የሀዋሳ ማእከል ሕግና ዕቅበተ እምነት ዋና ክፍል ተጠሪ የነበሩት አቶ አስማማው ታመነ አረፉ

በማኅበረ ቅዱሳን የሀዋሳ ማእከል ሕግና ዕቅበተ እምነት አገልግሎት ዋና ክፍል ተጠሪ የነበሩት አቶ አስማማው ታመነ ሐምሌ 18 ቀን 2012 ዓ.ም በደረሰባቸው ድንገተኛ የትራፊክ አደጋ ሕይወታቸው እንዳለፈ የሀዋሳ ማእከል አስታወቀ፡፡

የጅማ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች እስር እየተፈጸመባቸው እንደሆነ ታወቀ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በጅማ ሀገረ ስብከት የኮሮና ወረርሽኝን ለመከላከል የተላለፍወን አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሽፋን በማድረግ አግባብ ያልሆነ እስርና እንግልት በምእመናንና በአባቶች ላይ እየተፈጸመ መሆኑን በማኅበረ ቅዱሳን የጅማ ማእከል አስታወቀ፡፡

የቤተ ክርስቲያንን ቅርስ ዘርፈው እጅ ከፍንጅ የተያዙ ተጠርጣሪዎች ከእስር ተፈቱ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሜታ ሮቢ ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር የሚገኘውን የሙጤ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያንን ቅርስ ዘርፈው እጅ ከፍንጅ የተያዙ አራት ግለሰቦች በፍርድ ቤት ትእዛዝ ከእስር መፈታታቸውን የወዳ ቤተ ክህነቱ ሥራ አስኪያጅ መሪጌታ ክፍሌ ቱቦ አስታወቁ፡፡

በኮሌራ በሽታ ጉዳት ለደረሰባቸው ምእመናን ድጋፍ ተደረገ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት በኮሌራ ወረርሽኝ ምክንያት ጉዳት ለደረሰባቸው የዳሰነች ሕዝበ ክርስቲያን የእርዳታ ድጋፍ ተደረገ፡፡

ዘጠነኛው የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጉባኤ ሊካሄድ ነው

ዘጠነኛው የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጉባኤ በመጭው እሑድ ግንቦት ፴ ቀን ፳፻፲፪ ዓ/ም ሊካሄድ እንደሆነ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊ መምህር ዕንቈ ባሕርይ ተከሥተ አስታወቁ፡፡

የመካነ ነገሥት ግምጃ ቤት ማርያም የሐዲስ ኪዳን ደቀ መዛሙርት ተመረቁ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በማእከላዊ ጎንደር ሀገረ ስብከት በመካነ ነገሥት ግምጃ ቤት ማርያም የመጻሕፍተ ሐዲሳት እና ሊቃውንት ጉባኤ ቤት 18 የሐዲስ ኪዳን ደቀ መዛሙርት ኅዳር 21 ቀን 2012 ዓ.ም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እና ሕዝበ ክርስቲያን በተገኙበት በታላቅ ድምቀት ተመረቁ፡፡

የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታይ የሆኑ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ግፍ እየተፈጸመባቸው መሆኑ ተገለጸ

በአለፉት ሳምንታት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታይ ተማሪዎችን ከሚማሩበት ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች በማሳደድ እና የተወሰኑትን እንዳይወጡ በማገድ ሙሉ በሙሉ ከትምህርት ማፈናቀል የጀመሩት የጥፋት ኃይሎች በመቱና ቦንጋም ተመሳሳይ ድርጊት እየፈጸሙ መሆኑ ተገለጸ፡፡

የቦሌ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያንን ለማጥቃት የተደረገው ሙከራ ከሸፈ!

ኅዳር ፲፪ የቅዱስ ሚካኤል ዓመታዊ በዓል ከተከበረ በኋላ ኅዳር ፲፭ በቤተ ክርስቲያኑ ዙሪያ ተሰቅለው የነበሩትን ሰንደቅ-ዓላማዎችን እያወረዱ ወደነበሩት የሰንበት ትምህርት ቤት አገልጋዮች…..

አብያተ ክርስቲያናት መቃጠላቸውና መዘረፋቸው ተገለጸ

 

                                                                                                                                                                                                                                                                       በሕይወት ሳልለው     

በሲዳማ ጌዴኦ አማሮና ቡርጂ አህጉረ ስብከት በሁላ ወረዳ ቤተክህነት ሥር ወይም በሁላና ቦና ዙሪያ ወረዳ ፫ አብያተ ክርስቲያናት በጥፋት ኃይሎች መቃጠላቸውና ፪ ደግሞ መዘረፋቸው  ተገለጸ፡፡ከሐምሌ ፲፩ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ጀምሮ ለሦስት ተከታታይ ቀናት በቆየው የሲዳማ ዞን ክልል ይሁንልን ጥያቄ ረብሻ ለአብያተ ቤተ ክርስቲያናት መቃጠልና መዘረፍ መንስኤ መሆኑም ተገልጿል፡፡

መጋቤ ጥበባት ቀሲስ ሞላልኝ መርጊያ፤ የሲዳማ፤ጌዴኦ፤አማሮና ቡርጂ አህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ «ሀገረ ስብከቱ ከወረዳ ቤተክህነት ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ጥበቃቸውን እንዲያጠናክሩና ምእመናንም ተደራጅተው ራሳቸውንና አብያተ ክርስቲያናትን እየጠበቁና እንዲከላከሉ መልእክት የተላለፈ ቢሆንም የጥፋት ኃይሎቹ ከአካባቢው የፀጥታ ኃይልና ከምእመናን አቅም በላይ በመሆናቸው የከፋ ጉዳት ሊያደርሱ ችለዋል» በማለት አስረድተዋል፡፡የደረሰው ቃጠሎ በመጀመሪያ በዶያ ቅዱስ ሚካኤል የ፲፰ አባወራዎችን ንብረት በማጥፋት፤ ፸፪ ንዋያተ ቅዱሳትን ሙሉ በሙሉ በእሳት አውድሟል፡፡ ቤተክርስቲያኗን ለማትረፍ ሲረባረቡ የነበሩትን ፲ ሰዎችም አደጋ እንደደረሰባቸው ታውቋል፡፡

ዶያ ቅዱስ ሚካኤል

በሌላ በኩል በ፳፻፰ ዓ.ም. ተመሥርቶ ከኅዳር ፲ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም. ጀምሮ አገልግሎት መስጠት የጀመረው የጋታማ ገብረ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን በአካባቢው ጥፋት ኃይሎች በእሳት ሙሉ ለሙሉ ተቃጥሏል፡፡ ፵፫ አባወራዎች ንብረታቸው ሲዘረፍና ሲቃጠል፤  በአይነት ፵፯ የሚሆኑ ንዋያተ ቅድሳት ሙሉ በሙሉ በእሳት ተቃጥለዋል፡፡

፵፫ የሚሆኑ አባወራዎች ደግሞ ከቤተሰቦቻቸው ጋር በየሰው ቤት ተጠልለው እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የገታማ ገብረ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን

የሉዳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን የውስጥ ንዋያተ ቅድሳት በእሳት ተቃጥለዋል፡፡ የቤተ  ክርስቲያኑ በር፤መስኮት እና መንበር ሲሰባበር፤ደጀ ሰላሙ ሙሉ በሙሉ ወድሟል፡፡ ሥርዓተ አምልኮ ሲፈጽሙ በነበሩ ምእመናን ላይም የሀብት ዝርፊያ በቤታቸው ተካሔዷል፡፡ አቶ ሽፈራው ማሞ በተባሉት አባት ከፍተኛ የአካል ጉዳትም እንደደረሰ ምንጮች አያይዘው ጠቅሰዋል፡፡

ሉዳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን

የጭሮኔ ቅዱስ አማኑኤል ቤተክርስቲያን ታቦተ ሕጉ እስከ አሁን ያለበት ቦታ አልታወቀም፡፡ ቤተ ክርስቲያኑንና ንዋያተ ቅዱሳቱን ያቃጠሉት ግለሰቦች የካህናትን ልብሰ ተክህኖና የሰንበት ተማሪዎች አልባሳትን ለብሰው፤ ቆብ አጥልቀውና መስቀል ይዘው በመዞር ከጨፈሩ በኋላ ተመልሰው ቤተ  ክርስቲያኗን ማቃጠላቸውን የዐይን እማኞች አብራርተዋል፡፡

ንዋያተ ቅዱሳቱን

በተጨማሪም በ፲፱፻፱ የተመሠረተው የቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን ደግሞ በደረሰው ጥቃት ሙሉ ለሙሉ ተዘርፏል፡፡ አገልግሎት እየሰጡ የነበሩ መቃብር ቤቶች በርና መስኮቶች ተሰባብሯል፡፡

የቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ  ክርስቲያን

ሦስት ኦርቶዶክሳውያን በአሰቃቂ ሁኔት ተገድለዋል፡፡ ፪፻፶ ምእመናን ተሰደው ቦሬ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ተጠልለው ይገኛሉ፡፡በተፈጠረው ችግር የ፹፭ ዓመቱ አቶ ግርማ መልካ መንገድ ላይ ተገድለው ሲገኙ፤አቶ የኔነህ ተስፋዬ መገደላቸውን፤ እና ወጣት አድሱ የኔነህ ደግሞ አባቱን እያሳከመ እንዳለ መገደሉን ተገልጿል፡፡

ይህን ችግር ለመቅረፍ ሀገረ ስብከቱ ከመከላከያ ሠራዊት ጋር በመተባበር በአካባቢው ላይ የነበሩትን ምእመናን ለመታደግ ችሏል፡፡ የተጎዱ ምእመናንን ለመደገፍና የተቃጠሉ አብያተ ክርስቲያናትን መልሶ ለማቋቋም ኮሚቴ መቋቋሙን የሐዋሳ ማእከል ገልጿል፡፡

በመሆኑም የኮሚቴው አባላት በጥፋቱ የተቃጠሉ አብያተ ክርስቲያናት መረጃ በመሰብሰብ፣ ምእመናንን በማጽናናትና ከሐዋሳ ከተማ ነዋሪዎች ድጋፍ በማሰባሰብ ተጎጂዎችን እየረዱ እንደሆነ ሀገረ ስብከቱ ገልጿል፤ ይበልጥ ለመደገፍ በባንክ አካውንት ቁጥር 1000290647936፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ውስጥ ከፍቶ ገንዘብ በማሰባሰብ ላይ ይገኛል፡፡