የሕንዱ ፓትርያርክ የመስቀል በዓልን በአዲስ አበባ አከበሩ
በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው
መስከረም ፲፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም
የሕንድ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ማርቶማ ጳውሎስ ካልዕ የመስቀል ደመራ በዓልን በአዲስ አበባ ከተማ በመስቀል ዐደባባይ አከበሩ፡፡
ቅዱስነታቸው በዓለ መስቀልን በአዲስ አበባ ያከበሩት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ያቀረቡላቸውን መንፈሳዊ ግብዣ ተቀብለው ነው፡፡
ፓትርያርኩ በዕለቱ በሰጡት ቃለ ምዕዳን ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በቀረበላቸው መንፈሳዊ ጥሪ መሠረት ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ሐዋርያዊ ጉብኝት በማድረጋቸውና በዓለ መስቀልን በአዲስ አበባ ከተማ በማክበራቸው መላው የሕንድ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ምእመናን እንደተባረኩ፣ በዚህም ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል፡፡
መስቀልን ማክበር ማለት ራስን መፈለግና የመስቀሉን ክብር ከፍ ከፍ ማድረግ ማለት እንደኾነ የጠቀሱት ቅዱስነታቸው ኢትዮጵያውያን ምእመናን በመንፈሳዊ ሥርዓት ብቻ ሳይኾን በሕይወታቸው ጭምር የመስቀሉን ክብር እንደሚገልጹት መስክረዋል፡፡
የኢትዮጵያ የመስቀል በዓል አከባበር ሥርዓት በዓለም አቀፉ የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት በቅርስነት በመመዝገቡ መደሰታቸውንም ተናግረዋል፡፡
መላው ሕዝበ ክርስቲያን ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራውን ወደፈጸመበት መስቀል ሊመለከት እንደሚገባው ያስረዱት ቅዱስነታቸው በመልእክታቸው ማጠቃለያም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ለመላው ምእመናን አባታዊ ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡
በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው የሕንድ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከአምስቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት አንዷ ስትኾን፣ በርካታ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሰባክያነ ወንጌልና ካህናት እንደዚሁም ወደሦስት ሚሊዮን የሚደርሱ ምእመናን እንዳሏትና ሠላሳ በሚኾኑ አህጉረ ስብከቷ ሐዋርያዊ ተልእኮዋን በመወጣት ላይ እንደምትገኝ ታሪኳ ያስረዳል፡፡
በ፳፻፲ ዓ.ም የሚከበረውን በዓለ መስቀል በማስመልከት በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በተዘጋጀው ልዩ ዕትም መጽሔት በገጽ 12 – 13 እንደተጠቀሰው፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ማርቶማ ጳውሎስ ካልዕ በሕንድ ምሥራቅና ማላንካራ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በቅዱስ ቶማስ መንበረ ፓትርያርክ ሰባተኛውን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማርቶማ ዲዲሞስ ቀዳማዊን በመተካት ከስምንት ዓመታት በፊት ስምንተኛው ፓትርያርክ ኾነው ተሹመዋል፡፡
በዘመነ ፓትርያርክነታቸውም ሐዋርያዊ ጉብኝት በማድረግ በኦሪየንታል አኃት አብያተ ክርስቲያናት መካከል ያለው ሃይማኖታዊ ግንኙነት እንዲጠናከር ከፍ ያለ መንፈሳዊ ተግባር በመፈጸም ላይ ይገኛሉ፡፡
ቅዱስነታቸው መስከረም ፲፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ወደኢትዮጵያ በመጡ ጊዜም ከቦሌ ዓለም አቀፍ አየር መንገድ ጀምሮ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ እና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል መንፈሳዊ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡
ፓትርያርኩ በኢትዮጵያ በሚኖራቸው ቆይታም በዓለ መስቀልን ከማክበራቸው በተጨማሪ የቅዱስ ላሊበላ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናትን፣ ደብረ ሊባኖስን፣ ሰበታ ቤተ ደናግል የሴት መነኮሳይያት ገዳምን እና ሌሎችም ቅዱሳት መካናትን እንደሚጎበኙ፤ በሁለቱ አብያተ ክርስቲያናት መካከል ያለውን ሃይማኖታዊ ግንኙነት በሚመለከትም የመግባቢያ ሰነድ እንደሚፈራረሙ ለመረዳት ተችሏል፡፡
ከፓትርያርኩ የጉብኝት ዜና ስንወጣ የመስቀል ደመራ በዓል በመላው ዓለም በሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት መስከረም ፲፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በመንፈሳዊ ሥርዓት ተከብሯል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ መስቀል ዐደባባይ በዓሉ ሲከበርም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፤ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የየመምሪያ ሓላፊዎች፤ የገዳማት፣ አድባራት አስተዳዳሪዎች እና አገልጋይ ካህናት፤ የየሰንበት ት/ቤቶች እና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት፤ የኢፊድሪ ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በአጠቃላይ በመቶ ሺሕ የሚቈጠር ሕዝብ በሥርዓቱ ታድሟል፡፡
በዕለቱ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ቃለ ምዕዳን ሰጥተዋል፡፡
በቃለ ምዕዳናቸውም የሕንድ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ጥሪያቸውን አክብረው ወደኢትዮጵያ በመምጣት በዓሉን በጋራ በማክበራቸው መደሰታቸውን ገልጸው፣ ‹‹የመስቀል በዓል በየዓመቱ በደማቅ ሥርዓት የሚከበረው መስቀሉ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራውን የፈጸመበት በመኾኑ ነው›› በማለት በዓሉ የሚከበርበትን ምክንያት አስገንዝበዋል፡፡
አያይዘውም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሰላምን፣ አንድነትን፣ ፍቅርን እንደሰጠን ዂሉ፣ እኛ ኢትዮጵያውያንም አገራዊ አንድነታችንንና ወንድማማችነታችንን በመጠበቅ በመካከላችን ፍቅርንና ሰላምን ማስፈን፤ ዕድገታችንንም ማስቀጠል እንደሚገባን ቅዱስነታቸው አባታዊ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡
ከዚሁ ዂሉ ጋርም በቅርቡ በኦሮምያ እና ሱማሌ የኢትዮጵያ ክልሎች በተነሣው ግጭት ከዚህ ዓለም በሞት ለተለዩ ወገኖች ዕረፍትን፤ ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መጽናናትን፤ ጉዳት ለደረሰባቸውና ሕክምና ላይ ለሚገኙት ደግሞ ፈውስን እግዚአብሔር እንዲሰጣቸው ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ተመኝተዋል፡፡
በዕለቱ መንግሥትን ወክለው መልእክት ያስተላለፉት የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አቶ ደሪባ ኩማ በበኩላቸው ሃይማኖትና መንግሥት የተለያዩ ናቸው ማለት አንዳቸው በአንዳቸው አስተዳደር ጣልቃ አይገቡም ማለት እንጂ ለአገር ሰላም በሚጠቅሙ ብሔራዊ ጉዳዮች ላይ በጋራ አይመክሩም ማለት እንዳልኾነ አስታውሰዋል፡፡
የመስቀል በዓል አከባበር ሥርዓት በዓለም አቀፉ የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት በቅርስነት መመዝገቡ ለቱሪዝም ዕድገት ከሚኖረው አገራዊ ፋይዳ ባሻገር የኢትዮጵያን መልካም ገጽታ ለዓለም በማስተዋወቅ ረገድ ከፍተኛ ድርሻ እንዳለውም አስረድተዋል፡፡
በመጨረሻም ጸሎተ ቡራኬ ተደርጎ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ማርቶማ ጳውሎስ እና በዶክተር ሙላቱ ተሾመ የመስቀል ደመራው ከተለኮሰ በኋላ የበዓሉ አከባበር ሥርዓት በሰላም ተፈጽሟል፡፡
የምስል ወድምፅ ዝግጅቱ ተመርቆ በነጻ ተሠራጨ
በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው
መስከረም ፲፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በተሐድሶ መናፍቃን መሠረታዊ ስሕተት እና ወቅታዊ እንቅስቃሴያቸው ዙሪያ ያዘጋጀው የምስል ወድምፅ ዝግጅት መስከረም ፲፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ተመርቆ ለምእመናን በነጻ ተሠራጨ፡፡
በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ ማስተባበሪያ በተሰናዳው በዚህ የምስል ወድምፅ ዝግጅት፣ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ የሰሜን ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ መጋቤ ሐዲስ ቀሲስ እሸቱ ዓለማየሁ በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሐዲሳት ትርጓሜ መምህር እና ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ትምህርታዊ ማብራሪያ በመስጠት፣ ዲያቆን ምትኩ አበራ ደግሞ በማወያየት ተሳትፈውበታል፡፡
የአምስት ሰዓታት ጊዜን የሚወስደው ዝግጅቱ፣ ራሳቸውን ተሐድሶ ብለው የሚጠሩ መናፍቃን ለሚያነሧቸው የማደናገሪያ ጥያቄዎች መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምላሽ የተሰጠበት ሲኾን፣ ሕዝበ ክርስቲያኑ ራሱንና ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ከመናፍቃን ወረራ ለመጠበቅ ይችል ዘንድ ማኅበረ ቅዱሳን ለምእመናን በነጻ እንዲሠራጭ ማድረጉ ተገልጿል፡፡
ዝግጅቱ ለአንድ ዓመት ያህል እንደ ተደከመበት፤ በከፍተኛ ጥራት እንደ ተዘጋጀ እና ብዙ ገንዘብ ወጪ እንደ ተደረገበትም ከማስተባበሪያው ሪፖርት ለመረዳት ተችሏል፡፡
በዕለቱ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ፣ የግብጽ እና የሰሜን ሱዳን አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ድርጅት የበላይ ሓላፊ፤ አባቶች ቀሳውስት እና ወንድሞች ዲያቆናት፤ ሰባክያነ ወንጌል እና ዘማርያን፤ የሰንበት ት/ቤት እና የመንፈሳውያን ማኅበራት አባላት በአጠቃላይ ከሁለት ሺሕ አምስት መቶ በላይ ምእመናን ተገኝተዋል፡፡
በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይም በብፁዕ አቡነ ሉቃስ ቃለ ምዕዳን ተሰጥቷል፡፡ በዲያቆን ያረጋል አበጋዝ የፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ሒደቶችን የሚያስቃኝ የዳሰሳ ጥናት ቀርቧል፡፡ በዋና ጸሐፊው አቶ ውብእሸት ኦቶሮ አማካይነት የማኅበረ ቅዱሳን መልእክት ተላልፏል፡፡ በዋናው ማእከል መዘምራን በአማርኛ ቋንቋ፤ ከሰንዳፋ በመጡ የሰንበት ት/ቤት መዘምራን ደግሞ በአፋን ኦሮሞ ያሬዳዊ ዝማሬዎች ቀርበዋል፡፡
ብፁዕ አቡነ ሉቃስ በዕለቱ በሰጡት ቃለ ምዕዳን ሕዝበ ክርስቲያኑን ለመንፈሳዊ ጉባኤ ላሰባሰበ ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ካቀረቡ በኋላ በአዲስ ዓመት አዲስ ሐሳብ በማቅረብ የተሐድሶ ኑፋቄን ትምህርት ለመከላከል የሚያስችል ዝግጅት ለምእመናን ያሠራጨውን ማኅበረ ቅዱሳንን፣ በዝግጅቱ የተሳተፉ አባላትን እንደዚሁም በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ የተገኙ ምእመናንን አመስግነዋል፡፡
የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብዙ ፈተናዎችን እንዳሳለፈች ያወሱት ብፁዕነታቸው ምእመናን ተዋሕዶ ሃይማኖታቸውን አጽንቶ የመጠበቅ ድርሻ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡ ሃይማኖትን መጠበቅም ለአገር ሰላምና ጸጥታ፣ ለሕዝብ አንድነትና ፍቅር ዘብ መቆም ማለት መኾኑን አስረድተዋል፡፡
ራሱን ያዘጋጀ ወታደር ጠላቱን በቀላሉ ድል ለማድረግ እንደሚቻለው የጠቀሱት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ‹‹ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብና ቃለ እግዚአብሔርን በመማር ለመናፍቃን ምላሽ ለመስጠት ዘወትር የተዘጋጃችሁ ኹኑ›› በማለት ለምእመናን አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ባቀረቡት የፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ሒደቶችን የሚያስቃኝ አጠር ያለ የዳሰሳ ጥናት፣ በተለይ ከ፲፱፻፺ ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን ድረስ እንቅስቃሴያቸውን በሦስት ክፍለ ጊዜ በመመደብ ራሳቸውን ተሐድሶ ብለው የሚጠሩ መናፍቃን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱትን ጫና ማስረጃዎችን በመጥቀስ አሳይተዋል፡፡
እንደ ዲያቆን ያረጋል ማብራሪያ በ፲፱፻፺ ዓ.ም አራት የተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ መነኮሳት በቅዱስ ሲኖዶስ ተወግዘው መለየታቸው ለፀረ ተሐድሶው ተግባር ምቹ አጋጣሚ ቢኖረውም በአንጻሩ ግን ኦርቶዶክሳውያኑ ተሐድሶ መናፍቃን የሉም ብለን እንድንዘናጋ፤ መናፍቃኑ ደግሞ ውግዘትን በመፍራት የኑፋቄ ትምህርታቸውን በስውር እንዲያስፋፉ ምክንያት ኾኗል፡፡ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቀሰሴም በየጊዜው እየዘመነ በመምጣቱ አሁን ፈታኝ ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡
አያይዘውም ችግሮች ጉዳት ከማድረሳቸው በፊት የመካላከል ባህላችን ዝቅተኛ መኾን፣ የተሐድሶ ኑፋቄን ጉዳይ ከግለሰቦች ቅራኔ እንደ መነጨ አድርጎ መውሰድና ጉዳዩን በሽምግልና ለመፍታት መሞከር፣ የገንዘብ ዓቅም ማነስ፣ በሚታይ ጊዜያዊ ውጤት መርካት፣ የሰው ኃይል እጥረት፣ መሰላቸትና መዘናጋት ሐዋርያዊ ተልእኮው በሥርዓት እንዳይዳረስና የመናፍቃን ትምህርት በቀላሉ እንዲዛመት የሚያደርጉ ውስንነቶች መኾናቸውን ገልጸዋል፡፡
ሕዝበ ክርስቲያኑ መናፍቃኑ በሚያነሧቸው ጥያቄዎች አእምሮው እንዲጠመድና መምህራነ ቤተ ክርስቲያንም ለመናፍቃን ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ጊዜያቸውን እንዲያጠፉ መደረጋቸው ለሐዋርያዊ ተልእኮው መቀዛቀዝ ምክንያት መኾኑን አመላክተው ምእመናን ከተሐድሶ ኑፋቄ ትምህርት ራሳቸውንና ቤተ ክርስቲያንን ተግተው መጠበቅ እንዳለባቸው ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ አሳስበዋል፡፡
‹‹ምን እናድርግ?›› በሚለው የዳሰሳ ጥናታቸው ማጠቃለያም የተሐድሶ እንቅስቃሴን ለመከላከል በዐቢይነት የትምህርተ ሃይማኖት ዕውቀትን ማሳደግ እንደሚገባ፤ ለዚህም የሥልጠና መርሐ ግብሮችን፣ የሥነ ጽሑፍ ውጤቶችን እና የቪሲዲ ዝግጅቶችን መጠቀም ምቹ መንገድ እንደሚጠርግ ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ጠቁመዋል፡፡
በመናፍቃን ተታለው የተወሰዱ ምእመናንን ወደ ቤተ ክርስቲያን መመለስ እና በሚሊዮን የሚቈጠሩ ወገኖችን በማስተማር የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ ማድረግ ማኅበሩ ስልታዊ ዕቅድ ነድፎ ከሚያከናውናቸው ዐበይት ተግባራቱ መካከል መኾናቸውን የጠቀሱት ደግሞ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ውብእሸት ኦቶሮ ናቸው፡፡
የምስል ወድምፅ ዝግጅቱን ለምእመናን በነጻ ለማዳረስ መወሰኑ ማኅበረ ቅዱሳን ሕዝበ ክርስቲያኑ በሃይማኖቱ ጸንቶ እንዲኖር ለማበረታታት እና የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮ እንዲፋጠን ለማድረግ የሚተጋ ማኅበር ለመኾኑ አንዱ ማሳያ ነው ብለዋል – ዋና ጸሐፊው፡፡ ከዚህ የበለጠ ብዙ ሥራ ከማኅበሩና ከምእመናን እንደሚጠበቅም አስታውሰዋል፡፡
በሁለት ቋንቋዎች ብቻ የሚግባቡና በቍጥር ከዐሥር ሚሊዮን የማይበልጡ ምእመናን የሚገኙባት የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከስምንት በላይ የቴሌቭዥን ጣቢያዎች እንዳሏት ያወሱት አቶ ውብእሸት፣ ከሰማንያ በላይ ቋንቋዎችን የሚጠቀሙና ወደ አምሳ ሚሊዮን የሚደርሱ ምእመናን ባለቤት ለኾነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንድ የቴሌቭዥን ጣቢያ ብቻ በቂ አለመኾኑን ጠቁመዋል፡፡
አያይዘውም ይህን ጉዳይ የተገነዘበው ማኅበረ ቅዱሳን፣ የአየር ሰዓት በመከራየት በአሌፍ የቴሌቭዥን ጣቢያ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደሚገኝ በማስታወስ መንፈሳዊ የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩን አጠናክሮ ለመቀጠል ያመች ዘንድ በገንዘብም፣ በቁሳቁስም፣ በሐሳብም ምእመናን ድጋፍ እንዲያደርጉ ዋና ጸሐፊው ጠይቀል፡፡
ከዚሁ ዂሉ ጋርም ማኅበረ ቅዱሳን ሰባክያነ ወንጌልን በማሠልጠን፣ አዳዲስ አማንያንን በማስጠመቅ፣ በጠረፋማ አካባቢዎች አብያተ ክርስቲያናትን በማሳነጽ እና በመሳሉት ዘርፎች ፕሮጀክት ቀርፆ ለስብከተ ወንጌል መዳረስ የሚያከናውናቸውን ተግባራት በሚችሉት መንገድ ዂሉ በመደገፍ እና ከማኅበሩ ጎን በመቆም ምእመናን የሚጠበቅባቸውን ክርስቲያናዊ ድርሻ እንዲወጡ አቶ ውብእሸት ኦቶሮ በማኅበረ ቅዱሳን ስም ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡
በመልእክታቸው ማጠቃለያም ትምህርተ ወንጌልን በማዳረስ፤ የግንዛቤ ማዳበሪያ መርሐ ግብራትን በማዘጋጀትና ሥልጠና በመስጠት፤ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎትና ለሥልጠና መስጫ የሚውል ገንዘብ በመለገስ፤ የተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆችን በማጋለጥ በአጠቃላይ በልዩ ልዩ መንገድ ሱታፌ በማድረግ ኦርቶዶክሳዊው አስተምህሮ እንዲስፋፋ፣ የተሐድሶ ኑፋቄ ትምህርት ደግሞ እንዲዳከም ከፍተኛ አስተዋጽዖ ላበረከቱ ሰባክያነ ወንጌል እና በጎ አድራጊ ምእመናን በተጨማሪም ማኅበሩ ያስተላለፈውን ጥሪ ተቀብለው በድምፅ ወምስል ዝግጅቱ ምረቃ ላይ ለተገኙ ወገኖች ዅሉ ዋና ጸሐፊው በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም መንፈሳዊ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
በመጨረሻም የምስል ወድምፅ ዝግጅቱ በብፁዕ አቡነ ሉቃስ ቡራኬ ተመርቆ በቍጥር አንድ ሺሕ በሚኾኑ በባለ ፲፮ ጊጋ ባይት ፍላሽ ዲስኮች ለምእመናን የታደለ ሲኾን፣ በዕለቱ ያልተገኙ ምእመናን ከማኅበሩ ሕንጻ ድረስ በአካል በመምጣት ዝግጅቱን በፍላሽ እንዲወስዱ፤ በጎ አድራጊ ምእመናን ፍላሽ ዲስኮችን ገዝተው በማበርከት ለትምህርቱ መዳረስ ትብብር እንዲያደርጉ፤ ዝግጅቱ የደረሳቸው ወገኖችም እያባዙ ቤተ ክርስቲያንን ለሚወዱም ኾነ ለማይወዱ ወገኖች እንዲያዳርሱ፤ ዝግጅቱ ያልደረሳቸው ደግሞ ትምህርቱ በማኅበሩ ቴሌቭዥን ሲተላለፍ፣ በዩቲዩብ ሲለቀቅና በሲዲ ሲሠራጭ እንዲከታተሉ በማስተባበሪያው በኩል ማሳሰቢያ ከተሰጠ በኋላ በብፁዕነታቸው ቃለ ምዕዳን እና ጸሎተ ቡራኬ መርሐ ግብሩ ተጠናቋል፡፡
ከምረቃ መርሐ ግብሩ በኋላ ስለ ዝግጅቱ አስተያየት እንዲሰጡ የጠየቅናቸው ምእመናን፣ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ፈተና የኾነውን የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ ለመከላከል ይቻል ዘንድ ብዙ ገንዘብ ወጪ በማድረግ ያዘጋጀውን የምስል ወድምፅ ዝግጅት ለምእመናን በነጻ ማዳረሱ ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ ለመደገፍ የሚተጋ የቍርጥ ቀን ልጅ መኾኑን እንደሚያስረዳ መስክረዋል፡፡ ከማኅበሩ ጋር በመኾን የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት በሚቻላቸው ዓቅም ዅሉ የማኅበሩን አገልግሎት ለመደገፍም ቃል ገብተዋል፡፡
ከዚህ በተለየ ደግሞ የማኅበሩ አዳራሽ እና በምድር ቤቱ ወለል ላይ የተዘጋጁ ድንኳኖች ሞልተው በርካታ ምእመናን ቆመው መርሐ ግብሩን መከታተላቸውን፤ ከፊሉም መግቢያ አጥተው በመርሐ ግብሩ ለመሳተፍ አለመቻላቸውን ያስተዋሉ አንዳንድ በጎ አድራጊ ምእመናን በመንፈሳዊ ቍጭት ተነሣሥው ‹‹ብዙ ሕዝብ ማስተናገድ የሚችል ሰፊ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ መገንባት አለብን›› እየተባባሉ ሲነጋገሩ ተሰምቷል፡፡
በአውሮፓ የመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ ተካሔደ
በአውሮፓ ማእከል
ጳጕሜን ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም
በማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የሙያ አገልግሎት እና አቅም ማጎልበቻ ክፍል አስተባባሪነት ‹‹የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅርሶች›› በሚል ርእሰ ጉዳይ የመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጥናት ጉባኤ በስዊድን አገር በሉንድ ዩኒቨርሲቲ ከነሐሴ ፳፯ – ፳፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ተካሔደ፡፡
በጥናት ጉባኤው በታዋቂ ምሁራን በአማርኛ እና እንግሊዝኛ ቋንቋዎች በልዩ ልዩ አርእስት የተዘጋጁ የምርምር ሥራዎች የቀረቡ ሲሆን፣ ከአውሮፓ ሀገራት የመጡ በርካታ ምእመናን እና የስዊድን ዜጎች በተዳሚነት ተሳትፈዋል፡፡
በመጀመሪያው ጉባኤ በለንደን ከተማ የደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ የሆኑት ቀሲስ አባተ ጉበና ‹‹የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅርስ ጥቅሞች፣ የቤተ ክርስቲያን ደኖች እንደ አገር ብዝኀ ሕይወት ማሳያነት›› በሚል ርእስ ባስተላለፉት መልእክት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደን ጥበቃ የላቀ አስተዋጽዖ ከማበርከቷ ባሻገር የብዝኀ ሕይወት መገኛ እንደ ሆነችም አስረድተዋል፡፡
በሉንድ ዩኒቨርሲቲ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ሳሙኤል ሩቢንሰን፣ ‹‹የኢትዮጵያ ሃይማኖታዊ ቅርሶች ለክርስትና ታሪክ ያላቸው አስተዋጽዖ›› በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሑፍ በምዕራባውያን ጫና ምክንያት የክርስትና ታሪክ በመጀመሪያ ወደ አውሮፓ መግባቱ፤ በቅኝ ግዛት ዘመን ወደ አፍሪካ እና እስያ መስፋፋቱ በተዛባ መልኩ እንደሚነገር አውስተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክ በክርስትና ታሪክ ውስጥ የሚያካትቱ አካላትም የኢትዮጵያ ባህል ከሌሎች አገሮች ተገንጥሎ የወጣ እንደ ሆነ እና ለክርስትና ታሪክም አስተዋጽዖ እንደሌለው የማድረግ ዝንባሌ እንደሚታይባቸው ፕሮፌሰሩ አብራርተዋል፡፡ ‹‹በመጀመሪያው ምዕት ዓመት በነበረው የክርስትና አመሠራረት ላይ የኢትዮጵያን አስተዋጽዖ አለማካተት የክርስትናን ታሪክ ጎደሎ እንዲኾን ያደርዋል›› የሚሉት ፕሮፌሰር ሩቢንሰን፣ ክርስትና ከኢየሩሳሌም ወደ አውሮፓ፤ ከዚያም በቅኝ ግዛት ዘመን ወደ አፍሪካ እና እስያ ደረሰ የሚለው አስተሳሰብ ስሕተት መሆኑን በጥናታቸው ጠቁመዋል፡፡
‹‹የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅርሶች ታሪክና ጥበቃ›› በሚል ርእስ ጥናት ያቀረቡት የአርኪዮሎጅ እና አንትሮፖሎጅ ምሁሩ እንግሊዛዊው ፕሮፌሰር ዴቪድ ፊልፕሰን፣ ከዘመነ አክሱም ጀምሮ ያለውን የኢትዮጵያ ቅርሶችን ታሪክ ካስታወሱ በኋላ ስለ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት አሠራር፣ ስለሚደረግላቸው ክብካቤና ጥበቃ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ በዘራፊዎች ተወስደው በውጭ አገር የሚገኙ የኢትዮጵያ ቅርሶችን ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ የሚደረገውን ጥረት እንዳይሳካ የሚያደርጉ ጉዳዮችንም ዳሰዋል፡፡ ፕሮፌሰሩ ፊሊፕሰን በእንግሊዝ አገር የሚገኙ ቅርሶች ወደ ኢትዮጵያ ይመለሱ ተብሎ እንቅስቃሴ በሚደረግበት ወቅት ቅርሶችን በማስተዳደር ላይ ያሉት የብሪታንያ ሙዚየም ባለ ሥልጣናት ‹‹ቅርሶች ወደ ኢትዮጵያ ቢመለሱ፣ ጥበቃና ክብካቤ የሚያደርግላቸው የለም›› የሚል ምክንያት እንደሚሰጡ በጥናታቸው አውስተዋል፡፡ ይሁን እንጂ ከእንግሊዝ ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱ ቅርሶችም እንዳሉ የጠቆሙት ፕሮፌሰሩ ለአብነትም በ፲፰፻፸፪ ዓ.ም የተመለሰው ክብረ ነገሥት የተባለው መጽሐፍ በአዲስ አበባ ከተማ በመርካቶ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን በጥሩ ክብካቤ እንደሚገኝ ከሰባ ዓመታት በፊት ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ተሞክሮ በመነሣትም ዅሉም ቅርሶቿ ቢመለሱላት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሥርዓት እንደምትጠብቃቸው በመጠቆም ፕሮፌሰር ፊሊፕሰን ጥናታዊ ጽሑፋቸውን አጠናቀዋል፡፡
በኖርዌይ አገር የአካባቢያዊ ኬሚስትሪ ምሁሩ ዶክተር ኪዳኔ ፋንታ በበኩላቸው ‹‹የኢትዮጵያ ክርስቲያናዊ ሥዕላት ፊዚኮ – ኬሚካዊ ምርመራ›› በሚል ርእስ ባዘጋጁት ጥናታዊ ጽሑፋቸው ሥዕላቱ የተሠሩበትን ንጥረ ነገር ማወቅ ሥዕላቱን ለመጠበቅና እና እድሳት ለማድረግ ጠቀሜታ እንዳለው አመላክተዋል፡፡ ዘመኑ ያፈራቸውን የረቀቁ የቤተ ሙከራ መሣሪያዎች በመጠቀምና ምርመራ በማድረግ ልዩ ልዩ ሥዕላት፣ የሕንጻ ዓምዶች እና የብራና ጽሑፎች የተዘጋጁበትን ንጥረ ነገር፣ ዘመን እና ቦታ ለመለየትና ለመረዳት እንደሚቻልም በምሳሌ አስረድተዋል፡፡
ሌላኛው ጽሑፍ አቅራቢ የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ተከሥተ ነጋሽ ደግሞ ‹‹ዋሌ ኢየሱስ፣ የአክሱም ዘመን ቤተ ክርስቲያን በዛግዌ ምድር›› በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናት በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ውስጥ የሚገኘውን ጥንታዊ የዋሻ ቤተ ክርስቲያንን አሠራር የሚመለከት ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ የዋሌ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን አሠራር በአክሱም ዘመን ከታነጹ አብያተ ክርስቲያናት ጋር ተመሳሳይነት እንዳለውም አስረድተዋል። በቤተ ክርስቲያኑ ዙሪያ የሚኖሩ መነኮሳትና ካህናት ቤተ ክርስቲያኑ ከላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት አስቀድሞ በስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደ ተመሠረተ ማስረጃዎች መሆናቸውንም ፕሮፌሰር ተከሥተ ነጋሽ አውስተዋል፡፡
ነሐሴ ፳፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከቅዳሴ በኋላ በሉንድ ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ሁለተኛው የጥናት ጉባኤ የቀጠለ ሲኾን፣ በልዩ ልዩ አርእስት የተዘጋጁ ሦስት ጥናታዊ ጽሑፎች በአማርኛ ቋንቋ ቀርበዋል፡፡ በመጀመሪያ ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ቅርሶች ለመጠበቅ፣ ለምእመናን ምን ያኽል ትምህርት ተሰጥቷል?›› በሚል ርእስ የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ሽፈራው በቀለ እስከ አሁን ድረስ በአደረጉት የሰነድ ምርመራ የቅርሶችን ምንነት እና አጠባበቅ የሚያስረዱ ጽሑፎችን ማግኘት አለማቻላቸውን፤ በቤተ ክርስቲያን የሚሰጡ አብዛኞቹ ትምህርቶችም የቅርስ አያያዝን አለማካተታቸውን አስገንዝበዋል። በዚህ የተነሣም የቤተ ክርስቲያን ቅርሶች የመጥፋት አደጋ እንደ ተጋረጠባቸው ገልጸዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ሕንጻዎችን፣ ንዋያተ ቅድሳትን እና መጻሕፍትን ለመጠበቅና ከጥፋት ለመታደግ ይረዳ ዘንድ መሠረታዊ የቅርስ ጥበቃ፣ ክብካቤ እና ጥገናን የሚመለከቱ ሥልጠናዎችን መስጠት አስፈላጊ መሆኑንም ፕሮፌሰር ሽፈራው በጥናታቸው ማጠቃለያ ጠቁመዋል፡፡
በመቀጠል የፊሎሎጅ ምሁሩ ቀሲስ ዶክተር አምሳሉ ተፈራ ‹‹ጥንታዊ የብራና ላይ ጽሑፎቻችን ዘረፋ፣ የአያያዝ ጉድለትና ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች›› በሚል ርእስ የምርምር ሥራቸውን አቅርበዋል፡፡ የብራና ጽሑፎችን ምንነት፣ ዓይነትና ይዘት በመተንተን ጥናታቸውን የጀመሩት ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ፣ በውጭ ሀገራት የሚገኙ በርካታ የኢትዮጵያ ቅርሶች በአብዛኛው በዘረፋ መልክ የተወሰዱ፤ የተወሰኑት ደግሞ ነገሥታቱ ለመሪዎች በስጦታ መልክ ያበረከቷቸው መሆናቸውን አውስተዋል፡፡ እንደ ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ማብራሪያ በአጠቃላይ 6,245 የብራና መጻሕፍት በልዩ ልዩ መንገድ ከኢትዮጵያ የተወሰዱ ሲሆን፣ አብዛኞቹም በእንግሊዝ፣ በጀርመን፣ በጣልያን እና ቫቲካን አገሮች ይገኛሉ፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም ጥቂት የብራና ጽሑፎች በልዩ ልዩ ጊዜያት ወደ ኢትዮጵያ መመለሳቸውን አስታውሰው እርሳቸው ተሳትፎ ያደረጉበትን ከአሜሪካው ሀዋርድ ዩኒቨርሲቲ ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም የተመለሰውን የገድለ ሰራባሞን እና ሌሎችም ቅርሶችን በማስረጃነት ጠቅሰዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን፣ መንግሥት እና እያንዳንዱ ግለሰብ ቅርሶችን የመጠበቅ ሓላፊነት እንዳለበት በማሳሰብ ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ጥናታቸውን አጠቃለዋል፡፡
በጥናት ጉባኤው ማጠናቀቂያ ዕለትም ከጥናት አቅራቢዎች መካከል ፕሮፌሰር ዴቪድ ፊልፕሰን ‹‹በማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል ይህን ዐውደ ጥናት በማዘጋጀቱ በቤተ ክርስቲያኒቱ ዙሪያ የሚሠሩ ምርምሮችን ከሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን ልጆች ጋር ለመወያየት እድል ፈጥሮልኛል›› በማለት አስተያየት ከሰጡ በኋላ ዐውደ ጥናቱን ያዘጋጀውን ማኅበረ ቅዱሳንን አመስግነዋል፡፡ ሌሎች ጥናት አቅራቢዎችና ተሳታፊዎችም በጉባኤው እንደ ተደሰቱ ገልጸው ወደፊትም ይኽን ዓይነቱ የጥናት ጉባኤ ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል፡፡
በመጨረሻም ለዚህ ዓለም አቀፍ ጉባኤ መሳካት አስተዋጽዖ ላደረጉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ ለሉንድ ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል ሰበካ ጉባኤ፣ ለሉንድ ዩኒቨርሲቲ፣ ለፕሮፌሰር ሳሙኤል ሩቢንሰን፣ ጥናታዊ ጽሑፍ ላቀረቡና መልእክት ላስተላለፉ ምሁራን፣ ለተጋባዥ እንግዶች እና በጉባኤው ለተሳተፉ ምእመናን የዐውደ ጥናት ዝግጅት ኮሚቴው ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ተፈራ በኮሚቴው፤ ዲያቆን ዓለምነው ሽፈራው ደግሞ በአውሮፓ ማእከል ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
በአሜሪካ ለአራተኛ ጊዜ ዐውደ ርእይ ተካሔደ
በአሜሪካ ማእከል
ነሐሴ ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም
‹‹ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ›› በሚል ርእስ ማኅበረ ቅዱሳን ያዘጋጀው ፭ኛው ዙር ልዩ ዐውደ ርእይ በአሜሪካ አገር ለአራተኛ ጊዜ ለተመልካቾች ቀረበ፡፡
ዐውደ ርእዩ በአሜሪካ ማእከል በካሮላይና ግንኙነት ጣቢያ አስተባባሪነት ነሐሴ ፲፫ እና ፲፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በሻርሎት ከተማ በሚገኘው የግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አዳራሽ ቀርቦ በበርካታ ምእመናን ተጐብኝቷል፡፡
በመክፈቻ ሥርዓቱ ላይ የየአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ሰባክያነ ወንጌል፣ ቀሳውስት፣ ዲያቆናትና በርካታ ምእመናን የተገኙ ሲኾን፣ በአባቶች ጸሎት ከተከተፈተ እና በግንኙነት ጣቢያው የእንኳን ደኅና መጣችሁ መልእክት ከተላለፈ በኋላ ዐውደ ርእዩ በሁለቱም ቀናት ለተመልካቾች ክፍት ኾኖ ቆይቷል፡፡
ከአባቶች ካህናትና ከአዋቂ ምእመናን በተጨማሪ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የሚግባቡ በርካታ ታዳጊ ሕፃናትና ወጣቶችም በዐውደ ርእዩ መሳተፋቸውን ግንኙነት ጣቢያው በሪፖርቱ አስረድቷል፡፡
እንደ ግንኙነት ጣቢያው ማብራሪያ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ይመለከተኛል የሚሉ ምእመናን እየተበራከቱ መምጣታቸውን የዐውደ ርእዩ ተመልካቾቹ ያቀርቧቸው ከነበሩ አስተያየቶች ለመረዳት ተችሏል፡፡ ይህም የዐውደ ርእዩ ዓላማ መሳካቱን እንደሚያመላክት በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡
ከዚሁ ዅሉ ጋርም የአንድ ለአንድ ድጋፍ በማድረግ የአብነት ተማሪዎችን ለመርዳትና ለማስተማር ቃል የገቡ ምእመናን እንደ ነበሩም ግንኙነት ጣቢያው ጨምሮ ገልጿል፡፡
በመርሐ ግብሩ ማጠቃለያ ዕለት ቃለ መጠይቅ የተደረገላቸው አንዳንድ ምእመናን በዐውደ ርእዩ በመሳተፋቸው ደስተኞች መኾናቸውን ገልጠው ማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎቱን በአገር ውስጥ ብቻ ሳይገድብ ከኢትዮጵያ ውጪ ለሚኖሩ ምእመናንም ትምህርተ ወንጌል እንዲዳረስ የሚያደርገውን ጥረት አድንቀዋል፡፡ ይህ የማኅበሩ አገልግሎት ተጠናክሮ ሊቀጥል፣ ዐውደ ርእዩም በመላው ዓለም ሊዳረስ እንደሚገባው አስተያየት ሰጪዎቹ አሳስበዋል፡፡
በመጨረሻም ዐውደ ርእዩ በስኬት መጠናቀቁን ያስታወቀው የካሮላይና ግንኙነት ጣቢያ ጽ/ቤት እና የዝግጅት ኮሚቴው በልዩ ልዩ መንገድ አስተዋጽዖ ላደረጉ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፤ ለአታላንታ ንዑስ ማእከልና ሰንበት ትምህርት ቤት አባላት፤ በተለይ ከአራት ሰዓታት በላይ ተጕዘው በትዕይንት ገላጭነት ለተሳተፉ ወንድሞች እና እኅቶች፤ እንደዚሁም ለበጎ አድራጊ ምእመናን በማኅበረ ቅዱሳን ስም ምስጋና አቅርቧል፡፡
ዐውደ ርእዩ በኢንድያናፖሊስ ከተማ ቀረበ
በዝግጅት ክፍሉ
ነሐሴ ፲፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም
‹‹ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ›› በሚል ርእስ በማኅበረ ቅዱሳን የተዘጋጀው ልዩ ዐውደ ርእይ በአሜሪካ አገር በኢንዲያናፖሊስ ከተማ ለምእመናን ቀረበ፡፡
በማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማእከል ኢንዲያና ግንኙነት ጣቢያ አዘጋጅነት ሐምሌ ፳፱ እና ፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም የቀረበው ይህ ልዩ ዐውደ ርእይ በጸሎተ ወንጌል ተባርኮ በወጣቶች እና ሕፃናት ዘማርያን ያሬዳዊ መዝሙሮች ከቀረቡ በኋላ ከኢንዲያና እና አጎራባች ግዛቶች በመጡ ከሦስት መቶ ስልሳ በላይ በሚኾኑ ካህናትና ምእመናን እንደ ተጐበኘ የአሜሪካ ማእከል አስታውቋል፡፡
እንደ ማእከሉ ማብራሪያ የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ ሐዋርያዊ አገልግሎቷ፣ ተጋድሎዋ፣ ያጋጠሟት ችግሮች እና ችግሮቿን ከመፍታት አንጻር የምእመናን ድርሻ እንደዚሁም የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት በቤተ ክርስቲያን የሚሉ ጉዳዮች በዐውደ ርእዩ የተካተቱ የትዕይንት ክፍሎች ሲኾኑ፣ ትዕይንቶቹም በአማርኛ፣ ትግርኛ እና እንግሊዝኛ ቋንቋዎች ተተርጕመው ለወጣቶች እና ሕፃናት በሚመጥን መልኩ ቀርበዋል፡፡
መልአከ ሰላም ቆሞስ አባ ኃይለ ማርያም የኢንዲያናፖሊስ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ እና መልአከ ኃይል ቀሲስ ፍቅረ ኢየሱስ የኬንታኪ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ካህን ከሌሎች አባቶች ጋር በዐውደ ርእዩ ተገኝተው ከምእመናን ለሚነሡ ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት የአባትነት ድርሻቸውን ተወጥተዋል፡፡
የዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ወደ ትግርኛ ቋንቋ ተተርጕመው ለምእመናን እንዲቀርቡ በማድረግ በኢንዲያናፖሊስ ከተማ የሚኖሩ ትግርኛ ቋንቋ መናገር የሚችሉ ካህናት እና ምእመናን ድርሻ የላቀ እንደ ነበርም በማእከሉ ሪፖርት ተጠቅሷል፡፡
በአጠቃላይ የዐውደ ርእዩ ዝግጅት ላይ የኢንዲያናፖሊስ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ፣ የሰንበት ት/ቤቱ አባላት፣ የአጥቢያው ምእመናን፣ የኢንዲያና ግንኙነት ጣቢያ እና የቺካጎ ንዑስ ማእከል አባላት በገላጭነት፣ በአስተባባሪነት እና በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፎች ከፍተኛ ተሳትፎ አድርገዋል፡፡
በመጨረሻም የዝግጅት ኮሚቴው ሰብሳቢ ዶክተር በላይነህ ደስታ ለዝግጅቱ መሳካት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ላደረጉ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ ስፖንሰር (ድጋፍ) በማድረግ ለተባበሩ የግል ድርጅቶች እና ለበጎ አድራጊ ምእመናን ምስጋና ካቀረቡ በኋለ ዐውደ ርእዩ በአባቶች ጸሎት ተፈጽሟል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩን ሊቀጥል ነው
ነሐሴ ፲፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩን ከመስከረም ፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ጀምሮ በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ሊቀጥል ነው፡፡
በአሌፍ የቴሌቭዥን ጣቢያ በአዲስ ዓመት ልዩ ዝግጅት የሚጀምረው የማኅበሩ መንፈሳዊ የቴሌቭዥን መርሐ ግብር በአማርኛ፣ በአፋን ኦሮሞ እና በትግርኛ ቋንቋዎች የሚቀርብ ሲኾን፣ ሥርጭቱም ለጊዜው በየቀኑ ለሁለት ሰዓታት እንደሚተላለፍ የማኅበረ ቅዱሳን ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡
ማኅበሩ ካሁን በፊት በኢቢኤስ የቴሌቭዥን ጣቢያ በሳምንት ለአንድ ሰዓት በአማርኛ ቋንቋ ሲያስተላልፍ የነበረው መንፈሳዊ መርሐ ግብር በልዩ ልዩ ምክንያት ከተቋረጠ በኋላ በየሳምንቱ ለሁለት ሰዓታት በኢንተርኔት ቴሌቭዥን በሚያሠራጫቸው መንፈሳዊ ዝግጅቶቹ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ትምህርተ ወንጌል ሲያቀርብ ቆይቷል፡፡
ከዚሁ ዅሉ ጋርም የኦቢኤስ ቴሌቭዥን ጣቢያ ሥራ እስካቆመበት ጊዜ ድረስ በሳምንት ለሠላሳ ደቂቃ በአፋን ኦሮሞ ቃለ እግዚአብሔር ሲያስተምር መቆየቱ የሚታወስ ነው፡፡
በእግዚአብሔር መልካም ፈቃድ አገልግሎቱን ይበልጥ በማስፋት በመጪው አዲስ ዓመት በሚያስተላልፈው መንፈሳዊ የቴሌቭዥን ሥርጭቱም ኦርቶዶክሳዊውን አስተምህሮ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ለማዳረስ ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡
የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩንም ከመስከረም ፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ጀምሮ በሚከተለው የሥርጭት አድራሻ መከታተል የምትችሉ መኾኑን ማኅበሩ ያሳስባል፤
Aleph Television Nilesat (E8WB)
Frequency: 11595
Polarization: Vertical
Symbol Rate: 27500
FEC: 3/4
ማኅበረ መነኮሳቱ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠየቁ
በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው
ሐምሌ ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም
በምዕራብ ጐጃም ሀገረ ስብከት በሜጫ ወረዳ ቤተ ክህነት በጉታ ቀበሌ ልዩ ስሙ ናዳ በሚባል ቦታ የሚገኘው የፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም መነኮሳትና አብነት ተማሪዎች ሰኔ ፳፪ እና ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በጣለው ከባድ ዝናም እና በረዶ ምክንያት ያለሙት ፍራፍሬ ሙሉ በሙሉ በመውደሙ፣ መኖርያ ቤታቸውም በመፍረሱ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠየቁ፡፡
ምንኵስናን ከሊቅነት፣ አባትነትን ከሥራ ጋር አስተባብረው የያዙት የገዳሙ ዋና አስተዳዳሪ፣ የትርጓሜ መጻሕፍትና የቅኔ መምህሩ ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ በቦታው ተገኝተን ቃለ መጠይቅ ባደረግንላቸው ወቅት እንደ ገለጹልን በገዳሙ አካባቢ የሚገኘውን በጎርፍ የተሸረሸረ ሸለቆ በመከባከብ በ፲፱፻፹ ዓ.ም የተጀመረው የልማት ሥራ ገዳሙን በፌዴራል ሁለተኛ፤ በክልል ደግሞ አንደኛ ደረጃ እንዲያገኝና የክብር ሜዳልያ እንዲሸለም አድርጎታል፡፡
ዳሩ ግን ይህ የልማት ውጤት በበረዶው ምክንያት ከጥቅም ውጪ ኾኗል፡፡ ፍራፍሬውና ደኑም ተጨፍጭፏል፡፡ የጠበል መጠመቂያ ቦታዎች ተናውጠዋል፡፡ ንቦችም ከቀፎዎቻቸው ወጥተው ተሰደዋል፡፡ የመነኮሳቱና አብነት ተማሪዎች መኖርያ ቤቶችም ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ በአጠቃላይ ከሰባ ሄክታር በላይ የሚገመት ሰብል በበረዶው ናዳ መውደሙን ከገዳሙ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ ‹‹ወደዚህ ገዳም ከመጣሁበት ጊዜ ጀምሮ እንደዚህ ዓይነት ክሥተት ደርሶ አይቼ አላውቅም›› ይላሉ ዋና አስተዳዳሪው የጉዳቱን ከፍተኛነት ሲገልጹ፡፡
ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በደረሰን መረጃ ማኅበረ ቅዱሳን ከገዳሙ ድረስ ልዑካንን በመላክ ለጊዜው የዘር መግዣ ይኾን ዘንድ የሃያ ሺሕ ብር የገንዘብ ድጋፍ አድርጓል፡፡ ማኅበሩ ካሁን በፊት አንድ ትራክተር ገዝቶ በስጦታ ለገዳሙ ያበረከተ ሲኾን፣ ለወደፊትም ገዳሙን በቋሚነት ለመደገፍ አቅዷል፡፡
በመጨረሻም ላደረገው የገንዘብ ድጋፍ ማኅበረ ቅዱሳንን፤ በጉልበት ሥራ በመራዳታቸው ደግሞ የአካባቢውን ሕዝበ ክርስቲያን የገዳሙ ዋና አስተዳዳሪ አመስግነው፣ ሌሎች በጎ አድራጊ ምእመናንም ቀለብ በመስጠት፣ ዘር በመግዛት፣ ልብስ በመለገስ፤ ከፍ ሲል ደግሞ መኖርያ ቤት በማደስ በአጠቃላይ በሚቻላቸው አቅም ዅሉ ድጋፍ እንዲያደርጉ ዋና አስተዳዳሪው በገዳሙ ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም ከ፲፱፻፸፱ ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን ድረስ የትርጓሜ መጻሕፍት እና የቅኔ ትምህርት የሚሰጥበት ጥንታዊ ገዳም ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር ገዳሙ በልማት ሥራ የታወቀ ልዩ ቦታ ነው፡፡ ኾኖም በዘንድሮው ዓመት በወርኃ ሰኔ በአካባቢው በጣለው ከባድ በረዶ የተነሣ ፍራፍሬውና ደኑ በመውደሙ የገዳሙ መነኮሳትና የአብነት ተማሪዎች ኑሯቸው አደጋ ላይ ነው፡፡
ዝግጅት ክፍላችንም የገዳሙን መነኮሳት ከስደት፣ ጉባኤ ቤቱንም ከመዘጋት ለመታደግ፤ እንደዚሁም የልማት ቦታውን ወደ ጥንት ይዘቱ ለመመለስ ይቻል ዘንድ በተቻላችሁ አቅም ዅሉ ድጋፍ በማድረግ ከበረከቱ እንድትሳተፉ ይኹን ሲል መንፈሳዊ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡
ማሳሰቢያ
ገዳሙን በገንዘብ ለመደገፍ የምትፈልጉ ምእመናን በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መርዓዊ ቅርንጫፍ ሒሳብ ቍጥር፡- 10000 6261 1786 ገቢ ማድረግ የምትችሉ መኾኑን የገዳሙ ጽ/ቤት ያሳስባል፡፡ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘትም በስልክ ቍጥር፡- 09 18 70 81 36 በመደወል የገዳሙን ዋና አስተዳዳሪ ማነጋገር ይቻላል፡፡