የማኅበረ ቅዱሳን ፲፪ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ዳሰሳ

ጳጕሜን ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዝግጅት ክፍሉ

DSCN9300

የተወደዳችሁ ምእመናን! ማኅበረ ቅዱሳን ከነሐሴ ፳፯-፳፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረስ ፲፪ኛ ጠቅላላ ጉባኤውን በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽና በማኅበሩ ሕንጻ ፫ኛ ፎቅ ለሦስት ቀናት አካሒዷል፡፡ ከዓርብ ምሽት እስከ እሑድ ሌሊት ድረስ የነበረውን የጉባኤውን አጠቃላይ ይዘት በአጭሩ እናስቃኛችሁ!

DSCN8880

ከነሐሴ ፳፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ የማኅበሩ መደበኛ አገልጋዮች ለአገልግሎት የሚጠቀሙባቸውን ልዩ ልዩ ንብረቶቻቸውን በተዘጋጀላቸው ጊዜያዊ ቦታ በማስቀመጥ ቢሮዎቻቸውን ለእንግዶች ማረፊያ ለቀዋል፡፡ ከዚያች ሰዓት በኋላ የመግቢያ መለያ ከተሰጣቸው አባላት በስተቀር ማንኛውም አባል ወደ ሕንጻው እንዲገባ አይፈቀድለትም፡፡ በዚህ ጉባኤ ለመሳተፍ ከአሜሪካ፣ ከአውሮፓ፣ ከዐረብ አገሮችና ከአፍሪካ አህጉር፤ ከአገር ውስጥ ደግሞ ከአራቱም የኢትዮጵያ አቅጣጫዎች የመጡ በርካታ ወንድሞችና እኅቶች በአዲስ አበባ ከተማ ከመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም በስተምዕራብ አቅጣጫ በተገነባው የማኅበረ ቅዱሳን ሕንጻ ተሰባስበዋል፡፡

DSC01834

በዕለተ ዓርብ ነሐሴ ፳፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለጉባኤው ተሳታፊዎችና ጥሪ ለተደረገላቸው እንግዶች አቀባበል ከተደረገላቸው በኋላ ምሽት ፲፪ ሰዓት ላይ ጠቅላላ ጉባኤው በማኅበር ጸሎት ተጀምሮ በጸሎት እስከ ተጠናቀቀበት ነሐሴ ፳፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረስ የነበሩ መርሐ ግብራት የቀኖቹ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ፤ የማታዎቹ ደግሞ በማኅበሩ ሕንጻ ተከናውነዋል፡፡ ለተሳታፊዎቹ አቀባበል በተደረገበት ዕለትም ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት እንደሚገባ የሚያስገነዝብ ትምህርተ ወንጌል በመምህር ቸርነት አበበ ተሰጥቷል፡፡

DSCN8898

በዚህ ጠቅላላ ጉባኤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስን ጨምሮ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፣ ብፁዕ አቡነ ሰላማ፣ ብፁዕ አቡነ ገብርኤልና ብፁዕ አቡነ እንጦንስ ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡ ኹሉም የማኅበረ ቅዱሳን አባላት በእግዚአብሔር ጥበብ ለአገልግሎት የተጠሩ መኾናቸውን ተረድተው፣ የተሰጣቸውን ልዩ ልዩ ጸጋ ተጠቅመው፣ በፈተና ጸንተው ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በትዕግሥትና በትጋት ማገልገል እንደሚገባቸው የሚያተጋ መልእክት ያለው ትምህርተ ወንጌል ‹‹በወንዝ ዳር ጣለችው›› በሚል ኃይለ ቃል በዲያቆን ዶ/ር ያረጋል አበጋዝ ተሰጥቷል፡፡

በተጨማሪም የተሳታፊዎችን ግንዛቤ የሚያዳብሩ ጥናቶችም ቀርበዋል፡፡ ከእነዚህ መካከልም ኦርቶክሳዊነትን የሚፈታተኑ ዓለም ዓቀፍ ችግሮች በምእመናን ላይ የሚያደርሷቸውን ተጽዕኖዎችና መፍትሔዎቻውን በስፋት የዳሰሰ ጥናት ‹‹በፈታኝ ነባራዊ ኹኔታዎች እየኖሩ ኦርቶዶክሳዊ ተቋማዊ አገልግሎትን መፈጸም እንዴት ይቻላል?›› በሚል ርእስ በዲያቆን ብርሃኑ አድማስ፤ ከቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ ከማኅበራትና በጎ አድራጊ ምእመናን ጋር በመስማማት እንዴት ማገልገል እንደሚቻል የሚያስገነዝብ ‹‹የባለ ድርሻና አጋር አካላት ውጤታማነትና ስኬታማነት›› በሚል ርእስ በማኅበሩ ዋና ጸሐፊ በአቶ ተሰፋዬ ቢኾነኝ የቀረቡት ጥናቶች ይጠቀሳሉ፡፡

በጠቅላላ ጉባኤው ማኅበሩን የሚመሩ ሥራ አመራሮች ተመርጠዋል፡፡ ማኅበሩ በ፳፻፯ እና በ፳፻፰ ዓ.ም በሁለት ዓመታት ውስጥ ያከናወናቸው ዘርፈ ብዙ ተግባራት፤ የማኅበሩ አጠቃላይ የገቢ መጠንና ለአገልግሎት ማስፈጸሚያ ያወጣው ገንዘብ፤ ማኅበሩ አገልግሎቱን ለመፈጸም በሚያደርገው እንቅስቃሴ ያጋጠሙት ልዩ ልዩ ችግሮችና የተወሰዱ መፍትሔዎች በዝርዝር ለጉባኤው ቀርበዋል፡፡ እንደዚሁም የሁለት ዓመቱ አጠቃላይ የሒሳብ ሪፖርት በተመሰከረላቸውና ሕጋዊ ዕውቅና በተሰጣቸው የውጪ ኦዲተሮች ሪፖርት ተደርጓል፡፡ ሪፖርቱም የማኅበሩን ጥንቃቄ የተሞላበትና አርአያነት ያለው ዘመናዊ የሒሳብ አጠቃቀም ዘዴ የሚያመላክት መኾኑ በኦዲተሮቹ ተገልጿል፡፡

DSCN9249

ከጉባኤው አዳዲስ ክሥተቶች ውስጥ በጠቅላላ ጉባኤው ማጠቃለያ ነሐሴ ፳፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በዕለተ እሑድ ምሽት የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና የሰባክያነ ወንጌል ምክርና የአደራ ቃል ያለበት የ፳ ደቂቃ ዘጋቢ ፊልም የጉባኤውን ተሳታፊዎች አስለቅሷል፡፡ በተለይ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ ቤተ ክርስቲያን ችግር ውስጥ መኾኗንና ለአገር የዋለችው ውለታ ተረስቶ ምንም እንዳልሠራች መቈጠሯን ሲያስረዱ፤ እንደዚሁም ‹‹ምንም ብትበሳጩ ቤተ ክርስቲያንን በጠላትነት እንዳታዩአት በእግዚአብሔር አደራ እላችኋለሁ›› እያሉ ለወጣቶች መልእክት ሲያስተላልፉ አረጋዊው ጳጳስ ያሰሙት የነበረው የለቅሶ ድምፅና እርጅና ባደከመው ፊታቸው የሚፈሰው ዕንባቸው፤ እንደዚሁም በፊልሙ ላይ የብፁዕነታቸውን ቃለ ምዕዳን የሚቀበሉ ምእመናን ሰቆቃ የጠቅላላ ጉባኤውን መንፈስ ሙሉ በሙሉ ወደ ኀዘን ለውጦታል፡፡

ፊልሙ ከተጠናቀቀ በኋላ ሳይቀር የመርሐ ግብር መሪው ዕንባውን መቈጣጠር ሲያዳግተው ተስተውሏል፡፡ ‹‹ማርያም ኀዘነ ልቡና ታቀልል፤ ማርያም የልብን ኀዘን ታቀላለች›› የሚለው ዝማሬ ከተዘመረ በኋላ ነበር በመጠኑም ቢኾን የጉባኤው የኀዘን መንፈስ ወደ ውይይት ሊመለስ የቻለው፡፡ ዘጋቢ ፊልሙ የጉባኤውን ተሳታፊዎች ከማስለቀሱ ባለፈ ኹሉም የራሱን ድርሻ ዐውቆ ቤተ ክርስቲያንን በትጋት ለማገልገል እንዲነሣሣ ጭምር ማድረጉን አስተያየት ከሰጡ አባቶች፣ ወንድሞችና እኅቶች ስሜት ለመረዳት ተችሏል፡፡

DSCN9158

ጉባኤው ከኀዘኑ ሲረጋጋም በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፍ ባስመዘገቡት ውጤት በአርአያነት የተመረጡ ከአገር ውስጥ ደብረ ማርቆስ፣ ጎንደር፣ ደሴና ጅንካ፤ ከውጪ አገር ደግሞ አሜሪካ በድምሩ ፭ ማእከላት በተወካዮቻቸው አማካይነት የልምድ ተሞክሯቸውን አቅርበዋል፡፡ ከተሞክሮው መካከልም የአሜሪካ ማእከል የአካባቢውን ምእመናን በማስተባበር ሕፃናት የአብነት ትምህርት እንዲማሩ ማድረጉና ሕፃናቱ ከንባብ ጀምሮ እስከ መጽሐፍ ቤት ድረስ ያለውን የአብነት ሥርዓተ ትምህርት ሲያቀርቡ የሚያስቃኘው ዘጋቢ ፊልም የማእከሉን ጥረት ከማስደነቁ ባሻገር ኢትዮጵያውያን ወላጆች ‹‹እኛስ ምን ሠራን?›› እንዲሉ አድርጓቸዋል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ዋናው ማእከል በሁለት ዓመታት የአገልግሎት ጊዜው ያጋጠሙትን ችግሮች ያለፈበት መንገድና የወሰዳቸውን የመፈትሔ ርምጃዎች የሚያመለክት የልምድ ተሞክሮም በማኅበሩ ሰብሳቢ ለጉባኤው ቀርቧል፡፡

dscn9321

dscn9344

ተሳታፊዎች የቡድን ውይይት ሲያደርጉ

በመቀጠል የጠቅላላ ጉባኤው ዐቢይ ኰሚቴ ሰብሳቢ አቶ ዳንኤል ገብረ መድኅን በማጠቃለያ ሪፖርታቸው የጉባኤው ተሳታፊዎች ላሳዩት ታዛዥነት፣ ትሕትናና ቅንነት፤ እንደዚሁም በውይይትና አስተያየት በመስጠት ላደረጉት የነቃ ተሳትፎ፤ በተጨማሪም ድርጅቶችን ጨምሮ ድጋፍ ሰጪ ክፍሎችና በጎ አድራጊ ምእመናን በዐሳብ፣ በጉልበት፣ በገንዘብ፣ በቁሳቁስ አቅርቦት፣ በጽዳት ሥራ፣ የሕክምና አገልግሎት በመስጠትና በመስተንግዶ ላበረከቱት ልዩ ልዩ አስተዋጽዖ አቶ ዳንኤል በኰሚቴው ስም መንፈሳዊ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

DSCN9585

የጠቅላላ ጉባኤው ዐቢይ ኰሚቴ አባላት

በመጨረሻም የማኅበሩ ሰብሳቢ የማጠቃለያ ንግግር ሲያደርጉ በመጀመሪያ ጉባኤው በሰላም ተጀምሮ በሰላም እንዲፈጸም ያደረገውን ልዑል እግዚአብሔርን አመስግነው ለ፲፫ኛው ጉባኤ በሰላም እንዲያደርሳቸው መልካም ምኞታቸውን ከገለጹ በኋላ በጠቅላላ ጉባኤው ለተገኙ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ለተጋባዥ እንግዶችና ከመላው ዓለም ለመጡ የጉባኤው ተሳታፊዎች፤ እንደዚሁም አዳራሹን ለፈቀደው ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፣ ጠቅላላ ጉባኤው በአግባቡ እንዲከናወን ላደረገው ለዐቢይ ኰሚቴውና ለጉባኤው መሳካት ልዩ ልዩ ድጋፍ ላደረጉ አካላት ኹሉ በማኅበሩ ስም መንፈሳዊ ምስጋናቸውን ካቀረቡ በኋላ ከምሽቱ 7፡30 በአባቶች ጸሎት ፲፪ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ተፈጸሟል፡፡ ተሳታፊዎችም በከበሮና በጭብጨባ ‹‹ንሴብሖ ለእግዚአብሔር ስቡሐ ዘተሰብሐ›› እያሉ ጉባኤውን እግዚአብሔርን በዝማሬ አመስግነዋል፡፡

DSCN9588

በአጠቃላይ ለሦስት ቀናት የተካሔደው የማኅበረ ቅዱሳን ፲፪ኛው ጠቅላላ ጉባኤ የእግዚአብሔር ጥበቃ ያልተለየው ጉባኤ ነበር፤ ማለትም ማኅበሩ የጉባኤውን ተሳታፊዎች የሚጠብቅ ኃይል አላሰማራም፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በቅዱሳን መላእክት ተራዳኢነት ያለምንም መሰናክል በሰላም ሊጠናቀቅ ችሏል፡፡ ይህ ጉባኤ ከዚህ በፊት ከተካሔዱት ጉባኤያቱ በተለየ መልኩ ብፁዓን አበው የተገኙበት፤ በርካታ የጠቅላይ ቤተ ክህነት መምሪያ ሓላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የተሳተፉበት፤ ብዙ ቁም ነገሮች የተዳሰሱበትና አባላቱ የተደሰቱበት ልዩ ጉባኤ ነበር፡፡ ጠቅላላ ጉባኤው ውበት እንደኖረው ካደረጉት ነጥቦች መካከል እርስበርስ መደማመጥ፣ የተሳታፊዎቹ የነቃ ተሳትፎና ትሕትና፣ የአንድነት መንፈስና የምልዓተ ጉባኤው ጥንቃቄ የተሞላበት ውሳኔ ዋነኞቹ ሲኾኑ ለጉባኤው አስደሳች ክሥተት ከኾኑት መርሐ ግብራት ደግሞ በዘመናዊው ትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት አስመዝግበው የተሸለሙ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ሜዳልያዎቻቸውን ለማኅበሩ ማስረከባቸው አንደኛው ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ፲፪ኛው ጠቅላላ ጉባኤ እየተካሔደ ነው

ነሐሴ ፳፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የማኅበረ ቅዱሳን ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ከነሐሴ ፳፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽና በማኅበሩ ሕንጻ እየተካሔደ ነው፡፡

DSCN8874

ብፁዕ አቡነ ገብርኤል እና ብፁዕ አቡነ እንጦንስ

በጠቅላላ ጉባኤው መክፈቻ ዕለት ነሐሴ ፳፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፣ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የየመምሪያ ሓላፊዎች፣ ከአገር ውስጥና ከውጪ አገር ማእከላትና ወረዳ ማእከላት የመጡ የማኅበረ ቅዱሳን አመራር አባላት፣ የግቢ ጉባኤያት ተወካዮችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል፡፡

3

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

5

ጠቅላላ ጉባኤው በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጸሎት ከተከፈተበት ጊዜ ጀምሮ በቀኑ መርሐ ግብር በጠቅላይ ቤተ ክህነት፤ ማታ ደግሞ በማኅበሩ ሕንጻ በከፍተኛ ተሳትፎ በመከናወን ላይ የሚገኝ ሲኾን በጉባኤውም የማኅበሩ የሁለት ዓመታት አጠቃላይ የአገልግሎት ዕቅድ አፈጻጸምና የኦዲትና ኢንስፔክሽን ሪፖርቶች ቀርበው ጉባኤው ተወያይቶባቸዋል፡፡ እንደዚሁም ልዩ ልዩ ጥናታዊ ጽሑፎች በባለሙያዎች ቀርበዋል፡፡

DSCN9433

የሥራ አመራር አባላት ዕጣ በብፁዕ አቡነ ሉቃስ ሲወጣ

በዛሬው ዕለትም የማኅበሩ ቀጣይ ስልታዊ ዕቅድ በተሳታፊዎች የቡድን ውይይት ተደርጎበታል፡፡ በመቀጠልም በሚቀጥሉት አራት ዓመታት ማኅበሩን የሚመሩ የሥራ አመራር አባላት በምልዓተ ጉባኤው በተሰየመው አስመራጭ ኰሚቴ አቅራቢነት በብፁዕ አቡነ ሉቃስ ቡራኬ በጸሎትና በዕጣ ተመርጠዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ፲፪ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ዛሬ ምሽት የሚጠናቀቅ ሲኾን ሙሉ ዘገባውንም በሌላ ዝግጅት ይዘን እንቀርባለን፡፡

የአዳማ ማእከል ለአባቶች የዓቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ሰጠ

ነሐሴ ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአዳማ ማእከል

Adama

አባቶች በሥልጠና ላይ

በማኅበረ ቅዱሳን አዳማ ማእከል ከምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት፣ ከሙያ አገልግሎትና ዓቅም ማጐልበቻ ዋና ክፍል ጋር በመተባበር ለሀገረ ስብከቱ የየመምሪያ ሓላፊዎች፣ ለወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጆች፣ ለገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች በአጠቃላይ ፵ ለሚኾኑ አባቶች ከነሐሴ ፳፩-፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለሁለት ቀናት በሀገረ ስብከቱ የመሰብሰቢያ አዳራሽ የዓቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ሰጠ፡፡

በሥልጠናውም የሥራ አመራር ጥበብ፤ የውሳኔ አሰጣጥና የግጭት አፈታት ዘዴ፤ ሕግጋተ ቤተ ክርስቲያንና ቃለ ዓዋዲ ከሥራ አመራር አንጻር፤ እንደዚሁም የፋይናንስ አስተዳደርና ሒሳብ አያያዝ የሚሉ አርእስት የተካተቱ ሲኾን በተጨማሪም የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴን የተመለከተ የግንዛቤ ማስጨበጫ ገለጻ ለሠልጣኞቹ ተደርጎላቸዋል፡፡

በሥልጠናው ማጠናቀቂያ መርሐ ግብር ላይ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት ሥልጠናው ልምድ ባላቸው ባለሙያዎች መሰጠቱን አድንቀው ሥልጠናውን ያዘጋጀውን ማኅበረ ቅዱሳንን ካመሰገኑ በኋላ ‹‹ያገኛችሁትን ዕውቀት በተግባር ላይ በማዋል ብቁና ዘመናዊ አሠራርን የተላበሰ የሓላፊነት ሥራችሁን እንድትወጡ›› ሲሉ ለሠልጣኞቹ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

የሥልጠናው ተሳታፊዎች በበኩላቸው ‹‹የወሰድነው ሥልጠና መንፈሳዊውን አስተዳደር ከዘመናዊ የሥራ አመራር ጥበብ ጋር በማጣጣም ቤተ ክርስቲያናችንን በአግባቡ ማገልገል እንደምንችል የተረዳንበት ሥልጠና ነው፡፡ በተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ ዙሪያ የተሰጠው የግንዛቤ ማስጨበጫ ገለጻም ቤተ ክርስቲያናችንን ነቅተን እንድንጠብቅና የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱን በስፋት ለማዳረስ እንድንፋጠን አድርጎናል›› ብለዋል፡፡

የአዳማ ማእከል ሰብሳቢ መ/ር ጌትነት ዐሥራት ደግሞ ለቤተ ክርስቲያን ኹለንተናዊ ዕድገት በአንድነት ማገልገል የሚኖረውን ጠቀሜታ በመጥቀስ ማኅበሩ የራሳቸው መኾኑን ተገንዝበው በሚያስፈልገው ኹሉ ከማኅበሩ ጎን እንዲቆሙ፤ በምክርና በዐሳብም ድጋፍ እንዲያደርጉ አባቶችን አሳስበዋል፡፡

በመጨረሻም ለሥልጠናው መሳካት አስተዋጽዖና ድጋፍ ላደረጉት ለሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ለብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፤ ለሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነትና የየመምሪያ ሓላፊዎች፤ ለወረዳ ቤተ ክህነት፣ ለአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፤ እንደዚሁም ለአሠልጣኞችና ለበጎ አድራጊ ምእመናን መ/ር ጌትነት መንፈሳዊ ምስጋናቸውን በማኅበሩ ስም አቅርበዋል፡፡

ዐውደ ርእዩን በርካታ ምእመናን ጐበኙት

ነሐሴ ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአሜሪካ ማእከል

Mini 3

ዐውደ ርእዩ በአባቶች ቡራኬ ሲከፈት

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን በሚኒያ ፖሊስ ንዑስ ማእከል አዘጋጅነት ‹‹ማዕዶት ዘቤተ ጉባኤ ወገዳማት›› በሚል መሪ ቃል ከነሐሴ ፯-፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በሚኒያ ፖሊስ  ርእሰ አድባራት ጽርሐ አርያም ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ቅፅር ውስጥ የተካሔደውን ዐውደ ርእይ በርካታ ምእመናን እንደ ጐበኙት የሚኒያ ፖሊስ ንዑስ ማእከል አስታወቀ።

በዐውደ ርእዩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንና የገዳማት ታሪክ፣ የአብነት ትምህርት ቤቶች ሥርዓተ ትምህርትና ችግሮቶች፣ የደቀ መዛሙርቱ የኑሮ ኹኔታ፣ ማኅበሩ በገዳማትና በአብነት ት/ቤቶች ላይ እየሰጠው ያለው አገልግሎትና የተመዘገቡ ውጤቶች፣ እንደዚሁም ወደፊት ምእመናን ምን ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው የሚያስገነዝቡ ነጥቦች በ፰ ክፍላተ ትዕይንት ተከፋፍለው ቀርበውበታል፡፡

ዐውደ ርእዩ በሚኒያ ፖሊስ ርእሰ አድባራት ጽርሐ አርያም ቅድስት ሥላሴ ካቴድራልና የሴንት ፖል ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪዎች መልአከ አርያም ቆሞስ አባ ኃይለ ሚካኤል ሙላት እና መልአከ ገነት ቆሞስ አባ ዘርዐ ዳዊት ብርሃኔን ጨምሮ በአጥቢያዎቹ አገልጋይ ካህናትና ዲያቆናትም ተጐብኝቷል፡፡

Mini 4

ካህናትና ዲያቆናት የአብነት ሥርዓተ ትምህርትን ሲያሳዩ

የሚኒያ ፖሊስ ቅድስት ሥላሴ ካህናትና ዲያቆናት የአብነት ት/ት አሰጣጥ ሒደትን በክውን ትዕይንት መልክ ማቅረባቸው ለዐውደ ርእዩ ድምቀት ከመስጠቱ ባሻገር የቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንት በምን ዓይነት ሥርዓተ ት/ት አልፈው ለማዕረግ እንደሚደርሱ ጐብኚዎቹ ግንዛቤ እንዲኖራቸው አድርጓል፡፡

Mini

የዐውደ ርእዩ ጐብኚዎች በከፊል

ከጐብኚዎቹ መካከልም ጥቂት የማይባሉ ምእመናን በዐውደ ርእዩ መዘጋጀት የተሰማቸውን ደስታ በዕንባ ሲገልጹ የታዩ ሲኾን በአስተያየቶቻቸውም ማኅበሩ በየአገሩ እንደዚህ ዓይነት አስተማሪነት ያላቸውን መርሐ ግብራት ደጋግሞ እንዲያቀርብ አሳስበው ለዚህም የሚያስፈልገውን ኹሉ ድጋፍ ለማድረግ ፈቃደኛ መኾናቸውን ገልጸዋል፡፡

በመጨረሻም ለዐውደ ርእዩ መሳካት በገለጻ፣ በማስተባበርና ድጋፍ በማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያበረከቱ አባቶችን፣ የሰበካ ጉባኤ አመራሮችን፣ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችንና በጎ አድራጊ ምእመናንን ንዑስ ማእከሉ በማኅበረ ቅዱሳን ስም መንፈሳዊ ምስጋናውን አቅርቧል፡፡

የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ተተኪ መምህራንን አስመረቀ

ነሐሴ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በሐዋሳ ማእከል

Hawasa

በማኅበረ ቅዱሳን የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ከልዩ ልዩ ግቢ ጉባኤያት በመመልመል ለአንድ ወር ያሠለጠናቸውን ፶፮ የደረጃ ሁለት ተተኪ መምህራን የሲዳማ፣ ጌድዮ፣ አማሮና ቡርጂ አህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ፣ የሐዋሳ ማእከል አባላት፣ የቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምእመናን በተገኙበት በሐዋሳ ደብረ ታቦር ቅዱስ ሩፋኤል የካህናት ማሠልጠኛ ተቋም ነሐሴ ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም አስመረቀ፡፡

በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ጉባኤ አባ ሀብተ ማርያም ‹‹እግዚአብሔር የላከው የእግዚአብሔርን ቃል ይናገራል›› /ዮሐ.፫፥ ፴፬ / በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡

የዋናው ማእከል ተወካይ ዲ/ን ሙሉጌታ  ኃይለ ማርያም ባስተላለፉት መልእክት ምሩቃኑ ለአገልግሎት እንዲተጉና የተጣለባቸውን አደራ በትጋት እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

ሠልጣኞቹ ከወሰዷቸው ኮርሶች መካከል ትምህርተ ሃይማኖት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ሥርዓትና ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን፣ ነገረ ቅዱሳን፣ ትምህርተ ክርስትና፣ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር፣ ሐዋርያዊ ተልእኮ፣ ትምህርተ አበው፣ ነገረ ማርያምና ኦርቶዶክሳዊ የጾታ ትምህርት የሚገኙ ሲኾን በተጨማሪም ስለ ኦርቶዶክሳውያን መዝሙራትና ሐራ ጥቃዎች በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ላይ እያደረሱት ያለውን የተሐድሶ እንቅስቃሴ የሚመለከት የግንዛቤ ማስጨበጫ ገለጻ ተደርጎላቸዋል፡፡

ሚዲያ ክፍላችን ያነጋገራቸው አንዳድ ምሩቃን በሥልጠናው ጠቃሚ ዕውቀት እንደቀሰሙበትና በርካታ ቁም ነገሮችን እንዳገኙበት ገልጸው ለወደፊቱም ‹‹የየማእከላቱ ክትትልና ድጋፍ እንዳይለየን›› ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

በመጨረሻም የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ሓላፊ አቶ ዘሪሁን ከበደ የሀገረ ስብከቱን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ገብርኤልን፣ የሀገረ ስብከቱና የወረዳ ቤተ ክህነቱ ሓላፊዎችን፣ የሐዋሳ ደብረ ታቦር ቅዱስ ሩፋኤል አስተደዳሪና ካህናትን፣ መምህራንን እንደዚሁም ሥልጠናው እንዲሳካ ልዩ ልዩ ድጋፍ ያደረጉ አካላትን በማኅበሩ ስም ካመሰገኑ በኋላ መርሐ ግብሩ በአባቶች ጸሎት ተጠናቋል፡፡

በጥናትና ምርምር ማእከል አዘጋጅነት የጥናት ጉባኤ ተካሔደ

ነሐሴ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በካሣኹን ለምለሙ

DSCN8791

የጉባኤው ተሳታዎች በከፊል

በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል አዘጋጅነት ‹‹ጥናትና ምርምር ለቤተ ክርስቲያን ኹለንተናዊ አገልግሎት መጠናከር›› በሚል መሪ ቃል ፰ኛው ዓመታዊ የጥናት ጉባኤ ከነሐሴ ፳፩-፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በማኅበሩ ሕንጻ ፫ኛ ፎቅ አዳራሽ ተካሔደ፡፡

በጉባኤው ከቀረቡት ጥናቶች መካከልም ‹‹በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች የአስኳላ ትምህርት መማር አስፈላጊነት››፤ ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ ፍርድ ቤቶች የማቋቋም ሒደት›› እና ‹‹የግእዝ ቋንቋ ለኢትዮጵያ ቋንቋዎች ዕድገት ያበረከተው አስተዋጽዖ› የሚሉት ርእሰ ጉዳዮች ይገኙባቸዋል፡፡

DSCN8844

‹‹የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች የአስኳላ ትምህርት የመማር አስፈላጊነት›› በሚል ርእስ በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል የተዘጋጀውን ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡት የክፍሉ አባል የኾኑት አቶ ጌትነት ለወየው የአብነት ተማሪዎች ዘመናዊውን ትምህርት ቢማሩ ለቤተ ክርስቲያን ከሚሰጡት ውጤታማ አገልግሎት ባሻገር በታማኝነትና በሓላፊነት ከሙስና የጻዳ ሥራ በመሥራት ለአገር ዕድገትም የሚኖራቸው ኹለንተናዊ አስተዋጽዖ ከፍተኛ መኾኑን በጥናታቸው አመላክተዋል፡፡

DSCN8805

‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ ፍርድ ቤቶች የማቋቋም ሒደት›› በሚለው ርእስ ላይ ጥናት ያቀረቡት ጠበቃና የሕግ አማካሪ ዲ/ን ፊልጶስ ዓይናለም በበኩላቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአሁኑ ወቅት መንፈሳዊና ማኅበራዊ ግዴታዋን ከመወጣት አንጻር ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነች እንደምትገኝ ጠቅሰው በሥሯ የሚገኙ አገልጋዮችንና ምእመናንን ለማስተዳደር ያመች ዘንድ የራሷ የኾነ መደበኛ መንፈሳዊ ፍርድ ቤት ሊኖራት እንደሚገባ አስረድተዋል፡፡

‹‹የግእዝ ቋንቋ ለኢትዮጵያ ቋንቋዎች ዕድገት ያበረከተው አስተዋጽዖ›› በሚል ርእሰ ጉዳይ ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የባህልና ቋንቋዎች አካዳሚ ሓላፊና የሥነ ልሳን ረዳት ፕሮፌሰር ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም ደግሞ የግእዝ ቋንቋ ጥንታዊ መኾኑና በፊደል ቀረፃ፣ በትርጕም ሥራ፣ በቃላት ስያሜ፣ በመዝገበ ቃላት አገልግሎትና በመሳሰሉት ዘርፎች ለሌሎች ቋንቋዎች ሥነ ጽሑፍ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ማበርከቱ በኢትዮጵያ ከሚገኙ ቋንቋዎች ልዩ እንደሚያደርገው ተናግረዋል፡፡

በጥናት ጉባኤው ‹‹የክርስቶስ የማዳን ትምህርት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አማኞች ዘንድ ያለው ግንዛቤና የቅዱሳት መጻሕፍት ምስክርነት››፤ ‹‹አውጣኪ፣ ቅዱስ ዲዮስቆሮስና የኬልቄዶን ጉባኤ››፤ ‹‹የመጽሐፈ መዋሥዕት ይዘት ትንታኔ››፤ ‹‹ባሕረ ሐሳብ ጥንታዊው የኢትዮጵያውያን ትምህርት፣ በዘመን አቈጣጠር፣ በሥነ ከዋክብት ጥናትና በአየር ትንበያ›› በሚሉ ርእሰ ጉዳዮችም በዘርፉ ምሁራን ተመሳሳይ ጥናቶች ቀርበው ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

በመጨረሻም የመርሐ ግብሩ ተሳታፊዎች ላነሧቸው ልዩ ልዩ ጥያቄዎችና አስተያየቶች በጥናት አቅራቢዎቹ ምላሾች ከተሰጡ በኋላ የጥናት ጉባኤው በጸሎት ተፈጽሟል፡፡

ብፁዕ ሥራ አስኪያጁ የአንድነት ኑሮውን አበረታቱ

ነሐሴ ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

IMG_0049

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ

‹‹ለቤተ ክርስቲያናችን ንዋያተ ቅድሳትን ብቻ ሳይኾን ሰውም እንስጥ›› በሚለው መሪ ቃሉ የሚታወቀው ጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ የአንድነት ኑሮ ማኅበር ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ካህናትና በርካታ ምእመናን በተገኙበት ነሐሴ ፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ስብከተ ወንጌል አዳራሽ የገቢ ማሰባሰቢያ ጉባኤ አካሒዷል፡፡

በዕለቱ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ በክልል ትግራይ ደቡባዊ ዞን ማይጨው፣ ደቡባዊ ምሥራቅ ትግራይና የምሥራቃዊ ዞን አዲግራት አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የአንድነት ኑሮው ከየብሔረሰቡ የተውጣጣጡ ሰባክያንን በማሠልጠን ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት የሚያደርገውን አስተዋጽዖ አድንቀው ‹‹በዚህ አገልግሎታችሁ በርቱ፤ እኛም ከጎናችሁ ነን›› ሲሉ የአንድነት ኑሮውን አበረታተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሰላማ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በበኩላቸው ‹‹እግዚአብሔር ንጹሕ ልብ፣ ንጹሕ ሰውነት ይፈልጋልና በንጽሕና ኾናችሁ እንድታገለግሉ እግዚአብሔር ይርዳችሁ፤ ማኅበራችሁን ያስፋላችሁ›› የሚል አባታዊ ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡

IMG_0073

ብፁዕ አቡነ ሰላማ

በተመሳሳይ መልኩ የምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ኅሩያን ቀሲስ ታምሩ እሸቱ የሀገረ ስብከቱን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስን ወክለው ‹‹እኛም ከጎናችሁ ኾነን የምንችለውን ኹሉ እናደርጋለን›› ብለዋል፡፡

በዕለቱ በቀሲስ እሸቱ ታደሰና በዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ ትምህርተ ወንጌል የተሰጠ ሲኾን፣ በተጨማሪም የገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሰንበት ት/ቤትና የአንድነት ኑሮው መዘምራን፣ እንደዚሁም የአንድነት ኑሮው ሠልጣኞች ያሬዳውያን ዝማሬያትን አቅርበዋል፡፡

በመቀጠልም የአንድነት ኑሮው መግለጫ በስብከተ ወንጌል ሥልጠና ኰሚቴው አባል በአቶ ማናየ አባተ የቀረበ ሲኾን በመግለጫውም ከአዲስ አበባ ከተማ በ፻፶ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኝ የገጠር ቤተ ክርስቲያን ቆመው መሔድ የማይቻላቸው ካህን ታቦቱን አክብረው፤ ሌላ ጐልማሳ ደግሞ እርሳቸውን ተሸክሟቸው በበዓለ ጥምቀት ወደ ባሕረ ጥምቀት ሲወርዱ መታየታቸውን አስመልክቶ የቀረበው ዘገባ የጉባኤውን ተሳታፊዎች ያሳዘነ ነበር፡፡

IMG_0046

የጉባኤው ተሳፊዎች በከፊል

‹‹የአንድነት ኑሮው ዓላማና ተልእኮ ከመላው የኢትዮጵያ ክፍሎች የተውጣጡ በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ማስተማር የሚችሉ ሰባክያነ ወንጌልን በማሠልጠን ወንጌልን ማዳረስና የአብነት ትምህርት በማስተማር በአገልጋይ ካህን እጦት ምክንያት የተዘጉ አብያተ ክርስቲያናት አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ ነው›› ያሉት የቦርድ ሰብሳቢው ዲያቆን ሙሉጌታ ምትኩ የጉባኤው ዓላማም ለዚህ አገልግሎት ማስፈጸሚያ የሚውል ገንዘብ ለማሰባሰብ መኾኑን አስታውቀዋል፡፡ አክለውም ኹሉም ሕዝበ ክርስቲያን ከአንድነት ኑሮው ጋር በመኾን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መጠናከር የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ሰላማ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ የጉባኤው ፍጻሜ ኾኗል፡፡

‹‹ትርጓሜ ያሐዩ›› በሚል ኃይለ ቃል የውይይት መርሐ ግብር ተካሔደ

ነሐሴ ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዝግጅት ክፍሉ

በማበኅረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አዘጋጅነት ‹‹ትርጓሜ ያሐዩ፤ ትርጓሜ ያድናል›› በሚል ኃይለ ቃል ነሐሴ ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በግዮን ሆቴል ብሉ ሳሎን አዳራሽ የውይይት መርሐ ግብር ተካሔደ፡፡

IMG_0012

የመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች በከፊል

በመርሐ ግብሩ ላይ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የመንግሥት ባለ ሥልጣናት፣ የዩኒቨርሲቲ መምህራን፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎችና ጥሪ የተደረገላቸው ምእመናን የተገኙ ሲኾን የዋና ክፍሉ ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት ለተሳታፊዎች የእንኳን ደኅና መጣችሁ ንግግር ባደረጉበት ወቅት የመርሐ ግብሩ ዓላማ የመጻሕፍት ትርጓሜ ቤቶችን አስተዋጽዖ በማስገንዘብ ጉባኤ ቤቶችን ለማስፋፋትና ተተኪ ሊቃውንትን ለማፍራት የሚያስችል ግንዛቤ ለማስጨበጥ መኾኑን አስታውቀዋል፡፡

IMG_0002

ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ ሐዲስ

በዕለቱ የጎንደር መንበረ መንግሥት መድኀኔ ዓለም የአራቱ ጉባኤያት ምስክር መምህርና የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ ሐዲስ በአንድምታ ትርጕም ያዘጋጇቸው ትንቢተ ኢሳይያስ፣ ሃይማኖተ አበውና ድርሳነ ቄርሎስ ወጰላድዮስ ምስለ ተረፈ ቄርሎስ ተመርቀዋል፡፡

ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ መጻሕፍቱ ለጉባኤ ቤት መምህራንና ለደቀ መዛሙርት እንደዚሁም ለምእመናን የሚኖራቸው ጠቀሜታ የጎላ መኾኑን ጠቅሰው ‹‹መጻሕፍቱ በስሜ ቢዘጋጁም የመጻሕፍቱ ባለቤት ግን ጉባኤ ቤቱ ነው እንጂ እኔ አይደለሁም›› ብለዋል፡፡ ከመጻሕፍቱ ሽያጭ የሚገኘውም ገቢም ሙሉ በሙሉ ለጉባኤ ቤታቸው መኾኑን ተናግረዋል፡፡

በተጨማሪም በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤልና በዲያቆን ያረጋል አበጋዝ የትርጓሜ መጻሕፍትን ትውፊትና አስተዋጽዖ የሚዳስስ ጥናታዊ ጽሑፍ፤ እንደዚሁም የትርጓሜ መጻሕፍትን ታሪካዊ አመጣጥና የጉባኤ ቤቶችን ችግር የሚያስቃኝ ዘጋቢ ፊልም ከቀረበ በኋላ ሊቃውንቱንና ተጋባዥ እንግዶችን ያሳተፈ ጠቃሚ ውይይት ተካሒዷል፡፡

ከሰዓት በኋላ በዮድ አቢሲንያ የምግብ አዳራሽ በቀጠለው የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብርም ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ ‹‹የታቦር ጉባኤ›› በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል የሰጡ ሲኾን በትምህርታቸውም ከደብረ ታቦር ምሳሌዎች አንደኛው የመጻሕፍት ትርጓሜ ጉባኤ ቤት መኾኑን አስረድተዋል፡፡

IMG_0037

በዮድ አቢሲንያ አዳራሽ የተገኙ ሊቃውንትና ምእመናን በከፊል

ሊቀ ሊቃውንት በመቀጠልም የጎንደር መንበረ መንግሥት መድኀኔ ዓለም የትርጓሜ መጻሕፍት ምስክር ቤት ደቀ መዛሙርትን እያስተማረ የሚገኘው በመቃብር ቤት መኾኑ ለሥርዓተ ትምህርቱ መሰናክል እንደ ኾነባቸው ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም ለጉባኤ ቤቱ አገልግሎት የሚሰጥ ኹለ ገብ ዘመናዊ ሕንጻ በጎንደር ከተማ ለመገንባት በ፳፻፰ ዓ.ም የመሠረት ድንጋይ ቢቀመጥም በገንዘብ እጥረት ምክንያት ሕንጻው እስከ አሁን ድረስ አለመገንባቱን አስታውሰው ይህን ሕንጻ ለመገንባት መላው ሕዝበ ክርስቲያን ከጎናቸው እንዲቆም ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በመጨረሻም በአባቶች ጸሎት የውይይት መርሐ ግብሩ ተፈጸሟል፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ፳፰ ቤቶቿን አስመለሰች

ነሐሴ ፳ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

DSCN8710

መጋቤ ካህናት ኃይለ ሥላሴ ዘማርያም

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በራሷ ወጪ ካስገነባቻቸውና በደርግ ዘመነ መንግሥት በግፍ ከተወረሱባት በርካታ ቤቶቿ መካከል ፳፰ቱን ማስመለሷን የሕንጻዎችና ቤቶች አስመላሽ ኰሚቴ ሰብሳቢ አስታወቁ፡፡

በጠቅላይ ቤተ ክህነት የካህናት አስተዳደር መምሪያ ሓላፊ፣ የሕንጻዎችና ቤቶች አስመላሽ ኰሚቴ ሰብሳቢ መጋቤ ካህናት ኃይለ ሥላሴ ዘማርያም ለዝግጅት ክፍላችን እንደ ገለጹት አስመላሽ ኰሚቴው ባደረገው ያለሰለሰ ጥረት በሦስት ክፍለ ከተሞች ማለትም በልደታ ፲፰፤ በየካ ፭ እና በቂርቆስ ፭ በድምሩ ፳፰ ቤቶች ነሐሴ ፲፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለባለንብረቷ ለቤተ ክርስቲያን መመለሳቸው ተረጋግጧል፡፡

አስመላሽ ኰሚቴው ባደረገው የማጣራት ሥራ በአዲስ አበባ ከተማ በየክፍለ ከተሞች በደርግ መንግሥት እንደ ተወረሱ የቀሩ ሁለት መቶ ሰማንያ ሦስት ሕንጻዎችና ቤቶች እንደሚገኙ፤ ከእነዚህ መካከልም አንድ መቶ ሠላሳ ሰባቱ ሕጋዊ ማረጋገጫ እንደ ተገኘላቸው የጠቆሙት የኰሚቴው ሰብሳቢ በአሁኑ ሰዓት ፳፰ቱ ቤቶች መመለሳቸውን አድንቀው ቀሪዎቹ አንድ መቶ ዘጠኙ ደግሞ እስከ ነሐሴ ወር ፳፻፰ ዓ.ም መጨረሻ ድረስ ተመላሽ እንደሚኾኑ ጠቁመዋል፡፡

ለወደፊቱም ኹሉም ሕንፃዎችና ቤቶች ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲመለሱ ለማድረግ አስመላሽ ኰሚቴው ተግቶ እየሠራ መኾኑን ያስገነዘቡት ሰብሳቢው የተወረሱ ሕንፃዎችንና ቤቶችን ወደ ቤተ ክርስቲያን ለማስመለስ በሚደረገው ጥረት ልዩ ልዩ አስተዋጽዖ ላበረከቱ አካላት ኹሉ በቤተ ክርስቲያንና በአስመላሽ ኰሚቴው ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

በተያያዘ ዜና በዐሥር ሚሊዮን ዐርባ ዘጠኝ ሺሕ ብር ወጪ የተገዙ ዐሥር ዘመናዊ መኪኖች ሥራ መጀመራቸውን መጋቤ ካህናት ኃይለ ሥላሴ ዘማርያም ለዝግጅት ክፍላችን ተናግረዋል፡፡

የመኪኖቹ ሙሉ ወጪ የቤተ ክርስቲያኗ መኾኑን የጠቀሱት መጋቤ ካህናት ዐሥሩም መኪኖች የመጓጓዣ እጥረት ላለባቸው አህጉረ ስብከትና የጠቅላይ ቤተ ክህነት መምሪያዎች አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጋቸውን አስታውሰው መኪኖቹ በአፋጣኝ ሥራ እንዲጀምሩ መደረጉም የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ከዚህ ቀደሙ በተሻለ ኹኔታ እንዲከናወን ያደርጋል ብለዋል፡፡

በመጨረሻም መኪኖቹ በፍጥነት ወደ አገር ውስጥ እንዲገቡ ድጋፍ ላደረጉ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች መጋቤ ካህናት ኃይለ ሥላሴ በቤተ ክርስቲያኗ ስም ምስጋናቸውን ካቀረቡ በኋላ ለወደፊቱ ቤተ ክርስቲያን ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት ለምታከናውናቸው ተግባራትና ንብረቶቿን ለማስመለስ ለምታደርጋቸው እንቅስቃሴዎች ውጤታማነት ‹‹መላው ሕዝበ ክርስቲያን በጸሎታቸውና በዐሳባቸው ድጋፍ ሊያደርጉ ይገባል›› ሲሉ ለምእመናን ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ሕገ ቤተ ክርስቲያንን ማወቅ የችግሮች መፍትሔ መኾኑን ብፁዕ ሥራ አስኪያጁ ገለጡ

ነሐሴ ፲፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ዮሴፍ ይኵኖአምላክ

አቡነ ዲዮስቆሮስ

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ በክልል ትግራይ ደቡባዊ ዞን ማይጨው፣ ደቡባዊ ምሥራቅ ትግራይና የምሥራቃዊ ዞን አዲግራት አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ መመሪያዎችንና ደንቦችን ባለመረዳት በየጊዜው የሚፈጠሩ ችግሮችን ለማስወገድ ሕገ ቤተ ክርስቲያንን ማወቅ፣ ዐውቆም በተግባር ላይ ማዋል እንደሚገባ ገለጡ፡፡

ብፁዕ ሥራ አስኪያጁ ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል በጽ/ቤታቸው በሰጡት ቃለ መጠይቅ የካህናትና የምእመናን ድርሻ ምን መኾን እንዳለበት በቃለ ዐዋዲው በግልጽ መሥፈሩን አስታውቀው ‹‹ኹሉም ሕዝበ ክርስቲያን ክርስቲያናዊ መብትና ግዴታውን ዐውቆ እናት ቤተ ክርስቲያንን በፍቅር በማገልገል መንፈሳዊ አደራውን ሊወጣ ይገባል›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡

ከዚሁ ኹሉ ጋርም በኢትዮጵያውያን ምእመናን መካከል ለረጅም ጊዜ ተጠብቆ የቆየው እርስ በርስ የመፈቃቀርና የመደጋገፍ ባህል ለተከታዩ ትውልድ እንዲሻገር የኹሉንም ትኩረት እንደሚሻ ጠቅሰው ‹‹በቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርት የታነጸው በጎ ሥርዓት በዘመን አመጣሽ ጎጂ ልማዶች እንዳይበከል ተግተን ልንሠራ ይገባል›› ብለዋል፡፡

‹‹ኢትዮጵያዊው ባህል አብሮ መብላት መጠጣት ብቻ ሳይኾን በችግርና በደስታ ጊዜ በአብሮነት መኖር ነው›› ያሉት ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ የአብሮነት ትሥሥሩን ከሚያጠፉ የባህል ወረራዎች ምእመናኑ ራሳቸውን መጠበቅ እንዳለባቸውም አሳስበዋል፡፡

በመጨረሻም የእምነት ወረራ በከፍተኛ ደረጃ እየተስፋፋ መኾኑን ያስታወሱት ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ‹‹ምእመናንን ከነጣቂ ተኩላዎች ለመከላከል በስብከተ ወንጌል አገልግሎት የተጠናከረ ሥራ መሠራት አለበት›› በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ በልዩ ልዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ለዝግጅት ክፍላችን የሰጡትን ሙሉ ቃለ መጠይቅ ከነሐሴ ፩-፲፭ ቀን እና ከ፲፮-፴ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በሚታተመው የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ በቤተ አብርሃም ዓምድ ትከታተሉ ዘንድ ከወዲሁ እንጋብዛለን፡፡