አምስተኛው ዐውደ ርእይ በሰላም ተጠናቀቀ፡፡

ግንቦት ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ማኅበረ ቅዱሳን የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ በሚል መሪ ቃል ከግንቦት ፲፯-፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለስድስት ቀናት በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ያዘጋጀው አምስተኛው ዐውደ ርእይ ግንቦት ፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ 4፡00 በሰላም ተጠናቀቀ፡፡

ዐውደ ርእዩ ከተጀመረበት ዕለት እስከ ተጠናቀቀበት ሰዓት ድረስ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በብዙ ሺሕ ምእመናን፣ በመንግሥት ባለ ሥልጣናትና በሌሎች ቤተ እምነት ተከታዮችም ተጎብኝቷል፡፡

በዐውደ ርእዩ ከተሳተፉ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የሰቲት ሑመራ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ይህ ዛሬ ያየነው በማኅበረ ቅዱሳን የተዘጋጀ ትልቅና አስደናቂ ዐውደ ርእይ ነባሩን ኢትዮጵያዊ ሥርዓት፣ ቅርስ፣ ታሪክና ትውፊት የሚገልጽ ዐውደ ርእይ ነው፤ በመኾኑም በጣም የሚወደድ፣ የሚከበርና የሚደነቅ ነው ብለዋል፡፡ አክለውም ይህንን ነባር ሥርዓት ለማጥፋት የሚጥሩ ብዙ ሐሳውያንን ስላሉ ኹላችንም ከመንበረ ፓትርያርክ ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ጠንክረን መሥራት ይኖርብናል፤ ዐውደ ርእዩም እስከ ወረዳ ድረስ መታየት ይገባዋል ካሉ በኋላ በርቱ፤ ጠንክሩ፡፡ ኹሉም ነገር ለሰላም፣ ድህነትን ለማጥፋት፣ አንድነትን ለማጽናት፣ በአጠቃላይ ድንቁርናን ለማስወገድ መኾን ይኖርበታል በማለት አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋና የደቡብ ኦሞ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የሲኖዶስ አባል ደግሞ ይህንን የመሰለ ያማረ ጉባኤ ሳይ በጆሯችን የሰማነውን በዓይኖቻችንም ያየነውን እንመሰክራለን ተብሎ እንደተጻፈ የሰማሁትንና ያየሁትን መመስከር ግድ ይለኛል፡፡ ልጆቻችንን በዚህ ደረጃ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ያበቋቸው ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ናቸው፡፡ ብፁዕነታቸው እኔ ለኩሸዋለሁ፤ እናንተ አንድዱት የሚል ቃል ተናግረው ነበር፡፡ በእውነትም እርሳቸው የለኮሱት መንፈሳዊ ሕይወት፣ መንፈሳዊ አገልግሎት ነዷል፡፡ ከኢትዮጵያም ተርፎ በመላው ዓለም ተዳርሷልና ይህንን በማየታችን እጅግ በጣም ደስ ብሎናል ሲሉ የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም እግዚአብሔር የሚቋረጥ ሥራ አይወድምና በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የአባቶቻቸውን አደራ እንደ ጠበቁ ልጆች ማኅበረ ቅዱሳንም የአባታችሁን የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስን አደራ በመጠበቅ አገልግሎታችሁን ልትቀጥሉ፤ ፈተናዎችንም በመወያየትና በመነጋገር ልታልፏቸው ይገባል የሚል አባታዊ ምክር ለግሰዋል፡፡

በሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የኾኑት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤልም የዚህ ታላቅ ማዕድ ተካፋይ በመኾኔ እጅግ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡ በእናንተ በልጆቻችንም መንፈሳዊ ኩራት ይሰማናል፡፡ ልበ አምላክ ዳዊት በአባቶች ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ እንዳለው ኹሉ ተዋሕዶ እምነታችን እንደዚህ ለሃይማኖታችሁ የምትቆረቆሩ የምታስቡ ልጆች በማግኘቷና እኛም እንደዚህ ዓይነት ትውልድ ባለበት ሰዓት በመነሣታችን እጅግ ደስ ይለናል ሲሉ ስሜታቸውን ከገለጹ በኋላ ማኅበሩ የሠራው ሥራ የሚያስመሰግነው ቢኾንም በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈው እኛ ለጌታ የማንጠቅም ባሪያዎች ነን ማለት እንደሚገባውም ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም ይህ ሥራ የመጨረሻችሁ ሳይኾን የመጀመሪያችሁ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ከእናንተ ጋር ናቸው፡፡ ከአባቶቻችሁ መመሪያ እየተቀበላችሁ ከዚህ የበለጠ እንድታገለግሉ አደራ እላለሁ የሚል አባታዊ ምክር ሰጥተዋል፡፡

ሌሎች ብፁዓን አበውም ማኅበረ ቅዱሳንን አስነሥቶ ሕዝበ ክርስቲያኑን በዚህ መልኩ እንዲሰባሰብና ስለ ቤተ ክርስቲያኑ፣ ስለ ሃይማኖቱ እንዲማር በማድረጉ እግዚአብሔርን አመስግነዋል፤ በማኅበሩ ሥራ መደሰታቸውንም ገልጸዋል፡፡ ለወደፊትም ከአባቶች ጋር በመመካከር ከዚህ የበለጠ መትጋት እንደሚገባ አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡

አንዳንድ ያነጋገርናቸው ምእመናን እንደገለጹልን በዝግጅቱ ከመደሰታቸው የተነሣ ከቤተሰቦቻቸውና ከልጆቻቸው ጋር በመኾን ስድስቱን ቀን በሙሉ በዐውደ ርእዩ ተሳትፈዋል፡፡ በዐውደ ርእዩ መሳተፍ የሚኖረውን ጠቀሜታ አስመልክቶ ቃለ መጠይቅ ያደርግንላቸው ምእመናንም ዐውደ ርእዩ ኹሉም ምእመን ስለ ሃይማኖቱ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያኑና ስለ አገሩ ታሪክ እውቀት እንዲኖረው ከማድረጉ በተጨማሪ ራሱን እንዲያይና ድርሻውን በማወቅ የሚጠበቅበትን ሓላፊነት እንዲወጣ የሚያስችል ግንዛቤ ያስጨብጠዋል ብለዋል፡፡

ከአስተያየት መስጫ መዛግብት ላይ ከሰፈሩ ዐሳቦች ውስጥም ዐውደ ርእዩ በጣም አስተማሪ መኾኑን ገልጸው፣ የአዘጋጆቹን፣ የአስተናጋጆቹንና የገላጮቹን ጥንካሬ በማድነቅ እንደዚህ ዓይነቱ ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ከተማ ብቻ ሳይኾን፣ በየክፍለ ሀገሩና በየወረዳው መዘጋጀት እንደሚገባው፤ ትዕይንቶቹም ቀለል ባለ መልኩ በብሮሸርና በሲዲ መልክ ለምእመናን መዳረስ እንደሚኖርባቸው አስተያየት የሰጡ ሰዎችን ዐሳብ በአብዛኛው አንብበናል፡፡ በተጨማሪም ማኅበሩ በዐውደ ርእዩ ላይ የበጎ አድራጎት ማኅበራት ሥራዎች እንዲተዋወቁ ማድረጉ ያስመሰግነዋል፤ ለወደፊቱ እንደዚህ ዓይነት ዐውደ ርእይ ሲያዘጋጅ ከቤተ ክህነትና ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ጋር በጋራ ቢሠራ ደግሞ የበለጠ ውጤታማ ይኾናል የሚሉና ሌሎችም አስተያየቶች ተሰጥተዋል፡፡

በአንጻሩ የዐውደ ርእዩ ጊዜ ጠባብ መኾኑ፣ ማኅበሩ ኤግዚብሽን ማዕከሉ ውስጥ ለታዳሚዎች የሚኾን ምግብ ቤት ስላልተዘጋጀ፣ እንደዚሁም በትዕይንቶቹ አዳራሾች ውስጥ ጎብኝዎቹ ስለሚደራረቡና የልዩ ልዩ ትዕይንቶች ገላጮች ድምፅ ስለሚቀላቀል ለወደፊቱ ሰፊ ዝግጅት ያስፈልገዋል ብለዋል፡፡ ከዚህ በተለየ ደግሞ ማኅበሩ ራሱን የሚያስተዋውቅበት የትዕይንት ክፍል ማዘጋጀት ነበረበት የሚል አስተያየት በጽሑፍም በቃልም ተነሥቷል፡፡

ከውጪ አገር ከመጡ ጎብኝዎች መካከል ማርቆስ ሀይዲኛክና ባለቤቱ አገራቸው ቡልጋርያ በሃይማኖታቸውም የምሥራቅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባል መኾናቸውን ጠቅሰው በዚህ ዐውደ ርእይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክና ሥነ ጽሑፋዊ ጥበብ፣ የክርስቲያኖቹን ትጋትና መንፈሳዊ ሕይወት እንደዚሁም የአገሪቱን ሕዝብ ባህል እንደተረዱበት ለዝግጅት ክፍላችን ገልጸዋል፡፡

ከሌላ ቤተ እምነት ከመጡ ግለሰቦች መካከልም ማርሺያ ሲንግልተን የምትባል አንዲት አሜሪካዊት የፕሮቴስታንቲዝም እምነት ተከታይ በዚህ ዐውደ ርእይ በመሳተፏ እድለኛ መኾኗን ጠቅሳ በጉብኝቱም የኢትዮጵያ ኦርቶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በታሪክ የበለጸገና በመጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ ላይ የተመሠረተ መኾኑን ከገለጸች በኋላ ዐዲስ እውቀት እንዳገኝ ስላደረጋችኹኝ አመሰግናለሁ የሚል አስተያየቷን በእንግሊዝኛ ቋንቋ አስፍራለች፡፡

በተያያዘ ዜና አንድ ጣልያናዊ ጎልማሳ የእስልምና ሃይማኖት ተከታይ በዐውደ ርእዩ የኢትየጵያን ታሪክና የክርስትናን አስተምህሮ እንደተረዳበትና በመታደሙም ደስተኛ እንደኾነ ገልጾ፣ ዐውደ ርእዩ በርካታ ምሁራን የተሳተፉበት መኾኑን ከትዕይንቶቹ ይዘት መረዳቱን ከተናገረ በኋላ ማኅበሩንና አዘጋጆቹን አመስግኗል፡፡

በመጨረሻም በትናንትናው ዕለት ከምሽቱ 4፡00 ዐውደ ርእዩ ሲጠናቀቅ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚዎች፣ የዝግጅቱ አስተባባሪዎች፣ የትዕይንት ገላጮች፣ የአብነት ተማሪዎችና ሌሎችም ድጋፍ ሰጪ አካላት በኤግዚብሽን ማዕከሉ ግቢ ውስጥ ተሰባስበው ንሴብሖ ለእግዚአብሔር ስቡሐ ዘተሰብሐ እያሉ በሰላም ያስፈጸማቸውን ልዑል አግዚአብሔርን በዝማሬና በዕልልታ አመስግነዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማእከል

ግንቦት ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅድስት፣ አሐቲ፣ ከኹሉ በላይ የኾነች፣ በክርስቶስ ደም የተመሠረተች፣ በቅዱሳን ነቢያት ትንቢት የጸናች፣ በቅዱሳን ሐዋርያት ስብከት የታነፀች፣ በሊቃውንት አስተምህሮ የጸናች፣ በምእመናን ኅብረት የተዋበች ንጽሕት ማኅደረ ሃይማኖት ናት፡፡

የዚህችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ምእመናን ይረዱ ዘንድ ልዩ ልዩ ዘዴዎችን መጠቀም ይገባል፡፡ ከእነዚህ ዘዴዎች አንዱ ከሰሞኑ በማኅበረ ቅዱሳን አማካይነት በአዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለዕይታ ቀርቦ የሰነበተው ዓይነት ዐውደ ርእይ አንዱ ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን አምስተኛውን ዐውደ ርእይ ለምእመናን ሊያቀርብ የነበረው ከመጋቢት ፲፭-፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የነበረ ቢኾንም ዳሩ ግን ዐውደ ርእዩ በሰዓቱ ግልጽ ባልነበረ ምክንያት ላልተወሰነ ጊዜ ታግዶ ከቆየ በኋላ እግዚአብሔር ሥራውን የሚሠራበት ጊዜ ሲደርስ እነሆ ከግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለተመልካቾቹ ይፋ ኾነ፡፡

በዚህ ዐውደ ርእይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት፣ ዶግማ፣ ቀኖና እና ትውፊት በሰፊው ቀርቦ በምእመናን ሲታይ ሰንብቷል፡፡ በተጨማሪም በአንድነት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገልና የተቸገሩትን ለመርዳት የጎላ ድርሻ ያላቸው የጽዋ፣ የበጎ አድራጎትና የጉዞ ማኅበራት አገልግሎትም ተዳስሷል፡፡

ሊቃውንቱና ደቀ መዛምርቱ በዐውደ ርእዩ የሚሳተፉትን ጎብኝዎች ለማስደሰት የአገር ርቀት ሳይገድባቸው፣ መንገድ ሳያደክማቸው ከየመኖሪያ ቦታቸው በመምጣት በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለሳምንት ያህል ቆይተዋል፡፡

ዐውደ ርእዩ በአራት ዐበይት አርእስት ማለትም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት፣ የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ፣ የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ እና ምን እናድርግ በሚሉ የተከፋፈለ ሲኾን በእያንዳንዱ ትዕይንት ሥርም በርካታ አርእስት ተካተውበታል፡፡ እያንዳንዳቸው የያዟቸው ጭብጦችም የሚከተሉት ናቸው፤

ትዕይንት አንድ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት

ይህ ትዕይንት ሀልዎተ እግዚአብሔር፣ ነገረ ድኅነት፣ ነገረ ማርያም፣ ነገረ ቅዱሳን እና ነገረ ቤተ ክርስቲያን የሚዳሰሱበት ክፍል ሲኾን፣ በውስጡም ሀልዎተ እግዚአብሔር፣ እግዚአብሔር አምላክ በጊዜና በቦታ የማይወሰን፣ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው፣ የፍጥረታት ኹሉ አስገኚና እርሱ በገለጠው መጠን ብቻ የሚታወቅ እንጂ ባሕርዩ ተመርምሮ ሊደረስበት እንደማይቻል እንደዚሁም መልዕልተ ኵሉ (የኹሉ የበላይ) መኾኑን ያስረዳል፡፡

እግዚአብሔር ሲባልም አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ማለት እንደኾነ፤ እንደዚሁም እግዚአብሔር አምላክ በሥነ ፍጥረቱ፣ በአምላካዊ መግቦቱ፣ በሕሊና፣ በቅዱሳት መጻሕፍት፣ በዓለም ላይ በሚፈጸሙ ድርጊቶች ምስክርነት፣ ሥጋን በመልበስራሱን ለእኛ እንደገለጠልን በዚህ ትዕይንት ተብራርቷል፡፡

በተጨማሪም ሃይማኖት ማለት እግዚአብሔር ራሱን ለሰው ልጅ የገለጠበት መንገድ ስለመኾኑና ስለ አብርሃም እግዚአብሔርን ፈልጎ ማግኘት፣ በተጨማሪም በዓለም ላይ ብዙ ሃይማኖቶች ለመኖራቸው ምክንያቱ የሰይጣን ክፉ ሥራና የሰው ልጅ የመረዳት ዓቅም መለያየት ስለመኾኑ ተብራርቶበታል፡፡

ነገረ ድኅነት ደግሞ በአዳምና በሔዋን ምክንያት የዘለዓለም ሞት ተፈርዶበት የነበረው የሰው ልጅ ከሦስቱ አካላት አንዱ በኾነው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀልና ሞት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መቻሉን በማስረዳት እመቤታችን የመልአኩን ብሥራት ከሰማችበት ጊዜ ጀምሮ የጌታችን ፅንሰት፣ ልደት፣ስደት፣ ዕድገት፣ ጥምቀት፣ ትምህርት፣ ተአምራት፣ ሕማማት፣ ሞት፣ ትንሣኤ፣ ዕርገትና ዳግም ምጽአት የነገረ ድኅነት መሠረቶች መኾናቸውን ይተነትናል፡፡

እንደዚሁም እምነት፣ ምግባር እና ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን መፈጸም የሰው ልጆች ለመዳን ሊያሟሏቸው የሚገቡ ቅድመ ኹኔታዎች መኾናቸው በዚህ ርእስ ሥር ተካቷል፡፡

ነገረ ማርያምም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአምላክ እናት እንደመኾኗ ከመፅነሷ በፊት፣ በፅንሷ ጊዜም ኾነ ከፀነሰች በኋላ ዘለዓለም ድንግል ስለመኾኗ እንደዚሁም በእግዚአብሔር ፊት ቆማ ለእኛ እንደምታማልድ ያስረዳል፡፡

ነገረ ቅዱሳን ደግሞ ሰማያውያን መላእክትን ጨምሮ ያላቸውን ኹሉ ትተውእግዚአብሔርን ብቻ የተከተሉ፣ መከራ መስቀሉን ተሸክመው ሕይዎታቸውን በሙሉበ ተጋድሎ ያሳለፉ፣ በፍጹም ልቡናቸው ጸንተው እስከ መጨረሻው ድረስ እግዚአብሔርን የተከተሉቅዱሳን አባቶች እና እናቶች ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ጸጋና ሥልጣን በምድርም በሰማይም እንደሚያማልዱ ያስረዳል፡፡

በነገረ ቤተ ክርስቲያን ሥር ደግሞ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስአካል፣ የምእመናን ኅብረት፣ የሰው ልጆችና የመላእክት፣ በዓለመ ሥጋና በዓለመ ነፍስ ያሉ እንደዚሁም የሥውራንም የገሃዳውያንም (በግልጽ የሚታዩ)ምእመናን አንድነትመኾኗ፣ ይህቺ ቤተ ክርስቲያን በተጋድሎ ብትኖርም ነገር ግን ድል አድራጊ፤ በባሕርዩአም ቅድስት፣ አሐቲ (አንዲት)፣ ሐዋርያዊት፣ ኵላዊት እንደኾነች ተተንትኖበታል፡፡

ትዕይንት ሁለት፡- የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮ

በዚህ ትዕይንት የሐዋርያነትና የሐዋርያዊ አገልግሎት ትርጕም፣ ዓላማና አመሠራረትን ጨምሮ ስብከተ ወንጌል አንዴት እንደ ተስፋፋና እስከ ዛሬ ድረስ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሱ ፈተናዎችና መልካም አጋጣሚዎች የተካተቱበት ልዩ ልዩ መረጃና ትምህርት ቀርቦበታል፡፡

የሐዋርያዊ አገልግሎት መጀመርና መስፋፋት በኢትዮጵያ በሚለው የዚህ ትዕይንት ንዑስ ርእስ ሥር ከ፩ኛው እስከ ፯ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ የነበረው ሐዋርያዊ አገልግሎት ተዳሶበታል፡፡ የአባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን፣ የቅዱሳን ነገሥታት አብርሀ እና አጽብሀ፣ የዘጠኙ ቅዱሳን፣ የዐፄ ካሌብና የቅዱስ ያሬድ ሐዋርያዊ አገልግሎት ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት ያደረገው አስተዋፅዖ በርእሱ የተገለጡ የታሪክ ክፍሎች ናቸው፡፡

ሁለተኛው ንዑስ ርእስ ደግሞ ከ፰ኛው እስከ ፲ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ በዮዲት ጉዲት ምክንያት ቅዱሳት መጻሕፍትና አብያተ ክርስቲያናት በመቃጠላቸው፣ ሊቃውንቱና ምእመናኑ በመገደላቸውና በመሰደዳቸው በቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ላይ ጉዳት እንደ ደረሰ ያስረዳል፡፡

በሦስተኛ ደረጃ በዮዲት ጉዲት ዘመን በደረሰው በደል ቁጭት ያደረባቸው አባቶች በመነሣታቸው ምክንያት ከዐሥራ ፲፩ኛው እስከ ፲፮ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበረውን የሐዋርያዊ ተልዕኮ ትንሣኤ በመግለጽ ለዚህም የአራቱ ቅዱሳን ነገሥታት (ይምርሃነ ክርስቶስ፣ ሐርቤ/ገብረ ማርያም፣ ላሊበላና ነአኵቶ ለአብ) መነሣት፤ የሐይቅ እስጢፋኖስ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ገዳም መመሥረትና እንደ አቡነ ተክል ሃይማኖት ያሉ አባቶች፣ እንደዚሁም በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብና በዘመኑ የነበሩ አበው የስብከተ ወንጌል አገልግሎት፤ በተጨማሪም እንደ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ያሉ ቅዱሳን መጻሕፍትን በማዘጋጀት ያበረከቱትን ከፍተኛ አስተዋፅዖ ይገልጻል፡፡

በትዕይንት ሁለት በአራተኛ ደረጃ የተቀመጠው ነጥብም ከ፲፯ኛው እስከ ፲፰ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ በነበረው ጊዜ በግራኝ አሕመድ ወረራ ምክንያት ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናትና ቅዱሳት መጻሕፍት በመቃጠላቸው፣ ሊቃውንቱና ምእመናኑ በግፍ በመጨፍጨፋቸው የተነሣ በሐዋርያዊ አገልግሎቱ ላይ የከፋ ጉዳት መድረሱን ይገልጻል፡፡

በተመሳሳይ መልኩ በዚያ ዘመን ከባዕድ አገር የመጡ የሁለት አካል፣ ሁለት ባሕርይ አማኞች ተፅዕኖ ቢበረታም ተከራክረው መርታት የሚችሉና ለሃይማኖታቸው ሲሉ አንገታቸውን የሚሰጡ አባቶችና እናቶች የተገኙበት ወቅት እንደነበረም ተጠቅሷል፡፡ በዘመነ መሣፍንት በአገራችን ተስፋፍቶ የነበረውን የሁለት አካል ሁለት ባሕርይ አስተሳሰብ ተከትሎ በተፈጠረው የጸጋና የቅብዓት ትምህርት የተከሠተዉን ችግር ለመፍታት ከፍተኛ ጥረት መደረጉም ተገልጿል፡፡

በዚሁ ትዕይንት በአምስተኛ ደረጃ የተቀመጠው ነጥብም ከ ፲፱ኛው እስከ ፳ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ የነበረውን ሐዋርያዊ አገልግሎት የሚያስቃኝ ሲኾን፣ በውስጡም በዘመኑ መጽሐፍ ቅዱስ ከግእዝ ወደ አማርኛ መተርጐሙ፣ በግዳጅ ተይዘው ወደ ሌላ ሃይማኖት ሔደው የነበሩ ምእመናን ወደ ክርስትና መመለሳቸው፣ እንደዚሁም የነመምህር አካለ ወልድ እና መልአከ ሰላም አድማሱ መነሣት ለቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ መፋጠን መልካም አጋጣሚ እንደ ነበረ ያስረዳል፡፡

በተጨማሪም ቅዱስ ሲኖዶስ መቋቋሙ፣ የካህናት ማሠልጠኛዎችና መንፈሳውያን ኰሌጆች መመሥረታቸው፣ የሰበካ ጉባኤ መዋቅር መዘርጋቱ፣ ወጣቶች በሰንበት ትምህርት ቤቶችና በማኅበራት አገልግሎት መስጠት መጀመራቸው፣ የምእመናን መንፈሳዊ ተሳትፎ መጨመሩ፣ በውጭዎቹ ክፍላተ ዓለም አብያተ ክርስቲያናት መታነፀቸው እንደዚሁም ቤተ ክርስቲያናችን መገናኛ ብዙኃንና በአፍ መፍቻ ቋንቋ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት መስጠት መጀመሯ በተለይ ፳ኛውን መቶ ክፍለ ዘመን ለሐዋርያዊ ተልዕኮ የተመቸ እንዲኾን ማድረጋቸው ተብራርቶበታል፡፡

በትዕይንት ሁለት የመጨረሻው ርእስ ላይ ደግሞ በአሁኑ ሰዓት የቴሌቭዥንና የሌሎችም መገናኛ ዘዴዎች ሥርጭት አለመኖር፣ በልዩ ቋንቋዎች የሚያስተምሩ ሰባክያንና ካህናት እጥረት እንደዚሁም በየቋንቋው የቅዱሳት መጻሕፍት በበቂ ኹኔታ አለመታተም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ውሱንነት መገለጫዎች መኾናቸው ተጠቅሷል፡፡

ትዕይንት ሦስት፡- የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ

ይህ ትዕይንት ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን ለማስፋፋት ያሳለፈችውን ተጋድሎ፣ የመናፍቃንን ተፅዕኖና የሰማዕታትን ታሪክ፣ የተዋሕዶ ሃይማኖትን አስተምህሮ ለማስጠበቅ የተደረጉ ልዩ ልዩ ዓለም ዓቀፍና አገር ዓቀፍ ጉባኤያትን በዝርዝር የያዘ ሲኾን፣ በኃይል ሃይማኖቱን ለማጥፋት ይተጉ በነበሩ አካላት ምክንያት ቤተ ክርስቲያን ስላደረገችው ተጋድሎ፣ ስለ ቅዱስ እስጢፋኖስ ሰማዕትነትና በዘመነ ሰማዕታት በክርስቲያኖች ላይ ስለደረሰው መከራ፣ እንደዚሁም በርካታ ክርስቲያኖች በሰማዕትነት ስለማለፋቸው፣ በተጨማሪም ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ተነሥቶ ክርስቲያኖች ዕረፍት ስለማግኘታቸው የሚያትት ዐሳብ ይዟል፡፡

ይህ የትዕይንት ክፍል በአገራችን በኢትዮጵያም እንደ ዮዲት ጉዲት፣ ግራኝ አሕመድ፣ ዐፄ ሱስንዮስ፣ ፋሽስት ጣልያን፣ ያሉ ጠላቶች በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ጉዳት ተጠቅሷል፡፡ ቀጥሎም የዘመናችን ሰማዕታት በሚል ንዑስ ርእስ ሃይማኖታችንን አንክድም፣ ባዕድ አናመልክም ያሉ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች በ፲፱፻፺፱ ዓ.ም በጂማ ሀገረ ስብከት በበሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን፤ በቅርቡ በ፳፻፯ ዓ.ም ደግሞ በሊብያ በረሃና በሜዴትራንያን ባሕር ዳርቻ በግፍ የተገደሉ የግብፅ፣ የኢትዮጵያና የሌሎችም አብያተ ክርስቲያናት ሰማዕታትን ይዘክራል፡፡

በቃልም በጽሑፍም በሚበተኑ የሐሰት ትምህርቶች ምክንያት ቤተ ክርስቲያን የፈጸመችውን ተጋድሎ በማውሳት በዚህ የተነሣም ልዩ ልዩ ጉባኤያት መደረጋቸውን ይዘረዝራል፡፡ በዚህ መሠረት ከአይሁድ ወደ ክርስትና ሃይማኖት በመጡትና በቀደሙ ክርስቲያኖች መካከል የልዩነት ትምህርት በመከሠቱ ቅዱሳን ሐዋርያት በ፶ ዓ.ም በኢየሩሳሌም ጉባኤ ማድረጋቸውንና ከዚያ ጊዜ ጀምሮ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንደ ተመሠርተ ይገልጻል፡፡

በማያያዝም ሦስቱን ዓለም ዓቀፍ ጉባኤያትን (ጉባኤ ኒቅያ፣ ጉባኤ ቍስጥንጥንያ እና ጉባኤ ኤፌሶን) በማንሣት ውሳኔዎቻቸውን አስቀምጧል፤ ይኸውም፡- በ፫፳፭ ዓ.ም ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት አርዮስን ለማውገዝ በኒቅያ ባደረጉት ጉባኤ ጸሎተ ሃይማኖትን (መሠረተ እምነት) ማርቀቃቸውን፤ በ፫፹፩ ዓ.ም ፻፶ው ሊቃውንት መቅዶንዮስን ለማውገዝ በቍስጥንጥንያ ባደረጉት ጉባኤ ወነአምን በመንፈስ ቅዱስ እግዚእ ወማኅየዊ ዘሠረጸ እምአብ፤ ጌታ፣ ማኅየዊ በሚኾን ከአብ በሠረጸ በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን የሚለው ሐረግ በጸሎተ ሃይማኖት መካከተቱን፤ በ፬፴፩ ዓ.ም ደግሞ ፪፻ ሊቃውንት ንስጥሮስን አውግዘው በአንዲት የተዋሕዶ ሃይማኖት የሚያጸና ትምህርት ማስተማራቸውን ያትታል፡፡

በተጨማሪም በአገራችን በኢትዮጵያ በሃይማኖት ምክንያት በዐሥራ አምስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የሰንበትን አከባበር አስመልክቶ በቤተ ኤዎስጣቴዎስና በቤተ ተክለ ሃይማኖት መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት በ፲፬፻፶ ዓ.ም በደብረ ምጥማቅ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ አማካኝነት ጉባኤ ተደርጎ ሁለቱም ሰንበታት እኩል ይከበሩ የሚል ውሳኔ ስለመተላለፉ፤ ነሐሴ ፲፫ ቀን ፲፰፻፵፮ ዓ.ም በጎንደር ክፍለ ሀገር በደብረ ታቦር ከተማ አምባጫራ በተባለ ቦታ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አባቶች ከቅባትና ከጸጋዎች ጋር የሃይማኖት ጉባኤ አድርገው ጸጋና ቅባቶች ስለመረታታቸው፤ የቅባትና የጸጋ ትምህርት ፈጽሞ ባለመጥፋቱ ግንቦት ፳፩ ቀን ፲፰፻፸፭ ዓ.ም በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት በቦሩ ሜዳ በድጋሜ ከቅባትና ከጸጋዎች ጋር የሃይማኖት ጉባኤ ተደርጎ ቅባትና ጸጋ ተረተው የተዋሕዶ ሃይማኖት ስለመጽናቷ ይገልጻል፡፡

በመጨረሻም የመናፍቃን ሰርጎ ገብነትና የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻዎች የዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተናዎች መኾናቸው በዚህ ትዕይንት ከማስረጃ ጋር ቀርቧል፡፡

ትዕይንት አራት፡- ምን እናድርግ?

ይህ ትዕይንት ደግሞ ምእመናን በዐውደ ርእዩ ከተመለከቷቸውና ከሰሟቸው እውነታዎች በመነሣት የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ከመጠበቅና ድርሻቸውን ከማወቅ አኳያ ልዩ ልዩ ችግሮችን ለመቅረፍ ወደፊት ምን ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው የሚያስረዱ መረጃዎችን አካቷል፡፡

የመጀመሪያው ነጥብ ሐዋርያዊ ተልዕኮን የተመለከተ ሲኾን በርእሱም በ፲፬ አህጉረ ስብከት፣ በ፯፻፳ አጥቢያዎች በተደረገ ጥናት ፫፵፮ አብያተ ክርስቲያናት መዘጋታቸው፣ ፪፻፺፮ቱ አገልጋይ ካህናት እንደሌሉባቸው፣ ፻፷፰ቱ ደግሞ በዓመት/በወር አንድ ጊዜ ብቻ ቅዳሴ የሚቀደስባቸው እንደኾኑ ያስረዳል፡፡

በተያያዘ መረጃ ከ፲፱፻፹፬-፳፻ ዓ.ም ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ብቻ ሰባት ሚልየን ሰባት መቶ ሰባ ስድስት ሺሕ ሁለት ሃያ ስድስት ምእመናን ወደ ሌሎች ቤተ እምነቶች መወሰዳቸው፣ እንደዚሁም በአዲስ አበባ እና በሌሎች አብያተ ክርስቲያናት መካከል ያልተመጣጠነ የአገልጋዮች ሥርጭት መኖሩ በዚህ ርእስ ሥር ተገልጿል፡፡

በትዕይንት አራት ሌላው ነጥብ የመገናኛ ብዙኃን አጠቃቀም ንጽጽር ሲኾን በንጽጽሩም የግብፅ ኦርቶዶስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፻፴፬ የመካነ ድር፣ ፲፩ የቴሌቭዥን እና ፲ የሬድዮ ሥርጭት ሲኖራት፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግን ፲፪ የመካነ ድር፣ ፪ የሬድዮ፣ እና ፩ የቴሌቭዥን ሥርጭት ብቻ እንዳላት ተጠቅሷል፡፡

ሁለተኛው የትዕይንት አራት ጭብጥ ደግሞ ገዳማትና የአብነት ትምህርት ቤቶች በመተዳደሪያ ዕጦት፣ በድርቅ፣ በመዘረፍ፣ በበሽታ፣ ወዘተ የመሰሉ ችግር ውስጥ መውደቃቸውን ያስረዳል፡፡

በዚህ ትዕይንት ሦስተኛው ነጥብ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያልተቋቋሙባቸው አጥቢያዎች መኖርና ያሉትም በቂ አለመኾናቸው፣ የሰባክያነ ወንጌል እጥረትና ግቢ ጉባኤያት ያልተመሠረቱባቸው የትምህርት ተቋማት መኖራቸው ቤተ ክርስቲያን ካጋጠሟት ችግሮች መካከል እንደሚጠቀሱ ይናገራል፡፡

በአራተኛ ደረጃ የተቀመጠው ነጥብ እንደሚያስረዳው የንስሐ አባትና የንስሐ ልጆች ግንኙነት መላላት፣ የምእመናንን መንፈሳዊ የእርስበርስ ግንኙነት (ፍቅር) መቀነስ እንደዚሁም ችግሩ እኔን አይመለከተኝም ብለው የሚያስቡ ምእመናን መበራከት ከቤተሰብና ከማኅበራዊ ኑሮ አኳያ ቤተ ክርስቲያን ያጋጠሟት ችግሮች ናቸው፡፡

በአምስተኛ ደረጃ ከተቀመጠው ነጥብ እንደምንገነዘበው ደግሞ ውጤት ተኮር ዕርዳታ የመስጠት ችግር፣ በልዩ ልዩ ሱስና በአእምሮ ሕመም የተጠቁ ምእመናንን ማገዝ አለመቻሉ፣ ውስን በኾኑ የልማት ሥራዎች ላይ ማተኮር ቤተ ክርስቲያን በማኅበራዊ አገልግሎትና በልማት የጋጠሟት ችግሮች ናቸው፡፡

እነዚህን ከላይ የተዘረዘሩትንና መሰል ችግሮችን ለመቅረፍ በጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ በማኅበረ ቅዱሳን፣ በጽርሐ ጽዮን እና በደጆችሽ አይዘጉ ዓይነት ማኅበራት በስብከተ ወንጌልና በጥምቀት አገልግሎት፣ በሥልጠና፣ እንደዚሁም በሌላ ማኅበራዊና ልማታዊ እንቅስቃሴእየተደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ ቢኾንም ነገር ግን ይህ ብቻ በቂ ስላልኾነ ኹሉም የድርሻውን ቢወጣ የተሻለ ሥራ መሥራትና ለውጥ ማምጣት እንደሚቻል ይጠቁማል፡፡

ይህ ኹሉ ችግር በዚህ ከቀጠለ ቤተ ክርስቲያን ወደፊት በሚሊየን የሚቈጠሩ ምእመናንን፣ አገልጋይ ካህናትን፣ አርአያ የሚኾኑ ገዳማውያን መነኰሳትን ማጣት፤ በቤተሰብ ደረጃም ፍቅር የሌላቸውና ተስፋ የሌላቸው ወጣቶች እንዲበዙ ያደርጋል፡፡

በአጠቃላይ ከላይ የተጠቀሱ ችግሮች በዚሁ ከቀጠሉ ቤተ ክርስቲያን በምጣኔ ሀብትም፣ በማኅበራዊ አገልግሎትና በሌሎችም ዘርፎች ዓቅም የሌላትና ተሰሚነት ያጣች ትኾናለች የሚለው ዐሳብ በትዕይንቱ የተገለጸ ሥጋት ነው፡፡

ከዚህ ቀጥሎ በሥዕል መልክ የተቀናበረው መልእክት እርስዎ የትኛው ነዎት? ያልተረዳ? ያንተ/ያንቺ ድርሻ ነው የሚል? ተወቃቃሽ? ሳይመረምር የሚከተል? ማሰብ ብቻ ሥራ የሚመስለው? ተስፋ የቈረጠ? አልሰማም፤ አላይም፤ አልናገርም የሚል? የሚያወራ፣ የሚተች፣ ግን የማይሠራ? ሲል ይጠይቃል፡፡ የትዕይንቱ ማጠቃለያም ምን እናድርግ? በሚል ርእስ አራት የመፍትሔ አቅጣጫዎችን አስቀምጧል፤

፩. የክርስቶስ አካል በኾነችው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሕያው አካል እንኹን፤

፪. ቤተ ክርስቲያንን በመሰለን ብቻ ሳይኾን በኾነችው እንወቃት፤ እንረዳትም፤

፫. ስለ ቤተ ክርስቲያን ያገባኛል፤ ይመለከተኛል ብለን እንሥራ፤

፬. ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የኾነውና የማዳን ተግባሩን ኹሉ የፈጸመው ለሰው ልጅ ነው፤

ሰው! ሰው! ሰው!

ኑ፤ አብረን እንሥራ፤ ለውጥም እናመጣለን የሚለው ኃይለ ቃልም እንደማንቂያ ደወል የተቀመጠ መልእክት ነው፡፡

ዐውደ ርእዩ ከነዚህ ዐበይት ትዕይንቶች በተጨማሪ የሕፃናት ትዕይንትም የተካተተበት ሲኾን፣ በዚህ ትዕይንት ለሕፃናት አእምሮ የሚመጥኑ መንፈሳውያን ትምህርቶች ተዘጋጅተውበታል፡፡

በትዕይንቱ ውስጥም የአዳምና የሔዋን ታሪክ፣ ነገረ ድኅነት እና ነገረ ቅዱሳን በሥዕላዊ መግለጫ ቀርቧል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያን የዜማ መሣሪያዎችና ንዋያተ ቅድሳት፣ እንደዚሁም ፊደለ ሐዋርያና ሌሎችም የልጆችን ስሜት ሊያስደስቱ የሚችሉ የትዕይንቱ ክፍሎች ተዘጋጅተዋል፡፡ ሕፃናቱም ክፍሉ ውስጥ እየዘመሩ ይማራሉ፤ ይደሰታሉ፡፡

ከሁሉም በተለየ መንገድ ደግም ከቍጥር ፩ አዳራሽ በስተሰሜን አቅጣጫ ካሉት ዛፎች ሥር ጊዜያዊ ጎጆ ቀልሰው የሚገኙት የሁሉም ገባኤያት (የንባብ፣ የዜማ/የድጓ፣ የቅዳሴ፣ የቅኔ፣ የአቋቋም፣ የመጻሕፍትና የአቡሻሕር ጉባኤ ቤቶች) መምህራን ደቀ መዛሙርታቸውን በተግባር ሲያስተምሩመታየታቸው የኤግዚብሽን ማዕከሉን የኹሉም ጉባኤያት መገኛ ገዳም አስመስሎታል፡፡

የንባብ ተማሪዎች ከመምህራቸው ከመምህር ተክለ ጊዮርጊስ ደርቤ እግር ሥር ቁጭ ብለው መጽሐፎቻቸውን በአትሮንሶቻቸው ዘርግተው ተነሽ፣ ተጣይ፣ ወዳቂና ሰያፍ ሥርዓተ ንባብን ለመለየት ይችሉ ዘንድ ተጠንቅቀው ያነባሉ፡፡

የቅዳሴ ደቀ መዛሙርት ከመጋቤ ስብሐት ነጋ፤ የዜማ/የድጓ ደቀ መዛሙርት ደግሞ ከሊቀ ምሁራን ይትባረክ ካሣዬ፤ የዝማሬ መዋሥዕት ደቀ መዛሙርትም ከመጋቤ ብርሃናት ፈንታ አፈወርቅ እግር ሥር ቁጭ ብለው ትልልቅና ባለምልክት የዜማ መጻሕፍቶቻቸውን በአትሮንሶቻቸው ላይ አስቀምጠው በግዕዝ፣ ዕዝልና በዓራራይ በተመሠረተው የቅዱስ ያሬድ ሰማያዊ የዜማ ሥርዓት መሠረት ያዜማሉ፤ መምህራኑም እርማት ይሰጣሉ፡፡

የቅኔ ደቀ መዛሙርትም አንድም ግስ በማውረድ፣ አንድም ከመምህራቸው ፊት ኾነው ቅኔ በመንገርና በማሳረም፣ አንድም መምህራቸው የዘረፉላቸውን ቅኔዎች በመቀጸል ግቢውን አድምቀውታል፡፡ የአቋቋም ደቀ መዛሙርት ደግሞ ከመምህራቸው ከመምህር ዮሐንስ በርሄ ፊት ለፊት ክብ ሠርተው በመቀመጥ በዕለቱ የሚቀጽሉትን ቃለ እግዚአብሔር በጣቶቻቸው እያጨበጨቡ፣ በእግሮቻቸው እያሸበሸቡ ሲያዜሙ የንጋት አዕዋፍን ዝማሬ ያስታውሳሉ፡፡

የአቡሻሕርና የድጓ መምህር የኾኑት መጋቤ አእላፍ ወንድምነው ተፈራም እርጅና ሳይበግራቸው የዘመናት፣ የበዓላት፣ የዕለታትና የአጽዋማት ማውጫ ቀመር የኾውን የባሕረ ሐሳብ ትምህርት ለደቀ መዛሙርታቸው በማስቀጸል ላይ ናቸው፡፡ መምህር ዘለዓለም ሐዲስም የመጻሕፍት ትርጓሜ ደቀ መዛሙርታቸውን ከፊት ለፊታቸው አስቀምጠው ብሉዩንም፣ ሐዲሱንም፣ ሊቃውንቱንም፣ መነኰሳቱንም ለደቀ መዛሙርታቸው ይተረጕማሉ፡፡

ምን ይኼ! ብቻ የብራና መጻሕፍት አዘገጃጀትም የጉብኝቱ አካል ኾኖ ሰንብቷል፡፡ ከዚህ ሌላ ለትዕይንቱ መጨረሻ ከኾነው አዳራሽ ውስጥ ከሚጎበኙ የማኅበሩ ልዩ ልዩ ክፍሎች መካከል አንዱ በኾነው የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም የትዕይንት ክፍል ውስጥ ከጠረፋማ አከባቢዎች የመጡትና የአብነት ትምህርት በመማር ላይ የሚገኙት ሕፃናት ሴቶችና ወንዶች ብትፈልጉ ውዳሴ ማርያም፣ ቢያሻችሁ ደግሞ መልክዐ ማርያም ያነበንቡላችኋል፡፡ ይህም ቤተ ክርስቲያናችን በብሔር፣ በዘር፣ በቀለም፣ በጎሣና በጾታ ሳታበላልጥ የማይነጥፈውን መንፈሳዊ እውቀቷን ለኹሉም እንደምታካፍል አመላካች ነው፡፡

በልማት ተቋማት አስተዳደር ተዘጋጅተው ለሽያጭ የቀረቡት ንዋያተ ቅድሳት (መንበር፣ ልብሰ ተክህኖ፣ አክሊል፣ መጎናጸፊያ፣ ጽንሐሕ/ጽና፣ ቃጭል፣ ወዘተ) እንደዚሁም የቤተ ክርስቲያን የዜማ መሣሪያዎች በሥርዓት ተደርድረው እዩን፤ እዩን፤ ግዙን፤ ግዙን ይላሉ፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍቱም እንደዛው፡፡

ከዐውደ ርእዩ ጎን ለጎን ከምሽቱ 11፡00 ጀምሮ የንባብ፣ የቅዳሴና የሰዓታት፣ የአቋቋምና የዝማሬ መዋሥዕት፣ ባሕረ ሐሳብ (የአቡሻኽር ትምህርት)፣ ቅኔ፣ ትርጓሜ መጻሕፍት፣ ዜማ/ድጓ ምንነታቸውን፣ አገልግሎታቸውን፣ አቀራረባቸውንና ከቅዱሳት መጻሕፍት ጋር ያላቸውን ትስስር የሚያስረዱ ጥናቶች በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሲቀርቡ ሰንብተዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ እሑድ ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ሙስናን ከመዋጋት አንጻር ያለው ሚና እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ፈተናዎችና መፍትሔዎቻቸው በሚሉ አርእስት በዐዲስ አበባ መንገድ ትራንስፖርት ባለሥልጣን አዳራሽ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ ሁለት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡

ባጠቃላይ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽ ማዕከል በተዘጋጀው አምስተኛው የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ተነቧል፤ ተተርጕሟል፤ ተብራርቷል፡፡ በዓለማዊ ጉዳዮች ተጨናንቆ የነበረው የኤግዚብሽን ማዕከሉ በመንፈሳዊ ትምህርትና ጣዕመ ዜማ ደምቆ ለስድስት ቀናት ያህል በመሰንበቱ እጅግ ተደስቷል፡፡ ዐውደ ርእዩ በድጋሜ ቢታይ የሚልም ይመስላል፡፡ ምክንያቱም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአምስተኛው የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ኤግዚአብሽን ማዕከል በግልጽ ታይታለችና፡፡ እርሷን ማየት፣ ትምህርቷንም መስማት፣ ጣዕመ ዜማዋን ማጣጣም እጅግ አስደሳች ነውና፡፡

ከላይ በገለጽነው መልኩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለምእመናን ሲያስረዳ የነበረው ይህ ዐውደ ርእይ ግንቦት ፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ 4፡00 ገደማ በሰላም ተጠናቋል፡፡ ይህ ዐውደ ርእይ በእግዚአብሔር ኃይል፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት በሚያስደስትና በሚማርክ መልኩ ያለምንም ችግር ተከናውኗል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

አምስተኛው የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል

ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ከፍ ብሎ የሚሰማው የመዝሙር ድምፅና በማዕከሉ መግቢያ በር ላይ የተለጠፉ መንፈሳውያን ማስታወቂያዎች አካባቢው አንዳች ብርቱ ጉዳይ እንዳለበት ይመሰክራሉ፡፡ ብዙ የቆሙ መኪኖች፣ በሺሕ የሚቈጠሩ ምእመናን መንገዱን አጨናንቀውታል፡፡

ከዐዲስ አበባ ከተማ ብቻ ሳይሆን ከልዩ ልዩ የኢትዮጵያ ክፍላተ አህጉር የሚመጡ ምእመናንና ምእመናት ከግንቦት 17 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ እግሮቻቸውን ወደ አንድ አቅጣጫ አድርገዋል፤ ወደ ዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል፡፡ የጉዟቸው ምክንያት ደግሞ የማኅበረ ቅዱሳን አምስተኛው ዙር መንፈሳዊ ዐውደ ርእይ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን ዐውደ ርእይ ለማዘጋጀት ከዓመታት በፊት ዓቅዶ ሠርቷል፤ ዐውደ ርእዩ ለምእመናን ሊቀርብ የነበረውም ከመጋቢት 15-21 ቀን 2008 ዓ.ም የነበረ ቢኾንም ዳሩ ግን በሰዓቱ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ባይኾን ግልጽ ባልነበረ ምክንያት ዐውደ ርእዩ መታገዱ ሲሰማ ብዙ ምእመናን ተደናገጡ፡፡

የማኅበሩ ሥራ አመራር አባላትም፡- አይዟችሁ አትደንግጡ፤ ኹሉም በጊዜው ይኾናል፡፡ እግዚአብሔር በፈቀደበት ጊዜ ዐውደ ርእዩን እናሳያችኋለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ግን በትዕግሥት ኾነን እንጠባበቅ፤ ወዘተ እያሉ ዐውደ ርእዩን በጉጉት ሲጠባበቁ የነበሩትን ምእመናን እያጽናኑ ከሚመለከታው አካላት ጋር ውይታቸውን ቀጠሉ፡፡

እግዚአብሔር ሥራውን የሚሠራበት ጊዜ ሲደርስ በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት፣ በአባቶችና በእናቶች ጸሎት የማኅበሩና የተባባሪዎቹ ጥረት ተሳክቶ ዐውደ ርእዩ የሚታይበት ቀን ደርሶ እነሆ ከግንቦት 17 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለተመልካቾቹ ይፋ ኾነ፡፡

መስቀል ዐደባባይን በማቋረጥ ከሰሜን ወደ ምዕራብ አቅጣጫ ከፍ ብሎ ወደሚገኘው ቅፅር ግቢ ውስጥ ሲገሰግሱ የኢትዮጵያውያንን ባህል ገላጭ የኾነውንና ጠቢባኑ የተካኑበትን በረጅሙ ቆሞ ከርቀት የሚታየውን በኅብረ ቀለማት ያጌጠውን መሶብ ያገኛሉ፡፡

ይህንን መሶብ አለፍ እንዳሉ በግዙፉ መግቢያ በር ላይ አምስተኛው ዙር የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል፣ ከግንቦት 17-22 ቀን 2008 ዓ.ም የሚሉ ማስታዎቂያዎች በረጅም ብራና ቁልቁልና አግድም ተለጥፈው ይነበባሉ፡፡

ከታች ደግሞ የጸጥታ ባለሙያዎች ተመልካቾችን በጥንቃቄ እየፈተሹ ወደ ኤግዚብሽን ማዕከሉ ቅፅር እንዲገቡ ያደርጋሉ፡፡ የዐውደ ርእዩ ታዳሚዎችም በሩ ውስጥ የተመደቡትን የቲኬት ሽያጭ አስተባባሪዎች ፈቃድ ካገኙ በኋላ ወደ አዳራሾቹ ጥቂት እንደተጓዙ ከአስፋልቱ በስተቀኝ በኩል ተንጣሎ የሚታየውን ቍጥር አንድ አዳራሽን ያገኛሉ፡፡ ይህ አዳራሽ በቍጥር የመጀመሪያው ይሁን እንጂ በዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ግን የመጨረሻው ነው፡፡

በአስተባባሪዎች መሪነት ወደ ሰሜን ምዕራብ አቅጣጫ ጥቂት ተጉዘው ጊዜያዊ የእንግዶች ማረፊያ ድንኳን ውስጥ ቁጭ ብለው በድምፅና በምስል የታገዙ ልዩ ልዩ መንፈሳውያን መረጃዎችን ሲከታተሉ ከቆዩ በኋላ በተራ ቅደም ተከተላቸው መሠረት ወደ ትዕይንቱ አዳራሾች ያመራሉ፡፡

የኤግዚብሽን ማዕከሉ በስተሰሜን በኩልም ተጨማሪ የመግቢያ በር ያለው ሲኾን፣ እንደዋናው በር ኹሉ የመግቢያ ቅድመ ኹኔታዎችን ካሟሉ በኋላ ወደ ደቡብ አቅጣጫ ሲያመሩ በዋናው በር ከገቡ ታዳሚዎች ጋር በአንድ ድንኳን ውስጥ አብረው እንዲቆዩ ይደረጉና ወደ ትዕይንቶች ይገሰግሳሉ፡፡

ይህ መንፈሳዊ ዐውደ ርእይ በአባቶች ጸሎት ከተከፈተበት ዕለት ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በርካታ ምእመናን እየተመለከቱት ሲኾን፣ የምእመናኑ ቍጥርም ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ ነው፡፡

የዐውደ ርእዩ አዘጋጆችና አስተባባሪዎቹ ምእመናኑ ረጅም ሰዓት በመቆም እንዳይጉላሉ በማሰብ የሚቻላቸውን ኹሉ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ ስለዚህም ከኤግዚብሽን ማዕከሉ አዳራሾች በተጨማሪ ሰፋፊ ድንኳኖችን በማዘጋጀት ተጨማሪ መመልከቻ ቦታዎችን አመቻችተዋል፡፡

ትዕይንታተ ዐውደ ርእይ

ዐውደ ርእዩ በሦስት መንገድ ይጎበኛል፤ ይኸውም በገላጮች ማብራሪያ፣ በባነሮች (ብራናዎች) ላይ በተቀመጡ ጽሑፎችና መረጃዎች እንደዚሁም በድምፅ ወምስል በመታገዝ ነው፡፡ የዐውደ ርእዩ ዐበይት አርእስትም አራት ሲኾኑ እነዚህም፡-

የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት፤ ሁለተኛው የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ፤ ሦስተኛው የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ፤ አራተኛው ደግሞ ምን እናድርግ የሚሉ ናቸው፡፡ የእያንዳንዳቸውን ጭብጥ ለማስገንዘብ ያህል የአርእስቱን ዐሳብ በአጭሩ እንመልከት፤

ትዕይንት አንድ፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት

ይህ ትዕይንት ሀልዎተ እግዚአብሔር፣ ነገረ ድኅነት፣ ነገረ ማርያም፣ ነገረ ቅዱሳን እና ነገረ ቤተ ክርስቲያን የተካተቱበት ክፍል ነው፡፡ ሀልዎተ እግዚአብሔር በሚለው ርእስ እግዚአብሔር አምላክ በጊዜና በቦታ የማይወሰን፣ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው፣ የፍጥረታት ኹሉ አስገኝ፣ ከመሥፈርትና ከአመለካከት ውጪ፣ እርሱ በገለጠው መጠን ብቻ የሚታወቅ እንጂ ባሕርዩ ተመርምሮ ሊደረስበት እንደማይቻል እንደዚሁም መልዕልተ ኵሉ (የኹሉ የበላይ) ኾኖ ሳለ በፈቃዱ የትሕትና ሥራ መሥራቱን ያስረዳል፡፡

ነገረ ድኅነት ደግሞ በአዳምና በሔዋን ምክንያት የዘለዓለም ሞት ተፈርዶበት የነበረው የሰው ልጅ ከሦስቱ አካላት አንዱ በኾነው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀልና ሞት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መቻሉን፤ ንደዚሁም እምነት፣ ምግባር እና ምሥጢራተ በቤተ ክርስቲያንን መፈጸም የሰው ልጅ ለመዳን የሚያስፈልጉት ነገሮች መኾናቸው በዚህ ርእስ ሥር ተካቷል፡፡

ትዕይንት ሁለት፡- የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ

በዚህ ትዕይንት የሐዋርያነትና የሐዋርያዊ አገልግሎት ትርጕም፣ ዓላማና አመሠራረትን ጨምሮ ስብከተ ወንጌል አንዴት እንደተስፋፋና እስከ ዛሬ ድረስ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሱ ፈተናዎችን እንደዚሁም መልካም አጋጣሚዎችን በማካከተት ልዩ ልዩ መረጃዎችና ትምህርቶቸ ቀርበውበታል፡፡

ትዕይንት ሦስት፡- የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ

ይህ ትዕይንት ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን ለማስፋፋት ያሳለፈችውን ተጋድሎ፣ የመናፍቃንን ተፅዕኖና የሰማዕታትን ታሪክ፣ የተዋሕዶ ሃይማኖትን አስተምህሮ ለማስጠበቅ የተደረጉ ልዩ ልዩ ዓለም ዓቀፍና አገር ዓቀፍ ጉባኤያትን በዝርዝር ይዟል፡፡

ትዕይንት አራት፡- ምን እናድርግ?

ይህ ትዕይንት ደግሞ ምእመናን በዐውደ ርእዩ ከተመለከቷቸውና ከሰሟቸው እውነታዎች በመነሣት የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ከመጠበቅና ድርሻን ከማወቅ አኳያ ልዩ ልዩ ችግሮችን ለመቅረፍ ወደፊት ምን ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው የሚያስረዱ መረጃዎችን አካቷል፡፡

ዐውደ ርእዩ ከነዚህ ዐበይት ትዕይንቶች በተጨማሪ የሕፃናት ትዕይንትም የተካተተበት ሲኾን፣ በዚህ ትዕይንት ለሕፃናት አእምሮ የሚመጥኑ መንፈሳውያን ትምህርቶች ተዘጋጅተውበታል፡፡ ሕፃናቱም ክፍሉ ውስጥ እየዘመሩ ይማራሉ፤ ይደሰታሉ፡፡

ከሁሉም በተለየ መንገድ ደግም የሁሉም ገባኤያት (የንባብ፣ የዜማ/የድጓ፣ የቅዳሴ፣ የቅኔ፣ የአቋቋም፣ የመጻሕፍትና የአቡሻሕር ጉባኤ ቤቶች) ሊቃውንት (መምህራን) ደቀ መዛሙርታቸውን ሲያስተምሩ እስከ ጎጆዎቻቸውና እስከሚጠቀሙባቸው ዕቃዎች ድረስ በተግባር ይታያሉ፡፡ የብራና መጻሕፍት አዘገጃጀትም በባለሙያ አባቶች ይብራራል፡፡

የማኅበረ ቀዱሳንን ልዩ ልዩ ክፍሎች፣ እንደዚሁም የጽርሐ ጽዮንና የደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳውያን ማኅበራት አገልግሎት የሚቃኝባቸው ክፍሎችም የትዕይንቱ አካላት ናቸው፡፡ በማኅበሩ የሚዘጋጁ ንዋያተ ቅድሳትና መጻሕፍትም በሽያጭና በዕጣ መልክ ቀርበዋል፡፡

ማኅበረ ጽዮን የጉዞ ማኅበር፣ መቄዶንያ የአረጋውያንና የአእምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል፣ ዮድ አቢሲንያ አስጎብኚና የጉዞ ወኪል ስለሚሰጧቸው ተግባራት የሚገልጹባቸው ክፍሎችም ተካተዋል፡፡

ትዕይንቶቹን ተመልክተው የሚወጡ ምእመናንም ኾኑ የሌሎች እምነት ተከታዮች ለሚያነሷቸው ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን መውጫው በር ላይ ተሠይመዋል፡፡

የዐውደ ርእዩ ታዳሚዎች ጉብኝቱን ጨርሰው ሲወጡ ደግሞ የተሰማቸውን ስሜት ወይም ደግሞ ቅሬታ የሚያሰፍሩባቸው የአስተያየት መስጫ መዛግብት በብዛት ተደርድረዋል፤ ጎብኝዎቹም ስሜታቸውን እየጻፉ ወደየመጡበት ይመለሳሉ፡፡

ከዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ጎን ለጎንም ከግንቦት 17 ቀን 2008 ጀምሮ የአብነት ትምህርቶችን የተመለከቱ ጥናቶችና መንፈሳውያን ተውኔቶች እንደዚሁም መዝሙራት ከቀኑ 11፡00 እስከ ምሽት ድረስ ለጎብኝዎቹ በመቅረብ ላይ ይገኛሉ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለአምስተኛ ጊዜ ያዘጋጀው ይህ ዐውደ ርእይ መታየት ከጀመረ እነሆ ዛሬ አምስተኛውን ቀን ያስቈጠረ ሲኾን፣ እጅግ በሚማርክ ኹኔታ በአባቶች ካህናትና በምእመናን ብቻ ሳይኾን በሌሎች ሰዎችም እየተጎበኘ ይገኛል፡፡

ትናንትናና ዛሬም በርካታ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በዐውደ ርእዩ ተገኝተው አባታዊ ቡራኬ ሰጥተዋል፤ ማኅበሩ እየሠራ ያለውን ተግባር በማድነቅም ስሜታቸውን መዝገብ ላይ አስፍረዋል፡፡

ለዐውደ ርእዩ ድምቀት ከሰጡ ክሥተቶች መካከልም የሰንበት ት/ቤት ዘማርያን የመዝሙር ልብስ ለብሰው እየዘመሩ፤ እንደዚሁም በዛሬው ዕለት (ግንቦት 21 ቀን 2008 ዓ.ም) ጋብቻቸውን የፈጸሙ ጥንዶች ከአጃቢዎቻቸው ጋር በመኾን በዐውደ ርእዩ መታደማቸው ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡

ዐውደ ርእዩ ከተከፈተበት ቀን ጀምሮ በአስተያየት መስጫ መዛግብቱ ላይ የሰፈሩትን አስተያየቶች ስናነብና ቃለ መጠይቅ ስናደርግ ብዙ ምእመናን በዐውደ ርእዩ ራሳቸውን እንዳዩበትና ስለሃይማኖታቸው በቂ ግንዛቤ እንዳስጨበጣቸው እንደዚሁም የድርሻቸውን ለመወጣት እንዳነሣሣቸው ተረድተናል፡፡

በተጨማሪም ዐውደ ርእዩ በዐዲስ አበባ ብቻ ሳይኾን በየአገሩ ቢታይ፣ ትዕይንቶቹ በብሮሸርና በሲዲ መልክ ቢሠራጩ፣ ከጠቅላይ ቤተ ክህነትና ከሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ጋር በጋራ በመኾን ማቅረብ ቢቻል መልካም ነው የሚሉና የመሳሰሉ አስተያየቶች ተሰጥተዋል፡፡

በአንጻሩ በትዕይንቶቹ ገላጮችና በምስል ወድምፅ ዝግጅቶች መካከል የድምፅ መጋጨት እንዳይኖር ጥንቃቄ ቢደረግ፤ ግቢው ውስጥ በማኅበሩ የተዘጋጁ ምግቦችና መጠጦች ለሽያጭ ቢቀርቡ፤ ትዕይንቶቹ ሰፊ ጊዜ ተሰጥቷቸው በስፋት ቢተነተኑ፤ አዳራሾቹ ውስጥ ረጅም ሰዓት መቆየት ባይኖር፤ ወዘተ የመሰሉ በርካታ አስተያየቶችንም ከአንዳንድ ጎብኝዎች ለመረዳት ችለናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስን ጉባኤ መጀመር አስመልክቶ ከቅዱስ ፓትርያሪኩ የተሰጠ መግለጫ

ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች፣ እንደሚታወቀው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በዛሬው ዕለት ተጀምሯል፤ ቅዱስ ፓትርያሪኩ ጠዋት ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ለጋዜጠኞች የሰጡትን ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ወዓዲ እብለክሙ ለእመ ኀብሩ ክልኤቱ አው ሠለስቱ እምኔክሙ በውስተ ምድር በእንተ ኵሉ ግብር ዘሰአሉ ይትገበር ሎሙ በኀበ አቡየ ዘበሰማያት እስመ ኀበ ሀለዉ ክልኤቱ ወሠለስቱ ጉቡአን በስምየ ህየ እሄሉ አነ ማእከሎሙ፤ ዳግመኛም ከእናንተ ሁለቱ ወየም ሦስቱ በምድር ላይ ስለሚለምኑት ሥራ ሁሉ ቢተባበሩ፣ በሰማያዊ አባቴ ዘንድ ይደረግላቸዋል፤ ሁለቱ ወይም ሦስቱ በስሜ ተሰብስበው ካሉበት፣ እኔ ከዚያ በመካከላቸው እገኛለሁና /ማቴ.፲፰፥፲፱-፳/፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ከጌታችን፣ ከአምላካችንና ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተሰጠንን ዓቢይ ተልእኮ ወይም ሐዋርያዊ አገልግሎት በየተሠማራንበት ሀገረ ስብከት ስናከናውን ቆይተን፣ በዓለ ትንሣኤውን ካከበርን በኋላ፣ በቀኖና ሐዋርያት ድንጋጌ መሠት፣ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን ጉዳዮች ለመነጋገር በዚህ በረክበ ካህናት ዓመታዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አንድ ላይ ስለሰበሰብን፣ አምላካችን እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማይታበል ቃሉ እንዳስተማረን፣ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የገባው ቃል ኪዳን አለ፤ እርሱም ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር የተፈጸመ ጽኑ ቃል ኪዳን ነው፡፡ ቃል ኪዳኑም፡- ሁለቱ ወይም ሦስቱ በስሜ በተሰበሰቡበት፣ እኔ ከዚያ በመካከለቸው እገኛለሁ ይላል፡፡ በሁሉም ዘንድ እንደሚታወቀው፣ ቃል ኪዳን በሁለት ወገኖች መካከል የሚፈጸምና ለቃል ኪዳኑ መከበር የሁለቱንም የቃል ኪዳን አካላት ኃላፊነት በግልጽ የሚያስቀምጥ ነው፤በዚህ ሁኔታ እግዚአብሔር ከጥንት ጀምሮ ከቅዱሳን አበው ጋር ቃል ኪዳን መሥርቶ እንደነበረ በቅዱስ መጽሐፍ በየቦታው ተጽፎ እናገኛለን፡፡

ይሁንና በዘመነ ሐዲስ ጌታችን ቃል ከገባባቸው ዓበይት ነገሮች አንዱ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ነው፡፡ በዚህ ቃል ኪዳን ውስጥ ቅዱስ ሲኖዶስ በስመ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲሰበሰብ ሓላፊነት ተሰጥቶታል፡፡ ጌታችንም በስሙ በሚደረግ ጉባኤ እንደሚገኝ ቃል ገብቶአል፡፡

በመሆኑም የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በርእሰ መንበርነት፣ ቅዱስ ፓትርያርክ በመሪነት፣ ሊቃነ ጳጳሳት በአባልነት የሚገኙበት ዓቢይ ጉባኤ ነው፡፡ ቅዱስ ወይም ልዩ ጉባኤ የሚያሰኘውም ቅሉ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በርእሰ መንበርነት የሚገኝበት በመሆኑ ነው፡፡ ይህ ጉባኤ ጌታችን እስከ ዓለም ፈጻሜ ድረስ እንደማይለየው ሲገልጽ፡- ወናሁ አነ እሄሉ ምስሌክሙ እስከ ኅልቀተ ዓለም፤ እነሆ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ እኔ ከናንተ ጋር ነኝ ብሎ በቃሉ አረጋጦአል /ማቴ.፳፰፥፳/፡፡

እንግዲህ በየጊዜው ስመ እግዚአብሔርን ጠርተን በስሙ፣ ስለስሙ ብለን የምናካሂደው ቅዱስ ጉባኤ ወይም ቅዱስ ሲኖዶስ ይህን ያህል ታላቅ ክቡርና ጽኑ የሆነ አምላካዊ ቃል ኪዳን ያለው እንደመሆኑ መጠን፣ ለደረጃው በሚመጥን ክብርና ልዕልና መካሄድ ይኖርበታል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ጌታችን፣ አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን በአደራነት ያስረከበ ለዚህ ጉባኤ እንደሆነ በውል የሚታወቅ ነው፡፡

ይህ ቅዱስ ጉባኤ የእግዚአብሔር መንግሥት ወኪል እንደመሆኑ መጠን ድንበር የለውም፤ ምክንያቱም የእግዚአብሔር መንግሥት ድንበር የለውምና፡፡ ይህ ጉባኤ ገደብ የለሽ መንፈሳዊ ሥልጣን ከሕያው አምላክ ሲሰጠው፣ ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፤ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ ከሚል ትእዛዝ ጋር መታዘዙ የቅዱስ ሲኖዶስ መንፈሳዊ ሥልጣን ድንበር የማይገድበው መሆኑን በግልጽ ያሳያል /ማር.፲፮፥፲፭/፡፡

በመሆኑም የዚህ ቅዱስ ጉባኤ ሥራና ሓላፊነት ዓለም አቀፋዊ ይዘት ያለው መሆኑ ሊሠመርበት ይገባል፡፡ ይህም በመሆኑ ነው ዛሬ ቤተ ክርስቲያናችን በሁሉም ክፍላተ ዓለም አብያተ ክርስቲያናትን ከፍታ ሐዋርያዊ ተልእኮዋን በማካሄድ ላይ የምትገኘው፡፡

ይሁንና አሁን የምንገኝበት የሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ወቅት፣ የሴኩላሪዝም አስተሳሰብ ያየለበት፤ የዓለም ሉላዊነት የበረታበት፣ የጽንፈኝነትና የሽብርተኝነት መንፈስ የተስፋፋበት፣ እነዚህ ሁሉ በየፊናቸው ተሰልፈው በሃይማኖት ላይ ከባድ ተጽዕኖ የፈጠሩበት ዘመን ነው፡፡ ዓለም በዚህ ሥጋዊ ፍልስፍና እና ቁሳዊ አምሮት ቤተ ክርስቲያንን ለመውጋት ስትዘጋጅ እኛ የክርስቶስ ወኪሎች እንዲሁ ዝም ብለን የምናይበት ኅሊና ሊኖረን አይችልም፡፡

ቀደምት አበው እሾህን በእሾህ ብለው እንደተናገሩት፣ የዓለምን ጥበብ በክርስቶስ ጥበብ ለመቋቋም፣ በዓለም እየሆነ ያለውን ነገር ሁሉ መከታተልና ማወቅ፣ ለወደፊትም ሊያስከትለው የሚችለውን ሃይማኖታዊ፣ ማኅበራዊ፣ ሰብአዊና ባህላዊ ቀውስ አስቀድሞ በመተንበይ፣ ሕዝቡን በእግዚአብሔር ቃል ኃይል መጠበቅና መንከባከብ ከእኛ ይጠበቃል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

በሃይማኖት ዙሪያ ያንዣበቡ እነዚህ ዓለም አቀፍ ተፅዕኖዎች እጅግ አስጊ ቢሆኑም፣ እነርሱን ለመከላከል ብሎም ለመቀልበስ አሁንም ቢሆን ጊዜው አልመሸም፡፡ በተለይም በሀገራችን ያለው ሕዝብ፣ አሁንም ምርጫው እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን እንደሆነ በተጨባጭ የምናውቀው ሐቅ ነው፡፡ ይህንን ሕዝብ በሚገባ ማገልገል ከተቻለ፣ ችግሩን በሚገባ መቋቋም ይቻላል፡፡

ስለሆነም ሕዝበ ክርስቲያኑን በአግባቡ ለማገልገልና ለመጠበቅ፣ ከሁሉም በፊት የሕዝቡን ጥያቄ ማወቅ ያስፈልጋል፤ ቀጥሎም ለጥያቄው ተገቢ የሆነ መልስ በመስጠት ፍጹም መግባባት መፍጠር ይገባል፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑ ከሃይማኖት መሪዎችና ከአገልጋይ ካህናት የሚጠብቀውን ሁለንተናዊ አገልግሎት በሚገባ ካገኘና በሃይማኖቱ እንዲኮራ የሚያስችል ሁኔታ ከተመቻቸለት፣ ለተጠቀሱ ዓለም ዓቀፍ ተፅዕኖዎች ተንበርካኪ አይሆንም፡፡ ስለሆነም የኛው የጥበቃ ስልት መቀየስ ያለበት በዚሁ መንፈስ አቅጣጫ ነው፡፡

ሕዝበ ክርስቲያኑ በአሁኑ ጊዜ የሚጠይቃቸው ብዙ ነገሮች አሉ፤

ሕዝቡ፣ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና ለሃይማኖት መጠበቂያ ብሎ በእምነት የሚለግሰው ገንዘብና ንብረት ከምዝበራ ተጠብቆ ለታለመለት ዓላማ ብቻ እንዲውል ይፈልጋል፤

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መልካም አስተዳደር ሰፍኖ አድልዎ፣ ጭቅጭቅ፣ ንትርክ፣ መለያየት በአጠቃላይ ከሃይማኖቱ መርሕ ጋር የማይጣጣም ኋላ ቀር አሠራርና አስተሳሰብ ተወግዶ የተስተካከለ ሥርዓትን ማየት ይፈልጋል፤

ስለሃይማኖት ክብርና ህልውና ከልብ የሚቆረቆሩ፣ መልካም የሆነ ሥነ ምግባርና የተስተካከለ ሰብእና ያላቸው እንደዚሁም በኑሮአቸው ሁሉ ለሕዝበ ክርስቲያኑ እንደ ሞዴል የሚጠቀሱ ውሉደ ክህነትና ሠራተኞች እንዲመሩት ይፈልጋል፤

ሕዝቡ ቤተ ክርስቲያን በሁሉም መስክ ጠንካራ ዓቅምን ገንብታ እንደዚሁም ለሕዝበ ክርስቲያኑ መንፈሳዊና ማኅበራዊ ችግር ደራሽና አለሁላችሁ ባይ ኾና ማየት እንደሚፈልግ ከሚያነሣው ጥያቄ ማወቅ ይቻላል፡፡

ብፁዓን ሊቃ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

የእኛ ተልእኮ እግዚአብሔርንና ሕዝብን ማገልገል ከሆነ፣ የሕዝቡ ጥያቄም ከሞላ ጎደል የሚታወቅ ከሆነ፣ በተሰጠን አደራና ሓላፊነት መሠረት የሕዝበ ክርስቲያኑን ጥያቄ በጽሞና አዳምጠንና ተቀብለን፣ በቅዱስ መጽሐፍ አስተምህሮ፣ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ድንጋጌና ባሉን የቤተ ክርስቲያን ሕጎች ማእከልነት፣ ጥያቄውን የማስተናገድ ክርስቶሳዊ ግዴታ አለብን፡፡

ከሕግ የወጣ የሥራ አፈጻጸም ሲኖርም፣ ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ በወቅቱ ማረም ያስፈልጋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቱያናችን የመጨረሻ ውሳኔ ሰጭ አካል እንደመሆኑ መጠን፣ የቤተ ክርስቲያናችንን መልካም አስተዳደር ለማስፈን የሚያስችሉ ሕጎችን፣ ልዩ ልዩ ደንቦችን፣ መመሪያዎችን፣ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በማዘጋጀትና በማጽደቅ፣ እንደዚሁም በአፈጻጸማቸው ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ፣ ሕዝበ ክርስቲያኑን እሰየው የሚያሰኝ አሠራር ማረጋገጥ አለብን፡፡ ይኸ ሲሆን ብቻ ነው ሕዝቡን ከቁሳዊው ዓለም ማዕበል መታደግ የምንችለው፡፡

በመጨረሻም

ይህ የተቀደሰ ክርስቶሳዊና ሐዋርያዊ ጉባኤ ከልዩ ልዩ የቤተ ክርስቲያናችን አመራር አካላትና ከጉባኤው የሚቀርቡትን ሃይማኖታዊ ሀገራዊ ጉዳዮችን በጥልቀት በመፈተሽና በመመርመር እንደዚሁም ሕጋዊና ቀኖናዊ መፍትሔ በማስቀመጥ የተሳካ ውጤት ያስመዘግብ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እየጸለይንና ከልብ እየተመኘን የ፳፻፰ ዓ.ም የረክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ዛሬ መከፈቱን እናበሥራለን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤

አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም

ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን አምስተኛው ዙር ዐውደ ርእይ ተጀመረ፡፡

ዐውደ ርእዩ ለስድስት ተከታታይ ቀናት ከጠዋቱ 2፡00 እስከ ምሽቱ 1፡30 ድረስ ለተመልካቾች ክፍት ኾኖ ይቆያል፡፡

ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በማኅበረ ቅዱሳን የተዘጋጀውና በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው አምስተኛው ዙር መንፈሳዊ ዐውደ ርእይ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ የማኅበሩ ሥራ አመራር አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ እንደዚሁም የዐውደ ርእዩ ተመልካቾች በተገኙበት በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማእከል ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በአባቶች ጸሎት ተጀምሯል፡፡

በጸሎተ ወንጌሉ የተሰበከው ምስባክ፡- ጥቀ ዐቢይ ግብርከ እግዚኦ ወኵሎ በጥበብ ገበርከ መልዐ ምድረ ዘፈጠርከ፤ አቤቱ ሥራህ እጅግ ታላቅ ነው፡፡ ሁሉን በጥበብ አደረግህ፡፡ የፈጠርኸውም ፍጥረት ምድርን ሞላ፤ /መዝ.፻፫፥፳፬/ የሚለው ትምህርት ሲኾን፣ የተነበበው የወንጌል ክፍልም ሉቃ. ፲፥፳፩-፳፬ ያለው ኃይለ ቃል ነው፡፡

ጸሎተ ወንጌሉና ኪዳኑ እንደ ተፈጸመ ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ የመክፈቻ ንግግር ካደረጉ በኋላ ዐውደ ርእዩ በይፋ ለተመልካች ክፍት ኾኗል፡፡

የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ በሚል መሪ ቃል በተዘጋጀው በዚህ ዐውደ ርእይ የቤተ ክርስቲያን ማንነትና ሐዋርያዊ ተልዕኮ በዓለም፣ በአፍሪካና በኢትዮጵያ፣ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ፈተናዎችና ከምእመናን የሚጠበቁ ጉዳዮች የትእይንቱ አርእስት ኾነው ይቀርቡበታል፡፡

ዐውደ ርእዩ ከግንቦት ፲፯-፳፪ ቀን ፳፻፰ (17-22 ቀን 2008) ዓ.ም፣ ከጠዋቱ 2፡00 እስከ ምሽቱ 1፡30 ድረስ ለስድስት ተከታታይ ቀናት ለተመልካቾች ክፍት ኾኖ ይቆያል፡፡

ከመጋቢት ፲፭-፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለተመልካች ሊቀርብ የነበረው ይህ ዐውደ ርእይ ለጊዜው ግልጽ ባልነበረ ምክንያት ታግዶ ቢቆይም፣ ማኅበረ ቅዱሳን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ባደረገው ውይይት እገዳው ተነሥቶ ለእይታ በቅቷል፡፡

Tewahedoapp

ተዋሕዶ የአይፎን አፕሊኬሽን ተሻሽሎ አገልገሎት መስጠት ጀመረ::

አፕሊኬሽኑ ለሁሉም የአፕል ስልኮችና አይፓዶች በሚኾን መልኩ ተሻሽሎ ቀርቧል፡፡

ትምህርቶችን፣ ጸሎታትን፣ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶችን፣ የየዕለቱን ምንባባትና የአብያተ ክርስቲያናት መረጃዎችን ይዟል፡፡

ግንቦት ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

Tewahedoappበሰሜን አሜሪካ ማእከል

በእጅ ስልክ አማካይነት ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ትምህርቶችን፣ ስብከቶችን፣ መዝሙራትንና ጸሎታትን በቀላሉ ማግኘት የሚያስችለው ተዋሕዶ የአይፎን አፕሊኬሽን ተሻሽሎ አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ተገለጠ፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የሰሜን አሜሪካ ማእከል ሙያ አገልግሎትና ዐቅም ግንባታ ክፍል ለዝግጅት ክፍላችን በላከው መረጃ እንደገለጠው፤ በማእከሉ ታቅፈው ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በሞያቸው በሚያገለግሉ አባላት ቀደም ሲል የተዘጋጀው አፕሊኬሽኑ ለምእመናን ሰፊ አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡

ከተጠቃሚዎች በተሰጡ አስተያየቶችና በባለሞያዎቹ ምክርና ጥረት ለሁሉም የዓፕል ስልኮችና አይፓዶች በሚኾን መልኩ ተሻሽሎ ቀርቧል፡፡ በአዲስ መልክ የተሸሻለው ይህ አፕሊኬሽን ከበርካታ ትምህርቶች፣ ጸሎታት፣ መዝሙራት፣ ኪነ ጥበባዊ ዝግጅቶች በተጨማሪ የኢትዮጵያን ካላንደር (በዓላትና አጽዋማት ማውጫ)፣ በየዕለቱ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባትን እንዲሁም በአሜሪካ፣ በካናዳና አውሮፓ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትን አድራሻና መሠረታዊ መረጃዎችን ያካተተ ነው፡፡

በተጨማሪም አፕሊኬሽኑ ልዩ ልዩ ዓመታዊ በዓላት እና አጽዋማት ሲደርሱ ለተጠቃሚዎቹ ማስታወሻ እንዲልክ ኾኖ ተዘጋጅቷል፡፡ የማእከሉ ሙያና ዐቅም ማጎልበቻ ክፍል ምእመናን ይህንን አፕሊኬሽን እዚህ ላይ በመጫን እንዲገለገሉ፣ ላልሰሙትም እንዲያሰሙ ሲል ያበስራል፡፡

ርክበ ካህናት

ግንቦት ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ረክብ የሚለው ቃል ተራከበ ተገናኘ ከሚለው የግእዝ ግስ የወጣ ሲሆን ትርጕሙም ማግኛ፣ መገኛ፣ መገናኛ ማለት ነው /ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ገጽ ፰፴፩/፡፡ ርክበ ካህናትም የካህናት መገኛ፣ መገናኛ፣ ጉባኤ (መሰባሰቢያ)፣ መወያያ፣ ወዘተ የሚል ትርጕም ይኖረዋል፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን ቋንቋ ክህነት የሚለው ቃል ከጵጵስና ጀምሮ እስከ ዲቁና ድረስ ያሉትን መዓርጋት የሚያጠቃልል ስያሜ ሲሆን ካህን (ነጠላ ቍጥር)፣ ካህናት (ብዙ ቍጥር) በአንድ በኩል ቀሳውስትን የሚወክል ሆኖ በሌላ በኩል ደግሞ የጳጳሳት፣ የኤጲስ ቆጶሳት፣ የቀሳውስት፣ የዲያቆናት የጋራ መጠሪያ ሆኖ ያገለግላል፡፡ ርክበ ካህናት የቃሉ ትርጕም እንደሚያስረዳው የአባቶች ካህናት ማለትም የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት (የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት) ጉባኤ ማለት ነው፡፡

በዓሉ በየዓመቱ የትንሣኤ በዓል በዋለ በ፳፭ኛው ቀን ሁልጊዜ በዕለተ ረቡዕ ይዋል እንጂ ወሩና የሚውልበት ቀን ግን የበዓላትንና የአጽዋማትን ቀመር ተከትሎ ከፍና ዝቅ ሊል ይችላል፡፡ የአጽዋማትና የበዓላት ቀመር ከመዘጋጀቱ በፊት ማለትም በቅዱስ ድሜጥሮስ አማካኝነት ዐቢይ ጾም ሰኞ፣ ስቅለት ዓርብ፣ ትንሣኤ እሑድ፣ ርክበ ካህናት ረቡዕ፣ ዕርገት ሐሙስ፣ ጰራቅሊጦስ እሑድ እንዲሆን ከመደረጉ በፊት ርክበ ካህናት ግንቦት ፳፩ ቀን ይውል ነበር /መጽሐፈ ግጻዌ ግንቦት ፳፩/፡፡

ከዚህ በኋላ ግን ርክበ ካህናት በዓለ ትንሣኤ በዋለ በ፳፭ኛው ቀን፣ በበዓለ ሃምሳ እኩሌታ በዕለተ ረቡዕ ይዘከራል፡፡ በያዝነው ዓመት በ፳፻፰ ዓ.ም የትንሣኤ በዓል ከተከበረበት ዕለት (ሚያዝያ ፳፫ ቀን) ጀምሮ ብንቈጥር ፳፭ኛው ቀን ግንቦት ፲፯ ቀን ይሆናል፡፡ በመሆኑም የዘንድሮው ርክበ ካህናት ግንቦት ፲፯ ቀን (በነገው ዕለት) ይውላል ማለት ነው፡፡ ይህ በዓል ከቅዱሳን ሐዋርያት ጀምሮ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሲያስተዳድሩ የቆዩ አባቶቻችን በጋራ በመሰባሰብ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተቀላጠፈ አገልግሎት እንደዚሁም ለምእመናን አንድነትና መንፈሳዊ ዕድገት የሚበጁ መንፈሳውያን መመሪያዎችን የሚያስተላልፉበት ዕለት ነው፡፡

በቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል እንደተገለጸው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞት ከተነሣ በኋላ ለሦስተኛ ጊዜ ተገልጦ ከዐሥራ አንዱ ቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ምሳ በልቷል፡፡ ከምሳ በኋላም ጌታችን ቅዱስ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ ጠርቶ ትወደኛለህን? እያለ ከጠየቀው በኋላ እንደሚወደው ምላሽ መስጠቱን ተከትሎ በቅደም ተከተል በጎቼን ጠብቅ፤ ጠቦቶቼን አሰማራ፤ ግልገሎቼን ጠብቅ በማለት የአለቅነት ሥልጣን ሰጥቶታል፡፡ ይህ ምሥጢር ለጊዜው ጌታችን ሐዋርያትን፣ ሰብዐ አርድእትንና ሠላሳ ስድስቱን ቅዱሳት አንስት በአጠቃላይ መቶ ሃያውን ቤተሰብእ እንዲጠብቅና እንዲከባከብ ቅዱስ ጴጥሮስን ማስጠንቀቁን፤ ፍጻሜው ግን የቤተ ክርስቲያን አባቶች (ጳጳሳት) መምህራንንና መላው ሕዝበ ክርስቲያንን እንዲጠብቁና እንዲያስተዳድሩ በእግዚአብሔር መሾማቸውን የሚያስረዳ ትርጕም አለው /ዮሐ.፳፩፥፩-፲፯ (አንድምታ ትርጓሜ)/፡፡

ይህንን የጌታችን ትእዛዝና የሐዋርያትን ሥልጣነ ክህነት መሠረት በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜ ጉባኤ ያደርጋል፤ የመጀመሪያው ጉባኤ ጥቅምት ፲፪ ቀን (የቅዱስ ማቴዎስ በዓል) ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ይህ ርክበ ካህናት ነው፡፡ በዚህ ዕለት ቅዱስ ሲኖዶስ በሚያደርገው ጉባኤ የሚተላለፉ መመሪያዎችና የሚጸድቁ ውሳኔዎች ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት፣ ለምእመናን አንድነት፣ ለአገር ሰላምና ደኅንነት የሚጠቅሙ ይሆኑ ዘንድ ሁላችንም በጾም በጸሎት እግዚአብሔርን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ አምላካችን ቤተ ክርስቲያናችንንና አባቶቻችንን ይጠብቅልን፤ እኛንም ለአባቶች የሚታዘዝ ልቡና፣ ሓላፊነታችንን የምንወጣበትን ጥበብና ማስተዋሉን ያድለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ ሰባተኛ ዓመት የዕረፍት ቀናቸው ተዘከረ

በዕለቱ ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት በሚል ርእስ በ፲፱፻፺፮ ዓ.ም ባዘጋጁት መጽሐፋቸው ላይ የዳሰሳ ጥናት ቀርቧል፡፡

ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ በስእለት መልክ ለእግዚአብሔር መሰጠታቸውን እኅታቸው ተናግረዋል፡፡

ወጣቱ ትውልድ የእርሳቸውን ፈለግ ተከትሎ ቤተ ክርስቲያንን መጠበቅ ከቻለ አባ አበራ ሕያው ናቸው እንጂ አልሞቱም ተብሏል፡፡

ግንቦት ፲፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የሊቀ ገባኤ አባ አበራ በቀለ (ስመ ጥምቀታቸው ኃይለ መስቀል) ሰባተኛ ዓመት የዕረፍት ቀናቸው መታሰቢያ ቤተሰቦቻቸው፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራሮችና አባላት በተገኙበት ግንቦት ፲፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በማኅበሩ ሕንፃ ተዘክሯል፡፡

በዕለቱ ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት በሚል ርእስ በ፲፱፻፺፮ ዓ.ም ባዘጋጁት መጽሐፋቸው ላይ የዳሰሳ ጥናት ያቀረቡት ዲያቆን አሻግሬ አምጤ እንደገለጹት አባ አበራ ባለ ፬፹፬ ገጽ በሆነው በዚህ መጽሐፋቸው መግቢያ ላይ ክርስትና የፍቅር ሃይማኖት መሆኑንና የሃይማኖታችን ታሪክ በፍቅር ተጀምሮ በፍቅር መፈጸሙን አስረድተዋል፡፡ እንደዚሁም የሰው ልጅ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ ሦስት ዐበይት ነጥቦች እንደሚያስፈልጉና እነዚህም ማመን፣ መጠመቅና ትእዛዛትን መጠበቅ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡

በትምህርተ ሃይማኖት መቅድማቸውም ሃይማኖት ከእግዚአብሔር ለሰው የተሰጠ መሆኑን አስረድተው እምነት የሁሉ ነገር መሠረት እንደሆነ በማብራራት መሠረት ሕንፃዎችን ሁሉ እንደሚሸከም እምነትም ምግባራትን ሁሉ እንደምትይዝ፣ ሕንፃ ያለመሠረት እንደማይቆም ምግባርም ያለ ሃይማኖት እንደማይጸና የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን ትምህርት ጠቅሰው አስተምረዋል፡፡

በዳሰሳ አቅራቢው እንደተብራራው መጽሐፉ በክፍል አንድ አንቀጹ ሠለስቱ ምእት በኒቅያው ጉባኤ የደነገጉትን ጸሎተ ሃይማኖት እና በጉባኤ ቍስጥንጥንያ የተሰበሰቡ ፻፶ ሊቃውንትን ውሳኔ መጽሐፍ ቅዱስንና ሊቃውንትን መሠረት በማድረግ ያብራራል፡፡ ባጠቃላይም ስለ ሃይማኖት በመመስከር ላይ እንደሚያተኩር እና ሰይጣንን ክዶ የክርስቶስ ተከታይ ስለመሆን እንደሚያትት የጥናቱ አቅራቢ ዲያቆን አሻግሬ አስረድተዋል፡፡ ክፍለ ሁለት የክርስቶስ የማዳን ሥራና ጸጋ እውን የሚሆነው ቃሉን በመስማትና ምሥጢራትን በመፈጸም መሆኑን እንደሚያስረዳ፣ ክፍል ሦስት ደግሞ ክርስቲያናዊ ሕይወትና ምግባር በእምነት፣ በተስፋና በፍቅር መገለጡ ተብራርቶበታል፡፡

ምእመናን የመዳን ተስፋችን እውን እንዲሆን በሥስቱ አርእስተ ሃይማኖት ማለትም በእግዚአብሔር ፍቅር፣ በክርስቶስ ጸጋ እና በመንፈስ ቅዱስ ኅብረትና ረድኤት መመሥረት እንደሚገባን ይናገራል፡፡ በተጨማሪም አባ አበራ ፍቅርን አንደኛ እግዚአብሔር ለሰው ያለው ፍቅር፣ ሁለተኛ ሰው ለእግዚአብሔር ያለው ፍቅር እና ሦስተኛ ትእዛዛቱን መጠበቅ (አምላክህንና ባልንጀራህን ውደድ የሚሉትን) በማለት በሦስት ክፍል አቅርበውበታል፡፡ ይህም የአባ አበራ መጽሐፍ በዚህ ዓመት በማኅበረ ቅዱሳን እንደገና ታትሞ ገበያ ላይ ውሏል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም በሕይወት በነበሩበት ወቅት ያስተማሩት ትምህርትና ያደረጉት ንግግር በቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩምና በዲያቆን ሙሉዓለም ካሣ አስተባባሪነት በድምፅና ምስል ተቀናብሮ ለመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች የቀረበ ሲሆን ቀጥሎም ቤተሰቦቻቸውና በቅርብ የሚያውቋቸው ወዳጅ ዘመዶቻቸውና የመንፈስ ልጆቻቸው አባ አበራ ፍቅርን፣ መንፈሳዊነትን፣ ደግነትን፣ ቅንነትን እና ትሕትናን የተላበሱ፣ ከስስትና ከፍቅረ ንዋይ የራቁ አባት እንደነበሩ መስክረውላቸዋል፡፡

ታናሽ እኅታቸው ወ/ሮ ጸዳለ በቀለ አባ አበራ ሕፃን እያሉ ጥቅምት ፳፰ ቀን ወላጅ እናታቸው አዝለዋቸው በመንገድ ሲጓዙ በዘመኑ ታዳጊ ወንዶች ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ሽፍቶች ባገኗቸው ጊዜ እናታቸው አባቴ አማኑኤል ሆይ ልጄን ከነዚህ ሽፍቶች ብታድንልኝ የአንተ አገልጋይ ይሁን ብለው በስእለት መልክ ለእግዚአብሔር ሰጥተዋቸው ነበር፤ ይህም ሕይወታቸውን በሙሉ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት እንዲኖሩ አድርጓቸዋል ብለዋል፡፡

መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁንም ከሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ጋር በመሆን በስብከተ ወንጌልም በአስተዳደርም ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሲያገለግሉ መኖራቸውን አውስተው በተለይ ለወላጅ እናታቸው ልዩ ፍቅርና አክብሮት እንደነበራቸው ተናግረዋል፡፡ አክለውም የጻድቅ ሰው መታሰቢያ ለዘለዓለም ይኖራል የሚለውን ኃይለ ቃል መነሻ በማድረግ ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ራሳቸውን መሥዋዕት አድርገውና ልዩ ልዩ ፈተናዎችን ተቋቁመው ያሰቡትን መንፈሳዊ ዕቅድ ሁሉ አሳክተው ያለፉ አባት መሆናቸውን ጠቅሰው ወጣቱ ትውልድ የእርሳቸውን ፈለግ ተከትሎ ቤተ ክርስቲያንን መጠበቅ ከቻለ አባ አበራ ሕያው ናቸው እንጂ ሞቱ አይባልም ሲሉ መልእክታቸውን አጠቃለዋል፡፡

ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ በበኩላቸው አባ አበራ በአገር ውስጥም፣ ከአገር ውጪም በሚገኙ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት እየተዘዋወሩ ብዙ ዕውቀት መቅሰማቸውን ገልጸው፣ አክለውም ለሚሰማቸው ብቻ ሳይሆን ለሚመለከተቻውም አስተማሪ ሕይወት እንደነበራቸው፣ በሕይወት ከኖሩበት ጊዜ በላይ ካረፉ በኋላ ለብዙ ሰዎች ምሳሌ እንደሚሆኑና ሁሉም ሊማርባቸውና ሊያስታውሳቸው እንደሚገባ ገልጸው እኒህን አባት ለመዘከር ያመች ዘንድ በስማቸው የሚሰየም አንድ ስኮላርሺፕ ቢኖረን መልካም ነውና ሁላችንም ብናስብበት ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

በተጨማሪም ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ፣ ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ፣ አቶ ኤርምያስ ዓለሙ እና አቶ ሙሉጌታ ምትኩ ስለ አባ አበራ መንፈሳዊ ሕይወት ተመሳሳይ አሳብና አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

ከጽርሐ ጽዮን ማኅበር አባላት አንዷ የሆኑት ወ/ሮ ሙሉእመቤት በላቸውም፡- ክርስትና ማለት ራስን መካድ መሆኑን የተማርሁት ከአባ አበራ ነው፡፡ ሁላችንም አንረሳቸውም፡፡ እኛ ጊዜያችን እያለቀ ነው፡፡ እናንተ ወጣቶች ትግሉን እንደእርሳቸው ታገሉት፤ ትጥቁን እንደእርሳቸው ታጠቁት፡፡ የአባ አበራን ፈለግ ተከትላችሁ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ የሚመጣባችሁን ሁሉ ፈተና በጸጋ ተቀብላችሁ ወንጌልን ስበኩ ሲሉ እናታዊ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

በመጨረሻም በአባቶች ምክርና ጸሎተ ቡራኬ በስማቸው የተዘጋጀው ጸበል ጸሪቅ ከቀረበ በኋላ ከምሽቱ 2፡30 ገደማ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

ክቡር ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ ከአባታቸው ከግራ አዝማች በቀለ መኩሪያ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ በሸዋምየለሽ ድፋባቸው ከዐዲስ አበባ በስተምሥራቅ አቅጣጫ የረር አካባቢ በሚገኘው ልዩ ስሙ ቡኢ በተባለ ሥፍራ በዕለተ ስቅለት ሚያዝያ ፪ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም ተወልደው በ፸፫ ዓመታቸው ሚያዝያ ፭ ቀን ፳፻፩ ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው ይታወሳል፡፡

ለአርባ አምስት ዓመታት ያህል ቅድስት ቤተ ክርስቲያንንና ሀገራቸውን በፍጹም ፍቅር ሲያገለግሉ የቆዩት ሊቀ ጉባኤ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት ካበረከቱት ከፍተኛ አተዋጽዖ በተጨማሪ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነውን በውኃ እንፋሎት የሚንቀሳቀስ መኪና የሠሩ ጥበበኛም ነበሩ፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም እኒህ ታላቅ አባት ለቤተ ክርስቲያንና ለአገር ያበረከቱትን አስተዋጽዖ ግምት ውስጥ በማስገባት የሰባተኛ ዓመት የዕረፍት ቀናቸው እንዲዘከር አድርጓል፡፡

ፍልሰተ ዐፅሙ ለአቡነ ተክለ ሃይማኖት

ግንቦት ፲፪ ቀን፣ ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤ ግንቦት ፲፪ ቀን በዚህች ቀን ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት፣ ኢትዮጵያዊው ንጉሥ እስክንድር፣ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ቅዱስ መስቀል፣ ቅዱስ ሚናስ፣ ቅዱስ እስጢፋኖስ፣ የመላልዔል ልጅ ያሬድ፣ እንደዚሁም ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ይታሰባሉ፡፡ በዚህ ዝግጅት የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ፍልሰተ ዓፅም የሚያስታውስ ጽሑፍ ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

ስምዑ ወለብዉ ኦ ፍቁራንየ መጽሐፈ ዜናሁ ለክቡር ወቅዱስ ወለብፁዕ ፍቁረ እግዚአብሔር ዘይትነበብ በዕለተ ፍልሰተ ሥጋሁ አመ ፲ወ፪ ለግንቦት ዝ ውእቱ ድሙር ምስለ በዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ወበዓለ ሚካኤል ሊቀ መላእክት ፍቁሩ ለተክለ ሃይማኖት፤ ወዳጆቼ ሆይ፣ የከበረ፣ የተቀደሰ፣ የተደነቀ፣ የእግዚአብሔር ወዳጅ የሚሆን የአባታችን የተክለ ሃይማኖት ክብሩን፣ ገናንቱን የሚናገረውን፣ ዐፅሙ የፈለሰበትን ግንቦት ፲፪ ቀን የሚነበበውን መጽሐፍ አስተውላችሁ ስሙ፤ /ገድለ ተክለ ሃይማኖት ምዕ.፷፪፥፭/፡፡

ተክል ማለት ፍሬያማ ዕንጨት፣ ዛፍ፣ ቅመም፣ ቅጠላ ቅጠል፣ የሚበላ፣ የሚሸተት፣ ገነታዊ ዕፅ፣ እንዲሁም ሕግ ሥርዓት ማለት ነው /ማቴ.15፥13/፡፡ ሃይማኖት ማለት ደግሞ በሀልዎተ እግዚአብሔር፣ እግዚአብሔር የሁሉ አስገኚ መሆኑን፣ በሥላሴ አንድነትና ሦስትነት፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት ማመን አምኖም መመስከር ማለት ሲሆን ተክለ ሃይማኖት የሚለው ሐረግም የሃይማኖት ተክል፣ ይኸውም የጽድቅ ፍሬን ያፈራና ከኃጢአት ሐሩር ማምለጫ ዛፍ፣ ምእመናንን በቃለ ወንጌል ያጣፈጠ ቅመም፣ መዓዛ ሕይወቱ የሚማርክ፣ ቢመገቡት ረኃበ ነፍስን የሚያስወግድ ቅጠል፣ የጻድቃን መጠለያ ዕፅ የሚል ትርጕም ይኖረዋል ማለት ነው፡፡ መጽሐፈ ገድላቸውም ተክለ ሃይማኖት ማለት የአብ፣ የወልድ፣ የመንፈስ ቅዱስ ተክል ማለት ነው ሲል ይተረጕመዋል፡፡ አባታችን እርሳቸውም በአሚነ ሥላሴ ጸንተው ሌሎችንም እንዲጸኑና እንዲያምኑ አድርገዋልና፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖት በ፲፫ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ አካባቢ ከአገራችን ከኢትዮጵያ ምድር ከሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ከኢቲሳ መንደር ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብ እና ከእናታቸው እግዚእ ኀረያ አብራክ የተገኙ ቅዱስ አባት ናቸው፡፡ አባታችን ሕይወታቸዉን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ እንደ በሬ ተጠምደው፣ እንደገበሬ ታጥቀው ይህንን ዓለም ንቀው በጾም በጸሎት ተወስነው በብሕትውና ከመኖራቸው በተጨማሪ እንደቅዱሳን ሐዋርያት ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ የሰበኩ፣ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የፈወሱ ሐዋርያ ናቸው፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህንን ውለታቸውን በማሰብና ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን ቅድስና መሠረት በማድረግ በስማቸው ጽላት ቀርፃ ስታከብራቸው ትኖራለች፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከሚታወሱባቸው በዓላት መካከልም በዛሬው ዕለት የሚከብረው ፍልሰተ ዐፅማቸው አንደኛው ሲሆን ታሪኩንም በአጭሩ እነሆ፤

ጻድቁ አባታችን ምድራዊ ሕይወታቸውን በተጋድሎና በሐዋርያዊ አገልግሎት ከፈጸሙ በኋላ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ የሚያልፉበት ቀን በተቃረበ ጊዜ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን መላእክት፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ወደእርሳቸው በመምጣት የሚያርፉበት ዕለት መድረሱን ነግሯቸው የተጋድሏቸውን ጽናት አድንቆ በስማቸው መታሰቢያ ለሚያደርጉ፣ ለነዳያን ለሚመጸዉቱ ቤተ ክርስቲያን ለሚያሠሩ የምሕረት ቃል ኪዳን ሰጥቷቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖትም የዕረፍታቸው ጊዜ መቃረቡን ባወቁ ጊዜ የመንፈስ ልጆቻቸውን ጠርተው ጌታችን የነገራቸውን ሁሉ አስረድተው አባታዊ ምክርና ተግሣፅ ከሰጧቸው በኋላ ነሐሴ ፳፬ ቀን ከዚህ ዓለም ድካም ዐረፉ፡፡ የመንፈስ ልጆቻቸውም ለአንድ ቅዱስ አባትና ካህን በሚገባ ሥርዓት በማኅሌት፣ በዝማሬና በምስጋና ቀበሯቸው፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችንና ከቅዱሳን መላእክት ጋር ተገልጾ ታያቸው፤ ነፍሳቸውንም የጠራሽ፣ ንጽሕት ነፍስ ሆይ ወደእኔ ነዪ ብሎ በክብር ተቀበላት፡፡

በመጽሐፈ ገድላቸው እንደተጠቀሰው ቅዱስ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዚህ ዓለም የኖሩበት ዕድሜ ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ከዐሥር ወር ከዐሥር ቀን ነው፡፡ ገድላቸው ዕድሜያቸውን በመከፋፈል፡- በእናት አባታቸው ቤት ፳፪ ዓመት፤ በከተታ ፫ ዓመት፤ በዊፋት ፱ ወር፤ በዳሞት ፲፪ ዓመት፤ በአማራ ፲ ዓመት፤ በሐይቅ ፲ ዓመት፤ በደብረ ዳሞ ፲፪ ዓመት፤ በትግራይ ገዳማት በመዘዋወርና ወደ ኢየሩሳሌም በመመላለስ ፩ ዓመት፤ ዳዳ በሚባል አገር ፩ ወር፤ በአሰቦ ገዳም ፳፱ ዓመት ከ፲ ቀን መቆየታቸውን ይናገራል /ገ.ተ.ሃ.፶፱፥፲፬-፲፭/፡፡

ወደ ፍልሰተ ዐፅማቸው ታሪክ ስንመለስ መጽሐፈ ገድላቸው እንዲህ ሲል ይጀምራል፤ ስምዑ ወለብዉ ኦ ፍቁራንየ መጽሐፈ ዜናሁ ለክቡር ወቅዱስ ወለብፁዕ ፍቁረ እግዚአብሔር ዘይትነበብ በዕለተ ፍልሰተ ሥጋሁ አመ ፲ወ፪ ለግንቦት ዝ ውእቱ ድሙር ምስለ በዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ወበዓለ ሚካኤል ሊቀ መላእክት ፍቁሩ ለተክለ ሃይማኖት፤ ወዳጆቼ ሆይ፣ የከበረ፣ የተቀደሰ፣ የተደነቀ፣ የእግዚአብሔር ወዳጅ የሚሆን የአባታችን የተክለ ሃይማኖት ክብሩን፣ ገናንቱን የሚናገረውን፣ ዐፅሙ የፈለሰበትን ግንቦት ፲፪ ቀን የሚነበበውን መጽሐፍ አስተውላችሁ ስሙ፤ ይኸውም ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል ጋር የተክለ ሃይማኖት ወዳጅ ከመላእክት አለቃ ከቅዱስ ሚካኤል በዓል ጋር የተባበረ ነው፡፡ ወንድሞቻችን እንነግራችኋለን፤ እናስረዳችኋለን፡፡ እንደ ዮሐንስና እንደ ነቢዩ ኤርምያስ ከእናቱ ማኅፀን እግዚአብሔር የመረጠው የክቡር አባታችን ዐፅሙ የፈለሰበት ቀን ዛሬ ነው፤ /ገ.ተ.ሃ.፷፪፥፭-፰/፡፡

አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከዚህ ዓለም ከተለዩ በ፶፯ኛው ዓመት የካቲት ፲፱ ቀን ለመንፈስ ልጃቸው ለአባ ሕዝቅያስ ብርሃን ለብሰው በሕልም ተገለጡላቸውና ወዳጄ ሕዝቅያስ ሆይ ሰላም ለአንተ ይሁን! ጌታዬ በኋለኛው ዘመን ከዚህ ሥፍራ ልጆችህ ሥጋህን ያፈልሳሉ ያለኝ ዘመን ደርሷልና ሳትዘገይ ልጆቼን ሁሉ ቅጠራቸውና እስከምፈልስበት ቀን ድረስ ግንቦት ፲፪ ቀን ይሰብሰቡ፡፡ እናንተም በምስጋና በጸሎት መንፈሳዊ በዓልን አድርጉ፡፡ አባቴ ተክለ ሃይማኖት የሚለኝ ሁሉ በዚህች በፍልሰተ ዐፅሜ ቀን ይምጣ፤ መንፈሳዊ በዓልንም ያድርግ፡፡ እኔና ቅዱስ ሚካኤል ከወዳጄ አባ ፊልጶስ ጋር ስለኔ ፍቅር የተሰበሰበውን ሕዝብ ልንባርክ እንመጣለን፤ ከአሏቸው በኋላ ተሠወሯቸው፡፡

አባ ሕዝቅያስም እንደታዘዙት የአባታችሁን ዐፅም ከዋሻው ወደ ታላቁ ቤተ ክርስቲያን ታፈልሱ ዘንድ ኑ፤ ተሰብሰቡ ብለው የአባታችን ወዳጆች በያሉበት ሀገር ሁሉ መልእክት ላኩ፡፡ ምእመናንም ጥሪውን ተቀብለው በዓሉን ለማክበር ከአራቱም አቅጣጫ ተሰበሰቡ፡፡ ዐሥራ ሁለቱ መምህራንም መጡ፤ እነዚህም፡- የወረብ አገሩ አባ አኖሬዎስ፣ የፈጠጋሩ አባ ማትያስ፣ የእርናቱ አባ ዮሴፍ፣ የሞረቱ አባ አኖሬዎስ፣ የመርሐ ቤቴው አባ መርቆሬዎስ፣ የጽላልሹ አባ ታዴዎስ፣ የወገጉ አባ ሳሙኤል፣ የወንጁ አባ ገብረ ክርስቶስ፣ የድንቢው አባ መድኃኒነ እግዚእ፣ የዳሞቱ አባ አድኃኒ፣ የክልአቱ አባ ኢዮስያስ እና የመሐግሉ አባ ቀውስጦስ ናቸው፡፡

እነዚህ መምህራን ከአባ ሕዝቅያስ ጋር በመሆን የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ዐፅም ከዐረፈበት ዋሻ ባወጡት ጊዜ ዐፅማቸው ዕለት የተገነዘ በድን ይመስል ነበር፤ መዓዛውም ሽቱ፣ ሽቱ ይሸት ነበር፡፡ በአባታችን ዐፅም ቀኝና ግራም መስቀል ተተክሎ ነበር፡፡ በዐፅማቸውም ብዙ ድንቅ ተአምራት ተደርገዋል፡፡ ይህንን የአባታችንን ዐፅም አባ ሕዝቅያስና ዐሥራ ሁለቱ መምህራን በሣጥን አክብረው ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወስደው በመንበሩ ፊት ሦስት ጊዜ አዞሩት፡፡

በዚህች ዕለት አስቀድመው የካቲት ፲፱ ቀን ለአባ ሕዝቅያስ በሕልም እንደነገሯቸው ብፁዕ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከቅዱስ ሚካኤልና ከአባ ፊልጶስ ጋር ወደ ቤተ ክርስቲያኑ መጥተው ዐፅማቸው እስኪያረፍ ድረስ ከመንበሩ ተቀምጠው ቆይተው ዐፅማቸው ካረፈ በኋላ የተሰበሰበውን ሕዝብ ባርከው በክብር ወደ ሰማይ ዐረጉ፡፡ መምህራኑና ምእመናኑም በዓሉን በታለቅ ደስታ አክብረው በሰላም ወደየቤታቸው ተመለሱ፡፡ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ፍልሰተ ዐፅም ከዋለበት ዕለት ጋር ርክበ ካህናት አብሮ መዋሉ በዓሉን ልዩ ድምቀት ሰጥቶት ነበር /ገ.ተ.ሃ.፷፭፥፩-፳፬/፡፡

ከዚያ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በታላቁ ገዳም በደብረ ሊባኖስ ቅዱሳን ፓትርያሪኮች፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና በርካታ ምእመናን እየተሰበሰቡ በዓሉን በድምቀት ያከብራሉ፡፡ የብፁዕ አባታችን ዐፅማቸው በፈለሰበት ዕለት ዐሥራ ሁለቱ መምህራን እና በርካታ ምእመናንን እንደተሰበሰቡ ሁሉ እኛንም እግዚአብሔር አምላካችን በኢየሩሳሌም ሰማያዊት ይሰብስበን፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ የአቡነ ተክለ ሃይማኖትና የመንፈስ ልጆቻቸው ጸሎት፣ ረድኤትና በረከት ለዘለዓለሙ ይጠብቀን፡፡

ምንጭ፡-

ገድለ ተክለ ሃይማኖት፣ ፲፱፻፹፱ ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፪ ቀን፡፡

ቅዱስ ያሬድ ኢትዮጵያዊ

ግንቦት ፲፩ ቀን፣ ፳፻፰ ዓ.ም

ዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤ በየዓመቱ ግንቦት ፲፩ ቀን ከሚታወሱ ቅዱሳን መካከል የእመቤታችን እናት ቅድስት ሐና፣ ቅድስት ታውክልያ፣ ቅዱስ በፍኑትዩስ፣ አባ አሴር፣ ቅዱስ ያሬድ፣ ብፅዕት አርሴማ፣ ቅድስት ኤፎምያ፣ ቅድስት አናሲማ፣ ቅድስት ሶፍያ፣ አባ በኪሞስ፣ አባ አብላዲስ እና አባ ዮልዮስ ተጠቃሾች ሲሆኑ፣ በዛሬው ዝግጅታችን የቤተ ክርስቲያን እንዚራ፣ የኢትዮጵያ ብርሃን እየተባለ የሚጠራውን የቤተ ክርስቲያናችን ድምቀት፣ የአገራችን ኩራት የሆነውን የጥዑመ ልሳን፣ ኢትዮጵያዊ ማኅሌታይ የቅዱስ ያሬድን ታሪክ በአጭሩ ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

በ፭፻፭ ዓ.ም በአገራችን በኢትዮጵያ በአክሱም ከተማ ከአባቱ ከአብዩድ (ይስሐቅ) እና ከእናቱ ታውክልያ (ክርስቲና) አንድ ቅዱስ ተገኘ፤ ይኸውም ቅዱስ ያሬድ ነው /ገድለ ቅዱስ ያሬድ/፡፡ ቅዱስ ያሬድ ዕድሜው ለትምህርት ሲደርስ ከአጎቱ ከአባ ጌዴዎን ዘንድ ትምህርት ሊማር ቢሔድም ለበርካታ ዓመታት ትምህርት ሊገባው አልቻለም ነበር፡፡ በዚህም የተነሣ መምህሩ ይገርፉት፣ ይገሥፁት ነበር፡፡ እርሱም ከትምህርቱ ክብደት ባለፈ የመምህሩ ተግሣፅ ሲበረታበት ጊዜ ከአባ ጌዴዎን ቤት ወጥቶ በመሸሽ ላይ ሳለ ደክሞት ከአንድ ዛፍ ሥር ተቀመጠ፡፡

ከዛፉ ሥር ተጠልሎ ሳለ አንድ ትል ፍሬውን ለመመገብ ወደ ዛፉ ሲወጣ፣ ነገር ግን መውጣት ስለተሳነው በተደጋጋሚ ሲወድቅ ቆይቶ ከብዙ ሙከራ በኋላ ከዛፉ ላይ ሲወጣ፣ ፍሬውንም ሲመገብ ይመለከታል፡፡ ቅዱስ ያሬድ የትሉን ትጋት ከአየ በኋላ እርሱም በተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርግ የከበደው ምሥጢር እንደሚገለጽለት በማመን ወደ መምህሩ ተመልሶ ይቅርታ ከጠየቀ በኋላ ትምህርቱን እንደገና መቀጠል ጀመረ፡፡ እግዚአብሔርን በጸሎት እየተማጸነ ትምህርቱን ሲከታተል ከቆየ በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ ልቡናው ብሩህ ሆኖለት የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ትርጓሜን አጠናቆ መዓርገ ዲቁና ተቀበለ፡፡

እግዚአብሔርም የክብር መታሰቢያ ሊያቆምለት ወዷልና ከኤዶም ገነት ሦስት አዕዋፍን ልኮ በሰው አንደበት እንዲያናግሩት አደረጋቸው፡፡ እነርሱም ካናገሩት በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት አወጡትና በዚያም የሃያ አራቱን ካህናተ ሰማይ (ሱራፌል) ማኅሌት ተማረ፡፡ ወደ ምድርም ተመልሶ በአክሱም ጽዮን በሦስት ሰዓት ገብቶ በታላቅ ቃል፡- ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌ ሉያ ለወልድ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ ቀዳሚሃ ለጽዮን ሰማየ ሣረረ ወበዳግም አርአዮ ለሙሴ ዘከመ ይገብር ግብራ ለደብተራ፤ ለአብ ምስጋና ይገባል፤ ለወልድ ምስጋና ይገባል፤ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይገባል፡፡ የጽዮን ደገኛዋ ሰማይን ፈጠረ፡፡ ዳግመኛም እንዴት መሥራት እንዳለበት የድንኳንን አሠራር ለሙሴ አሳየው፤ አስተማረው እያለ በዜማ እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡ የቅዱስ ያሬድን ድምፅ የሰሙ ሁሉ ጳጳሳቱና ነገሥታቱ ሳይቀሩ ካህናቱም ምእመናኑም ወደርሱ ተሰብስበው ሲሰሙት ዋሉ፡፡ ይህንንም ምስጋና አርያም ብሎ ጠራው፤ ይኸውም በዜማ ትምህርት ቤት ከቃል ትምህርቶች አንደኛው ሆኖ በመሰጠት ላይ ይገኛል፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር ይህንን ሊቅ፡- አምሳሊሆሙ ለሱራፌል፤ የሱራፌል አምሳላቸው ይለዋል፡፡ ከመላእክት ወገን የሆኑት ሱራፌል እግዚአብሔርን ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እያሉ በመንበሩ ፊት ቆመው እንደሚያመሰግኑ ሁሉ ቅዱስ ያሬድም ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እያለ በመላእክት ቋንቋ እግዚአብሔርን አመስገኗልና፤ ደግሞም የተማረው ከእነርሱ ነውና የሱራፌል አምሳላቸው ተባለ፡፡ እርሱም፡- ሃሌ ሉያ ዋይ ዜማ ዘሰማዕኩ በሰማይ እመላእክት ግናይ እንዘ ይብሉ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር መልዐ ሰማያተ ወምድረ ቅድሳተ ስብሓቲከ፤ ምስጋና ለእግዚአብሔር ይሁን! ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር፤ የምስጋናህ ስፋት ሰማይና ምድርን መላ፤ /ኢሳ.፮፥፫/እያሉ ሲያመሰግኑ ከመላእክት የሰማሁት ምስጋና ምንኛ ድንቅ ነው? በማለት ዜማውን የተማረው ከመላእክት መሆኑን በድርሰቱ መስክሯል፡፡

ከዚያ በኋላ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ከዓመት እስከ ዓመት ድረስ በየክፍለ ዘመኑ በክረምትና በበጋ፣ በመጸውና በጸደይ፣ በአጽዋማትና በሰንበታት፣ እንዲሁም በመላእክት፣ በጻድቃን፣ በሰማዕታት፣ በደናግል በዓላት የሚደረስ ቃለ እግዚአብሔር በሦስት ዜማዎች ማለትም በግእዝ፣ በዕዝልና በአራራይ ደረሰ፡፡ የሰው ንግግር፣ የአዕዋፍ፣ የእንስሳትና የአራዊት ጩኸት ሁሉ ከነዚህ ከሦስቱ ዜማዎች እንደማይወጡ መጽሐፈ ስንክሳር ይናገራል፡፡

በአንዲት ዕለት ቅዱስ ያሬድ ከብሉይና ከሐዲስ፣ እንደዚሁም ከሊቃውንትና ከመነኮሳት የተውጣጣውን መንፈሳዊ ድርሰቱን በዘመኑ ከነበረው ከንጉሥ ገብረ መስቀል ፊት ቆሞ ሲዘምር ንጉሡ በድምፁ በመማረኩ የተነሣ ልቡናው በተመስጦ ተሠውሮበት (የሚያደርገዉን ባለማወቁ) የቅዱስ ያሬድን እግር በጦር ወጋው፡፡ ከቅዱስ ያሬድ እግር ደምና ውኃ ቢፈስስም ነገር ግን ማኅሌቱን እስኪፈጽም ድረስ ሕመሙ አልተሰማውም ነበር፡፡

ንጉሡም ያደረገዉን ሁሉ ባወቀ ጊዜ ደነገጠ፤ ጦሩንም ከእግሩ ነቅሎ ስለፈሰሰው ደምህ ዋጋ የምትፈልገዉን ሁል ለምነኝ እያለ ተማጸነው፡፡ ቅዱስ ያሬድም ላትከለክለኝ ማልልኝ ብሎ ቃል ካስገባው በኋላ ወደ ገዳም ሔዶ ይመነኩስ ዘንድ እንዲፈቅድለትና እንዲያሰናብተው ለመነው፡፡ ንጉሡም ከመኳንንቱ ጋር እጅግ አዘነ፤ ተከዘ፡፡ ከእርሱ እንዲለይ ባይፈልግም ነገር ግን መሐላዉን ማፍረስ ስለከበደው እያዘነ አሰናበተው፡፡

ከዚያም ቅዱስ ያሬድ በአክሱም ጽዮን ቤተ መቅደስ በታቦተ ጽዮን ፊት ቆሞ፡- ቅድስት ወብፅዕት ስብሕት ወቡርክት ክብርት ወልዕልት አንቀጸ ብርሃን መዐርገ ሕይወት፤ ፈጽሞ የከበርሽና የተመሰገንሽ፣ ከፍ ከፍም ያልሽ፣ የብርሃን መውጫ የሕይወት ማዕረግ የሆንሽƒ‚ƒƒ‚ እያለ አንቀጸ ብርሃን የተባለውን የእመቤታችን ምስጋና እስከ መጨረሻው ድረስ ደረሰ፡፡ ይህንን ጸሎት ሲያደርስም አንድ ክንድ ያህል ከመሬት ከፍ ብሎ ይታይ ነበር፡፡ከዚህ በኋላ ወደ ሰሜን አገር ሔዶ (ሰሜን ተራሮች አካባቢ) በጾም በጸሎት ተወስኖ ሥጋውን እጅግ እያደከመ ኖሮ ገድሉን በዚያው ፈጸመ፡፡ እግዚአብሔርም ስሙን ለሚጠራ፣ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው፤ ከዚያም በሰላም ዐረፈ፡፡ /ምንጭ፡- መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፩/

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በገድለ ቅዱስ ያሬድ ላይና በመጽሐፈ ስንክሳር እንደመዘገቡልን ግንቦት ፲፩ ቀን ቅዱስ ያሬድ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ ያረፈበት ቀን ነው፤ እዚህ ላይ ግን አከራካሪ ጉዳይ አለ፤ ይኸውም አንደኛው ቅዱስ ያሬድ ሞቶ ተቀብሯል የሚል ሲሆን፣ ሌላኛው ደግሞ ቅዱስ ያሬድ እስከነ ነፍሱ ተሠወረ እንጂ አልሞተም የሚል ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ ሞተ የሚሉ ወገኖች ከሚጠቅሷቸው ማስረጃዎች ውስጥ በመጽሐፈ ስንክሳር፡- ወበዛቲ ዕለት አዕረፈ ያሬድ ማኅሌታይ፤ በዚህች ዕለት ማኅሌታይ ያሬድ ዐረፈ፤ እና ወእምዝ አዕረፈ በሰላም፤ ከዚህ በኋላ በሰላም ዐረፈ የሚሉት ሐረጋት የሚገኙ ሲሆን፣ ተሠወረ የሚሉት ደግሞ እዚያው ስንክሳሩ ላይ፡- ወእምዝ ሖረ ሀገረ ሰሜን ወነበረ ህየ ወፈጸመ ገድሎ፤ ከዚህ በኋላ ወደ ሰሜን አገር ሒዶ ገድሉን በዚያ ፈጸመ፤ ተብሎ የተገለጸውን እንደማስረጃ ይጠቅሳሉ፡፡

በእርግጥ ቃሉን በትኩረት ለተመለከው ሰው ዐረፈ ማለት ሞትን ብቻ ሳይሆን እንደነ ሄኖክ ከዚህ ዓለም ጣጣና እንግልት ተለይቶ በሕይወት እያሉ (ሳይሞቱ) ተሠውሮ መኖርንም ያመለክታል፡፡ ገድሉን በሰሜን አገር ፈጸመ የሚለውም መሠወሩን ብቻ ሳይሆን መሞቱንም ሊያመለክት ይችላል የሚሉም አሉ፡፡ ነገር ግን የቤተ ክርስቲያን መምህራን እንደሚያስተምሩን እነእገሌ ቀበሩት የሚል ቃል ስለማይገኝ ቅዱስ ያሬድ ተሠወረ እንጂ ሞተ ተብሎ አይነገርለትም፡፡ ለዚህም ማስረጃ እርሱ በተሠወረበት ተራራ እስከ አሁን ድረስ የከበሮ (የማኅሌት) ድምፅ ይሰማል፤ የዕጣን መዓዛ ይሸታል፡፡ ይህም ቅዱሱ ከሰው ዓይን ተሠውሮ እግዚአብሔርን እያመሰገነ እንደሚገኝ አመላካች ነው፡፡

የቅዱስ ያሬድ ድርሰቶችም ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን ለአገርም ድንቅና ወደር የሌላቸው ሀብቶች ናቸው፡፡ በመሆኑም የዜማ ድርሰቶቹ (ድጓ፣ ጾመ ድጓ፣ ምዕራፍ፣ ዝማሬ፣ መዋሥዕት) እንደሌሎቹ ቅርሶች ሁሉ በዩኔስኮ እንዲመዘገቡ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ከፍተኛ ርብርብ በያደርጉ መልካም ነው፡፡ በቅዱስ ያሬድ ዜማ የሚደምቀው በዓለ ጥምቀት በዩኔስኮ ሲመዘገብ ዜማውን ከበዓሉ ለይቶ ማስቀረት የታሪክ ተወቃሾች ያደርገናልና ሁላችንም እናስብበት እንላለን፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ እኛንም በአባታችን በቅዱስ ያሬድ ጸሎት ይማረን፡፡ በረከቱም ከእኛ ጋር ለዘለዓለም ትኑር፤ አሜን፡፡