ቅዱስ ሩፋኤል

ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት

በዲያቆን ዮሴፍ ይኵኖአምላክ

ጳጕሜን ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወርኀ ጳጕሜን የዓለም ፍጻሜ መታሰቢያ ተደርጋ ትታሰባለች፡፡ በዚህ የተነሣ ምእመናን በጾምና በጸሎት (በሱባዔ) ያሳልፏታል፡፡ በተለይም በቅዱስ ሩፋኤል ዕለት ሰማያት የሚከፈቱበት (ርኅዎተ ሰማይ) መኾኑን በማመን ምእመናን ጸሎታቸውን ከምንጊዜውም በበለጠ ያቀርባሉ፡፡ ወደ ወንዞች በመሔድና በሚዘንበው ዝናብ ይጠመቃሉ፡፡ ወርኀ ጳጕሜን የጌታችን ምጽአት የሚታሰብባት በመኾኗ የሚዘመረው መዝሙር፣ የሚነበቡ ምንባባትና ቅዱስ ወንጌሉ እንደዚሁም የሚሰበከው ምስባክ ይህንኑ ምሥጢር የሚያሳዩ ናቸው፡፡

በወርኀ ጳጉሜን ከሚታሰቡ እና ከሚከበሩ በዓላት መካከል በየዓመቱ ጳጕሜን ፫ ቀን የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት በልዩ ልዩ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ይከበራል፡፡ የቅዱስ ሩፋኤል በዓሉ የሚከበርባቸው ምክንያቶችም ሁለት ናቸው፤ እነርሱም አንደኛው በዓለ ሢመቱን ምክንያት በማድረግ ሲኾን፣ ሁለተኛው ደግሞ ቅዳሴ ቤቱ ነው፡፡ ‹ሩፋኤል› የሚለው የስሙ ትርጓሜ ‹ደስ የሚያሰኝ፣ ቸር፣ መሐሪ፣ ቅን የዋህ› ማለት ነው፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል ያለ ማቋረጥ ፈጣሪያቸው ልዑል እግዚአብሔርን ከሚያመሰግኑ ቅዱሳን መላእክት አንዱ ነው፡፡ ‹‹ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ›› እንዲል (ጦቢት ፲፪፥፲፭)፡፡

የሰው ልጆች ከተያዙበት የኀጢአት ቍስል ይፈወሱ ዘንድ በአማላጅነቱና በጸሎቱ የማይለይ መልአክ ነው፡፡ ‹‹በበሽታ ላይ በሰው ልጆችም ቍስል ላይ የተሾመው ቅዱስ ሩፋኤል ነው›› በማለት ሄኖክ ከእግዚአብሔር መልአክ ያገኘውን የምስክርነት ቃል ጽፏል (ሄኖክ ፲፥፲፫)፡፡ ቅዱስ ሩፋኤል በሰውነታችን ላይ የሚወጣውን ደዌም ኾነ ቍስል ይፈውስ ዘንድ ከልዑል እግዚአብሔር ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ ‹‹በሰው ቍስል ላይ የተሾመ ከከበሩ መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው›› እንዳለ ሄኖክ (ሄኖክ ፮፥፫)፡፡ ለቈሰሉ ፈውስን የሚያሰጣቸው፤ ላረገዙ ሴቶች ረዳታቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሴት በፀነሰችበት ወቅት ቅዱስ ሩፋኤል አይለያትም፡፡ ሕፃኑ (ኗ በማኅፀን እያለ (ች) ተሥዕሎተ መልክዕ (በሥላሴ አርአያ መልኩ /ኳ/ መሳል) ከጀመረበት ቀን አንሥቶ እስከሚወለድበት ቀን ድረስ ቅዱስ ሩፋኤል በጥበቃው አይለያቸውም፡፡ በመውለጃቸው ቀን ሴቶች ከሚደርስባቸው ጭንቀትና ሕመም ስሙን ጠርተው ይማጸኑታል፡፡ ፈታሔ ማኅፀን ነውና ቅዱስ ሩፋኤልም ጭንቀታቸውን ያቀልላቸዋል፡፡

አስማንድዮስ የተባለ ጋኔን በወለተ ራጉኤል ላይ አድሮ ባሎቿን እየገደለ ቢያሰቃያት ቅዱስ ሩፋኤል ጋኔኑን አስጨንቆ አስወጥቶላታል (ጦቢት ፫፥፰-፲፯)፡፡ ቅዱስ ሩፋኤል ‹‹ዳግመኛም እግዚአብሔር ሩፋኤልን፣ አዛዝኤልን እጁን እግሩን አስረህ በጨለማ ውስጥ ጣለው አለው›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሄኖክ ፫፥፭-፯)፡፡ ለቃየን ልጆች ሰይፍና ሾተል መሥራትን፣ የምንዝር ጌጥ ማጌጥን፣ መቀንደብን ያስተማረ አዛዝኤል የተባለውን ጋኔን በእሳት ሰይፍ እየቀጣ በረቂቅ አስሮ ወደ ጥልቁ የጣለው ይኸው መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል ነው (ሄኖክ ፪፥፲፰)፡፡ የጦቢትን ልጁ ጦቢያን በሰው አምሳል ተገልጦ ከተራዳው በኋላ ወደ ሰማይ በሚያርግበት ጊዜ ራሱን ሲገልጥ ‹‹የቅዱሳንን ጸሎት ከሚያሳርጉ ወደ ከበረ ወደ ገነነ ወደ እግዚአብሔር ጌትነትም ከሚያገቡ ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ አላቸው›› (ጦቢት ፲፪፥፲፭)፡፡

በቅዱስ ሩፋኤል ተራዳዒነት ከተደረጉ ተአምራት መካከል በእስክንድርያ አቅራቢያ በምትገኝ ደሴት በታነጸች ቤተ ክርስቲያኑ ያደረገው ተአምር አንደኛው ነው፡፡ በመጽሐፈ ስንክሳር እና በድርሳነ ሩፋኤል እንደ ተጻፈው ብዙ ምእመናን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጠች፤ ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና፡፡ የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ዓሣ አንበሪው ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው፡፡ ምእመናኑም ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔር በከበረ መልአክ ሩፋኤል ስም ጮኹ፡፡ ያን ጊዜ ቅዱስ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ ‹‹እግዚአብሔር አዝዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጥ ጸጥ ብለህ ቁም!›› ባለው ጊዜ አንበሪው ጸጥ ብሎ ቆሟል፡፡ በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገልጠዋል፡፡ ለሕሙማንም ፈውስ ኾኗል፡፡ የቅዱስ ሩፋኤል ተራዳዒነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የ፳፻፲ ዓ.ም ዘመን መለወጫን አስመልክቶ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ የሰጡት ቃለ በረከት

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የ፳፻፲ ዓ.ም ዘመን መለወጫን አስመልክቶ የሰጡትን ሙሉዉን ቃለ በረከት እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ

ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዘተናገረ በበዓለ ርእሰ ዐውደ ዓመት ዘዕሥራ ምእት ወዐሠርቱ ዓመተ ምሕረት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

  • በአገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
  • ከአገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ
  • የአገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
  • በሕመም ምክንያት በየጠበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤
  • እንደዚሁም የሕግ ታራሚዎች ኾናችሁ በየማረሚያ ቤተ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

የዘመናትና የፍጥረታት ፈጣሪ የኾነው እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ከዘመነ ማቴዎስ ሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት ወደ ዘመነ ማርቆስ ሁለት ሺሕ ዐሥር ዓመተ ምሕረት በሰላም አደረሳችሁ፡፡

“አንሶስዉ እንዘ ብክሙ ብርሃን፤ ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ” (ዮሐ. ፲፪፥፴፭)

የብርሃን ጸጋ ለሰው ልጆች ወይም በአጠቃላይ ለፍጥረታት ዅሉ ከተሰጠው የእግዚአብሔር ስጦታዎች ትልቁ ነው፤ ብርሃን የሥራ መሣሪያ ነው፤ ብርሃን የመልካም ነገር ሁሉ ተምሳሌት ነው፡፡ እግዚአብሔር ራሱ በባሕርዩ ብርሃን ከመኾኑም ሌላ በእርሱ ዘንድ የማይጠፋ ብርሃን እንዳለ በቅዱስ መጽሐፍ ተገልጿል፡፡ የሰው ልጅ ከወዲያ ወዲህ፣ ከወዲህ ወዲያ ተንቀሳቅሶ፣ ነግዶ፣ አርሶ፣ ሠርቶ፣ ተምሮና አስተምሮ ለኑሮው የሚያስፈልገውን ዅሉ ለማግኘት ብርሃን የግድ ያስፈልጋል፡፡

ከዚኽም ጋር ሙሉ ጤና፣ ቀና የኾነ አእምሮ፣ ሰላምና ፍቅር ለሰው ልጅ ብልጽግና ወሳኝ ቦታ አላቸው፡፡ እነዚህ በሰው ልጅ መንፈሳዊና ሥጋዊ ሕይወት ላይ ያላቸው ጸጋ እጅግ የላቀ በመኾኑ በቅዱስ መጽሐፍ አገላለጽ ብርሃን እየተባሉ ይጠቀሳሉ፡፡ እንደዚሁም ዕድሜና መልካም ዘመን በተመሳሳይ አገላለጽ ብርሃን ተብሎ ይመሠጠራል፡፡ ምክንያቱም ብርሃን በሌለበት ኹኔታ ምንም ሥራ መሥራት እንደማይቻል ሰላማዊ ዘመን ከሌለም ልማትና ዕድገት ማስመዝገብ አይቻልማና ነው፡፡ በመኾኑም ዕድሜና ዘመንም ሌላው ታላቁ የእግዚአብሔር ብርሃን ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ” ሲል የዕድሜና የጊዜ ብርሃንነትን ማመልከቱ እንደ ኾነ ዐውደ ምንባቡ በግልጽ ያሳያል፡፡ ምክንያቱም እርሱ በዚኽ ዓለም በመምህርነት የተገለጸበት ዘመን ወደ መጠናቀቁ እየተቃረበ በነበረበት ጊዜ የተናገረው ከመኾኑ ጋር ባለችው አጭር ጊዜ የትምህርት ዕድሜ ወይም ዘመን ሰዎች በእርሱ ብርሃንነት እንዲያም የቀሰቀሰበትና ያስተማረበት ትምህርት ነው፡፡ በእርግጥም ላስተዋለውና በሥራ ለተጠቀመበት ጊዜ ታላቁ ብርሃን ነው፡፡ ጊዜ ሲቀና ነገሩ ዅሉ ብርሃን ይኾናል፡፡ ጊዜው ከጨለመ ደግሞ ዙሪያው ዅሉ ጨለማ ይኾናል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት

ዕድሜያችን ወይም ዘመናችን በሕይወታችን ውስጥ ለልማትም ኾነ ለጥፋት፣ ለጽድቅም ኾነ ለኀጢአት፣ ለትንሣኤም ኾነ ለውድቀት መሣሪያነቱ የታወቀ ነው፡፡ ምክንያቱም ዅሉም የሚሠራውና የሚከናወነው በጊዜው ነውና፡፡ በዘመናት ውስጥ ብርሃናውያን የኾኑ ዓመታት እንደ ነበሩ ዅሉ ጽልመታውያን የኾኑ ዓመታትም በአገራችንም ኾነ በሌላው ዓለም እንደ ነበሩ እናውቃለን፡፡ እነዚኽ ተቃራኒ የኾኑ ነገሮች በየፊናቸው ለሰው ልጆች ያተረፉት ስጦታም በስማቸው ልክ እንደ ኾነ ይታወቃል፡፡ ይኹን እንጂ ዘመናትን ብርሃውያን ወይም ጽልመታውያን እንዲኾኑ በማድረግ ረገድ የሰው ልጅ ሚና ትልቅ እንደኾነ የማይካድ ነው፡፡

የሰው ልጅ የማስተዋልና የመቻቻል፣ የመታገሥና የመወያየት፣ የፍቅርና የስምምነት፣ የሰላምና አንድነት ጠቃሚነትን ዘንግቶ በስሜትና በወቅታዊ ትኩሳት፣ እንደዚሁም እግዚአብሔርን የሰላም ድምፅ አልሰማ ብሎ በራስ ወዳድነትና በስግብግብነት ተሸንፎ ወደ ትርምስ ሲገባ ዘመኑ ጽልመታዊ መኾኑ አይቀሬ ነው፡፡ በሰው ችኩልና ደካማ አስተሳሰብ የተጨናነቀ ጽልመታዊ ዘመን ከውድመትና ከጥፋት በቀር አንዳችም ትርፍ እንደሌለው ከአገራችን ተሞክሮ የበለጠ መምህር አይኖርም፡፡

በሌላ በኩል ሰዎች ከእርስ በርስ ግጭት ተላቀው ሰላምንና ፍቅርን፣ አንድትንና እኩልነትን፣ መቻቻልንና መስማማትን፣ መወያየትንና መቀራረብን፣ ወንድማማችነትንና መከባበርን ያረጋገጠ፣ ትዕግሥትና አስተዋይነት የማይለየው የእግዚአብሔርን ድምፅ በመከተልና አእምሮን በማስፋት መኖር ሲጀምሩ ዘመኑ ብርሃናዊ እንደሚኾን፣ ልማቱና ዕድገቱም እንደሚፈጥንና እንደሚረጋገጥ አሁንም በአገራችን ወቅታዊ ተሞክሮ ተረድተዋል፡፡ ይኽ ዅሉ እውነታ የሚያሳየው የዘመን ብርሃንነትና ጽልመትነት የሚወሰነው እኛ ሰዎች በምናውጠነጥነው አስተሳሰብና በምናደርገው እንቅስቃሴ እንደ ኾነ ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ ለዚኽም ነው ሓላፊነቱም ተመልሶ ወደ እኛ የሚመጣው፡፡

ጌታችንም ምርጫውንና ውሳኔውን ለእኛ ትቶ “ብርሃን ስላላችሁ በብርሃን ተመላለሱ” በማለት ገለጻውንና ትምህርቱን ብቻ መናገሩ ከዚህ የተነሣ እንደ ኾነ ማስተዋል ይገባል፡፡ ከእነዚህ ከሁለቱ የሚሻለንን መምረጥና መከተል የእኛ ፈንታ ነው፡፡ ምርጫችን ሰላምና አንድነት ከኾነ ዘመኑ ብርሃን ነው፤ ተቃራኒው ከኾነ ደግሞ የኋልዮሽ ጉዞ ይኾናል፡፡ ስለ ኾነም ምርጫችን ሰላምና አንድነት እንዲኾን ዅላችንም ተስማምተን መወሰን አለብን፡፡

ማንም ሰው ብርሃንና ጨለማ ጎን ለጎን ቀርበውለት የትኛውን ትመርጣለህ የሚል ጥያቄ ቢቀርብለት ያለማመንታት ብርሃኑን እንደሚመርጥ ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ችግሩ ሰዎች ይህን ግልጽና ጠቃሚ ምርጫ ተቀብለው ተጠቃሚ እንዳይኾኑ ብዙ የሚያታልሉና በድብብቆሽ የሚመላለሱ አካላት በመካከሉ ይገቡና ጨለማውን ብርሃን፣ ብርሃኑንም ጨለማ አስመስለው ሰውን ወደ ገደል መክተታቸው ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ብርሃናዊና መልካም የኾነ ምርጫችንን ጥያቄ ውስጥ እንዲገባ ያድርጉታል፡፡ እኛ ሰዎች አእምሯችንን በሚገባ መጠቀም ያለብን እዚኽ ላይ ነው፡፡ ማለትም እኛው ራሳችን የሚጠቅመንና የማይጠቅመንን የመለየት ዓቅም ስላለን ዓቅማችንን ተጠቅመን ለዘላቂ ጥቅማችንና ለትክክለኛ ምርጫችን መወገን ይኖርብናል ማለት ነው፡፡

ሰዎች የኾን ዅላችን ባለ አእምሮዎች ኾነን ተፈጥረናል፡፡ አእምሮ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያመሳስለን ስለ ኾነ ከሀብት ዅሉ የበለጠ ሀብት ነው፡፡ ይህንን አእምሯችንን ካዳመጥነውና ከተከተልነው ሐቁን አይስትም፡፡ አመዛዝኖ፣ ገምግሞ፣ ለክቶ ጠቃሚውን ነገር ከልባችን ውስጥ ቁጭ ያደርግልናል፡፡ ነገር ግን ትዕግሥትን፣ ማገናዘብን፣ ቆም ብሎ ማሰላለሰልን፣ ምክንያታዊ መኾንን፣ ማመዛዘንን፣ ፈሪሀ እግዚአብሔርን፣ ፈቃደ እግዚአብሔርን መከተልን ይፈልጋልና እነዚኽን እንደ ግብአት አድርገን ልናቀርብለት ይገባል፡፡ ይህንን መጠቀም ስንችል የዘመናችንና የዕሜያችን ብርሃን ዋስትና ይኖረዋል፡፡ ጨለማም አያሸንፈውም፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት

ለዐሥር ዓመታት ያህል የተጓዝንበት የሦስተኛው ሺሕ ወይም ሚሊኒየም ዓቢይ ዘመን ለኢትዮጵያ አገራችን ብርሃናዊ ዘመን የፈነጠቀበት ወቅት ነው፡፡ ምክንያቱም በዚህ ዘመን ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ያልተነካ ሀብታችን እርሱም የዓባይ ወንዝ ሀብታችንን ለመቋደስ የሚያስችል ግዙፍ የልማት ሥራ ተጀምሮ ወደ መጠናቀቅ እየተቃረበ ያለበት እጅግ ብርሃናዊ ዘመን በመኾኑ ነው፡፡

በሠለጠነው የምዕራቡ ዓለም ካልኾነ በቀር በአፍሪካ ምድር ለዚያውም በድርቅ፣ በረኃብና በጦርነት ትታወቅ በነበረችው ኢትዮጵያ ይኾናሉ ተብለው የማይታሰቡ እጅግ ግዙፍ የኾኑና የሕዝባችንን መሠረታዊ የዕድገት ለውጥ የሚያረጋግጡ የኮንስትራክሽንና የኢንዱስትሪ፣ የትምህርትና የጤና ተቅዋማት በፍጥነት እየገሠገሡ መገኘት በዚህ ብርሃናዊ ዘመን የዕለት ተዕት ትእይንት እንደ ኾኑ በዓይን እየታየ ነው፡፡ ይኽ ጸጋ እንዲሁ ያለ መሥዋዕትነት የተገኘ ሳይኾን እኛ ኢትዮጵያውያን ከዅሉ በላይ ሰላምንና ልማትን መርጠን በአንድነት ወደ ብርሃናዊ አስተሳሰብ ስለ ገባን ነው፡፡ እግዚአብሔርም “በብርሃን ተመላሱ” ያለው ይኽን ለማመልከት ነውና በዚህ ምክንያት ትክክለኛ ምርጫችንን እርሱ ስለባረከልን የልማትና የዕድገት ተምሳሌት መኾን እንደቻልን አንስተውም፡፡

ዛሬም ወደማንወደውና ወደማንመርጠው ጨለማ ሊከቱን የሚሹ እንደ ኤች አይ ቪ ኤድስና ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር፣ እንደዚሁም በሕዝባችን መካከል መለያየትና መቃቃር ሊያስከትሉ የሚችሉ አፍራሽ ድርጊቶች ብቅ ብቅ በማለት እየተፈታተኑን እንደ ኾኑ መዘንጋት የለበትም፡፡ እነዚኽ ዅሉ በተግባር ያየናቸው የሕዝባችን ቀንደኛ ፀርና የጨለማ አበጋዞች፣ የልማታችንና የሰላማችን ዕንቅፋቶች ናቸውና ሕዝቡ በተለመደው ሃይማኖታዊና አርቆ ማሰብ ኀይሉ እንዲመክታቸው በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

በመጨረሻም

የዛሬ ዐሥር ዓመት “ታላቅ ነበርን ታላቅም እንኾናለን” በማለት ለሦስተኛው ሺሕ ወይም ሚሊኒየም ዓቢይ ክፍለ ዘመን የገባነውን ቃል በማደስ በአዲሱ ዓመት ካለፈው ዓመት በበለጠ ጠንክረን በመሥራት፣ ልማታችንንና ዕድገታችንን በፍጥነት በማሳደግ፣ የኤች አይ ቪ ኤድስ በሽታን ባለን የተሞክሮ አሠራር በመመከት፣ እንደዚሁም ሕገ ወጥ ዝውውርን፣ አገርንና ሕዝብን የሚጎዳ ድርጊትን በማክሸፍ፣ በሃይማኖትና በሰላም መርሕ በመመራት አዲሱን ዘመን ብርሃናዊ እንድናደርገው መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

አዲሱን ዘመን የሰላም፣ የፍቅርና የብልጽግና ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

መስከረም ፩ ቀን ፳፻ወ፲ ዓ.ም

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ዘመነ ክረምት – ክፍል ሰባት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ጳጕሜን ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! በክፍል ስድስት ዝግጅታችን አራተኛውን የዘመነ ክረምት ንዑስ ክፍል ማለትም ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን እና መዓልትን መነሻ አድርገን ወቅቱን ከሕይወታችን ጋር በማዛመድ መንፈሳዊ ትምህርት አቅርበን ነበር፡፡ በዚህ ዝግጅት ደግሞ አምስተኛውን የዘመነ ክረምት ንዑስ ክፍል (ቀዱስ ዮሐንስን) የሚመለከት አጭር ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ ይኹንላችሁ!

፭. ዮሐንስ

ከመስከረም ፩ – ፰ ቀን (ከዮሐንስ እስከ ዘካርያስ) ያለው አምስተኛው ክፍለ ክረምት ‹ዮሐንስ› በመባል ይታወቃል፡፡ ይህ ክፍለ ጊዜ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለማጥመቅ የተመረጠው፣ የዓዋጅ ነጋሪው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ትምህርቱ፣ ጥምቀቱ፣ ምስክርነቱ፣ አገልግሎቱ፣ ክብሩ፣ ቅድስናው፣ ገድልና ዕረፍቱ በአጠቃላይ ዜና ሕይወቱ ከአዲሱ ዓመት ጋር እየተጣጣመ የሚዳሰስበት የብሥራት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ሳምንት የቅዱስ ዮሐንስን አገልግሎት የሚመለከቱ ትምህርቶች በቤተ ክርስቲያን በስፋት ይቀርባሉ፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ አዲስ ዓመት በመጣ ቍጥር የቅዱስ ዮሐንስ ክብረ በዓልም አብሮ ይዘከራል፡፡

ሕዝበ ክርስቲያኑም ለአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን ‹‹ለቅዱስ ዮሐንስ በዓል እንኳን በሰላም አደረሳችሁ›› እያሉ መልካም ምኞታቸውን ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መግለጻቸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት የቅዱስ ዮሐንስ በዓል ከአዲስ ዓመት መባቻ ጋር በአንድነት ሲከበር ለመቆየቱ ማስረጃ ነው፡፡ ይኸውም የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ከጳጕሜን ፩ ቀን ጀምሮ በእስር ቤት ከቆየ በኋላ መስከረም ፪ ቀን በሰማዕትነት ዐርፏል፡፡ ቅዱሱ የሐዲስ ኪዳን አብሣሪ ነውና፣ ደግሞም ዕለቱ ቃል ኪዳን የተቀበለበት ቀን ነውና ስሙና ግብሩ ከዘመን መለወጫ ጋር አብሮ ይታወስ ዘንድ በዓሉ መስከረም ፩ ቀን በሥርዓተ ማኅሌት ይከበራል፡፡ ለዚህም ነው – ሊቃውንቱ ‹‹ርእሰ ዐውደ ዓመት ዮሐንስ ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ›› እያሉ የአዲስ ዓመት መጀመርያ፣ የመጥቅዕ እና አበቅቴ መነሻ መኾኑን በሚገልጽ ኃይለ ቃል ቅዱስ ዮሐንስን የሚያወድሱት፡፡

ታሪኩን ለማስታወስ ያህል ዮሐንስ ማለት ‹እግዚአብሔር ጸጋ ነው› ማለት ነው፡፡ ትርጓሜ ወንጌልም ፍሥሐ ወሐሴት (ተድላና ደስታ) ይለዋል፤ ወላጆቹ በእርሱ መወለድ ተደስተዋልና (ሉቃ. ፩፥፲፬)፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ የካህኑ ዘካርያስና የቅድስት ኤልሳቤጥ ልጅ ነው፡፡ ቅድስት ኤልሳቤጥ መካን (ካ ይጠብቃል) በመኾኗ እነዚህ የእግዚአብሔር ሰዎች ልጅ አልነበራቸውም፡፡ ልጅ ይሰጣቸው ዘንድም እግዚአብሔርን ዘወትር በጸሎት ይማጸኑት ነበር (ሉቃ. ፩፥፭-፯)፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን የካህኑ ዘካርያስ ጸሎቱ እንደ ተሰማና ሚስቱ ቅድስት ኤልሳቤጥ እንደምትወልድ፤ ስሙን ዮሐንስ እንደሚለው፤ በመወለዱ ብዙዎች እንደሚደሰቱ፤ ልጁም በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ እንደሚኾን፤ የወይን ጠጅና የሚያሰክር መጠጥ እንደማይጠጣ፤ እንደዚሁም ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ መንፈስ ቅዱስ እንደሚሞላበት የእግዚአብሔር መልአክ ለዘካርያስ ነገረው (ሉቃ.፩፥፰-፲፯)፡፡ በዚህ ቃለ ብሥራት መሠረት ቅዱስ ዮሐንስ ሰኔ ፴ ቀን ተወለደ፡፡ ሕፃኑ ዮሐንስም አደገ፤ በመንፈስም ጠነከረ፤ ለእስራኤል እስከታየበት ቀን ድረስ በምድረ በዳ ኖረ (ሉቃ. ፩፥፹)፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ፴ ዓመት ሲሞላውም በነቢዩ በኢሳይያስ ቃል ‹‹መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ!›› እያለ እየሰበከ በዮርዳኖስ ዙሪያ ወዳለው አገር ዅሉ ወጣ (ሉቃ. ፫፥፫-፮)። የይሁዳ አገር ሰዎች ዅሉ ኀጢአታቸውን እየተናዘዙ ከእርሱ ይጠመቁ ነበር። እርሱም ቃለ ወንጌልን ይሰብክላቸው ነበር (ሉቃ. ፫፥፯-፲፬)፡፡ በመጨረሻም ‹‹ድንበር አታፍርሱ፤ ዋርሳ አትውረሱ›› እያለ ንጉሡ ሄሮድስንና ሄሮድያዳን በመገሠፁ ምክንያት አንገቱን በሰይፍ ተቈርጦ በሰማዕትነት ዐርፏል፡፡ ካረፈ በኋላም የራስ ቅሉ ክንፍ አውጥቶ በዓለም እየተዘዋወረ ፲፭ አምስት ዓመት ወንጌልን አስተምሯል፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ምን ልታዩ ወደ ምድረ በዳ ወጣችሁ? … ነቢይን? አዎን ይህ ከነቢይም ይበልጣል።እነሆ መንገድህን በፊትህ የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁተብሎ የተጻፈለት እርሱ ነው፤ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም፤ ልትቀበሉትስ ብትወዱ ይመጣ ዘንድ ያለው ኤልያስ ይህ ነው፤ የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ›› በማለት የቅዱስ ዮሐንስን ታላቅነት ለሕዝቡ ተናግሯል (ማቴ. ፲፩፥፱-፲፩)። እንደዚሁም ቅዱስ ዮሐንስን ከነቢዩ ኤልያስ ጋር በማመሳሰል ስለ አገልግሎቱ አስተምሯል (ማቴ. ፲፩፥፪-፲፱)።

ሊቁም ከመላእክት፣ ከነቢያት፣ ከካህናት፣ ከሐዋርያት መካከል እንደርሱ መለኮትን ለማጥመቅ የተመረጠ አለመኖሩን በመጥቀስ ‹‹ዮሐንስ ከማከ ሶበ ፈተዉ ወጽሕቁ፤ እሳተ ነዳዴ ኢተክህሎሙ ያጥምቁ፤ ራጉኤል በትጋሁ ወኢዮብ በጽድቁ፤ ዮሐንስ ሆይ! ራጉኤል በትጋቱ፣ ኢዮብም በጽድቁ ቢመኙም ኾነ ቢጨነቁ እንደ አንተ የሚነድ እሳትን (መለኮትን) ሊያጠምቁ አልተቻላቸውም›› ብሎ ታላቅነቱን መስክሮለታል (መልክአ ዮሐንስ መጥምቅ፣ ለአዕይንቲከ)፡፡

በአጠቃላይ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ከአዲስ ኪዳን አበው አንዱ የኾነ፣ ንጹሓን ነቢያት፣ ቅዱስ ገብርኤልና አባቱ ዘካርያስ ትንቢት የተናገሩለት፣ ከሕፃንነቱ ጀምሮ ቅኑት እንደ ገበሬ፣ ጽሙድ እንደ በሬ ኾኖ እግዚአብሔርን ያገለገለ፣ በፍጹም ልቡ ዓለምን የናቀ፣ ከተድላዋና ከደስታዋም የተለየ፣ አምላክን ለማጥመቅ የታደለ ሐዋርያ፣ መምህር፣ ሰማዕት፣ ባሕታዊ፣ ነቢይ፣ ጻድቅ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ሰኔ ፴ ቀን የተወለደበት፤ መስከረም ፩ ቀን ቃል ኪዳን የተቀበለበት፤ መስከረም ፪ ቀን በሰማዕትነት ያረፈበት፤ ጥር ፲፩ ቀን ጌታችንን ያጠመቀበት፤ የካቲት ፴ ቀን ራሱ የተገኘችበት፤ ሚያዝያ ፲፭ ቀን ራሱ ያረፈችበት (ነፍሱ የወጣችበት)፤ ሰኔ ፪ ቀን ደግሞ ፍልሰተ ዐፅሙ (ዐፅሙ የፈለሰበት) በዓል በቤተ ክርስቲያናችን ይከበራል፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ ሕይወቱና ትምህርቱ፣ ያደረጋቸው ድንቆችና ተአምራት፣ እንደዚሁም እግዚአብሔር የሰጠው ቃል ኪዳንና አገልግሎቱን በሰማዕትነት መፈጸሙ በመጽሐፈ ስንክሳር፣ በትርጓሜ ወንጌል (ወንጌለ ሉቃስ) እና በገድለ ዮሐንስ መጥምቅ በሰፊው ተጽፏል፡፡

እንግዲህ እኛም እንደ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ከኀጢአት ተለይተን፣ ራሳችንን ለጽድቅ ሥራ አስገዝን፣ በንጽሕና ኾነን አዲሱን ዓመት ለመቀበል ከዅሉም በላይ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንዘጋጅ፡፡

ይቆየን

ወርኀ ጳጕሜን

በዲያቆን ዳንኤል ክብረት

ጳጕሜን  ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የኢትዮጵያን የዘመን አቈጣጠር ለየት ከሚያደርጉት ነጥቦች አንዱ ‹ጳጕሜን› የምትባል ዐሥራ ሦስተኛ ወር መኖሯ ነው፡፡ ‹ጳጕሜ› ማለት በግሪክ ቋንቋ ‹ጭማሪ› ማለት ሲኾን፣ ወርኀ ጳጕሜን ዓመቱ በሠላሳ ቀናት ሲከፈል የሚተርፉት ዕለታት ተሰባስበው የሚያስገኟት፤ ወይም በየዕለቱ በፀሐይና በጨረቃ አቈጣጠር መካከል የሚፈጠሩት ልዩነቶች ተሰባስበው የተከማቹባት ተጨማሪ ወር ናት፡፡ ወርኀ ጳጕሜን የቤት ኪራይና የወር ደመወዝ የማንከፍልባትና የማንቀበልባት፤ መብራትና ውኃ ግን ከነሐሴ ወር ጋር ጨምረው የሚያስከፍሉባት፤ ሲሻት አምስት፣ ሲያስፈልጋት ስድስት፣ አልፎ አልፎ ሰባት የምትኾን ወር ናት፡፡ ከዐሥራ ሁለቱ የኢትዮጵያ ወሮች መካከል ወርኀ ጳጕሜን በብዙ መንገድ የተለየች ናት፡፡ በአንድ በኩል በጣም ትንሿ ወር ናት፡፡ ሲቀጥልም ወርኃዊ በዓላት የማይውሉባት ወር ናት፡፡ ደግሞም ከሌሎች ወሮች በተለየ መልኩ የቀኖቿ መጠን የሚቀያየሩ ብቸኛ ወር ናት፡፡ ከሌሎች የኢትዮጵያ ወሮች በተለየም ስሟ ኢትዮጵያዊ ያልኾነ ወር ናት፡፡ በሁለት ዘመናት መካከል እንደ መሸጋገሪያ የምትታይም ናት፡፡

ዓመቱ በዐውደ ፀሐይ ሲለካ 365 ቀናት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ሲኾን፣ በጨረቃ ሲለካ ደግሞ 354 ቀናት ከ22 ኬክሮስ፣ ከ1 ካልዒት፣ ከ36 ሣልሲት፣ ከ52 ራብዒት፣ ከ48 ኀምሲት ነው፡፡ በሁለቱ አቈጣጠር መካከል (በፀሐይና በጨረቃ) በዓመት ውስጥ ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ7 ኬክሮስ ይኾናል፡፡ በዘመን አቈጣጠራችን ከዕለት በታች የምንቈጥርባቸው ስድስት መለኪያዎች አሉን፡፡ እነዚህም ኬክሮስ፣ ካልዒት፣ ሣልሲት፣ ራብዒት፣ ኀምሲትና ሳድሲት ናቸው፡፡ 60 ሳድሲት 1 ኀምሲት፣ 60 ኀምሲት 1 ራብዒት፣ 60 ራብዒት 1 ሣልሲት፣ 60 ሣልሲት 1 ካልዒት፣ 60 ካልዒት 1 ኬክሮስ ነው፡፡ 60 ኬክሮስ 1 ዕለት፤ 1 ኬክሮስ ደግሞ 24 ደቂቃ ነው፡፡ ወርኀ ጳጕሜንን ለማግኘት የሚረዳንም የየዕለቱን ልዩነታቸውን መመልከቱ ነው፡፡ በየዕለቱ በጨረቃና በፀሐይ መካከል ያለው የጊዜ ስሌት 1 ኬክሮስ ከ52 ካልዒት ከ31 ሣልሲት ይኾናል፡፡ ይህም ማለት 5 ሰዓት ከ48 ደቂቃ ከ46 ካልዒት ነው፤ ይህ ልዩነት በአንድ ወር ምን ያህል እንደሚደርስ ለማወቅ በ30 ብናበዛው 30 ኬክሮስ ከ1560 ካልዒት፣ ከ930 ሣልሲት ይኾናል፡፡ የዓመቱን ለማግኘት ደግሞ በ12 ብናበዛው 360 ኬክሮስ ከ18720 ካልዒት፣ ከ11160 ሣልሲት ይመጣል፡፡

360 ኬክሮስ ለ60 ሲካፈል 6 ዕለታትን ይሰጠናል፡፡ 18720 ካልዒትን በስድሳ በማካፈል 312 ኬክሮስን እናገኛለን፡፡ ይኸውም ትርፉን 12 ኬክሮስ ትተን 300ውን ኬክሮስ ለ60 በማካፈል 5 ዕለት እናገኛለን ማለት  ነው፡፡ ውጤቱም 5 ዕለት ከ12 ኬክሮስ ይኾናል፡፡ 11160 ሣልሲትን ለ60 ብናካፍለው 186 ካልዒት ወይም ደግሞ 3 ኬክሮስና 6 ካልዒት ይኾናል፡፡ ከላይ ኬክሮስን በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነው 6 ዕለት ‹ሕጸጽ› ይባላል፡፡ ፀሐይና ጨረቃን እኩል መስከረም አንድ ላይ ዓመቱን ብናስጀምራቸው ፀሐይ የወሯ መጠን ምንጊዜም 30 ሲኾን፣ ጨረቃ ግን በአንደኛው ወር 29፤ በሌላኛው ወር ደግሞ 30 ስለምትኾን ዓመቱ እኩል አያልቅም፡፡ የጨረቃ ዓመት የሚያልቀው ነሐሴ 24 ቀን ነውና፡፡ ይህም ማለት ጨረቃ በሁለት ወር አንድ ጕድለት ታመጣለች ማለት ነው፡፡

ይህንን ነው ሊቃውንቱ ‹ሕጸጽ› (ጕድለት) ያሉት፡፡ በዚህም መሠረት ከላይ ኬክሮሱን በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነውን 6 ዕለት ለጨረቃ ሕጸጽ ስንሰጠው የመስከረም (ጥቅምት) 1፣ የጥቅምት (ኅዳር) 2፣ የጥር (የካቲት) 3፣ የመጋቢት (ሚያዝያ) 4፣ የግንቦት (ሰኔ) 5፣ የሐምሌ (ነሐሴ) 6 ኾነው ተካፍለው ያልቃሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በጨረቃና በፀሐይ ዑደት መካከል በዓመት ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ይኾናል፡፡ ስድስቱን ዕለታት ጨረቃ ለምታጋድልበት ሕጸጽ ብንሰጠው ቀሪ 5 ዕለት ይኖረናል፡፡ ወርኀ ጳጕሜን ማለት እነዚህ 5 ቀናት ናቸው፡፡ የዐሥራ አንዱን ዕለታት ከፈጸምን ሽርፍራፊዎቹን (15 ኬክሮስና 6 ካልዒትን) እንመልከት፤ ከላይ እንደ ተጠቀሰው በፀሐይና በጨረቃ ዓመታት መካከል የተፈጠሩትን 11 ቀናት ስድስቱ ለሕጸጽ ማሟያ ሲገቡ የቀሩት 5 ዕለታት ናቸው ጳጕሜን የምትባለውን ወር ያስገኟት፡፡

በጎርጎርዮሳውያኑ አቈጣጠር እነዚህ 5ቱ ዕለታት በጃንዋሪ፣ ማርች፣ ሜይ፣ ጁላይና ኦገስት ላይ ስለ ተጨመሩ ወሮቹ 31 ሊኾኑ ችለዋል፡፡ ይኽን የከፈለው ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በ46 ዓ.ዓ የነበረው ዩልየስ ቄሣር ነው፡፡ ዩልየስ ለአራቱ ወሮች 30 ቀን፣ ለአንዱ 28 /29 (በየአራት ዓመቱ)፣ ለቀሩት ሰባት ወሮች ደግሞ 31 ቀን ሰጥቷቸዋል፡፡ አምስቱን ወሮች 31 ያደረጋቸው ከጳጕሜን ወስዶ ሲኾን ለሁለቱ ወሮች አንዳንድ ቀን የጨመረላቸው ደግሞ ከፌቡርዋሪ (የካቲት) 2 ቀናት ወስዶ ወሩን 28 በማድረግ ነው፡፡ ከእንግዲህ የሚተርፉት ከላይ የየዕለቱን ልዩነት በዓመት ስናባዛ የቀሩት 15 ኬክሮስና 6 ካልዒት ናቸው፡፡ ሁለቱን ከላይ ያገኘናቸውን ውጤቶች ስንደምራቸው (12 ኬክሮስ + 3 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት) 15 ኬክሮስ ከ 6 ካልዒት ይመጣሉ፡፡ 1 ዕለት 60 ኬክሮስ በመኾኑ 1 ዕለትን (60 ኬክሮስን) ለማግኘት ከላይ ያገኘነውን 15 ኬክሮስ በ4 ማባዛት ይኖርብናል፡፡

በአራት ዓመት አንድ ጊዜ ጳጕሜን 6 ቀን የምትኾነውም እነዚህ በየዓመቱ የተሰባሰቡ 15 ኬክሮሶች አንድ ላይ መጥተው በአራት ዓመት አንድ ጊዜ አንድ ዕለት ስለሚኾኑ ነው፡፡ እርሷም ሠግር (leap year) ትባላለች፡፡ ጎርጎርዮሳውያኑ ይኽቺን ሠግር በፌቡርዋሪ ወር ላይ ጨምረው ወሩን በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ 29 ቀን ያደርጉታል፡፡ 15ቱ ኬክሮስ በአራት ዓመት ተደምረው አንድ ዕለት መጡና በአራት ዓመት አንድ ጳጕሜን ስድስት ቀን እንድትኾን አድርገዋታል፡፡ የቀረችው 6 ካልዒትስ የት ትግባ ከተባለ ካልዒት አንዲት ዕለት ትኾን ዘንድ 3600 ካልዒት ያስፈልጋሉ፡፡ ይህንን ያህል ካልዒት ለማግኘት ደግሞ 600 ዓመታት ያስፈልጉናል፡፡ ከዚኽ ስሌት አኳያ ጳጕሜን በየስድስት መቶ ዓመታት ሰባት ቀን ትኾናለች፡፡

ጳጕሜን 5 ቀን በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ዘንድ ‹ዕለተ ምርያ› ወይም ‹የተመረጠች ቀን› ትባላለች፡፡ ሊቃውንቱ የጌታችንን ልደት ሲያሰሉባት የቆየችው ዕለት በመኾኗ ነው ይህንን ስያሜ ያገኘችው፡፡ የጌታችንን ልደት ቀን የምትወስነው የጳጕሜን 5ኛዋ ቀን ናት፡፡ በዓለ ልደት የሚውለውም ጳጕሜን 5 በዋለበት ቀን ነው፡፡ ለምሳሌ ዘንድሮ (2009 ዓ.ም) ጳጕሜን 5 ቀን እሑድ ይውላል፤ ስለዚህም በ2010 ዓ.ም የሚበረው በዓለ ልደት እሑድ ይኾናል ማለት ነው፡፡ በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ ጳጕሜን 6 ቀን ስትኾን ልደት በ28 የሚከበረውም በዓለ ልደት ጳጕሜን 5 ቀንን (ዕለተ ምርያን) ስለማይለቅ ነው፡፡ በዘመነ ዮሐንስ ስድስተኛዋ የጳጕሜን ቀን በዓለ ልደትን በአንድ ቀን ዝቅ ብሎ እንዲከበር ስለምታደርገው ልደትን ታኅሣሥ 28 ቀን እናከብራለን፡፡ ታድያ ምነው ጥምቀት፣ ግዝረትና ሌሎችም በዓላት አይለወጡም? ቢሉ ሊቃውንቱ የሚሰጡት ምላሽ ‹‹ትውልድ ሱባዔ እየቈጠረ በተስፋ የጠበቃት ዕለተ ልደትን ስለ ኾነ ነው፡፡ ሌሎቹ በዓላት የመጡት በልደቱ ምክንያት ነውና›› የሚል ነው፡፡

በጎርጎርዮሳውያን አቈጣጠርም በአራት ዓመት አንድ ጊዜ በዓለ ልደት ዝቅ ብሎ ይከበራል፡፡ የእነርሱ በግልጽ የማይታወቀው ጭማሪዋ ፌብርዋሪ (የካቲት) ላይ ስለምትኾን ነው፡፡ ይህ ደግሞ አዲሱን ዓመት ካከበሩ በኋላ ይመጣል፡፡ በእኛ አቈጣጠር ግን ጭማሪዋ የምትወድቀው ጳጕሜን መጨረሻ ላይ ስለ ኾነና ከአዲስ ዓመት በፊት ተደምራ ስለምትቈጠር ቍጥሯ ጐልቶ ይታወቃል፡፡ በአጠቃላይ ‹ጳጕሜን› የምትባለው አስገራሚዋና ትንሿ ወራችን እንዲህ በስሌት የተሞላች፣ በሦስት ዓመታት አምስት ቀን ኾና ቆይታ በአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ ስድስት፣ በየስድስት መቶ ዓመት ደግሞ ሰባት ቀን የምትኾን ወር ናት፡፡ እንደዚሁም ታላላቆቹ ወሮች ምንም ሳይፈጥሩ የልደትን ቀን የምትወስን፣ የዓመቱን ሠግር የምታመጣ፣ ታሪከኛ ወርም ናት፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡