ዐውደ ርእዩ በሺሕ በሚቈጠሩ ምእመናን እየተጐበኘ ነው፡፡

ሰኔ ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ በሚል መሪ ቃል የአዳማ ማእከል በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ መልካም ፈቃድ በአዳማ ከተማ በደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ደብር ያዘጋጀው ዐውደ ርእይ ከሰኔ ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ በሺሕ በሚቈጠሩ የናዝሬት (የአዳማ) ከተማና የአካባቢው ምእመናን እየተጐበኘ ይገኛል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ፣ ምክትል ዋና ጸሐፊው አቶ ሰይፈ ዓለማየሁ እና የኅትመትና ኤሌክሮኒክስ ሚድያ ዋና ክፍል ምክትል ሓላፊ አቶ አክሊሉ ለገሠ ሰኔ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በአዳማ ከተማ በደብረ ናዝሬት ኢየሱስ በመገኘት የአዳማ ማእከል ያዘጋጀውን ዐውደ ርእይ የጐብኙ ሲኾን፣ ዝግጅት ክፍላችንም በዕለቱ በቦታው በመገኘት ይህንን ዘገባ አጠናቅሯል፡፡

አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ የዐውደ ርእዩን ዓላማ ለዝግጅት ክፍላችን ሲገልጹ ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን ዐውደ ርእይ ያዘጋጀው ቤተ ክርስቲያን በመንፈሳዊ ዕውቀት የበለጸጉና ዕውቀታቸውንም በተግባር መለወጥ የሚችሉ፤ ከውጪ ኾነው የሚመለከቱና የሚተቹ ሳይኾኑ የቤተ ክርስቲያኗ አገልግሎት የኔ ነው የሚሉና ክርስትናን በሕይወት የሚኖሩ ምእመናንን ለማፍራትና የድርሻቸውንም እንዲወጡ ለማስገንዘብ መኾኑን ተናግረዋል፡፡

አቶ ሰይፈ ዓለማየሁ በበኩላቸው ይህ ዐውደ ርእይ በየማእከላቱ እንዲታይ ማኅበሩ አቅጣጫ መስጠቱንና የአምቦ ማእከል በቀዳሚነት ዐውደ ርእዩን ማስጐብኘቱን ገልጸው፣ *እንደ አዳማ ማእከል ኹሉ ሌሎች ማእከላትም ይህንን ተሞክሮ በመውሰድ በ፳፻፱ ዓ.ም የአገልግሎት ዘመን የዕቅዳቸው አካል በማድረግ ይህንን ዐውደ ርእይ ለምእመናን ማስጐብኘት ይጠበቅባቸዋል* ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

አቶ ሰይፈ አያይዘውም የአዳማ ከተማና የአካባቢው ምእመናን ዐውደ ርእዩን እየጐበኙ የሚገኙት ያለምንም ክፍያ መኾኑን ጠቅሰው *ማኅበራችን የተቋቋመው ለአገልግሎት እንጂ ለትርፍ አይደለምና በኪሳራም ቢኾን ሕዝበ ክርስቲያኑን ማስተማር ይገባናል፡፡ ምእመናኑ በገንዘብ ምክንያት የቤተ ከርስቲያን አስተምህሮ ሊያመልጣቸው ስለማይገባ፤ ደግሞም የዐውደ ርእዩ ዓላማ ማስተማር እንጂ ገንዘብ መሰብሰብ ስላልኾነ ዐውደ ርእዩ በነጻ እንዲታይ አድርገናል ሲሉ ዐውደ ርእዩ ያለ ክፍያ እንዲታይ የተደረገበትን ምክንያት አስረድተዋል፡፡

የአዳማ ማእከል ሰብሳቢ መምህር ጌትነት ዐሥራትም የዐውደ ርእዩ ዓላማ ምእመናን የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ በማወቅና የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ችግሮች በመገንዘብ የድርሻቸውን እንዲወጡ ለማነሣሣት መኾኑን ገልጸው ቦታውን ከመፍቀድ ጀምሮ ለዐውደ ርእዩ መሳካት አስተዋጽኦ ላበረከቱ ለሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ለብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፣ ለሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ለመጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት፣ ለየመምሪያ ሓላፊዎች፣ ለደብረ ናዝሬት ኢየሱስ እና ደብረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ካቴድራል አስተዳዳሪ ሊቀ ጉባኤ አባ ተክለ ሃይማኖት ወልዱ፣ ለደብሩ ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤትና አገልጋይ ካህናት፣ ለሰንበት ት/ቤት ወጣቶች፣ እንደዚሁም ለመንፈሳውያን ማኅበራትና ለበጎ አድራጊ ምእመናን ማእከሉንና የዐውደ ርእይ ዝግጅት ኰሚቴውን ወክለው ምስጋና አቅርበዋል፡፡

ዐውደ ርእዩ በትዕይንት ገላጮች ብቻ ሳይኾን በድምፅ ወምስል በታገዙ መረጃዎች እንደሚቀርብ፤ እንደዚሁም የአብነት መምህራንና ደቀ መዛሙርቱ ሥርዓተ ትምህርት፣ የዋናው ማእከልና የአዳማ ማእከል ሥራዎች የትዕይንቱ አካላት እንደ ኾኑ የገለጹት የዐውደ ርእይ ዝግጅት ኰሚቴው ሰብሳቢ መምህር ኃይለ ኢየሱስ ከበረ ደግሞ በአባቶች ጸሎት ከተከፈተበት ዕለት ጀምሮ እስከ ሰኔ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረስ ከአምስት ሺሕ በላይ ምእመናን እንደ ጐበኙት ጠቅሰው በቀን በአማካይ እስከ ስምንት መቶ የሚደርሱ ጐብኚዎች መታደማቸውን አስታውቀዋል፡፡

ዝግጅት ክፍላችን ካነጋገራቸው ከትዕይንት ገላጮች መካከል አቶ ፍሬ ሰንበት ተክለ ሚካኤል የተባሉ ወንድም ሃይማኖታዊ ድርሻቸውን ለመወጣትና እርሳቸው የሚያውቁትን ለሌሎች ለማካፈል በማሰብ በትዕይንት ገላጭነት በማገልገል ላይ እንደሚገኙ ነግረውናል፡፡

በዐውደ ርእዩ ከታደሙ ምእመናን መካከልም አንዳንዶቹ በዐውደ ርእዩ ብዙ ቁም ነገር መጨበጣቸውን ጠቅሰው በአንጻሩ ግን በተለይ በጠረፋማ አካባቢዎች በባዕድ አምልኮ ውስጥ የሚኖሩ ወገኖች ለመጠመቅ እየፈለጉ ነገር ግን በሰባክያንና በካህናት እጥረት ምክንያት የቤተ ክርስቲያን አባላት ሳይኾኑ በመቅረታቸው ማዘናቸውን ገልጸውልናል፡፡

ሌሎቹ ደግሞ ዐውደ ርእዩ ተዋሕዶ ሃይማኖታችንን ይበልጥ እንድንወዳትና የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ችግሮችንም እንድንገነዘብ አድርጎናል፤ ከዚህ በኋላ የሚጠበቅብንን ኹሉ ለማድረግ ዝግጁ ነን ብለዋል፡፡ አክለውም ይህንን ዐውደ ርእይ እስከ ማእከል ድረስ እንዲታይ በማድረጉ ማኅበረ ቅዱሳንን አመስግነዋል፡፡

በመጨረሻም የአዳማ ማእከልና የዐውደ ርእዩ ዝግጅት ኰሚቴው አባላት ከኹሉም በላይ በአገልግሎታቸው ኹሉ ላልተለያቸው ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ካቀረቡ በኋላ ዐውደ ርእዩ ሰኔ ፳፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም እንደሚጠናቀቅ ገልጸው አሁንም ምእመናኑ መጐብኘታቸውን እንዲቀጥሉ ሲሉ መንፈሳዊ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

አዳዲስ አማንያን እየተበተኑ መኾናቸው ተነገረ፡፡

ሰኔ ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ወንጌል ባልተዳረሰባቸው ፳፫ ገጠርና ጠረፋማ አህጉረ ስብከት ላይ ትኩረት አድርጎ ከአህጉረ ስብከት፣ ከወረዳ ቤተ ክህነቶች፣ ከማእከላትና ወረዳ ማእከላት ጋር በመተባበር አዳዲስ አማንያንን በማስጠመቅ ላይ የሚገኘው በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር በ፳፻፰ ዓ.ም የአገልግሎት ዘመን ዐሥራ አንድ ሺሕ አማንያንን ለማስጠመቅ ዐቅዶ ቢነሣም በእግዚአብሔር ቸርነት ከሃያ ሺሕ በላይ አዳዲስ አማንያን የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ አድርጓል፡፡

0005

የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብሩ አስተባባሪ አቶ ጌትነት ወርቁ ለዝግጅት ክፍላችን እንደ ገለጹት በቅርቡ ሰኔ ፲፪ እና ሰኔ ፲፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት በዳራማሎ ወረዳ ቤተ ክህነት በሌፌ እና በጐጌ ቀበሌዎች በተደረገው የጥምቀት መርሐ ግብር በሌፌ ሁለት ሺሕ ሰባ፤ በጐጌ ደግሞ ሰባት መቶ ሃያ አምስት በድምሩ ሁለት ሺሕ ሰባት መቶ ዘጠና አምስት ሰዎች የሥላሴ ልጅነትን አግኝተዋል፡፡

ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብሩ በአምስት አካባቢዎች ማለትም በግልገል በለስ፣ ያቤሎ፣ ጂንካ፣ ዐርባ ምንጭና ከፋ የጥምቀት አገልግሎት ለመስጠት እየሠራ የሚገኝ ሲኾን፣ የሰኔውን ወር ጨምሮ በአራት አመታት ውስጥ በእነዚህ ቦታዎች ስድሳ ዘጠኝ ሺህ አዳዲስ አማንያንን በማስተማር እንዲጠመቁ አድርጓል፡፡

0003
ኾኖም ግን የበጀት ማነስ፣ በአካባቢው ቋንቋ የሚያስተምሩ ሰባክያነ ወንጌልና ካህናት እጥረት፣ እንደዚሁም ምእመናኑ ከተጠመቁ በኋላ ትምህርተ ወንጌል የሚያገኙበት፣ ልጆቻቸዉን ክርስትና የሚያስነሡበትና ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን የሚቀበሉበት ቤተ ክርስቲያን በቅርብ አለመኖር የሥላሴ ልጅነትን ያገኙት ምእመናን እንዲበተኑና በመናፍቃን እንዲነጠቁ እያደረጋቸው መኾኑን አስተባባሪው አቶ ጌትነት ተናግረዋል፡፡

ከዚህ በላይ ቍጥር ያላቸው አማንያንን ለማስጠመቅና ተዋሕዶ ሃይማኖታችንን ይበልጥ ለማስፋፋት ይቻል ዘንድ መላው ሕዝበ ክርስቲያን ከማኅበሩ ጎን በመቆም የድርሻቸዉን አስተዋጽዖ ቢያበረክቱ የበለጠ ውጤት ማምጣት እንደሚቻል የገለጹት አቶ ጌትነት ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያው የተለያዩ ፕሮጀክቶችን አዘጋጅቶ እየሠራ መኾኑን ጠቅሰው ለፕሮጀክቶቹ መሳካትም የበጎ አድራጊ ምእመናን ድጋፍ እንዳይለየን ሲሉ ጥሪያቸውን ያስተላልፋሉ፡፡

በመጨረሻም መርሐ ግብሩን በገንዘብ መደገፍ የሚፈልጉ ምእመናን፣ ለማኅበረ ቅዱሳን ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር በአዋሽ ባንክ ሒሳብ ቍጥር 0130 4024 2244 00 ገቢ በማድረግ እንዲተባበሩ ጠቁመው በተጨማሪም በስልክ ቍጥር 0913 57 48 15 /0911 63 95 52 ስልክ ቢደዉሉ ስለ መርሐ ግብሩ የበለጠ መረጃ ማግኘት እንደሚችሉ አስተባባሪው አስታውቀዋል፡፡

*መስቀላችሁ የቃል ኪዳን ምልክታችሁ*

ሰኔ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ይህ ኃይለ ቃል ከማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊና የግቢ ጉባኤያት ማደራጃ ማስተባባሪያ ዋና ክፍል ሓላፊ ከአቶ እስጢፋኖስ ታፈሰ ንግግር የተወሰደ ሲኾን፣ ይኸውም የአቃቂ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች በተመረቁበት ዕለት ተገኝተው ያስተላለፉት መልእክት ነው፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል፣ በአዲስ አበባ ማእከል ግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያና በአቃቂ ቃሊቲ ወረዳ ማእከል አማካይነት በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በአቃቂ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ግቢ ጉባኤ በምሕንድስና የትምህርት ዘርፍ ትምህርታቸዉን ያጠናቀቁና በማኅበሩ የሚሰጡ ልዩ ልዩ የትምህርተ ሃይማኖት ኮርሶችን ሲከታተሉ የነበሩ ተማሪዎች አባቶች ካህናት፣ የማኅበሩ አገልጋዮችና የተመራቂ ቤተሰቦች በተገኙበት ሰኔ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በማኅበረ ቅዱሳን ሕንፃ ሦስተኛ ፎቅ አዳራሽ ተመርቀዋል፡፡

የምረቃ ሥርዓቱ በአባቶች ጸሎት ከተከፈተ በኋላ *ፍሬ ፃማከ ተሴሰይ፤ የድካምህንም ፍሬ ትመገባለህ* /መዝ.፻፳፯፥፪/ በሚል ኃይለ ቃል በዲ/ን ዶ/ር ቴዎድሮስ በለጠ ትምህርተ ወንጌል ከተሰጠ በኋላ በተመራቂዎች የበገና ዝማሬ የቀረበ ሲኾን፣ በመቀጠልም በግቢ ጉባኤው በልዩ ልዩ ክፍሎች በሥራ አስፈጻሚነት በትጋት ሲያገለግሉ የቆዩና በተቋሙ በተማሩት የትምህርት ዘርፍ የላቀ ውጤት ያስመዘገቡ አምስት ተመራቂዎች ከአባቶች እጅ የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡

አቶ እስጢፋኖስ ታፈሰ በምረቃ ሥርዓቱ ላይ ተገኝተው የማኅበሩን መልእክት ባስተላለፉበት ወቅት *ይህ ዛሬ የተቀበላችሁት መስቀል ለመንፈሳዊ አገልግሎት ለምትገቡት ቃል ኪዳን ምልክትና መክሊታችሁ መኾኑን በመገንዘብ ከልጅነት እስከ ዕውቀት ድረስ መንፈሳዊ ሀብቷን ሳትነፍግ ያሳደገቻችሁን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በዕውቀታችሁ፣ በገንዘባችሁና በጉልበታችሁ እንድታገለግሉ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጠበቀ መልእክቷን ታስተላልፋለች* በማለት ማኅበሩን ወክለው መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

በተጨማሪም *ተመራቂዎች በሰንበት ትምህርት ቤቶችና በሰበካ ጉባኤያት የላቀ ተሳትፎ እንድታደርጉ፤ በምትሠማሩበት የሥራ መስክም ክርስቲያናዊ ጨዋነትን በማንጸባረቅ ታታሪነትን፣ ታማኝነትን፣ ሥራ አክባሪነትን፣ ቁጥብነትን በተግባር በመፈጸምና አገራችንን ከልዩ ልዩ ችግሮች ለማላቀቅ በሚደረገው እንቅስቃሴ ኹሉ በመሳተፍ የዜግነት ግዴታችሁን እንድትወጡ፤ እንደዚሁም በየማእከላት፣ ወረዳ ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች በማገልገል በግቢ ውስጥ የነበራችሁን መንፈሳዊ ሕይወት እንድትቀጥሉ አደራ እንላለን* ብለዋል፡፡

በመጨረሻም በአባቶች ጸሎት የምረቃ ሥርዓቱ ተፈጽሟል፡፡

የአቃቂ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ግቢ ጉባኤ ከተቋቋመ አምስት ዓመታትን እንዳስቈጠረና ማኅበረ ቅዱሳን የግቢውን ተማሪዎች ሲያስመርቅም ዘንድሮ ሁለተኛ ጊዜው እንደ ኾነ በማኅበረ ቅዱሳን አዲስ አበባ ማእከል የግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያ መደበኛ አስተባባሪ ዲ/ን ዘመኑ ገረመው ለዝግጅት ክፍላችን ገልጸውልናል፡፡

*ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን እየገነባን እኛ ከቤቱ ርቀናል*

ሰኔ ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በደብረ ማርቆስ ማእከልና በዝግጅት ክፍሉ

ይህ ኃይለ ቃል የብፁዕ አቡነ ማርቆስ የምሥራቅ ጐጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ የበላይ ሓላፊ ንግግር ሲኾን፣ ኃይለ ቃሉን የተናገሩትም በደብረ ማርቆስ ከተማ ሰኔ ፲፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የባሕረ ጥምቀት ግንባታ የመሠረት ድንጋይ በተቀመጠበት ዕለት ነው፡፡

በሥርዓቱ ላይም ብፁዕነታቸውን ጨምሮ የሀገረ ስብከቱ የየመምሪያ ሓላፊዎች፣ በከተማው የልዩ ልዩ አብያተ ክርስቲያናት አገልጋይ ካህናትና የአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን ታቦተ ሕግ በማክበር፤ እንደዚሁም የምሥራቅ ጐጃም ዞን አስተዳደር፣ የደብረ ማርቆስ ከተማ ከንቲባና ሌሎችም የመንግሥት ባለሥልጣናት ተገኝተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ በዕለቱ ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ የባሕረ ጥምቀቱ የመሠረት ድንጋይ በቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን (በበዓለ ኀምሳ) መቀመጡ የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ የሚያሳይ መኾኑን ጠቅሰው *የቀድሞ አባቶቻችን ቤታቸዉ ሳይቀር ቤተ ክርስቲያን ነበር፤ በአሁኑ ሰዓት ግን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን እየገነባን እኛ ከቤቱ ርቀናል፡፡ ስለኾነም ከኹሉም አስቀድሞ ራሳችንን ወደ ቤተ ክርስቲያን ማቅረብ ያስፈልጋል* ሲሉ አባታዊ መልእክታቸዉን አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕነታቸው አያይዘውም በባሕረ ጥምቀቱ ቦታ ላይ የጸበል መጠመቂያ ገንዳ፣ ዐዉደ ምሕረት፣ አጥርና የተለያዩ የግንባታ ሥራዎች እንደሚከናወኑና የግንባታዉ ጠቅላላ ወጪም ከ፲፰ እስከ ፳ ሚሊዮን ብር እንደሚጠይቅ የባለሙያዎችን ጥናት መነሻ በማድረግ ጠቁመዋል፡፡ በተጨማሪም ለቦታዉ መከበርና ለግንባታዉ መፋጠን ኹሉም ምእመናን ሃይማኖታዊ ሓላፊታቸዉን መወጣት እንደሚገባቸው አባታዊ ምክራቸዉን ለግሰዋል፡፡

የምሥራቅ ጐጃም ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ማእምራን ቆሞስ አባ እንባቆም ጫኔ የባሕረ ጥምቀቱን ቦታ አስመልክቶ ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት ከኰሚቴው ጎን በመሰለፍ ቦታውን ለማስከበር ልዩ ልዩ ድጋፍ ሲያደርግ የነበረውን የደብረ ማርቆስ ሕዝብ አመስግነው *ይህንን ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ሥራ በመፈጸም ለትውልድ ለማስተላለፍ እንዲቻል መላው ሕዝበ ክርስቲያን በጸሎቱ፣ በዐሳቡ፣ በዕውቀቱ፣ በገንዘቡና በጉልበቱ ድጋፉ እንዳይለየን* ሲሉ በእግዚአብሔር ስም ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የምሥራቅ ጐጃም ዞን አስተዳዳሪ አቶ ምግባሩ ከበደ በዕለቱ ንግግር ሲያደርጉ *ጥያቄያችሁ መልስ በማግኘቱ እንኳን ደስ አላችሁ* ካሉ በኋላ ባሕረ ጥምቀቱን *ቤተ ክርስቲያን ለረዥም ጊዜ ጠብቃ ያቆየችዉን ወርቃማ የሥነ ምግባር፣ የሰላምና የፍቅር አስተምህሮ የማስጠበቂያ ቦታ ማድረግ ይገባል* ብለዋል፡፡

በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ማርቆስ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ የዕለቱ መርሐ ግብር ተፈጽሟል፡፡

የምሥራቅ ጐጃም ሀገረ ስብከት በብፁዕ አቡነ ማርቆስ መመሪያ ሰጭነት መስከረም ፳፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በተቋቋመው ኰሚቴ ጥያቄ መሠረት ግንቦት ፲፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለባሕረ ጥምቀት አገልግሎት የሚዉል ፶ ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ መረከቡን ከደብረ ማርቆስ ማእከል የደረሰን ዘገባ ያመለክታል፡፡

የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርቱን ዛሬ አስመረቀ፡፡

ሰኔ ፲፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በብሉይና በሐዲስ ኪዳን ትርጓሜ ለአምስትና ለሦስት ዓመታት ያስተማራቸውን ደቀ መዛሙርት ዛሬ ረፋድ ላይ በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ አስመረቀ፡፡

በምረቃው ሥርዓት ላይም ቅዱስ ፓትርያርኩን ጨምሮ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የልዩ ልዩ መምሪያዎች ሓላፊዎች፣ የሀገረ ስብከት ሠራተኞች፣ የገዳማት፣ የአድባራትና የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎች፣ የኮሌጁ መምህራን፣ ደቀ መዛሙርትና ሠራተኞች፣ እንደዚሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና የተመራቂዎች ቤተሰቦች ተገኝተዋል፡፡

የኮሌጁ ዋና ዲን ሊቀ ኅሩያን ሠርጸ አበበ የመክፈቻ ንግግር ባደረጉበት ወቅት ኮሌጁ ከተመሠረተበት ከ፲፱፴፭ ዓ.ም ጀምሮ በርካታ ሊቃውንትን በማፍራት ላይ እንደሚገኝ ጠቅሰው በዛሬው ዕለትም በቀኑና በማታው መርሐ ግብር ትርጓሜ መጻሕፍትን ተምረው በድምሩ ፪፴፮ (ሁለት መቶ ሠላሳ ስድስት) ዕጩ መምህራን መመረቃቸዉን፤ ከእነዚህ መካከልም አንደኛው ማየት የተሳናቸው፤ ሁለቱ ደግሞ ሴቶች መኾናቸውን ተናገረዋል፡፡

በዕለቱ በመንፈሳዊ ኮሌጁ ደቀ መዘሙርትና ዕጩ መምህራን ያሬዳዊ ዝማሬ የቀረበ ሲኾን፣ በተጨማሪም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትንና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን የሚያወድሱ፤ አስተዳደራዊ ችግሮች እንዲስተካከሉ የሚጠቁሙ ቅኔያት ከተበረከቱ በኋላ ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገቡ ተመራቂዎች ከቅዱስ ፓትርያርኩና ከብፁዕ ሥራ አስኪያጁ እጅ የሽልማትና የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡

ተመራቂ መምህራኑም በተወካያቸው አማካኝነት የዓቋም መግለጫቸዉን ያሰሙ ሲኾን፣ በዓቋም መግለጫቸውም ለመምህራን የበጀት ማስተካከያ እንዲደረግና በኮሌጁ ከሚሰጡት የብሉያትና የሐዲሳት ትርጓሜ ትምህርቶች በተጨማሪ መጻሕፍተ ሊቃውንትና መነኮሳትም መካተት እንደሚገባቸው ጠቅሰዋል፡፡

ተመራቂዎቹ አያይዘውም የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ጠብቀው እንደሚያስጠብቁ፤ የመናፍቃንን (የሐራ ጥቃዎችን) የኑፋቄ ትምህርት በጽናት እንደሚታገሉ፤ በስብከተ ወንጌል አገልግሎታቸዉም እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ሕይወታቸዉን አሳልፈው እንደሚሰጡ፤ እንደዚሁም ቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው የሚያወጣቸውን ቀኖናዎችን በማክበር ቤተ ክርስቲያንን በታዛዥነት እንደሚያገለግሉ ቃል ገብተዋል፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ በምረቃ ሥርዓቱ ላይ ንግግር ሲያደርጉ እንደገለጹት መንፈሳዊ ኮሌጁ ያሉበት ችግሮች መዋቅራቸዉን ጠብቀው ለጠቅላይ ቤተ ክህነትና ለቅዱስ ሲኖዶስ ቢቀርቡ ተገቢ እንደ ኾነ ገልጸው *ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጉዳዮችን በማጣራት ለችግሮቹ አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ ነው* ብለዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊም አባታዊ ቃለ ምዕዳን በሰጡበት ወቅት ስብከተ ወንጌል ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ አገልግሎት መኾኑን ጠቅሰው የቤተ ክርስቲያን አባቶችን ጨምሮ ኹሉም ሕዝበ ክርስቲያን ግንባር ቀደም በመኾን የጊዜውን የኑሮ ኹኔታ ባገናዘበ መልኩ የመምህራኑንና የደቀ መዛሙርቱን በጀት ለማስተካከል መዘጋጀት እንደሚገባቸው ተናግረዋል፡፡

በመጨረሻም በቅዱስ ፓትርያርኩ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ የምረቃ ሥርዓቱ ከቀኑ 6፡25 ተፈጽሟል፡፡

ወረደ መንፈስ ቅዱስ

ሰኔ ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መንፈስ ቅዱስ ማለት ከሦስቱ አካላት (ከቅድስት ሥላሴ) አንዱ፤ የእግዚአብሔር አብ፣ የእግዚአብሔር ወልድና የራሱም አካላዊ እስትንፋስ የኾነው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡

*ወረደ መንፈስ ቅዱስ* የሚለው የግእዝ ዓረፍተ ነገርም *መንፈስ ቅዱስ ወረደ* የሚል ትርጕም ያለው ሲኾን፣ ይህ ሲባልም በሰዉኛ ቋንቋ ከከፍታ ወደ ዝቅታ፣ ከሩቅ ወደ ቅርብ መምጣቱን ወይም መውረዱን ሳይኾን የእግዚአብሔር መንፈስ በሐዋርያት ላይ አድሮ ሰማያዊ ሀብትን፣ ዕውቀትን፣ ጥበብን መግለጹንና ልዩ ልዩ ጸጋን ማደሉን ያመላክታል፡፡

ይህ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ለጊዜው ለሐዋርያት ቢሰጥም፣ በእነርሱ ላይ ብቻ ሳይገደብ እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ በምእመናን ላይም አድሮ ይኖራል፡፡

ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ ወረደ የሚለው ትምህርት መንፈስ ቅዱስን በቦታ፣ በጊዜና በወሰን መገደቡን አያመለክትም፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ በዓለሙ ኹሉ የሞላ ነውና፡፡ በሰው ላይ አድሮ ጥበብን ሲገልጽ ግን ሞላ፤ አደረ፤ ወረደ ተብሎ ይነገራል፡፡ ይኸውም ሥራዉን በሰው ላይ መግለጡን፣ ጸጋዉንም ማብዛቱን ለማመልከት የሚያገለግል ቋንቋ ነው፡፡

ከላይ እንደ ተገለጸው እግዚአብሔር በቅዱሳን ሐዋርያት ላይ ፍርኃትን አስወግዶ ጥብዓትን (ጭካኔን)፣ ስጋትን አጥፍቶ ቈራጥነትን (ድፍረትን) ማሳደሩን፤ እንደዚሁም ሰማያዊ ሀብትን፣ ዕውቀትን፣ ጥበብንና ጸጋን እንዲያገኙ ማድረጉን፤ በዚህም ሐዋርያት ለስብከተ ወንጌልና ለሰማዕትነት የሚያበቃ ቅድስና ላይ መድረሳቸዉን ያመለክታል፡፡

መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ የወረደው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደባት፣ በተጠመቀባትና ከሞታን ተለይቶ በተነሣባት በዕለተ ሰንበት (በሰንበት ክርስቲያን) ሲኾን፣ መንፈስ ቅዱስ ከወረደበት ሰንበት (ከኀምሳኛው ቀን) ጀምሮ እስከሚቀጥለው ሰንበት ያለው ጊዜም (ስምንቱ ቀናት) ዘመነ ጰራቅሊጦስ ወይም ሰሙነ ጰራቅሊጦስ ይባላል፡፡ ይህም መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ ስለ መውረዱና በምእመናን ላይ ስለ ማደሩ የሚነገርበት ወቅት ነው፡፡

በዚህ ሰሙን በቤተ ክርስቲያን የሚነገረው ቃለ እግዚአብሔር፣ የሚሰጠውም ትምህርት የመንፈስ ቅዱስን በሐዋርያት ላይ መውረድ የሚመለከት ነው፡፡ ስለዚህም ከኀምሳኛው ቀን (ከበዓለ ጰራቅሊጦስ) ቀጥሎ በሚመጣው እሑድ (በስምንተኛው ቀን) በሌሊት በሊቃውንቱ የሚዘመረው መዝሙር፡- *ወረደ መንፈስ ቅዱስ ላዕለ ሐዋርያት ከመ ዘእሳት ወተናገሩ በነገረ ኵሉ በሐውርት* የሚል ሲኾን፣ ትርጕሙም መንፈስ ቅዱስ በእሳት አምሳል በሐዋርያት ላይ መውረዱንና በእርሱ ኃይል በዓለሙ ኹሉ ቋንቋዎች መናገራቸዉን የሚያስረዳ ነው፡፡

በዚህ ዕለት በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም፡- የሚከተሉት ናቸው፤ ኤፌ.፬፥፩-፲፯፤ ፩ኛዮሐ.፪፥፩-፲፰፤ ሐዋ.፪፥፩-፲፰፤ መዝ.፷፯፥፲፰ (ምስባክ)፤ ዮሐ.፲፬፥፩-፳፪ (ወንጌል)፡፡

የምንባባቱ ፍሬ ዐሳብም የጳውሎስ መልእክት፡- እያንዳንዳችን መንፈስ ቅዱስ በገለጸልን መጠን የየራሳችን ልዩ ልዩ ጸጋ እንዳለን፤ የዮሐንስ መልእክት፡- የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚፈጽም ለዘለዓለም ሕያው እንደ ኾነ፤ የሐዋርያት ሥራ፡- መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ እንደ ወረደና በዓለሙ ኹሉ ቋንቋዎች መናገር እንደቻሉ፤ መዝሙረ ዳዊት (ምስባኩ)፡- እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ልዩ ልዩ ጸጋን እንደሚሰጥ፤ የዮሐንስ ወንጌል፡- እግዚአብሔር እኛን ልጆቹን እንደ ወላጅ አልባ እንደማይተወን ያስረዳሉ፡፡

ቅዳሴውም ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ ሲኾን፣ ይህም ምሥጢረ ሥላሴን፣ የጌታችንን ሰው መኾን፣ ሕማሙን፣ ሞቱን፣ ትንሣኤዉን፣ ዕርገቱንና መንፈስ ቅዱስን መላኩን ይናገራል፡፡

ቅድስት በኾነች በጽርሐ ጽዮን በሐዋርያት ላይ የወረደው የእግዚአብሔር አብ ጸጋ፣ የእግዚአብሔር ወልድ ፍቅር፣ የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አንድነት በኹላችን ላይ ይደር፤ እጽፍ ድርብም ይኹን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ጰራቅሊጦስ ከሣቴ ምሥጢር

ሰኔ ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በመምህር ማዕበል ፈጠነ

ጰራቅሊጦስ ማለት ከሣቴ ምሥጢር ማለት ነው፡፡ ይኸውም በግብሩ ታውቋል፡፡ በበዓለ ጰራቅሊጦስ አበው ሐዋርያት ብዙ ምሥጢር በመንፈስ ቅዱስ ተገልጾላቸው ብሉይና ሐዲስን ተርጕመዋል፡፡

ማለትም ወደ ኋላ ተመልሰው *እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ በመጨረሻው ቀን ሥጋ በለበሰ ኹሉ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ፡፡ ልጆቻችሁ ትንቢት ይናገራሉ፤* ተብሎ የተነገረውን ትንቢት ጠቅሰው፣ በመብረቅ መጽሔት ተሞልተው ወደ ፊት የሰው ልጅ በሃይማኖትና በምግባር የሚወርሳትን የመንግሥተ ሰማይን ተስፋ አብሥረዋል /ሐዋ.፪፥፲፯፤ ኢዩ.፪፥፲፰/፡፡

ከቀደመው ቋንቋቸው ሌላ ፸፩ ቋንቋ ተገልጾላቸው በ፸፪ ቋንቋ አስተምረዋል፡፡ ይህ ሲባል ግን በዘመኑ የነበረው ሕዝብ እርስበርስ ይግባባቸው የነበሩት ቋንቋዎች ፸፪ ስለ ነበሩ ነው እንጂ መንፈስ ቅዱስ ከዚህም በላይ ቋንቋዎችንና ጥበብን መግለጽ እንደሚቻለው ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ጥንተ ነገሩስ እንደምን ነው ቢሉ ጌታችን በዚህ ዓለም ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ወንጌለ መንግሥትን አስተምሮ በመልዕልተ መስቀል ተሰቅሎ፣ በሲኦል የነበሩ ነፍሳተ ሙታንን ከዲያብሎስ ባርነት ነጻ አውጥቶ የሲኦልን በር ዘግቷል፡፡

በዚህ ዓለም ደግሞ ብርሃነ መለኮቱን ገልጾ ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ፵ ቀን ለአበው ሐዋርያት በመጽሐፈ ኪዳን የተገለጹ ረቂቅ ምሥጢራትን አስተምሮ መንፈስ ቅዱስ ትርጕሙን እንደሚነግራቸው፤ በሰዓቱ ግን መሸከም እንደማይችሉ ነግሯቸው ባረገ በ፲ኛው ቀን ለ፲፪ቱ ሐዋርያት፣ ለ፸፪ቱ አርድእትና ለ፴፮ቱ ቅዱሳት አንስት በአጠቃላይ ለ፻፳ው ቤተሰብ መንፈስ ቅዱስን ልኮላቸዋል፡፡ በዚህ ጊዜ በአዲስ ልሳን መናገር ጀምረዋል፡፡

አዲስ ልሳን ሲባልም በዓለም የሌለ ሌላ ባዕድ ቋንቋ ማለት አይደለም፡፡ የዓለም ቋንቋዎች ኹሉ በመንፈስ ቅዱስ እሳትነት በሐዋርያት አንደበት ተዋሐዱ፤ በልቦናቸው አደሩ፤ ሐዋርያት በዕውቀት ታነፁ ማለት ነው እንጂ፡፡ እንደሚታውቀው የሰው ልጅ የዓለማትን ቋንቋ በሙሉ ተምሮ ለማወቅ አይቻለዉም፡፡ አበው ሐዋርያት ግን ከሥጋዊ፣ ከደማዊ መምህር በመማር፤ መልክአ ፊደል በማጥናት ሳይኾን፣ መንፈስ ቅዱስ ገልጾላቸው አንደበታቸው ሰይፍ፣ ልሳናቸው ርቱዕ፣ ኾኖ በልዩ ልዩ ቋንቋዎች መናገር ችለዋል፡፡

ነገር ግን ሐዋርያት ባዕድ ቋንቋ አላመጡም፡፡ ጌታም የገለጸላቸው የዚህ ዓለም ብርሃን እንደመኾናቸው በዓለም የሚነገሩ ቋንቋዎችን ነው፡፡ ሰው የማይሰማውን ቋንቋ ቢናገሩ ኖሮ ከነፋስ ጋር እንደመናገር ይቈጠር ነበር /፩ኛቆሮ.፲፬፥፱/፡፡ ይህንንም ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ *ወአኀዙ ይንብቡ ዘዘዚአሆሙ በነገረ ኵሉ በሐውርት በከመ ወሀቦሙ መንፈስ ቅዱስ፤ ኹሉም መንፈስ ቅዱስን ተሞሉ፡፡ ይናገሩ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እንዳደላቸው መጠንም እየራሳቸው በአገሩ ኹሉ ቋንቋ ይናገሩ ጀመሩ፤* በማለት ገልጾታል /ሐዋ.፪፥፬/፡፡

በዚህ ጊዜ ቤተ አይሁድ በከፊል አንጎራጎሩ፤ አሕዛብ ተደመሙ፡፡ ሐዋርያትን በገዛ ቋንቋቸው ሲናገሩ ሰምተው *እኛ የጳርቴ፣ የሜድ፣ የኢላሜጤም ሰዎች ስንኾን፣ በእኛ ቋንቋ እነሆ የእግዚአብሔርን ጌትነት ሲናገሩ እንሰማዋቸዋልን* ሲሉ አደነቁ፤ ከእግራቸው ሥርም ወደቁ፡፡ በቅፅበትም ሦስት ሺህ ነፍሳት አምነው ተጠመቁ፡፡

በዚህ ዘመን በግላቸው ቤተ እምነት መሥርተው የሚኖሩ ባዕዳን *መንፈስ ቅዱስ ወረደልን፤ አዲስ ልሳን ተገለጠልን፤ እልል በሉ፤* እያሉ ዐይናቸውን ይጨፍናሉ፤ አእምሯቸውን ይስታሉ፡፡ በአንደበታቸውም እነርሱ የማያውቁትን፤ ሌላ ሰውም ሊሰማው የማይችለዉን ትርጕም የሌለዉን ጩኸት፣ እነርሱ ልሳን የሚሉትን ድምፅ ያነበንባሉ፡፡

የመንፈስ ቅዱስ ዓላማ ሰዎች እርስበርስ እንዲግባቡ ትርጕም ያለዉን ቋንቋ መግለጽ እና ኹሉም በየቋንቋው የእግዚአብሔርን የምሥራች ቃል እንዲማር፣ እንዲያውቅና እንዲረዳ ማድረግ ነው፡፡ ልሳን ማለትም ሰው ሊረዳውና ሊግባባት የሚችል ቋንቋ ማለት እንጂ ድምፅ በማውጣት ብቻ የሚገለጽ ጩኸት አይደለም፡፡ መናፍቃኑ ልሳን የሚሉት ግን ይህንኑ ዓይነት ባዶ ጩኸት ነው፡፡ ይህም ከሰይጣን እንጂ ከመንፈስ ቅዱስ እንዳልኾነ ያጠይቃል፡፡

የመንፈስ ቅዱስ የሆነው አዲስ ልሳን ግን ትናንት በአበው ሐዋርያት ዘመን የነበረ፤ ዛሬም በእኛ ዘመን ያለ፤ ለመጭው ትውልድም የሚተላለፍ ሕያው ልሳን ነው፡፡ ለምን ቢሉ ከሣቴ ምሥጢሩ (ምሥጢር ገላጩ) መንፈስ ቅዱስ ነውና፡፡

እንግዲህ በነቢያት የተነገረው፣ በሐዋርያት ልቡና በእሳት አምሳል የተገለጠው ምሥጢረ መንፈስ ቅዱስ ይህ ነው፡፡ ይህ ምሥጢር ከትውልድ ወደ ትውልድ ተላልፎ በሐዋርያት ልቡና ቀርቷል፤ ከሐዋርያት ልቡና ያልደረሰው ደግሞ በልበ መንፈስ ቅዱስ ቀርቷል፡፡ ዓውደ ትምህርቱ ይህ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ስም የተገነባው ዘመናዊ ሕንጻ ተመረቀ፡፡

ሰኔ ፲፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በደመላሽ ኃይለ ማርያም

በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት በከላላ ወረዳ ቤተ ክህነት በ፳፻፫ ዓ.ም በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ መሠረቱ የተቀመጠው፣ ከስምንት ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገበት በአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ስም የተገነባው ባለ ሦስት ፎቅ ኹለገብ ዘመናዊ ሕንጻ ሰኔ ፲፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ተመረቀ፡፡

በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይም ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፤ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ የሊቃውንት ጉባኤ ሓላፊ፣ የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ጠባቂና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፤ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝና ሌሎችም የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አስፈጻሚ አባላት፣ የዞኑ የመንግሥት ባለ ሥልጣናት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና በርካታ ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ የመክፈቻ ንግግር ባደረጉበት ወቅት ማኅበሩ ከሚሠራቸው ፻፳ወ፮ (126) ፕሮጀክቶች መካከል ይህ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ፕሮጀክት አንዱ መኾኑን ገልጸው፣ ከመሠረቱ መቀመጥ ጀምሮ እስከ ፍጻሜው ድረስ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስና የየመምሪያ ሓላፊዎች ላደረጉት አስተዋጽኦ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

ይህ ዘመናዊ ሕንጻ በከተማው ካሉት አራት ሕንጻዎች መካከል አንዱ ሲኾን፣ በውስጡም ለእንግዳ ማረፊያ አገልግሎት የሚውሉ ዐሥራ ስምንት ክፍሎች፣ የባንክ ወይም የምግብ አገልግሎት የሚሰጥ ክፍል፣ ለንግድ ሥራ የሚኾኑ ሱቆች እና ሌላም ሥራ ሊሠራባቸው የሚችሉ ክፍሎችን የያዘ ሲኾን፣ ከዚህ ኹሉ አገልግሎት የሚገኘው ገንዘብ ተሰብስቦ ለደብረ ባሕርይ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ እና አባ በጸሎተ ሚካኤል ገዳም አገልግሎት ማጠናከሪያነት እንደሚውል የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር የኾኑት ዲ/ን አእምሮ ይሄይስ አስረድተዋል፡፡

ዲ/ን አእምሮ አያይዘውም የአባ ጊዮርስ ዘጋሥጫ ዘመናዊ ሕንጻ በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ የበላይ ሓላፊነት በሚዋቀረው ኰሚቴ እንደሚመራ ገልጸው፣ በዚህም የማኅበረ ቅዱሳን ድጋፍ የሚቀጥል መኾኑን ተናግረዋል፡፡

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስና ሌሎች የክብር እንግዶች ሕንጻውን ከጐበኙ በኋላ በአባቶች ጸሎት እና ቡራኬ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ኾኗል፡፡

የ፭ኛው አገር ዓቀፍ የሰ/ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ አጭር ዳሰሳ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሰኔ ፲፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ከ፳፻፬ ዓ.ም ጀምሮ በየዓመቱ በበዓለ ጰራቅሊጦስ ሳምንት የአንድነት ጉባኤውን ያካሒዳል፡፡

በያዝነው ዓመትም ከሰኔ ፲-፲፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለሦስት ቀናት በቆየው ጉባኤ የየአህጉረ ስብከቶች ሰ/ት/ቤቶች ሪፖርቶችና ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡

ለሦስት ቀናት በቆየው በዚህ የሰንበት ት/ቤቶች ጠቅላላ የአንድነት ጉባኤ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች፣ እንደዚሁም የወጣቶች የአገልግሎት ፈተናዎችና መፍትሔዎቻቸው፣ በ፳፻፰ ዓ.ም የአገልግሎት ዘመን የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያና የሰ/ት/ቤት ወጣቶች ጠንካራና ደካማ ጎኖች ተዳስሰዋል፡፡

ሰኔ ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የአሕዛብንና የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴ በሚመለከት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ በተገኙበት ለጉባኤው የቀረበው ጥናታዊ ጽሑፍ ከፍተኛ መነቃቃትን ፈጥሯል፡፡

በጉባኤው መዝጊያ ዕለትም የ፳፻፱ ዓ.ም ዕቅድ የትኩረት አቅጣጫዎችን አስመልክቶ ሰፊ ውይይት ተካሒዷል፡፡

በውይይቱም የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት የዕድሜ ገደብና የሥራ አስፈጻሚዎች የአገልግሎት ዘመን መሻሻል አለበት ተብሏል፡፡

በተጨማሪም የ፳፻፱ ዓ.ም ዓመታዊ የተግባር ዕቅድ በጉባኤው ውይይት ከተደረገበት በኋላ ዕቅዱ ጸድቆ ሥራ ላይ እንዲውል ተወስኗል፡፡

የ፳፻፱ ዓ.ም የመሪ ዕቅዱ ግቦች፡- ቤተ ክርስቲያን የሰ/ት/ቤት አገልግሎትን ለማስፋትና ለማጠናከር መዘገጀቷን ማሳወቅ፣ በዓላማው ዙሪያ ሕዝቡን በስፋት ማነሣሣትና ለተግባር ማንቀሳቀስ፤ ቢጽ ሐሳውያንን የመከላከል ዘመቻ፤ እንደዚሁም የሰ/ት/ቤቶችን ሥርዓተ ትምህርት የማስቀጠልና የመከለስ ጥናት ሲኾኑ፣ በመሪ ዕቅዱ በመጀመሪያ አንድ ዓመት ከመንፈቅም፡- የሰንበት ት/ቤቶችን የዝማሬ ሥርዓት እና የሰንበት ት/ቤቶችን አንድነት መዋቅር ማጠናከር የሚሉ ነጥቦች ተካተዋል፡፡

በጉባኤው መዝጊያ ዕለት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት እና ብፁዕ አቡነ ማትያስ ካልዕ የካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የተገኙ ሲኾን፣ በዕለቱ ቅዱስ ፓትርያርኩ ‹‹አንትሙሰ ንበሩ በኢየሩሳሌም እስከ ትለብሱ ኃይለ እምአርያም፤ እናንተ ግን ከላይ ኀይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ፤›› /ሉቃ.፳፬፥፵፱/ በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡

ቅዱስነታቸው ትምህርት በሰጡበት ወቅትም ‹‹ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ እስኪወርድላቸው ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ እንዲቆዩ ታዝዘዋል፡፡ እኛም እግዚአብሔር ማስተዋሉን፣ ጥበቡንና ጸጋውን እንዲያድለን በቤተ ክርስቲያን መቆየት ይገባናል፤›› ብለዋል፡፡

እንደዚሁም ‹‹ወጣቱ ትውልድ ትኩስ ስለኾነ ኹሉም ነገር የሚጎዳ አይመስለውም፡፡ ክፉዉን ከበጎው ለመለየት የሚቻለን መንፈስ ቅዱስ ሲያድርብን ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ የሚያድርብን ደግሞ ሐቀኝነት፣ ፍቅር፣ ሰላም፣ እምነት፣ አንድነት ሲኖረን ነው፡፡ ጊዜውም መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት የወረደበት ወቅት ነውና ራሳችንን ለመንፈስ ቅዱስ ማደሪያነት ማዘጋጀት ይገባናል፤›› ሲሉ አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ቅዱስነታቸው አያይዘውም ‹‹ይህ ዓለም በብዙ ጣጣዎች የተሞላ ነውና በአገልግሎታችሁ ላይ ልዩ ልዩ ፈተና ሊመጣባችሁ ይችላል፡፡ በዚህ ጊዜ ፀላዔ ሠናያት ሰይጣንን ፃእ መንፈስ ርኵስ ማለት ያስፈልጋል፤›› ካሉ በኋላ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ለቤተ ክርስቲያን ሞገስ፣ ድምቀትና ተጨማሪ ሀብት መኾናቸውን ጠቅሰው ‹‹የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ለቤተ ክርስቲያኒቱ ህልውና ስትሉ የምታነሡትን ጥያቄ ለመመለስ ዝግጁ ነን፤›› ሲሉ ቃል ገብተዋል፡፡

በመጨረሻም ‹‹ይህንን ሰላማዊ ጉባኤ በሰላም በማካሔዳችሁ ለደስታችን ወሰን የለውም፡፡ በዛሬው ዕለት በዚህ ጉባኤ ተገኝቼ ቡራኬ በመስጠቴ ደስታ ይሰማኛል፤›› ሲሉ ስሜታቸውን ገልጸዋል፡፡

የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ዋና ሓላፊ መ/ር ዕንቈባሕርይ ተከሥተ የመዝጊያ ንግግር ባደረጉበት ወቅት ለጉባኤው መሳካት አስተዋፅኦ ያደረጉ አካላትንና በጉባኤው የተገኙ የየሰንበት ት/ቤት ተወካዮችን ካመሰገኑ በኋላ ለየሀገረ ስብከቱ ሰ/ት/ቤት መምሪያዎች ፴፬ የመዝሙር ሲዲዎች በነጻ እንዲሠራጩ መደረጉን ገልጸው ‹‹ከእንግዲህ የመናፍቃንን ዘፈንና ቀረርቶ የምንሰማበት ጊዜ አይኖርም፡፡ ከዚህ በኋላ ኹላችንም ወደ ድጓው፣ ጾመ ድጓው ነው የምንሔደው!›› የሚል ቁጭት አዘል መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

ሰኔ ፲ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ረፋድ ላይ በቅዱስ ፓትርያርኩ ጸሎተ ቡራኬ የተከፈተው ይህ የአንድነት ጉባኤ ባለ ፲፭ ነጥብ የጋራ የአቋም መግለጫውን በፓትርያርኩ ፊት ካቀረበ በኋላ በቅዱስነታቸው ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ሰኔ ፲፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ ፲፩ ተፈጽሟል፡፡

በጋራ የአቋም መግለጫውም፡- የተሐድሶ መናፍቃን የእምነት መግለጫ፣ የሰ/ት/ቤቶች በየቦታው መቋቋም፣ የአባላት የአገልግሎት ዘመን መሻሻል፣ የሰ/ት/ቤት ወጣቶች እንግልትና ስም የማጥፋት ዘመቻ፣ ወዘተ የመሳሰሉ ዐበይት ነጥቦች ተካተውበታል፡፡ የጉባኤውን ሙሉ የጋራ አቋም መግለጫ ተራ ቍጥሮችን፣ አንዳንድ ቃላትንና ፊደላትን አስተካክለን እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የአገር አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ፭ኛ ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ የወጣ የጋራ አቋም መግለጫ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃለ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የወሊሶ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የደቡባዊ ዞን የማይጨው፤ የምሥራቅ ትግራይ አዲግራትና መቐለ ዙሪያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፤

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ፤ የጉራጌ ስልጤ፣ ከምባታና ሐድያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፤

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤

የጠቅላይ ቤተ ክህነት የየመምሪያ ሓፊዎች፣ ጥሪ የተደረገላችሁ የክብር እንግዶች፤

እኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤን ወክለን በ፭ኛው አገር አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት አጠቃላይ ጉባኤ ላይ የተሳተፍን የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ አባላት፣ ከሰኔ ፲-፲፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ላለፉት ሦስት ቀናት በማደራጃ መምሪያው ዓመታዊ የአገልግሎት ዘገባ፣ በ፳፭ አህጉረ ስብከት የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት እና የሰንበት ት/ቤቶች ዋና ክፍል የሥራ ክንውን ሪፖርት፤ እንደዚሁም የሰንበት ት/ቤቶች አባላት በኾኑ ባለሙያዎች በቀረቡ ሦስት ጥናታዊ ጽሑፎች ላይ ሰፊ ውይይት አድርገናል፡፡

የመምሪያው ዘገባም ኾነ ከ፳፭ አህጉረ ስብከት የመጡ ተወካዮች ያቀረቡት ሪፖርት ሰንበት ት/ቤቶች እጅግ በርካታ ተግባራት እያከናወኑ እንደሚገኙና የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ ለማፋጠን እየተጉ መኾናቸውን አስገንዝቧል፡፡

ኾኖም ግን በየአህጉረ ስብከቱ ያሉ መናፍቃን እና አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ተጽዕኖዎች፣ በየአጥቢያ ሰንበት ት/ቤቶች እየደረሱ ያሉ የአስተዳደር በደሎች፣ የበጀት እና የመምህራን እጥረት፣ የመሰብሰቢያና የመማሪያ ቦታ አለመኖር፣ የአንዳንድ አህጉረ ስብከት ስፋት እና ለትራንስፖርት አመቺ አለመኾን አገልግሎቱን እየተፈታተኑ ያሉ ዋና ዋና ችግሮች ኾነው ተመዘግበዋል፡፡

በመጨረሻም በሪፖርቱም ኾነ በጥናታዊ ጽሐፎቹ የተጠቀሱትን ዋና ዋና ችግሮች በመለየት በተደረገው የጋራ ውይይት በቀጣይነት ሰንበት ት/ቤቶች በጋራ የምንሠራቸውን እና የምንስማማባቸውን የሚከተሉትን የአቋም መግለጫዎች አውጥተናል፤

፩.የሰ/ት/ቤቶች አንድነት የ፭ ዓመት ዕቅድ ማለትም ከ፳፻፮-፳፻፲ ዓ.ም ድረስ የታቀደውን መሪ ዕቅድ በቀሩት ጊዜያትም ለመፈጸምና ለማስፈጸም ቃል እንገባለን፡፡

፪.የሰ/ት/ቤቶች አጠቃላይ መሪ ዕቅድ የኹሉም አጥቢያ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዕቅድ አካል እንዲኾን እና የጠቅላይ ቤተ ክህነት መምሪያዎችም የሰ/ት/ቤቶችን መሪ ዕቅድ ከዕቅዳቸው ጋር በማገናዘብ በዕቅድ እንዲካተቱ ይደረግ ዘንድ እንጠይቃለን፤

፫.መልክዓ ምድርን መሠረት ያደረገ የሰንበት ት/ቤቶች ትስስር በማጠናከር ሰንበት ት/ቤቶች ባልተቋቋሙባቸው አጥቢያዎች እንዲቋቋሙ፣ በተቋቋሙባቸው ደግሞ የተጠናከረ አገልግሎት እንዲሰጥባቸው ለማድረግ እንሠራለን፡፡

፬.በአገር አቀፍ ሰ/ት/ቤቶች አንድነት የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴና መጠነ ሰፊ ጥፋትን አስመልክቶ በመረጃ ክፍል የተሰበሰቡና የተደራጁ ማስረጃዎችን ለቅዱስነትዎና ለቅዱስ ሲኖዶስ እንድናቀርብ እንዲፈቀድልን በአንድነት እንጠይቃለን፡፡

፭.በ፳፻፬ ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ የተወገዙ ፲፮ ግለሰቦችና ፰ ማኅበራት ያስተላለፏቸው የምንፍቅና ትምህርቶችና መጻሕፍት በሊቃውንት ጉባኤ መልስ እንዲሰጣቸው የታዘዘ ቢኾንም ነገር ግን እስከ ዛሬ ድረስ ምላሽ ባለመሰጠቱ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ የእምነት መግለጫ የሚል የክህደት መግለጫ እስከ ማውጣት ደርሰዋል፡፡ ስለኾነም ለእነዚህ አካላት አስቸኳይ ምላሽ ይሰጥልን ዘንድ በአንድነት እንጠይቃለን፡፡

፮.በአሁኑ ሰዓት በቤተ ክርስቲያኒቷ ተልእኮ አፈጻጸም ላይ ተጽዕኖ እየፈጠረ ያለው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴ ለማስቆም ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ በየደረጃው ያሉ የቤተ ክርስቲያን አካላት አፋጣኝ ርምጃ እንዲወስዱ እንጠይቃለን፡፡

፯.ከዚህ ቀደም በአዲስ አበባ ሰ/ት/ቤቶች የቀረበው የፕሮቴስንታዊ ተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ መረጃ ውሳኔ እንዲሰጠው፤ ውሳኔው ተግባራዊ ይሆን ዘንድም ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ ያሉ የቤተ ክርስቲያኒቷ አካላት አስፈላጊውን ርምጃ እንዲወስዱ እንጠይቃለን፡፡

፰.በአሁኑ ጊዜ በአንዳንድ የቤተ ክርስቲያን ሓላፊዎች በተሳሳተ አመክንዮ በሰንበት ት/ቤት ወጣቶች እና አባላት ላይ እየደረሰ ያለው እስር፣ እንግልት እና ወከባ እንዲቆምልን በአንጽዖት እንጠይቃለን፡፡

፱.ከዚህ ጋር ተያይዞ የመንግሥት የፍትሕ አካላትም ከአጥፊዎች ጋር በመተባበር የሰንበት ት/ቤት አባላትን ከማሰር እና ከማንገላታት እንዲታቀቡ እንዲደረግ በቅዱስ ሲኖዶስ በኩል መመሪያ እንሰጥልን እንጠይቃለን፡፡

፲.በቃለ ዓዋዲው እና በ፲፱፻፹፮ ዓ.ም በወጣው ውስጠ ደንብ ላይ የተጠቀሰው የሰ/ት/ቤቶች የዕድሜ ገደብ እንዲነሣልን በድጋሜ እንጠይቃለን፡፡

፲፩.ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ አንሥቶ እስከ አጥቢያ ሰ/ት/ቤቶች የሚደርስ የፋይናንስ ትስስር እና አያያዝ ሥርዓት በመምሪያው በኩል ተጠንቶ እንዲጸድቅልን እንጠይቃለን፡፡

፲፪.በዘመናችን ሚዲያ በወጣቱ እና በሕፃናት አስተዳደግ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እየፈጠረ ስለሚገኝ፣ የቤተ ክርስቲያኒቷን አስተምህሮ ለምእመናን በስፋት ማዳረስ እንዲቻል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የሚመራ እና የሚተዳደር፣ ቤተ ክርስቲያኒቷንም የሚወክል የቴሌቭዥን መርሐ ግብር ሥርጭት በመጀመሩ ከመምሪያው ጀምሮ እስከ አጥቢያ ያለን ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት በጋራ ለመሥራት ቃል እንገባለን፡፡

፲፫.ተወካዮቻቸውን ያልላኩ አህጉረ ስብከት ተለይተው በጠቅላይ ቤተ ክህነት የማያዳግም ርምጃ እንዲወሰድባቸው እንጠይቃለን፡፡

፲፬.በቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊና ልማታዊ ጉዳዮች ከአባቶቻችን ጋር በመኾን ያለንን አቅም አሟጠን በመጠቀም ለቤተ ክርስቲያናችን ዕድገት እና ልዕልና የበኩላችንን ድርሻ እንወጣለን፡፡

፲፭.የቤተ ክርስቲያናችንን ኹለንተናዊ ችግሮች ለመፍታት ከመንፈሳዊ ኮሌጆች ምሩቃን ጋር ተባብረን የምንሠራ መኾናችንን እንገልጻለን፡፡

ሰኔ ፲፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም፡፡

የደቡብ ማእከላት የአንድነት ጉባኤ አካሔዱ፡፡

ሰኔ ፲ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በሐዋሳ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በሐዋሳ ማእከል አዘጋጅነት በደቡብ ማስተባበሪያ ሥር ያሉት የዘጠኝ ማእከላት ሥራ አስፈጻሚዎችና አባላት ከሰኔ ፫-፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረስ በሐዋሳ ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የግቢ ጉባኤ አዳራሽ የልምድ ልውውጥና የአንድነት ጉባኤ አካሔዱ፡፡

በዕለቱ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ፣ እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር አባል አቶ ፋንታኹን ዋቄ የተገኙ ሲኾን፣ በመርሐ ግብሩ መክፈቻ ላይም የነቃህ ኹን /ራእ.፫፥፪/ በሚል ኃይለ ቃል ወቅታዊውን የቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና ሓላፊነትን መሠረት ያደረገ ትምህርተ ወንጌል በዲያቆን ስንታየሁ ጂሶ ተሰጥቷል፡፡ በጉባኤውም ፺ የየማእከላት ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤና የሐዋሳ ማእከል አባላት ተሳትፈዋል፡፡

በጉባኤው ሁለተኛ ቀን የቤተ ክርስቲያንን ኹለንተናዊ አገልግሎት ለመደገፍ የማኅበረ ቅዱሳንን ድርሻ የሚያመለክት ሥልጠና በማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ የተሰጠ ሲኾን፣ በልምድ ልውውጡ መርሐ ግብርም መልካም አርአያነት ያላቸው ማእከላትና ንዑሳን ክፍሎች የልምድ ተሞክሯቸውን ለጉባኤው ተሳታፊዎች አካፍለዋል፡፡

እንደዚሁም በደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊ በመ/ር ዘሪሁን ከበደ የዘጠኙም ማእከላት የአራት ዓመት የማኅበረ ቅዱሳን ስልታዊ ዕቅድ አፈጻጸም ማጠቃለያ የቀረበ ሲኾን፣ በተጨማሪም በጉባኤው ፫ኛ ቀን ውሎ፣ Living the Orthodx Life in the Era of Globalization and Secular Humanism፤ ኦርቶዶክሳዊ ሕይወት በዘመነ ሉላዊነትና ዓለማዊነት በሚል ርእስ በአቶ ፈንታሁን ዋቄ የግማሽ ቀን ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡

በመጨረሻም የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊ ይህ ጉባኤ ለየማእከላቱ አገልግሎት መነሣሣት የሚኖረውን አስተዋጽኦ ከገለጹና የ፳፻፱ ዓ.ም ተመሳሳይ ጉባኤ አዘጋጅ ወላይታ ዶ ማእከል እንዲሆን ከተወሰነ በኋላ ሰኔ ፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ ፭ ሰዓት የአንድነት ጉባኤው ተፈጽሟል፡፡