ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን ጾመ?

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ  

በገዳም ቆሮንቶስ ፵ ቀንና ለሊት የጾመው

ሀ/ ሕግን ሊፈጽም

የሕግ ሁሉ ባለቤት የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር ጾምን ለአዳም የሰጠው ጥንታዊው ሕግ ከእግዚአብሔር ዘንድ ሰማያዊ ዋጋ የሚያገኝበት ጸንቶ እንዲቆም የሚያስችለውና ከክፉ የሚጠብቀው መንፈሳዊ መከላከያው መድኃኒት ሆኖ የተሰጠው ፤  ኦሪትም የተሰራችው በጾም ነበር፡፡ አባታችን ሙሴ ኦሪት ዘዳግም  ፱፥፱ ላይ “ሁለቱን የድንጋይ ጽላት እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር የተማማለባቸውን የቃልኪዳን ጽላት እቀበል ዘንድ ወደ ተራራ በወጣሁ ጊዜ በተራራውም አርባ ቀንና አርባ ለሊት ተቀምጬ ነበር፤ እንጀራ አልበላሁም፤ ውሃም አልጠጣሁም”፤ አለ፡፡ በዚህም ሙሴ የኦሪትን ሕግ ተቀበለ፤ እናም ሕግን ለመቀበል በቅድሚያ መጾም ያስፈልጋል ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሕግን ሲፈጽም በቅድሚያ የወንጌል መጀመሪያ ያደረገው ጾምን ነው፤ የማቴዎስ ወንጌል ፬፥፩-፲፩ ላይ “እኔ ሕግ ልሽር ሳይሆን ልፈጽም ወደ ምድር ወርጃለሁ”፤ አለ፡፡

ለ/ዕዳችንን ሊከፍል (ካሳ ሊሆነን)፤

እግዚአብሔር ለአባታችን አዳም “ይህንን ዕፀ በለስ አትብላ፤ የበላህ እንደሆነ ትሞታለህ”፤ ብሎት የነበረውን ትእዛዝ ተላልፎ በራሱ ፍቃዱ ተጠቅሞ የተከለከለችዋን ፍሬ በላ፤ ሕግንም ጣሰ፡፡ ስለዚህ አዳም በመብላት ያመጣውን ሞት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ  ለ፵ ቀን ለ፵ ለሊት ባለመብላት ባለመጠጣት ዕዳችንን ከፈለ፡፡ ደሙን አፍሶ፤ ሥጋውን ቆርሶ፤ በቀራንዮ አደባባይ ተሰቅሎ አዳምን ከሞት ወደ ሕይወት፤ ከሲኦል ወደ ገነት መለሰው፡፡

ሐ/ለአርያነት፤ የመንፈሳዊና የበጎ ምግባር ሁሉ መነሻው ጾም ነው፡፡  የዕለተ ዐርብ የማዳኑን ሥራ በጾም ጀመረ፤ የወንጌል ሥራ መጀመሪያም አደረጋት፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በዮርዳኖስ ከተጠመቀ በኋላ  ሥራውን በጾም እንደ ጀመረ ሐዋርያትም ስለተረዱ እርሱን በመምሰል ሥራቸውን በጾም ጀመሩት፡፡ አባቶቻችን ጾምን የትምህርት መጀመሪያ አደረጓት፤ በዚህም ለዘለዓለም ከእግዚአብሔር ጋር በመንግሥቱ እንዲኖሩ በር ስለከፈተላቸው ለአርአያነት ነው ብለን ተቀበልነው፡፡ ሆኖም ሳይጾም ጹሙ አላለንም፤ በምድር እስካለንና እርሱ አርአያ እስከሆነን ድረስ  ከመዓትና ከዘላለም እሳት ለመዳን በጾምና ጸሎት ልንኖር ያስፈልጋል፡፡፡

መ/ሊያስተምረን፤ የተፈቀደውን እየፈጸምን፤ የተከለከልነውን በመተው ሕግ እያከበርን በትምህርተ ወንጌል ድኅነትን እንድናገኝና የነፍሳችን ቁስል እንዲፈወስ ለክርስቶስ ሕይወታችንን መስጠት አለብን፡፡ እንዲሁም ለመጾም ድፍረት ያላት ነፍስ ቀጣይነት ባለው መንፈሳዊ ልምምድ ራስን መግዛት ለሥጋ ፈቃድ የሚያስፈልገውን ምግብና መጠጥ በመተው የሥጋ ፈቃድን ድል በመንሣት ለነፍስ ፈቃድ ማስገዛት ይቻላል ፡፡ ይህቺ ነፍስ ክርስቶስ ያስተማራትን ከተገበረች የሚመጣባትን ከባድ ነገር ሁሉ እስራቱንና ግርፋትን መቋቋም ይቻላታል፡፡ ስለዚህ መጾም በኃጢአታችን እንድንጸጸትና ወደ አግዚአብሔር እንድንመለስ (እንድንቀርብ )ብቻ ሳይሆን ለዘለዓለም ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር ያለንን ፍቅር ለመግለጽ እንድንችል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሮናል፡፡

ሠ/ ዲያብሎስን ድል ለመንሣት፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማቴዎስ ወንጌል ፬፥፩-፲፩ ላይ መዋዕለ ጾሙ ሲፈጸም ሰይጣን በሦስት ነገር ማለትም በስስት፣ በትዕቢትና በፍቅረ ንዋይ ተፈታተነው፡፡ በስስት ቢፈትነው በትዕግስት፣ በትዕቢት ቢቀርበው በትሕትና፤ በፍቅረ ንዋይ ሊያታልለው ቢሞክር በጸሊአ ንዋይ ድል ነሣው፡፡ ዛሬ እነዚህን ማሳቻ መንገዶች ለይተን ጠላታችንን ድል መንሣት እንችላለን፤ ክርስቶስ ሳጥናኤልን ስለ እኛም ተዋጋው፤ በገሃነም ጣለው፡፡ በዮሐዋንስ ወንጌል ፲፮፥፴፫ ላይ “ስለዚህ እኔ ዓለምን ድል ነስቼዋለኹና ድል ንሱ” ያለበት ምክንያትም ጾም ደዌ ነፍስን ትፈውሳለችና፡፡ የሥጋ ምኞትን አጥፍታ የነፍስን ረኃብ ታስታግሳለችና፤ ከዲያብሎስ ቁራኝነት በማላቀቅ ከክርስቶስ ጋር አንድ ታደርጋለች፡፡

እኛ ለምን እንጾማለን?

ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጾም ለነፍሳችን ካሳ እንደሆነን ሁሉ እየጾምን፤ ጠላታችን ሳጥናኤልን ድል ነሥተን አባቶቻችን የወረሱትን ርስት እንድንወርስ እንጾማለን፡፡ ጾም በመንፈሳዊ ሕይወት የመበልጸጊያና የሰውነት መሻትን ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አድርጎ የማቅረቢያ መንገድ ነው፡፡ በዚህም ጾም የወንጌልና የበጎ ሥራ ሁሉ መጀመሪያና የትሩፋት ጌጥ እንደሆነ ሁሉ፤ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው፤ አልፋና ኦሜጋ ልዑል እግዚአብሔር ለአዳም የሰጠው የመጀመሪያ ትእዛዙ ነው፡፡ ዘፍጥረት ፪፡፲፯ ላይ “ነገር ግን መልካሙንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና”፤ ብሎ ያዘዘው ትእዛዝ ይህ ነውና፡፡

ጾም ስንል፤ ፩ኛ እግዚአብሔርን የምንፈራበትና ከእግዚአብሔር ምሕረት የምንለምንበት መንገድ ነው፡፡

ዕዝራ ፰፡፳፫ ላይ “ስለዚህም ነገር ጾምን ወደ እግዚአብሔር ለመንን፤ እርሱም ተለመነን”፤ በማለት ጾም እግዚአብሔርን መለመኛ እና ጸሎታችንን እንዲሰማን የምናደርግበት መሣሪያችን መሆኑን በተግባር እንዳገኙ እንረዳበታለን፡፡

፪ኛ ኀዘናችንን እና ችግራችንን ለእግዚአብሔር የምንነግርበትና  የምናቀርብበት መንገድ ነው፡፡

ነቢዩ ኢዩኤልም ሕዝበ እስራኤልን ሐዘን በገጠማቸው ጊዜ፤ በመከራም ሳሉ ትንቢተ ኢዩኤል ፩፥፲፬ ላይ የነገራቸው ቃል “ጾምን ቀድሱ፤ ጉባኤውንም አውጁ፤ ሽማግሌዎችንና በምድር የሚኖሩትን ሁሉ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ቤት ሰብስቡ፤ ወደ እግዚአብሔር ጩኹ”፤ በማለት ወደ እግዚአብሔር መጸለይ እንደሚገባ ነግሮናል፡፡ ትንቢተ ኢዩኤል ፪፡፲፪ ላይም “እግዚአብሔር በፍጹም ልባችሁ በጾምም፣በለቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ፤ በጽዮን መለከትን ንፉ፤ ጾምንም ቀድሱ፤ ጉባኤውንም አውጁ”፤ በማለት ነግሮናል፡፡ ስለዚህ ለእግዚአብሔር በመብላት፣ በመጠጣትና በሥጋ ፍላጎት ሆነን የፍላጎታችን፣ የሰላማችንንና የአንድነታችን መሻት መጠየቅ የለብንም፡፡ መጀመሪያ እራሱ ክርስቶስ ማድረግ ያለብንን የተግባር ሥራ እንድንሰራ የነገረን ከችግራችንና ከሐዘናችን ለመላቀቅ በምድር ለምንኖር ሁሉ መጾም እንዳለብን እራሱ ባለቤቱ እግዚአብሔር በነቢያት አድሮ ነግሮናል፡፡

፫ኛ ስብራታችን የምንጠግንበትንና መልካም የሆነ ትውልድ የሚታነጽበት መሣሪያ ነው፤

ትንቢተ ኢሳያስ ፶፰፡፲፪ ላይ “ከድሮ ዘመን የፈረሱት ስፍራዎችህ ይሠራሉ፤ መሠረትህም ለልጅ ልጅ ዘመን ይሆናል፤ አንተም ሰባራውን ጠጋኝ የመኖሪያ መንገድንም አዳሽ ትባላለህ”፡፡ እንዲሁም በቁጥር ፭ ላይ “እኔ ይህንን ጾም የመረጥሁ አይደለሁም”፤ እንደዚችም ባለች ቀን ሰው ራሱን ማሳዘን እንደሌለበትና በዚህም ጾም ራሱን ቢያስገዛ በዚያን ጊዜ በእግዚአብሔር ይታመናል፤ በምድርም በረከት ላይ ይኖረዋል፤ እግዚአብሔርም በያዕቆብም ርስት ይመግበዋል፤ እርሱ እግዚአብሔር ተናግሯልና”፡፡

፬ኛ የአምልኮ መንገድ ነው፤

የሐዋርያት ሥራ ፲፫፡፩-፪ ላይ እንደተገለጸው መንፈስ ቅዱስ ለሥራ የጠራቸውን በርናባስንና ሳውልን ያሰናበቷቸውም በጾምና በጸሎት ነበር፡፡ በዚያም ጊዜም ከጾሙ፤ ከጸለዩ፤ እጃቸውንም ከጫኑ በኃላ አሰናበቷቸው፡፡ አንድ ሰው የአምልኮ መንገድ ሲጀምር መጾም መጸለይ እንዳለበት እራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረን፤ ጾም የአምልኮ መንገድ ስለሆነች ነው፡፡ ሐዋርያትንም የጠፋውን ትውልድ ለመፈለግ ሐዋርያዊ ጉዞ ከማድረጋቸው በፊት ጾመዋል፡፡

፭ኛ አጋንትን የምናወጣበት እና ርኩሳን መናፍስትን የምንዋጋበት መሣሪያችን ነው፤ማር ፱፡፳፱  ጌታችን ደቀመዛሙርቱ ማውጣት አቅቷቸው የነበረውን ጋኔን እርሱ ካወጣው በኋላ ወደ እርሱ ቀርበው “እኛ ልናወጣው ያልቻልን ስለምን ነው?” ብለው በጠየቁት ጊዜ ስለ እምነታቸው ማነስ መሆኑን ነገራቸው:: “ይህ ወገን በጸሎትና በጾም ካልሆነ በምንም ሊወጣ አይችልም’ ነው ያላቸው፡፡ ስለሆነም ያለ ጾምና ጸሎት አጋንንት ማውጣት አይቻልም፡፡ ጾምን እየነቀፉና እያጥላሉ እንዲሁም በተግባር ሳይጾሙ አጋንንት እናወጣለን ማለት፤ የአጋንንት መዘባበቻና መጫወቻ እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል፡፡

ዘወረደ እምላዕሉ አይሁድ ሰቀሉ፤ ከላይ(ከሰማይ) የወረደውን አይሁድ ሰቀሉት፤(ቅ/ያሬድ)

 

 

ዲያቆን አቢይ ሙሉቀን

በቦታ የማይወሰነው አምላክ ሥጋን በመዋሕዱ ወረደ፤ ተወለደ፤ ተሰደደ፤ ተራበ፤ ተጠማ፣ ተሰቀለ እየተባለ ይነገርለታል፡፡ የእኛን ሥጋ ተዋሕዶ ወደዚህ ዓለም መጥቶ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት በመወሰን ተወለደ፤ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ወንጌልን ዞሮ አስተማረ፤ በመስቀል ላይ መከራን ተቀበለ፤ ሞተ፤ተቀበረ፤ተነሣ፤ ዐረገ፡፡ ዘለዓለማዊ አምላክ በመሆኑም በሁለም ስፍራ ይኖራል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በዐቢይ ጾም እግዚአብሔር ሊመሰገንበት የሚገባውን ምስጋና በጀመረበት ክፍሉ “ሃሌ ሃሌ ሉያ ዘወረደ እምላዕሉ አይሁድ ሰቀሉ ወሚመ ኢያእመሩ እግዚአ ኵሉ ዘያሐዩ በቃሉ፤ ቅድመ ዓለም የነበረ፣ ዛሬም ያለ፣ ዓለምን አሳልፎ የሚኖር፤ ከላይ (ከሰማይ) የወረደውን አይሁድ ሰቀሉት፤” ብሏል፡፡ ነገር ግን  አላወቁም፤ በቃሉ የሚያድን የሁሉ ጌታ ነውና” በማለት ጾመ ድጓ በሚባለው ድርሰት ይገልጸዋል፡፡

በዚህ ክፍለ ንባብ ሊቁ ቅድመ ዓለም የነበረ፣ ዛሬም ያለ፣ ወደፊትም ዓለምን አሳልፎ የሚኖር እንደ ሆነ፣ እንዲሁ ስለ ልዕልናው በሰማያት የምትኖር ይባላልና ከሰማይ የወረደውን አይሁድ ሰቀሉት አለ፡፡ እርሱ ራሱ ለደቀ መዛሙርቱ የጸሎት ሥርዓት ሲያስተምራቸው “አባታችን ሆይ በሰማያት የምትኖር…” ብላችሁ ጸልዩ ብሎ የእርሱ አባትነት ሰማያዊ እንጂ ምድራዊ እንዳልሆነና ከምድራዊ አባት የተለየ እንደሆነ በማስረዳት “በሰማያት የምትኖር በሉኝ” አለ፡፡ ሊቁም ይህን መሠረት አድርጎ “ከሰማይ የወረደውን አይሁድ ሰቀሉት” አለን፡፡

ከሰማይ የወረደው ቅድመ ዓለም አብ ያለ እናት በማይመረመር ጥበቡ የወለደው ድኅረ ዓለም ድንግል ማርያም ያለ አባት በማይመረመር ጥበብ የወለደችው ኢየሱስ ክርስቶስ ወልደ አብ ወልደ ማርያም ነው፡፡ ሥጋዊ ልደት የሆነ እንደሆነ ከአባት ዘር ከእናት ደም ተከፍሎ ይወለዳል፡፡ የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ግን ከአብ ያለእናት፤ ከእናት ያለአባት ሲሆን  እንዲህ ነው ተብሎ አይመረመርም፡፡ በማይመረመር ልዩ ጥበብ ስለተወለደ ስለልዕልናው በሰማይ የምትኖር ይባላል፡፡ ዘበእንተ ዕበይከ ትትሜሰል በደመናት፤ ስለልዕልናህ በደመናት ትመሰላለህ እንዲል፤ ስለዚህ ከላይ ከሰማይ የወረደውን ማለት በልዕልና ያለውን የሚኖረውን አምላክ አይሁድ ሰቀሉት፡፡

የአይሁድን ግብዝነት የጌታን ሁሉን ቻይነትም ሲያስረዳን፤  “ምንም አላወቁም፤ የሰቀሉት በቃሉ የሚያድነውን የሁሉን ጌታ ነው” ይለናል፡፡ በማቴዎስም ወንጌል ፱፥፲፰ ታሪኩ ተመዝግቦ እንደምናገኘው የመቶ አለቃው ልጁ በታመመበት ጊዜ “እባክህ አድንልኝ” በማለት ተማጸነው፤ “እኔ መጥቼ አድንልኃለሁ” ብሎትም ነበር፡፡ የመቶ አለቃውም በበኩሉ ፍጹም እምነትን የተሞላ ስለነበር “ሁሉ ይቻልሃል፤ በቃልህ ብቻ ተናገር ልጄ ይድናል” ብሎ ስለሁሉን ቻይነቱ  በምሳሌ ተናገረ፡፡ ጌታም የመቶ አለቃውን እምነት አድንቆ እንደወደድክ ይደረግልህ አለው፤ ልጁም ተፈወሰ፡፡ ይህንም የሚያውቀው ሊቁ ቅዱስ ያሬድ “እግዚአ ኵሉ ዘየሐዩ በቃሉ የሚያድን የሁሉ ጌታ” በማለት ገልጾታል፡፡

እንግዲህ ቤተ ክርስቲያን ጌታ ከሰማየ ሰማያት መውረዱን፣ ከድንግል ማርያም መወለዱን፣ መሰደዱን፣ መጠመቁን፣ በገዳመ ቆሮንቶስ መጾሙን በአጠቃላይ የነገረ ድኅነት ጉዞ ብላ ትገልጸዋለች፡፡ ገዳመ ቆሮንቶስ ገብቶ ፵ መዓልት  ፵ ሌሊት ጾመ፡፡ የዐቢይ ጾም ሳምንት መግቢያ የሆነውን የመጀመሪያውን ሳምንት “ዘወረደ፤ ከሰማይ የወረደው አምላክ” በማለት ታስበዋለች፡፡

በዚህም ሳምንት ከሰማየ ሰማያት መውረዱን፣ ከድንግል ማርያም መወለዱን፣ ለዓለም ቤዛ ሲል መከራ መቀበሉን የምናስብበት ሳምንት ነው፡፡ ይህ ሳምንት ጾመ ሕርቃል በመባልም ይታወቃል፡፡ ጾመ ሕርቃል የተባለበትም ምክንያት ጌታችን የጾመው ፵ መዓልት ፵ ሌሊት ሲሆን እኛ ግን ፶፭  ቀናት እንጾማለን ፡፡  ይህም የሆነበት ምክንያት ጌታ ከጾመው ፵ ቀን በተጨማሪ ቅዳሜና እሁድ ለብቻው ተቆጥሮ አንድ ሳምንት፡፡ በመጨረሻ ያለው አንድ ሳምንት ሰሙነ ሕማማት በመሆኑ በመጀመሪያ ያለው አንድ ሳምንት ደግሞ ጾመ ሕርቃል ይባላል፡፡ ሐዋርያት፡- ጌታ ፵  መዓልት ፵  ሌሊት ከዘረጋ ሳያጥፍ ከቆመ ሳይቀመጥ ነው የጾመው፤ እኛ ደግሞ እሑድና ቅዳሜ አንጾምም በማለት በመጀመሪያ ያለውን አንድ ሳምንት ጨምረው ጹመውታል፡፡

ሌላው በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ ፲፭ እንደምናገኘው በ፯ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በኢየሩሳሌም ፎቃ፣ በሮም ደግሞ ሕርቃል የሚባሉ ነገሥታት ነበሩ፡፡ ይህ የኢየሩሳሌሙ ንጉሥ ፎቃ ጨካኝና ለክርስቲያኖች የማይራራ ሆነ፡፡ በዚህ ጊዜ ሕዝቡ፤ ለሮሙ ንጉሥ “እባክህ ከእንዲህ ካለው ጨካኝ ንጉሥ አድነን፤ እኛ ላንተ እንገዛለን” በማለት ይልኩበታል፡፡ እርሱም ለጊዜው ቸል ብሏቸው ቆይቶ ነበር፡፡ከዕለታት አንድ ቀን “ግዙራን ይነሥእዋ ለመንግሥትከ፤ ክርስቲያኖች መንግሥትህን ይወርሷታል” የሚል ራእይ አይቶ፤ ይህ የኢየሩሳሌሙ ንጉሥ ነው በማለት እንደገና የላካችሁብኝን ነገር አልረሳሁትም፡፡ ነገር ግን ሐዋርያት ነፍስ ያጠፋ ዕድሜ ዘመኑን ይጹም ብለዋልና፤ ያን ብፈራ ነው እንጂ አላቸው፡፡ እነሱም የአንድ ሰው ዕድሜ ፸ ፹ ነው፤ እኛ ተከፋፍለን እንጾምልሃለን ብለውት ጠላታቸውን አጥፍቶላቸዋል፡፡ እነሱም ተከፋፍለው አንድ ሳምንት ጹመውታል፡፡

ስለዚህም በንጉሡ በሕርቃል ምክንያት ስለተጾመ ጾመ ሕርቃል ይባላል፡፡ ታሪክ ያላወቁት አንድ ጊዜ ብቻ ጾሙ፡፡ ታሪክ ያወቁት ደግሞ ቀድሞም ሐዋርያት ጹመውታል በማለት መጾም ቀጥለዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ይህን መሠረት አድርጋ ከጌታ ጾም መግቢያ ላይ እንዲጾም ሥርዓት ሠርታለች፤ በመሆኑም ምእመናን ከጾሙ በረከት ያገኙ ዘንድ እንዲጾሙ ታስተምራለች፡፡ በዘመኑ ክርስቲያኖች ከጨካኙ ግዛት የዳኑበት ነው፡፡ ዛሬም ምእመናን ከጨካኙ ዲያብሎስ ፈተና፣ መከራና የጭካኔ አገዛዝ ነጻ የሚወጡበት ነውና ሊጾሙት ይገባል፡፡

በአጠቃላይ ይህ ጾም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ከሰማየ ሰማያት መውረድ፤ ከቅድስት ድንግል ማርያም መወለድና ወደዚህ ዓለም መምጣት የሚታሰብበት ስለሆነ “ዘወረደ” ተብሎ ተሰይሟል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ “እስመ ጾም ትፌውስ ቁስለ ነፍስ ወታጸምም ኵሎ ዘሥጋ ፍትወታተ፤ጾም የነፍስን ቁስል ታድናለች፤ የሥጋን ፍላጎትንም ታስታግሳለች፡፡” ጾመን፤ ጸልየን፤ የሚታገለንን የሥጋ ፍላጎት ለማስታገሥ፣ ነፍሳችንን ለማዳን፣  ከእግዚአብሔር ጋር ለመገናኘት፣ የኃጢአት ስርየት ለማግኘት ይህን ጾም በመጾም በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን እናገኝ ዘንድ እግዚአብሔር ይፍቀድልን፤ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

አእመረ አሸብር “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሔድ በቁጥጥር ሥር ዋለ

 

“የቅዳሴ ሥርዓት” እየፈጸምን ነው በማለት ሲያጭበረብሩ

                                                                                                                            በእንዳለ ደምስስ

 በጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በኑፋቄው ምክንያት የተወገዘው አእመረ አሸብር ከግብረ አበሮቹ ጋር በግለሰብ ቤት ውስጥ “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሔድ የካቲት ፲ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም በቁጥጥር ሥር ዋለ፡፡

 “መዳን በማንም የለም” በሚል ርእስ በ፳፻፲፩ ዓ.ም ባሳተመው የኑፋቄ መጽሐፉ በቅዱስ ሲኖዶስ ተወግዞ የተለየው አእመረ አሸብር በአርባ ምንጭ ከተማ በጫሞ ቀበሌ በግለሰብ መኖሪያ ቤት ውስጥ ከግብረ አበሮቹ ጋር ቅዳሴ እንቀድሳለን በማለት የቤተ ክርስቲያንን ንዋያተ ቅድሳት በመጠቀም ልብሰ ተክህኖ ለብሰው፣ ክክርስቶስ ሥጋና ደም ጋር የማይገናኝ ተራ ነገር በማቅረብ “ሥጋ ወደሙ” ነው በማለት፣ የመጾር መስቀል በመጠቀም “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሄዱ እንደነበር ከሥፍራው የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

     ከዓርብ የካቲት ፰ ቀን ጀምሮ እስከ እሑድ የካቲት ፲ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ጉባኤ ማዘጋጀታቸውንና ዓርብና ቅዳሜ የትምህርትና የምክክር ጉባኤ፣ እሑድ “ቅዳሴ” እናካሒዳለን በማለት ቀደም ብለው በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ በለቀቁት ማስታወቂያ እንዲሁም ከተማው ላይ ማስታወቂያ በባነር አሠርተው በይፋ መስቀላቸውን የዓይን እማኞች ገልጠዋል፡፡

         የሀገረ ስብከቱ የፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ኮሚቴ፣ የአርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ፣ የስብከተ ወንጌል ኃላፊዎች እንዲሁም ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን በመሆን ወደ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሄድ ጉዳዩን አሳውቀዋል፡፡ ብፁዕነታቸውም ቅዳሜ የካቲት ፱ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም “የቤተ ክርስቲያንን ንዋያተ ቅድሳትን ስለማስከበር” በሚል ለሚመለከታቸው አካላት ጉዳዩን ትኩረት ሰጥተው መፍትሔ እንዲፈልጉ ለአርባ ምንጭ ከተማ ፖሊስ ጽ/ቤት፣ ለአርባ ምንጭ ከተማ ፍትሕና ፀጥታ ጽ/ቤት፣ ለጋሞ ጎፋ ዞን ፍትሕና ፀጥታ ጽ/ቤት፣ ለጋሞ ጎፋ ዞን ፖሊስ መምሪያ ጽ/ቤት በደብዳቤ አሳውቀዋል፡፡

   ብፁዕነታቸው ለሚመለከታቸው አካላት በላኩት ደብዳቤም ከዚህ ቀደም በኑፋቄያቸው በሀገረ ስብከቱ ተወግዘው የተለዩ ግለሰቦች ቅዳሴ እንቀድሳለን በማለት ቤተ ክርስቲያን ላይ በማላገጥና የራሷን የሆኑትን ቅዳሴዋንና ንዋያተ ቅድሳቷንና ከራሷ ያገኙትን መዓርግ በመያዝና በመጠቀም በ፲/፮/፳፻፲፩ ዓ.ም ፕሮግራም ሊያካሔዱ ማሰባቸውን ያስረዳል፡፡ ፕሮግራም እንደሚያካሄዱም በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ በመልቀቅ ምእመናንና ቤተ ክርስቲያንን ያስቆጣ ድርጊት በአርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ሰበካ ጉባኤ የቀረቡ የሕዝብ አቤቱታዎች እንደደረሳቸው የገለጹት ብፁዕነታቸው የሚመለከተው አካል ለሰላም ሲባል ትልቅ ትኩረት በመስጠት መፍትሔ ሊሰጥ ይገባዋል በማለት አሳውቀዋል፡፡

ብፁዕነታቸው በተጨማሪም በዚሁ አቤቱታቸው “የዚህች ቤተ ክርስቲያንም ሆነ የሀገረ ስብከቱ አቋም ሰላምን መስበክ ነው” ያሉት ብፁዕነታቸው ከዚህች ቤተ ክርስቲያን እስከወጡ ድረስ የቤተ ክርስቲያኒቱን መገልገያ ንብረቶች (ንዋያተ ቅድሳት) ሥርዓቷንም ሆነ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ያገኙትን መዓርጋት ሊተዉና የራሳቸውን እምነት ሊያካሔዱ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ የራሳቸውን ፕሮግራም ማካሔዱን እንደማይቃወሙና የቤተ ክርስቲያን የሆኑትንም ንብረቶች እና ሥርዓቶች ሊመልሱ ይገባል ብለዋል፡፡

እሑድ ጠዋት በቦታው መረጃው የደረሳቸው የሕግ አካላት ባለመገኘታቸው ከፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ኮሚቴ፣ ከሰበካ ጉባኤ እንዲሁም ከስብከተ ወንጌል የተውጣጡ አባላትና ወጣቶች እንዲሁም ምእመናን ተሰባስበው ቅዳሴ ወደሚያካሔዱበት ቤት በመሔድ ግለሰቦቹ ሲጠቀሙባቸው የነበሩትን ንዋያተ ቅድሳት እንዲመልሱ ቢጠየቁም ፈቃደኛ ባለመሆናቸው የለበሱትን ልብሰ ተክህኖ በማስወለቅ፣ ከበሮ፣ መስቀል፣ መጻሕፍትና ሌሎች ንዋያተ ቅድሳት ይዘው ወደ አርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ሲመለሱ፣ የሕግ አካላትም በመድረስ ግለሰቦቹን በቁጥጥር ሥር በማዋል ወደ ፖሊስ ጣቢያ ተወስደዋል፡፡

ሰኞ ጠዋት የችግሩን አሳሳቢነት በመግለጽ አስፈላጊና ሕጋዊ መንገድ ተከትሎ የቤተ ክርስቲያኗ ጥያቄ እንዲመለስ በማለት በብፁዕነታቸው የተጻፈው ሁለተኛ ደብዳቤ በመያዝ ለሚመለከተው አካል ቢያመለክቱም የሚመለከተው አካል ደብዳቤውን ተቀብሎ ጉዳዩ ከባድ በመሆኑ ከዞኑና ከከተማው ኃላፊዎች ጋር መመካከር አለብን በማለቱ ክስ እስካሁን አለመመሥረቱ ተገልጿል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ሲኖዶስ እያከናወነ ስላለው  ጥረት ሲገልጹ “ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያናችን መገለጫ የሆኑትን ያሬዳዊ ዜማና ንዋያተ ቅድሳት ለማስጠበቅ ውይይቶችን ሲያደርግ እንደቆየና በአሁኑ ወቅትም የአእምሮ ንብረት በሚል ኮሚቴ ተቋቁሞ በጥናት ላይ ይገኛል” ብለዋል፡፡ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከትም በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አማካይነት የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ አዋቅሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ሥራዎችን እየሠራ እንደሚገኝ ለዝግጅት ክፍላችን ገልጠዋል፡፡

     በሕግ አካላት ቁጥጥር ሥር ውለው ከነበሩት ግለሰቦች ውስጥ አንዱ አእመረ አሸብር ሲሆን፣ ከዚህ ቀደም የሊቃውንት ጉባኤ አባል የነበረና በኑፋቄው ምክንያት የተወገዘ ግለሰብ  ነው፡፡ የካቲት ፲፩ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ጠዋት ከፖሊስ ጣቢያ እንደተለቀቁም የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

የቤተ ክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት እንዲከበሩ ሀገረ ስብከቱ          ለሚመለከታቸው አካላት የጻፈው ደብዳቤ

የነነዌ ሰዎች እምነት ንስሓና የጾም አዋጅ

 

መ/ር ቢትወደድ ወርቁ

ትንቢተ ዮናስ አራት ምዕራፎች ያሉት፤ እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚነሣ ትውልድ ሁሉ ሊማርበትና ራሱን ሊያስተካክልበት የተጻፈ ታላቅ የትንቢት መጽሐፍ ነው፡፡ በዚህ የነቢዩ ዮናስ መጽሐፍ የተጠቀሱት ነቢዩ ዮናስን ጨምሮ የነነዌ ሰዎች ፣ንጉሡ ፣ዮናስ በየዋህነት ከእግዚአብሔር ፊት ወደ ተርሴስ ሊኮበልልበት የተሳፈረበት መርከብ ባለቤቶች /መርከበኞች/ እና ሌሎች ፍጥረታት ዓሣ አንበሪው፣የባሕር ማዕበሉ፣እግዚአብሔር ነቢዩ ዮናስን ያስተማረበት ትልና ቅሉ ሁሉ የነነዌ ሰዎች በኃጢአት ምክንያት ከመጣባቸው የጥፋት ዋዜማ አንስቶ ከኃጢአት ተመልሰው መዓቱ በምሕረት ቊጣው በትዕግሥት እሰከ ተለወጠላቸውና ከቅጣቱም እስከዳኑበት ጊዜ ድረስ የነበራቸው ተግባርና እግዚአብሔር የሠራላቸው የቸርነት ሥራዎች የተገለጡበት መጽሐፍ ነው፡፡

  መጽሐፉም እያንዳንዱ ቢዘረዘር ትልቅ መጽሐፍም ሊወጣው የሚችል ከመሆኑ አንጻር ያን ወደ ቤተክርስቲያን መጥተን ሊቃውንቱንና መምህራንን በመጠየቅ እንዲሁም ሌሎች ምሥጢራትን የሚያብራሩ  ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ መረዳት እንችላለን፡፡ አሁን ግን ባለንበት ወቅት በግላዊ፤ ቤተሰባዊና ሀገራዊ አኗኗራችን ከገባንበትና ሊገጥመን ከሚችሉ ችግሮች አንጻር የነነዌ ሰዎችን ታሪክ መስተዋት አድርገን ራሳችንን እንመለከትበት ዘንድ ታሪካቸውን በአጭሩ መቃኘትና የንስሓ መንገዳቸውን መከተል ተገቢ ይሆናል ፡፡ በመጽሐፍ ያለው ታሪክ በሙሉ የተጻፈልን ለፍጹም ትምህርትና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀን እንሆን ዘንድ እንዲሁም ለተግሣጽ ልባችንንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ጥበብ ይጠቅማልና (፪ጢሞ ፫÷፲፮-፲፯)

                የነነዌ ሰዎች የጥፋት ዋዜማ

ለነነዌ ሰዎችና ለከተማይቱ ጥፋት ምክንያት ሊሆን የነበረው  ምን እንደነበር መጽሐፍ ሲነግረን “የእግዚአብሔር ቃል ወደ አማቴ ልጅ ወደ ዮናስ እንዲህ ሲል መጣ፤ ተነሥተህ ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ ክፋታቸውም ወደፊቴ ወጥቶአልና፤ በእርሷ ላይ ስበክ”(ዮናስ ፩÷፪ )ይላል፡፡ የነነዌን ከተማ “ታላቂቱ ከተማ” ያሰኛት ብልፅግናዋና እድገቷ ብቻ ሳይሆን በሥሯ የነበሩ ሰዎች ይፈጽሙ የነበረው ታላቅ ክፋት ነበር፡፡ስለዚህም የነዋሪዎቿ ክፋት እግዚአብሔርን አሳዝኖት ከክፋታቸው እንዲመለሱ የክፋት ሥራቸውን እንዲተውና ንስሓ እንዲገቡ ይነግራቸው ዘንድ ነቢዩ ዮናስን ወደ እነርሱ እንዲሄድ ላከው ፡፡ ባዕድ አምልኮትንና ጣዖትን ማስፈን፤ ለጣዖታት መስገድና መሠዋት ፣ ጥንቆላን ማስፋፋት ፣ሥር እየማሱ ቅጠል እየበጠሱ የሰዎችን አኗኗር ማጎሳቆልና ማዘበራረቅ ፣በዘፈንና አስረሽ ምችው ሰክሮ ዝሙትንና ሌሎች የሥጋ ፈቃዳትን በራስና በሌሎች ላይ ማንገሥ ነው፤ (ገላ ፭÷፲፯-፲፱)፡፡  የኃጢአት ሥራ  ከእግዚአብሔር ይልቅ ደስታና ተድላን በመውደድ ለዚያም በሰዎች መካከል ጠብን ከመዝራትና እንዲጋጩ ከማድረግ አንስቶ የራስን ጥቅም ብቻ በመመልከትም ማታለልን ሰዎች የሚጠፉበትንም መንገድ መቀየስና ለዚያም ቀንና ሌሊት በመትጋት ወደ ፍጻሜ ማድረስ ነው፤(ምሳ ፮÷፲፮-፲፱)፡፡ ክፉ ሰዎች የሚጠፉበትንና እግዚአብሔር የሚያሳዝኑበትን ሐሳብ ንግግርና ተግባራትን አጠቃሎ ይይዛል፡፡

   ክፋትንም የሚያደርግ ሁሉ በእግዚአብሔር  ዘንድ የተጠላ ነው፤ ዘዳ ፳፭÷፲፭፡፡  የነነዌ ሰዎችንም ለጥፋት ያቀረባቸውና ከተማይቱንም “በሦስት ቀን ውስጥ ትገለበጣለች” (ዮናስ ፫÷፬) እስከ መባል ያደረሳት ክፋታቸው ነው፡፡ ሰው ልቡናውን ከክፋት ካላራቀ ራሱም ይጠፋል፡፡ ክፋቱም በዙሪያው ላሉት ሁሉ ተርፎ ሌላ ጥፋትን ይወልዳል ፡፡ አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር በቀድሞው ዘመን ለእስራኤል ዘሥጋ ” ኢየሩሳሌም ሆይ ትድኚ ዘንድ ልብሽን ከክፉ ነገር እጠቢ”፤ (ኤር ፬÷፲፬ ) ማለቱም ለዚህ ነው፡፡ ዛሬም ከራሳችን አንስቶ ዙሪያችንን ስንመለከት እግሮቻችን ወደ ክፋት የሚሮጡ፤ እጆቻችንም ደምን ለማፍሰስ የሚፋጠኑና በራሳችንም የክፋት ሐሳብ እየተራቀቅን ጠቢባን ሆነናል የምንል ሰዎች በዝተናል (ምሳ ፩÷፲፮)፡፡ ልበ አምላክ ክቡር ዳዊት እንደተናገረውም “ከኃጢአታችን ተመልሰን ንስሓ ካልገባን ክፋታችን ይገድለናል”፤(መዝ ፴፫÷፳፩)፡፡ የነነዌ ሰዎች ጥፋታቸው እስኪነገራቸው ድረስ በኃጢአት ሥራ ጸንተው ይኖሩ እንደ ነበር፤ ዛሬም በክፉ ሐሳብ ንግግርና ተግባር ላይ ካለን እኛም በጥፋት ዋዜማ ላይ እንደሆን ልንረዳ ይገባናል ፡፡

                  የእግዚአብሔር ቸርነትና የንስሓ ጥሪ

የነነዌ ሰዎች በመጥፎ ምግባራቸውና ኃጢአታቸው ምክንያት ሊጠፉ ሲገባቸው የቸርነት ባለቤት አምላካችን እግዚአብሔር እንዳይጠፉ በነቢዩ ዮናስ አንደበት የቸርነቱን የንስሓ ጥሪ አሰምቷቸዋል፡፡ “ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ የምነግርህንም ስብከት ስበክላት”(ዮናስ ፫÷፪) እንዲል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን እኛ ከኃጢአታችን ከተመለስን ከስሕተታችን ተምረን ለመታረምና ሕይወታችንን ለማስተካከል ከፈቀድን እንደ ወጣችሁ፤ እንደ ጠፋችሁና እንደ ረከሳችሁ ቅሩ አይልም፡፡ በበደላችንና በኃጢአታችን ካሳዘነው ይልቅ በኃዘንና በጸሎት ፍጹም በሆነ ንስሓ ከተመለስን ይደሰታል፡፡ እርሱ ብቻ ሳይሆን ቅዱሳን መላእክቱም በሰማይ ይደሰታሉ፤ “ንስሓ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ ምክንያት በሰማይ መላእክት ዘንድ ታላቅ ደስታ ይሆናልና”(ሉቃ ፲፭÷፲) እንደተባለ፡፡ ስለሆነም ዛሬም በገባንበት የጥፋት መንገድ ፣ ተመቻችተንና ተደላድለን እየኖርን ካለንበት የኃጢአት መንደር በመውጣት ንስሓ በመግባት ሰላማዊ አኗኗርንና መንግሥተ ሰማያትን ገንዘብ እንድናደርግ ያስተምረናል ፡፡ “ንስሓ ግቡ፤ ኃጢአትም እንቅፋት እንዳይሆንባችሁ ከኃጢአታችሁ ተመለሱ፤ የበደላችሁትን በደል ሁሉ ከእናንተ ጣሉ፤ አዲስ ልብና አዲስ መንፈስም ለእናንተ አድርጉ፤ የእስራኤል ቤት ሆይ ስለምን ትሞታላችሁ ? የሟቹን ሞት አልፈቅድምና ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ስለዚህ ተመለሱና በሕይወት ኑሩ” (ሕዝ ፲፰÷፴-፴፪ )እንዲል፡፡ዛሬም ቢሆን በኃጢአት እየኖርን የሚታገሠን ንስሓ እንድንገባ ነው፤ (፪ጴጥ ፫÷፱) ንስሓ ካልገባንም ቅጣት መምጣቱ የማይቀር መሆኑን ልብ ማለት ይገባናል፤(ሮሜ ፲፩÷፳፪)፡፡

የነነዌ ሰዎች መመለስ

የነነዌ ሰዎች ንስሓ እንደማይገቡና በልባቸው ትዕቢት ሞልቶ፤ ከጀመረ ይጨርሰኝ ካፈርኩ አይመልሰኝ፤ብለው በበደላቸው ጸንተው እንደሚኖሩ ሰዎች አልሆኑም ፡፡ ኃጢአታቸውና በደላቸው እንዲሁም ንስሓ ካልገቡ ሊመጣ ያለው ጥፋት ሲነገራቸው በዙፋን ካለው ንጉሥ በዐደባባይ እስካለው ችግረኛ ሁሉም በአንድነት ሆነው ነቢዩ ዮናስ የሰበከውን የንስሓ ስብከት በልቡናቸው አምነው ተቀበሉ፡፡ ማመናቸውንም ከንጉሣቸው ጋር በመሆን ለጾም አዋጅ በመንገር ገለጡ፡፡ እምነታቸውንና ጾማቸውንም በንስሓ አጅበው አለቀሱ፡፡በዚህም እግዚአብሔር ቊጣውን በትዕግሥት መዓቱን በምሕረት ለወጠላቸው ፡፡

 “የነነዌ ሰዎችም እግዚአብሔርን አመኑ፤ ለጾም አዋጅ ነገሩ፤ ከታላቁ ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ፤ንጉሡም ከዙፋኑ ተነሥቶ መጎናጸፊያውን አውልቆ ማቅም ለበሰ፤ በአመድም ላይ ተቀመጠ” (ዮናሰ ፫÷፭-፮) ተብሎ እንደ ተነገረ፡፡ ኃጢአታቸውን አምነው ንስሓ በማይገቡ ሰዎች እግዚአብሔር “የወደቁ አይነሡምን ? የሳተስ አይመለስምን ? ምን አድርጌሃለው ብሎ ከኃጢአቱ ንስሓ የገባ የለም …”(ኤር ፰÷፬) በማለት ይገረማል፤ ይደነቃልም፡፡ የነነዌ ሰዎች ግን በእምነታቸው፤በንስሓቸውና በጾማቸው እግዚአብሔርን አስደሰቱት፡፡ በዚህም በሐዲስ ኪዳን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ንስሓ በማይገቡ ላይ እንደሚፈርዱ ሲመሠክርላቸው “የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነሥተው ይፈርዱበታል፤ በዮናስ ስብከት ንስሓ ገብተዋልና ብሏል”፤ (ማቴ ፲፪÷፵፩)፡፡ ስለሆነም ከጥፋት እንድንድን ከክፉ ሐሳባችን፤ ንግግራችንና ተግባራችን ተመልሰን ንስሓ እንግባ ፡፡ “የንስሓ ኃዘን መዳንን፤ የዓለምም ኃዘን ሞትን ያመጣልና”፤(፩ ቆሮ ፯÷፲) እምነትን፤ ንስሓንና እውነተኛ ጾምን ገንዘብ አድርገን ለክብር ለመብቃት እንድንችል እግዚአብሔር በቸርነቱ ይርዳን፤ እመቤታችንም በምልጃዋ፤ ቅዱሳንም ሁሉ በጸሎታቸው አይለዩን አሜን!!

የሩቅ ምሥራቅ ግንኙነት ጣቢያ በህንድ ሀገር ፭ተኛ ዙር ሐዊረ ሕይወት አደረገ

         ሕይወት ሳልለው

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ  የማኅበረ ቅዱሳን የሩቅ ምሥራቅ ግንኙነት ጣብያ በህንድ ሀገር የሚኖሩ አባላቱንና ምእመናንን በማስተባበር ከጥር ፲፭ እስከ ጥር ፳፩ ቀን  ፳፻፲፩ ዓ/ም ወደ ኬሬላ ፭ተኛውን ዙር የሐዊረ ሕይወት ጉዞ አካሄደ፡፡

በአባ ጂኦ ዮሴፍ መሪነት ፺፱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች መንፈሳዊ ጉዞ አድርገዋል፡፡ በህንድ ኬሬላ ግዛት ኮታይም ከተማ ወስጥ በሚገኙ ቅዱስ ጊዮርጊስና የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን  ማርታ ማርያም ኦርቶዶክስ ሴርያን ቤተ ክርስቲያን፣ የመነኮሳት ገዳም፣ ማር ባስልዮስ ገዳም እንዲሁም የኦርቶዶክስ ቲኦሎጂካል (ነገር መለኮት) ሴሚናሪ እና የማር ባስልዮስ ክርስቲያን የኢንጅነሪንግና ቴክኖሎጅ ኮሌጅንም በዋነኛነት ጎብኝተዋል፡፡

ኮትያም ወደሚገኘው ኦርቶዶክስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በተደረገው ጉዞ ላይ ለምእመናኑ፤ “የቤተ ክርስቲያን ምሥጢራት” በሚል ርእስ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ከህንድ ቤተ ክርስቲያን ጋር ያነጻጸረ ትምህርት በዶ/ር ረጂ ማቲው ተሰጥቷል :: በዚሁ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተማሪዎች የበገና መዝሙርና በህንዳውያን ዘማሪዎች በህንድ ቋንቋ የተዘጋጀ መዝሙር በጋራ ቀርቧል፡፡ በጉዞው ላይ የነበሩት አባ ኦ ቶማስም “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በባህልና በበርካታ ንዋያተ ቅድሳት የታጀበች ናት” ሲሉ አድነቀዋል፡፡  በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው ዘቫላካራ ማርታ ማርያም ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በቀድሞው የኢትዮጵያ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እንደተጎበኘ አባ ጂኦ ለምእመናኑ አስታውቀዋል፡፡፡፡

ከማእከሉ በአውቶብስ ሦስት ሰዓት፤ በጀልባ አንድ ሰዓት ተኩል የሚፈጀው እና በደሴት ወደተከበበው የቅዱስ ቶማስ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጉዞም ያደረጉ ሲሆን ቤተ ክርስቲያኗ በቁጥር ትንሽ አባላት እና ጥቂት አገልጋይ እንዳሏትም አስገንዝቧቸዋል፤ ከዚህ ባሻገር በቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በወቅቱ ሲጠቀሙበት የነበሩት ባህላዊ ቅርሶችና ንዋየ ቅድሳትን ጎብኝተዋል፡፡ የጉዞው ተሳታፊዎችም “ከቦታው በረከትን አግተኝናል” ሲሉም የምስክርነታቸውን ቀል ሰጥተዋል፡፡

በከበሮ፣ በጸናጽል፣ በመቋሚያና በበገና ህብር የቀረበው ያሬዳዊ ዝማሬ መርሐ ግብር ላይ ሰፊ ማብራሪያ የሰጠው መ/ር ሳምሶን ስለመሳሪያዎቹ ለህንድ አባቶችና ለምእመናን ገለጻ አድርጓል፡፡ ስለአጠቃላይ መርሐግብሩ ከተሳታፊዎች ሐሳብ ተሰብስቦ፣ የአጋጠማቸው ችግሮች ላይ ውይይት በማድርግና የመፍተሔ አቅጣጫ በመስጠት፣ ፭ተኛው ዙር ሐዊረ ሕይወት  በሰላም ተጠናቋል፡፡

 

 

በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ለስብከተ ወንጌል የሚሰማሩ ሰባክያነ ወንጌል ተመረቁ

 

                               ተመራቂዎች በከፊል

በእንዳለ ደምስስ

  በማኅበረ ቅዱሳን አዳማ ማእከል ሥር የሚገኘው የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል ከአዳአ ወረዳ ቤተ ክህነት፤ ከበጎ አድራጊ ምእመናንና ማኀበራት ጋር በመተባበር በሁለተኛ ዙር ገጠር ተኮር የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማጠናከር በአፋን ኦሮሞ ቋንቋ ለ፰ ወራት በሂዲ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወካህን መልከ ጼዲቅ አብያተ ክርስቲያናት ያሰለጠናቸውን ፴፬ ተተኪ ሰባክያነ ወንጌል ጥር ፭ ቀን ፳፻፲ወ፩ ዓ.ም የአድአ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቀ ካህን፤የየአጥቢያዎቹ አስተዳዳሪዎች፣ በጎ አድራጊ ምእመናንና የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል አባላት በተገኙበት አስመረቀ፡፡

ሰልጣኞቹ ከ፲ አጥቢያዎች የተመለመሉ ሲሆን፣፱ የትምህርት አይነቶችን ሲከታተሉ መቆየታቸውን፣አብዛኛዎቹ ሰልጣኞችም ካህናትና ዲያቆናት መሆናቸው አቶ ሀብታሙ ዘውዱ የወረዳ ማእከሉ ሰብሳቢ በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት ገልጸዋል፡፡ካህናቱና ዲያቆናቱ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ስልጠናውን መውሰዳቸውም ለወደፊቱ ከስብከተ ወንጌል አገልግሎት በተጨማሪ የቤተ የመቅደስ አገልግሎትን ለማጠናከር መልካም አጋጣሚ እንደሆነና አብያተ ክርስቲያናቱም ለሥልጠና የሚሆኑ ቦታዎችን በማመቻቸት የነበራቸው ተሳትፎ ታላቅ እንደነበር ጠቅሰዋል፡፡

“የሥልጠናው ዋና ዓላማ ምእመናን በሚያውቁት ቋንቋ በማስተማር ከነጣቂ ተኲላዎች ለመጠበቅ ነው፡፡ የሥልጠናው ሙሉ ወጪም ብር 123,348.90 (አንድ መቶ ሀያ ሦስት ሺህ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንትብር ከዘጠና ሳንቲም) በባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ የቀድሞ ግቢ ጉባኤ ተመራቂዎች የተሸፈነ ነው” ብለዋል፡፡ የቀድሞ ተመራቂዎቹ ያበረከቱት አስተዋጽኦ በአርአያነት የሚጠቀስ መሆኑን የጠቆሙት ሰብሳቢው ይህንን መልካም ተሞክሮ ሌሎችም ማኀበራት በመውሰድ ሊማሩበት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

ለተመራቂዎቹ ባስተላለፉት መልእክትም “ሰልጣኞች ከምረቃ በኋላ ትምህርት በቃን ሳትሉ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እግር ሥር  ቁጭ ብላችሁ መማር፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ ይገባችኋል፡፡ ዋናው ዓላማችሁንም ባለመዘንጋት ስብከተ ወንጌል ባልተስፋፋባቸው ቦታዎች እየተዘዋወራችሁ ቤተ ክርስቲያን የጣለችባችሁን ኃላፊነት እንድትወጡ ይጠበቅባችኋል” በማለት በሪፖርታቸው አስገንዝበዋል፡፡

የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል አባላት ከግልና ከማኀበራዊ ጉዳያቸው ቅድሚያ ለሥልጠናው ልዩ ትኩረት መስጠታቸው፣ የአዳአ ወረዳ ቤተ ክህነት ለአገልግሎት የሚያስፈልጉ ነገሮችን በማሟላትና ለአጥቢያዎች መመሪያ በመስጠት ስልጠናው የተሳካ እንዲሆን ታላቅ አስተዋጽዖ ማበርከታቸውን በመግለጽ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

የወረዳ ቤተ ክህነቱ ሊቀ ካህን መልአከ ፀሐይ ቀሲስ እንዳለ ሐረገወይን ባስተላለፉት መልእክትም የወረዳ ማእከሉ ለስበከተ ወንጌል አገልግሎት መስፋፋት የሚሰጠውን አገልግሎት አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ያሳሰቡ ሲሆን ለተመራቂዎችም “በቋንቋ ምክንያት የሚጠፋውን ትውልድ ከሞት ወደ ሕይወት የመመለስ አደራ አለባችሁ” ብለዋል፡፡

የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል ከአድአ ወረዳ ቤተ ክህነት፣ ከበጎ አድራጊ ምእመናንና ማኅበራት ጋር በመተባበር በአፋን ኦሮሞ ቋንቋ ተተኪ ሰባኪያነ ወንጌል ለማፍራት ፕሮጀክት ቀርጾ በመጀመሪያው ዙር በድሬ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ከ፰ አጥቢያዎች የተመለመሉትን ፳፫ ሰልጣኞችን ለስምንት ወራት አሰልጥኖ የካቲት ፳፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በአባቶች ቡራኬ አስመርቋል፡፡

ምንጭ፤ምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 26ኛ ዓመት ቊ8ቅጽ 26ኛ ቊጥር 398 ከጥር 1-15 ቀን2011ዓ.ም

 

 

 

በቃጠሎ የወደመውን ቤተ ክርሰቲያን ለመገንባት እንቅስቃሴ ተጀመረ

 

በእንዳላ ደምስስ

ጥር 15 ቀን 2011 ዓ.ም በቃጠሎ የወደመውን የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያንን ለመገንባት እንቅስቃሴ መጀመሩን ሊቀ ኅሩያን መ/ር ወጋየሁ ደምሴ የባሌ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ዋና ጸሐፊ ገለጹ፡፡

“በቃጠሎው ቤተ ክርስቲያኑ ሙሉ ለሙሉ ወድሞ ነው የደረስነው፡፡ ሕዝቡም ከፍተኛ ሐዘን ነው የተሰማው፡፡ ሁላችንም ልባችን ተሰብሮ በዕንባ ስንራጭ ነበር፡፡ ነገር ግን ሕዝቡ አልቅሶ ብቻ አልተበተነም፡፡ዕንባውን አብሶ ገንዘብ የማሰባሰቡን ሥራ በመጀመር የመፍትሔ እርምጃ ነው የወሰደው፡፡” ሲሉ የገለጹት የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ ናቸው፡፡ሀገረ ስብከቱ ካህናቱን፣ የሰበካ ጉባኤ አባላትን፣ የወረዳ ቤተ ክህነት ተወካዮችንና የሀገር ሽማግሌዎችን በማሰባሰብ ዘጠኝ አባላት ያሉት የሕንጻ አሰሪ ኮሚቴ በማዋቀር ቤተ ክርስቲያኑን በድጋሚ ለመገንባት ገንዘብ የማሰባሰብ ሥራው መጀመሩንና እስከ አንድ ሚሊዮን ብር ማሰባበሰብ መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡

ከገንዘብ በተጨማሪም ምእመናን የአንገት ሐብላቻውንና የጣት ቀለበታቸውን በመስጠት፣ እናቶች ከመቀነታቸው እየፈቱ በመንፈሳዊ ስሜትና ቁጭት አቅማቸው የፈቀደውን ያህል ማበርከታቸውን ለዝግጅት ክፍላችን ተናግረዋል፡፡

ሙስሊሙ ኅብረተሰብም በቤተ ክርሰቲያኑ መቃጠል ከፍተኛ ሐዘን እንደተሰማውና በቦታው በመገኘት ገንዘብ በመለገስ፣ እንዲሁም የግንባታ እቃዎችን ለመስጠት ቃል በመግባት መሳተፋቸውን፣ ቤተ ክርስቲያኑን ለማሠራትም በመስጊድ ውስጥ ሙስሊሙን በማስተባበር ገንዘብ ለማሰባበስብ ጥረት እያደረጉ እንደሚገኙ የሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ዋና ጸሐፊ ተናግረዋል፡፡

“በዛሬው ውሏችንም ለተቋቋመው የሕንጻ አሰሪ ኮሚቴ እወቅና ለመስጠት ሰበካ ጉባኤው ለወረዳው ቤተ ክህነት፣ የወረዳ ቤተ ክህነቱም ለሀገረ ስብከቱ ደረጃውን ጠብቆ በደብዳቤ በመጠየቅ እውቅና ተሰጥቷቸዋል፡፡” ያሉት ሊቀ ኅሩያን መ/ር ወጋየሁ የባንክ ሒሳብ (አካውንት) በመክፈትም ሕጋዊነት ባለው አሠራር ገቢ የማሰባሰብ ሂደቱ እንደቀጠለ ገልጸዋል፡፡

አገልግሎትን በተመለከተም ቤተ ክርስቲያኑ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ስላለው ከሰበካ ጉባኤውና ከሕንፃ አሰሪ ኮሚቴው ጋር በመመካከር አዳራሹን በማመቻቸት ሙሉ የቤተ ክርስቲያኑ አገልግሎት ማለትም ኪዳንና ቅዳሴ ሳይቋረጥ መቀጠሉንና የቃጠሎውን መንስኤ በተመለከተም የሕግ አካላት እያጣሩ መሆኑን ለዝግጅት ክፍላችን ገልጸዋል፡፡

በባሌ ሀገረ ስብከት የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ተቃጠለ

በእንዳለ  ደምስስ

በባሌ ሀገረ ስብከት ሮቤ ከተማና አካባቢው ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር የሚገኘው የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ጥር 15 ቀን 2011 ዓ.ም ከረፋዱ 5፡00 ሰዓት ላይ ለጊዜው ባልታወቀ መንስኤ መቃጠሉን መ/ር ያሬድ ገ/ማርያም የወረዳው ቤተ ክህነት ጸሐፊ ገለጹ፡፡

የቃጠሎው መንስኤና የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ በመጣራት ላይ እንደሚገኝ የገለጹት መ/ር ያሬድ፤ ቤተ ክርስቲያኑ በቃጠሎው ምክንያት ሙሉ ለሙሉ መውደሙንና በአገልጋዮችና በአካባቢው ምእመናን ጥረት ታቦቱን ብቻ ማዳን መቻሉን ለዝግጅት ክፍላችን ተናግረዋል፡፡ዝርዝሩን እንደደረሰን እናቀርባለን፡፡

 

በጥምቀት በዓል የሃይማኖት አባቶች የሰላም ጥሪያቸውን አስተላለፉ!

                                                                                                        ሕይወት ሳልለው
የጥምቀት በዓል አከባበር በጃንሜዳ እና በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት በድምቀት በተከበረበት ቀን፤ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ለቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ባስተላላፉት መልእክት ላይ ምእመናን በተለይም ወጣቶች በፍቅርና በመቻቻል መኖር እንዳለባቸው አሳሰቡ፡፡“የዛሬ ፵ ዓመት የሆነውን ዓይነት አካሄድና ታሪካዊ ስሕተት እንዳትፈጽሙ ተጠንቀቁ! የምትሹትንና የምትመኙትን ማግኘት የምትችሉት አንድነትና ሰላም እስካለ ብቻ ነው፡፡ አርቆ በማየትና አስተውሎ በመራመድ፤በትዕግሥትና በመቻቻል ሳይሆን በኃይልና በጉልበት የምንፈልገውን ማግኘት እንችላለን ብላችሁ ከሆነ ሁሉንም ልታጡ ትችላላችሁና አስተውሉ!” በማለት ገልጸዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ፤ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ ፤ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን ጨምሮ፤እንዲሁም የባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶክተር ኂሩት ካሣው፤ ረ/ፕሮፌሰር ነቢዩ ባዬ የአዲስ አበባ ከተማ ባሕልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ኃላፊ እና ከተለያዩ ሥፍራዋች ለመጡ ምእመናን መልካም የጥምቀት በዓልን የተመኙት ፓትርያኩ፤ ይህ በዓል የንስሓ ጥሪ መሆኑንም አስታውሰዋል፡፡‹‹መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ››፤ብሎ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ እንዳስተማረን፤በዚህ አስከፊ ዘመን የንስሓን አስፈላጊነት መረዳትና መተግበር እንዳለብን አሳስበዋል፡፡
በዓለ ጥምቀት በዋነኛ የመዳን ሥርዓት መጀመሪያ መሆኑና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥር ፲፩ ቀን በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ እኛ እንድንጠመቅ እንዳስተማረን ‹‹ወውእቱ ያጠምቀክሙ በመንፈስ ቅዱስ ወበእሳት፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል፤››ተብሎ በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ ፫ ቁጥር ፲፮ ላይ እንደ ተገለፀውም ለእኛ ድኅነት ሆኖልናል፡፡

‹‹ጥምቀት ማለት ሰፋ ያለ ትርጒም ቢኖረውም ምሥጢራዊ ትርጒሙን ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው መንፃት፤መለወጥ፤ መሻገር፤ አዲስ ሕይወት፤ አዲስ ልደት፤ አዲስ ምሕረት የሚሉትን ሐሳቦች ያመሰጥራል›› በማለትም ቅዱስ ፓትርያርኩ አብራርተዋል፡፡ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ማርቶማ የሕንድ ማላንካራ ኦርቶዶክስ ሶርያ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ፤የቅዱስነታቸውን ሐሳብ በመደገፍ እንዲህ በማለት መልካም ምኞታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ማርቶማ

‹‹ይህ በዓል የብርሃን በዓል ቢሆንም እኛ እንደምናውቀው ዓለማችን በድቅድቅ ጨለማ የምትገኝ ሲሆን ለዚህ ጨለማ ብርሃን ያስፈልገዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለዓለም ተስፋ ናት፡፡ ምክንያቱም ይህን የመሰለ በዓል በየትኛውም ዓለም አይከበርምና፡፡እኛም በዚህ ታላቅ በዓል ወቅት በጸሎት ከእናንት ጋር ነን፤››በማለት ከማጽናናታቸውም በተጨማሪ በክርስቲያኖች መካከል መልካም የሆነና የጠነከረ ግንኙነት ሰላም እንዲኖር ያደረገ እግዚአብሔርን ዘወትር እንደሚያመሰግኑና እግዚአብሔር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንዲጠብቅልንና ኢትዮጵያን እንዲባርክ በመመኘት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የሊቃውንቱ ምንጭ እንዳይደርቅ ደቀ መዛሙርትን ማፍራት እንደሚገባ ተገለጸ

 

ተመራቂ ደቀ መዛሙርት

ዲ/ን ዘአማኑኤል አንተነህ

     የሊቃውንቱ ምንጭ እንዳይደርቅ ደቀ መዛሙርትን ማፍራት እንደሚገባ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርሰቲያን የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ገለጹ፡፡

ብፁዕነታቸው ይህንን ቃል የተናገሩት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በጎንደር ከተማ የደብረ ኃይል ወደብረ ጥበብ በዓታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ለሦስት ተከታታይ ዓመታት የአቋቋም ትምህርት ሲከታተሉ የቆዩ ፶፬ ደቀ መዛሙርት ጥር ፫ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም. ሲያስመርቅ ባስተላለፉት መልእከት ነው፡፡

በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስን ጨምሮ ብፁዕ አቡነ ዮሐንስ የብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ረዳት ሊቀ ጳጳስ የተገኙ ሲሆን፣ደቀ መዛሙርቱ ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ እጅ የአቋቋም የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ለደቀ መዛሙርቱ ባስተላለፉት መልእክት “እናንተ የምድር ጨው ናችሁ! ተመርቃችሁ ስትወጡ ብዙ ነገር ይጠበቅባችኋል፡፡ ጨው ሁናችሁ ዓለሙን የማጣፈጥ ኃላፊነት አለባችሁ” በማለት ተመራቂ ደቀ መዛሙርቱ በተማሩት ትምህርት ወንበር ዘርግተው በማስተማርና ለምእመናን ትምህርተ ወንጌልን በመስጠት በተለይም ለገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን በመድረስ የተጣለባቸውን አደራ እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

    ብፁዕነታቸው አያይዘውም “አሁን በዝታችሁ ትታያላችሁ፡፡ነገር ግን በአብያተ ክርስቲያናት ስትከፋፈሉ ቊጥራችሁ አነስተኛ ነው፡፡አሁንም ብዙ መሥራት፣መማር፣ ማስተማር እና የሊቃውንቱ ምንጭ እንዳይደርቅ ደቀ መዛሙርትን ማፍራት ይገባችኋል” ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ዮሐንስ በበኩላቸው “ህየንተ አበዊኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ፣ በአባቶችስ ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ” በማለት የቅዱስ ዳዊትን ቃል መነሻ በማድረግ ለደቀ መዛሙርቱ ባስተላለፉት መልእክት “እናንተ ደቀ መዛሙርት የዓለም ብርሃን ናችሁ፣ከዚህ ወጥታችሁ  አብያተ ክርስቲያናትን ሀገራችሁን በቅንነት በተሰጣችሁ አደራ እንድታገለግሉ አደራ እንላለን” ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የአቋቋም ምስክር ጉባኤ ቤቱ መምህር መጋቤ አእላፍ ክቡር ጥላሁን ያፈሯቸው ደቀ መዛሙርት የተማሩትን ትምህርት በተግባር ይተረጉሙ ዘንድ ከቤተ ክርስቲያን አባቶች ድጋፍ ሊደረግላቸው እንደሚገባ በመግለጽ “እነዚህ ደቀ መዛሙርት ዛሬ ተመርቀዋል፤ነገር ግን እየለመኑ ተምረው እየለመኑ መኖር የለባቸውም፡፡በርካታ ደቀ መዛሙርት ከትምህርት ገበታቸው የሚሰደዱት ሥራ አላገኝም እያሉ ነውና እንደ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ሁሉ ቅዱስ ሲኖዶስ በየቤተ ክርስቲያኑ የሚመደቡበትን መንገድ ቢያመቻች ጥሩ ነው” ሲሉ አሳስበዋል፡፡

ክቡር መምህር መጋቤ አእላፍ  በጉባኤ ቤቱ የሚታየውን ችግር ሲያስረዱም “ማኀበረ ቅዱሳን ለጉባኤ ቤቱ ዘመናዊ ቤት ሰርቶልናል ነገር ግን አሁንም የሠርከ ኀብስቱ እጥረት አሳሳቢ ስለሆነ ለተማሪው ፍልሰት ምክንያት እየሆነብን ነውና መፍትሄ እንሻለን፡፡ደቀ መዛሙርቱ የሚማሩት ከየሀገራቸው ትንንሽ ልጆችን እያስመጡ ልጆቹ በየመንደሩ በመንቀሳቀስ “በእንተ ስማ ለማርያም”ብለው ምግብ ያመጡላቸዋል፡፡እነሱ ደግሞ እነዚህን ልጆች ያስተምሯቸዋል፡፡ አብያተ ክርስቲያናት ለአብነት ትምህርት ቤቶች ከዚህ በላይ ትኩረት ሰጥታ መሥራት አለባቸው ”ሲሉ ገልጸዋል፡፡

 ማኀበረ ቅዱሳን ለጉባኤ ቤቱ ባለ ሁለት ፎቅ ሕንፃ በ፳፻፰ ዓ.ም ሠርቶ ያስረከበ ሲሆን፣ ከሕንፃው በተጨማሪ ለ፶፭ ተማሪዎች ለእያንዳንዳቸው በየወሩ የ፫፻፹፭ ብር ድጋፍ ያደርጋል፤ ቤተ ክህነትም ለ፴ ተማሪዎች ለእያንዳንዳቸው ፹፬ ብር በየወሩ ይደጉማል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ለጉባኤ ቤቱ ያሠራው ሕንፃም ቤተ መጻሕፍት፣ ክሊኒክ፣ የመምህር ቢሮ፣ ምግብ ቤት፣ መማሪያ ክፍልና መኖሪያ ለደቀ መዛሙርቱ ማሟላቱም በደቀ መዛመርቱ የምርቃት መርሐ ግብር ላይ ተገልጿል፡፡

ጉባኤ ቤቱ በርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን ያፈራ ሲሆን፤ ለአብነት ያህል አለቃ ገብረ ሐና፣መሪጌታ ሐሴት፣መሪጌታ ገብረ ማርያም፣ መሪጌታ ገብረ ዮሐንስ፣ መሪጌታ አሚር እሸቱ፣ መሪጌታ ላቀው፣ መምህር ክፍሌ ወልደ ፃድቅ፣ መጋቤ አእላፍ ሄኖክ ወልደ ሚካኤል እና አሁን በማስተማር ላይ የሚገኙት መጋቤ አእላፍ ክቡር ጥላሁን እና ሌሎችም ይጠቀሳሉ፡፡ በጉባኤ ቤቱም ማኅተሙን ለማግኘት ከሁለት እስከ ሦስት ዓመት ይፈጃል፡፡ በጉባኤ ቤቱ ከ፪፻ ያላነሡ ደቀ መዛሙርት በትምህርት ገበታ ላይ የሚገኙ ሲሆን፣ በየዓመቱም የደቀመዛሙርቱ ምርቃት አይቋረጥም፡፡

አሁን በማስተማር ላይ የሚገኑኙት መጋቤ አእላፍ ክቡር ጥላሁን ከመጋቤ እእላፍ ሄኖክ ወልደ ሚካኤል በ፲፱፻፺፯ ዓ.ም ወንበሩን በመረከብ እስከ አሁን ድረስ ከ፲፻ በላይ የሚሆኑ የአቋቋም መምህራንን አፍርተዋል፡፡

በብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ እና በብፁዕ አቡነ ዮሐንስ ትምህርተ ወንጌል እና ቃለ ምዕዳን፣ በተጨማሪም በደቀ መዛሙርቱ ቅኔ እና ያሬዳዊ ወረብ ቀርቧል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይም የሀገረ ስብከቱ የመምሪያ ሓላፊዎች፣ የአብነት መምህራን እና ምእመናንም ተገኝተዋል፡፡