‹‹ከክፉ መንገዳችሁ ተመለሱ›› (ኤር.፲፰፥፲፩)
ሥነ ምግባር ሰዎች በዕለት ተዕለት ኑሮችን ውስጥ የምናሳየው ጠባይ ወይም ድርጊት፣ አንድን ነገር ለመሥራትና ላለመሥራት የሚወስኑበት ኅሊናዊ ሚዛን ነው፡፡ በጎ ሥነ ምግባር ክፉ የሆኑ ነገሮችን አስወግዶ ደግ የሆኑትን መምረጥ መሥራት ሲሆን በተቃራኒው ክፉ ሥነ ምግባር ከበጎ ይልቅ ክፉ ነገሮችን መርጦ መሥራት ማለት ነው፡፡ ክፉ የሚለው ቃል የመልካም ነገር ተቃራኒ፣ የበጎ ነገር መጥፋት፣ ሐሰት፣ ኃጢአት፣ በሰው ልጅ ላይ የሚደርስ የሥጋና የነፍስ መከራ ተብሎ ሊተረጎም ይችላል፡፡ ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ክፉና በጎን መለየት እንዲችሉ አስቀድሞ በሕገ ልቡና ከዚያም በሕገ ኦሪት ከዚያም በሥጋ ተገልጦ የሰው ልጅ ሊኖር የሚገባውን ኑሮ ምሳሌ አርአያ ሆኖ አሳይቶናል፡፡