ብዙኃን ማርያም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፳ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በቤተ ክርስቲያናችን ከሚዘከሩ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ክብረ በዓላት መካከል መስከረም ፳፩ ቀን የሚውለው በዓል ብዙኃን ማርያም በመባል ይታወቃል፡፡ በዓሉ በሁለት ዐበይት ምክንያቶች ይከበራል፤ የመጀመሪያው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሃይማኖታዊ ውሳኔ ለማዘጋጀት ከሩቅም ከቅርብም የተሰባበሰቡት ቀን፤ ሁለተኛው ደግሞ ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ዕፀ መስቀል በግሸን ደብረ ከርቤ የተቀመጠበት ዕለት መኾኑ ነው፡፡ ሁለቱንም ታሪኮች ከዚህ ቀጥለን እንመለከታቸዋለን፤

በ፫፻፳፭ ዓ.ም አርዮስ የሚባል መናፍቅ የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት አልቀበልም በሚል ክህደት እርሱ ተሰናክሎ ለሌሎችም መሰናክል ኾነ፡፡ ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት አርዮስ ክህደቱን እንዲተው ቢመክሩትም ሊመለስ አልቻለም፡፡ ይህ የአርዮስ ክህደትም በሊቃውንቱ መካከል መለያየትን ፈጠረ፡፡ ጊዜው ታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ‹‹አብያተ ጣዖታት ይትአጸዋ አብያተ ክርስቲያናት ይትረኀዋ፤ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ! አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ!›› የሚል ዐዋጅ የነገረበት ወቅት ነበርና ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ በአርዮስ ክህደት ምክንያት በኒቅያ የሃይማኖት ጉባኤ እንዲካሔድ በየአገሩ ላሉ ሊቃውንት መልእክት አስተላለፈ፡፡

በዚህም መሠረት ከሚያዝያ ፳፩ ቀን ጀምሮ እስከ መስከረም ፳፩ ቀን ድረስ ፳፫፻፵፰ (ሁለት ሺሕ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንት) ሊቃውንት በኒቅያ ተሰበሰቡ፡፡ ኒቅያ ለዚህ ጉባኤ የተመረጠችበት ምክንያትም ጳጳሱን ከማኅበረ ካህናቱ፤ ንጉሡን ከሠራዊቱ ጋር አጠቃላ ለመያዝ የምትችል ሰፊና ምቹ ቦታ ከመኾኗ ባሻገር ለኹሉም አማካይ ሥፍራ ስለነበረች ነው፡፡ በጉባኤው ከተሰበሰቡ ሊቃውንት መካከልም እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ሙታንን ያስነሡ፣ ለምጽ ያነጹ፣ አንካሳ ያረቱ፣ የዕውራንን ዓይን ያበሩ ድውያንን የፈወሱ፣ ሌላም ልዩ ልዩ ተአምር ያደረጉ፤ እንደዚሁም ስለ ርትዕት ሃይማኖታቸው በመጋደል ዓይናቸው የፈረጠ፣ እጃቸው የተቈረጠ አበው ይገኙበታል፡፡

ሊቃውንቱ ሱባዔ ይዘው በጸሎት ከቆዩ በኋላ ኅዳር ፱ ቀን በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሊቀ መንበርነት፣ በእለእስክንድሮስ አፈ ጉባኤነት ጉባኤው ተጀመረ፡፡ ንጉሡ ሊቃውንቱን ‹‹ስማችሁን፣ አገራችሁንና ሃይማኖታችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ›› ባላቸው ጊዜም ከ፳፫፻፵፰ቱ መካከል ፫፻፲፰ (ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ) ሊቃውንት ሃይማኖታቸውን ሲገልጹ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ፤ ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በመለኮት፣ በሥልጣን፣ በፈቃድ፣ በህልውና አንድ ነው›› ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ንጉሡም ‹‹ሃይማኖት እንደ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት ይኹን›› ብሎ ዐዋጅ አስነግሯል፡፡

፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በጉባኤው አርዮስን አውግዘው በመለየት ‹‹ነአምን በአሐዱ አምላክ፤ በአንድ አምላክ እናምናለን›› የሚለውን የሃይማኖት ጸሎት (የሃይማኖት መሠረት) እና ሌሎችንም የሃይማኖት ውሳኔዎች ደንግገዋል፡፡ ሊቃውንቱ ጉባኤውን ያካሔዱት ኅዳር ፱ ቀን ይኹን እንጂ በአንድነት የተሰባሰቡት መስከረም ፳፩ ቀን ስለ ነበረ ይህ ዕለት ብዙኃን ማርያም እየተባለ ይጠራል፡፡ ብዙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ለሃይማኖታዊ ጉባኤ የተሳባሰቡበት ዕለት ነውና፡፡ እነዚህ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በኦሪት ዘፍጥረት የተጠቀሱት የአብርሃም ብላቴኖች ምሳሌዎች ናቸው (ዘፍ. ፲፬፥፲፬)፡፡

በሌላ በኩል መስከረም ፳፩ ቀን የጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በአምባሰል ተራራ በግሸን ደብረ ከርቤ የገባበትና በዓሉ የከበረበት ዕለት ነው፡፡ ታሪኩም በአጭሩ የሚከተለው ነው፤

ዐፄ ዳዊት መንፈሳዊና ደግ ንጉሥ ነበሩ፡፡ በዘመናቸው በኢትዮጵያ ቸነፈር ተከሥቶ ሕዝቡ ስለ ተሰቃየባቸው እጅግ አዘኑ፤ በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ቢያመለክቱም ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላኩ ባሕታዊ መጥተው ‹‹የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል አስመጥተህ በአገርህ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አሠርተህ ብታስቀምጥ ረሃቡ፣ ቸነፈሩ ኹሉ ይታገሥልሃል›› አሏቸው፡፡ ዐፄ ዳዊትም ከብዙ ገጸ በረከት (ስጦታ) ጋር ‹‹የጌታችንን መስቀል ላኩልኝ›› የሚል መልእክት አስይዘው መልእክተኞችን ወደ ኢየሩሳሌም ሰደዱ፡፡ መልእክተኞቹም በታዘዙት መሠረት መስቀሉን ይዘው መምጣታቸውን ዐፄ ዳዊት ሲሰሙ ‹‹ክተት ሠራዊት ምታ ነጋሪት›› ብለው አሳውጀው መስቀሉን ለመቀበል ጉዞ ጀመሩ፡፡

ዐፄ ዳዊት ስናር (ሱዳን) ደርሰው ከመልእክተኞቹ ጋር ተገናኝተው መስቀሉን በክብር አጅበው ወደ መካከል ኢትዮጵያ ለማስገባት ሲነሡም ከበቅሏቸው ወድቀው ጥቅምት ፱ ቀን ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፤ በዚህም ሠራዊታቸው ተደናግጠው የጌታችንን መስቀል እዚያው ትተው የዐፄ ዳዊትን አስከሬን ይዘው ተመለሱ፡፡ መስቀሉ በስናር ከቆየ በኋላ የዐፄ ዳዊት ልጅ ዘርዐ ያዕቆብ ሲነግሡ ወደ መሃል ኢትዮጵያ አምጥተው ቤተ ክርስቲያን አሠርተው ለማስቀመጥ ቢያስቡም ምቹ ቦታ ግን ሊያገኙ አልቻሉም ነበር፡፡ ንጉሡና ሠራዊታቸው ምቹ ቦታ ሲፈልጉ መስቀሉን በኤረር ተራራ፣ በደብረ ብርሃን፣ በመናገሻ ማርያም ዓምባ፣ በእንጦጦ ጋራ ብዙ ጊዜ አስቀምጠውት ቆይተዋል፡፡

መስቀሉ በእንጦጦ ጋራ ሳለ እግዚአብሔር አምላክ ‹‹አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል፤ መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አስቀምጥ›› የሚል ቃል ለንጉሡ በራእይ ነገራቸው፡፡ መስቀሉን ወደወሎ ሀገረ ስብከት እንዲወስዱትም አዘዛቸው፡፡ ንጉሡና ሠራዊታቸው በእግዚአብሔር መሪነት መስቀሉን ይዘው ወሎ ሲደርሱም ጌታችን ወደ አምባሰል እያመለከተ ‹‹አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል፤ መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አስቀምጥ›› ይላቸው ነበር፡፡ ንጉሡ መስቀሉን ይዘው ወደ ቦታው ሲያመሩ መስቀለኛው የግሸን ተራራን አገኙ፤ በዚያም ቤተ ክርስቲያን አሠርተው በ፲፬፻፵፮ (1446) ዓ.ም የጌታችንን መስቀል በክብር አስቀምጠውታል፡፡

ከዚህ በኋላ ንጉሡ ‹‹መካከሏ ገነት፤ ዳሯ እሳት ይኹን! የበረረ ወፍ፣ የሠገረ ቆቅ አይታደንባት! በድንገት ሰው የገደለ፣ ቋንጃ የቈረጠ ወንጀለኛ አይያዝባት!›› ብለው ዐዋጅ አስነግረዋል፡፡ የእመቤታችን ጽላትም አብሮ በግሸን ደብረ ከርቤ እንዲቀመጥ አድርገዋል፡፡ ስለዚህም መስከረም ፳፩ ቀን በየዓመቱ በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡ ኀጢአታቸውን ለካህን ተናዘው፣ ንስሐ ገብተው በዚህ ዕለት ወደ ግሸን ደብረ ከርቤ በመሔድ የሚጸልዩና የሚማጸኑ ምእመናን ኹሉ እስከሰባት ትውልድ ድረስ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደሚያገኙም ጤፉት በተባለችው መጽሐፍ ተጠቅሷል፡፡ የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ፣ የእመቤታችን አማላጅነት፣ የክርስቶስ የመስቀሉ ኃይል፣ የአባቶቻችን ሊቃውንትና ነገሥታት በረከት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ / አፈወርቅ ተክሌ፤ ፳፻፭ .ም፣ አዲስ አበባ፤ ገጽ ፫፻፶፬፫፻፶፮፡፡

የሕንዱ ፓትርያርክ የመስቀል በዓልን በአዲስ አበባ አከበሩ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፲፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የሕንድ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ማርቶማ ጳውሎስ ካልዕ የመስቀል ደመራ በዓልን በአዲስ አበባ ከተማ በመስቀል ዐደባባይ አከበሩ፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ማርቶማ ጳውሎስ ካልዕ

ቅዱስነታቸው በዓለ መስቀልን በአዲስ አበባ ያከበሩት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ያቀረቡላቸውን መንፈሳዊ ግብዣ ተቀብለው ነው፡፡

ፓትርያርኩ በዕለቱ በሰጡት ቃለ ምዕዳን ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በቀረበላቸው መንፈሳዊ ጥሪ መሠረት ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ሐዋርያዊ ጉብኝት በማድረጋቸውና በዓለ መስቀልን በአዲስ አበባ ከተማ በማክበራቸው መላው የሕንድ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ምእመናን እንደተባረኩ፣ በዚህም ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል፡፡

መስቀልን ማክበር ማለት ራስን መፈለግና የመስቀሉን ክብር ከፍ ከፍ ማድረግ ማለት እንደኾነ የጠቀሱት ቅዱስነታቸው ኢትዮጵያውያን ምእመናን በመንፈሳዊ ሥርዓት ብቻ ሳይኾን በሕይወታቸው ጭምር የመስቀሉን ክብር እንደሚገልጹት መስክረዋል፡፡

የኢትዮጵያ የመስቀል በዓል አከባበር ሥርዓት በዓለም አቀፉ የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት በቅርስነት በመመዝገቡ መደሰታቸውንም ተናግረዋል፡፡

መላው ሕዝበ ክርስቲያን ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራውን ወደፈጸመበት መስቀል ሊመለከት እንደሚገባው ያስረዱት ቅዱስነታቸው በመልእክታቸው ማጠቃለያም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ለመላው ምእመናን አባታዊ ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡

በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው የሕንድ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከአምስቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት አንዷ ስትኾን፣ በርካታ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሰባክያነ ወንጌልና ካህናት እንደዚሁም ወደሦስት ሚሊዮን የሚደርሱ ምእመናን እንዳሏትና ሠላሳ በሚኾኑ አህጉረ ስብከቷ ሐዋርያዊ ተልእኮዋን በመወጣት ላይ እንደምትገኝ ታሪኳ ያስረዳል፡፡

በ፳፻፲ ዓ.ም የሚከበረውን በዓለ መስቀል በማስመልከት በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በተዘጋጀው ልዩ ዕትም መጽሔት በገጽ 12 – 13 እንደተጠቀሰው፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ማርቶማ ጳውሎስ ካልዕ በሕንድ ምሥራቅና ማላንካራ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በቅዱስ ቶማስ መንበረ ፓትርያርክ ሰባተኛውን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማርቶማ ዲዲሞስ ቀዳማዊን በመተካት ከስምንት ዓመታት በፊት ስምንተኛው ፓትርያርክ ኾነው ተሹመዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ማርቶማ ጳውሎስ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ጋር

በዘመነ ፓትርያርክነታቸውም ሐዋርያዊ ጉብኝት በማድረግ በኦሪየንታል አኃት አብያተ ክርስቲያናት መካከል ያለው ሃይማኖታዊ ግንኙነት እንዲጠናከር ከፍ ያለ መንፈሳዊ ተግባር በመፈጸም ላይ ይገኛሉ፡፡

ቅዱስነታቸው መስከረም ፲፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ወደኢትዮጵያ በመጡ ጊዜም ከቦሌ ዓለም አቀፍ አየር መንገድ ጀምሮ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ እና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል መንፈሳዊ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡

ፓትርያርኩ በኢትዮጵያ በሚኖራቸው ቆይታም በዓለ መስቀልን ከማክበራቸው በተጨማሪ የቅዱስ ላሊበላ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናትን፣ ደብረ ሊባኖስን፣ ሰበታ ቤተ ደናግል የሴት መነኮሳይያት ገዳምን እና ሌሎችም ቅዱሳት መካናትን እንደሚጎበኙ፤ በሁለቱ አብያተ ክርስቲያናት መካከል ያለውን ሃይማኖታዊ ግንኙነት በሚመለከትም የመግባቢያ ሰነድ እንደሚፈራረሙ ለመረዳት ተችሏል፡፡

ከፓትርያርኩ የጉብኝት ዜና ስንወጣ የመስቀል ደመራ በዓል በመላው ዓለም በሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት መስከረም ፲፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በመንፈሳዊ ሥርዓት ተከብሯል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ መስቀል ዐደባባይ በዓሉ ሲከበርም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፤ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የየመምሪያ ሓላፊዎች፤ የገዳማት፣ አድባራት አስተዳዳሪዎች እና አገልጋይ ካህናት፤ የየሰንበት ት/ቤቶች እና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት፤ የኢፊድሪ ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በአጠቃላይ በመቶ ሺሕ የሚቈጠር ሕዝብ በሥርዓቱ ታድሟል፡፡

በዕለቱ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ቃለ ምዕዳን ሰጥተዋል፡፡

በቃለ ምዕዳናቸውም የሕንድ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ጥሪያቸውን አክብረው ወደኢትዮጵያ በመምጣት በዓሉን በጋራ በማክበራቸው መደሰታቸውን ገልጸው፣ ‹‹የመስቀል በዓል በየዓመቱ በደማቅ ሥርዓት የሚከበረው መስቀሉ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራውን የፈጸመበት በመኾኑ ነው›› በማለት በዓሉ የሚከበርበትን ምክንያት አስገንዝበዋል፡፡

አያይዘውም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሰላምን፣ አንድነትን፣ ፍቅርን እንደሰጠን ዂሉ፣ እኛ ኢትዮጵያውያንም አገራዊ አንድነታችንንና ወንድማማችነታችንን በመጠበቅ በመካከላችን ፍቅርንና ሰላምን ማስፈን፤ ዕድገታችንንም ማስቀጠል እንደሚገባን ቅዱስነታቸው አባታዊ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡

ከዚሁ ዂሉ ጋርም በቅርቡ በኦሮምያ እና ሱማሌ የኢትዮጵያ ክልሎች በተነሣው ግጭት ከዚህ ዓለም በሞት ለተለዩ ወገኖች ዕረፍትን፤ ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መጽናናትን፤ ጉዳት ለደረሰባቸውና ሕክምና ላይ ለሚገኙት ደግሞ ፈውስን እግዚአብሔር እንዲሰጣቸው ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ተመኝተዋል፡፡

በዕለቱ መንግሥትን ወክለው መልእክት ያስተላለፉት የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አቶ ደሪባ ኩማ በበኩላቸው ሃይማኖትና መንግሥት የተለያዩ ናቸው ማለት አንዳቸው በአንዳቸው አስተዳደር ጣልቃ አይገቡም ማለት እንጂ ለአገር ሰላም በሚጠቅሙ ብሔራዊ ጉዳዮች ላይ በጋራ አይመክሩም ማለት እንዳልኾነ አስታውሰዋል፡፡

የመስቀል በዓል አከባበር ሥርዓት በዓለም አቀፉ የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት በቅርስነት መመዝገቡ ለቱሪዝም ዕድገት ከሚኖረው አገራዊ ፋይዳ ባሻገር የኢትዮጵያን መልካም ገጽታ ለዓለም በማስተዋወቅ ረገድ ከፍተኛ ድርሻ እንዳለውም አስረድተዋል፡፡

በመጨረሻም ጸሎተ ቡራኬ ተደርጎ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ማርቶማ ጳውሎስ እና በዶክተር ሙላቱ ተሾመ የመስቀል ደመራው ከተለኮሰ በኋላ የበዓሉ አከባበር ሥርዓት በሰላም ተፈጽሟል፡፡

የምስል ወድምፅ ዝግጅቱ ተመርቆ በነጻ ተሠራጨ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፲፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በተሐድሶ መናፍቃን መሠረታዊ ስሕተት እና ወቅታዊ እንቅስቃሴያቸው ዙሪያ ያዘጋጀው የምስል ወድምፅ ዝግጅት መስከረም ፲፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም  ተመርቆ ለምእመናን በነጻ ተሠራጨ፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ ማስተባበሪያ በተሰናዳው በዚህ የምስል ወድምፅ ዝግጅት፣ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ የሰሜን ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ መጋቤ ሐዲስ ቀሲስ እሸቱ ዓለማየሁ በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሐዲሳት ትርጓሜ መምህር እና ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ትምህርታዊ ማብራሪያ በመስጠት፣ ዲያቆን ምትኩ አበራ ደግሞ በማወያየት ተሳትፈውበታል፡፡

በምስል ወድምፅ ዝግጅቱ የተሳተፉ መምህራነ ወንጌል

የአምስት ሰዓታት ጊዜን የሚወስደው ዝግጅቱ፣ ራሳቸውን ተሐድሶ ብለው የሚጠሩ መናፍቃን ለሚያነሧቸው የማደናገሪያ ጥያቄዎች መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምላሽ የተሰጠበት ሲኾን፣ ሕዝበ ክርስቲያኑ ራሱንና ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ከመናፍቃን ወረራ ለመጠበቅ ይችል ዘንድ ማኅበረ ቅዱሳን ለምእመናን በነጻ እንዲሠራጭ ማድረጉ ተገልጿል፡፡

ዝግጅቱ ለአንድ ዓመት ያህል እንደ ተደከመበት፤ በከፍተኛ ጥራት እንደ ተዘጋጀ እና ብዙ ገንዘብ ወጪ እንደ ተደረገበትም ከማስተባበሪያው ሪፖርት ለመረዳት ተችሏል፡፡

በዕለቱ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ፣ የግብጽ እና የሰሜን ሱዳን አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ድርጅት የበላይ ሓላፊ፤ አባቶች ቀሳውስት እና ወንድሞች ዲያቆናት፤ ሰባክያነ ወንጌል እና ዘማርያን፤ የሰንበት ት/ቤት እና የመንፈሳውያን ማኅበራት አባላት በአጠቃላይ ከሁለት ሺሕ አምስት መቶ በላይ ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይም በብፁዕ አቡነ ሉቃስ ቃለ ምዕዳን ተሰጥቷል፡፡ በዲያቆን ያረጋል አበጋዝ የፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ሒደቶችን የሚያስቃኝ የዳሰሳ ጥናት ቀርቧል፡፡ በዋና ጸሐፊው አቶ ውብእሸት ኦቶሮ አማካይነት የማኅበረ ቅዱሳን መልእክት ተላልፏል፡፡ በዋናው ማእከል መዘምራን በአማርኛ ቋንቋ፤ ከሰንዳፋ በመጡ የሰንበት ት/ቤት መዘምራን ደግሞ በአፋን ኦሮሞ ያሬዳዊ ዝማሬዎች ቀርበዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ በዕለቱ በሰጡት ቃለ ምዕዳን ሕዝበ ክርስቲያኑን ለመንፈሳዊ ጉባኤ ላሰባሰበ ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ካቀረቡ በኋላ በአዲስ ዓመት አዲስ ሐሳብ በማቅረብ የተሐድሶ ኑፋቄን ትምህርት ለመከላከል የሚያስችል ዝግጅት ለምእመናን ያሠራጨውን ማኅበረ ቅዱሳንን፣ በዝግጅቱ የተሳተፉ አባላትን እንደዚሁም በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ የተገኙ ምእመናንን አመስግነዋል፡፡

የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብዙ ፈተናዎችን እንዳሳለፈች ያወሱት ብፁዕነታቸው ምእመናን ተዋሕዶ ሃይማኖታቸውን አጽንቶ የመጠበቅ ድርሻ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡ ሃይማኖትን መጠበቅም ለአገር ሰላምና ጸጥታ፣ ለሕዝብ አንድነትና ፍቅር ዘብ መቆም ማለት መኾኑን አስረድተዋል፡፡

ራሱን ያዘጋጀ ወታደር ጠላቱን በቀላሉ ድል ለማድረግ እንደሚቻለው የጠቀሱት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ‹‹ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብና ቃለ እግዚአብሔርን በመማር ለመናፍቃን ምላሽ ለመስጠት ዘወትር የተዘጋጃችሁ ኹኑ›› በማለት ለምእመናን አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ባቀረቡት የፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ሒደቶችን የሚያስቃኝ አጠር ያለ የዳሰሳ ጥናት፣ በተለይ ከ፲፱፻፺ ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን ድረስ እንቅስቃሴያቸውን በሦስት ክፍለ ጊዜ በመመደብ ራሳቸውን ተሐድሶ ብለው የሚጠሩ መናፍቃን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱትን ጫና ማስረጃዎችን በመጥቀስ አሳይተዋል፡፡

እንደ ዲያቆን ያረጋል ማብራሪያ በ፲፱፻፺ ዓ.ም አራት የተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ መነኮሳት በቅዱስ ሲኖዶስ ተወግዘው መለየታቸው ለፀረ ተሐድሶው ተግባር ምቹ አጋጣሚ ቢኖረውም በአንጻሩ ግን ኦርቶዶክሳውያኑ ተሐድሶ መናፍቃን የሉም ብለን እንድንዘናጋ፤ መናፍቃኑ ደግሞ ውግዘትን በመፍራት የኑፋቄ ትምህርታቸውን በስውር እንዲያስፋፉ ምክንያት ኾኗል፡፡ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቀሰሴም በየጊዜው እየዘመነ በመምጣቱ አሁን ፈታኝ ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡

አያይዘውም ችግሮች ጉዳት ከማድረሳቸው በፊት የመካላከል ባህላችን ዝቅተኛ መኾን፣ የተሐድሶ ኑፋቄን ጉዳይ ከግለሰቦች ቅራኔ እንደ መነጨ አድርጎ መውሰድና ጉዳዩን በሽምግልና ለመፍታት መሞከር፣ የገንዘብ ዓቅም ማነስ፣ በሚታይ ጊዜያዊ ውጤት መርካት፣ የሰው ኃይል እጥረት፣ መሰላቸትና መዘናጋት ሐዋርያዊ ተልእኮው በሥርዓት እንዳይዳረስና የመናፍቃን ትምህርት በቀላሉ እንዲዛመት የሚያደርጉ ውስንነቶች መኾናቸውን ገልጸዋል፡፡

ሕዝበ ክርስቲያኑ መናፍቃኑ በሚያነሧቸው ጥያቄዎች አእምሮው እንዲጠመድና መምህራነ ቤተ ክርስቲያንም ለመናፍቃን ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ጊዜያቸውን እንዲያጠፉ መደረጋቸው ለሐዋርያዊ ተልእኮው መቀዛቀዝ ምክንያት መኾኑን አመላክተው ምእመናን ከተሐድሶ ኑፋቄ ትምህርት ራሳቸውንና ቤተ ክርስቲያንን ተግተው መጠበቅ እንዳለባቸው ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ አሳስበዋል፡፡

‹‹ምን እናድርግ?›› በሚለው የዳሰሳ ጥናታቸው ማጠቃለያም የተሐድሶ እንቅስቃሴን ለመከላከል በዐቢይነት የትምህርተ ሃይማኖት ዕውቀትን ማሳደግ እንደሚገባ፤ ለዚህም የሥልጠና መርሐ ግብሮችን፣ የሥነ ጽሑፍ ውጤቶችን እና የቪሲዲ ዝግጅቶችን መጠቀም ምቹ መንገድ እንደሚጠርግ ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ጠቁመዋል፡፡

በመናፍቃን ተታለው የተወሰዱ ምእመናንን ወደ ቤተ ክርስቲያን መመለስ እና በሚሊዮን የሚቈጠሩ ወገኖችን በማስተማር የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ ማድረግ ማኅበሩ ስልታዊ ዕቅድ ነድፎ ከሚያከናውናቸው ዐበይት ተግባራቱ መካከል መኾናቸውን የጠቀሱት ደግሞ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ውብእሸት ኦቶሮ ናቸው፡፡

የምስል ወድምፅ ዝግጅቱን ለምእመናን በነጻ ለማዳረስ መወሰኑ ማኅበረ ቅዱሳን ሕዝበ ክርስቲያኑ በሃይማኖቱ ጸንቶ እንዲኖር ለማበረታታት እና የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮ እንዲፋጠን ለማድረግ የሚተጋ ማኅበር ለመኾኑ አንዱ ማሳያ ነው ብለዋል – ዋና ጸሐፊው፡፡ ከዚህ የበለጠ ብዙ ሥራ ከማኅበሩና ከምእመናን እንደሚጠበቅም አስታውሰዋል፡፡

በሁለት ቋንቋዎች ብቻ የሚግባቡና በቍጥር ከዐሥር ሚሊዮን የማይበልጡ ምእመናን የሚገኙባት የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከስምንት በላይ የቴሌቭዥን ጣቢያዎች እንዳሏት ያወሱት አቶ ውብእሸት፣ ከሰማንያ በላይ ቋንቋዎችን የሚጠቀሙና ወደ አምሳ ሚሊዮን የሚደርሱ ምእመናን ባለቤት ለኾነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንድ የቴሌቭዥን ጣቢያ ብቻ በቂ አለመኾኑን ጠቁመዋል፡፡

አያይዘውም ይህን ጉዳይ የተገነዘበው ማኅበረ ቅዱሳን፣ የአየር ሰዓት በመከራየት በአሌፍ የቴሌቭዥን ጣቢያ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደሚገኝ በማስታወስ መንፈሳዊ የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩን አጠናክሮ ለመቀጠል ያመች ዘንድ በገንዘብም፣ በቁሳቁስም፣ በሐሳብም ምእመናን ድጋፍ እንዲያደርጉ ዋና ጸሐፊው ጠይቀል፡፡

ከዚሁ ዂሉ ጋርም ማኅበረ ቅዱሳን ሰባክያነ ወንጌልን በማሠልጠን፣ አዳዲስ አማንያንን በማስጠመቅ፣ በጠረፋማ አካባቢዎች አብያተ ክርስቲያናትን በማሳነጽ እና በመሳሉት ዘርፎች ፕሮጀክት ቀርፆ ለስብከተ ወንጌል መዳረስ የሚያከናውናቸውን ተግባራት በሚችሉት መንገድ ዂሉ በመደገፍ እና ከማኅበሩ ጎን በመቆም ምእመናን የሚጠበቅባቸውን ክርስቲያናዊ ድርሻ እንዲወጡ አቶ ውብእሸት ኦቶሮ በማኅበረ ቅዱሳን ስም ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡

በመልእክታቸው ማጠቃለያም ትምህርተ ወንጌልን በማዳረስ፤ የግንዛቤ ማዳበሪያ መርሐ ግብራትን በማዘጋጀትና ሥልጠና በመስጠት፤ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎትና ለሥልጠና መስጫ የሚውል ገንዘብ በመለገስ፤ የተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆችን በማጋለጥ በአጠቃላይ በልዩ ልዩ መንገድ ሱታፌ በማድረግ ኦርቶዶክሳዊው አስተምህሮ እንዲስፋፋ፣ የተሐድሶ ኑፋቄ ትምህርት ደግሞ እንዲዳከም ከፍተኛ አስተዋጽዖ ላበረከቱ ሰባክያነ ወንጌል እና በጎ አድራጊ ምእመናን በተጨማሪም ማኅበሩ ያስተላለፈውን ጥሪ ተቀብለው በድምፅ ወምስል ዝግጅቱ ምረቃ ላይ ለተገኙ ወገኖች ዅሉ ዋና ጸሐፊው በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም መንፈሳዊ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

በመጨረሻም የምስል ወድምፅ ዝግጅቱ በብፁዕ አቡነ ሉቃስ ቡራኬ ተመርቆ በቍጥር አንድ ሺሕ በሚኾኑ በባለ ፲፮ ጊጋ ባይት ፍላሽ ዲስኮች ለምእመናን የታደለ ሲኾን፣ በዕለቱ ያልተገኙ ምእመናን ከማኅበሩ ሕንጻ ድረስ በአካል በመምጣት ዝግጅቱን በፍላሽ እንዲወስዱ፤ በጎ አድራጊ ምእመናን ፍላሽ ዲስኮችን ገዝተው በማበርከት ለትምህርቱ መዳረስ ትብብር እንዲያደርጉ፤ ዝግጅቱ የደረሳቸው ወገኖችም እያባዙ ቤተ ክርስቲያንን ለሚወዱም ኾነ ለማይወዱ ወገኖች እንዲያዳርሱ፤ ዝግጅቱ ያልደረሳቸው ደግሞ ትምህርቱ በማኅበሩ ቴሌቭዥን ሲተላለፍ፣ በዩቲዩብ ሲለቀቅና በሲዲ ሲሠራጭ እንዲከታተሉ በማስተባበሪያው በኩል ማሳሰቢያ ከተሰጠ በኋላ በብፁዕነታቸው ቃለ ምዕዳን እና ጸሎተ ቡራኬ መርሐ ግብሩ ተጠናቋል፡፡

ከምረቃ መርሐ ግብሩ በኋላ ስለ ዝግጅቱ አስተያየት እንዲሰጡ የጠየቅናቸው ምእመናን፣ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ፈተና የኾነውን የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ ለመከላከል ይቻል ዘንድ ብዙ ገንዘብ ወጪ በማድረግ ያዘጋጀውን የምስል ወድምፅ ዝግጅት ለምእመናን በነጻ ማዳረሱ ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ ለመደገፍ የሚተጋ የቍርጥ ቀን ልጅ መኾኑን እንደሚያስረዳ መስክረዋል፡፡ ከማኅበሩ ጋር በመኾን የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት በሚቻላቸው ዓቅም ዅሉ የማኅበሩን አገልግሎት ለመደገፍም ቃል ገብተዋል፡፡

ከዚህ በተለየ ደግሞ የማኅበሩ አዳራሽ እና በምድር ቤቱ ወለል ላይ የተዘጋጁ ድንኳኖች ሞልተው በርካታ ምእመናን ቆመው መርሐ ግብሩን መከታተላቸውን፤ ከፊሉም መግቢያ አጥተው በመርሐ ግብሩ ለመሳተፍ አለመቻላቸውን ያስተዋሉ አንዳንድ በጎ አድራጊ ምእመናን በመንፈሳዊ ቍጭት ተነሣሥው ‹‹ብዙ ሕዝብ ማስተናገድ የሚችል ሰፊ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ መገንባት አለብን›› እየተባባሉ ሲነጋገሩ ተሰምቷል፡፡

ዘመነ ክረምት – የመጨረሻ ክፍል

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፲፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! በክፍል ስምንት ዝግጅታችን ስድስተኛውን የክረምት ንዑስ ክፍል (ዘመነ ፍሬን) በሚመለከት ወቅታዊ ትምህርት ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ በዛሬው የመጨረሻ ክፍል ዝግጅታችን ደግሞ ሰባተኛውን ክፍለ ክረምት (ፀአተ ክረምትን ወይም ዘመነ መስቀልን) የሚመለከት ትምህርት ይዘን ቀርበናል፡፡ ትምህርቱን እንድትከታተሉ መንፈሳዊ ግብዣችንን አስቀድመናል፡፡ መልካም የንባብ ጊዜ ይኹንላችሁ!

፯. ፀአተ ክረምት (ዘመነ መስቀል)

ከመስከረም ፲፮ – ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ሰባተኛው የክረምት ክፍለ ጊዜ ፀአተ ክረምት ወይም ዘመነ መስቀል በመባል የሚታወቅ ሲኾን ይኸውም የክረምት መውጣት እና በአተ መጸው (የመጸው መግባት) የሚሰበክበት ወቅት ነው፡፡ የፀአተ ክረምት መጨረሻ የሚኾነውም መስከረም ፳፭ ቀን ነው፡፡ ‹ፀአተ ክረምት› የሚለው የግእዝ ቃላት ጥምረት ‹የክረምት መውጣት› የሚል ትርጕም አለው፡፡ የክረምት መውጣት ሲባል ለዘመነ ክረምት የተሰጠው ጊዜ በዘመነ መጸው መተካቱን ለማመልከት እንጂ ክረምት ተመልሶ አይመጣም ለማለት አይደለም፡፡ የሰው ልጅ ምድራዊ ሕይወት እስከሚያበቃበት እስከ ኅልፈተ ዓለም ድረስ የወቅቶች መፈራረቅም አብሮ ይቀጥላልና፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም ይህንን የወቅቶች መፈራረቅ ለመግለጽ ነው ‹‹መግባት፣ መውጣት›› እያሉ በክፍል በክፍል የሚያስቀምጧቸው፡፡

ጠቢቡ ሰሎሞን ‹‹እስመ ናሁ ክረምት ኀለፈ ወዝናም ገብአ ድኅሬሁ ጽጌ አስተርአየ በውስተ ምድርነ ጊዜ ገሚድ በጽሐ ቃለ ማዕነቅ ተሰምዐ በምድርነ በለስ አውጽአ ሠርጸ አውያን ጸገዩ ወወሀቡ መዓዛ፤ እነሆ ክረምት ዐለፈ፤ ዝናቡም ዐልፎ ሔደ፡፡ አበባ በምድር ላይ ታየ፤ የመከርም ጊዜ ደረሰ፡፡ የቊርዬውም ቃል በምድራችን ተሰማ፡፡ በለሱ ጐመራ፤ ወይኖችም አበቡ፤ መዓዛቸውንም ሰጡ፤›› (መኃ. ፪፥፲፩-፲፫) በማለት እንደ ተናገረው አሁን የክረምቱ ጊዜ አብቅቶ ሌላ ወቅት ዘመነ መጸው ተተክቷል፡፡ መጭው ዘመን የተስፋ፣ የንስሐና የጽድቅ ወቅት እንዲኾንልን እግዚአብሔርን ከፊት ለፊታችን ማስቀደም ይኖርብናል፡፡ እርሱ ከቀደመ መሰናክሎቹን ለማለፍ፣ ፈተናዎችንም ለመወጣት ምቹ ኹኔታዎችን እናገኛለንና፡፡ ክረምቱ አልፎ መጸው ሲተካ ምድር ባገኘችው ዝናም አማካይነት የበቀሉ ዕፀዋት በአበባና በፍሬ ይደምቃሉ፡፡ ምእመናንም በተማርነው ቃለ እግዚአብሔር ለውጥ በማምጣት እንደ ዕፀዋት በመንፈሳዊ ሕይወታችን አፍርተን ክርስቲያናዊ ፍሬ ማስገኘት ይኖርብናል፡፡ በዚህ ፍሬያችን ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔር መንግሥት ለመውረስ እንችላለንና፡፡

አንድ ክፍለ ጊዜ (ወቅት) ሲያልፍ ሌላ ክፍለ ጊዜ ይተካል፡፡ ‹‹ሲሞት ሲተካ፣ ሲፈጭ ሲቦካ›› እንደሚባለው የሰው ልጅ ሕይወትም እንደዚሁ ነው፡፡ አንደኛው ሲሞት ሌላኛው ይወለዳል፤ አንደኛው ሲወለድ ሌላኛው ይሞታል፡፡ ወቅቶችም የጊዜ ዑደት መንገዶች እንደ መኾናቸው ለሰው ልጅ ምቾት እንጂ ለራሳቸው ጥቅም የተዘጋጁ ሕያዋን ፍጥረታት አይደሉም፡፡ በመኾኑም ራሳቸውን እየደጋገሙ ይመላለሳሉ፤ የሰው ልጅ ግን አምሳሉን ይተካል እንጂ ራሱ ዳግመኛ ተመልሶ አይመጣም፡፡ እንግዲህ ክርስቶስ ለፍርድ ሲመጣ እንዳናፍር ዳግም በማናገኛት በዚህች ምድራዊ ሕይወታችን የማያልፍ ክርስቲያናዊ ምግባር ሠርተን ማለፍ ይጠበቅብናል፡፡ ከሞት በኋላ ዘለዓለማዊ ፍርድ እንጂ ንስሐ የለምና፡፡

መንፈሳዊ ዓላማችን ይሳካልን ዘንድም እግዚአብሔርን በጸሎት እንጠይቀው፡፡ እንደዚህ እያልን፤ ‹‹ድኅረ ኀለፈ ክረምት ወገብአ ዝናም፤ ዘአርአይከ እግዚኦ ጽጌያተ ገዳም፤ አፈወ ሃይማኖት ነዓልድ ወፍሬ ምግባር ጥዑም፤ አትግሀነ ለስብሐቲከ ከመ ትጋሆሙ አዳም፤ ለጽብስት ንህብ ወነአስ ቃህም፡፡›› ትርጕሙም፡- ‹‹ክረምት ካለፈ፣ ዝናምም ወደ ቦታው ከተመለሰ በኋላ የዱር አበቦችን ያሳየህ አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ! የሃይማኖት ሽቱን እናስገኝና የሚጣፍጥ የምግባር ፍሬን እናፈራ ዘንድ ተወዳጅ እንደ ኾነው የታታሪዋ ንብና የብልሃተኛዋ ገብረ ጕንዳን ትጋት እኛንም ለምስጋናህ አትጋን›› ማለት ነው (መጽሐፈ ስንክሳር፣ የመስከረም ፳፭ ቀን አርኬ)፡፡

በተጨማሪም በዚህ ወቅት (ከመስከረም ፲፮ – ፳፭ ቀን ድረስ ባለው ክፍለ ክረምት) ነገረ መስቀሉን የሚመለከት ትምህርት በቤተ ክርስቲያናችን በሰፊው ይነገራል፡፡ ማለትም ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጅ ድኅነት ሲል በፈቃዱ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ስለ መሞቱ፣ በሞቱም ዓለምን ስለ ማዳኑ፣ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ያፈሰሰሰበት ዕፀ መስቅሉ የተቀደሰ ስለ መኾኑ ከሌሎች ጊዜያት በላይ በስፋት የሚነገረውና ትምህርት የሚሰጠው በዚህ ወቅት ነው፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም በአይሁድ ቅናት በጎልጎታ ለ፫፻ ዓመታት ያህል ተቀብሮ የቆየው የጌታችን ዕፀ መስቀልን ለማውጣት በንግሥት ዕሌኒ አማካይነት ቍፋሮ መጀመሩ፣ መስቀሉ ከወጣ በኋላም በዐፄ ዳዊትና በልጃቸው በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ጥረት ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ በግሸን ደብረ ከርቤ መቀመጡ የሚዘከረው በእነዚህ ዐሥር የፀአተ ክረምት ዕለታት ውስጥ ነው፡፡ እኛ ምእመናን ይህንን የመስቀሉን ነገር በልቡናችን ይዘን በክርስትናችን ምክንያት የሚገጥመንን ልዩ ልዩ ዓይነት ፈተና በትዕግሥት ማሳለፍ ይጠበቅብናል፡፡

ማጠቃለያ

ትምህርታችንን ለማጠቃለል ያህል ዘመነ ክረምት ስለ ሥነ ፍጥረት ዘርዘር ባለ መልኩ የሚነገርበት፤ ፍጡርን ከፈጣሪ መናን (ምግብን) ከተመጋቢ ለይቶ የሚያሳይ እና የሚያሳውቅ ዘመን ነው፡፡ በዚህ ወቅት የውኃ ባሕርይ ይሠለጥናል፤ ውኃ አፈርን ያጥባል፤ እሳትን ያጠፋል፡፡ ኾኖም ግን ውኃ በብሩህነቱ ከእሳት፤ በቀዝቃዛነቱ ከነፋስ፤ በእርጥብነቱ ከመሬት ጋር ተስማምቶ ከሦስቱ ባሕርያት ጋር ይኖራል፡፡ ይህን ምሥጢር ከሕይወታችን ጋር አያይዘን ስንመለከተው ዘመነ ክረምት የክርስትና ምሳሌ ነው፡፡ በክረምት ወቅት ገበሬው ብርዱንና ዝናሙን ሳይሰቀቅ ለሥራ ይሰማራል፤ በበጋው የእጁን ፍሬ ያገኝ ዘንድ የክረምቱን መከራ ይታገሣል፡፡ ይህም ምእመናን በሰማያዊው ዓለም የምናገኘውን ተድላና ደስታ በማሰብ በምድር ቆይታችን ወቅት የሚደርስብንን ልዩ ልዩ መከራ በትዕግሥት ማሳለፍ እንደሚገባን ያስገነዝባል፡፡

ዘመነ ክረምት ዕፀዋቱ በስብሰው ከበቀሉ፣ ካበቡና ካፈሩ በኋላ የሚጠቅሙት በሪቅ፣ በጎተራ እንደሚሰበሰቡ፤ እንክርዳዶቹ ደግሞ በእሳት እንደሚቃጠሉ ዅሉ እኛም ተወልደን፣ አድገን፣ ዘራችንን ተክተን እንደምንኖር፤ ዕድሜያችን ሲያበቃም እንደምንሞት፤ ሞተንም እንደምንነሣና መልካም ሥራ ከሠራን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንደምንገባ፤ በኀጢአት ከኖርን ደግሞ በገሃነመ እሳት እንደምንጣል የምንማርበት ወቅት ነው፡፡ በመኾኑም ሰይጣን በሚያዘንበው የኀጢአት ማዕበል እንዳንወሰድና በኋላም በጥልቁ የእሳት ባሕር እንዳንጣል ዅላችንም ቅዱሳት መጻሕፍትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያዘጋጁልንን የቃለ እግዚአብሔር ዘር በእርሻ ልቡናችን በመዝራት (በመጻፍ) እንደየዓቅማችን አብበን፣ ያማረ ፍሬ አፍርተን መንግሥቱን ለመውረስ መዘጋጀት ይኖርብናል፡፡ ይህንን እንድናደርግም የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእናታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነትና የቅዱሳኑ ዅሉ ተራዳኢነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ተአምረ ማርያም በጼዴንያ

በዝግጅት ክፍሉ

መስከረም ፲ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ መስከረም ፲ ቀን ከሚዘከሩ በዓላት መካከል የእመቤታችን በዓል አንደኛው ሲኾን ይኸውም ጼዴንያ በምትባል አገር ከሥዕሏ ተአምር የተደረገበት ዕለት ነው፡፡ በተአምረ ማርያም እና በመጽሐፈ ስንክሳር እንደ ተመዘገበው ቅዱስ ሉቃስ ከሣላት ሥጋ የለበሰች ከምትመስል የእመቤታችን የሥዕል ሠሌዳ ቅባት ይንጠፈጠፍ ነበር፡፡ ከዚህች የእመቤታችን ሥዕል የተገለጠው ተአምርና ታሪክም በአጭሩ የሚከተለው ነው፤

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን የምትወድና በሚቻላትም ዂሉ የምታገለግላት፣ ቤቷንም ለእንግዳ ማደሪያ ያደረገች አንዲት ማርታ የምትባል ሴት ነበረች፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አባ ቴዎድሮስ የሚባሉ መነኵሴ ከእርሷ ዘንድ በእንግድነት አድረው በማግሥቱ ከቤቷ ሲወጡ ማርታ የሚሔዱበትን አገር በጠየቀቻቸው ጊዜ  እርሳቸውም ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው ቅዱሳት መካናትን እንደሚሳለሙ ነገሯት፡፡ ማርታም ከእርሷ ገንዘብ ወስደው የእመቤታችንን ሥዕል ገዝተው ይዘውላት እንዲመጡ ለመነቻቸው፡፡ መነኵሴውም በራሳቸው ገንዘብ ሥዕሉን ገዝተው እንደሚያመጡላት ቃል ገቡላት፡፡ አባ ቴዎድሮስ ኢየሩሳሌም ደርሰው ቅዱሳት መካናትን ከተሳለሙ በኋላ ሥዕሏን ሳይገዙ ወደ አገራቸው ተመለሱ፡፡ ያን ጊዜም ‹‹ሥዕል መግዛትን ለምን ረሳህ?›› የሚል የሚያስደነግጥ ቃልን ሰምተው ወደ ገበያ ተመልሰው መልኳ ያማረና የተወደደ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል ገዝተው በሐርና በንጹሕ ልብስ ጠቅልለው ይዘው እየተጓዙ ሳሉ ከሚያስፈራ ዱር ውስጥ ደረሱ፡፡ በዚያም ወንበዴዎች ተነሡባቸውና ከእነርሱ ሊሸሹ ሲሉ ‹‹መንገድህን ሒድ›› የሚል ቃል ከሥዕሏ ወጣ፤ መነኵሴውም መንገዳቸውን በሰላም ተጓዙ፡፡ ሁለተኛም አንበሳ ሊበላቸው በተነሣባቸው ጊዜ ከዚያች ሥዕል የሚያሥፈራ ድምፅ ወጥቶ አንበሳውን አባረረላቸው፡፡

አባ ቴዎድሮስ ይህን ዂሉ ድንቅ ተአምር ባዩ ጊዜም ያቺን ሥዕል ለማርታ ከመስጠት ይልቅ ወደ አገራቸው ሊወስዷት ወደዱ፡፡ በመርከብ ተሳፍረው በሌላ አቅጣጫ ሲሔዱም ታላቅ ነፋስ ተነሥቶ ወደ ማርታ አገር ወደ ጼዴንያ ወሰዳቸው፡፡ ከመርከብም ወርደው ከብዙ እንግዶች ጋር ወደዚያች መበለት ቤት ደረሱ፡፡ ነገር ግን ማንነታቸውን ለማርታ አልገለጡላትም፤ እርሷም አላወቀቻቸውም ነበር፡፡ በማግሥቱም ተሠውረው ወደ አገራቸው ሊሔዱ ሲሉ የቅፅሩ ደጃፍ ጠፍቶባቸው ሲፈልጉ ዋሉ፡፡ በመሸባቸው ጊዜም ወደ ማደሪያቸው ተመለሱ፡፡ ማታ ማታ በሩን ያዩታል፤ ነግቶ መሔድን ሲሹ ግን የበሩ መንገድ ይሠወርባቸዋል፡፡ እንዲህም ኾነው እስከ ሦስት ቀን ድረስ ቆዩ፡፡ ማርታም ‹‹አባቴ ሆይ አእምሮህ ተነክቷልን? ስትቅበዘበዝ አይሃለሁና ምን ኾነህ ነው?›› ሰትል ጠየቀቻችው፡፡ እርሳቸውም ከእመቤታችን ሥዕል የተደረገውን ተአምር እና ሥዕሏን ይዘው ለመጥፋት ያደረጉትን ጥረት ዂሉ ነግረው፣ ራሳቸውን ገልጠው ሥዕሏን ሰጧት፡፡ እርሷም የእመቤታችንን ሥዕል ተቀብላ የተጠቀለለችበትን ልብስ በፈታችው ጊዜ ወዝ ከሥዕሊቱ ሲንጠፈጠፍ አገኘች፡፡ ከደስታዋ ብዛት የተነሣም የአባ ቴዎድሮስን እጃቸውንና እግራቸውን ሳመች፡፡

ከዚህም በኋላ ያቺን ሥዕል ወደ ጸሎት ቤቷ ወስዳ በታላቅ ክብር አኖረቻት፡፡ ማንም እንዳይዳስሳትም የነሐስ መስኮትን ሠራችላት፡፡ በቀንና በሌሊትም የሚያበሩ መቅረዞችን በፊቷ ሰቀለች፤ ከመቅረዞች ውጭም የሐር መጋረጃን ጋረደች፡፡ ከሥዕሊቱ በታችም እየተንጠፈጠፈ የሚወርደው የወዝ ቅባት የሚጠራቀምበት ከዕብነ በረድ የተሠራ ወጭት አኖረች፡፡ እኒያ መነኰስም እስከሚሞቱበት ቀን ድረስ የእመቤታችን ድንግል ማርያምን ሥዕል እያገለገሉ ኖሩ፡፡ የአገሩ ሊቀ ጳጳስም የእመቤታችን ሥዕል ሥጋ የለበሰች ኹና ባገኙና ተአምሯንም በተመለከቱ ጊዜ ከዚህ አምላካዊ ግብር የተነሣ አደነቁ፡፡ ከሥዕሏ ከሚንጠባጠበው ቅባት ቀድተው ለበረከት ሲካፈሉም ወዲያውኑ በወጭቱ ውስጥ መላ፡፡ ሥዕሊቱን ወደ ሌላ ቦታም ሊወስዷት በፈለጉ ጊዜም ንውጽውጽታ ኾኖ ብዙዎች በድንጋጤ ወደቁ፡፡ ሥዕሊቱም እስከ ዛሬ ድረስ በዚያች አገር (በጼዴንያ) ትገኛለች፡፡

‹‹እግዚአብሔር በቅዱሳኑ ላይ ድንቅ ነው›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፷፯፥፴፭) እግዚአብሔር አምላካችን በልዩ ልዩ መንገድ ለሰው ልጅ ተአምራቱን ይገልጣል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ተመዝግቦ እንደምናገኘው እግዚአብሔር ከዓለት ላይ ውኃ እያፈለቀ ሕዝቡን ያጠጣል፡፡ እንደዚሁም ቅዱሳን ሐዋርያት በቃላቸውም፣ በልብሳቸውም፣ በጥላቸውም ሙታንን በማስነሣት፤ ሕሙማንን በመፈወስ ተአምራትን ያደርጉ ነበር፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ጴጥሮስ በጥላው፤ ቅዱስ ጳውሎስም በልብሱ ቅዳጅ ያደርጓቸው የነበሩ ተአምራትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከግዑዝ ዓለት ውስጥ ውኃ የሚያፈልቅ አምላክ ከሥጋዋ ሥጋ፤ ከነፍሷ ነፍስ ተዋሕዶ ካከበራት ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ወዝ እንዲፈስ ቢያደርግ ምን ይሳነዋል? ሐዋርያት ከእግዚአብሔር ዘንድ በተሰጣቸው ጸጋ በልብሳቸውና በሰውነታቸው ጥላ ተአምራትን ማድረግ እንደ ተቻላቸው ዂሉ አምላክን በማኅፀኗ የተሸከመችው ወላዲተ አምላክ ቅድስት ድንግል ማርያምም በሥዕሏ ወዝ ብዙ ሕሙማንን መፈወስ ይቻላታል፡፡ ከቅዱሳን ልብስና ጥላ የእርሷ ሥዕል ይከብራልና፡፡ ስለዚህም ነው በየዓመቱ መስከረም ፲ ቀን በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት የሚከበረው፡፡

የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፤ የልጇ፣ የወዳጇ የጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቸርነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዘመነ ክረምት – ክፍል ስምንት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፮. ዘመነ ፍሬ

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! በክፍል ሰባት ዝግጅታችን አምስተኛውን የክረምት ንዑስ ክፍል (ቅዱስ ዮሐንስን) የሚመለከት ትምህርት ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ስድስተኛውን ክፍለ ክረምት (ዘመነ ፍሬን) የሚመለከት ትምህርት ይዘን ቀርበናል፡፡ እንድትከታተሉን መንፈሳዊ ግብዣችንን አስቀድመናል፡፡ መልካም የንባብ ጊዜ ይኹንላችሁ!

ከመስከረም ፱ – ፲፭ ቀን ያለው ስድስተኛው ክፍለ ክረምት ‹ፍሬ› ይባላል፡፡ ‹ዘመነ ፍሬ› ደግሞ ‹የፍሬ ወቅት፣ የፍሬ ዘመን፣ የፍሬ ጊዜ› ማለት ሲኾን ይኸውም ልዩ ልዩ አዝርዕት በቅለው፣ አድገው፣ አብበው ለፍሬ የሚደርሱበት፤ የሰው ልጅ፣ እንስሳትና አራዊትም ጭምር የዕፀዋቱን ፍሬ (እሸት) የሚመገቡበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚቀርቡ ምንባባትና ትምህርቶችም ይህንኑ ምሥጢር የሚዳስሱ ናቸው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ምድርን ከፈጠረ በኋላ በጥፍር የሚላጡትን (ሎሚ፣ ሙዝ፣ ትርንጎ፣ ወዘተ)፤ በማጭድ የሚታጨዱትን (ስንዴ፣ ጤፍ፣ ገብስ፣ ወዘተ)፤ በምሳር የሚቈረጡትን (ወይራ፣ ዋርካ፣ ዋንዛ፣ ዝግባ፣ ወዘተ)፤ የገነት ዕፀዋትን ፈጥሯል፡፡ እነዚህም በራሳቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ስንዴ፣ገብስ፣ ጤፍ፣ ወዘተ)፤ በጎድናቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ማሽላ፣ በቆሎ፣ ባቄላ፣ ወዘተ)፤ በውስጣቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ዱባ፣ ቅል፣ ወዘተ)፤ በሥራቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ሽንኩርት፣ ቀይ ሥር፣ ካሮት፣ ድንች፣ ወዘተ) ተብለው በአራት ይመደባሉ (ምንጭ፡- ትርጓሜ ኦሪት ዘፍጥረት ፩፥፮-፲፫)፡፡

ተፈጥሯቸውም እንደ ሰው ከአራቱ ባሕርያት ነው፡፡ ከነፋስ በመፈጠራቸው በነፋስ ያብባሉ፤ ያፈራሉ፡፡ ከእሳት በመፈጠራቸው እርስበርሳቸው ሲፋተጉ እሳት ያስገኛሉ (አንዳንዶቹ)፡፡ ከውኃ በመፈጠራቸው ፈሳሽ ያወጣሉ፡፡ ከአፈር በመፈጠራቸው ሲቈረጡ በስብሰው ወደ አፈርነት ይቀየራሉ፡፡ እኛ የሰው ልጆችም በተፈጥሯችን (በባሕርያችን) ከዕፀዋት ጋር እንመሳሰላለን፡፡ በነፋስ ባሕርያችን ፍጥነት፤ በእሳት ባሕርያችን ቍጣ፤ በውኃ ባሕርያችን መረጋጋት፤ በመሬት ባሕርያችን ትዕግሥት ወይም ሞት ይስማማናልና፡፡ በሌላ በኩል የአዘርዕት ከበሰበሱ በኋላ መብቀልና ማፍራት የትንሣኤ ሙታን ምሳሌ ነው፡፡ አዝርዕት ከበሰበሱ በኋላ ፍሬ እንደሚያስገኙ ዅሉ ሰውም ከሞተ በኋላ ተነሥቶ እንደ ሥራው መጠን ዋጋውን ይቀበላልና፡፡ ይህንን ቅዱስ ጳውሎስ በምሳሌ አስተምሮናል፡፡ እንዲህ ሲል፤ ‹‹… የሙታን ትንሣኤ ደግሞ እንዲሁ ነው፡፡ በመበስበስ ይዘራል፤ ባለ መበስበስ ይነሣል፡፡ በውርደት ይዘራል፤ በክብር ይነሣል፡፡ በድካም ይዘራል፤ በኃይል ይነሣል፡፡ ፍጥረታዊ አካል ይዘራል፤ መንፈሳዊ አካል ይነሣል …›› (፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፵፪-፵፬)፡፡

አዝርዕት ተዘርተው ከበሰበሱ በኋላ በቅለው፣ አብበው በራሳቸው፣ በጎድናቸው፣ በውስጣቸውና በሥራቸው እንደሚያፈሩ ዅሉ እኛም በራስ እንደ ማፍራት ፈሪሃ እግዚአብሔርን፤ በጎድን እንደ ማፍራት እርስበርስ መደጋገፍንና መተሳሰብን፤ በውስጥ እንደ ማፍራት ንጽሕናን፤ በሥር እንደ ማፍራት ትሕትናን ገንዘብ ማድረግን ከዕፀዋትና ከአዝርዕት መማር ይገባናል፡፡ እንደዚሁም ዕፀዋት ሠላሳ፣ ስድሳ፣ መቶና ከዚያ በላይ መልካም ፍሬ እንደሚያፈሩ በመልካሟ መሬት በክርስትና የተዘራን እኛ ክርስቲያኖችም ዘር የተባለውን የእግዚአብሔርን ቃል በሚገባ ተምረን ከወጣኒነት ወደ ማእከላዊነት፤ ከማእከላዊነት ወደ ፍጹምነት በሚያደርስ የጽድቅ ሥራ በመትጋት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መፋጠን ይኖርብናል (ማቴ. ፲፫፥፳፫)፡፡

ዕፀዋት የሚሰጡት ፍሬ እንደየማፍራት ዓቅማቸው ይለያያል፤ ፍሬ የማያፈሩ፣ ጥቂት ፍሬ የሚያፈሩ፣ ብዙ ፍሬ የሚያፈሩ ዕፀዋት ይገኛሉ፡፡ እንደዚሁ ኹሉ ምእመናንም በክርስትና ሕይወታችን የሚኖረን በጎ ምግባር የአንዳችን ከአንዳችን ይለያል፡፡ ፍሬ የክርስቲያናዊ ምግባር እንደዚሁም የሰማያዊው ዋጋ ምሳሌ ነውና፡፡ በክርስትና ሕይወት ያለምንም በጎ ምግባር የምንኖር ኀጥአን ብዙዎች የመኾናችንን፤ እንደዚሁም ጥቂት በጎ ምግባር ያላቸው ምእመናን የመኖራቸውን ያህል በአንጻሩ ደግሞ በጽድቅ ላይ ጽድቅ፣ በመልካም ሥራ ላይ መልካም ሥራን የሚፈጽሙ፤ ከጽድቅ ሥራ ባሻገር በትሩፋት ተግባር ዘወትር ጸንተው የሚኖሩ አባቶችና እናቶችም ጥቂቶች አይደሉም፡፡ ይህን ዓይነት የክርስቲያናዊ ሕይወት ልዩነት ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹በጥቂት የሚዘራ በጥቂት ደግሞ ያጭዳል፤ በበረከትም የሚዘራ በበረከት ደግሞ ያጭዳል … ለዘሪ ዘርን ለመብላትም እንጀራን በብዙ የሚሰጥ እርሱም የምትዘሩትን ዘር ይሰጣችኋል፤ ያበረክትላችሁማል፡፡ የጽድቃችሁንም ፍሬ ያሳድጋል›› በማለት ይገልጸዋል (፪ኛ ቆሮ. ፱፥፮-፲)፡፡ ገበሬ በዘራው መጠን ሰብሉን እንዲሰበስብ ‹‹ለዂሉም እንደየሥራው ዋጋውን ትከፍለዋለህ›› ተብሎ እንደ ተጻፈው ክርስቲያንም በሠራው መጠን ዋጋውን ያገኛልና በጸጋ ላይ ጸጋን፣ በበረከት ላይ በረከትን ከእግዚአብሔር ዘንድ ይጨመርልን ዘንድ ዂላችንም መልካም ሥራን በብዛት ልንፈጽም ይገባናል፡፡ ‹‹… እንግዲህ ወንድሞች ሆይ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ታገሡ፡፡ እነሆ ገበሬው የፊተኛውንና የኋለኛውን ዝናብ እስኪቀበል ድረስ እርሱን እየታገሠ የከበረውን የመሬት ፍሬ ይጠብቃል፡፡ እናንተ ደግሞ ታገሡ፤ ልባችሁንም አጽኑ፡፡ የጌታ መምጣት ቀርቧልና›› እንዳለን ሐዋርያው (ያዕ. ፭፥፯-፰)፡፡

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ‹‹ምድርኒ ወሀበት ፍሬሃ፤ ምድርም ፍሬዋን ሰጠች›› (መዝ. ፷፮፥፮፤ ፹፬፥፲፪) የሚለውን የዳዊት መዝሙርና ሌሎችንም ተመሳሳይ ኃይለ ቃላት ሲተረጕሙ ምድር በኢየሩሳሌም፣ በቤተ ክርስቲያን፣ በምእመናን፣ በእመቤታችን፤ ፍሬ ደግሞ በቃለ እግዚአብሔር (በሕገ እግዚአብሔር)፣ በአምልኮተ እግዚአብሔር፣ እንደዚሁም በጌታችን አምላካችን መድኂታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚመሰል ያስተምራሉ፡፡ በዚህ መሠረት ‹‹ምድርኒ ወሀበት ፍሬሃ፤ ምድርም ፍሬዋን ሰጠች›› በሚለው ኃይለ ቃል ምድር የተባለች ኢየሩሳሌም የዘሩባትን እንደምታበቅል፤ የተከሉባትን እንደምታጸድቅ፤ አንድም ይህቺ ዓለም ፍሬን፣ አምልኮተ እግዚአብሔርን እንደምታቀርብ፤ ቤተ ክርስቲያን ወይም ምእመናን እግዚአብሔርን ሲያመልኩ እንደሚኖሩ፤ ከዚሁ ዂሉ ጋርም ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንደ ተወለደ የሚያስረዳ ምሥጢር አለው፡፡ ‹‹ምድርኒ ወሀበት ፍሬሃ፤ ምድርም ፍሬዋን ሰጠች›› – ምድር ከተባለች ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍሬ የተባለው ክርስቶስ መገኘቱን ለማጠየቅም ቅዱስ ገብርኤል በሉቃስ ወንጌል የተናገረው ቃል ማስረጃ ነው (ሉቃ. ፩፥፳፰)፡፡ እኛም የመልአኩን ቃል መሠረት አድርገን በዘወትር ጸሎታችን ‹‹ቡርክት አንቲ እምአንስት ወቡሩክ ፍሬ ከርሥኪ፤ አንቺ ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ፤ የማኅፀንሽ ፍሬም የተባረከ ነው›› እያልን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እና ለልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ ውዳሴ እናቀርባለን፡፡

በማቴዎስ ወንጌል ፲፫፥፩-፳፫ ተጽፎ እንደምናገኘው ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የክርስትና ሕይወትን ከዘርና ፍሬ ጋር በማመሳሰል አስተምሯል፡፡ ይኸውም አንድ ገበሬ ዘር ሲዘራ በመንገድ ዳር የወደቀው ዘር ከመብቀሉ በፊት በወፎች እንደ ተበላ፤ በጭንጫ ላይ የተጣለውም ወዲያውኑ ቢበቅልም ነገር ግን ጠንካራ ሥር ስለማይኖረው በፀሐይ ብርሃን እንደ ጠወለገ፤ በእሾኽ መካከል የወደቀው ደግሞ ሲበቅል በእሾኽ እንደ ታነቀ፤ ከዂሉም በተለየ መልኩ በመልካም መሬት ላይ የተጣለው ዘር ግን አድጎ መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ ፍሬ እንደ ሰጠ የሚያስረዳ ነው፡፡ ይህም ምሳሌ አለው፡፡ ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ እንደ ተረጐመው በመንገድ ዳር የተዘራው ዘር የእግዚአብሔርን ቃል ሰምቶ የማያስተውል ክርስቲያን ምሳሌ ነው፤ ሙሉ እምነት ስለማይኖረው በመከራው ጊዜ አጋንንት ይነጥቁታልና፡፡ በጭንጫ ላይ የተዘራው ደግሞ ቃሉን ሰምቶ ወዲያው በደስታ የሚቀበል፣ ነገር ግን ተግባራዊ የማያደርግ ክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡ ይህ ምእመን በጠንካራ እምነት ላይ የጸና አይደለምና በሃይማኖቱ ምክንያት መከራ ወይም ስደት በደረሰበት ጊዜ ፈጥኖ ይሰናከላል፡፡ በእሾኽ መካከል የተዘራውም ቃሉን የሚሰማ ነገር ግን በዚህ ዓለም ዐሳብና ባለጠግነት ተታሎ ቃሉን የማይተገብር ክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡

በመልካም መሬት የተዘራው ደግሞ ቃሉን ሰምቶ የሚተገብር ክርስቲያን ምሳሌ፡፡ እንደዚህ ዓይነት ምእመን በተማረው ትምህርት ጸንቶ ይኖራል፤ መልካም ሥራም ይሠራል፡፡ በመልካም መሬት የተዘራው ዘር ስለ አንዱ ፋንታ መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ እንደሚያፈራ ዅሉ በክርስቲያናዊ ግብር ጸንቶ የሚኖር ምእመንም ሥራውን በሦስት መንገድ ማለትም በወጣኒነት፣ በማእከላዊነትና በፍጹምነት ደረጃ እንደሚወጣ፤ ዋጋውንም በሥራው መጠን እንደሚያገኝ የሚያስረዳ ነው፡፡ አንድም ባለ መቶ ፍሬ የሰማዕታት፤ ባለ ስድሳ የመነኮሳት፤ ባለ ሠላሳ በሕግ ተወስነው በዓለም የሚኖሩ ምእመናን ምሳሌ ነው፡፡ በተመሳሳይ ምሥጢር ዂሉም የፍሬ መጠን በዅሉም ጾታ ምእመናን ሕይወት ውስጥ እንደሚስተዋል ሊቃውንት ይተረጕማሉ፡፡ ስለዚህም በሰማዕትነትም፣ በምንኵስናም፣ በዓለማዊ ሕይወትም ውስጥ የሚኖሩ ምእመናን መልካም ግብራቸው እጅግ የበዛ ከኾነ በባለ መቶ ፍሬ፤ መካከለኛ ከኾነ በባለ ስድሳ፤ ከዚህ ዝቅ ያለ ከኾነ ደግሞ በባለ ሠላሳ ፍሬ ይመሰላል (ምንጭ፡- ትርጓሜ ወንጌለ ማቴዎስ)፡፡

ከዚሁ ዂሉ ጋርም ዕፀዋት ለመጠለያነት የማይጠቅሙ እንደዚሁም ለምግብነት ወይም ደግሞ ለመድኀኒትነትና ለሌላም ልዩ ልዩ አገልግሎት የሚጠቅም ፍሬ የማያስገኙ ከኾነ ተቈርጠው ይጣላሉ፡፡ ምእመናንም ‹ክርስቲያን› ተብለን እየተጠራን ያለ ምንም በጎ ምግባርና መንፈሳዊ ሕይወት ከኖርን ከእግዚአብሔር መንግሥት ውጪ እንኾናለን፡፡ ከኀጢአት ካልተለየን በምድር መቅሠፍት ይታዘዝብናል፤ በሰማይም ገሃነመ እሳት ይጠብቀናል፡፡ ይህን እውነት በመረዳት ዂላችንም በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን ልንኖር ያስፈልጋል፡፡ ‹‹… ምሣር በዛፎች ሥር ተቀምጧል፤ እንግዲህ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ዂሉ ይቈረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል›› (ማቴ. ፫፥፲) ተብሎ እንደ ተጻፈው ፍሬ የማያፈሩ ዕፀዋት በምሣር ተቈርጠው እንዲጣሉ እኛም ያለ መልካም ሥራ ከኖርን በእግዚአብሔር ዘለዓለማዊ ፍርድ ከገነት፣ ከመንግሥተ ሰማያት እንባረራለን፡፡ ይህ ክፉ ዕጣ እንዳይደርስብን ከሃይማኖታችን ሥርዓት፣ ከቤተ ክርስቲያናችን ትምህርት ሳንወጣ የቅዱሳንን ሕይወት አብነት አድርገን ለጽድቅ ሥራ እንሽቀዳደም፡፡ ‹‹እንግዲህ እነዚህን የሚያኽሉ ምስክሮች እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን እኛ ደግሞ ሸክምን ዅሉ ቶሎም የሚከበንን ኀጢአት አስወግደን የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤›› በማለት ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን (ዕብ. ፲፪፥፩-፪)፡፡

ይቆየን

የኢትዮጵያ ዘመን አቈጣጠር

በዲያቆን ኃይለ ኢየሱስ ቢያ

መስከረም  ፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የዘመን አቈጣጠር ዓመታትን፣ ወራትን፣ ሳምንታትን፣ ዕለታትን፣ ደቂቃን እና ድቁቅ ሰዓታትን በየሥፍራቸው (በየመጠናቸው) የሚገልጽ፤ የሚተነትን፤ የሚለካ የቤተ ክርስቲያን የቍጥር ትምህርት ነው፡፡ እነዚህ ዅሉ ተመርምረው፣ ተመዝነው፣ ተቈጥረው ሲያበቁ ምድብና ቀመር ተሰጥቷቸው የሚገኙበትን ውሳኔና ድንጋጌ የሚያሳውቅ የዘመን አቈጣጠር – ‹ሐሳበ ዘመን› ይባላል፡፡ ዓመታት፣ ወራት፣ ሳምንታት፣ ዕለታትና ሰዓታት የሚለኩት (የሚሠፈሩት፣ የሚቈጠሩት) በሰባቱ መሥፈሪያና በሰባቱ አዕዋዳት ነው፡፡ ሰባቱ መሥፈርታት የሚባሉትም፡- ሳድሲት፣ ኃምሲት፣ ራብዒት፣ ሣልሲት፣ ካልዒት፣ ኬክሮስ እና ዕለት ሲኾኑ ሰባቱ አዕዋዳት ደግሞ፡- ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅ፣ ዐውደ ዓመት፣ ዐውደ ፀሐይ፣ ዐውደ አበቅቴ፣ ዐውደ ማኅተም እና ዐውደ ቀመር ናቸው፡፡

  • ዐውደ ዕለት – ከእሑድ እስከ ቅዳሜ ያሉት ሰባቱ ዕለታት ሲኾኑ፤ አውራኅን (ወራትን) ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
  • ዐውደ ወርኅ – በፀሐይ ፴ ዕለታት፣ በጨረቃ ፳፱ ወይም ፴ ዕለታት ናቸው፤ ዓመታትን ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
  • ዐውደ ዓመት – በፀሐይ ቀን አቈጣጠር ፫፻፷፭ ቀን ከ፲፭ ኬክሮስ፤ በጨረቃ አቈጣጠር ፫፻፶፬ ቀን ከ፳፪ ኬክሮስ ነው፡፡ እነዚህ ሦስቱ በዕለት፤ አራቱ ደግሞ በዓመት ይቈጠራሉ፡፡ ዘመናትን ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
  • ዐውደ ፀሐይ – ፳፰ ዓመት ነው፤ በዚህ ዕለትና ወንጌላዊ ይገናኙበታል፡፡
  • ዐውደ አበቅቴ – ፲፱ ዓመት ነው፤ በዚህ ፀሐይና ጨረቃ ይገናኙበታል፡፡
  • ዐውደ ማኅተም – ፸፮ ዓመት ነው፤ በዚህ አበቅቴና ወንጌላዊ ይገናኙበታል፡፡
  • ዐውደ ቀመር – ፭፻፴፪ ዓመት ነው፤ በዚህ ዕለትና ወንጌላዊ፣ አበቅቴም ይገናኙበታል፡፡

የዘመናት (የጊዜያት) ክፍል እና መጠን

አንድ ዓመት በፀሐይ ፫፻፷፭ ቀን ከ፲፭ ኬክሮስ፤ በጨረቃ ፫፻፶፬ ቀን ከ፳፪ ኬክሮስ ነው፡፡ አንድ ወር በፀሐይ ፴ ዕለታት አሉት፤ በጨረቃ ፳፱ ወይም ፴ ዕለታት አሉት፡፡ አንድ ዕለት ፳፬ ሰዓት፤ አንድ ቀን ፲፪ ሰዓት፤ አንድ ሰዓት ፷ ደቂቃ ነው፡፡ አንድ ደቂቃ ፷ ካልዒት፤ አንድ ካልዒት ፩ ቅጽበት ነው፡፡ ኬክሮስ ማለት የክፍለ ዕለት ሳምንት (የዕለት ፩/፷ ወይም ፩/፳፬ኛ ሰዓት) ነው፡፡ አንድ ዕለት ፳፬ ሰዓት ወይም ፷ ኬክሮስ ነው፡፡

ክፍላተ ዓመት (የዓመት ክፍሎች)

የዓመት ክፍሎች፡- መጸው፣ በጋ፣ ፀደይ እና ክረምት ናቸው፡፡

  • ከመስከረም ፳፮ እስከ ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ክፍለ ዓመት መጸው ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት ሌሊቱ ረጅም፣ ቀኑ አጭር ነው፡፡
  • ከታኅሣሥ ፳፮ እስከ መጋቢት ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ክፍለ ዓመት በጋ ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት የቀኑና የሌሊቱ ርዝመት እኩል ነው፡፡
  • ከመጋቢት ፳፮ እስከ ሰኔ ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ወቅት ፀደይ ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት ቀኑ ይረዝማል፤ ሌሊቱ ያጥራል፡፡
  • ከሰኔ ፳፮ እስከ መስከረም ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ክረምት ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት የቀኑና የሌሊቱ ርዝመት እኩል ነው፡፡

የዘመናት አከፋፈል በአራቱ ወንጌላውያን እና ዘመን የሚለወጥበት ሰዓት

  • ማቴዎስ ዘመኑን ከምሽቱ ፩ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከሌሊቱ ፮ ሰዓት ይፈጽማል፡፡
  • ማርቆስ ዘመኑን ከሌሊቱ ፯ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከጠዋቱ ፲፪ ሰዓት ይፈጽማል፡፡
  • ሉቃስ ዘመኑን ከጠዋቱ ፩ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከቀኑ ፮ ሰዓት (በቀትር) ይፈጽማል፡፡
  • ዮሐንስ ዘመኑን ከቀኑ ፯ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከቀትር በኋላ ከምሽቱ ፲፪ ሰዓት ይፈጽማል፡፡

የወራት፣ የሌሊትና የቀን ሥፍረ ሰዓት

  • መስከረም – ሌሊቱ ፲፪፤ መዓልቱም (ቀኑ) ፲፪ ሰዓት ነው፡፡
  • ጥቅምት – ሌሊቱ ፲፫፤ መዓልቱ ፲፩ ሰዓት ነው፡፡
  • ኅዳር – ሌሊቱ ፲፬፤ መዓልቱ ፲ ሰዓት ነው፡፡
  • ታኅሣሥ – ሌሊቱ ፲፭፤ መዓልቱ ፱ ሰዓት ነው፡፡
  • ጥር – ሌሊቱ ፲፬፤ መዓልቱ ፲ ሰዓት ነው፡፡
  • የካቲት – ሌሊቱ ፲፫፤ መዓልቱ ፲፩ ሰዓት ነው፡፡
  • መጋቢት – ሌሊቱ ፲፪፤ መዓልቱ ፲፪ ሰዓት ነው፡፡
  • ሚያዝያ – ሌሊቱ ፲፩፤ መዓልቱ ፲፫ ሰዓት ነው፡፡
  • ግንቦት – ሌሊቱ ፲፤ መዓልቱ ፲፬ ሰዓት ነው፡፡
  • ሰኔ – ሌሊቱ ፲፱፤ መዓልቱ ፲፭ ሰዓት ነው፡፡
  • ሐምሌ – ሌሊቱ ፲፤ መዓልቱ ፲፬ ሰዓት ነው፡፡
  • ነሐሴ – ሌሊቱ ፲፩፤ መዓልቱ ፲፫ ሰዓት ነው፡፡

የበዓላት እና አጽዋማት ኢየዐርግ እና ኢይወርድ (ከፍታ እና ዝቅታ)

  • ጾመ ነነዌ ከጥር ፲፯ ቀን በታች፤ ከየካቲት ፳፩ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ዐቢይ ጾም ከየካቲት ፩ ቀን በታች፤ ከመጋቢት ፭ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ደብረ ዘይት ከየካቲት ፳፰ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፪ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ሆሣዕና ከመጋቢት ፲፱ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፳፫ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ስቅለት ከመጋቢት ፳፬ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፳፰ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ትንሣኤ ከመጋቢት ፳፮ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፴ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ርክበ ካህናት ከሚያዝያ ፳ ቀን በታች፤ ከግንቦት ፳፬ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ዕርገት ከግንቦት ፭ ቀን በታች፤ ከሰኔ ፲፱ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ጾመ ሐዋርያት ከግንቦት ፲፮ ቀን በታች፤ ከሰኔ ፳ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ጾመ ድኅነት ከግንቦት ፲፰ ቀን በታች፤ ከሰኔ ፳፪ ቀን በላይ አይውልም፡፡

የተውሳክ አወጣጥ

፩. የዕለት ተውሳክ

የዕለት ተውሳክ በቅዳሜ ይጀምራል፡፡ የቅዳሜ ተውሳክ ፰፤ የእሑድ ተውሳክ ፯፤ የሰኞ ተውሳክ ፮፤ የማክሰኞ ተውሳክ ፭፤ የረቡዕ ተውሳክ ፬፤ የሐሙስ ተውሳክ ፫፤ የዓርብ ተውሳክ ፪ ነው፡፡

፪. የአጽዋማትና የበዓላት ተውሳክ

የነነዌ ተውሳክ አልቦ (ባዶ)፤ የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬፤ የደብረ ዘይት ተውሳክ ፩፤ የሆሣዕና ተውሳክ ፪፤ የስቅለት ተውሳክ ፯፤ የትንሣኤ ተውሳክ ፱፤ የርክበ ካህናት ተውሳክ ፫፤ የዕርገት ተውሳክ ፲፰፤ የጰራቅሊጦስ ፳፰፤ የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ ፳፱፤ የጾመ ድኅነት ተውሳክ ፩ ነው፡፡

በዓላት እና አጽዋማት የሚውሉባቸው ዕለታት

  • ጾመ ነነዌ፣ ዐቢይ ጾም እና ጾመ ሐዋርያት – ሰኞ፡፡
  • ደብረ ዘይት፣ ሆሣዕና፣ ትንሣኤ እና ጰራቅሊጦስ – እሑድ፡፡
  • ስቅለት – ዓርብ፡፡
  • ርክበ ካህናት እና ጾመ ድኅነት – ረቡዕ፡፡
  • ዕርገት – ሐሙስ ቀን ይውላል፡፡

መጥቅዕ እና አበቅቴ

መጥቅዕ እና አበቅቴ ከየት መጣ ቢሉ፣

የመጀመሪያው – የፀሐይና የጨረቃ ቀን አቈጣጠር ልዩነት ነው፡፡ አንድ ዓመት በፀሐይ ፫፻፷፭ ቀን ከ፲፭ ኬክሮስ፤ በጨረቃ ፫፻፶፬ ቀን ከ፳፪ ኬክሮስ ነው፡፡ የሁለቱ ልዩነት (፫፻፷፭ – ፫፻፶፬ = ፲፩) አበቅቴ ይባላል፡፡

ሁለተኛው – የቅዱስ ድሜጥሮስ ሱባዔ ውጤት ነው፡፡ ቅዱስ ድሜጥሮስ በዓላትና አጽዋማት የሚውሉበት ቀን በጥንተ ዕለቱ እንዲውል ለማድረግ ይመኝ ነበርና ከሌሊቱ ፳፫ ሱባዔ፤ ከቀኑ ፯ ሱባዔ ገብቷል፡፡ ፳፫×፯ = ፻፷፩ ይኾናል፡፡ ፻፷፩ ለ፴ ሲካፈል ፭ ይደርስና ፲፩ ይተርፋል፤ ይህን ቀሪ አበቅቴ አለው፡፡ ፯ በሰባት ሲባዛ ፵፱ ይኾናል (፯×፯ = ፵፱)፡፡ ፵፱ ለ፴ ሲካፈል (፵፱÷፴) ፩ ደርሶ ፲፱ ይቀራል፤ ይህን ቀሪ መጥቅዕ አለው፡፡

ዓመተ ዓለምን፣ ወንጌላዊን፣ ዕለትን፣ ወንበርን፣ አበቅቴን፣ መጥቅዕን፣ መባጃ ሐመርን፣ አጽዋማትን እና በዓላትን ለይቶ ለማወቅ ሒሳባዊ ሰሌቱ እንዲሚከተለው ነው፤

ዓመተ ዓለምን ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ኵነኔ ሲደመር ዓመተ ምሕረት ሲኾን፣ ውጤቱ ዓመተ ዓለም ይባላል፡፡ ለምሳሌ ፶፭፻ + ፳፻፲ = ፸፭፻፲ (5500 + 2010 = 7510)፤ ፸፭፻፲ (7510) ዓመተ ዓለም ይባላል፡፡

ወንጌላዊን ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ዓለምን ለአራት ማካፈል ነው፡፡ ዓመተ ዓለሙ ለአራት ተካፍሎ ፩ ሲቀር ዘመኑ ማቴዎስ፤ ፪ ሲቀር ማርቆስ፤ ፫ ሲቀር ሉቃስ፤ ያለ ቀሪ ሲካፈል ዮሐንስ ይኾናል፡፡

ዕለቱን (ለምሳሌ መስከረም ፩ ቀንን) ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ዓለም ሲደመር መጠነ ራብዒት (ለአንድ ወንጌላዊ የደረሰው) ሲካፈል ለሰባት ነው፡፡ ዓመተ ዓለም እና መጠነ ራብዒት ተደምሮ ለሰባት ተካፍሎ ፩ ሲቀር ማክሰኞ፤ ፪ ሲቀር ረቡዕ፤ ፫ ሲቀር ሐሙስ፤ ፬ ሲቀር ዓርብ፤ ፭ ሲቀር ቅዳሜ፤ ፮ ሲቀር እሑድ፤ ያለ ቀሪ እኩል ሲካፈል ሰኞ ይኾናል፡፡

ተረፈ ዘመኑን (ወንበሩን) ለማግኘት ዓመተ ዓለም ለሰባት ተካፍሎ የሚገኘው ቀሪ ተረፈ ዘመን (ወንበር) ይባላል፡፡ ከቀሪው ላይ ስለ ተጀመረ ተቈጠረ፤ ስላልተፈጸመ ታተተ (ተቀነሰ) ብሎ አንድ መቀነስ ስሌቱ ሲኾን ቀሪው ወንበር ይባላል፡፡

አበቅቴን ለማግኘት ወንበር ሲባዛ በጥንተ አበቅቴ (፲፩) ሲካፈል ለ፴ ኾኖ ቀሪው አበቅቴ ይባላል፡፡ መጥቅዕን ለማግኘት ወንበር ሲባዛ በጥንተ መጥቅዕ (፲፱) ሲካፈል ለ፴ ኾኖ ቀሪው መጥቅዕ ይባላል፡፡

ከዚህ ላይ አዋጁን (መመሪያውን) እንመልከት፤ አዋጁም መጥቅዕ ከ፲፬ በላይ ከኾነ መጥቅዕ በመስከረም ይውላል፤ የመስከረም ማግስት (ሳኒታ) የካቲት ይኾናል፡፡ ፲፬ ራሱ መጥቅዕ መኾን አይችልም፡፡ መጥቅዕ ከ፲፬ በታች ከኾነ በጥቅምት ይውላል፤ የጥቅምት ማግስት (ሳኒታ) ጥር ነው፡፡ መጥቅዕ ሲደመር አበቅቴ ውጤቱ ዅልጊዜ ፴ ነው፡፡ መጥቅዕ አልቦ (ዜሮ) ሲኾን መስከረም ፴ የዋለበት የቀኑ ተውሳክ መባጃ ሐመር ይኾናል፡፡

መባጃ ሐመርን ለማግኘት የዕለት ተውሳክ ሲደመር መጥቅዕ ሲካፈል ለሠላሳ ነው (የዕለት ተውሳክ+መጥቅዕ÷፴ = መባጃ ሐመር)፡፡ ቍጥሩ ለሠላሳ መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወሰዳል፡፡

የአጽዋማት እና የበዓላት ተውሳክ አወጣጥ

ጾምን ለማግኘት ስሌቱ መባጃ ሐመር ሲደመር የጾም ተውሳክ ሲካፈል ለሠላሳ ነው (መባጃ ሐመር+የጾም ተውሳክ÷፴ = ጾም)፡፡ ቍጥሩ ለሠላሳ መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወሰዳል፡፡ በዓላትን ለማግኘት ስሌቱ መባጃ ሐመር ሲደመር የበዓል ተውሳክ ሲካፈል ለሠላሳ ነው (መባጃ ሐመር+የበዓል ተውሳክ÷፴ = በዓል)፡፡ ቍጥሩ ለሠላሳ መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወሰዳል፡፡ በዚህ ሒሳብ መሠረት በየዓመቱ የሚመላለሱ በዓላት እና አጽዋማት የሚዉሉበትን ቀን ማወቅ ይቻላል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዝክረ ዐውደ ዓመት

በዶክተር ታደለ ገድሌ

መስከረም ፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የዓለም ሕዝብ በየዓመቱ በታላቅ ደስታ ከሚያከብራቸውና ከሚዘክራቸው በዓላት መኻከል አንዱ የዘመን መለወጫ በዓል ነው፡፡ ዕለታት እየበረሩ፣ ወራት እየተቀመሩ አልፈው አዲስ ዘመን በባተ ቍጥር ሕዝብ ዅሉ ፍሥሐ ያደርጋል፡፡ ሰላምን፣ ብልጽግናን፣ ጤንነትን፣ ፍቅርን፣ … ለወዳጅ ዘመድ ይመኛል፡፡ አዲሱ ዓመት ዘመነ ሰላም፣ ዘመነ ጥጋብ … እንዲኾን መልካም ምኞቱን ይገልጻል፡፡ አዲስ የሥራ ዕቅድና ምኞትን በስሜቱ ያሠርፃል፡፡ ወደ ተግባርም ለመተርጐም ሌት ተቀን ይፋጠናል፡፡ በአገራችን ኢትዮጵያ የዘመን መለወጫ በዓል መስከረም ፩ ቀን ይከበራል፡፡ ‹‹ለመኾኑ በኢትዮጵያ መስከረም የአዲስ ዓመት መባቻ ኾኖ የተመረጠው ለምንድን ነው? በአራቱ ወንጌላውያንና በአራቱ እንስሳ (ኪሩቤል) መካከል ያለው የስያሜ ትሥሥርስ ምሥጢሩ ምንድን ነው?›› የሚሉና የመሳሰሉ ጥያቄዎች በአእምሯችን ሊመላለሱ ይችላሉ፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢ ለነበሩት አለቃ አያሌው ታምሩ በአንድ ወቅት እነዚህን ጥያቄዎች አቅርበንላቸው (የካቲት መጽሔት፣ 15ኛ ዓመት ቍጥር 1፤ መስከረም 1984 ዓ.ም፣ ገጽ 4 – 7 እና 34)፤ ኢትዮጵያውያን አዲስ ዓመትን በመስከረም የሚያከብሩት ከኖኅ በፊትና በኋላ በተዘረጋው ስሌተ ዘመን እንደ ኾነ በማስረዳት የሚከተለውን ትምህርት ሰጥተዋል፤

የኢትዮጵያ ይዞታ መሠረተ ባሕርይ ከጥንት ጀምሮ ሃይማኖት ሲኾን በጽሑፍም በአፈ ታሪክም እየተወራረሰ የመጣ ነገር ነው፡፡ በሰው ፍልስፍና ወይም በመንግሥት ለውጥ ምክንያት የተናወጠ ነገር የለም፡፡ ለውጦች ጦርነቶችና ግጭቶች፣ በተለያዩ የመንግሥት መሪዎች ቢፈራረቁም መሠረተ እምነትን አልነኩም፡፡ የአገሪቱን ባህልና ታሪክ የሚነካ ለውጥ አልደረሰም፡፡ ነገር ግን ባለ ሥልጣናት በሹም ሽር ሲቀያየሩ በምርጫ የመንበረ መንግሥት መቀመጫ ቦታ ልውውጥም ሲደረግ መጥቷል፡፡ አዲስ ዓመት ከጥንት ከአዳም ጀምሮ የነበረ በዓል ነው፡፡ ከአዳም ጀምሮ የመጣውን የቍጥር ዘመን በጽሑፍ ያስተላለፈው ሄኖክ ነው፡፡ ይኸውም ሳምንታት በፍጥረት ከእሑድ እስከ ቅዳሜ ሰባት፣ የዕለት ሰዓት ሃያ አራት፣ የወር ቀናት ሠላሳ፣ የዓመት ቀናት ሦስት መቶ ስልሳ አራት ሲኾኑ ስልሳ አምስተኛዋ መዛወሪያ ቀን ናት፡፡ ጳጕሜን አምስት ቀን ስትኾን የሚዘለው ስድስተኛው ቀን ሠግር (የወር መባቻ) ይኾናል፡፡

የኢትዮጵያ ዘመን አቈጣጠር ከጥፋት ውኃ በፊት ሦስት ትውልዶችን አሳልፏል፡፡ እነርሱም ሄኖክ፣ ላሜህና ኖኅ ናቸው፡፡ ኖኅ የሰው ልጆች ዅሉ አባት እንደ ኾነው እንደ አዳም የሚቈጠር ከጥፋት ውኃ በመጨረሻ የተረፈ አባት ነው፡፡ ኖኅ ከአባቶቹ የተቀበለውን ጥበብ ዅሉ ለልጆቹ አስተላለፈ፡፡ ለአብነትም ዛሬ የምንጠቀምበት የኮሶ መድኃኒት የኖኅ ተረፈ ጥበብ ነው፡፡ ኖኅ በሰኔ ወር ከመርከብ በወጣ ጊዜ የበግ መሥዋዕት ሠውቶ ሰውን ከእግዚአብሔር ጋር አስታረቀ፡፡ እግዚአብሔርም ያን ጊዜ ከኖኅ ጋር አዲስ ቃል ኪዳን መሠረተ፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ልቡ ምንም ክፉ ቢኾንና ቅጣትም የማይቀርለት ቢኾን ጨርሶ እንደማያጠፋው ለኖኅ ቃል ገባለት፡፡ ምልክቱንም የቀስቱን ደጋን ወደራሱ፣ ገመዱን ደግሞ ወደ ሰው ልጆች አድርጐ በደመና ላይ ቀስት ስሎ አሳይቶታል፡፡ 

ጌታ ‹‹መዓልትና ሌሊት፣ በጋና ክረምት፣ ብርድና ሙቀት፣ ዘርና መከር ጊዜያቸውን ጠብቀው ሲፈራረቁ ይኖራሉ፡፡ በምድር ላይ ይህ አይቀርም›› በማለት እንደ ተናገረው በቃሉ መሠረት ክረምት ገባ፡፡ ክረምቱ ካለፈ በኋላ የዓመት መሥፈሪያ ሦስት መቶ ስልሳ አምስት ቀናት በመኾናቸው መስከረም አንድ ቀን የአዲስ ዓመት መባቻ ኾነ፡፡ አዲስ ዓመት ሥራውን ጨርሶ በሔደ ቍጥር፣ ዕለት ግን በየጊዜው እየታደሰ ይሔዳል፡፡ እስከ አዲስ ኪዳን መጀመሪያ ድረስ አበው በልዩ ልዩ ጊዜያት የተገለጹላቸውን ምልክቶች በመያዝ የየዘመናትን ብተት (መግቢያ) የእግዚአብሔርን ዙፋን ተሸካሚ በኾኑ በኪሩቤል መላእክት እያመሳሰሉ ገጸ ሰብእ፣ ገጸ ላህም (ላም) ገጸ ንሥር (አሞራ)፣ ገጸ አንበሳ እያሉ ዓመታትን ይመድቡ ነበር፡፡ ከስብከተ ሐዲስ በኋላ ግን ይህ ተሽሮ ወንጌልን በጻፉት አርድእት ስም ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስ፣ ዮሐንስ ስም ተሰየመ፡፡ ወንጌላውያኑ ወንጌልን ሲጽፉ ዕለት ተቀደም (በቅደም ተከተል) ነውና ተራቸውን ጠብቀው በየዓመቱ ይመላለሳሉ፡፡ ይህም ማለት ዘመኑ ዘመነ ምሕረት መኾኑን ለማብሠርና ድኅነት (መዳን) የሚሰበክበት ዘመን መምጣቱን ለመግለጽ ነው፡፡

በገጸ ሰብእ የተተካው ማቴዎስ ነው፡፡ ምሥጢሩም ‹‹ጌታ ከሰማይ ወረደ፤ ሰው ኾነ›› ብሎ ማስተማሩን የሚያመለክት ነው፡፡ በገጸ አንበሳ የተተካው ማርቆስ ነው፡፡ ይኸውም አሕዛብ በግብጽ (ምሥር) በላህም (በላም)፣ በጣዕዋ (ጥጃ) አምሳል ጣዖት አሠርተው ያመልኩ ስለ ነበር ያንን አምልኮ አጥፍቶ፣ ሽሮ በክርስቶስ እንዲያምኑ ስላደረገ ነው፡፡ በገጸ እንስሳ (ላህም) የተተካው ሉቃስ ነው፡፡ ምሳሌነቱም የጌታን መሥዋዕትነት ስለሚያስተምር ነው፡፡ በገጸ ንሥር የተተካው ዮሐንስ ነው፡፡ ንሥር ከአዕዋፍ ዅሉ መጥቆ ይሔዳል፡፡ መሬትም ላይ ምንም ኢ ምንት ነገር ብትወድቅ አትሠወረውም፡፡ ዓይኑ ጽሩይ (ብሩህ) ነው፡፡ ይህም ማለት ቅዱስ ዮሐንስ ዓለም ሳይፈጠር፣ ዘመን ሳይቈጠር ወደ ነበረው ኹኔታ በሕሊናው ርቆ በመሔድ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ቀዳማዊ ቃል መኾኑን፤ እግዚአብሔርም ዓለሙን የፈጠረው በእርሱ ቃል እምነት መኾኑን፤ ያም ቃል ሰው መኾኑን ስለሚያስተምር ነው ገጸ ንሥር የተባለው፡፡ የሦስቱ ወንጌላውያን ትምህርት ታሪክ ጠቀስ ኾኖ ለሰሚዎችና አንባቢዎች ዅሉ በቶሎ ሲረዳ፣ የዮሐንስ አስተምህሮ ግን ጥልቅ የአእምሮ ብስለትና ምርምርን ይጠይቃል፡፡

ዘመን በተለወጠ ቍጥር ከሰው ልጆች ስሜት ጋር አብሮ የሚንቀሳቀስ ተስፋ አለ፡፡ በጥፋት ዘመን ሰማይ በደመና ተሸፍኖ፣ ከላይ ዝናም፣ ከታች የሚፈልቀው ጎርፍ የኖኅ ሰዎችን አስጨንቋቸው ነበር፡፡ በኋላ ግን ምድር ላይ ለውጥ ታየ፡፡ ነፋስ ነፈሰ፡፡ ብርሃን ፈነጠቀ፡፡ አበባ አበበ፡፡ የኖኅ መልእክተኛ የኾነችው ርግብም ‹‹ማየ አይህ ነትገ፤ የጥፋት ውኃ ጐደለ›› እያለች ርጥብ ቄጠማ በአፏ ይዛ መጥታ ስታበሥረው የኖኅ ሰዎች ከመርከቧ ወደ መሬት ሲወርዱ በመጀመሪያ አበባ፣ እንግጫ፣ ቄጠማ፣ የለመለመ ሣር … አገኙ፡፡ እግዚአብሔርንም በአንቃዕድዎ ልቡና አመሰገኑና በዓላቸውን አከበሩ፡፡ በዚህም አምሳል ክረምት አልፎ መሬት በምታሸበርቅበት በምታብበት ከመስከረም አንድ ቀን ጀምሮ አዲስ ዓመታችንን እናከብራለን፡፡ ሰውም ከመሬት የተገኘ በመኾኑ እንደ ዕፀዋትና እንደ አበቦች ዅሉ በመስከረም ወር በተስፋ ስሜት ይለመልማል፡፡ ያጣው አገኛለሁ፣ የታመመው እድናለሁ ብሎ በቁርጥኝነት ይነሣሣል፡፡ በዘልማድም እምነቶች ይገለጻሉ፤ ‹‹በዮሐንስ እረስ፣ በማቴዎስ እፈስ … ጳጕሜ ሲወልስ ጎታህን አብስ … ጳጕሜ ሲበራ ስንዴህን ዝራ›› እያሉ ገበሬዎች ይናገራሉ፤ ይተነብያሉ፡፡ ገበሬዎች ገና በግንቦት ወር የክረምቱን አገባብ ለይተው የሚዘሩትን ዘር ደንብተው የሚያውቁ ሜትሮሎጂስቶች (የአየር ጠባይዕ ትንበያ ባለሙያዎች) ናቸው፡፡

አለቃ አያሌው እንዳስተማሩት ዐውደ ዓመት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባሕረ ሐሳብ መሠረት የሚከበርና መንፈሳዊ ምሥጢር ያለው ሃይማኖታዊም አገራዊም በዓል ነው፡፡ በቅዱስ ዮሐንስ በዓል በቤተ ክርስቲያን ከሚፈጸመው መንፈሳዊ አገልግሎት ባሻገር በአዲሱ ዓመት ዋይዜማ በየቤቱ ጨፌና ቄጠማ ይጎዘጎዛል፡፡ አበባ በሥርዓቱ እየተዘጋጀ በየቦታው ይቀመጣል፡፡ ልጆችና አረጋውያን አዳዲስ ልብሳቸውን ለብሰው በደስታ ይፈነድቃሉ፡፡ አመሻሽ ላይ ችቦ አቀጣጥለው ‹‹ኢዮሃ አበባዬ መስከረም ጠባዬ … ኢዮሃ የበርበሬ ውኃ … በሸዋ በጎንደር፣ በትግራይ በወሎ፣ በሐረርጌ፣ በሲዳሞ … ያላችሁ እንዴት ከረማችሁ? እንኳን ከዘመን ዘመን ከጨለማ (ሰኔ፣ ሐምሌ፣ ነሐሴ) ወደ ብርሃን (መስከረም) በሰላም አሸጋገራችሁ! … እንጉሮ ገባሽ በያመቱ ያምጣሽ …›› እያሉ ያቀጣጠሉትን ችቦ በአየር ላይ እየወረወሩ ደስታቸውን ሲገልጹ፣ የምሽቱም የችቦ እሳት ርቀት እስከሚወስነው አድማስ ድረስ ከቀዬ ቀዬ፣ ከአድባር እስከ አድባር፣ ከመንደር እስከ መንደር … ሲንቀለቀልና ሲንቦገቦግ መሬት የእሳት ላንቃዋ ተከፍቶ ነበልባል የምትተፋ ትመስላለች፡፡ የአየር ላይ ወጋገኑን ሲመለከቱት ደግሞ እግዚአብሔር ከመንበረ ጸባዖቱ ወርዶ የብርሃን አክሊል ደፍቶ ቀይ መጐናጸፊያ ተጎናጽፎ ጨለማውን እየገፈፈ በጠፈር (በአየር) ላይ እየተንሳፈፈ ወደ መሬት የሚወርድባት የመጨረሻዋን የምጽአትን ቀን ታስታውሳለች – የዕንቍ ጣጣሽ ሌሊት፡፡

አባቶች የችቦ ብርሃን ላሰባሰበው ሕዝብ ቡራኬና ምርቃት ያደርጋሉ፡፡ ‹‹የተዘራውን እኽል እኽለ በረከት፣ የዘነመውን ዝናም ዝናመ ምሕረት፣ ዘመኑን የሰላም ዓመት ያድርግልን፡፡ እኽል ይታፈስ፤ ይርከስ፡፡ ሳቢ በሬውን፣ አራሽ ገበሬውን ይባረክ፣ ቁንጫ፣ ተባይ ተምች፣ አንበጣ … ፀረ ሰብል ዅሉ እንደ ችቦው ተቀጣጥለው ይንደዱ …›› እያሉ ይመርቃሉ፡፡ እናት አባት በልጆቻቸው፣ በወዳጅ ዘመዶቻቸው የተበረከተላቸውን የእንግጫ ጉንጉን በራሳቸው፣ በእንጀራ ማቡኪያና መሶቡ፣ ከቤቱ ምሰሶ ላይ … ያሥራሉ፡፡ ይህ በአበባ የተዘጋጀ የእንግጫ ጉንጉን የመስቀል ደመራ ዕለት ከእሳቱም ከዐመዱም ላይ ይጣላል፡፡ ተምሳሌቱም እንደ ቁንጫ ዅሉ ቁርጥማቱ ራስ ምታቱ፣ ምችጎንፍ ቁርጠቱ፣ ምቀኛ፣ ሸረኛ፣ ሰላቢው፣ ሌባ፣ ቀማኛ ቀጣፊው … እንዲቃጠልና እንዲጠፋ ነው፡፡ በቤቱም (በአባወራው ቤት) በረከትና ሞገስ (አግሟስ) እንዲቀርብም ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በአዲስ ዓመት አዲስ ሕይወት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ወንጌላዊው ዮሐንስ በራእዩ ‹‹እነሆሉን አዲስ አደርጋለሁአዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፤ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፡፡ ባሕርም ወደ ፊት የለም›› በማለት እንደ ተናገረው (ራእ. ፳፩፥፩-፭) ዘመን እያለፈ አዲስ ዘመን ይተካል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን በዕድሜ ላይ ዕድሜን እየጨመረ፣ ዘመናትን እያፈራረቀ በየጊዜያቱ አዲስ ዓመትን ያመጣልናል፡፡ አሁንም በእርሱ ቸርነት ለ፳፻፲ ዓመተ ምሕረት ደርሰናል፡፡ እኛም ዘመን በመጣ ቊጥር ‹‹እንኳን በሰላም አደረሳችሁ!›› እንባባላለን፡፡ ስለ ትናንትና እንጂ ስለ ነገ ባናውቅም እስከ ዛሬ ድረስ በመቆየታችንም እንደሰታለን፡፡ ነገን በተስፋ ለሚጠባበቅ ሰው በእውነትም ዓመት አልፎ ዓመት ሲተካ በጣም ያስደስታል፡፡ ነገር ግን ያለፈውን ዓመት ስንዋሽ፣ ስንሰርቅ፣ ስንዘሙት፣ ስንጣላ፣ ስንተማማ፣ ስንደባደብ፣ ስንሰክር አሳልፈን ከኾነ ‹‹እንኳን አደረሳችሁ!›› የሚለው ቃል ርግማን ይኾንብናል፡፡

ስለ ተለወጠው ዘመን ሳይኾን ስላልተቀየረው ሰብእናችን፤ ስላልተለወጠው ማንነታችን፤ ስላልታደሰው ሥጋችን ማሰብ ይኖርብናል፡፡ በኀጢአት እየኖሩ ዐውደ ዓመትን ማክበር ራስን ያለ ለውጥ እንዲቀጥል ማበረታታት ነውና ከምንቀበለው ዘመን ይልቅ መጪውን ዘመን ለንስሐ ለማድረግ መዘጋጀት ይጠበቅብናል፡፡ ያሳለፍነውን የኀጢአት ጊዜ እያሰብን እስከ ዛሬ ድረስ የጠበቀንን እግዚአብሔርን እያመሰገንን ሕይወታችንን በጽድቅ ልናድስ ይገባናል፡፡ በንስሐ ባልታደሰ ሕይወታችን በዕድሜ ላይ ዕድሜ ቢጨመርልን ለእኛም ለዘመኑም አይበጅምና፡፡ ‹‹ባረጀ ልብስ አዲስ እራፊ የሚያኖር የለም፤ መጣፊያው ልብሱን ይቦጭቀዋልና፡፡ መቀደዱም የባሰ ይኾናል›› እንዳለ ጌታችን በወንጌል (ማቴ. ፱፥፲፯)፡፡

ያለ ክርስቲያናዊ ምግባር እየኖርን ዘመንን ብቻ የምንቈጥር ከኾነ ሕይወታችንን ከሰብአዊነት ክብር ብሎም ከክርስቲያናዊ ሕይወት በታች እናደርገዋለን፡፡ ራስን ከጊዜ ጋር ማወዳደር መቻል ክርስቲያናዊ ሓላፊነት ነው፡፡ ይኸውም ጊዜ ሳይቀድመኝ ልቅደመው ብሎ ማሰብ መቻል ነው፡፡ በአሮጌ ሕይወት ውስጥ ኾነን ዓመቱን አዲስ ከማለት ይልቅ ከኀጢአት ወደ ጽድቅ በመሸጋገር ራሳችንን በጽድቅ ሥራ ማደስ ይበልጣል፡፡ ስለዚህም ያለፈውን ዓመት በምን ኹኔታ አሳለፍሁት? በመጭው ዓመትስ ምን ማድረግ ይጠበቅብኛል? በሚል ጥያቄ መነሻነት በአዲሱ ዓመት መንፈሳዊ ዕቅድ ሊኖረን ይገባል፡፡

በመሠረቱ ዘመን ራሱን እየደገመ ይሔዳል እንጂ አዲስ ዓመት የለም፡፡ ሰዓታትም ዕለታትም እየተመላለሱ በድግግሞሽ ይመጣሉ እንጂ ከዚህ በፊት ያልነበረ ሰዓት ወይም ቀን ወይም ደግሞ ወር አለዚያም ዓመት የለም፡፡ ወርኀ መስከረምም ለብዙ ሺሕ ዓመታት ራሱን እየደገመ በየዓመቱ አዲስ ሲባል ይኖራል እንጂ ሌላ መስከረም የለም፡፡ ‹‹የኾነው ነገር እርሱ የሚኾን ነው፤ የተደረገውም ነገር እርሱ የሚደረግ ነው፡፡ ከፀሐይም በታች አዲስ ነገር የለም፡፡ ማንምእነሆ ይህ ነገር አዲስ ነውይል ዘንድ ይችላልን? እርሱ ከእኛ በፊት በነበሩት ዘመናት ተደርጎአል›› እንዳለ ጠቢቡ ሰሎሞን (መክ. ፩፥፱-፲)፡፡ ዘመን አዲስ የሚባለው እኛ ሰዎች (ክርስቲያኖች) ሕይወታችንን በጽድቅ ስናድስ ነው፡፡ ያለ መልካም ሥራ የሚመጣ ዓመት፤ ከክፉ ግብር ጋር የምንቀበለው ዘመን አዲስ ሊባልም፣ ሊኾንም አይችልም፡፡ የሰው ልጅ መንፈሳዊ ሕይወት በመልካም ሥራ ሲዳብር ግን መጭው ዘመን ብቻ ሳይኾን ያለፈው ዘመንም አዲስ ነው፡፡

በዘመናት ዑደት ውስጥ ሕይወታቸውን በሙሉ በጽድቅ የሚያሳልፉ ወይም ኀጢአታቸውን በንስሐ የሚያጸዱ ብዙ ጻድቃን ምእመናን ቢኖሩም ሰውነታችንን ጥለን በክፉ ምግባር እየኖርን  ዕድሜያችንን የምንቈጥር ኃጥኣን ጥቂቶች አይደለንም፡፡ ስለኾነም በኀጢአት ያሳለፍነውን ዘመን በማሰብ መጭውን ዘመን ለመልካም ሥነ ምግባር ልናውለው፤ አንድም ለንስሐ መግቢያ ልናደርገው ያስፈልጋል፡፡ ‹‹የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት፤ በመዳራትና በሥጋ ምኞትም፣ በስካርም፣ በዘፈንም፣ ያለ ልክም በመጠጣት፣ ነውርም ባለበት፣ በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃል›› በማለት ቅዱስ ጴጥሮስ አስተምሮናልና (፩ኛ ጴጥ. ፬፥፫)፡፡ እናም ለአዲስ ዓመት አዲስ ሕይወት እንደሚያስፈልግ በመረዳት ራሳችንን በንስሐ ሳሙና አሳጥበን በንጽሕና ልንኖር ያስፈልጋል፡፡ ‹‹ታጠቡ፤ ሰውነታችሁንም አንጹ፡፡ የሥራችሁን ክፋት ከዓይኔ ፊት አስወግዱ፡፡ ክፉ ማድረግን ተዉ … ልባችሁን አንጹ፤ ሰውነታችሁንም ንጹሕ አድርጉ›› ተብለን ታዝዘናልና (ኢሳ.፩፥፲፮፤ መጽሐፈ ኪዳን)፡፡

በአጠቃላይ በዚህ አዲስ ዓመት ከክፉ ምግባር ዅሉ ተለይተን፣ ከዚህ በፊት በሠራነው ኀጢአታችን ንስሐ ገብተን፣ ለወደፊቱ በጽድቅ ሥራ ኖረን እግዚአብሔርን ልናስደስት ይገባናል፡፡ ‹‹ይደልወነ ከመ ንግበር በዓለ ዐቢየ በኵሉ ንጽሕና እስመ ይእቲ ዕለት ቅድስት ወቡርክት፡፡ ወንርኀቅ እምኵሉ ምግባራት እኩያት፡፡ ወንወጥን ምግባራተ ሠናያተ ወሐዲሳተ በዘቦቶን ይሠምር እግዚአብሔር፤ አሁንም በፍጹም ንጽሕና ታላቅ በዓልን አድርገን ልናከብር ይገባናል፡፡ ይህቺ ዕለት ከሌሎች ዕለታት ተለይታ የተባረከች ናትና፡፡ ከክፉ ሥራዎችም ተለይተን እግዚአብሔር ደስ የሚሰኝባቸውን አዳዲስ የኾኑ በጎ ሥራዎችን እንሥራ›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መጽሐፈ ስንክሳር፣ መስከረም ፩ ቀን)፡፡

የተወደዳችሁ ምእመናን! ‹‹ዐዘቅቱ ይሙላ፤ ተራራውና ኮረብታውም ዅሉ ዝቅ ይበል፡፡ ጠማማውም የቀና መንገድ ይኹን፡፡ ሸካራውም መንገድ ትክክል ይኹን፡፡ ሥጋም የለበሰ የእግዚአብሔርን ማዳን ይይ›› ተብሎ እንደ ተነገረው (ሉቃ. ፫፥፫-፮) በኑፋቄ የጎደጎደው ሰውነታችንን በቃለ እግዚአብሔር በመሙላት፤ በትዕቢት የደነደነውን ተራራውን ልቡናችንን በትሕትና በማስገዛት፤ በክፋት የተጣመመው አእምሯችንን በቅንነት በማስጓዝ፤ በኀጢአት የሻከረውን ልቡናችንን በንስሐ በማስተካከል አዲሱን ዓመት የመልካም ምግባር ዘመን እናድርገው፡፡ በተጨማሪም ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹እንግዲህ ያለ እርሾ እንዳላችሁ አዲሱን ሊጥ ትኾኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ አስወግዱ›› በማለት እንዳዘዘን (፩ኛ ቆሮ.፭፥፯)፣ በኀጢአት እርሾ የተበከለውን ሰውነታችንን በጽድቅ ሕይወት እናድሰው፡፡ በአዲሱ ዓመት በክርስቲያናዊ ምግባር መኖር ከቻልን ከጊዜ ጋር የሚጣጣም አዲስ ሕይወት ይኖረናል ማለት ነው፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም የደስታችን መጠን በልክ መኾን አለበት፡፡ አሁን አሁን የበዓሉን መንፈሳዊነት የሚያጠፉ እንደ ከልክ በላይ መመገብና መመጣት፣ መስከር፣ መጨፈር፣ መጮኽ፣ ወዘተ. የመሳሰሉ የውጭ ዓለም የባህል ወረራዎች በየከተሞች ተስፋፍተዋል፡፡ እነዚህ ሰይጣናዊ ድርጊቶች ወጣቱን ትውልድ ለጥፋት የሚጋብዙ የኀጢአት መሣሪያዎች ናቸውና ለራሳችንም ለአገራችንም ህልውና ሲባል አጥብቀን ልንከላከላቸው ይገባል፡፡ አዲሱን ዓመት ለማየት እንደ ጓጉ በልዩ ልዩ ምክንያት ለመድረስ ያልታደሉትን፤ በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ ተይዘው በየጠበሉና በየሆስፒታሉ የሚሰቃዩትን፤ በጦርነት፣ በረሃብ፣ በስደት፣ ወዘተ. በመሳሰሉ ችግሮች የሚጨነቁትን ወገኖቻችንን በማሰብና መንፈሳዊ ትውፊቱን የጠበቀ አከባበርን መሠረት በማድረግ ዓመት በዓሉን ማክበር ይጠበቅብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በአውሮፓ የመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ ተካሔደ

ካህናት አባቶች፣ ጥናት አቅራቢ ምሁራን፣ የዝግጅት ኮሚቴው አባላት እና የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

በአውሮፓ ማእከል

ጳጕሜን ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የሙያ አገልግሎት እና አቅም ማጎልበቻ ክፍል አስተባባሪነት ‹‹የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅርሶች›› በሚል ርእሰ ጉዳይ የመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጥናት ጉባኤ በስዊድን አገር በሉንድ ዩኒቨርሲቲ ከነሐሴ ፳፯ – ፳፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ተካሔደ፡፡

በጥናት ጉባኤው በታዋቂ ምሁራን በአማርኛ እና እንግሊዝኛ ቋንቋዎች በልዩ ልዩ አርእስት የተዘጋጁ የምርምር ሥራዎች የቀረቡ ሲሆን፣ ከአውሮፓ ሀገራት የመጡ በርካታ ምእመናን እና የስዊድን ዜጎች በተዳሚነት ተሳትፈዋል፡፡

በመጀመሪያው ጉባኤ በለንደን ከተማ የደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ የሆኑት ቀሲስ አባተ ጉበና ‹‹የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅርስ ጥቅሞች፣ የቤተ ክርስቲያን ደኖች እንደ አገር ብዝኀ ሕይወት ማሳያነት›› በሚል ርእስ ባስተላለፉት መልእክት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደን ጥበቃ የላቀ አስተዋጽዖ ከማበርከቷ ባሻገር የብዝኀ ሕይወት መገኛ እንደ ሆነችም አስረድተዋል፡፡

በሉንድ ዩኒቨርሲቲ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ሳሙኤል ሩቢንሰን፣ ‹‹የኢትዮጵያ ሃይማኖታዊ ቅርሶች ለክርስትና ታሪክ ያላቸው አስተዋጽዖ›› በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሑፍ በምዕራባውያን ጫና ምክንያት የክርስትና ታሪክ በመጀመሪያ ወደ አውሮፓ መግባቱ፤ በቅኝ ግዛት ዘመን ወደ አፍሪካ እና እስያ መስፋፋቱ በተዛባ መልኩ እንደሚነገር አውስተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክ በክርስትና ታሪክ ውስጥ የሚያካትቱ አካላትም የኢትዮጵያ ባህል ከሌሎች አገሮች ተገንጥሎ የወጣ እንደ ሆነ እና ለክርስትና ታሪክም አስተዋጽዖ እንደሌለው የማድረግ ዝንባሌ እንደሚታይባቸው ፕሮፌሰሩ አብራርተዋል፡፡ ‹‹በመጀመሪያው ምዕት ዓመት በነበረው የክርስትና አመሠራረት ላይ የኢትዮጵያን አስተዋጽዖ አለማካተት የክርስትናን ታሪክ ጎደሎ እንዲኾን ያደርዋል›› የሚሉት ፕሮፌሰር ሩቢንሰን፣ ክርስትና ከኢየሩሳሌም ወደ አውሮፓ፤ ከዚያም በቅኝ ግዛት ዘመን ወደ አፍሪካ እና እስያ ደረሰ የሚለው አስተሳሰብ ስሕተት መሆኑን በጥናታቸው ጠቁመዋል፡፡

ጥናት አቅራቢዎች

‹‹የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅርሶች ታሪክና ጥበቃ›› በሚል ርእስ ጥናት ያቀረቡት የአርኪዮሎጅ እና አንትሮፖሎጅ ምሁሩ እንግሊዛዊው ፕሮፌሰር ዴቪድ ፊልፕሰን፣ ከዘመነ አክሱም ጀምሮ ያለውን የኢትዮጵያ ቅርሶችን ታሪክ ካስታወሱ በኋላ ስለ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት አሠራር፣ ስለሚደረግላቸው ክብካቤና ጥበቃ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ በዘራፊዎች ተወስደው በውጭ አገር የሚገኙ የኢትዮጵያ ቅርሶችን ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ የሚደረገውን ጥረት እንዳይሳካ የሚያደርጉ ጉዳዮችንም ዳሰዋል፡፡ ፕሮፌሰሩ ፊሊፕሰን በእንግሊዝ አገር የሚገኙ ቅርሶች ወደ ኢትዮጵያ ይመለሱ ተብሎ እንቅስቃሴ በሚደረግበት ወቅት ቅርሶችን በማስተዳደር ላይ ያሉት የብሪታንያ ሙዚየም ባለ ሥልጣናት ‹‹ቅርሶች ወደ ኢትዮጵያ ቢመለሱ፣ ጥበቃና ክብካቤ የሚያደርግላቸው የለም›› የሚል ምክንያት እንደሚሰጡ በጥናታቸው አውስተዋል፡፡ ይሁን እንጂ ከእንግሊዝ ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱ ቅርሶችም እንዳሉ የጠቆሙት ፕሮፌሰሩ ለአብነትም በ፲፰፻፸፪ ዓ.ም የተመለሰው ክብረ ነገሥት የተባለው መጽሐፍ በአዲስ አበባ ከተማ በመርካቶ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን በጥሩ ክብካቤ እንደሚገኝ ከሰባ ዓመታት በፊት ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ተሞክሮ በመነሣትም ዅሉም ቅርሶቿ ቢመለሱላት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሥርዓት እንደምትጠብቃቸው በመጠቆም ፕሮፌሰር ፊሊፕሰን ጥናታዊ ጽሑፋቸውን አጠናቀዋል፡፡

በኖርዌይ አገር የአካባቢያዊ ኬሚስትሪ ምሁሩ ዶክተር ኪዳኔ ፋንታ በበኩላቸው ‹‹የኢትዮጵያ ክርስቲያናዊ ሥዕላት ፊዚኮ – ኬሚካዊ ምርመራ›› በሚል ርእስ ባዘጋጁት ጥናታዊ ጽሑፋቸው ሥዕላቱ የተሠሩበትን ንጥረ ነገር ማወቅ ሥዕላቱን ለመጠበቅና እና እድሳት ለማድረግ ጠቀሜታ እንዳለው አመላክተዋል፡፡ ዘመኑ ያፈራቸውን የረቀቁ የቤተ ሙከራ መሣሪያዎች በመጠቀምና ምርመራ በማድረግ ልዩ ልዩ ሥዕላት፣ የሕንጻ ዓምዶች እና የብራና ጽሑፎች የተዘጋጁበትን ንጥረ ነገር፣ ዘመን እና ቦታ ለመለየትና ለመረዳት እንደሚቻልም በምሳሌ አስረድተዋል፡፡

ሌላኛው ጽሑፍ አቅራቢ የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ተከሥተ ነጋሽ ደግሞ ‹‹ዋሌ ኢየሱስ፣ የአክሱም ዘመን ቤተ ክርስቲያን በዛግዌ ምድር›› በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናት በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ውስጥ የሚገኘውን ጥንታዊ የዋሻ ቤተ ክርስቲያንን አሠራር የሚመለከት ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ የዋሌ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን አሠራር በአክሱም ዘመን ከታነጹ አብያተ ክርስቲያናት ጋር ተመሳሳይነት እንዳለውም አስረድተዋል። በቤተ ክርስቲያኑ ዙሪያ የሚኖሩ መነኮሳትና ካህናት ቤተ ክርስቲያኑ ከላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት አስቀድሞ በስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደ ተመሠረተ ማስረጃዎች መሆናቸውንም ፕሮፌሰር ተከሥተ ነጋሽ አውስተዋል፡፡

ነሐሴ ፳፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከቅዳሴ በኋላ በሉንድ ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ሁለተኛው የጥናት ጉባኤ የቀጠለ ሲኾን፣ በልዩ ልዩ አርእስት የተዘጋጁ ሦስት ጥናታዊ ጽሑፎች በአማርኛ ቋንቋ ቀርበዋል፡፡ በመጀመሪያ ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ቅርሶች ለመጠበቅ፣ ለምእመናን ምን ያኽል ትምህርት ተሰጥቷል?›› በሚል ርእስ የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ሽፈራው በቀለ እስከ አሁን ድረስ በአደረጉት የሰነድ ምርመራ የቅርሶችን ምንነት እና አጠባበቅ የሚያስረዱ ጽሑፎችን ማግኘት አለማቻላቸውን፤ በቤተ ክርስቲያን የሚሰጡ አብዛኞቹ ትምህርቶችም የቅርስ አያያዝን አለማካተታቸውን አስገንዝበዋል። በዚህ የተነሣም የቤተ ክርስቲያን ቅርሶች የመጥፋት አደጋ እንደ ተጋረጠባቸው ገልጸዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ሕንጻዎችን፣ ንዋያተ ቅድሳትን እና መጻሕፍትን ለመጠበቅና ከጥፋት ለመታደግ ይረዳ ዘንድ መሠረታዊ የቅርስ ጥበቃ፣ ክብካቤ እና ጥገናን የሚመለከቱ ሥልጠናዎችን መስጠት አስፈላጊ መሆኑንም ፕሮፌሰር ሽፈራው በጥናታቸው ማጠቃለያ ጠቁመዋል፡፡

ጥናት አቅራቢዎች

በመቀጠል የፊሎሎጅ ምሁሩ ቀሲስ ዶክተር አምሳሉ ተፈራ ‹‹ጥንታዊ የብራና ላይ ጽሑፎቻችን ዘረፋ፣ የአያያዝ ጉድለትና ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች›› በሚል ርእስ የምርምር ሥራቸውን አቅርበዋል፡፡ የብራና ጽሑፎችን ምንነት፣ ዓይነትና ይዘት በመተንተን ጥናታቸውን የጀመሩት ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ፣ በውጭ ሀገራት የሚገኙ በርካታ የኢትዮጵያ ቅርሶች በአብዛኛው በዘረፋ መልክ የተወሰዱ፤ የተወሰኑት ደግሞ ነገሥታቱ ለመሪዎች በስጦታ መልክ ያበረከቷቸው መሆናቸውን አውስተዋል፡፡ እንደ ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ማብራሪያ በአጠቃላይ 6,245 የብራና መጻሕፍት በልዩ ልዩ መንገድ ከኢትዮጵያ የተወሰዱ ሲሆን፣ አብዛኞቹም በእንግሊዝ፣ በጀርመን፣ በጣልያን እና ቫቲካን አገሮች ይገኛሉ፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም ጥቂት የብራና ጽሑፎች በልዩ ልዩ ጊዜያት ወደ ኢትዮጵያ መመለሳቸውን አስታውሰው እርሳቸው ተሳትፎ ያደረጉበትን ከአሜሪካው ሀዋርድ ዩኒቨርሲቲ ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም የተመለሰውን የገድለ ሰራባሞን እና ሌሎችም ቅርሶችን በማስረጃነት ጠቅሰዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን፣ መንግሥት እና እያንዳንዱ ግለሰብ ቅርሶችን የመጠበቅ ሓላፊነት እንዳለበት በማሳሰብ ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ጥናታቸውን አጠቃለዋል፡፡

በጥናት ጉባኤው ማጠናቀቂያ ዕለትም ከጥናት አቅራቢዎች መካከል ፕሮፌሰር ዴቪድ ፊልፕሰን ‹‹በማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል ይህን ዐውደ ጥናት በማዘጋጀቱ በቤተ ክርስቲያኒቱ ዙሪያ የሚሠሩ ምርምሮችን ከሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን ልጆች ጋር ለመወያየት እድል ፈጥሮልኛል›› በማለት አስተያየት ከሰጡ በኋላ ዐውደ ጥናቱን ያዘጋጀውን ማኅበረ ቅዱሳንን አመስግነዋል፡፡ ሌሎች ጥናት አቅራቢዎችና ተሳታፊዎችም በጉባኤው እንደ ተደሰቱ ገልጸው ወደፊትም ይኽን ዓይነቱ የጥናት ጉባኤ ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል፡፡

በመጨረሻም ለዚህ ዓለም አቀፍ ጉባኤ መሳካት አስተዋጽዖ ላደረጉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ ለሉንድ ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል ሰበካ ጉባኤ፣ ለሉንድ ዩኒቨርሲቲ፣ ለፕሮፌሰር ሳሙኤል ሩቢንሰን፣ ጥናታዊ ጽሑፍ ላቀረቡና መልእክት ላስተላለፉ ምሁራን፣ ለተጋባዥ እንግዶች እና በጉባኤው ለተሳተፉ ምእመናን የዐውደ ጥናት ዝግጅት ኮሚቴው ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ተፈራ በኮሚቴው፤ ዲያቆን ዓለምነው ሽፈራው ደግሞ በአውሮፓ ማእከል ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡