሰደው ቦሬ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ተጠልለው ይገኛሉ፡፡በተፈጠረው ችግር የ፹፭ ዓመቱ አቶ ግርማ መልካ መንገድ ላይ ተገድለው ሲገኙ፤አቶ የኔነህ ተስፋዬ መገደላቸውን፤ እና ወጣት አድሱ የኔነህ ደግሞ አባቱን እያሳከመ እንዳለ መገደሉን ተገልጿል፡፡

ይህን ችግር ለመቅረፍ ሀገረ ስብከቱ ከመከላከያ ሠራዊት ጋር በመተባበር በአካባቢው ላይ የነበሩትን ምእመናን ለመታደግ ችሏል፡፡ የተጎዱ ምእመናንን ለመደገፍና የተቃጠሉ አብያተ ክርስቲያናትን መልሶ ለማቋቋም ኮሚቴ መቋቋሙን የሐዋሳ ማእከል ገልጿል፡፡

በመሆኑም የኮሚቴው አባላት በጥፋቱ የተቃጠሉ አብያተ ክርስቲያናት መረጃ በመሰብሰብ፣ ምእመናንን በማጽናናትና ከሐዋሳ ከተማ ነዋሪዎች ድጋፍ በማሰባሰብ ተጎጂዎችን እየረዱ እንደሆነ ሀገረ ስብከቱ ገልጿል፤ ይበልጥ ለመደገፍ በባንክ አካውንት ቁጥር 1000290647936፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ውስጥ ከፍቶ ገንዘብ በማሰባሰብ ላይ ይገኛል፡፡

በአፋን ኦሮሞ የተዘጋጁ ሦስት የኮርስ መጻሕፍት ታትመው በሥርጭት ላይ የሚገኙት

 

– Barattootni Yaa’iiwwan Mooraa Afaan Oromoon barattan Baga Gammaddan! Kitaaboleen koorsii sadii Afaan Oromootiin, adeemsa barnoota isa haaraatiin qophaa’anii isiniif dhiyaataniiru! Kanneen kaanis dhiyootti isin harka gahu!

 

በአፋን ኦሮሞ የምትማሩ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች፡- እንኳን ደስ አላችሁ!

በአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት መሠረት በአፋን ኦሮሞ የተዘጋጁ ሦስት የኮርስ መጻሕፍት ታትመው ቀርበውላችኋል! ሌሎቹም መጻሕፍት በቅርቡ ታተመው በእጃችሁ ይገባሉ!!!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መገናኛ ብዙኃን አገልግሎት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ኅዳር ፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ድርጅት አቋቁማ መደበኛ የሃያ አራት ሰዓት የቴሌቭዥን መርሐ ግብር ከጀመረች ከሁለት ዓመታት በላይ ተቈጥረዋል፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን፣ የቴሌቭዥን ሥርጭቱን አጀማመርና ጠቅላላ አገልግሎት በአጭሩ የሚያስቃኝ ጽሑፍ ይዘን ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ ይኹንላችሁ!

በቤተ ክርስቲያናችንና በአገራችን ታሪክ እንደሚታወቀው ያልተበረዘና ያልተከለሰ ኦርቶዶክሳዊ ዶግማና ሥርዓተ አምልኮ፣ የትርጓሜና የባሕረ ሐሳብ ትምህርት፣ በብራና የተጻፉ ቅዱሳት መጻሕፍት፣ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት፣ መሥዋዕተ ኦሪት ይቀርብባቸው የነበሩና እስከ አሁን ድረስ ተጠብቀው የቆዩ ጥንታውያን አድባራትና ገዳማት፣ የቅዱስ ያሬድ የዜማ ድርሰቶች፣ ሥርዓተ ማኅሌትና የመንፈሳውያን በዓላት አከባበር ሥርዓት፣ ወዘተ. የመሳሰሉ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቅርሶች በሙሉ ዓለምን የሚያስደምሙ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሀብቶችና ልዩ ስጦታዎች ናቸው፡፡

ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ በመጽሐፋቸው እንደ ጠቀሱት ሙሉ ትምህርት፣ ፍጹም ቋንቋ ከነፊደሉ፣ ሥነ ጥበብ፣ ሥነ ጽሑፍ፣ ኪነ ጥበብ፣ ታሪካዊና ጥንታዊ ቅርስ፣ እምነት፣ ነጻነት፣ አንድነት፣ የአገር ፍቅር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለኢትዮጵያ ሕዝብ ካበረከተቻቸው ብዙ ስጦታዎች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ እንደ ብፁዕነታቸው ማብራሪያ አሁንም ቢኾን ትውልዱ ጀግንነትን፤ አገር ወዳድነትን፤ ለሃይማኖት፣ ለታሪክና ለባህል ተቆርቋሪነትን ይዞ እንዲያድግ በማስተማርና በማበረታታት ረገድ ቤተ ክርስቲያን ድርሻ አላት (የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ)፡፡

በረከታቸው ይደርብንና ካሁን በፊት በየጊዜው የተነሡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በቃል በማስተማርና መጻሕፍትን በማሳተም እነዚህን ሀብቶቿን ለመጠበቅና ለዓለም ለማስተዋወቅ ያደረጉት አስተዋጽዖ ከፍተኛ ነው፡፡ ከኅትመት ውጤቶች ባሻገርም መገናኛ ብዙኃንን በመጠቀም ቃለ እግዚአብሔር ለማስተማር ቀደምት የቤተ ክርስቲያን አባቶች ብዙ ደክመዋል፡፡ ለዚህም በአሁኑ ሰዓት አገልግሎት ባይሰጥም ቀደም ሲል የተጀመረው የሬድዮ መርሐ ግብር እንደዚሁም አሁንም አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙት መንፈሳዊ መጽሔቶች፣ ጋዜጦችና ድረ ገጾች ማስረጃዎች ናቸው፡፡ መገናኛ ብዙኃንን በተለይም የቴሌቭዥን ሥርጭትን በመጠቀም ረገድ እንደ ግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ያሉ አኃት አብያተ ክርስቲያናት ተሞክሮ በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው፡፡

ብዙ ጊዜ እንደሚነገረው በሁለት ቋንቋዎች ብቻ የሚግባቡና በቍጥር ከዐሥር ሚሊዮን የማይበልጡ ምእመናን የሚገኙባት የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከዐሥር በላይ የቴሌቭዥን ጣቢያዎችን በመክፈት ትምህርተ ወንጌልን በመላው ዓለም በማዳረስ ላይ ትገኛለች፡፡ በምእመናን ብዛት ከኢትዮጵያ ብዙ እጥፍ የምታንሰዋ ግብጽ በዚህ መልኩ የመገናኛ ብዙኃን ተጠቃሚ ከኾነች ከሰማንያ በላይ ቋንቋዎችን የሚናገሩና ወደ አምሳ ሚሊዮን የሚደርሱ ምእመናን ባለቤት ለኾነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንድ ብቻ ሳይኾን በርካታ የቴሌቭዥን ጣቢያዎች እንደሚያስፈልጓት አያጠያይቅም፡፡ ይህን እውነት ከግምት ውስጥ በማስገባት ቅዱስ ሲኖዶስ ባሳለፈው ውሳኔ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከዓመታት በፊት የሃያ አራት ሰዓት የቴሌቭዥን መርሐ ግብር ማሠራጨት ጀምራለች፡፡

በ፳፻፱ ዓ.ም በታተመው ዐዋጅ ነጋሪ መጽሔት እንደ ተገለጸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ድርጅት እንዲቋቋም ለማድረግ ጥናት እንዲካሔድ ለመጀመሪያ ጊዜ የተወሰነው በጥቅምት ወር ፳፻፮ ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ነው፡፡ በዚያው ዓመት በግንቦት ወር በተካሔደው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ፤ ሦስት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ በርካታ ባለሙያዎችና ሊቃውንት የተሳተፉበት ጥናት ለምልዓተ ጉባኤው ቀርቦ የድርጅቱ መተዳደሪያ ደንብ፣ የአርትዖትና የቴክኒክ መመሪያ ጸድቆ ሥራው እንዲጀመር ተወስኗል፡፡

ድርጅቱ፣ በቋሚ ሲኖዶስ በተሰየመው የቦርድ ሥራ አመራር ከአንድ ዓመት በላይ ተጨማሪ ጥናቶችን ሲያደርግ ቆይቶ በጥቅምት ወር ፳፻፰ ዓ.ም ለሥራው የሚያስፈልገው በጀት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተወስኖለታል፡፡ ቦርዱ የተፈቀደውን በጀትና የተጠናውን ጥናት ወደ ተግባር ለመለወጥ ውድድር በማድረግ ለድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ እንዲቀጠር አድርጓል፡፡ በቅዱስ ሲኖዶስ በጸደቀው የድርጅቱ መተዳደሪያ ደንብ መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ድርጅት ዋና መሥሪያ ቤት በጠቅላይ ጽ/ቤቱ ግቢ ውስጥ ይገኛል፡፡

በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት አባታዊ መመሪያ ሰጭነት አስፈላጊ ቅድመ ኹኔታዎችን በሟሟላት፣ ተደጋጋሚ ውይይቶችንና ዓለም አቀፍ ዳሰሳዎችን በማድረግ ለሥርጭቱ ያመነበትን የሳተላይት ጣቢያ አወዳድሮ በመምረጥና የውል ስምምነት በማዘጋጀት በአፋጣኝ የሥርጭት አገልግሎቱን ጀምሯል፡፡ በኢየሩሳሌም ከሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት ጋር በተደረገ ስምምነት መሠረትም የቴሌቭዥን መርሐ ግብራቱ በአገር ውስጥ ተዘጋጅተው ኢየሩሳሌም በሚገኘው የሳተላይት ድርጅት አማካይነት ይሠራጫሉ፡፡ የቴሌቭዥን ጣቢያው የሥርጭት አድራሻም የሚከተለው ነው፤

Ethiopian Orthodox Tewahedo Church Television (EOTC TV)

Satellite: Eutelsat/Nilesat (ኢትዮጵያ)

Frequency …. 11353 (5) Vertical

Symbol rate …. 27500/FEC…5/6

Satellite: Galaxy 19 (G-19) (ሰሜን አሜሪካ)

Frequency …. 11960/Vertical

Symbol rate …. 22000/FEC…3/4

የድርጅቱ መዋቅርና አገልግሎት የተሟላ እንዲኾን በአስተዳደርና ፋይናንስ፣ በመርሐ ግብር ዝግጅት እና በቴክኒክ ዘርፍ ቦርዱ በሰየማቸው የቅጥርና የምዘና ኮሚቴ አባላት አስፈጻሚነት የሠራተኞች የቅጥር ሒደት ተከናውኗል፡፡ በቅጥር ሒደቱም ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት በወጣው ማስታወቂያ መሠረት ላመለከቱ ሠራተኞችና ለቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ቅድሚያ ተሰጥቷል፡፡ የሥርጭቱን አጠቃላይ ይዘትና ዓይነት በተመለከተም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የቦርድ አባላትና የሚዲያ ባለሙያዎች የሚገኙበት የይዘትና የዓይነት ዝግጅት ኮሚቴ ተዋቅሯል፡፡ ይዘቱንና ዓይነቱን የሚያርምና የሚገመግም የኤዲቶሪያል ኮሚቴም ተቋቁሟል፡፡ የኤዲቶሪያል ኮሚቴው አባላትም በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪጁ የተሰየሙና በቦርዱ የተመረጡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ናቸው፡፡ ድርጅቱ ካለበት ሠፊ ሥራና ከባድ ሓላፊነት አኳያ በቋሚነት የሚያስፈልጉት በርከት ያሉ ስቱዲዮዎች፣ የቅድመ ሥርጭትና ድኅረ ሥርጭት ተግባራት ማከናወኛነት የሚያገለግሉ በርካታ ክፍሎች፣ አብያተ መዛግብት፣ አስተዳደርና የባለሙዎች ቢሮዎች እንዲሟሉ ለማድረግ ድርጅቱ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና ከሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ አባቶች መመሪያን በመቀበል በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡

(ምንጭ፡- ዐዋጅ ነጋሪ መጽሔት፣ ፱ኛ ዓመት፣ ቍጥር ፲፪፤ ጥቅምት ፳፻፱ ዓ.ም፣ ገጽ 77-78)፡፡

ጽሑፋችንን ለማጠቃለል ያኽል፣ የሥልጣኔ ውጤቶች በተበራከቱበትና አብዛኞቹ ወጣቶች ዓለማዊ መልእክት በሚያስተላልፉ መገናኛ ብዙኃን ተጽዕኖ ውስጥ በወደቁበት በአሁኑ ዘመን ወጣቱን ትውልድ ወደ ጥፋት ከሚወስዱ መልእክቶች ለመታደግ ያመች ዘንድ ትምህርተ ወንጌልን ለማዳረስና ኦርቶዶክሳዊ ሕይወትን ለማስተማር፤ የቤተ ክርስቲያናችንን ሥርዓተ እምነት፣ ትውፊትና ልዩ ልዩ ሀብቷን ወይም የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቅርሶቿን ለትውልድ ለማቆየት ብሎም ለዓለም ለማስተዋወቅ፤ እንደዚሁም በየጊዜው በቅዱስ ሲኖዶስ የሚወጡ መመሪያዎችንና መልእክቶችን በአፋጣኝ ወደ ሕዝበ ክርስቲያኑ ለማስተላለፍ መገናኛ ብዙኃንን፣ ከመገናኛ ብዙኃንም የቴሌቭዥን ሥርጭትን መጠቀም ከፍተኛ ጠቀሜታ አለው፡፡

በዚህ ዓላማ መሠረት የተጀመረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቴሌቭዥን ሥርጭትም በልዩ ልዩ ዓምዶቹ ትምህርተ ወንጌል በመስጠት፤ ቅዱሳት መካናትን፣ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ የቤተ ክርስቲያን ቅርሶችን በማስተዋወቅ፤ ጠቃሚ የኾኑ ማኅበራዊና ወቅታዊ ጉዳዮችን በማቅረብና መንፈሳዊ ዜናዎችን በመዘገብ አገልግሎቱን እንደ ቀጠለ ነው፡፡ የቴሌቭዥን ሥርጭቱን በተቀላጠፈ መልኩ ለማስቀጠልና ለምእመናን ለማዳረስ ይቻል ዘንድም መላው ሕዝበ ክርስቲያን ሐሳብ አስተያየት በመስጠትና በሌላም ልዩ ልዩ መንገድ በተቻለን አቅም ዂሉ የቤተ ክርስቲያናችንን የመገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ድርጅት በመደገፍ የሚጠበቅብንን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት እንወጣ ሲል የማኅበረ ቅዱሳን አማርኛ ድረ ገጽ ዝግጅት ክፍል መንፈሳዊ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የፀረ ተሐድሶ አገልግሎት በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት

ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፣ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፲፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹እንግዲህ ሒዱና በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው አሕዛብን ዅሉ አስተምሩ፤›› (ማቴ. ፳፰፥፲፱) በማለት ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባዘዘው ቃል መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረታዊ ተልእኮዋ ስብከተ ወንጌልን ለዓለም ማዳረስና ያላመኑትን በማሳመን፤ ያመኑትን እንዲጸኑ በማድረግ ዅሉንም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ማቅረብ ነው፡፡ ነገር ግን አካላቸው ከውስጥ፣ ልቡናቸው ከውጭ የኾነ፤ ራሳቸውን ተሐድሶ ብለው የሚጠሩ፤ በኅቡዕም፣ በገሃድም አስተምህሮዋን የሚፃረሩና ምእመናኗን የሚያደናግሩ የቤተ ክርስቲያን ጠላቶች ለሐዋርያዊ ተልእኮዋ እንቅፋት ኾነውባታል፡፡ ይህን የመናፍቃንን ሤራ ለመከላከልም ልዩና ወጥ አሠራር መዘርጋት ተገቢ መኾኑ ስለ ታመነበት ቅዱስ ሲኖዶስ በወርኃ ግንቦት ፳፻፰ ዓ.ም ባደረገው ምልዓተ ጉባኤ የፀረ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ ኮሚቴ እንዲቋቋም ውሳኔ አሳልፏል፡፡

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በዛሬው ዝግጅታችን የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ ከተግባር ላይ አውለው ሐዋርያዊ ተልእኳቸውን በትጋት እያከናወኑ ከሚገኙ አህጉረ ስብከት መካከል የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ አገልግሎትን በአጭሩ ልናስታውሳችሁ ወደድን፡፡ መልካም ንባብ!

መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት፣ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ

በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የሚመራው የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ዐሥራ አምስት ወረዳ አብያተ ክህነት እና ከአራት መቶ በላይ አብያተ ክርስቲያናት እንዳሉት ከጽ/ቤቱ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት እንደ ገለጹልን፣ ሀገረ ስብከቱ ሰበካ ጉባኤያትን በየቦታው በማዋቀር፣ ሰባክያነ ወንጌልንና ካህናትን በመመደብ የስብከተ ወንጌል ተልእኮውን በማስፋፋት ላይ ይገኛል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንቅፋት የኾነውን የተሐድሶ ነን ባዮች መናፍቃንን እንቅስቃሴ ለመቈጣጠርም የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ ተቀብሎ የፀረ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ ኮሚቴን አቋቁሞ አገልግሎቱን ቀጥሏል፡፡ ከሥራ አስኪያጁ ማብራርያ እንደ ተረዳነው ኮሚቴው የተቋቋመው ከሀገረ ስብከት ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ነው፡፡ ዓላማው ምእመናን ከኑፋቄ ትምህርት ተጠብቀው በኦርቶዶክሳዊው አስተምህሮ ጸንተው እንዲኖሩ ማድረግ ሲኾን፣ አባላቱም ከሀገረ ስብከቱ ሠራኞች ጀምሮ ከካህናት፣ ከሰንበት ት/ቤት ወጣቶች፣ ከማኅበረ ቅዱሳን አባላትና ከምእመናን የተመረጡ ናቸው፡፡

‹‹የመናፍቃንን ሤራ ለማፍረስና ምእመናንን ከቅሰጣ ለመከላከል የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴው ድርሻ የጎላ ነው›› ይላሉ ሥራ አስኪያጁ የኮሚቴውን አስፈላጊነት ሲገልጹ፡፡ ሀገረ ስብከቱ በአፋጣኝ ኮሚቴ አቋቁሞ አገልግሎት መጀመሩ እንደሚያስመሰግነው የሚያብራሩት መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ፣ በዚህ ተግባሩም ለሌሎች አህጉረ ስብከት እንደ አብነት ከመጠቀሱ አልፎ የልምድ ተሞክሮ በማካፈል ላይ መኾኑንም አስገንዝበዋል፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል ቤተ ክርስቲያን በሰጠችው አደራ መሠረት አባላቱን በማስተባበር፣ መመሪያ በማዘጋጀት፣ ሥልጠናዎችን በመስጠት፣ መረጃዎችን በማቅረብና የቁሳቁስ ድጋፍ በማድረግ ከሀገረ ስብከቱ ጎን ኾኖ የኮሚቴውን አገልግሎት እየደገፈ እንደሚገኝና የማእከሉ ድጋፍም ለሀገረ ስብከቱም ኾነ ለኮሚቴው ብዙ ሥራ እንዳቀለለት አስረድተዋል፡፡

ሊቀ ጉባኤ ቆሞስ አባ ተክለ ሃይማኖት ወልዱ፣ በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት የናዝሬት ደብረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ካቴድራል አስተዳዳሪ እና የሀገረ ስብከቱ ፀረ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ ኮሚቴ ሰብሳቢ

በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት የናዝሬት ደብረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ካቴድራል አስተዳዳሪ ሊቀ ጉባኤ ቆሞስ አባ ተክለ ሃይማኖት ወልዱ ደግሞ የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴው ሰብሳቢ ናቸው፡፡ እርሳቸው እንዳብራሩት ኮሚቴው አገልግሎቱን የጀመረው በወርኃ ታኅሣሥ ፳፻፱ ዓ.ም ሲኾን፣ ወደ አገልግሎት ከመግባቱ አስቀድሞ መተዳደርያ ሕጉንና የሥነ ምግባር ደንቡን፣ እንደዚሁም የሥልጠና ሰነዱን በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ከማጸደቁ ባሻገር ለአባላቱ የሥራ ድርሻቸውን አሳውቋል፡፡ የኮሚቴውን ዓላማ ለምእመናን ማስተዋወቅ፤ በየዐውደ ምሕረቱ የሚሰጠው ትምህርት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ማድረግና ሥልጠና መስጠት ከኮሚቴው ተግባራት መካከል የሚጠቀሱ ሲኾን፣ የመናፍቃንን እንቅስቃሴ፣ ጫናዎቹንና መከላከያ መንገዶቹን በማመላከት ኦርቶዶክሳዊውን አስተምህሮ ማሳወቅም በሥልጠናው የተካተቱ ጉዳዮች ናቸው፡፡ ኮሚቴው፣ ካሁን ቀደም ለሀገረ ስብከቱና ለየወረዳ ቤተ ክህነቱ ሠራተኞች፣ ለካህናት፣ ለሰንበት ት/ቤት አባላትና ለማኅበረ ምእመናን የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርትና ሥልጠና ሰጥቷል፡፡ ሥልጠናውም በናዝሬት ከተማ በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ሙሉ ለሙሉ የተሰጠ ሲኾን፣ በየገጠሩ ለሚኖሩ ምእመናንም በቅርብ ጊዜ እንዲዳረስ ይደረጋል፡፡

ከሰብሳቢው ገለጻ እንደ ተረዳነው ስለ መናፍቃን እንቅስቃሴ መረጃ በማሰባሰብና ለምእመናን የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና በመስጠት አገልግሎቱን የጀመረው ኮሚቴው፣ ወደፊትም ይህን መንፈሳዊ ተልእኮዉን አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡ ተግባሩን በሥርዓት ለማከናወን እንዲያመቸውም በሳምንት አንድ ቀን ጉባኤ ያካሒዳል፡፡ የኮሚቴው አባላት እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው መሥራታቸው፤ ምሥጢር ጠባቂነታቸው፤ ከራስ ሐሳብና ጥቅም ይልቅ የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ የሚያስቀድሙና ልዩነቶችን በውይይት የመፍታት ልምድ ያዳበሩ መኾናቸው ለአገልግሎቱ መፋጠን ከፍተኛ አስተዋፅዖ አለው ይላሉ ሊቀ ጉባኤ የአባላቱን ጥንካሬ በማድነቅ፡፡

ማኅበረ ምእመናን ኦርቶዶክሳዊውን አስተምህሮ በሚገባ እንዲያውቁ የሚያበቃ ትምህርትና ሥልጠና መስጠት፤ በየዐውደ ምሕረቱ የሚቀርበው ትምህርተ ወንጌል በስፋት እንዲቀጥል መደገፍ፤ የአፅራረ ቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴ እንዲዳከምና ኦርቶዶክሳዊው አስተምህሮ እንዲስፋፋ ማድረግ፤ ሐሰተኞች መምህራንን በመከታተል ከስሕተታቸው እንዲታረሙ መምከር፤ ካልተመለሱም ተወግዘው እንዲለዩ ለቅዱስ ሲኖዶስ ማቅረብ ኮሚቴው ወደፊት ለማከናወን ያቀዳቸው ተግባራት መኾናቸውንም ሊቀ ጉባኤ ቆሞስ አባ ተክለ ሃይማኖት ጨምረው ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም አፅራረ ቤተ ክርስቲያን በተለይ ራሳቸውን ‹ተሐድሶ› ብለው የሚጠሩ መናፍቃን ማን ይነካናል ብለው በድፍረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እየተሳደቡ፣ አባቶችንም እያጥላሉ እንደ ኾነ፤ የተሳሳተ ትምህርታቸውን ለማስፋፋት ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ እንደሚገኙ፤ ቍጥራቸውም በዘመናት ሳይኾን በቀናት እየጨመረ እንደ መጣ ጠቅሰው፣ በሀገረ ስብከቱ የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ የተቋቋመው እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ ይህን የመናፍቃኑን እንቅስቃሴ ለመከላከል መኾኑን አብራርተዋል፡፡

አቶ ኃይለ ኢየሱስ ከበረ፣ የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴው ጸሐፊ

የፀረ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ ኮሚቴው ጸሐፊ አቶ ኃይለ ኢየሱስ ከበረ በበኩላቸው ኮሚቴው ከሀገረ ስብከቱ ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ባለው መዋቅር ልዩ ልዩ ክፍሎችን የሚመሩ ሰባት አባላት እንዳሉት፤ ከክፍሎቹ መካከልም የትምህርትና ግብረ መልስ፣ መረጃና ትንተና፣ ቁጥጥርና ክትትል፣ እንደዚሁም የመርሐ ግብር ክፍል ተጠቃሾች መኾናቸውን አስታውሰው፣ የመናፍቃንን እንቅስቀሴ በሚመለከት ለወጣቶች ልዩ ሥልጠና ለመስጠት መታቀዱንም ጠቁመዋል፡፡ ጸሐፊው እንዳስረዱት፣ ኮሚቴው ለመጀመሪያ ጊዜ እንደ መቋቋሙ የልምድ ማነስ፣ የመረጃ ችግር፣ የድጋፍ ሰጪ አካላት እጥረት እና የመናፍቃን እንቅስቃሴ በፍጥነት መስፋፋት ከመሰናክሎች መካከል የሚጠቀሱ ሲኾን፣ በአዎንታዊ መልኩ ከሀገረ ስብከት እስከ አጥቢያ የሚደርስ ሰፊ መዋቅር ያለው መኾኑ፤ አገልግሎቱ በአጭር ጊዜ ውስጥ በስፋት መዳረሱ፤ ወጥነት ባለው አሠራር መዋቀሩ የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴውን አገልግሎት በአርአያነት እንዲጠቀስ ያደርገዋል፡፡

በመጨረሻም የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ፣ የኮሚቴው ሰብሳቢ እና ጸሐፊው የሚከተለውን መልእክት አስተላልፈዋል፤

‹‹በቤተ ክርስቲያን ላይ ፈተና ቢበዛባትም የተመሠረተችው በክርስቶስ ደም ነውና አትሸነፍም›› የሚሉት መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት፣ የኮሚቴው ዓላማ ከግብ ደርሶ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ ለማፋጠን ይቻል ዘንድ አባቶች ምእመናንን ተግተው ቃለ እግዚአብሔርን እንዲያስተምሩ፤ ምእመናኑም ትክክለኛ እረኞቻቸውን በመለየት ቃሉን እንዲማሩ፤ በአጠቃላይ መላው ሕዝበ ክርስቲያን በፈተናዎች ሳይደናገጡ በጸሎት እንዲበረቱና ራሳቸውንም ሌሎችንም ከኑፋቄ ትምህርት በመጠበቅ ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

ሊቀ ጉባኤ ቆሞስ አባ ተክለ ሃይማኖት ወልዱ በበኩላቸው፤‹‹ከአሁን በፊት የተሐድሶ መናፍቃን ጉዳይ የማኅበረ ቅዱሳን የፈጠራ ወሬ ነው ይባል ነበር፡፡ አሁን ግን ጉዳዩ ቤተ ክርስቲያንን የሚፈታተን መኾኑ ተደርሶበታል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም የመናፍቃኑን እንቅስቃሴ በመከላከል ረገድ ከሕዝበ ክርስቲያኑ ጋር ኾኖ የሚጠበቅበትን የልጅነት ድርሻ በመወጣት ላይ ነው፡፡ ወደፊትም በዚህ መንፈሳዊ አገልግሎቱ ሊቀጥል ይገባል›› ሲሉ አባታዊ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡ በተጨማሪም የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴው ዓላማ ኦርቶዶክሳዊውን አስተምህሮ በማስጠበቅ እነርሱን ለመንግሥተ ሰማያት ማዘጋጀት እንደ ኾነ ተገንዝበው፣ በመላው ዓለም የሚገኙ ምእመናን በሐሳብ፣ በገንዘብ፣ በዕውቀት፣ ወዘተ. በመሳሰሉ መንገዶች አገልግሎቱን በመደገፍ የቤተ ክርስቲያንን ችግር ሊቀርፉና የስብከተ ወንጌል ተልእኮውን ሊያስፋፉ እንደሚገባ በኮሚቴው ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፣ የሀገረ ስብከቱ፣ የየወረዳ አብያተ ክህነቱና የየሰበካ ጉባኤያቱ ሠራተኞች፤ የየሰንበት ት/ቤቶች ወጣቶች፣ የማኅበረ ቅዱሳንና የሌሎችም መንሳውያን ማኅበራት ድጋፍ ኮሚቴው አገልግሎቱን በአግባቡ እንዲወጣ አድርጎታል የሚሉት አቶ ኃይለ ኢየሱስ ከበረ ደግሞ፣ ለወደፊትም ከዚህ በበለጠ ውጤታማ ይኾን ዘንድ የአባቶች፣ የወንድሞችና እኅቶች ተሳትፎ እንዳይለየን ሲሉ ድጋፍ ጠይቀዋል፡፡ የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴውን ዓላማ በፍጥነት ከግብ ለማድረስ ይቻል ዘንድም ዅሉም ምእመናን በተለይ የሰንበት ት/ቤትና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት የመናፍቃንን እንቅስቃሴ እየተከታተሉ ለኮሚቴው እንዲያቀርቡ፤ ማኅበረ ቅዱሳንን የመሰሉ ድጋፍ ሰጪ አካላትም በቁሳቁስ፣ በገንዘብ፣ በሐሳብ፣ በመረጃ አቅርቦትና ሥልጠና በመስጠት ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ በማሳሰብ ጸሐፊው መልእክታቸውን አጠቃለዋል፡፡

ዝግጅት ክፍላችንም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት አስተምህሮ ሳይበረዝና ሳይከለስ ለትውልዱ ይዳረስ ዘንድ የፀረ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ኮሚቴ እንዲቋቋም ውሳኔ በማሳለፉ ለቅዱስ ሲኖዶስ ያለውን አክብሮት እየገለጸ፣ እንደ ምሥራቅ ሸዋ ዅሉ ሌሎች አህጉረ ስብከትም ሐዋርያዊ ተልእኮውን እንዲያስፋፉና የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ አቋቋመው የመናፍቃንን ሤራ እንዲከላከሉ በመደገፍ ዅላችንም የቤተ ክርስቲያናችንን አስተምህሮ የመጠበቅና የማስጠበቅ ሓላፊነታችንን እንወጣ ሲል ያሳስባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የወደቁትን እናንሣ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹እናንተ የአባቴ ቡሩካን፣ ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ትወርሱ ዘንድ ኑ፡፡ ተርቤ አብልታችሁኛልና፤ ተጠምቼ አጠጥታችሁኛልና፤ እንግዳም ኾኜ ተቀብላችሁልና፡፡ ታርዤ አልብሳችሁኛልና፤ ታምሜም ጐብኝታችሁኛልና፤ ታስሬም ወደ እኔ መጥታችሁ ጠይቃችሁኛልና፤›› (ማቴ. ፳፭፥፴፬-፴፯) ተብሎ በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈው፣ ክርስቲያኖች የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ ከምንበቃባቸው ትእዛዛት መካከል አንደኛው ሰዎችን መርዳት ነው፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎችን መርዳት የሚያስገኘውን ሰማያዊ ዋጋ ሲገልጽም ‹‹በእኔ ካመኑ ከእነዚህ ከታናናሾች ወንድሞቼ ለአንዱ ያደረጋችሁትን ዅሉ ለእኔ አደረጋችሁት፤›› በማለት ቃል ኪዳን ሰጥቷል (ማቴ. ፳፭፥፵)፡፡

ይህን ቃል ባለማስተዋልና በሥጋዊ ስንፍና በመያዝ ለራሳችን ድሎት ብቻ የምንሽቀዳደም ራስ ወዳዶች ብዙዎች ብንኾንም፣ በአንጻሩ ቃሉን ተስፋ በማድረግ በገዛ ፈቃዳቸው ተነሣሥተው፣ በማኅበር ተሰባስበው ሰዎችን በመርዳት ክርስቲያናዊ ተግባር የሚፈጽሙ በጎ አድራጊ ምእመናን በየአገሩ አሉ፡፡ ጧሪ ቀባሪ ያጡ ሕሙማንንና አረጋውያንን የማሳከም፣ የመከባከብና ራሳቸውን እንዲችሉ የማገዝ ዓላማና ርእይ ሰንቀው በአዲስ አበባ ከተማ ከተቋቋሙ የበጎ አድራጎት ማኅበራት መካከል የወደቁትን አንሡ የነዳያን መርጃ ማኅበር አንዱ ነው፡፡ የማኅበሩ ተቋማዊ ጠባይዕና አሠራር ምን ዓይነት ነው? የገቢ ምንጩ ምንድን ነው? ሒሳብ አያያዙስ እንዴት ነው? ድጋፍ የሚያስፈልጋቸውን ሰዎች የሚያሰባስበው በምን ዓይነት መሥፈርት ነው? የሚሉና ሌሎች ጥያቄዎችን አንሥተንላቸው፣ የማኅበሩ መሥራች አቶ ስንታየሁ አበጀ ማብራርያ ሰጥተውናል፡፡ የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በዛሬው ዝግጅታችን፣ መሥራቹ የሰጡንን ቃለ ምልልስ እና ማኅበሩ ባሳተመው ብሮሸር ላይ የተጠቀሱ ተግባራቱን መነሻ በማድረግ የማኅበሩን አገልግሎት እናስቃኛችኋለን፡፡ መልካም ንባብ!

አቶ ስንታየሁ አበጀ፣ የማኅበሩ መሥራች

የወደቁትን አንሡ የነዳያን መርጃ ማኅበር ከዐሥራ ዘጠኝ ዓመታት በፊት በአቶ ስንታየሁ አበጀ አስተባባሪነት ተመሠረተ፡፡ እኒህ ምእመን በደረሰባቸው ሥጋዊ ችግር ምክንያት ጠያቂ አጥተው በየጎዳናውና በየመቃብር ቤቱ ሲንገላቱ ኖረው ከዓመታት በኋላ ቆመው መሔድ ስለ ተቻላቸው ‹‹እግዚአብሔር በልዩ ጥበቡ እኔን ከወደቅሁበት ያነሣኝ ለትምህርት ነው፡፡ ስለዚህ እንደኔ የሚጠይቃቸው ያጡ ሰዎችን ከየወደቁበት ማንሣት አለብኝ›› የሚል መልካም ርእይ ሰንቀው፣ ከበጎ ፈቃደኞች ጋር ኾነው መስከረም ፩ ቀን ፲፱፻፺ ዓ.ም ‹‹የወደቁትን አንሡ›› በሚል ስያሜ የነዳያን መርጃ ማኅበር አቋቋሙ፡፡ ማኅበሩ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ነዳያንን የመደገፍ፣ አረጋውያንን የመንከባከብና ጧሪ ቀባሪ ያጡ ወገኖችን የመርዳት ተልእኮውን ቀጥሏል፡፡

መሥራቹ እንደ ገለጹልን ማኅበሩ ለዓላማው ማስፈጸሚያ የሚውለውን የገቢ ምንጭ የሚያገኘው ከአባላቱ ወርኃዊ መዋጮ፣ እንደዚሁም በአገር ውስጥና በውጭ አገር ከሚኖሩ በጎ አድራጊዎች ነው፡፡ በሒሳብ አያያዝም ዘመናዊና ሕጋዊ አሠራርን በመከተል ገቢውንና ወጪውን በደረሰኝ ይቈጣጠራል፤ ኦዲትም ያስደርጋል፡፡ የሚተዳደረውም በቦርድ አወቃቀር ሲኾን፣ ሕጋዊ ፈቃድና እውቅና አግኝቶ በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኅበራት ኤጀንሲ ተመዝግቧል፡፡ የራሱ መተዳደርያ ደንብና ስልታዊ ዕቅድም አዘጋጅቷል፡፡ ወደፊት ለሚያከናውናቸው ተግባራትም ከፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ቢሮ፣ ከሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ጋር የፕሮጀክት ስምምነት ተፈራርሟል፡፡ ማኅበሩ ዘር፣ ሃይማኖት፣ ፆታ ሳይለይ ልዩ ርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ሰዎች ከሠላሳ በላይ በሚኾኑ ሠራተኞቹ አማካይነት ድጋና ክብካቤ ያደርጋል፡፡ በዚህ ተግባሩ ባበረከተው አገራዊ አስተዋጽዖም በየጊዜው ከመንግሥትና ከሌሎች ልዩ ልዩ ተቋማት የምስጋና ገጸ በረከትና የሜዳልያ ሽልማት ተበርክቶለታል፡፡

የማኅበሩ ማእከል ውጫዊና ውስጣዊ ገጽታ በከፊል

ከጽ/ቤቱ ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው ማኅበሩ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ እስከ ፳፻፰ ዓ.ም ድረስ ለስድስት መቶ ሃያ ሦስት ሰዎች የምግብ፣ የመጠለያና የሕክምና ድጋፍ አድርጓል፡፡ ከእነዚህ መካከል ሁለት መቶ አንዱ በማኅበሩ በተደረገላቸው ርዳታ ከሕመማቸው ተፈውሰዋል፡፡ አራቱ በማኅበሩ ውስጥ ተቀጥረው በማገልገል ላይ ሲኾኑ፣ ቀሪዎቹ ደግሞ በልዩ ልዩ የሥራ መስክ ተሰማርተው ራሳቸውን እያስተዳደሩ ነው፡፡ ሦስት መቶ ዐሥራ ሁለቱ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡ ማኅበሩ ካሁን በፊት ቤት ተከራይቶ አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ ሲኾን፣ በአሁኑ ሰዓት ደግሞ በጉለሌ ክፍለ ከተማ ፈረንሳይ ለጋስዮን አንቀጸ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አካባቢ ከመንግሥት በተሰጠው ቦታ ባስገነባው የአረጋውያን መጦርያና መንከባከቢያ በርካታ ሕሙማንንና አረጋውያንን አሰባስቦ የምግብ፣ የልብስ፣ የመጠለያና የሕክምና አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ ከዚህ ዓለም በሞት የሚለዩትንም በክብር እንዲሸኙ ያደርጋል፡፡ በዚህ ዓመትም አገልግሎቱን በይበልጥ አጠናክሮ በከፍተኛ ባለሙያዎች በመታገዝ ከሦስት መቶ በላይ አረጋውያንን በማእከሉ በማሰባሰብ፤ ለሦስት መቶ አረጋውያን የተመላላሽና የቤት ለቤት ድጋፍ በማድረግ፤ እንደዚሁም ለአረጋውያኑና ለተንከባካቢዎቻቸው ልዩ ልዩ ሥልጠናዎችን በመስጠት የበጎ አድራጎት ተልእኮውን ሲወጣ ቆይቷል፤ ወደፊትም ይቀጥላል፡፡

ጕብኝት ባደረግንበት ወቅት እንዳስተዋልነው በማኅበሩ እየተጦሩ ከሚገኙ ወገኖች መካከል አንዳንዶቹ የአብነት መምህራን፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ በመንግሥትና በግል ድርጅቶች ሓላፊነት የነበራቸው ሰዎች ናቸው፡፡ እነዚህ የቤተ ክርስቲያንና የአገር ባለውለታዎች በሕመም፣ በጤና እና በእርጅና ምክንያት የአልጋ ቁራኛ፣ የደዌ ዳኛ ኾነው ጎዳና ላይ በወደቁበት ወቅት ይህ ማኅበር ደርሶላቸው አስፈላጊውን ዅሉ ድጋፍ እያደረገላቸው ይገኛል፡፡ በተለይ የአእምሮ ሕሙማንና ከአንድ በላይ በኾነ የጤና እክል የተጠቁ ማለትም የማየትም የመስማትም የመንቀሳቀስም ችግር ያለባቸውና ሰውነታቸውን መቈጣጠር የማይችሉ አባቶች፣ እናቶች፣ ወንድሞችና እኅቶች ኹኔታ ልብን ይነካል፡፡ እነዚህ ወገኖች የሚንቀሳቀሱትም፣ የሚመገቡትም፣ የሚለብሱትም፣ የሚጸዳዱትም በሰው ርዳታ ነው፡፡ እነርሱን ያየ ሰው የማኅበሩን ዓላማ በግልጽ ይረዳዋል የሚል እምነት አለን፡፡ የማኅበሩ መሥራች እንደ ነገሩን የሠራተኞችን ደመወዝ ሳይጨምር ለሕሙማኑ የዳይፐር መግዣ ብቻ በየቀኑ ከአንድ ሺሕ አራት መቶ ስልሳ አምስት ብር በላይ ወጪ ይደረጋል፡፡ ይህም ማኅበሩ ሰውን ለመርዳት ሲል የሚከፍለውን መሥዋዕትነትና የሚያሳልፈውን ውጣ ውረድ የሚያመለክት ነው፡፡

በማእከሉ ድጋፍ ከሚደረግላቸው ሕሙማንና አረጋውያን ጥቂቶቹ

በአጠቃላይ ‹‹መልካም ሥራ የክፉ ቀን ስንቅ ነው›› በሚለው መሪ ቃሉ የሚታወቀው የወደቁትን አንሡ የነዳያን መርጃ ማኅበር በጤና፣ በእርጅና ወይም በሌላ ልዩ ልዩ ምክንያት በየመንገዱ ወድቀው የሚለምኑ ወገኖችን በማሰባሰብ፤ እንደዚሁም በያሉበት ቦታ ባለሙያዎችን በመላክ የሕክምና፣ የምግብ እና የልብስ ድጋፍ እንዲያገኙ ያደርጋል፡፡ ለወደፊትም ይህን ተግባሩን በስፋት አጠናክሮ ለመቀጠል ዕቅድ አውጥቶ በመተግበር ላይ ነው፡፡ የማእከሉ ክሊኒክ በአካባቢው ለሚገኙ ድጋፍ ፈላጊ የኅብረተሰብ ክፍሎች የሕክምና አገልግሎት እንዲሰጥ ማድረግ፤ ተጨማሪ የመጠለያና የሆስፒታል ተቋማትን መገንባት፤ የጎዳና ላይ ምጽዋትን ተቋማዊ በማድረግ ነዳያን ወጥ በኾነ መንገድ ርዳታ እንዲያገኙ ማመቻቸት፤ ከርዳታ ድርጅቶችና በጎ አድራጎት ማኅበራት ጋር በጥምረት በመሥራት የአረጋውያንን ችግር በጋራ መፍታት ከማኅበሩ ዕቅዶች መካከል የሚጠቀሱ ተግባራት ናቸው፡፡

‹‹ስድስቱ ቃላተ ወንጌል በወደቁትን አንሡ የነዳያን መርጃ ማኅበር ውስጥ ይፈጸማሉ፤›› የሚሉት የማኅበሩ መሥራች አቶ ስንታየሁ አበጀ የየተቋማት ሠራተኞች፣ የድርጅት ባለቤቶች በጥቅሉ በጎ አድራጊ ወገኖች መጥተው ሕሙማኑን በመጠየቅና ቦታውን በመጐብኘት፣ የሚቻላቸው ደግሞ በምግብ፣ በቁሳቁስ (ልብስ፣ ፍራሽ፣ አልጋ፣ ወዘተ.) አቅርቦት እንደዚሁም የገንዘብ፣ የጉልበትና የሐሳብ ድጋፍ በማድረግ ቢተባበሩ የወደቁ ወገኖችን በማንሣት፣ ነዳያንን በመደገፍ፣ የታመሙትን በማሳከምና አረጋውያንን በመከንከባከብ ማኅበሩ ከዚህ ቀደሙ በበለጠ ሓላፊነቱን በአግባቡ ለመወጣት እንደሚቻለው አስረድተዋል፡፡ መሥራቹ እንደ ነገሩን ክርስትና፣ ሰርግ፣ ምረቃ፣ ተዝካርና የመሳሰሉ መርሐ ግብሮችን ማኅበሩ በሚያከራያቸው አዳራሾች ማዘጋጀት ደግሞ ሌላው የርዳታ ማድረጊያ መንገድ ነው፡፡ በመጨረሻም ላለፉት ዓመታት በልዩ ልዩ መንገድ ማኅበሩን በመደገፍ፤ እንደዚሁም ለትውልድ እንዲተላለፍ ኾኖ በታነጸው የአረጋውያን መጦርያ ማእከልና ክሊኒክ ግንባታ በመሳተፍ ላበረከተው አስተዋጽዖ አቶ ስንታየሁ ኅብረተሰቡን በእግዚአብሔር ስም አመስግነው፣ ‹‹ወደፊትም ማኅበሩ በሚያከናውናቸው ዘርፈ ብዙ ተግባራት ዓቅሙ በሚፈቅደው ዅሉ በመሳተፍ ኅብረተሰቡ ታሪካዊ አሻራውን እንዲያኖርና ወገናዊ ግዴታውን እንዲወጣ ይኹን›› ሲሉ በአረጋውያንና በዓቅመ ደካሞች ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

አምላካችን በመንግሥቱ ያስበን ዘንድ ዅላችንም ከማኅበሩ ጋር በመኾን የወደቁትን እናንሣ የዝግጅት ክፍላችን መልእክት ነው፡፡ ማኅበሩን መደገፍ፣ በአባልነት መሳተፍ ወይም በመጦርያ ማእከሉ የሚገኙ ሕሙማንንና አረጋውያንን መጠየቅ ለምትፈልጉ የማእከሉ አድራሻ፡- አዲስ አበባ ከተማ የካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 01 ፈረንሳይ ለጋስዮን ከገነተ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን 600 ሜትር ገባ ብሎ ራስ ካሣ በሚባለው ሰፈር ከአንቀጸ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አጠገብ ነው፡፡ ስለ ማኅበሩ አገልግሎት የበለጠ መረጃ ለማግኘትም በሚከተሉት አድራሻዎች መጠየቅ ይቻላል፡፡

የቢሮ ስልክ ቍጥር፡- +251-111-243-401

አቶ ስንታየሁ አበጀ፡- 09 12 01 70 32 /09 35 99 92 92

ወ/ሮ ዓይናለም ኃይሌ፡- 09 11 23 91 59 /09 35 40 17 17

የፓስታ ሳጥን ቍጥር፡- 25404

E-mail፡- yewodekutnansu@gmail.com

aynalemamit@yahoo.com

Web site፡- www.yewedekutnansu.org

ገንዘብ በባንክ ገቢ ማድረግ የምትፈልጉ፣ የወደቁትን አንሡ የነዳያን መርጃ ማኅበር፡-

  1. በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሐል ከተማ ቅርንጫፍ፣ የተንቀሳቃሽ ሒሳብ ቍጥር፡- 10000 0454 4513 ወይም 10000 2418 3959
  2. ኅብረት ባንክ ሒሳብ ቍጥር፡- 1141 1161 0272 1018 አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ብላችሁ እንድትልኩ ማኅበሩ ይጠይቃል፡፡ ገንዘቡ ወደ ባንክ ከገባ በኋላም ለሒሳብ ቍጥጥር ያመች ዘንድ በሦስት ኮፒ አሠርታችሁ አንዱን ኮፒ ለማኅበሩ እንድታደርሱ በአክብሮት ያሳስባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የበረዶ ናዳ በገዳመ ናዳ

ፈለገ ብርሃን ናዳ ቅድስት ማርያም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ፈለገ ብርሃን ናዳ ቅድስት ማርያም ገዳም በምዕራብ ጐጃም ሀገረ ስብከት ሜጫ ወረዳ ቤተ ክህነት በጉታ ቀበሌ ልዩ ስሙ ናዳ በሚባል ቦታ ይገኛል፡፡ ገዳሙ በዐሥራ ስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተመሠረተ ሲኾን፣ ታቦተ ሕጉም ከጣና ቂርቆስ ገዳም እንደ መጣ ይነገራል፡፡ ለብዙ ዓመታት ‹እንቍርቍሪት ጽዮን› እየተባለ ሲጠራ የቆየው ገዳሙ፣ ከዓመታት በኋላ ‹ናዳ ማርያም› ተብሎ ተሰይሟል፡፡ ናዳ የተባለበት ምክንያትም የሚከተለው ታሪክ ነው፤ በአካባቢው ዋናው ገዳም የሚባል ሌላ ጥንታዊ ገዳም ነበረ፡፡ በዚህ ገዳምም አባ ናዳ የሚባሉ አባት ይጸልዩበት ነበር፡፡ በዙርያውም በርካታ መነኮሳት ነበሩ፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አባ ናዳ በመሰላል ወጥተው የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን ጣርያ ሲከድኑ መሰላሉ አንሸራቷቸው ወደቁ፡፡ በዚህ ጊዜ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተገልጻ በደኅና ካነሣቻቸው በኋላ ‹‹ወዳጄ አባ ናዳ ሆይ! ለዘለዓለም ስምህ በዚህ ቦታ ይጠራ›› በማለት ቃል ኪዳን ሰጠቻቸው፡፡ አባ ናዳም ገዳሙን አሁን ባለበት አኳኋን እንዲጸና አደረጉ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ‹እንቍርቍሪት› የሚለው ስያሜ ተለውጦ ‹ናዳ ማርያም› ወይም ‹ናዳ ጽዮን› ተብሎ መጠራት ጀመረ፡፡

በአዲስ መልክ እየተገነባ የሚገኘው የክብረ ደናግል ናዳ ቅዱስ ላልይበላ ሕንጻ

ፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም በየጊዜው የመጥፋት ፈተና ቢያጋጥመውም በእግዚአብሔር ፈቃድ እንደ ገና እየተመለሰ እስካሁን ድረስ ክብሩ እንደ ተጠበቀ፤ ወሰኑ እንደ ተከበረ፤ ልማቱም እንደ ቀጠለ ነው፡፡ ገዳሙ የአብነት ትምህርት ማእከል በመኾኑና ዙርያው በምንጭ በመከበቡ የተነሣ ከ፲፱፻፹፮ ዓ.ም ጀምሮ በጊዜው የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በነበሩት ብፁዕ አቡነ በርናባስ ፈቃድ ‹ፈለገ ብርሃን› ተብሎ ተሰይሟል፡፡ ገዳሙ በዚህ መልኩ እየሰፋ መጥቶ በአሁኑ ሰዓት አገልግሎቱም ጉባኤ ቤቱም በአግባቡ እየተከናወነ ነው፡፡ ከፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በተጨማሪ የክብረ ደናግል ናዳ ቅዱስ ላልይበላ እና የጋፈራ ደብር ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ሕንጻ አብያተ ክርስቲያናት ለመነኮሳቱ እና ለአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን አገልግሎት በመስጠት ላይ ናቸው፡፡ በአሁኑ ሰዓትም የክብረ ደናግል ቅዱስ ላሊበላ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በዘመናዊ ጥበብ በአዲስ መልክ በመገንባት ላይ ይገኛል፡፡

(ምንጭ፡- ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ፤ ገዳሙ ያሳተመው ብሮሸር)

ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ

ምንኵስናን ከሊቅነት፣ አባትነትን ከሥራ ጋር አስተባብረው በያዙት በሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ አማካይነት ከ፲፱፻፸፱ ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን ድረስ በገዳሙ የትርጓሜ መጻሕፍት እና የቅኔ ትምህርት በመሰጠት ላይ ነው፡፡ ከሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ ጉባኤ ቤት ተምረው በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፍ ተሰማርተው ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የሚያገለግሉ ካህናትና መምህራንም እጅግ በርካታ ናቸው፡፡ የገዳሙ ዋና አስተዳዳሪ፣ የትርጓሜ መጻሕፍትና የቅኔ መምህሩ ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ እንደ ገለጹልን ገዳሙ ከሚታወቅባቸውና ከሚደነቅባቸው ተግባራት አንደኛው የልማት ሥራ ሲኾን፣ ልማቱ በስፋት የተጀመረውም በ፲፱፻፹ ዓ.ም ነው፡፡ በገዳሙ አካባቢ የሚገኘውን በጎርፍ የተሸረሸረ ሸለቆ በመከባከብ የተጀመረው የልማት ሥራ ውጤታማ ኾኖ ገዳሙን በፌዴራል ሁለተኛ፤ በክልል ደግሞ አንደኛ ደረጃ እንዲያገኝና የክብር ሜዳልያ እንዲሸለም አድርጎታል፡፡

የገዳሙ አትክልት በከፊል

የገዳሙ መነኮሳት ከመንፈሳዊው አገልግሎታቸው ጎን ለጎን በጕልበታቸው ያለሙት የአትክልት እና የደን ይዞታ የተመልካች ቀልብን ይስባል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በዘንድሮው ዓመት (፳፻፱ ዓ.ም) በወርኃ ሰኔ በአካባቢው አንድ አዲስ ነገር ተከሠተ፡፡ ነገሩም እንዲህ ነው፤

ዘመነ ጸደይ (በልግ) ተፈጽሞ ዘመነ ክረምት ሊገባ ቀናት ብቻ ቀርተዋል፡፡ ክረምቱ በይፋ ባይገባም በገዳሙ ማኅበረ መነኮሳት እና በአካባቢው አርሶ አደሮች የክረምቱ ተግባር መከናወን ከጀመረ ቆየት ብሏል፡፡ ‹‹ሰኔ እና ሰኞ›› እንደሚባለው ወርኃ ሰኔ ልዩ የሥራ ወቅት ናትና ማኅበረ መነኮሳቱ እና የአካባቢው አርሶ አደሮች ለሥራ በመሯሯጥ ላይ ናቸው፡፡ ከላይ በሚወርደው ዝናም የራሰው፤ ከምድር በእርሻ ብዛት የለመለመው የፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም እና የአካባቢው መሬትም የተዘራበትን አብቅሎ አርሶ አደሮቹንና መነኮሳቱን አስደስቷል፡፡ በማጭድ ከሚታጨዱ ሰብሎች መካከል በቆሎን የመሰሉ አዝርዕት እየፋፉ ናቸው፤ በእጅ ከሚለቀሙት መካከል ደግሞ በተለይ ገዳሙን የልማት ማእከል ያደረጉት፤ በልዩ ልዩ ጊዜ ለሽልማት ያበቁት እና ስሙ ከፍ ከፍ እንዲል፣ በመንግሥት ዘንድም ልዩ ትኩረት እንዲሰጠው ያስቻሉት፤ ለበርካታ ዓመታት የተለፋባቸው የአቦካዶ፣ ሙዝ፣ ማንጎ፣ ብርቱካን፣ ፓፓዬ፣ ትርንጎ፣ ሎሚ እና የመሳሰሉ ጣፋጭ ተክሎች ፍሬያቸው ተንዠርግጎ አላፊ አግዳሚውን ያስጎመዣል፡፡ መነኮሳቱም የድካማቸውን ዋጋ በፍሬ አይተዋልና እየተደሰቱ ፍሬውን ለቅመው አንድም ለምግብ፣ አንድም ለሽያጭ ለማቅረብ ዝግጅት ላይ ናቸው፡፡

ማኅበረ መነኮሳቱ በሥራ ላይ

በ፳፻፱ ዓ.ም፣ ወርኃ ሰኔ በገባ በሃያ ሁለተኛው ቀን ከሰዓት በኋላ እንዲህ ኾነ፤ የገዳሙ መነኮሳት እና የአካባቢው አርሶ አደር ከፊሉ በአረም፣ ከፊሉም እንስሳትን በመጠበቅ ላይ ናቸው፡፡ ወቅቱ የዘመነ ክረምት ዋይዜማ ነውና ሰማይ በመባርቅቱ ድምፅ አጅቦ ዝናም ስጦታውን ወደ ምድር ሊልክ ተቻኩሏል፡፡ የሰማይ መልእክተኛ ደመናም ከውቅያኖሶች የቀዳውን ዝናም ተሸክሞ ወደ ምድር ሊያደርስ ተዘጋጅቷል፡፡ የዝናም መጓጓዣ ነፋስም ዝናሙን በመግፋት ደመናን እየተራዳው ነው፡፡ ምድር የሚወርደውን ዝናም ትጠጣ ዘንድ ሳስታ አፏን ከፍታ በመጠበቅ ላይ ናት፡፡ አዝርዕቱም ተዘርተው ያልበቀሉት በፍጥነት ለመብቀል፤ የበቀሉት ደግሞ ፍሬ ለመስጠት በአጠቃላይ በልምላሜ ለመረስረስ ወደ ላይ አሰፍስፈው ዝናሙን ይጠባበቃሉ፡፡ የመብረቁ ድምፅ፣ ብልጭታው፣ ጉርምርምታው እና የደመናው ጥቁረት ከወትሮው ጊዜ የተለየ ነው፡፡

ጥቁር ደመና በናዳ ሰማይ

ከቆይታ በኋላ በአንዲት ቅጽበት ማንም ያልጠበቀው ልዩ አጋጣሚ ተከሠተ፡፡ ለትምህርት ይኹን ለተግሣፅ፣ ለመዓትም ይኹን ለመቅሠፍት ብቻ ከእግዚአብሔር በቀር እኛ በማናውቀው ምክንያት በቀበሌው እና በገዳሙ ዙርያ ዝናምና ማዕበል የተቀላቀለበት ከባድ የበረዶ ናዳ ወረደ፡፡ በበረዶውም ከታላላቆቹ ጀምሮ እስከ ታናናሾቹ ድረስ ዕፀዋቱ በእሳት እንደ ተቃጠሉ ኩምሽሽ፣ እርር አሉ፡፡ ፍሬ ያፈሩ ተክሎችም ረገፉ፡፡ ገና ያልበቀሉትም በማዕበል ተወሰዱ፡፡ በፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም መነኮሳት ክንድ የተተከሉ የአቦካዶ፣ ሙዝ፣ ማንጎ፣ ብርቱካን፣ ፓፓዬ፣ ትርንጎ፣ ሎሚ እና የመሳሰሉ ጣፋጭ ተክሎች ፍሬያቸው ሙሉ በሙሉ ረገፈ፡፡ ያፈሉት ችግኝ ተጨፈጨፈ፡፡ የገበሬው፣ የመነኮሳቱ እና የእንስሳቱ መኖርያ ቤቶችም በበረዶ ፈራረሱ፡፡ የጠበል መጠመቂያ ቦታዎች ተናወጡ፡፡ የገዳሙ ንቦችም ከቀፎዎቻቸው ተሰደዱ፡፡ በዚህ የተነሣም በናዳ ማርያም ገዳም እና በአካባቢው ጸጥታ ነገሠ፡፡ ፍርኃትም ሰፈነ፡፡ የአካባቢው ነዋሪዎች እንደ ነገሩን የበረዶ ናዳው ሰኔ ሃያ ሦስት ቀንም ቀጥሎ ነበር፡፡ ጥፋቱ እንደ ገና ተደገመ፡፡ በአጠቃላይ ከሰባ ሄክታር በላይ የሚገመት ሰብል በበረዶው ናዳ ወደመ፡፡

ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ በበረዶ የተጎዳውን አትክልት ሲያስጐበኙ

ከጉዳቱ በኋላ የገዳሙ ዋና አስተዳዳሪ ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ ደቀ መዛሙርታቸውን እና ማኅበረ መነኮሳቱን ይዘው ጸሎተ ምሕላ ያዙ፡፡ የደረሰው ጥፋት እንዳይደገም፤ የወደመው ሰብልም እንዲመለስ፤ መነኮሳቱ፣ የአብነት ተማሪዎች እና ምእመናኑ ተስፋ ቈርጠው እንዳይበተኑ እግዚአብሔርን በጸሎት ይማጸኑት ጀመር፡፡ ዋና አስተዳዳሪው የጠፋውን ሰብል እና በአካባቢው የደረሰውን ጉዳት ላለማየት ከበዓታቸው አልወጣም ብለው ነበር፡፡ ከዕለታት በኋላ ግን የአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን ከራሱ ይልቅ የገዳሙን ጉዳይ አስቀድሞ በጉልበት፣ በእርሻ ሥራ እና ዘር በድጋሜ በመዝራት መነኮሳቱን ለማገዝ መምጣቱን ሲሰሙ ምእመናኑን ለማበረታታት ከበዓታቸው ወጡ፡፡ እኛም አባን ያገኘናቸው በዚህ ወቅት ነበር፡፡ ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ ያዩት ነገር አዲስ ኾኖባቸዋል፡፡ ‹‹ከዚህ ገዳም ከመጣሁበት ጊዜ ጀምሮ እንደዚህ ዓይነት መዓት ደርሶ አያውቅም›› ይላሉ ሊቀ ብርሃናት የደረሰውን ጉዳት ከፍተኛነት ሲገልጹ፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑ ከየአቅጣጫው ስልክ ሲደውልላቸውም ‹‹ደኅና ነን፤ አልተጎዳንም›› ይላሉ፡፡ ይህ ዅሉ ጉዳት ደርሶ እንዴት ለሰዎቹ ‹‹ደኅና ነን›› ይላሉ ብለን ስንጠይቃቸው ሊቀ ብርሃናት የሰጡን ምላሽ ‹‹እናትህ ሞተች ተብሎ አይነገርም›› የሚል ነበር፡፡ በእርግጥ እርሳቸው እንደ ነገሩን በሰው እና በእንስሳት ላይ የደረሰ ጉዳት አለመኖሩ ማኅበረ መነኮሳቱን አስደስቷቸዋል፡፡ ከዚህ በተረፈ ግን የደከሙበት ሰብል እና አትክልት ከጥቅም ውጪ ኾኗል፡፡

በበረዶው ናዳ የረገፈው ፍራፍሬ በከፊል

የገዳሙ ደን እና ፍራፍሬ በበረዶ ናዳ ቢወድምም ዋና አስተዳዳሪው እና ማኅበረ መነኮሳቱ ብሩህ ፊታቸው አልቀዘቀዘም፡፡ ጉባኤ ቤቱም አልተፈታም፡፡ ገዳማውያኑ በተለመደው መንፈሳዊ ቋንቋ ‹‹እግዚአብሔር ይመስገን! ደኅና ነን … በአትክልት ላይ እንጂ በሰውና በእንስሳት ላይ የደረሰ ጉዳት የለም … ዅሉም ነገር ለበጎ ነው … ከዚህ የባሰ አያምጣ …›› እያሉ እነርሱን ለመጠየቅና ጉዳን ለማየት የሚመጡ ምእመናንን ያረጋጋሉ፡፡ ገዳማውያን እንዲህ ናቸው፤ ተበድለው እንዳልተበደሉ፤ ተጎድተው እንዳልተጎዱ፤ ተቸግረው እንዳልተቸገሩ በማመን በኾነው ነገር ዅሉ እግዚአብሔርን ያመሰግናሉ፡፡ በዚህ ዓመት በፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም እና በአካባቢው በወርኃ ሰኔ የደረሰው ጉዳት እግዚአብሔርን ወደማማረር የሚገፋፋ ከባድ ፈተና ቢኾንም የገዳሙ አባቶች እና እናቶች ግን እግዚአብሔርን ማመስገናቸውን ለቅጽበት አላቋረጡም ነበር፡፡ በስበብ አስባቡ እግዚአብሔርን ና ውረድ የምንል ምእመናን ከእነርሱ ትምህርት ልንወስድ ይገባል፡፡

ከበረዶው ናዳ በኋላ የአካባቢው ምእመናን የገዳሙን መነኮሳት በጕልበት ሥራ ሲደግፉ

የገዳሙ መነኮሳትና የአብነት ተማሪዎች የወደፊት ኑሯቸው አሳሳቢ ነው፡፡ ምክንያቱም ‹‹የዕለት እንጀራችንን ዛሬ ስጠን›› እያሉ እየጸለዩ ለምግብ እና ለአካባቢ ጥበቃ ይጠቅም ዘንድ በጉልበታቸው ወጥተው ወርደው ያበቀሉት ሰብል፣ ያለሙት አትክልት፣ ያፈሉት ችግኝ አሁን የለምና፡፡ የያዙት አማራጭ የተጎዳውን ሰብል እየገለበጡ እንደ ገና ዘር መዝራት ነው፡፡ ይህ መፍትሔ ግን በበቆሎ ፋንታ ዳጉሳንና የመሳሰሉ አዝርዕትን ለመተካት እንጂ ሙዙን፣ አቦካዶውን፣ ፓፓዬውን፣ ማንጎውን፣ ወዘተ የመሳሰሉ አትክልቶችን ለመተካት አያስችልም፡፡ እነዚህን ተክሎች ወደ ነበሩበት ለመመለስ የዓመታት ጥረትን ይጠይቃልና፡፡ ስለኾነም መላው ሕዝበ ክርስቲያን በገዳሙ እና በአካባቢው የደረሰውን ጉዳት ከግምት ውስጥ በማስገባት በሚቻለን አቅም ዅሉ አስቸኳይ ርዳታ ልናደርግላቸው ያስፈልጋል፡፡

የ አብነት ተማሪዎች በከፊል

በእርግጥ ማኅበረ ቅዱሳን ከገዳሙ ድረስ ልዑካንን በመላክ ለመነኮሳቱ የዘር መግዣ ይኾናቸው ዘንድ ለጊዜው የሃያ ሺሕ ብር የገንዘብ ድጋፍ አድርጓል፡፡ ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በደረሰን መረጃ ማኅበሩ ካሁን በፊት ለገዳሙ ካበረከተው ትራክተር (የእርሻና የዕቃ ማጓጓዣ መሣርያ) በተጨማሪ ለወደፊትም በቋሚነት ገዳሙን ለመደገፍ አቅዷል፡፡ በቦታው ተገኝተን ዋና አስተዳዳሪውን ባነጋገርንበት ወቅት ላደረገው የገንዘብ ድጋፍ ማኅበረ ቅዱሳንን፤ በጉልበት ሥራ በመራዳታቸው ደግሞ የአካባቢውን ሕዝበ ክርስቲያን አመስግነዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለገዳሙ ያበረከተው የእርሻና የዕቃ ማጓጓዣ መሣርያ

ኾኖም ግን ይህ ድጋፍ በቂ አይደለምና ሌሎች በጎ አድራጊ ምእመናንም ቀለብ በመስጠት፣ ዘር በመግዛት፣ ልብስ በመለገስ እና ከፍ ሲል ደግሞ መኖርያ ቤት በማደስ በአጠቃላይ በሚቻላቸው ዅሉ ድጋፋቸውን እንዲያደርጉ ዋና አስተዳዳሪው ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ በገዳሙ ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ዝግጅት ክፍላችንም የገዳሙን መነኮሳት ከስደት፣ ጉባኤ ቤቱንም ከመዘጋት ለመታደግ፤ እንደዚሁም የልማት ቦታውን ወደ ጥንት ይዘቱ ለመመለስ ይቻል ዘንድ በተቻላችሁ አቅም ዅሉ ድጋፍ በማድረግ ከበረከቱ እንድትሳተፉ ይኹን ሲል መንፈሳዊ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡ በመጨረሻም የአባቶቻችን አምላክ ገዳሞቻችንን ከድንገተኛ አደጋ እና ከጥፋት፤ መነኮሳቱንና የአብነት ተማሪዎችንም ከስደት ይጠብቅልን እያልን ጽሑፋችንን አጠቃለልን፡፡

ማሳሰቢያ

ገዳሙን በገንዘብ ለመደገፍ የምትፈልጉ ምእመናን በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መርዓዊ ቅርንጫፍ ሒሳብ ቍጥር፡- 10000 6261 1786 ገቢ ማድረግ የምትችሉ መኾኑን የገዳሙ ጽ/ቤት ያሳስባል፡፡ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘትም በስልክ ቍጥር፡- 09 18 70 81 36 በመደወል የገዳሙን ዋና አስተዳዳሪ ማነጋገር ይቻላል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

አርአያነት ያለው ተግባር በአዳማ ማእከል

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሰኔ ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምርያ ማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል በየጊዜው መልካም ተግባራትን ያከናውናል፡፡ ማእከሉ በዚህ ዓመት ከፈጸማቸው አርአያነት ያላቸው ተግባራት መካከል ሦስቱን በዚህ ዝግጅት እናስታውሳችኋለን፤

ከወራት በፊት ማለት በመጋቢት ወር ፳፻፱ ዓ.ም ማእከሉ ከሞጆ ወረዳ ማእከል ጋር በመተባበር ኮምፒውተር ከነፕሪንተሩ ለሉሜ ወረዳ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በስጦታ መልክ አበርክቷል፡፡ የንብረት ርክክቡ በተፈጸመበት መጋቢት ፳፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም የማእከሉ ሰብሳቢ መ/ር ጌትነት ዐሥራት ‹‹ማእከሉ ይህንን ድጋፍ ያደረገው የቤተ ክህነቱን አሠራር ወቅቱ በሚፈልገው መልኩ ማዘመን አስፈላጊ ስለኾነ፤ ማኅበረ ቅዱሳንም የቤተ ክርስቲያናችንን መዋቅር በሚቻለው አቅም ዅሉ የመደገፍና የማገዝ ሓላፊነት ስላለበት ነው›› በማለት ማእከሉ የኮምፒውተር ድጋፍ ያደረገበትን ምክንያት አስረድተዋል፡፡

ማእከሉ ኮምፒውተሩን ለወረዳ ቤተ ክህነቱ ሲያስረክብ

ቤተ ክርስቲያንን በዅለንተናዊ መልኩ ለመደገፍ እና የቤተ ክህነቱ አሠራር ወቅቱን በሚዋጅ መልኩ እንዲቀላጠፍ ለማድረግ ማኅበረ ቅዱሳን እየሰጠ ያለው አገልግሎት የሚያስመሰግነው ትልቅ ተግባር መኾኑን በዕለቱ የተገኙት የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ትፍሥሕት ቀሲስ ሙሉጌታ ቸርነት ተናግረዋል፡፡ ድጋፍ የተደረገለት ወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ሥዩማን ቀሲስ ዋስይኹን ገብረ ኢየሱስም ማእከሉ ይህን ድጋፍ ማድረጉ ማኅበረ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያንን ለመደገፍ ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ተግባር እንደኾነ ገልጸዋል፡፡ ‹‹የተበረከተልን ኮምፒውተር የጽ/ቤታችንን አሠራር ዘመናዊ ከማድረጉ ባሻገር የተቀላጠፈ አገልግሎት ለመስጠትም ያስችለናል›› ያሉት ሥራ አስኪያጁ ስለ ተደረገላቸው ድጋፍም ማኅበረ ቅዱሳንን አመስግነዋል፡፡

ገዳማውያኑ የሕክምና መድኀኒት እና ሳሙና ሲቀበሉ

በሌላ የአገልግሎት ዘርፍ ደግሞ በማእከሉ አስተባባሪነት የአዳማ ከተማ ሆስፒታል ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች በደብረ ከዋክብት ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ለሚገኙ ገዳማውያንና የአብነት ተማሪዎች ግንቦት ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም የሕክምና አገልግሎት ሰጥተዋል፡፡ በዚህ መንፈሳዊ ተግባር ለሰባ ተማሪዎች የእከክ በሽታ፤ ለዐሥራ አራት ተማሪዎች ቀላል የመተንፈሻ አካል ሕመም፤ ለዐርባ ስምንት ተማሪዎች የሆድ ትላትል፤ ለአራት አባቶች የቀላል ሕክምና ርዳታ ተደርጎላቸዋል፡፡

ገዳማውያኑ የአካባቢ ጤና አጠባበቅን የሚመለከት ትምህርት ሲማሩ

በተጨማሪም አንድ መቶ የንጽሕና መጠበቂያ ሳሙና ለገዳማውያኑ ተበርክቷል፡፡ እንደዚሁም ለአንድ መቶ አምሳ የአብነት ተማሪዎች የአካባቢ ጤና አጠባበቅን የሚመለከት ትምህርት ተሰጥቷል፡፡ ይህን አገልግሎት ለመፈጸም መድኃኒት እና ሌሎች ቁሳቁሶች የተገዙበት ወጪ የተሸፈነው በግቢ ጉባኤውና በበጎ አድራጊ ምእመናን እንደ ኾነ ማእከሉ ለዝግጅት ክፍላችን የላከው ዘገባ ያመላክታል፡፡

በቅርቡ ደግሞ ‹‹መልካም ሥራን አብረን እንሥራ›› በሚል መሪ ቃል ልዩ መርሐ ግብር በማዘጋጀት ማእከሉ ግንቦት ፳፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በአዳማ ከተማ የበጎ አድራጎት አገልግሎት ሰጥቷል፡፡ ምእመናንን በማስተባበር የደም እጥረት ላለባቸው ሕሙማን እና ወላድ እናቶች ደም መለገስ፣ የአካባቢን ንጽሕና መጠበቅ የመርሐ ግብሩ ክፍሎች ነበሩ፡፡ በርካታ ምእመናን ከፍተኛ የደም መጠን እንዲለግሱ በማድረጉ የአዳማ ከተማ የደም ባንክ ጽ/ቤት ማእከሉን አመስግኗል፡፡

በመርሐ ግብሩ በቍጥር ከአምስት መቶ በላይ የሚኾኑ በጎዳና የሚኖሩ ወጣቶችን እና ሕፃናትን ንጽሕና የመጠበቅ፤ ልብስ አሰባስቦ የማልበስና ምግብ የመመገብ ተግባር ተከናውኗል፡፡ ወደ ሥራ መሠማራት የሚፈልጉ ወጣቶች ሥራ እንዲጀምሩ ለማገዝም የሊስትሮ ዕቃ ከነቁሳቁሱ ማእከሉ አስረክቧቸዋል፡፡ በዕለቱ የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ የሚያስችል የግንዛቤ ማዳበርያ ትምህርትም በከተማው ትራፊክ ፖሊስ ባለሙዎች ቀርቧል፡፡

ምእመናን ደማቸውን ሲለግሱ

ማእከሉ ከላከልን መረጃ እንደ ተረዳነው የማእከሉ አባላት፣ በአዳማ ከተማ የሚገኙ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች፤ የአቡነ ጎርጎርዮስ ት/ቤት መምህራን፣ ተማሪዎችና ወላጆች፤ እንደዚሁም የአዳማ ከተማ ምእመናን በበጎ አድራጎት መርሐ ግብሩ ተሳትፈዋል፡፡ የአዳማ ከተማ ከንቲባ፣ የከተማው ባህልና ቱሪዝም፣ የማኅበራዊ ጉዳዮች እና የደም ባንክ ጽ/ቤቶች ሓላፊዎች፤ የአዳማ ከተማ ኮሚኒኬሽን ጽ/ቤት ባለሙያዎች እና የኦሮምያ ቴሌቪዥን ድርጅት ጋዜጠኞች በሥፍራው ተገኝተዋል፡፡

የበጎ አድራጎት ተግባሩ በተከናወነበት ዕለት ከሰባት መቶ በላይ ተሳታፊዎች የታደሙበት መርሐ ግብር በአዳማ ከተማ ምክር ቤት አዳራሽ ተዘጋጅቶ ነበር፡፡ በዕለቱ የአዳማ ከተማ ከንቲባ ጽ/ቤት ሓላፊ አቶ ለማ ኃይሌ የመክፈቻ ንግግር ሲያደርጉ ‹‹በርቱልን! እግዚአብሔር ይስጣችሁ! ባደረጋችሁት በጎ ተግባር በከተማው ከንቲባ ጽ/ቤት ስም የተሰማን ደስታ ከፍ ያለ ነው፤›› በማለት የማኅበሩን አገልግሎት አድንቀዋል፡፡ አቶ ለማ አያይዘውም አዳማ ከተማ ለነዋሪዎቿ ምቹ እንድትኾን እና የተቸገሩ ሰዎች ራሳቸውን እንዲችሉ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ‹‹ማኅበሩ ከጽ/ቤታችን ጋር በጋራ እንደሚሠራ ተስፋ እናደርጋለን›› ብለዋል፡፡

በጎዳና ለሚኖሩ ወገኖች የተዘጋጁ አልባሳት

የአዳማ ከተማ የባህልና ቱሪዝም ጽ/ቤት ሓላፊ ወ/ሮ ዘይነባ አማን በበኩላቸው ‹‹ማኅበሩ ያደረገው አስተዋጽዖ ለሌሎች ቤተ እምነት ተከታዮችና የኅብረተሰብ ክፍሎች ትልቅ አርአያነት ያለውና ፈር ቀዳጅ ተግባር በመኾኑ በጽ/ቤቴ ስም ምስጋናዬን እያቀረብሁ፣ ወደ ፊትም ከማኅበሩ ጋር በጋራ ለመሥራት ዝግጁ ነን›› በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በጎ አድራጎት የቤተ ክርስቲያን አንዱ ተልእኮዋ እንደ ኾነ፤ ማኅበረ ቅዱሳንም የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ የሚደግፍ ማኅበር በመኾኑ ይህን የበጎ አድራጎት አገልግሎት ለመስጠት እንደ ተነሣሣ የማእከሉ ሰብሳቢ መ/ር ጌትነት ዐሥራት አስገንዝበዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያንም ኾነ ለአገር እያበረከተ ያለውን ዘርፈ ብዙ አገልግሎትም ሰብሳቢው በሰፊው አስረድተዋል፡፡

ወጣቶቹ አካባቢን በማጽዳት ሥራ ላይ

በመጨረሻም አገልግሎቱን በአግባቡ ለመስጠት እንዲቻል ልዩ ልዩ ድጋፍ ላደረጉ የመንግሥት ተቋማትና የሥራ ሓላፊዎች፤ ለበጎ አድራጊ ምእመናንና በአገልግሎቱ ለተሳተፉ ወገኖች ዅሉ ሰብሳቢው በማኅበሩ ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

እኛም እንደ ዝግጅት ክፍል የቤተ ክርስቲያናችንን መንፈሳዊ ተልእኮ ይበልጥ ለማጉላት፤ የአገራችንን ስም በመልካም ጎን ለማስጠራት ይቻል ዘንድ አዳማ ማእከል ከላይ የተጠቀሱትንና እነዚህን የመሰሉ አርአያነት ያላቸው ተግባራቱን አጠናክሮ ቢቀጥል፤ የሌሎች ማእከላት፣ የሰንበት ት/ቤቶች እና የማኅበራት አባላትም ይህን የማእከሉን ፈለግ ቢከተሉ መልካም ነው እንላለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የትሩፋት ሥራ በቆጠር ገድራ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

አሁን የምንገኝበት የዐቢይ ጾም ሳምንት ስለ ገብር ኄር (ታማኝ አገልጋይ) እና ገብር ሐካይ (ሰነፍ አገልጋይ) የሚነገርበት ወቅት ነው፡፡ ይኸውም ስለ አገልግሎት ትርፋማነትና ዋጋ የምንማርበት ሳምንት ነው፡፡ በተሰጣቸው መክሊት እጥፍ አትርፈው እንደ ተወደሱት ታማኝ አገልጋዮች እኛ ምእመናንም በሃይማኖት ጸንተን፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ጎልምሰን እግዚአብሔር እንደየአቅማችን በሰጠን ልዩ ልዩ ጸጋ ተጠቅመን መንፈሳዊ ትርፍ ካስመዘገብን ከአምላካችን ዘንድ ዋጋ እናገኛለን፡፡ በአንጻሩ በሃይማኖታችን ካልጸናን፣ በክርስቲያዊ ምግባር ካልበረታን፣ ጸጋችንን እንደ ሰነፉ ባርያ ደብቀን መንፈሳዊ ትርፍ ካላስመዘገብን እጣ ፋንታችን ቅጣት ይኾናል፡፡

በምድራዊው ሕይወታችን የተሰጠንን ጸጋ ደብቀን ያለ ምግባር የምንኖር ምእመናን ብዙ የመኾናችንን ያህል፣ ከዚህ በተቃራኒ ደግሞ ከሚበሉት ቈርሰው፣ ከሚጠጡት ቀንሰው፣ ከሚለብሱት ከፍለው ለችግረኞች የሚደርሱ፤ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መፋጠን የሚሽቀዳደሙ፤ በሚጠፋ ገንዘባቸው የማያልፈውን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ የሚተጉ በጎ አድራጊ ምእመናንም አይታጡም፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን እግዚአብሔር አምላክ በሰጣቸው ልዩ ልዩ ጸጋ ለማትረፍ የተነሡ፣ እንደ ልጅነታቸው ቤተ ክርስቲያን የምትጠብቅባቸውን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት ለመወጣት የወሰኑ በጎ አድራጊ ምእመናን በቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም በማከናወን ላይ የሚገኙትን አርአያነት ያለው የትሩፋት ሥራ ልናስታውሳችሁ ወደድን፡፡ በመጀመርያም የገዳሙን ታሪክ በአጭሩ እናቀርባለን፤

‹ቆጠር› የሚለው ቃል ቦታውን የመሠረቱት ግለሰብ ስም ሲኾን፣ በጊዜ ሒደት ቃሉ የጎሣ መጠርያ ኾኖ ቀጥሏል፡፡ ‹ገድራ› በአካባቢው ቋንቋ የዛፍ ዓይነትን የሚያመለክት ቃል ነው፡፡ አካባቢው ‹ገድራ› የተሰኘው ዛፍ የሚበዛበት በመኾኑ ቦታው ‹ቆጠር ገድራ› ተብሎ ይጠራል፡፡ አካባቢው በተፈጥሮ ደን የተከበበ ሥፍራ ሲኾን፣ ነዋሪዎቹ ከዚህ ደን ውስጥ ዕፀዋትን እንዳይቆርጡ ቃል ኪዳን ገብተዋል፡፡ ስለዚህም የደኑ ህልውና ተጠብቆ ይኖራል፡፡ የቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳምም በዚህ ቦታ የተመሠረተ ጥንታዊ ገዳም ነው፡፡ ገዳሙ ከጉራጌ ሀገረ ስብከት መንበረ ጵጵስና ወልቂጤ ከተማ በአምሳ ሁለት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል፡፡

በዳግማዊ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት የነበሩ የአካባቢው ምእመናን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ሊያስገነቡ ቦታዎችን መርጠው ዕጣ ሲጥሉ ዕጣው በተደጋጋሚ ‹ይነኹራ› ለተባለው ቦታ ወጣ፡፡ በዚያ ሥፍራም በመድኃኔ ዓለም ስም ቤተ ክርስቲያን አነጹ፡፡ ይህ ቤተ ክርስቲያን በዕድሜ ብዛት በመጎዳቱ በየጊዜው ዕድሳት እየተደረገለት እስከዛሬ ቆይቷል፡፡ በአሁኑ ሰዓትም ለበርካታ ሕዝበ ክርስቲያን አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ በወቅቱ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ የዚህን ሕንጻ የመሠረት ድንጋይ ለማስቀመጥ በ፳፻፪ ዓ.ም ወደ ቦታው በሔዱ ጊዜ ‹ቆጠር ገድራ› ከሚባለው ደናማ ሥፍራ ሲደርሱ በቦታው በመማረካቸው ከደኑ ውስጥ ገብተው ‹‹ገዳም ገዳም ሸተተኝ፤ ከዚህ ቦታ አልወጣም›› አሉ፡፡ ከጥቂት ሰዓታት ቆይታ በኋላ ጉዟቸውን ቀጥለው ይነኹራ መድኃኔ ዓለም ደርሰው ትምህርተ ወንጌልና ቃለ ቡራኬ ሰጥተው ‹‹ዛሬ ከዚህ ቦታ ላይ የመሠረት ድንጋይ እንዳኖር እግዚአብሔር አልፈቀደልኝም›› ብለው የመሠረት ድንጋዩን ሳያስቀምጡ ወደ አዲስ አበባ ከተማ ተመለሱ፡፡

በሌላ ጊዜ ከሕዝበ ክርስቲያኑ ጋር ውይይት አካሒደው በዕድሳት መልክ በድጋሜ ከሚታነጸው ይነኹራ መድኃኔ ዓለም በተጨማሪ በቆጠር ገድራም በኪዳነ ምሕረት ስም ቤተ ክርስቲያን እንዲታነጽ አዘዙ፡፡ ብፁዕነታቸው ፍጻሜውን ሳያዩ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ ቢያርፉም በጥቅምት ወር ፳፻፫ ዓ.ም እርሳቸው በመረጡት ቦታ የመሠረት ድንጋይ ተቀምጦ ነሐሴ ፲፮ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም የቤተ ክርስቲያኑ ቅዳሴ ቤት ከበረ፡፡ በቆጠር ገድራ በአንድ ወቅት በተደረገ ቁፋሮ ሰባት ጥንታውያን የዋሻ ቤተ መቅደሶች፣ ሦስት የሱባዔ መያዣ ቦታዎችና ልዩ ልዩ ንዋያተ ቅድሳት ተገኝተዋል፡፡ ይህም በዚያ ሥፍራ ቀደም ሲል ቤተ ክርስቲያን ታንጾ እንደ ነበር የሚጠቁም ማስረጃ ነው፡፡ በቁፋሮ የተገኙ ሰባቱ የዋሻ ቤተ መቅደሶችም፡- የደብረ ቢዘን ቤተ መቅደስ፣ ቤተ ጎልጎታ፣ ቤተ መድኅን፣ ቤተ ጠበብት፣ ቤተ ኤፍራታ፣ ቤተ ደብረ ብርሃን እና ቤተ ደናግል ይባላሉ፡፡

ከእነዚህ ቤተ መቅደሶች መካከል በቤተ ጎልጎታ የኦሪት መሥዋዕት ይቀርብበት እንደ ነበረ፤ በውስጡም ከወርቅ የተሠራ መሠዊያ እንደ ተገኘና ይህን መሠዊያም በስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን በሥፍራው ሲያገለግሉ የነበሩ አባ ማትያስ የተባሉ አባት እንዳይዘረፍ ብለው ቆፈረው እንደ ቀበሩት የአካባቢውን ታሪክ የሚያውቁ አባቶች ይናገራሉ፡፡ የቦታው ታሪክና የንዋያተ ቅድሳቱ ዝርዝርም በቁፋሮው በወጣው ‹ዝንቱ መጽሐፍ ዘአቡነ ማትያስ› በተባለው የብራና መጽሐፍ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ በቁፋሮ የወጡት የወርቅ መሠዊያ፣ የብራና መጻሕፍት፣ ቅዱሳት ሥዕላት፣ እርፈ መስቀል እና ሌሎች ጥንታውያን ንዋያተ ቅድሳት ቤተ መዘክር እስከሚሠራላቸው ድረስ እንዳይጠፉ በምሥጢር እንዲጠበቁ ተደርገዋል፡፡ በዚህ ሥፍራ ከአሁን በፊት ያልወጡና ወደ ፊት በቁፋሮ የሚገኙ ንዋያተ ቅድሳት እንዳሉም ይታመናል፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም በገዳሙ የፈለቁት፣ በአምስት ቅዱሳን ማለትም በኪዳነ ምሕረት፣ መጥምቀ መለኮት ዮሐንስ፣ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እና አባ ማትያስ ስም የተሰየሙት ጠበሎች ለበርካታ ሕሙማን ፈውስ እየሰጡ ተአምራትን እያሳዩ ነው፡፡ በቍጥር ወደ ፳፪ የሚደርሱ የሌላ እምነት ተከታዮችም በገዳሙ ጠበሎች ከሕመማቸው ተፈውሰው፣ የክርስትና ጥምቀትን ተጠምቀው የሥላሴን ልጅነት አግኝተዋል፡፡

ምንጭ፡

  • የማኅበረ ቅዱሳን ኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚድያ ዋና ክፍል፤
  • የገዳሙ ሕንጻ አሠሪ ኰሚቴ ያሳተመው በራሪ ወረቀት፤
  • የጉራጌ ዞን ባህል ቱሪዝም እና መንግሥት ኮሚኒኬሽን፡፡
img_0748

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ሲከፈት

የዚህ ዅሉ ታሪክ ባለቤት ለኾነችው ቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም ደረጃውን የጠበቀ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን፣ የአብነት ት/ቤት፣ የካህናት ማሠልጠኛ ተቋም እና ቤተ መዘክር ለመሥራት እግዚአብሔር ያስነሣቸው የአካባቢው ተወላጆች ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ፈቃድ አግኝተው በመፋጠን ላይ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ በጎ አድራጊ ምእመናን ከሀገረ ስብከቱና ወረዳ ቤተ ክህነቱ ጋር በመተባበር ገዳሙን የትምህርትና የልማት ማእከል ለማድረግ እንቅስቃሴ ላይ ናቸው፡፡ የገዳሙን ታሪክ ለትውልድ ለማስተላለፍ ያመች ዘንድ ሰባክያነ ወንጌልንና አስጐብኚዎችን ለመመደብም ታቅዷል፡፡

003

በአጠቃላይ ገዳሙን ወደ ጥንት ስሙና ታሪኩ ለመመለስ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ በዚህ መልካም የትሩፋት ሥራም የሕንጻዎቹን ዲዛይን በነጻ በመሥራትና ኰሚቴውን በማስተባበር፣ እንደዚሁም ዓላማውን በማስተዋወቅ ማኅበረ ቅዱሳን ድጋፍ በማድረግ ላይ ሲኾን፣ ማኅበረ ጽዮንም ሌላው አጋር አካል ነው፡፡ ለዚህ መልካም ተግባር የተቋቋመው ሕንጻ አሠሪ ኰሚቴም ለታቀዱት ዘርፈ ብዙ የልማት ሥራዎች ገቢ በማሰባሰብ መንፈሳዊ ተልእኮውን በአግባቡ እየተወጣ ነው፡፡ ኰሚቴው ካከናወናቸው የግንዛቤ ማስጨበጫ እና የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብራት መካከልም የካቲት ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቦሌ አየር ማረፊያ አካባቢ በሚገኘው ዮድ አቢሲንያ የባህል ምግብ አምባሳደር ያደረገው ልዩ መርሐ ግብር አንዱ ነው፡፡

img_0795

የመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች በከፊል

በጸሎተ ወንጌል በተከፈተው በዚህ መርሐ ግብር በካህኑ የተነበበው፣ በዓለ ደብረ ታቦርን የሚመለከተው፣ ‹‹… ሦስት ዳስ እንሥራ …›› የሚለው ኃይለ ቃል የሚገኝበት የወንጌል ክፍል ከገዳሙ የልማት ሥራ ጋር የሚተባበር ምሥጢር አለው (ማቴ. ፲፯፥፩-፬)፡፡

img_0809

መምህር አባ ኤልሳዕ ከደቀ መዛሙርታቸው ጋር ኾነው የአብነት ሥርዓተ ትምህርትን በተግባር ሲያሳዩ

በዕለቱ የገዳሙ አስተዳዳሪ መምህር አባ ኤልሳዕ ከደቀ መዛሙርታቸው ጋር ተገኝተው ንባብ፣ ዜማ፣ ቅኔ፣ የመጻሕፍት ትርጓሜ እና የአቋቋም ሥርዓተ ትምህርትን ለመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች በተግባር አሳይተዋል፡፡

img_0757

ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ ትምህርተ ወንጌል ሲሰጡ

ዲ/ን ብርሃኑ አድማስም ‹‹የመስጠትና የመቀበል ስሌት›› (ፊልጵ. ፬፥፲-፳) በሚል ኃይለ ቃል ገንዘብንም ኾነ ሌላ ንብረትን ለመንፈሳዊ ዓላማ ማዋል ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያሰጠውን ልዩ ጸጋና የሚያስገኘውን ጥቅም ቅዱሳት መጻሕፍትን ዋቢ በማድረግ አስተምረዋል፡፡

ቀሲስ ምንዳዬ ብርሃኑ እና መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ ደግሞ መዝሙር አቅርበዋል፡፡

img_0753

ቀሲስ ምንዳዬ ብርሃኑ መዝሙር ሲያቀርቡ

img_0779

መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ በገና ሲደረድሩ

የመርሐ ግብሩ መሪ ዲ/ን ደረጀ ግርማ በበኩላቸው በበጎ አድራጊ ምእመናን የተጀመረው ይህ ገዳሙን የማሳደግ ሥራ ዓላማው በየጊዜው እየቀዘቀዘ የመጣውን የአብነት ትምህርት ለማስፋፋት፣ ጥንታውያን ቅርሶችን በመጠበቅ ለትውልድ ለማስተላለፍ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለማሳደግ እና ስብከተ ወንጌልን በስፋት ለማዳረስ መኾኑን አስገንዝበዋል፡፡

img_0815

የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ዲዛይን ተመርቆ ሲከፈት

የገዳሙን ታሪክ የሚያስቃኝ ዘጋቢ ፊልምም ሌላው የመርሐ ግብሩ አካል የነበረ ሲኾን የኰሚቴው ሰብሳቢ እና የዮድ አቢሲንያ የባህል ምግብ አምባሳደር ባለቤት አቶ ትእዛዙ ኮሬ ‹‹የሰማይ አምላክ ያከናውንልናል፤ እኛ በርያዎቹም ተነሥተን እንሠራለን›› በሚል ርእስ በዘገባ መልክ የኰሚቴውን እንቅስቃሴ ለጉባኤው አስረድተዋል፡፡ በዚህ መርሐ ግብር በገዳሙ ሊሠራ የታቀደው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን፣ ዘመናዊ የአብነት ት/ት ቤት እና የቤተ መዘክር ዲዛይን በአባቶች ቡራኬ ተመርቋል፡፡ በመርሐ ግብሩ የታደሙ ምእመናንም ለዚህ መልካም ሥራ በመሽቀዳደም የሚችሉትን ዅሉ ለማድረግ ቃል ከመግባታቸው ባለፈ በዕለቱ በሚሊዮን የሚቈጠር ገንዘብ ገቢ አድርገዋል፡፡ የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ዲዛይን በከፍተኛ መንፈሳዊ ፉክክር በአንድ መቶ ሃያ ሺሕ ብር ጨረታ መሸጡም ብዙዎችን አስደንቋል፡፡ ይህም ሕዝበ ክርስቲያኑ ገንዘቡን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ለማዋል ያለውን ቍርጠኝነት ያሳያል፡፡

001-copy

ይህን የትሩፋት ሥራ በመደገፍና በማስተባበር የተሳተፉ አካላትን ዅሉ የኰሚቴው ሰብሳቢ አቶ ትእዛዙ ኮሬ በእግዚአብሔር ስም አመስግነው የአካባቢው ተወላጆች ሥራውን ቢጀምሩትም ሓላፊነቱ ግን ለዅላችንም ነውና እያንዳንዱ ምእመን እግዚአብሔር ከሰጠው ገንዘብ ላይ ዐሥራት በማውጣት የገዳሙን ልማት መደገፍ እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡ በመቀጠል በዕለቱ የተሰበሰበውን ገንዘብ ያበረከቱ ምእመናንን ሰብሳቢው ካመሰገኑ በኋላ ይህ ገቢ ለታቀደው ልዩ ልዩ ተግባር በቂ ስለማይኾን መላው ሕዝበ ክርስቲያን በያሉበት ርብርብ እንዲያደርጉና የገዳሙን ልማት በጋራ እንዲደግፉ በኰሚቴው አባላት ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ መርሐ ግብሩም በአባቶች ጸሎት ተፈጽሟል፡፡

img_0774

አቶ ትእዛዙ ኮሬ የኰሚቴውን የሥራ እንቅስቃሴ ሪፖርት ሲያደርጉ

በቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም ሊሠራ የታቀደውን መንፈሳዊ ተግባር በገንዘብ፣ በጉልበት፣ በቁሳቁስ ወይም በሐሳብ ለመደገፍ የምትፈልጉ ምእመናን በስልክ ቍጥር፡- 09 11 72 27 93 ወይም 09 21 06 23 82 በመደወል ተጨማሪ መረጃ መጠየቅና ድጋፍ ማድረግ የምትችሉ መኾኑን ኰሜቴው ያሳስባል፡፡ እኛም እንደ ዝግጅት ክፍል የኰሜቴው ሥራና የምእመናኑ ተሳትፎ አርአያነት ያለው፣ ሊበረታታ የሚገባው ተግባር በመኾኑ ይህን መንፈሳዊ እንቅስቃሴ በዚህ መልኩ አስታወስናችሁ፡፡ በመጨረሻም ይህን የትሩፋት ሥራ በመደገፍ የሚጠበቅብንን የልጅነት ድርሻ እንወጣ በማለት መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአደረጃጀት መዋቅር እንዲጸድቅ በዕንባ ተጠየቀ

 ጥር 6/2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

  • ቅዱሰ አባታችን ለልጆቼ ምን ላውርሳቸው? ሙስናን? የምእመናን ተወካይ
  • የቤተ ክርስቲያኗን አስተዳደር እናስተካክላለን ብለን ከዚህ ደርሰን ወደኋላ እንመለሳለን ማለት ዘበት ነው፡፡ በጭራሽ አይሞከርም!!! ሐቋንም ይዤ እጓዛለሁ!!!  ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ያስጠናው መዋቅራዊ ለውጥ ቤተ ክርስቲያናችንን ወደ ተሻለ ልማት ያራምዳል፤ ሙስናን ያጠፋል፤ወደ ሌላ በረት የገቡትን በጎች ይመልሳል፤ እኛም የቤተ ክርስቲያን አካል በመሆናችን የተሻለ አገልግሎት እንድንሰጥ የሚያደርገን በመሆኑ በአስቸኳይ ተግባር ላይ እንዲውልልን በማለት በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚገኙ ምእመናን ጥር 5 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ለቅዱስ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በንግግርና በእንባ ጠየቁ፡፡

ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ጀምሮ ምእመናን በጠቅላይ ቤተ ክህነት ግቢ ውስጥ መሰባበሰባቸውን ቀጥለዋል፡፡ የምእመናኑ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት በቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት በመገኘት ምእመናን የሚያቀርቡት ጥያቄ እንዳላቸውና ይህንንም ለማቅረብ እንዲችሉ ፈቀዳቸውን ለመጠየቅ ቀርበዋል፡፡ የቅዱስነታቸው ልዩ ጽ/ቤት በርካታ ምእመናንን ማስተናገድ ስለማይችል 60 ምእመናን ብቻ እንዲገቡ ተፈቀደ፡፡ ሆኖም ግን በግቢው ውስጥ ቁጥራቸው ከ500 በላይ ምእመናንና ምእመናት በመገኘታቸው የጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ እንዲፈቀድ ተደርጎ ምእመናንን ወደ አዳራሹ በመግባት ቦታቸውን ያዙ፡፡

ቅዱስነታቸው ምእመናኑን ለማነጋገር ፈጠን ፈጠን እያሉ ወደ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ገብተው በመምጣት በግራም፤ በቀኝም የሚገኙትን ምእመናንን እየባረኩ ቦታቸውን ከያዙ በኋላ መርሐ ግብሩን በጸሎት ከፍተዋል፡፡
ከጸሎት በኋላ የምእመናን ተወካዮች ለቅዱስነታቸው ጥያቄዎቻቸውን በጽሑፍ ማቅረባቸውን ቀጠሉ፡፡

“በአኩሪ ታሪክና ምግባር የምትታወቀው ቤተክርስቲያናችን የዘመናት ስሟንና ክብሯን የማይመጥን እኩይ ተግባራት የሚፈጸምባት ቦታ፤ ከሃይማኖት ይልቅ ግላዊ ጥቅም በሚያስቀድሙ የውስጥ አርበኞች ብልሹ አሠራር፤ ዘረኝነት፤ ሙስና እና የሥነምግባር ጉድለት ጎልቶ የሚታይባትና ተከታዮቿን የሚያሸማቅቅ ተግባር የሚፈጽሙባት እየሆነች መጥታለች” በማለት በእድሜ ገፋ ያሉ አዛውንት በንባብ ገለጹ፡፡

የውስጥ የቤተክርስቲያን ጠላቶች ያሏቸውንም መለያቸውን ሲገልጹ፡- “ዘመናዊ የፋይናንስ ሥርዓት ኃላፊነትና ተጠያቂነት ሥራ ላይ እንዳይውል በጥብቅ ይከላከላሉ፤ ከአጥቢያ ጀምሮ እስከ ሀገረ ስብከት እንዲሁም ጠቅላይ ቤተ ክህነት ድረስ በተዘረጋ የሙስና መረብ ከሕጋዊ መዋቅሩ በበለጠ እርስ በእርስ በመደጋገፍ፤ የተፈጸሙ ጥፋቶችን ይሸፋፈናሉ፤የሥራ ዕድገት በሙያና በትምህርት ብቃት ላይ የተመሠረተ ሳይሆን በዘመድና በጉቦ እንዲፈጸም ያደርጋሉ፣ ጥፋተኛነቱ የተረጋገጠ የደብር አለቃ ወይም ኃላፊ ላይ ተገቢውን የሥነ ሥርዓት ዕርምጃ በመውሰድ ፋንታ ወደ ሌላ የተሻለ ቦታ እንዲዘዋወሩ ይደረጋል” በማለት በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እየተካሔደ ያለውን ብልሹ አሠራር ተቃውመዋል፡፡

አዛውንቱ ቀጥለውም በአሁኑ ወቅት በሰፊው የሚስተዋለው የሥነ ምግባር ግድፈቶች፣ ጎጣዊ/ዘረኛ አሠራሮችና የሙስና መንሰራፋት ለመምዕመናን ወደ መናፍቃን ጎራ መጉረፍ ምክንያት ከመሆናቸውም ባሻገር ፤በቁጥራቸው ጥቂት የማይባሉ የቤተክርስቲያን አገልጋዮች የተጠናና የተደራጀ በሚመስል ሁኔታ የሚፈጽሙትን የሥነ ምግባር ጉድለቶች በማየት አንዳንድ ምዕመናን ከቤተክርስቲያን እየራቁ እንደሚገኙ ጠቁመዋል፡፡

“የአደረጃጀትና የአሠራር ማሻሻያ ጥናቱ ተግባራዊ ሆኖ ቤተክርስቲያኒቱን ሰንገው አላንቀሳቅስ ያሏት ሙስናና ጎጠኝነት ተወግደው፤ ምዕመናን ለቤተክርስቲያን የሚሰጡት ገንዘብ ለታለመለት ዓላማ ለማዋል ያስችላል ተብሎ በጉጉት ሲጠበቅ፤ በጥናቱ ያልተደሰቱ የተወሰኑ ግለሰቦች ባቀረቡት ቅሬታ ጥናቱ ተግባራዊ ከመሆን ታግዶ እንደገና ባዲስ መልክ እንዲታይ መወሰኑን በከፍተኛ ድንጋጤ ነው የሰማነው፡፡ በቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ተንሠራፍቶ የቆየው ሙስናና ብልሹ አሠራር ጊዜ ሊሠጠው የማይገባ ለነገ ሊባል የማይችል ባስቸኳይ ርምጃ መወሰድ ያለበት ስለሆነ የቤተክርስቲያቱን ሥር የሰደደና የተከማቸ ችግር ያስወግዳል ተብሎ ተስፋ የተጣለበትና የቤተክርስቲያኒቱ የበላይ አካል በሆነው በቅዱስ ሲኖዶስ የጸደቀው ጥናት ባስቸኳይ ተግባራዊ እንዲደረግ በአጽንኦት እንጠይቃለን” ብለዋል፡፡

የተቋማዊ ለውጡ ጥናት በቅዱስ ሲኖዶስ ተቀባይነት ማግኘቱ በራሱ ከፍተኛ ውጤት ቢሆንም አስፈላጊው የአፈጻጸም ስልትና በቁርጠኝነት ሥራ ላይ ሊያውል የሚችል ቅን ታታሪ ታማኝ ተግዳሮቶችን በከፍተኛ ጽናት መቋቋም የሚችል የሰው ኃይል ካልተመደበለት ብልጣብልጦቹ እጅ ወድቆ የታሰበውን ውጤት ሳያስገኝ ሊከሽፍ እንደሚችል የጠቆመው መግለጫው፤ ተቋማዊ ለውጡን በተሟላና በተሳካ ሁኔታ ሥራ ላይ ለማዋልና ዘለቄታማነቱን ለማረጋገጥ ይቻል ዘንድ ትኩረት ያስፈልጋቸዋል ያሏቸውን ነጥቦች በዝርዝር አቅርበዋል፡፡

  1. በጥናቱ ላይ ጥያቄ ያለው ግለሰብ ወይም ቡድን ቢኖር ጥያቄውን በዝርዝር አቅርቦ በጥናት ቡድኑ ታይቶ በቅዱስ ሲኖዶስ የሚታመንበት ነገር ካለ አስፈላጊው ማሻሻያ ከሚደረግበት በስተቀር በጉጉት የምንጠብቀው የጥናት ውጤት ቢቻል ለማስቆም ካልተቻለም ለማዘግየት እንደገና በአዲስ መልክ እንዲታይ እየተደረገ ያለው አካሄድ ቆሞ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ልዕልና ተጠብቆ በውሳኔው መሠረት እንዲፈጸም እንዲደረግ፤
  2. የተጠናውን የአሠራርና የአደረጃጀት ጥናት የሚገመግም አዲስ ኮሚቴ በተመለከተም ጥናቱን ሊያዳብር በሚችል መልኩ በፍጥነት ሰርተው ያቀርባሉ ብሎ ለማሰብ ከኮሚቴው አባላት መካከል ከአሁን ቀደም በሀገረ ስብከቱም ሆነ በጠቅላይ ቤተክህነት ውስጥ በተመሳሳይ ችግር ተጠቃሽ የሚሆኑ ሰዎች መካተታቸው ያሳሰበን በመሆኑ እንደገና እንዲታይልን እንዲደረግ
  3. ተቋማዊ ለውጡን አስመልክቶ ቅዱስ ሲኖዶስ ያስተላለፈው ውሳኔ እንዳይፈጸም በሚያውኩና በሚቃወሙ ላይ ሌሎችን ሊያስተምር የሚችል ጥብቅ የሥነ ሥርዓት ርምጃ እንዲወሰድ እንዲደረግ፤
  4. ከቅን የቤተክርስቲያን አገልጋይ ካህናትና ሠራተኞች፣ ከሰንበት ት/ቤት እንዲሁም ከምዕመናን የተውጣጣ ተጠሪነቱ ለቅዱስ ሲኖዶስ የሆነ የተቋማዊ ለውጥ አስፈጸሚ አካል እንዲቋቋም፤
  5. ከዚህ ቀደም በቤተክርስቲያን ሀብትና ንብረት ላይ ከፍተኛ ምዝበራ የፈጸሙ ሁሉ ጉዳያቸው ተጣርቶ ተገቢው ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድልን፣
  6. ስለ ጎጠኝነትና ሙስና አስከፊነት የሥልጠናና ትምህርት መርሃ ግብር ቀርጾ ተግባራዊ እንዲደረግ፣
  7. ከሙስና የጸዱትንና የላቀ መልካም ተግባር የሚፈጸሙትን አገልጋዮች በመሸለም እንዲበረታቱ እንዲደረግ፣
  8. ቤተክርስቲያኒቱ ከወቅታዊ ሁኔታዎች አንጻር እራሷን እየፈተሸች፣ ችግሮቿን እየለየች መፍትሔ በማስቀመጥ ተግባራዊ እርምጃ ለመውሰድ የሚያስችላት የጥናትና ምርምር ማዕከል እንዲቋቋም እንዲደረግ፣
  9. ከመንግሥት አሠራር ልምድ በመቅሰም በስፋት የተንሰራፋውን የሙስና ተግባር መቋቋም ይቻል ዘንድ የሥነ ምግባርና ጸረ ሙስና አካል ከጠቅላይ ቤተክህነት እስከ አጥቢያ ቤተክርስቲያን እንዲቋቋም እንዲደረግ በቅድስት ቤተክርስቲያናቸን ስም አበከረን እንጠይቃለን በማለት በመግለጫቸው አቅርበዋል፡፡

በተጨማሪም በቅዱስነታቸው ፈቃድ የምእመናን ተወካዮች ጥናቱን አስመልከቶ ሀሳባቸውን ከገለጹት መካከል፡-

“ይህ አዲስ መዋቅር ቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ብዝበዛን፤ የአስተዳደር ብልሹነትን፤ ግማሹ እያለቀሰ ሌላው እየተደሰተ እንደፈለገ እየሆነ ያለበት አስቸጋሪ ሁኔታን የሚያስተካክል ነው፡፡ የዚህ መዋቅር መውጣት የሚያስደነግጣቸው ይኖራሉ፡፡ ምክንያቱም የገንዘብ ብዝበዛን፤ ብልሹ አስተዳደርን ስለሚያስቆም በዚህ ሕይወት ውስጥ የበለጸጉና ከፍተኛ ጥቅማጥቅሞችን ያገኙ የነበሩ ግለሰቦች የለመዱት ሲቋረጥባቸው ሊደነግጡ ይችላሉ፡፡ እንኳን ቤተ ክህነት በቤተ መንግሥት ውስጥ አዳዲስ አሠራሮች ለሀገርና ለሕዝብ የሚጠቅሙ ጉዳዮች ሲነሱ ሁሉም እልል ብሎ አይቀበልም፡፡ ይህ የመዋቅር ጥናት በቤተ ክርስቲያናችን ታሪክ ውስጥ ታላቅ ምእራፍ የከፈተ ነውና እርስዎ ጀምረውታል፤ ለስምዎ፤ ለታሪክዎና ለቤተ ክርስቲያኗ ሕልውና ሲሉ ያስፈጽሙት፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ከብዝበዛ ያድኗት፤ ከፍጻሜም ያድርሱት” በማለት የእድሜ ባለጸጋና ቀድሞ ቃለ ዓዋዲን ካረቀቁ ሊቃውንት መካካል የነበሩ አባት እንባ እየተናነቃቸው ተናግረዋል፡፡

አንድ እናትም ንግግራቸውን ቀጠሉ “የእግዚአብሔር ዓላማ የጠፉትን ወደ ቤቱ ለመመለስ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን ትንሣኤ ደርሷል ብለን እናምናለን፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን ችግር በሚገባ አውቀናል፤አዝነናል፤ አልቅሰናል፤ ዋጋችንንም አግኝተናል፤ ተቀጥተናል ይበቃናል፡፡ ልጆቻችን ቤተ ክርስቲያናችንንና እምነታችንን ይረከቡ ዘንድ እኛ ወላጆች ድልድዮች ነን፡፡ቤተ ክርስቲያናችንን ለልጆቻችን ለማስረከብ እንድንችል ይርዱን፡፡ቅዱስ አባታችን ለልጆቼ ምን ላውርሳቸው? ሙስናን??? ቅዱስ አባታችን ቤተ ክርስቲያን አሁን በሌላ በረት ያሉ ልጆቿን የምትሰበስብበት ሰዓት ደርሷል፡፡ይህ ጥናት ተግባራዊ ቢሆን የጠፉ ልጆቿ በሕይወት ይኖራሉ፡፡በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተሰበሰብነው ምእመናንን እንዳንበተን ይህ መዋቅር በቶሎ ተግባራዊ ይደረግልን” በማለት እያለቀሱ ተማጽነዋል፡፡

ቅዱስነታቸውም ለቀረቡት የምእመናንን ጥያቄዎች በማረጋጋት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ “ይህንን ጉዳይ ገና ከመግባቴ ያወጅኩት እኔ ነኝ፡፡ሙስና፤ የገንዘብ ብክነት፤ ሓላፊነት የጎደለው አስተዳደር እንዲጠፋና መልካም አስተዳደር፤ ሓላፊነትና ተጠያቂነት ያለው አሠራር እንዲሰፍን መሥራት አለብን፡፡ አንድ ጥናት የተወሰኑ ሰዎች ያጠኑታል፡፡ ከዚያም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲያዩት ይደረጋል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የቤተ ክርስቲያንን ቋንቋ፤ ባሕል ተመርኩዘው ቢያጠኑት ይጠነክራል፡፡ ለቅዱስ ሲኖዶስ ቀርቦ ይጸድቃል፡፡ በፍጹም ስጋት አይግባችሁ፤ ጩኸቱ የእኔ ነው፡፡ ተጠናክሮ እንጂ ተዳክሞ አይመጣም፡፡

ቤተ ክርስቲያን ትክክለኛ መስመሯን እንድትይዝ ነው ፍላጎታችን፡፡ የቤተ ክርስቲያኗን አስተዳደር እናጠራለን፤ እናስተካክላለን ብለን ከዚህ ደርሰን ወደኋላ እንመለሳለን ማለት ዘበት ነው፡፡ በጭራሽ አይሞከርም!!! ሐቋን ይዤ እጓዛለሁ!!! እናንተም ደግፋችሁን ቤተ ክርስቲያናችን የቀድሞ ቅድስናዋን መመለስ አለብን፡፡ ስለዚህ የቤተ ክርስቲኗ ሊቃውንትና የዘመናዊውን የአስተዳደር ትምህርት የተማሩ ምሁራን ተቀናጅተው፤ አይተውት ጠርቶ እንዲመጣ ይደረጋል፡፡ ችግር ካለበት ያኔ ሀሳብ ልንሰጥበት እንችላለን፡፡አይዟችሁ አትፍሩ” በማለት ምእመናንን በማረጋጋት ባርከው የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡ ምእመናንም እግዚአብሔር ይመስገን ይህችን ቀን ቀድሶ ለሰጠን እያሉ በመዘመር ቅዱስነታቸውን ሸኝተዋል፡፡