ኖላዊ ኄር
ታኅሣሥ ፳፯፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
ቸርነትና ምሕረት የባሕርይ ገንዘቡ የሆነ ትዕግሥቱ የበዛ፣ የዓለም ቤዛ፣ መድኃኔ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ቸር እረኛችን ነው፡፡ “አነ ውእቱ ኖላዊ ኄር፤ መልካም እረኛ እኔ ነኝ” በማለት እንደ ነገረን ቸር ጠባቂያችን ነው፡፡ (ዮሐ.፲፥፲፩)
የሰው ዘርም መከራና ፍዳ ከመላባት ጸአር ገአር ከበዛባት ከዚህች ምስቅልቅል እና አስከፊ ምድር በሰላም ተለይቶ የነፍስን ዕረፍት የሚያገኘው እንዲሁም መንግሥተ ሰማያትን የሚወርሰው በእውነተኛው የበጎች እረኛ እንደሆነ እራሱ ባለቤቱ ነግሮናል፡፡ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ እኔ የበጎች በር ነኝ። ከእኔ በፊት የመጡ ሁሉ ሌቦችና ወንበዴዎች ናቸው፤ ዳሩ ግን በጎቹ አልሰሙአቸውም። በሩ እኔ ነኝ፤ በእኔ የሚገባ ቢኖር ይድናል፥ ይገባልም ይወጣልም መሰማርያም ያገኛል። ሌባው ሊሰርቅና ሊያርድ ሊያጠፋም እንጂ ስለ ሌላ አይመጣም፤ እኔ ሕይወት እንዲሆንላቸው እንዲበዛላቸውም መጣሁ።
….መልካም እረኛ እኔ ነኝ። መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል። እረኛ ያልሆነው በጎቹም የእርሱ ያልሆኑ ሞያተኛ ግን ተኵላ ሲመጣ ባየ ጊዜ በጎቹን ትቶ ይሸሻል፤ ተኵላም ይነጥቃቸዋል በጎቹንም ይበትናቸዋል። ሞያተኛ ስለ ሆነ ለበጎቹም ስለማይገደው ሞያተኛው ይሸሻል። መልካም እረኛ እኔ ነኝ፥ አብም እንደሚያውቀኝ እኔም አብን እንደማውቀው የራሴን በጎች አውቃለሁ የራሴም በጎች ያውቁኛል፤ ነፍሴንም ስለ በጎች አኖራለሁ። ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምፄንም ይሰማሉ፥ አንድም መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ” እንዲል፡፡ (ዮሐ.፲፥፯-፲፮)
ቸሩ መድኃኔዓለም ከዚህ ዓለም የኃጢአት ማዕበል ስጥመት ጠብቆ፣ ካለንበት ችግርና መከራ አውጥቶ፣ ወደ ሰላማዊ መንገድ መርቶ፣ በሃይማኖት አጽንቶ፣ የነፍስን ዕረፍት፣ መንፈሳዊ ፍሬ እንድናፈራ፣ ርስተ መንግሥተ ሰማያት እንድወርስ ይርዳን፤ አሜን!
ስብሐት ለእግዚአብሔር!
