የቅዱስ ሲኖዶስን ጉባኤ መጀመር አስመልክቶ ከቅዱስ ፓትርያሪኩ የተሰጠ መግለጫ

ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች፣ እንደሚታወቀው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በዛሬው ዕለት ተጀምሯል፤ ቅዱስ ፓትርያሪኩ ጠዋት ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ለጋዜጠኞች የሰጡትን ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ወዓዲ እብለክሙ ለእመ ኀብሩ ክልኤቱ አው ሠለስቱ እምኔክሙ በውስተ ምድር በእንተ ኵሉ ግብር ዘሰአሉ ይትገበር ሎሙ በኀበ አቡየ ዘበሰማያት እስመ ኀበ ሀለዉ ክልኤቱ ወሠለስቱ ጉቡአን በስምየ ህየ እሄሉ አነ ማእከሎሙ፤ ዳግመኛም ከእናንተ ሁለቱ ወየም ሦስቱ በምድር ላይ ስለሚለምኑት ሥራ ሁሉ ቢተባበሩ፣ በሰማያዊ አባቴ ዘንድ ይደረግላቸዋል፤ ሁለቱ ወይም ሦስቱ በስሜ ተሰብስበው ካሉበት፣ እኔ ከዚያ በመካከላቸው እገኛለሁና /ማቴ.፲፰፥፲፱-፳/፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ከጌታችን፣ ከአምላካችንና ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተሰጠንን ዓቢይ ተልእኮ ወይም ሐዋርያዊ አገልግሎት በየተሠማራንበት ሀገረ ስብከት ስናከናውን ቆይተን፣ በዓለ ትንሣኤውን ካከበርን በኋላ፣ በቀኖና ሐዋርያት ድንጋጌ መሠት፣ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን ጉዳዮች ለመነጋገር በዚህ በረክበ ካህናት ዓመታዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አንድ ላይ ስለሰበሰብን፣ አምላካችን እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማይታበል ቃሉ እንዳስተማረን፣ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የገባው ቃል ኪዳን አለ፤ እርሱም ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር የተፈጸመ ጽኑ ቃል ኪዳን ነው፡፡ ቃል ኪዳኑም፡- ሁለቱ ወይም ሦስቱ በስሜ በተሰበሰቡበት፣ እኔ ከዚያ በመካከለቸው እገኛለሁ ይላል፡፡ በሁሉም ዘንድ እንደሚታወቀው፣ ቃል ኪዳን በሁለት ወገኖች መካከል የሚፈጸምና ለቃል ኪዳኑ መከበር የሁለቱንም የቃል ኪዳን አካላት ኃላፊነት በግልጽ የሚያስቀምጥ ነው፤በዚህ ሁኔታ እግዚአብሔር ከጥንት ጀምሮ ከቅዱሳን አበው ጋር ቃል ኪዳን መሥርቶ እንደነበረ በቅዱስ መጽሐፍ በየቦታው ተጽፎ እናገኛለን፡፡

ይሁንና በዘመነ ሐዲስ ጌታችን ቃል ከገባባቸው ዓበይት ነገሮች አንዱ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ነው፡፡ በዚህ ቃል ኪዳን ውስጥ ቅዱስ ሲኖዶስ በስመ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲሰበሰብ ሓላፊነት ተሰጥቶታል፡፡ ጌታችንም በስሙ በሚደረግ ጉባኤ እንደሚገኝ ቃል ገብቶአል፡፡

በመሆኑም የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በርእሰ መንበርነት፣ ቅዱስ ፓትርያርክ በመሪነት፣ ሊቃነ ጳጳሳት በአባልነት የሚገኙበት ዓቢይ ጉባኤ ነው፡፡ ቅዱስ ወይም ልዩ ጉባኤ የሚያሰኘውም ቅሉ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በርእሰ መንበርነት የሚገኝበት በመሆኑ ነው፡፡ ይህ ጉባኤ ጌታችን እስከ ዓለም ፈጻሜ ድረስ እንደማይለየው ሲገልጽ፡- ወናሁ አነ እሄሉ ምስሌክሙ እስከ ኅልቀተ ዓለም፤ እነሆ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ እኔ ከናንተ ጋር ነኝ ብሎ በቃሉ አረጋጦአል /ማቴ.፳፰፥፳/፡፡

እንግዲህ በየጊዜው ስመ እግዚአብሔርን ጠርተን በስሙ፣ ስለስሙ ብለን የምናካሂደው ቅዱስ ጉባኤ ወይም ቅዱስ ሲኖዶስ ይህን ያህል ታላቅ ክቡርና ጽኑ የሆነ አምላካዊ ቃል ኪዳን ያለው እንደመሆኑ መጠን፣ ለደረጃው በሚመጥን ክብርና ልዕልና መካሄድ ይኖርበታል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ጌታችን፣ አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን በአደራነት ያስረከበ ለዚህ ጉባኤ እንደሆነ በውል የሚታወቅ ነው፡፡

ይህ ቅዱስ ጉባኤ የእግዚአብሔር መንግሥት ወኪል እንደመሆኑ መጠን ድንበር የለውም፤ ምክንያቱም የእግዚአብሔር መንግሥት ድንበር የለውምና፡፡ ይህ ጉባኤ ገደብ የለሽ መንፈሳዊ ሥልጣን ከሕያው አምላክ ሲሰጠው፣ ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፤ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ ከሚል ትእዛዝ ጋር መታዘዙ የቅዱስ ሲኖዶስ መንፈሳዊ ሥልጣን ድንበር የማይገድበው መሆኑን በግልጽ ያሳያል /ማር.፲፮፥፲፭/፡፡

በመሆኑም የዚህ ቅዱስ ጉባኤ ሥራና ሓላፊነት ዓለም አቀፋዊ ይዘት ያለው መሆኑ ሊሠመርበት ይገባል፡፡ ይህም በመሆኑ ነው ዛሬ ቤተ ክርስቲያናችን በሁሉም ክፍላተ ዓለም አብያተ ክርስቲያናትን ከፍታ ሐዋርያዊ ተልእኮዋን በማካሄድ ላይ የምትገኘው፡፡

ይሁንና አሁን የምንገኝበት የሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ወቅት፣ የሴኩላሪዝም አስተሳሰብ ያየለበት፤ የዓለም ሉላዊነት የበረታበት፣ የጽንፈኝነትና የሽብርተኝነት መንፈስ የተስፋፋበት፣ እነዚህ ሁሉ በየፊናቸው ተሰልፈው በሃይማኖት ላይ ከባድ ተጽዕኖ የፈጠሩበት ዘመን ነው፡፡ ዓለም በዚህ ሥጋዊ ፍልስፍና እና ቁሳዊ አምሮት ቤተ ክርስቲያንን ለመውጋት ስትዘጋጅ እኛ የክርስቶስ ወኪሎች እንዲሁ ዝም ብለን የምናይበት ኅሊና ሊኖረን አይችልም፡፡

ቀደምት አበው እሾህን በእሾህ ብለው እንደተናገሩት፣ የዓለምን ጥበብ በክርስቶስ ጥበብ ለመቋቋም፣ በዓለም እየሆነ ያለውን ነገር ሁሉ መከታተልና ማወቅ፣ ለወደፊትም ሊያስከትለው የሚችለውን ሃይማኖታዊ፣ ማኅበራዊ፣ ሰብአዊና ባህላዊ ቀውስ አስቀድሞ በመተንበይ፣ ሕዝቡን በእግዚአብሔር ቃል ኃይል መጠበቅና መንከባከብ ከእኛ ይጠበቃል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

በሃይማኖት ዙሪያ ያንዣበቡ እነዚህ ዓለም አቀፍ ተፅዕኖዎች እጅግ አስጊ ቢሆኑም፣ እነርሱን ለመከላከል ብሎም ለመቀልበስ አሁንም ቢሆን ጊዜው አልመሸም፡፡ በተለይም በሀገራችን ያለው ሕዝብ፣ አሁንም ምርጫው እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን እንደሆነ በተጨባጭ የምናውቀው ሐቅ ነው፡፡ ይህንን ሕዝብ በሚገባ ማገልገል ከተቻለ፣ ችግሩን በሚገባ መቋቋም ይቻላል፡፡

ስለሆነም ሕዝበ ክርስቲያኑን በአግባቡ ለማገልገልና ለመጠበቅ፣ ከሁሉም በፊት የሕዝቡን ጥያቄ ማወቅ ያስፈልጋል፤ ቀጥሎም ለጥያቄው ተገቢ የሆነ መልስ በመስጠት ፍጹም መግባባት መፍጠር ይገባል፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑ ከሃይማኖት መሪዎችና ከአገልጋይ ካህናት የሚጠብቀውን ሁለንተናዊ አገልግሎት በሚገባ ካገኘና በሃይማኖቱ እንዲኮራ የሚያስችል ሁኔታ ከተመቻቸለት፣ ለተጠቀሱ ዓለም ዓቀፍ ተፅዕኖዎች ተንበርካኪ አይሆንም፡፡ ስለሆነም የኛው የጥበቃ ስልት መቀየስ ያለበት በዚሁ መንፈስ አቅጣጫ ነው፡፡

ሕዝበ ክርስቲያኑ በአሁኑ ጊዜ የሚጠይቃቸው ብዙ ነገሮች አሉ፤

ሕዝቡ፣ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና ለሃይማኖት መጠበቂያ ብሎ በእምነት የሚለግሰው ገንዘብና ንብረት ከምዝበራ ተጠብቆ ለታለመለት ዓላማ ብቻ እንዲውል ይፈልጋል፤

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መልካም አስተዳደር ሰፍኖ አድልዎ፣ ጭቅጭቅ፣ ንትርክ፣ መለያየት በአጠቃላይ ከሃይማኖቱ መርሕ ጋር የማይጣጣም ኋላ ቀር አሠራርና አስተሳሰብ ተወግዶ የተስተካከለ ሥርዓትን ማየት ይፈልጋል፤

ስለሃይማኖት ክብርና ህልውና ከልብ የሚቆረቆሩ፣ መልካም የሆነ ሥነ ምግባርና የተስተካከለ ሰብእና ያላቸው እንደዚሁም በኑሮአቸው ሁሉ ለሕዝበ ክርስቲያኑ እንደ ሞዴል የሚጠቀሱ ውሉደ ክህነትና ሠራተኞች እንዲመሩት ይፈልጋል፤

ሕዝቡ ቤተ ክርስቲያን በሁሉም መስክ ጠንካራ ዓቅምን ገንብታ እንደዚሁም ለሕዝበ ክርስቲያኑ መንፈሳዊና ማኅበራዊ ችግር ደራሽና አለሁላችሁ ባይ ኾና ማየት እንደሚፈልግ ከሚያነሣው ጥያቄ ማወቅ ይቻላል፡፡

ብፁዓን ሊቃ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

የእኛ ተልእኮ እግዚአብሔርንና ሕዝብን ማገልገል ከሆነ፣ የሕዝቡ ጥያቄም ከሞላ ጎደል የሚታወቅ ከሆነ፣ በተሰጠን አደራና ሓላፊነት መሠረት የሕዝበ ክርስቲያኑን ጥያቄ በጽሞና አዳምጠንና ተቀብለን፣ በቅዱስ መጽሐፍ አስተምህሮ፣ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ድንጋጌና ባሉን የቤተ ክርስቲያን ሕጎች ማእከልነት፣ ጥያቄውን የማስተናገድ ክርስቶሳዊ ግዴታ አለብን፡፡

ከሕግ የወጣ የሥራ አፈጻጸም ሲኖርም፣ ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ በወቅቱ ማረም ያስፈልጋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቱያናችን የመጨረሻ ውሳኔ ሰጭ አካል እንደመሆኑ መጠን፣ የቤተ ክርስቲያናችንን መልካም አስተዳደር ለማስፈን የሚያስችሉ ሕጎችን፣ ልዩ ልዩ ደንቦችን፣ መመሪያዎችን፣ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በማዘጋጀትና በማጽደቅ፣ እንደዚሁም በአፈጻጸማቸው ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ፣ ሕዝበ ክርስቲያኑን እሰየው የሚያሰኝ አሠራር ማረጋገጥ አለብን፡፡ ይኸ ሲሆን ብቻ ነው ሕዝቡን ከቁሳዊው ዓለም ማዕበል መታደግ የምንችለው፡፡

በመጨረሻም

ይህ የተቀደሰ ክርስቶሳዊና ሐዋርያዊ ጉባኤ ከልዩ ልዩ የቤተ ክርስቲያናችን አመራር አካላትና ከጉባኤው የሚቀርቡትን ሃይማኖታዊ ሀገራዊ ጉዳዮችን በጥልቀት በመፈተሽና በመመርመር እንደዚሁም ሕጋዊና ቀኖናዊ መፍትሔ በማስቀመጥ የተሳካ ውጤት ያስመዘግብ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እየጸለይንና ከልብ እየተመኘን የ፳፻፰ ዓ.ም የረክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ዛሬ መከፈቱን እናበሥራለን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤

አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም

ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን አምስተኛው ዙር ዐውደ ርእይ ተጀመረ፡፡

ዐውደ ርእዩ ለስድስት ተከታታይ ቀናት ከጠዋቱ 2፡00 እስከ ምሽቱ 1፡30 ድረስ ለተመልካቾች ክፍት ኾኖ ይቆያል፡፡

ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በማኅበረ ቅዱሳን የተዘጋጀውና በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው አምስተኛው ዙር መንፈሳዊ ዐውደ ርእይ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ የማኅበሩ ሥራ አመራር አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ እንደዚሁም የዐውደ ርእዩ ተመልካቾች በተገኙበት በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማእከል ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በአባቶች ጸሎት ተጀምሯል፡፡

በጸሎተ ወንጌሉ የተሰበከው ምስባክ፡- ጥቀ ዐቢይ ግብርከ እግዚኦ ወኵሎ በጥበብ ገበርከ መልዐ ምድረ ዘፈጠርከ፤ አቤቱ ሥራህ እጅግ ታላቅ ነው፡፡ ሁሉን በጥበብ አደረግህ፡፡ የፈጠርኸውም ፍጥረት ምድርን ሞላ፤ /መዝ.፻፫፥፳፬/ የሚለው ትምህርት ሲኾን፣ የተነበበው የወንጌል ክፍልም ሉቃ. ፲፥፳፩-፳፬ ያለው ኃይለ ቃል ነው፡፡

ጸሎተ ወንጌሉና ኪዳኑ እንደ ተፈጸመ ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ የመክፈቻ ንግግር ካደረጉ በኋላ ዐውደ ርእዩ በይፋ ለተመልካች ክፍት ኾኗል፡፡

የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ በሚል መሪ ቃል በተዘጋጀው በዚህ ዐውደ ርእይ የቤተ ክርስቲያን ማንነትና ሐዋርያዊ ተልዕኮ በዓለም፣ በአፍሪካና በኢትዮጵያ፣ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ፈተናዎችና ከምእመናን የሚጠበቁ ጉዳዮች የትእይንቱ አርእስት ኾነው ይቀርቡበታል፡፡

ዐውደ ርእዩ ከግንቦት ፲፯-፳፪ ቀን ፳፻፰ (17-22 ቀን 2008) ዓ.ም፣ ከጠዋቱ 2፡00 እስከ ምሽቱ 1፡30 ድረስ ለስድስት ተከታታይ ቀናት ለተመልካቾች ክፍት ኾኖ ይቆያል፡፡

ከመጋቢት ፲፭-፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለተመልካች ሊቀርብ የነበረው ይህ ዐውደ ርእይ ለጊዜው ግልጽ ባልነበረ ምክንያት ታግዶ ቢቆይም፣ ማኅበረ ቅዱሳን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ባደረገው ውይይት እገዳው ተነሥቶ ለእይታ በቅቷል፡፡

Tewahedoapp

ተዋሕዶ የአይፎን አፕሊኬሽን ተሻሽሎ አገልገሎት መስጠት ጀመረ::

አፕሊኬሽኑ ለሁሉም የአፕል ስልኮችና አይፓዶች በሚኾን መልኩ ተሻሽሎ ቀርቧል፡፡

ትምህርቶችን፣ ጸሎታትን፣ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶችን፣ የየዕለቱን ምንባባትና የአብያተ ክርስቲያናት መረጃዎችን ይዟል፡፡

ግንቦት ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

Tewahedoappበሰሜን አሜሪካ ማእከል

በእጅ ስልክ አማካይነት ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ትምህርቶችን፣ ስብከቶችን፣ መዝሙራትንና ጸሎታትን በቀላሉ ማግኘት የሚያስችለው ተዋሕዶ የአይፎን አፕሊኬሽን ተሻሽሎ አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ተገለጠ፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የሰሜን አሜሪካ ማእከል ሙያ አገልግሎትና ዐቅም ግንባታ ክፍል ለዝግጅት ክፍላችን በላከው መረጃ እንደገለጠው፤ በማእከሉ ታቅፈው ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በሞያቸው በሚያገለግሉ አባላት ቀደም ሲል የተዘጋጀው አፕሊኬሽኑ ለምእመናን ሰፊ አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡

ከተጠቃሚዎች በተሰጡ አስተያየቶችና በባለሞያዎቹ ምክርና ጥረት ለሁሉም የዓፕል ስልኮችና አይፓዶች በሚኾን መልኩ ተሻሽሎ ቀርቧል፡፡ በአዲስ መልክ የተሸሻለው ይህ አፕሊኬሽን ከበርካታ ትምህርቶች፣ ጸሎታት፣ መዝሙራት፣ ኪነ ጥበባዊ ዝግጅቶች በተጨማሪ የኢትዮጵያን ካላንደር (በዓላትና አጽዋማት ማውጫ)፣ በየዕለቱ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባትን እንዲሁም በአሜሪካ፣ በካናዳና አውሮፓ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትን አድራሻና መሠረታዊ መረጃዎችን ያካተተ ነው፡፡

በተጨማሪም አፕሊኬሽኑ ልዩ ልዩ ዓመታዊ በዓላት እና አጽዋማት ሲደርሱ ለተጠቃሚዎቹ ማስታወሻ እንዲልክ ኾኖ ተዘጋጅቷል፡፡ የማእከሉ ሙያና ዐቅም ማጎልበቻ ክፍል ምእመናን ይህንን አፕሊኬሽን እዚህ ላይ በመጫን እንዲገለገሉ፣ ላልሰሙትም እንዲያሰሙ ሲል ያበስራል፡፡

የሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ ሰባተኛ ዓመት የዕረፍት ቀናቸው ተዘከረ

በዕለቱ ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት በሚል ርእስ በ፲፱፻፺፮ ዓ.ም ባዘጋጁት መጽሐፋቸው ላይ የዳሰሳ ጥናት ቀርቧል፡፡

ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ በስእለት መልክ ለእግዚአብሔር መሰጠታቸውን እኅታቸው ተናግረዋል፡፡

ወጣቱ ትውልድ የእርሳቸውን ፈለግ ተከትሎ ቤተ ክርስቲያንን መጠበቅ ከቻለ አባ አበራ ሕያው ናቸው እንጂ አልሞቱም ተብሏል፡፡

ግንቦት ፲፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የሊቀ ገባኤ አባ አበራ በቀለ (ስመ ጥምቀታቸው ኃይለ መስቀል) ሰባተኛ ዓመት የዕረፍት ቀናቸው መታሰቢያ ቤተሰቦቻቸው፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራሮችና አባላት በተገኙበት ግንቦት ፲፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በማኅበሩ ሕንፃ ተዘክሯል፡፡

በዕለቱ ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት በሚል ርእስ በ፲፱፻፺፮ ዓ.ም ባዘጋጁት መጽሐፋቸው ላይ የዳሰሳ ጥናት ያቀረቡት ዲያቆን አሻግሬ አምጤ እንደገለጹት አባ አበራ ባለ ፬፹፬ ገጽ በሆነው በዚህ መጽሐፋቸው መግቢያ ላይ ክርስትና የፍቅር ሃይማኖት መሆኑንና የሃይማኖታችን ታሪክ በፍቅር ተጀምሮ በፍቅር መፈጸሙን አስረድተዋል፡፡ እንደዚሁም የሰው ልጅ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ ሦስት ዐበይት ነጥቦች እንደሚያስፈልጉና እነዚህም ማመን፣ መጠመቅና ትእዛዛትን መጠበቅ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡

በትምህርተ ሃይማኖት መቅድማቸውም ሃይማኖት ከእግዚአብሔር ለሰው የተሰጠ መሆኑን አስረድተው እምነት የሁሉ ነገር መሠረት እንደሆነ በማብራራት መሠረት ሕንፃዎችን ሁሉ እንደሚሸከም እምነትም ምግባራትን ሁሉ እንደምትይዝ፣ ሕንፃ ያለመሠረት እንደማይቆም ምግባርም ያለ ሃይማኖት እንደማይጸና የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን ትምህርት ጠቅሰው አስተምረዋል፡፡

በዳሰሳ አቅራቢው እንደተብራራው መጽሐፉ በክፍል አንድ አንቀጹ ሠለስቱ ምእት በኒቅያው ጉባኤ የደነገጉትን ጸሎተ ሃይማኖት እና በጉባኤ ቍስጥንጥንያ የተሰበሰቡ ፻፶ ሊቃውንትን ውሳኔ መጽሐፍ ቅዱስንና ሊቃውንትን መሠረት በማድረግ ያብራራል፡፡ ባጠቃላይም ስለ ሃይማኖት በመመስከር ላይ እንደሚያተኩር እና ሰይጣንን ክዶ የክርስቶስ ተከታይ ስለመሆን እንደሚያትት የጥናቱ አቅራቢ ዲያቆን አሻግሬ አስረድተዋል፡፡ ክፍለ ሁለት የክርስቶስ የማዳን ሥራና ጸጋ እውን የሚሆነው ቃሉን በመስማትና ምሥጢራትን በመፈጸም መሆኑን እንደሚያስረዳ፣ ክፍል ሦስት ደግሞ ክርስቲያናዊ ሕይወትና ምግባር በእምነት፣ በተስፋና በፍቅር መገለጡ ተብራርቶበታል፡፡

ምእመናን የመዳን ተስፋችን እውን እንዲሆን በሥስቱ አርእስተ ሃይማኖት ማለትም በእግዚአብሔር ፍቅር፣ በክርስቶስ ጸጋ እና በመንፈስ ቅዱስ ኅብረትና ረድኤት መመሥረት እንደሚገባን ይናገራል፡፡ በተጨማሪም አባ አበራ ፍቅርን አንደኛ እግዚአብሔር ለሰው ያለው ፍቅር፣ ሁለተኛ ሰው ለእግዚአብሔር ያለው ፍቅር እና ሦስተኛ ትእዛዛቱን መጠበቅ (አምላክህንና ባልንጀራህን ውደድ የሚሉትን) በማለት በሦስት ክፍል አቅርበውበታል፡፡ ይህም የአባ አበራ መጽሐፍ በዚህ ዓመት በማኅበረ ቅዱሳን እንደገና ታትሞ ገበያ ላይ ውሏል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም በሕይወት በነበሩበት ወቅት ያስተማሩት ትምህርትና ያደረጉት ንግግር በቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩምና በዲያቆን ሙሉዓለም ካሣ አስተባባሪነት በድምፅና ምስል ተቀናብሮ ለመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች የቀረበ ሲሆን ቀጥሎም ቤተሰቦቻቸውና በቅርብ የሚያውቋቸው ወዳጅ ዘመዶቻቸውና የመንፈስ ልጆቻቸው አባ አበራ ፍቅርን፣ መንፈሳዊነትን፣ ደግነትን፣ ቅንነትን እና ትሕትናን የተላበሱ፣ ከስስትና ከፍቅረ ንዋይ የራቁ አባት እንደነበሩ መስክረውላቸዋል፡፡

ታናሽ እኅታቸው ወ/ሮ ጸዳለ በቀለ አባ አበራ ሕፃን እያሉ ጥቅምት ፳፰ ቀን ወላጅ እናታቸው አዝለዋቸው በመንገድ ሲጓዙ በዘመኑ ታዳጊ ወንዶች ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ሽፍቶች ባገኗቸው ጊዜ እናታቸው አባቴ አማኑኤል ሆይ ልጄን ከነዚህ ሽፍቶች ብታድንልኝ የአንተ አገልጋይ ይሁን ብለው በስእለት መልክ ለእግዚአብሔር ሰጥተዋቸው ነበር፤ ይህም ሕይወታቸውን በሙሉ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት እንዲኖሩ አድርጓቸዋል ብለዋል፡፡

መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁንም ከሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ጋር በመሆን በስብከተ ወንጌልም በአስተዳደርም ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሲያገለግሉ መኖራቸውን አውስተው በተለይ ለወላጅ እናታቸው ልዩ ፍቅርና አክብሮት እንደነበራቸው ተናግረዋል፡፡ አክለውም የጻድቅ ሰው መታሰቢያ ለዘለዓለም ይኖራል የሚለውን ኃይለ ቃል መነሻ በማድረግ ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ራሳቸውን መሥዋዕት አድርገውና ልዩ ልዩ ፈተናዎችን ተቋቁመው ያሰቡትን መንፈሳዊ ዕቅድ ሁሉ አሳክተው ያለፉ አባት መሆናቸውን ጠቅሰው ወጣቱ ትውልድ የእርሳቸውን ፈለግ ተከትሎ ቤተ ክርስቲያንን መጠበቅ ከቻለ አባ አበራ ሕያው ናቸው እንጂ ሞቱ አይባልም ሲሉ መልእክታቸውን አጠቃለዋል፡፡

ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ በበኩላቸው አባ አበራ በአገር ውስጥም፣ ከአገር ውጪም በሚገኙ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት እየተዘዋወሩ ብዙ ዕውቀት መቅሰማቸውን ገልጸው፣ አክለውም ለሚሰማቸው ብቻ ሳይሆን ለሚመለከተቻውም አስተማሪ ሕይወት እንደነበራቸው፣ በሕይወት ከኖሩበት ጊዜ በላይ ካረፉ በኋላ ለብዙ ሰዎች ምሳሌ እንደሚሆኑና ሁሉም ሊማርባቸውና ሊያስታውሳቸው እንደሚገባ ገልጸው እኒህን አባት ለመዘከር ያመች ዘንድ በስማቸው የሚሰየም አንድ ስኮላርሺፕ ቢኖረን መልካም ነውና ሁላችንም ብናስብበት ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

በተጨማሪም ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ፣ ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ፣ አቶ ኤርምያስ ዓለሙ እና አቶ ሙሉጌታ ምትኩ ስለ አባ አበራ መንፈሳዊ ሕይወት ተመሳሳይ አሳብና አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

ከጽርሐ ጽዮን ማኅበር አባላት አንዷ የሆኑት ወ/ሮ ሙሉእመቤት በላቸውም፡- ክርስትና ማለት ራስን መካድ መሆኑን የተማርሁት ከአባ አበራ ነው፡፡ ሁላችንም አንረሳቸውም፡፡ እኛ ጊዜያችን እያለቀ ነው፡፡ እናንተ ወጣቶች ትግሉን እንደእርሳቸው ታገሉት፤ ትጥቁን እንደእርሳቸው ታጠቁት፡፡ የአባ አበራን ፈለግ ተከትላችሁ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ የሚመጣባችሁን ሁሉ ፈተና በጸጋ ተቀብላችሁ ወንጌልን ስበኩ ሲሉ እናታዊ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

በመጨረሻም በአባቶች ምክርና ጸሎተ ቡራኬ በስማቸው የተዘጋጀው ጸበል ጸሪቅ ከቀረበ በኋላ ከምሽቱ 2፡30 ገደማ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

ክቡር ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ ከአባታቸው ከግራ አዝማች በቀለ መኩሪያ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ በሸዋምየለሽ ድፋባቸው ከዐዲስ አበባ በስተምሥራቅ አቅጣጫ የረር አካባቢ በሚገኘው ልዩ ስሙ ቡኢ በተባለ ሥፍራ በዕለተ ስቅለት ሚያዝያ ፪ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም ተወልደው በ፸፫ ዓመታቸው ሚያዝያ ፭ ቀን ፳፻፩ ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው ይታወሳል፡፡

ለአርባ አምስት ዓመታት ያህል ቅድስት ቤተ ክርስቲያንንና ሀገራቸውን በፍጹም ፍቅር ሲያገለግሉ የቆዩት ሊቀ ጉባኤ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት ካበረከቱት ከፍተኛ አተዋጽዖ በተጨማሪ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነውን በውኃ እንፋሎት የሚንቀሳቀስ መኪና የሠሩ ጥበበኛም ነበሩ፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም እኒህ ታላቅ አባት ለቤተ ክርስቲያንና ለአገር ያበረከቱትን አስተዋጽዖ ግምት ውስጥ በማስገባት የሰባተኛ ዓመት የዕረፍት ቀናቸው እንዲዘከር አድርጓል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን አዘጋጅነት ሁለት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀረቡ

ግንቦት ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

ዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በጸሎተ ሃይማኖት *ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ* የሚለው ንባብ *በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሆነ* ተብሎ መስተካከል አለበት ተብሏል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዕቃ ቤትና በቅዱሳት መካናት አማካኝነት የቅርስ ቤተ መዛግብት እንደሆነች ተገልጿል፡፡

ወጣቱ ትውልድ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የመጠበቅና የማስጠበቅ ኃላፊነት እንዳለበት ተነግሯል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማዕከል አዘጋጅነት *የአርዮስና መንፈቀ አርዮሳውያን ተጽዕኖ በቤተ ክርስቲያን ላይ* እና *የቤተ ክርስቲያን ተንቀሳቃሽ ቅርሶችን የመጠበቅ ሒደት በአድባራትና ገዳማት* በሚሉ ዐበይት አርእስት የሚመለከታቸው ምሁራንና ተሳታፊ ምእመናን በተገኙበት ቅዳሜ ግንቦት ፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በማኅበሩ አዳራሽ ሁለት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡

*የአርዮስና መንፈቀ አርዮሳውያን ተጽዕኖ በቤተ ክርስቲያን ላይ* በሚለው ርእሰ ጉዳይ ላይ ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡት ቀሲስ ዶክተር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል ሲሆኑ በጥናታቸውም የአርዮስ የኑፋቄ ትምህርት የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት የሚቃወም መሆኑን ጠቅሰው አርዮስና ኑፋቄዉ በ፫፻፲፰ ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት በ፫፳፭ ዓ.ም በኒቅያ በተደረገው ጉባኤ ቢወገዝም ትምህርቱ ግን እስከ ዛሬ ድረስ ቤተ ክርስቲያንን እየተፈታተናት እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡

አያይዘውም በጉባኤ ኒቅያ በተወሰነው የሃይማኖት መሠረት (ጸሎተ ሃይማኖት) ውስጥ *ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ* የሚለው የግእዝ ንባብ *በመለኮቱ ከአብ ጋር የሚተካከል* ተብሎ መተርጐሙ ትክክል አለመሆኑን መረጃ በማስደገፍ ገልጸው ይህ ሐረግ *በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሆነ* ተብሎ መስተካከል እንዳለበትና የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትም ይህንን ምሥጢር ለምእመናን ማስረዳት እንደሚገባቸው ተናግረዋል፡፡

*የቤተ ክርስቲያን ተንቀሳቃሽ ቅርሶችን የመጠበቅ ሒደት በአድባራትና ገዳማት* በሚለው ርእስ ላይ ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡት ዲያቆን አለባቸው በላይ ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዕቃ ቤትና በቅዱሳት መካናት አማካኝነት በቅርስ ቤተ መዛግብትነት የምትገኝ መሆኗን ጠቅሰው ወጥ የሆነ መመሪያና ዕቅድ አለመኖር፣ የቅርስ አጠባበቅና ክብካቤ ችግር፣ ወዘተ የመሰሉ ተግዳሮቶች እንዳሉባት በጥናታቸው ጠቁመዋል፡፡

በጥናታቸው ማጠቃለያም ቤተ ክርስቲያናችን የእምቅ ተንቀሳቃሽ ቅርሶች ባለቤት መሆኗን ገልጸው የዕቅድና ወጥ መመሪያ ዝግጅት፣ የአስተዳደርና የዓቅም ግንባታ ሥራ፣ ለምእመናን ስለቅርሶች ግንዛቤ መስጠትና የባለቤትነት ስሜት እንዲያድርባቸው ማድረግ፣ ወዘተ የመሰሉ ተግባራት ለቅርስ አጠባበቅ ችግር መፍትሔ ሊሆኑ እንደሚችሉ በዝርዝር አስረድተው *ሁላችንም ይህንን በመረዳትና የተጀመሩ መልካም አጋጣሚዎችን በመጠቀም ለወደፊት የተሻለ መሥራት ይጠበቅብናል* ብለዋል፡፡

በዐውደ ጥናቱ ላይ ከተገኙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከል አንዱ የሆኑት መልአከ ታቦር ተሾመ ዘርይሁን አስተያየት በሰጡበት ወቅት፣ *ትልቁ ነገር የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች መመለስ ነው፤ ማኅበረ ቅዱሳን መምህራንን በመጋበዝ እንደዚህ ዓይነት ጥናታዊ ውይይት ማካሔዱ ለአባቶች ተገዢ መሆኑን አመላካች ተግባር ነው* ብለዋል፡፡ በተጨማሪም *ቤተ ክርስቲያናችን፣ Living Church of Living Faith and Ever Growing Church – ዘለዓለማዊት፣ የዘለዓለማዊው ሃይማኖት መሪ የሆነች እና ዘለዓለም የምታድግ ናት፤ ስለሆነም ወጣቱ ትውልድ የዚህችን ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ የመጠበቅና የማስጠበቅ ኃላፊነት አለበት* ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በመጨረሻም በሁለቱም ጥናቶች ላይ ከተሳታፊዎች ለተነሡ ጥያቄዎች በአቅራቢዎቹ ምላሽ ተሰጥቶ ሲያበቃ የውይይቱ መሪ ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ የማጠቃለያ ንግግር ካደረጉ በኋላ በአባቶች ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

ሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ሚካኤል መታሰቢያ ሐውልት ቆመላቸው

ግንቦት 14 ቀን 2008 ዓ.ም በድምቀት ይመረቃል፡፡

ግንቦት 7 ቀን 2008 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

ለሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ሚካኤል በጎሬ ከተማ ላይ የተሠራላቸው መታሰቢያ ሐውልት ግንቦት 14 ቀን 2008 ዓ.ም በድምቀት እንደሚመረቅ መታሰቢያ ሐውልቱን በማስገንባት ላይ የሚገኘው ኮሚቴ አስታወቀ፡፡

የሐውልቱ ምርቃት ቅዱስ ፓትርያርኩን ጨምሮ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ከፍተኛ የመንግሥት አካላት፣ የኢትዮጵያ አርበኞች ማኅበር፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የልዩ ልዩ መምሪያ ሓላፊዎችና የጎሬ ሕዝብ በተገኙበትይመረቃል፡፡

ሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ሚካኤል ጎንደር ጠቅላይ ግዛት በደብረ ታቦር አውራጃ እስቴ ወረዳ ልጫ መስቀለ ክርስቶስ በሚባል ቦታ ከአባታቸው ከቄስ ገብረ ክርስቶስና ከእናታቸው ወ/ሮ ትኩዬ በ1874 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ ከፊደል ጀምሮ ጸዋትወ ዜማ፣ ዝማሬና መዋስዕት፣ ድጓ፣ ጾመ ድጓ፣ መዝገበ ቅዳሴ ከነትርጓሜው፣ አቋቋምና ቅኔ በተለያዩ ቦታዎች በመዘዋወር ከታላላቅ መምህራን ተምረዋል፡፡

ግንቦት 25 ቀን 1921 ዓ.ም ከዐራት አባቶች ጋር ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ግብፅ በማቅናት ብፁዕ አቡነ ሚካኤል ተብለው ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰዋል፡፡ ከብፁዕነታቸው ጋር ጵጵስናን የተቀበሉት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፣ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ፣ ብፁዕ አቡነ አብርሃም ናቸው፡፡

ከግብፅ እንደተመለሱም ብፁዕ አቡነ ሚካኤል የምዕራብ ኢትዮጵያ /የጎሬና የወለጋ ጠቅላይ ግዛት/፣ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የምሥራቅ ኢትዮጵያ፣ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ የትግራይና የሰሜን ኢትዮጵያ፣ ብፁዕ አቡነ አብርሃም የጎንደርና የጎጃም ጠቅላይ ግዛት ሊቃነ ጳጳሳት ሆነው ተሹመው ቅድስት ቤተ ክርስቲያንና ሀገርን አገልግለዋል፡፡

በ1928 ዓ.ም ፋሺስት ኢጣሊያ ኢትዮጵያን በወረረችበት ወቅት ከፍተኛ ተጋድሎ ከፈፀሙ አባቶች መካከል ሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ሚካኤል አንዱ ናቸው፡፡ ሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ አዲስ አበባ ላይ በፋሺስት ኢጣሊያ ከተገደሉ ከዐራት ወራት በኋላ ጎሬ ላይ ፋሺስትን አውግዘው ሰማዕትነት ተቀብለዋል፡፡

በመተከል ሀገረ ስብከት ግልገል በለስ 8620 አዳዲስ አማንያን ተጠመቁ

ሚያዝያ 17 ቀን 2008 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

እስከዚህ ዕድሜያችን ድረስ ስንጠብቃችሁ ነበር ተጠማቂያኑ፡፡

02gilgel 2በመተከል ሀገረ ስብከት በግልገል በለስ ማእከል ሥር በሚገኙ 3 ወረዳዎች 8620 አዳዲስ አማንያንን ሚያዝያ 15 እና 16 ቀን 2008 ዓ.ም መጠመቃቸውን የማኅበረ ቅዱሳን ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር ገለጸ፡፡

በማንዱራ፣ ድባጤ እና ዳንጉ ወረዳዎች የሚገኙት እነዚህ አዳዲስ አማንያን በማኅበረ ቅዱሳን አስተባባሪነት ከሀገረ ስብከቱ፣ ከወረዳ ቤተ ክህነቶች እና ከግልገል በለስ ማእከል ጋር በመተባበር የቅድሰት ቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሲማሩ መቆየታቸውን ከማኅበሩ የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልዩ ፍቅር እንዳላቸው የገለጹት ተጠማቂያኑ እስከዚህ ዕድሜያችን ድረስ ስንጠብቃችሁ ነበር በማለት ሲናፍቁት የነበረው ጊዜ በመድረሱና ፍላጎታቸው በመሳካቱ መደሰታቸውን ተናግረዋል፡፡

የመረጃው ዝርዝር እንደደረሰን እናቀርባለን፡፡

ሆሳዕና

ሚያዝያ 14 ቀን 2008 ዓ.ም

በመምህር ኃለ ማርያም ላቀው

ሆሳዕና የሚለው ቃል በዕብራይስጥ ሆሼዕናህ የሚል ሲሆን ትርጉሙም እባክህ አሁን አድን ማለት ነው፡፡ ይህ ቃል በዘመነ ብሉይ በቀደምት ነቢያት ዘንድ የተለመደ ቃል ነው፡፡ አቤቱ እባክህ አሁን አድን፣ አቤቱ እባክህ አሁን አቅና፣ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩከ ነው፡፡ መዝ.117፡25-26 የሆሳዕና በዓል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ የሚቀድሙትና የሚከተሉት ሕዝብ በተለይም አእሩግና ሕፃናት ሆሳዕና ለዳዊት ልጅ፣ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፣ ሆሳዕና በአርያም በማለት ጌታችንን በክብር መቀበላቸው የሚታወስበት በዓል ነው፡፡ በዓሉም ሆሳዕና የሚለውን ስያሜ ያገኘው በዕለቱ ከተዘመረው መዝሙር ነው፡፡

በሌላ አነጋገር ይህ ዕለት የጸበርት እሑድ /Palm Sunday/ ይባላል፡፡ ታሪካዊ አመጣጡ የመልካም ምኞትና የድል አድራጊነት መገለጫ ሆኖ ከደገኛው አባታችን ይስሐቅ ልደት ጋር ተያይዞ የመጣ ነው፡፡ ይኸውም ሣራ የወላድነት ዕድሜዋን ጨርሳ ልማደ እንስት ከተቋረጠባት በኋላ ሁሉን ቻይ የሆነ አምላክ ይስሐቅን በሰጣት ጊዜ ዘመዶችዋ የተሰማቸውን ደስታ ለመግለጽ የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ የጎበኟትን አምላክ አመስግነዋል፡፡ እስራኤል ከአስከፊው የግብፃውያን አገዛዝ ተላቀው ባሕረ ኤርትራን በደረቅ ሲሻገሩ የተሰማቸውን እጥፍ ድርብ ደስታ በገለጡ ጊዜ፣ እንዲሁም ዮዲት የተባለች ንግሥተ እስራኤል ሆሎፎርኒስ የተባለ አላዊ ንጉሥን ድል ባደረገች ጊዜ ቤተ እስራኤል እንደ ሰንደቅ ዓለማ የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ አደባባይ ወጥተው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል፡፡

በዘመነ ሐዲስም መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር ከዲያብሎስ ቁራኝነት ከሲኦል ባርነት ነጻ ለማውጣት ወደ ዙፋን መስቀሉ /ሉቃ.22፤18/ በተጓዘ ጊዜ ሕፃናት እና አእሩግ ነጻ የሚወጡበት ቀን መድረሱን እነርሱ ሳያውቁ እግዚአብሔር ባወቀ ዘንባባ በመያዝ ዘምረዋል፡፡ እስራኤል ዘንባባ በመያዝ እንዳመሰገኑት እኛም አስራኤል ዘነፍስ ዕለቱን ዘንባባ /ጸበርት/ በግንባራችን በማሰር በዓሉን በየዓመቱ እያስታወስን እናከብራለን፡፡ በዚህ ዕለት ዘንባባ እየተባረከ ለሕዝቡ ይታደላል፡፡

ሕፃናትና አእሩግ ለዳዊት ልጅ መድኃኒት መባል ይገባዋል፡፡ እያሉ ዘምረዋል፡፡ ይህ ሁሉ በአንድ ወገን የነበረው የአቀባበል ሥነ ሥርዓት ሲሆን በሌላ በኩል የነበረው አቀባበል ደግሞ እጅግ የሚያሳዝን ነበር፡፡ ሥርዓተ ኦሪትን፣ ትንቢተ ነቢያትን በሚገባ እንከተላለን ይሉ የነበሩ ጸሐፍት ፈሪሳውያን መምህር ሆይ ደቀ መዛሙርትህን ገሥጻቸው አሉት፡፡ ጌታችንም መልሶ እነዚህ ዝም ቢሉ ድንጋዮች ይጮኻሉ ሲል መልሶላቸዋል፡፡ ቅናት አቅላቸውን ያሳታቸው ፈሪሳውያንም የዋህ የሆነው ሕዝብ ምስጋና ወደ ጥላቻ እንዲለወጥ አድርገዋል፡፡ ከሁሉ የሚያሳዝነው በዕለተ ሆሳዕና እሑድ ዘንባባ ይዘው የዘመሩለትን ጌታ ዓርብ ይሰቀል ዘንድ ይገባል ብለዋል፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ፡፡ በዚህም በነቢዩ ዘካርያስ እንዲህ ተብሎ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመ፡፡እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ሆኖ በአህያም፣ በአህያዪቱ ግልገል በውርንጫዪቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል፡፡ ዘካ.9፡9፤ ማቴ.21፡4፤ ማር.11፡1-10፤ሉቃ.19፡28-40፤ ዮሐ.12፤15፡፡ ጌታችን በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱ የሰላም ንጉሥ መሆኑን ያመለክታል፡፡ እስራኤል ዘመነ ምሕረት ሲሆንላቸው አባቶቻቸው በአህያ ጀርባ ተቀምጠው ይታዩ ነበር፡፡ ጌታም እውነተኛ የኅሊና ሰላም ይዤላችሁ መጣሁ ሲለን በአህያ ጀርባ ወደ ቤተ መቅደስ ሕይወታችን ተጉዟል፡፡

መላእክት በዕለተ ልደቱ በሰማይ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይገባዋል በምድር ሰላም ለሰው ሁሉ ይሁን /ሉቃ.2፡13/ እያሉ የዘመሩለት የሰላም ባለቤት ነው፡፡ በመዋዕለ ትምህርቱም ሰላሜን እሰጣችኋለሁ /ዮሐ.14፡27/ ብሎ እንዳስተማረ ያን ሰላም የሚሰጥበትን ዕለት መቅረቡን ለማመልከት ነው፡፡ በሌላ በኩልም በአህያ ጀርባ መቀመጡ ኅቡዕ ምሥጢር አለው፡፡ በአህያ ጀርባ የተቀመጠ ሰው ሌላውን አሳድዶ አይዝም፣ እርሱም ሮጦ አያመልጥም፡፡ በዚህም ጌታችን በእምነት ለሚፈልጉት የሚገኝ ቅርብ ሲሆን በእምነት ለማይፈልጉት ግን የማይገኝ መሆኑን አስተምሯል፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች ፀሐይ ዕድሜያችን ሳትጠልቅ በእምነት እንፈልገው፡፡ አሞጽ4፡፡ የአህያን ጀርባ ያልናቀ ጌታችን ትሑት ሰብእና እና የተሰበረ ልቡና ወዳለው ሰው ዘወትር ይጓዛል፣ የተዋረደውንና የተሰበረውን ልብ አይንቅም፡፡ ኢሳ.66፡2፤ መዝ.50፡17፡፡

ለታሰሩት መፈታትን ሊሰብክ ሰው የሆነ ጌታችን ከማሰሪያዋ በተፈታች አህያ እንደተቀመጠ ሁሉ ከኃጢአት እስራት በተፈታ ሕይወት ዛሬም ያድራል፤ የኅሊና ሰላምን ይሰጣል፡፡ ስለዚህ ንስሐ ገብተን ጌታችንን ሆሳዕና በአርያም እያልን ልናመሰግነው ይገባል፡፡

ምንጭ፡ ሐመር ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ፣ መጋቢት/ሚያዝያ 1996 ዓ.ም

ማኅበረ ቅዱሳን በሰሜን አሜሪካ ሜኖሶታ ሁለት ከተሞች የኦሮምኛ ቴሌቪዥን ሥርጭት ጀመረ

ሚያዚያ 11 ቀን 2008 ዓ.ም

ከአሜሪካ ማእከል

ማኅበረ ቅዱሳን በሰሜን አሜሪካ ሜኖሶታ ውስጥ በሚገኙ በሚኖፖሊስ እና በቅዱስ ጳውሎስ /Minneapolis & Saint Paul/ ሁለት ከተሞች ከሚያዚያ 9 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ ሥርጭቱን ማስተላለፍ መጀመሩን የአሜሪካ ማእከል ገለጸ፡፡

የቴሌቪዥን ሥርጭቱ በየሳምንቱ እሑድ ከቀኑ 10፡00 ሰዓት /Sunday at 4:00 PM USA Central time/ በቻናል 75 የሚተላለፍ ሲሆን ምእመናን መርሐ ግብሩን እንዲከታተሉ ማእከሉ አስታውቋል፡፡

በተያያዘ ዜና በአሜሪካ የሜኖፖሊስ ማእከል ሚያዚያ 8 እና 9 ቀን 2008 ዓ.ም ጉባኤ ማካሔዱን የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

01admaa

አዳማ ማእከል የሐዊረ ሕይወት አካሔደ

መጋቢት 23 ቀን 2008 ዓ.ም

ከአዳማ ማእከል

01admaaበማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል ለ4ኛ ጊዜ ያዘጋጀውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በመቂ ግራዋ ጃዌ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን መጋቢት 11 ቀን 2008 ዓ.ም አካሔደ፡፡

መርሐ ግብሩ በደብሩ ሊቀውንተ ቤተ ክርስቲያን በጸሎተ ወንጌል የተጀመረ ሲሆን በማእከሉ መዝምራንና በቀሲስ ምንዳየ ብርሃኑ መዝሙር ቀርቦ በዲ/ን ዳንኤል ክብረት ዓላማ(ተልዕኮ) ያለው ክርስቲያን€ በሚል ርዕስ የወንጌል ትምህርት ተሰጥቷል፡፡

በምክረ አበው መርሐ ግብር ከምእመናን የተሰበሰቡ ጥያቄዎችን መሠረት አድርጎ በተሐድሶ እንቅስቃሴ ላይ የምእመናንና የሊቃውንት ድርሻ፤ ገድላትና ድርሳናት ከመጽሐፍ ቅዱስ አንጻር ያላቸው አገልግሎት፤ ሉላዊነትን እንዴት መቋቋም ይቻላል፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሀገራችን ያደረገችው አስተዋጽኦ፣ . . . አስመለክቶ በዲ/ን ዳንኤል ክብረት እና ዲ/ን ያረጋል አበጋዝ መልስ ተሰጥቶባቸው የጠዋት መርሐ ግብሩ ተጠናቋል፡፡

ከሰዓት በኋላ በተከናወነው ቀጣይ መርሐ ግብር በዲ/ን ያረጋል አበጋዝ ጌታ ሆይ አድነኝ ብሎ ጮኸ€ በሚል ርዕስ የወንጌል ትምህርት፣ በመቂ ግራዋ ጃዌ አቡነ ገብረ መንፈስ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ በተከታታይ ቀርበዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ በግንባታ ላይ የሚገኝ በመሆኑ ከምእመናን የ27 ሺሕ(27000) ብር ድጋፍ ተደርጓል፡፡